ቅድስት ኢየሉጣና ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ
ክፍል 2
ዲ/ን ደረሰ ተሾመ
በክፍል አንድ ጽሑፋችን እንገለጽነዉ በአረማዊው የሮም ንጉሥ በዲዮቅልጥያኖስ ዘመነ መንግሥት የተሾመው አረማዊው መኰንን እለእስክንድሮስ ክርስቲያኖችን ማሳደድና መግደል በጀመረ ጊዜ፣ ቅድስት ኢየሉጣ ልጇን ይዛ ወደ ጠርሴስ ብትሰደድም መኰንኑ ተከታትሎ በመምጣት ለጣዖት እንዲሰግዱና ሃይማኖታቸውን እንዲለውጡ አዘዛቸው።ቅዱሳኑ ግን በክርስቶስ ፍቅር ጸንተው እምነታቸውን አንክድም በማለታቸው በዓይንና በአፍንጫቸው ውስጥ ጨውና ሰናፍጭ ከመጨመር ጀምሮ፣ በጋሉ የብረት ችንካሮች መላ ሰውነታቸውን በማሠቃየት፣ እሳት በማንደድ፣ በመጋዝ በመሰንጠቅና በፈላ የጋን ውኃ ውስጥ በመጨመር በብዙ ዓይነት ጭካኔ የተሞላበት የሥቃይ መሣሪያዎች አሠቃይተዋቸዋል። (ስንክሳር ዘጥር ፲፭)
በዚህ ሁሉ መከራና ሥቃይ ውስጥ ግን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ በመምጣት ከሥቃያቸው ያድናቸው፣ የእሳቱንና የፈላውን ውኃ ኃይል ያቀዘቅዝላቸው ነበር። እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ በፈላው ውኃ ፊት በፈራች ጊዜም ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ፦ «እናቴ ሆይ አትፍሪ፤ አናንያ፣ አዛርያና ሚሳኤልን ከእሳት ነበልባል ያዳናቸው እግዚአብሔር እኛንም ያድነናል» እያለ ያረጋጋትና በተጋድሎዋ እንድትጸና ያበረታት ነበር። ቅዱሳኑ ይህንን የመከራ መንገድ አልፈው በሰማዕትነት ካረፉ በኋላ ከእግዚአብሔር ዘንድ የታላቅ ቃል ኪዳን ባለቤት ሆነዋል፤ ቤተ ክርስቲያናችንም በዓለ ክብራቸውን በዓመት ሁለት ጊዜ በድምቀት ታስባቸዋለች። አንደኛው ጥር ፲፭ ቀን በሰማዕትነት ያረፉበት ዋና በዓላቸው ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ ሐምሌ ፲፱ ቀን ከፈላ ውኃና ከእሳት ነበልባል የዳኑበት፣ ቅዱስ ገብርኤል የተራዳቸውና ከእግዚአብሔር ዘንድ ታላቅ ቃል ኪዳን የተቀበሉበት ዕለት ነው።
ቅድስት ኢየሉጣ በጨካኙ መኰንን ፊት ስትቆም፣ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ደግሞ በሦስት ዓመቱ በእሳትና በፈላ ውኃ ፊት አልተናወጠም። ይህ ተጋድሎ ለዛሬው ትውልድ የሚያስተላልፈው ዋና ዋና መልእክቶች አሉ፣ለአብነትም፦
፩. ፈተናን በጽናት ማለፍ፦ ቅዱሳኑ መከራን በድል አልፈዋል። “እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለሁ።”እንዲል (የዮሐንስ ራእይ ፪፥፲) እውነተኛ ክርስቲያናዊ ማንነት በጊዜያዊ ችግር አይናወጥም።
፪. የወላጅና የልጅ መንፈሳዊ ትስስር፦ ምንም እንኳን በሦስት ዓመት እንዲህ ያለ ጥብአት እና ገድል የተገኘው በፈቃደ እግዚአብሔር ቢሆንም እናት ልጇን በሃይማኖትና በፈሪሃ እግዚአብሔር ማሳደጓ ለመንፈስ ቅዱስ የተዘጋጀ ቤተ መቅደስ አድርጋዋለች፣”በሕፃኑ ላይም የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ አደረበት ታላላቅ ድንቆችና ተአምራቶችንም አደረገ ብዙዎች በሽተኞችንም አዳናቸው” (ስንክሳር ዘወርኀ ሐምሌ 19)። ልጅ ደግሞ እናቱ በፈራች ጊዜ አባቶቻችንን ቸል ያላለ፣ ሰማዕታትን የታደገ እግዚአብሔር እኛንም አይዘነጋንም ብሎ አጸናት። ይህም በቤተሰብ ውስጥ እርስ በእርስ በመንፈስ የመደጋገፍን ጥቅም ያሳያል።
