ቅዱስ ላሊበላ
ቅዱስ ላሊበላ ከአባቱ ዣን ስዩምና ከእናቱ ኪርወርና በታኅሣሥ ፴፱፣ ፲፻፩ ዓ.ም በላስታ ቡግና ወረዳ ልዩ ስሟ ሮሀ በተባለችው ሥፍራ ተወለደ፡፡ አባቱ በላስታ አውራጃ የቡግናው ገዢ ነበር፤ እናቱ ደግሞ አገልጋይ ነበረች፡፡ የልደቱን ነገር አስቀድሞ ቅዱስ ሚካኤል ለእናቱ ነግሯት ነበር፤ ቅዱስ ላሊበላ በተወለደ ጊዜም ብዙ ነጫጭ ንቦች መጥተው በሰውነቱ ላይ አርፈው እንደ ማር እየላሱት ስለታዩ እናቱ ‹‹ልጄን ንብ ዘበኛ ሆኖ ይጠብቅልኛል›› ስትል ስሙን ‹‹ላል ይበላል›› ብላዋለች፡፡ ‹ላል› በአገውኛ ‹ንብ› ማለት ነው፡፡ በጊዜ ብዛት በተለምዶ ነው ‹‹ላሊበላ›› ተብሎ መጠራት ተጀመረ፡፡ ንቦቹ ግን ሥጋዊ ንቦች ሳይሆኑ በንብ የተመሰሉ መላእክት ናቸው፡፡ ንጉሥ መሆኑን እያመለከቱ ሃይማኖትና ምግባር ማር ከእርሱ እንደሚቀዳ ለማመልከት በንብ ሠራዊት ተመስለው ሰውነቱን ላሱት፡፡