፫. ‘አይዞህ/ሽ” የሚል ትውልድ፦ ክርስትና ለብቻ የሚሮጡት የብቸኝነት መንገድ ሳይሆን በጋራ የሚቆሙበት፣በጸሎት የሚተሳሰቡበት የድኅነት በር ነው። ዛሬ በጭንቀት፣ በደዌና በችግር ሳለን ወንድማችንና እኅታችን “አይዞህ አትፍራ/አትፍሪ” በጸሎትህ/ሽ አስበኝ/አስቢኝ መባባልን ገንዘብ ማድረግ እንደሚገባን አስተምረውናል። ብንደጋገፍ የምናተርፈው ለራሳችን ነው፣ በክርስትና በሚመጣ መከራ እና ሥቃይ ውስጥ ብቻችንን ያለን ቢመስለን እንኳን እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ነው። ዛሬ በብዙ መከራ ውስጥ በሞት አፋፍ ላሉ ሰዎች ድካም ከመሆን ይልቅ ብርታት ለመሆን አይዟችሁ ማለት የክርስትና ግዴታ ነው።
፬. የማይለየው የመላእክት ተራዳኢነት፦ በመከራቸው ሁሉ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል አልተለያቸውም። “የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሠፍራል፤ ያድናቸውማል” (መዝ. ፴፬፥፯) እንደተባለ፣ በእግዚአብሔር ለሚታመኑ ሁሉ የመላእክት ጥበቃ አይለያቸውም። እግዚአብሔርን በመፍራት ሕይወት መላእክት ከእኛ ጋር ናቸውና።
፭.መመኪያቸው እግዚአብሔር ነበር፦ ተሰደው በሰው አገር ወገን ዘመድ የሚሉት በሌለበት ቦታ እንኳን ተስፋቸው እና መመኪያቸው ያደረጉት እግዚአብሔርን ነበር። እኛም ዛሬ ከሥልጣን፣ ከዘመድ ከቋንቋ፣ ከዘር ከሀብትና ከዝና በላይ የሆነ እግዚአብሔርን መመኪያችን ልናደርገው ይገባል።”እግዚአብሔር ረዳቴ ነው፥ አልፈራም..”(መዝሙረ ዳዊት ፻፲፰፥፮ / ዕብራውያን ፲፫፥፮) እንዲል።
በዚህ ውጣ ውረድ በተሞላው ዓለም ውስጥ እምነትን፣ ማንነትንና ሥነ ምግባርን አጽንቶ መያዝ ትልቅ ተጋድሎ በሆነበት ዘመን—የቅዱስ ቂርቆስና የቅድስት ኢየሉጣ ታሪክ ለእኛ ለዚህ ዘመን ትውልድ ታላቅ የሕይወት መብራት ነው።
የዚህ ዓለም ጊዜያዊ ጥቅምና ክብር የሚያልፍ ነው፤ የቅዱሳኑ ጽናት ግን ዘለዓለማዊ አክሊልን አጎናጽፏቸዋል። እኛም በቀንም በሌሊትም የቅዱሳኑን ጸሎትና የመልአኩን ምልጃ ተስፋ በማድረግ፦ “በተአምኖ ንሴፎ ትንባሌ ዚአከ መዓልተ ወሌሊተ ዕቀበኒ አንተ”(በእግዚአብሔር ታምነን በቀንም በሌሊትም የአንተን ልመና ተስፋ እናደርጋለን) እያልን በመንፈሳዊ ሕይወታችን ልንጸና ይገባል።
የሰማዕታቱ ቅዱስ ቂርቆስና ቅድስት ኢየሉጣ ጸሎትና በረከት፣ የቅዱስ ገብርኤል አማላጅነትና ጥበቃ አይለየን!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!
እስመ ለመላእክቲሁ ይኤዝዞሙ በእንቲአከ/ መላእክቱን ስላንተ ያዛቸዋል. (መዝሙር ፺፥፲፩)
ዲ/ን ይትባረክ
ክፍል 1
ይህንን ቃል የተናገረው ቅዱስ ዳዊት ነው፡፡የቅዱሳን መላእክትን ተልእኮ ከቅዱሳን ሰዎች ጋራ ያላቸውን ግንኙነት፤አምላካችን እግዚአብሔር ስሙን ለሚጠሩ ስለ ስሙ ለሚጋደሉ በዐላውያን በመናፍቃን ዘንድ ሕያው ምስክር ሆነው መከራን የሚቀበሉ ሰዎችን ለመርዳት ለመታደግ ለማገልገል ለማጽናት ለማበርታት መላእክቱን እንደሚያዛቸው መላእክቱም እንደሚታዘዙ የታዘዙበትን ተልእኮም እንደሚወጡ ሰማዕታቱ በኀይለ እግዚአብሔር በእደ መላእክት ተደግፈው በክንፈ መላእክት ተጠልለው ለቅድስና ለክብረ ቅዱሳን እንደሚበቁ ለተስፋው ቃል ፍጻሜ እንደሚደርሱ የድል አክሊል እንደሚቀዳጁ ሲያመላክት…..
‹‹እስመ ለመላእክቲሁ ይኤዝዞሙ በእንቲአከ ከመ ይዕቀቡከ በኩሉ ፍናዊከ ወበእደዊሆሙ ያነሥኡከ ከመ ኢይትዐቀፍ በዕብን እግርከ….መላእክቱን ስላንተ ያዝዛቸዋልና በሥራህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ በእጃቸው ያነሱህ ዘንድ እግርህ በድንጋይ እንዳትሰናከል…›› ይላል፡፡ (መዝ ፺፥፲፩-፲፫፤ዘፀ ፳፫፥፳ ማቴ ፬፥፮)
መላእክት ስለ ሰው ልጆች የታዘዙበት ጥላ ከለላ የሆኑበት አቅፈው ደግፍው ለክብር ያበቁበት ስለ ሰው ልጆች ታዝዘው በመዓትም በምሕረትም በቁጣም በትሕትናም የተገለጹበት ወዳጅን ረድተው ጠላትን ቀጥተው የተገለጡበት ታሪክ በመጽሐፍ ቅዱስ በብዙ ቦታ ተጠቅሷል በብዙ ቅዱሳን ሕይወት ውስጥ ታይቷል፡፡(ዘፀ ፳፫፥፳ ማቴ ፬፥፮፤፩ኛ.መቃ ፲፫፥፳፩፤ኢያ ፭፥፲፫፤ኢሳ ፷፫፥፱…….)
በጣም ብዙ ምሳሌ መጥቀስ አስረጅ ታሪክ ማቅረብ የሚቻል ቢሆንም ለዛሬ ማንሳት የፈለግነው ግን ከመላእክት ወገን አንዱን በተራዳኢነቱ በመታዘዙ ለሰው ልጆች ባለው ቅርበትና አጋዥነት በብዙ ቅዱሳን ሰማዕታት የተጋድሎ የምስክርነት ሥራ ውስጥ በርኅራኄውና በቁጣው በፍቅሩና በአስፍሪነቱ የሚጠቀሰው ቅዱስ ገብርኤል ለቅዱስ ቂርቆስና ለእናቱ ለቅድስት ኢየሉጣ ያደረገውን ተራዳኢነት ነው፡፡
ይህ ገናና መልአክ ጥንት በሥነ ፍጥረት ዓለመ መላእክትን ያረጋጋ ነው፤ሦስቱን ሕፃናት ከእቶን እሳት ያወጣ መልአክ ነው ፤ይህ መልአክ ኤልሳቤጥን በእርጅናዋ ዘመን እንድትወልድ ያበሠረ ነው፤ይህ መልአክ ካህኑ ዘካርያስን አንደበቱን የዘጋ ነው፤ ይህ መልአክ ድንግል ማርያምን ለዛ ባለው ቃል በትሁት ማንነት ቀርቦ ያናገረ የልዑል ክርስቶስን መወለድ ያበሠረ የተስፋ ቃሉ ፍጻሜ መድረሱን ያስረዳ አብሣሬ ትስብእት ፍጡነ ረድኤት የሆነ መልአክ ነው፡፡
ወደ መነሻ ታሪካችን ስንመለስ ሐምሌ 19 ቀን ይህ መልአክ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስንና እናቱን ቅድስት ኢየሉጣን ከእሳት ማዳኑ የሚዘከርበት ዕለት ነው፡፡ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ሀገሩ ሮም አንጌቤን ነው፡፡ አባቱ ቆዝሞስ እናቱ ኢየሉጣ ሲሆኑ ቅድስት ኢየሉጣ ከአዝማደ ነገሥት ነበረች፡፡ዲዮቅልጥያኖስ በነገሠ በ20 ዓመት (በ303 ዓ.ም) በአባ አባጋግዮስ ምክንያት ‹‹አብያተ ክርስቲያናት ይትዐጸዋ አብያተ ጣዖታት ይትረኃዋ ››የሚል አዋጅ ሲታወጅ ብዙ ክርስቲያኖች እንደ ሽንኩርት ተላጡ እንደ ጎመን ተቀረደዱ በሰይፍ ተቆረጡ በእሳት ተቃጠሉ ብዙ መከራ ደረሰ ብዙዎቹም ተሰደዱ፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ቂርቆስ የሦስት ዓመት ሕፃን ሆኖ ከናቱ ጋር ወደ ጠርሴስ ሸሹ፡፡
ይሁን እንጅ በዚያም መስፍነ ብሔሩ እለእስክንድሮስ ክርስቶስን ካጂ ለጣኦት ስገጂ አላት፡፡‹‹ዐይን እያለው ለማያይ ጆሮ እያለው ለማይሰማ በቃልህ አዝዘህ በእጅህ አበጅተህ ላቆምከው ምስል አልሰግድም እስኪ ይህንን ህፃን ጠይቀው›› አለችው፡፡መስፍኑም ቅዱስ ቂርቆስን ‹‹አንተ ሕፃን ብዙ ወርቅ እሰጥሃለሁ ለዚህ ጣዖት ስገድ›› አለው፡፡መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ነበርና ‹‹አንሰ ኢይሰግድ ለአማልክቲከ ርኩሳን ዘኢይክሉ አድኅኖ ርእሶሙ…ራሳቸውን ማዳን ለማይችሉ ርኩሳን ጣዖቶችህ አልሰግድም›› አለው፡፡(መዝገበ ታሪክ ክፍል 2)
በዚህ ጊዜ ተበሳጭቶ በብረት ጋን ውኃ አፍልታችሁ ዝፍት ተይ ጨምራችሁ በዚያ ጣሏቸው ብሎ አዘዘ፡፡ዝፍት ተይ ጨምረው በብረት ጋን ውኃ አፍልተው ‹‹ድምፃ ለጽሕርት ከመ ነጎድጓደ ክረምት ››ይላል የውኃው መፍለቅለቅ ፍላቱ እንደ ክረምት ነጎድጓድ እስከ 42 ምዕራፍ ድረስ እስኪሰማ ይጮህ ነበር ፡፡በዚያ ሊጥሏቸው ሲወስዷቸው ቅድስት ኢየሉጣ ልቧ ታወከ ፈራች ልጇ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ግን ‹‹ፍርሃቷን አርቅላት›› እያለ ለእናቱ ይጸልይ ነበር፡፡
እንዲህም አላት ‹‹ጥብዒኬ እምየ እምዝ ዳግመ ኢይረክበነ ሞት…ሁለተኛ ሞት አያገኘንምና እናቴ ሆይ በርች ጨክኚ..አናንያን አዛርያን ሚሳኤልን ያዳነ እኛንስ ያድነን የልምን ? ››እያለ አጽናናት፡፡በዚህ ጊዜ ጨክነው ተያይዝው በእሳት ወደፈላው የጋን ዉኃ ገብተዋል፡፡ቅዱስ ዳዊት መላእክቱን ስላንተ ያዝዛቸዋል ያለው እንደነሱ ላለው ሕያው ምስክሮቹ ነውና ከመላእክት አንዱ ፍጡነ ረድኤት ቅዱስ ገብርኤል ፈጥኖ መጣ በበትረ መስቀሉ እሳቱን ሲመታዉ 42 ምዕራፍ እስኪሰማ የፈላው ዉሃ እንደ ጥዋት ጤዛ ቀዘቀዘ ቅድስት ኢየሉጣና ሕፃኑ ቂርቆስ በሰላም ከእሳቱ ወጡ፡፡
‹‹መንክር እግዚአብሔር በላዕለ ቅዱሳኒሁ›› እንዳለ ቅዱስ ዳዊት ..እግዚአብሔር በቅዱስ ቂርቆስ እና በእናቱ ቅድስት እየሉጣ ላይ የሠራው ተአምር እጅግ የሚደንቅ ተአምር እንደሆነ እንረለልን፡፡
አምላከ ቅዱስ ቂርቆስ ወኢየሉጣ በእደ መልአኩ ይጠብቀን አሜን፡፡
አብርሃም ርእየ ፫ተ እደወ፤ በዛቲ ዕለት ምሥጢረ ሥላሴ ዜነወ።
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ፩ አምላክ አሜን!
አብርሃም ርእየ ፫ተ እደወ፤ በዛቲ ዕለት ምሥጢረ ሥላሴ ዜነወ።
“አብርሃም ሦስት ሰዎችን አየ፤ በዚያችም ቀን የቅድስት ሥላሴ ምሥጢር ተገለጠ።“
መምህር ይባቤ አበራ
የቅድስት ሥላሴ በዓልን ስናከብር የምናስበው ታላቁን የእምነታችንን ምሥጢር ነው።
አብ፣ ወልድ መንፈስ ቅዱስ በመለኮት አንድ በአካል በግብር ሦስት ናቸው ።
አምላክ ውእቱ አብ፤ ወአምላክ ውእቱ ወልድ፤ ወአምላክ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ ወኢይትበሀሉ ፫ተ አማልክተ፡፡ አላ ፩ዱ አምላክ፡፡
አብ አምላክ ነው፤ወልድም አምላክ ነው፤ መንፈስ ቅዱስም አምላክ ነው፡፡ ግን ሦስት አማልክት አይባሉም አንድ አምላክ እንጂ፡፡
“ወከመዝ ውእቱ እምነትነ በቅድስት ሥላሴ ዘይሴብሑ እምነ ኵሉ ዘውእቶሙ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ወኢንትአመን በካልእ አምላክ እምእሉ ፫ቱ አካላት እለ ፍሉጣን በገጻት ወኢሂ ፍሉጣን በህላዌ መለኮት በከመ ይቤ ዐቢይ መምህር ባስልዮስ በድርሳኑ በእንተ ሃይማኖት ዘቅድስት ሥላሴ ዘውእቶሙ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ህላዌ ዘኢተገብረ ወሥልጣን ከሀሊ ለፈጽሞ ኵሉ ፍጥረታት፡፡ ቅዱስ አትናቴዎስ ዘአንጾኪያ
በሁሉ ዘንድ የሚመሰገኑ በቅድስት ሥላሴ የምናምነው እምነት እንዲህ ነው፤ እነዚህም አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ናቸው፤ በገጽ ልዩ በባሕርየ መለኮት የማይለዩ ከሚሆኑ ከእነዚህ ከሦስቱ አካላት በቀር፤ በሌላ አምላክ አናምንም፤ በቅድስት ሥላሴ ስለማመን በተናገረበት ድርሳኑ፤ ደገኛው መምህር ባስልዮስ እንደተናገረ፤ እነዚህም ያልተፈጠረ ባሕርይ ፍጥረትንም ሁሉ ለመፍጠር፤ ለማሳለፍ የሚቻለው ሥልጣን (አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ) ናቸው” ።
አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ በስም በአካል በግብር ሦስት በባሕርይ በሕልውናና በፈቃድ አንድነት ጽኑዓን (የጸኑ) ናቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ተገኙ፣ በዚህ ጊዜ ያልፋሉ አይባሉም መጀመሪያም መጨረሻም እነርሱ ናቸውና፡፡ ቅድስት ሥላሴን የሰው አእምሮ አጥንቶ እና ተመራምሮ ሊደርስበት አይችልም ምክንያቱም ከዕውቀትና ከአእምሮ በላይ ስለሆነ ይህንንም ለማስረዳት ሊቁ ቅዱስ አትናቴዎስ ዘአንጾኪያ
“ወበፈጢረ ኵሉ ፍጥረታት ቅድስት ሥላሴ ኅቡራነ መለኮት እለ ርሑቃን እምኵሉ ዓቅም ወኁልቊ፡፡ ቅዱስ አትንቴዎስ ዘአንጾኪያ
በከሀሊነት ፍጥረትን ሁሉ በመፍጠር ከአብ ከወልድ ጋር አንድ ነው፤ በመለኮት አንድ የሚሆኑ፤ ሦስት አካላት ከመወሰን፤ ከቊጥር ሕግ ሁሉ የራቁ ናቸው”፡፡ ሃይ.አበ ፻፰፡፪
እንዲህ ስለተባለ ግን ስለ ሥላሴ ማወቅና መማር አይቻልም ማለት አይደለም ምክንያቱም በመጻሕፍት ተጽፎ እንደምናገኘውና አባቶቻችን እንዳስተማሩን ቅድስት ሥላሴ በባሕርያቸው የማይመረመሩ ቢሆንም ለእኛ ግን በምንችለውና በምንረዳው ልክ እንደ አቅማችን በተለያየ መንገድ ራሳቸውን ገልጸውልናል ሥላሴ እንደ እናት ርኅሩኀን ናቸውና በእናት ሥርዓት ‹‹ቅድስት ሥላሴ›› እንላቸዋለን፡፡ ይህንንም ሊቁ አባታችን ቅዱስ ዮሐንስ ዘአንጾኪያ በሃይማኖተ አበውእንዲህ ሲል ይገልጸዋል
ወኢናንቀለቅል ለግሙራ ኀበ ካልእ ሃይማኖት በእንተ ቅድስት ሥላሴ ቅዱስ የሐንስ ዘአንጾኪያ
ስለ ምሥጢረ ሥላሴ ካመንነው እምነት ወደ ሌላ ሃይማኖት አንናወጥም በማለት ሥላሴን ቅድስት ሥላሴ ብሎ በሴት (በእናት) አንቀጽ ሲናገር እናያለን ስለዚህ ሥላሴ እኛ በምንረዳው ልክ በተለያየ አገላለጽ ተገልጸዋል ካልን ከተገለጹበት መንገድ አንዱ በኦሪት ዘፍጥረት ምዕራፍ ፲፰፡፩_፲፮ ተጽፎ እንደ ምናገኘው ለአባታችን ለቅዱስ አብርሃምና ለእናታችን ለቅድስት ሣራ የተገለጸበት መንገድ ነው ከፍጥረታት ወገን ከእመቤታችን ቀጥሎ የአብርሃምን ያህል በሥላሴ ዘንድ የተወደደ ሰው የለም አባታችን ቅዱስ አብርሃም የደግነት ሁሉ አባት ነውና ስለዚህ ዛሬ የምናስበውና ምናከብረው ይህንን ነው ።
ይኸውም ታሪኩን ስንመለከተው ፡- አብርሃም በተመሳቀለ መንገድ በቀትርም ጊዜ እርሱ በድንኳኑ ደጃፍ ተቀምጦ ሳለ እግዚአብሔር በመምሬ የአድባር ዛፍ ተገለጠለት። ዓይኑንም አነሣና እነሆ፥ ሦስት ሰዎች በፊቱ ቆመው አየ ባያቸውም ጊዜ ሊቀበላቸው ከድንኳኑ ደጃፍ ተነሥቶ ሮጠ፥ ወደ ምድርም ሰገደ፥እንዲህም አለ፦
አቤቱ፥ በፊትህስ ሞገስ አግኝቼ እንደ ሆነ ባሪያህን አትለፈኝ ብዬ እለምናለሁ ጥቂት ውኃ ይምጣላችሁ፥ እግራችሁን ታጠቡ፥ ከዚህችም ዛፍ በታች ዕረፉ ቍራሽ እንጀራም ላምጣላችሁ፥ ልባችሁንም ደግፋ ከዚያም በኋላ ትሄዳላችሁ ስለዚህ ወደ ባሪያችሁ መጥታችኋልና። እነርሱም፦ እንዳልህ አድርግ አሉት። አብርሃምም ወደ ድንኳን ወደ ሣራ ዘንድ ፈጥኖ ገባና፦ ሦስት መስፈሪያ የተሰለቀ ዱቄት ፈጥነሽ አዘጋጂ፥ ለውሺውም፥ እንጎቻም አድርጊ አላት።
አብርሃምም ወደ ላሞቹ ሮጠ፥ እጅግ የሰባም ታናሽ ጥጃ ያዘና ለብላቴናው ሰጠው፥ ያዘጋጅም ዘንድ ተቻኰለ። እርጎና ወተትም ያዘጋጀውንም ጥጃ አመጣ፥ በፊታቸውም አቀረበው እርሱም ከዛፉ በታች በፊታቸው ቆሞ ነበር፥ እነርሱም በሉ። እነርሱም፦ ሚስትህ ሣራ ወዴት ናት? አሉት። እርሱም፦ በድንኳኑ ውስጥ ናት አላቸው። እርሱም፦ የዛሬ ዓመት እንደ ዛሬው ጊዜ ወደ አንተ በእውነት እመለሳለሁ ሚስትህ ሣራም ልጅን ታገኛለች አለ። ሣራም በድንኳን ደጃፍ በስተ ኋላው ሳለች ይህንን ሰማች።
አብርሃምና ሣራም በዕድሜአቸው ሸምግለው ፈጽመው አርጅተው ነበር በሴቶች የሚሆነውም ልማድ ከሣራ ተቋርጦ ነበር። ሣራም በልብዋ እንዲህ ስትል ሳቀች፦ ካረጀሁ በኋላ በውኑ ፍትወት ይሆንልኛልን? ጌታዬም ፈጽሞ ሸምግሎአል።እግዚአብሔርም አብርሃምን አለው። ካረጀሁ በኋላ በውኑ እወልዳለሁን? ስትል ሣራ ለምን ሳቀች? በውኑ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር አለን? የዛሬ ዓመት እንደ ዛሬው ጊዜ ወደ አንተ እመለሳለሁ ሣራም ልጅን ታገኛለች። ሣራም ስለ ፈራች፦ አልሳቅሁም ስትል ካደች። እርሱም፦ አይደለም፥ ሳቅሽ እንጂ አላት ። ከታሪኩ እንደምረዳው በብሉይ ኪዳን ከሚገርሙ የሥላሴ ምሳሌዎች አንዱ በአብርሃም ቤት የተፈጸመው ነው ። ምክንያቱም የሠላሴ አንድነትና ሦስትነት የተገለጸበት ነውና
ይህ የአብርሃም መስተንግዶ ታላቅ ትምህርት አለው፤
- አብርሃም እንግዳን አክብሮ በመቀበሉ ሥሉስ ቅዱስን ለመቀበል በቃ እኛም እንደ አብርሃም እንግዳ ተቀባይ ብንሆን እንደ አብርሃም በጸጋ የእግዚአብሔር ማደሪያ እንሆናለን
- አብርሃም እንግዳን አክብሮ በመቀበሉ ከሥሉስ ቅዱስ ተስፋው ተነገረው እኛም እንደ አብርሃም እንግዳ ተቀባይ ብንሆን እንደ በዚህ ዓለም የጨለመብን ተስፋ በሥላሴ ይበራልናል ።
- አብርሃም እንግዳን አክብሮ በፍቅር በመቀበሉ የፍቅር ባለቤት የሆኑ ሥሉስ ቅዱስ ፍቅራቸውን ገለጹበት እኛም እንደ አብርሃም እንግዳን በፍቅር ተቀባይ ብንሆን እንደ አብርሃም ፍቅር ባለቤት ሥሉስ ቅዱስ ፍቅርን በጸጋ ያጎናጽፉናል
- አብርሃም እንግዳን አክብሮ በእምነት በመቀበሉ ከሥሉስ ቅዱስ የእምነቱን ዋጋ ተቀብሏል እኛም እንደ አብርሃም እንግዳን በእምነት ተቀባይ ብንሆን እንደ አብርሃም ሥሉስ ቅዱስ የእምነታችንን ዋጋ በመንግሥተ ሰማያት ይሰጡናል ።
በአጠቃላይ በዚህ በዓል የሥላሴ ፍቅር የአብርሃም እምነት የሣራ ትዕግሥት በአንድነት የታየበት ብዙ ትምህርት የምንማርበት በዓል ነው በፍቅር መኖር በእምነት መጽናት ትዕግስትን ገንዘብ ማድረግ ይገባናል ።
በምግባር በሃይማኖት ጸንተን እንደ አእምሮአችን ስፋት በምንችለው መጠን ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እያልን በምስጋና ጸንተን የሥላሴን መንግሥት እንወርስ ዘንድ ሥሉስ ቅዱስ ጥበብ ምሥጢርን ይግለጹልን አሜን።
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
ሥጋንም የሚገድሉትን ነፍስን ግን መግደል የማይቻላቸውን አትፍሩ …›› (ማቴ፲፣፳፰)
ከዲ/ን ተስፋዬ ቻይ
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱሳን ሐዋርያትን የምሥራቹን ወንጌል ሰብከው የጨለመውን የሰው ልጅ ልቡና በወንጌል ብርሃንነት ያበሩ ዘንድ፣ ከጣዖተ አምልኮ አውጥተው የፈጠራቸውን የሚመግባቸውን እግዚአብሔር ያውቁና ያመልኩ ዘንድ፣ በጠላት ዲያቢሎስ አሳሳችነት የመረረ ሕይወታቸውን በወንጌል ጨውነት ያጣፍጡ ዘንድ ወደ ዓለም በላካቸው ጊዜ ጠላት ዲያሎስ በክፉዎች እያደረ መከራ እንደሚያመጣባቸው፣ ይህንንም እንደ እባብ ብልህ ፣እንደ ርግብ የዋህ ሆነው እንዲያልፉ ፣ሳይፈሩና ሳይሰቀቁ እንዲመሰክሩ አዘዛቸው ፤ መከራቸው ስደት ፣መጠማት፣ ግርፋትና ረኀብ ባቻ ሳይሆን ሥጋዊ ሞት( የነፍስ ከሥጋ መለየት) እንደሚገጥማቸውና ይህም አንዳች እንዳያስፈራቸው ነገራቸው፤ ምድራዊ ሩጫቸው በሰማዕትነት ቢገታም ሰማየያዊ መኖሪ ዘለዓለማዊ ሕይወት እንዳለ የታመነውን ተስፋ ሰጣቸው፡፡ ቅዱሳን አበው ሐዋርያት ጌታችን ሞትን ድል አድርጎ በተነሣ በአርባኛው ቀን፣ ካረገ በአሥረኛው ቀን ባናገረው ትንቢት ፣በገባላቸው ቃል መሠረት የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ላከላቸው፣በጾም በጸሎ መንፈሳዊ ተግባራቸውን ጀመሩ ፤እምነታቸው ጸንቶ፣ፍርሃት ርቆላቸው ጥቡዐን ( ደፋሮች) ሆነው የእውቀት ተከፍሎ ሳይኖርባቸው ፤ዓለምን በዕጣ ተከፋፍለው የምሥራቹን ወንጌል ማስተማር ጀመሩ፡፡
ክቡር የሆነውን የሰው ልጅ ከገባበት ከንቱ ሕይወት አውጥተው ወደ ሕይወት ይመሩት ጀመር፣ የእግዚአብሔርን አምላክነት፤ የድንግል ማርያምን ጸጋ በረከት፣ የቅዱሳንን ክብር እየገለጡ፣ የዲያቢሎስን ሐሰተኛነት ፣የጣዖት አምልኮን ከንቱነት እያጋለጡ፤ በወንጌል ብርሃንነት በክፋት የጨለመውን እያበሩ፣ በተስፋ መቁረጥ የመረረ ሕይወት ያጣፍጡ ጀመር፤ ሐሰተኛ የሐሰት አባት ጠላት ዲያብሎስ በአላውያን ነገሥታት እያደረ፣ ከአገር አገር ያሳድዳቸው፣መከራ ያጸናባቸው ጀመር፣ የተጠሩበትን ዓላማ ፣የሚጓዙበትን ፍኖት መዳረሻ ያውቃሉና በመከራው ፣በግርፋቱ ፣በመራብ መጠማቱ ፣በመታሠሩ ሰይሰቀቁ፣ሳይፈሩ ፤ወንጌልን አስተማሩ፡፡
የሰውን ልጅ በቅናት ከፈጣሪው አጣልቶ በኃጢአት ምርኮኝነት በባርነት ገዘቶ የነበረው ሰይጣን( ዲያሎስ) በመድሃኒት ክርስቶስ መከራ መስቀል ፣ሞትና ትነሣኤ ነጻ እንደወጡ የምሥራቹን በመስበካቸው ፤የመከራውን ዓይነት በቅዱሳን ሐዋርያት አደረሰባቸው እነርሱ ግን ‹‹…ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል መከራ ወይስ ጭንቀት፣ወይስ ስደት፣ወይስ ረኀብ፣ወይስ ራቁትነት፣ወይስ ፍረሃት፣ወይስ ሰይፍ ነውን፣ስለአንተ ቀኑን ሙሉ እንገደላለን እንደሚታዱ በጎች ተቆጠርን…››( ሮሜ ፰፣፴፭) በማለት ሁሉን በሚያስችል አምላካቸው ሁሉን ችለው ወንጌልን ሰበኩ ፤የተሰጠው የተስፋ ቃል ፣የተነገረው ትንቢት፣ የተመሰለው ምሳሌ መፈጸሙን፣አዳምና ልጆቹ ከሲዖል እስራት፣ከባርነት ወደ ነጻነት፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን፣ ከሲዖል ወደ ገነት፣ከውረደት ወደ ክብር መመለሱን አወጁ፤ በአዳምና ልጆቹ ዕንባ መፍሰስ ይፈነድቅ፣ በሰቆቃቸው ይስቅ የነበረ ዲያቢሎስ መታሠሩን ሲዖል ተመዝብራ፣ ገነት መከፈቷን አበሠሩ፡፡
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክረስቶስ አስቀድሞ እንደነገራቸው ፣እስራቱ፣ ግርፋቱ፣ በእሳት መተኮሱ በሾተል ( በሰይፍ) መመተሩ ተፈራረቆባቸው፤ ቅዱስ ኤፍሬም ቤዛዊት ዓለም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ባወደሱበት የሐሙስ ውዳሴ ማርያም ላይ ‹‹..አማን መነኑ ሰማዕት ጣዕማ ለዛ ዓለም ወመዓዉ ደሞሙ በእንተ እግዚአብሔር ወተዐገሱ ሞተ መሪረ በእንተ መንግሥተ ሰማያት..›› ሰማዕታት የዚህችን ዐዓለም ጣዕም በእውነት ናቁ ደማቸውንም ስለ እግዚአብሔር አፈሰሱ ስለ ምንግሥተ ሰማያትም መራረ ሞትን ታገሡ፡፡( ውዳሴ ማርያም ዘሐሙስ ዳዊት ዘነግሠ) በማለት እንደገለጸው በእምነት ጸንተው በምግባር ጎልብተው ታገሡ፤ ብርኃናቸው በሰው ፊት በራላቸው፣ በሰገነት ላይ ስበኩ ያላቸውን እውነትና ፍቅሩን መሠከሩ ሰማዕትነትን ተቀበሉ፡፡
ቅድስት ቤተክረስቲያን ስለክርቶስ ፍቅር መስክረው ሰማዕትነት የጠቀበሉ ቅዱሳን አበው ሐዋርያትን በስማቸው ቤተክርስቲን አንጻ ፣ መታሰቢያቸውን ታከብራለች በተሰጣቸው ቃልኪዳን ምዕመናን እንዲድኑ፣በረከታቸውን እንዲያገኙ ፣በቃል ኪዳናቸው ትማጸናለች፤ ሐምሌ አምስት ቀን መታሰቢያ ከሚደረግላቸው ፣ገድላቸው ከሚዘከርላቸው አባቻችን መካከል ብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ ተጠቃሽ ናቸው፡፡
ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስ የዮና ልጅ ስምዖን ተብሎ በመጽሐፍ ቅዱስ ስሙ ተጠቅሶ የምናገኘው ቅዱስ ጴጥሮስ ከቅዱስ እንድርያስ ወንድሙ ጋር በመሆን እንደ አባታቸው ዮና ዓሣ እያጠመዱ በመሸጥ ሕወታቸውን ይመሩ ነበር፤ጌታችን ‹‹ ስምዖን ሆይ ከእንግዲህ ወዲህ ሰውን እንድታጠምድ አደርግሃለሁ ›› በማለት ተከተሉኝ ብሎ ወንድማማቾቹን አስከተላቸው ቅዱስ ጴጥሮስ አብረውት ከነበሩ ሐዋርያት መካከል ፈጣንና ጥያቄዎችን ይጠይቅ ነበረ ሊቀ ሐዋርትም ነው፤ጌታችን ‹‹ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል ብሎ ሲጠይቅ ፤ሰዎች የሚሉትን ከገለጸ በኋላ ‹‹ አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ ›› ብሎ መሰከረ በዚህም ‹‹ብጹዕ ነህ ››ተብሎ ተመስግኗል ፡፡ (ማቴ ፲፮፤፩ ) ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታችን በተያዘባት በዚያች ሌሊት እስከ ቀያፋ ግቢ ድረስ ተከትሎ ነበር ፤ከጌታችን ጋር እንደሆነ ሲጠየቅ አላውቀውም ቢልም ንስሐ ገብቶ ተጸጽቶ ጌታችንም ይቅር ብሎታል፡፡
ጌታችን ከማረጉ በፊት ቅዱስ ጴጥሮስን ‹‹ ግልገሎቼን ፣ጠቦቶቼን ፣በጌቼን ጠብቅ በማለት እንዳዘዘው (አደራ እንደሰጠው ) ድውያነ ሥጋን በተአምራት ድውያነ ነፍስን በወንጌል ትምህርት እያዳነ ያላመኑትን አሳምኖ ወደ ክርስትና እምነት መልሷል ፡፡ወንጌልን ይሰብክ በነበረበት ወቅት ታስሮ ከወህኒ ቢገባም እግዚአብሔር መልአኩን ልኮ ከእሥር ቤት እንዲወጣ አድርጎታል ( የሐ.ሥራ 12፣1-) ፤ከማስተማር በተጨማሪም ሁለት መልዕክታትን ጽፏል ፤በወንጌል ተልእኮ በነበረ ጊዜ አግርጶስና አስታብዮስ የሚባሉ የሮም መኳንንት ሊያስገድሉት ሲሹ ምዕመናን እንዲሸሽ ግድ አሉት በዚህን ጊዜ ከሮም ከተማ ወጥቶ ሲሄድ ጌታን በዕለተ ዐርብ መስቀል ተሸክሞ እንደነበረ ሆኖ ተገለጸለት ቅዱስ ጴጥሮስም
‹‹ጌታ ሆይ በኢየሩሳሌም አይሁድ እንደሰቀሉህ በሮም ከተማ ልትሰቀል መጣህን ››አለ ጌታችንም ‹‹ በሮም ከተማ የሚሰቀልልኝ ካላገኘሁ እሰቀላለሁ ››አለው ቅዱስ ጴጥሮስም ወደ ሮም ተመለሶ ማስተማር ቀጠለ ኔሮን ቄሣር ይዞ አሰረው ፤ጌታችን አስቀድሞ ‹‹በሸመገልክ ጊዜ ወገብህን ያስታጥቁሃል›› በማለት ስለ አሟሟቱ ነግሮት ነበርና በስቅላት እንዲሞት ሲፈረድበት ‹‹እንደ ጌታዬ ወደ ላይ አትስቀሉኝ የቁልቁሊት ስቀሉኝ አለ ፤ ሊቀ ሐዋርያት ፣ትሁቱና ታታሪው ፣ፈጣኑ ፣ጠይቆ የሚረዳ ፣ተጸጽቶ የሚመለስ በአንደበቱ ትምህርት በተግባር ህይወቱ ክርስትናን የገለጠ የናቃትን ዓለም ዞሮ ያልተመለከተ ኃጢአትን በንስሐ ድል የነሣ አምላኩን ሁሉን ጥሎ የተከተለ ብዙዎችን በትምህርቱ ከጣዖት አምልኮ ወደ ክርስትና ከጨለማ ወደ ብርሃን ከሞት ወደ ህይወት ያሻገረ ታላቁ ሐዋርያ ቅዱስ ጴጥሮስ ሐምሌ አምስት ቀን በመስቀል የቁልቄሊት ሰቅለውት ሰማዕትትነት ተቀበለ ፡፡ ካረፈም በኋላ መርቄሎስ የሚባላው ደቀ መዝሙር ከመስቀል አውርዶ እንደ አገሩ ልማድ በወተት እና በወይን አጥቦ ሽቶ ቀብቶ በነጭ ልብስ ገንዞ በክብር ቫቲካን በሚባል ሥፍራ አኖረው ፡፡ ጸሎቱ በረከቱ በእኛ በሕዝበ ክርስቲያኖች ላይ አድሮ ይኑር አሜን !
ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ፡– የቀድሞ ስሙ ሳውል ሲሆን ትርጉሙም ስጦታ ማለት ነው የትውልድ ሥፍራውም በጠርሴስ ከተማ ነው ዕድሜው 15 ዓመት ሲሆነው በኢየሩሳሌም ከተማ ከነበረው የገማልያል ትምህርት ቤት ገባ ፤በዚህም የአይሁድን ሥርዓት እየተማረ እስከ 30 ዓመቱ ቆየ በዚሁም እድሜው የአይሁድ ሸንጎ አባል ሆነ ፡፡ በአይሁድ ሸንጎ አባልነት ለሁለት ዓመታት በሠራበት ወቅት ለኦሪታዊ እምነቱ ቀናተኛ ፈሪሳዊ በመሆኑ ክርስቲያኖችን በማንኛውም አጋጣሚ ይቃወም ነበር ፡፡ሐዋርያት ወንጌልን በሚስተምሩበት ጊዜ ከሚቃወሟቸው መካከል እንዱም ነበር ቅዱስ እስጡፋኖስ በአይሁድ ሸንጎ በቀረበ ጊዜ የተከራከረው እንዲሁም የወጋሪዎችን ልብስ ይጠብቅ የነበረውም እርሱ ነው፡፡
ክርስቲያኖችን ሊያስር ወደ ደማስቆ ከተማ አመራ ጥቂት ሲቀረው ከሰማይ ብርሃን ወርዶ አካባቢውን አለበሰው ሳውልም ከምድር ወደቀ ማየትም ተሳነው ከሰማይም ‹‹ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ ›› የሚለውን ድምጽ ሲሰማ እየተርበተበት ‹‹…ጌታ ሆይ ማን ነህ ?›› በማለት በጭንቅ ውስጥ ሆኖ ጠየቀ ጌታችንም ‹‹አንተ የምታሳድደኝ እኔ የናዝሪቱ ኢየሱስ ነኝ የመውጊያውን ብረት ብትቃወም ለአንተ ይብስብሃል ›› ሲል ተናገረው፡፡ ከአሳዳጅነት ሕይወት አውጥቶ ወንጌልን የሚሰብክ ሐዋርያ አደረገው ፡፡
ቀድሞ ለአይሁድ ሥርዓት በነበረው ቅንዓት የሚታወቀው ቅዱስ ጳውሎስ ወንጌልን ሊሰብክ በመነሳቱ አይሁድ በክፋት ተነሱበት ፤ቀድሞ ያሳድዳቸው የነበሩ ክርስቲያኖች የቅዱስ ጳውሎስን መመለስ ሊያምኑ አልቻሉም፤በሁለት በኩል ፈተናዎች ገጠሙት፤ይህንን ሁሉ ተቋቁሞ ወንጌልን ሰበከ፤ለደቀመዛሙርቱ ( ለምዕመናን ክርስያን የሚለውን ስያሜ የሰየመው ቅዱስ ጳውሎስ ነው ። ‹‹ደቀ መዛሙርትም መጀመሪያ በአንጾኪያ ክርስቲያን ተባሉ››የሐ ሥራ ፲፩፤ ፳፯ ቅዱስ ጳውሎስ ለወንጌል ተልዕኮ ሦስት ታላላቅ ጉዞዎችን ወደ ተለያዩ አገራት አድርጓል በዚህም አገልግሎቱ ብዙ መከራን ተቀብሏል ፡፡ አስረውታል ፣ገርፈውታል ብዙ እንግልትን ተቀብሏል፤ለቆሮንቶስ ምዕመናን በላከው መልእክቱ ስለደረሰበት መከራ እንዲህ ገልጧል ‹‹ …በድካም አብዝቼ ፣በመገረፍ አብዝቼ ፣በመታሠር አትርፌ ፣በመሞት ብዙ ጊዜ ሆንሁ ፡፡አይሁድ አንድ ሲጎድል አርባ ጅራፍ አምስት ጊዜ ገረፉኝ ፡፡ ሦስት ጊዜ በበትር ተመታሁ ፣አንድ ጊዜ በድንጋይ ተወገርኩ ፣መርከቤ ሦስት ጊዜ ተሰበረ ሌሊትና ቀን በባሕር ውስጥ ኖርሁ ፤ብዙ ጊዜ በመንገድ ሄድኩ በወንዝ ፍርሃት ፣በወንበዴዎች ፍርሃት ፣በወገኔ በኩል ፍርሃት ፣በከተማ ፍርሃት ፣በምድረ በዳ ፍርሃት ፣በባሕር ፍርሃት ፣በውሸተኞች ወንድሞች በኩል ፍርሃት ነበረብኝ በድካምና በጥረት ብዙ ጊዜም በመጦም በብርድና በራቁትነት ነበርሁ የቀረውንም ነገር ሳልቆጥር ዕለት ዕለት የሚከብድብኝ የአብያተክርስቲያናት አሳብ ነው ፡፡›› 2ኛ ቆሮ ፲፩፣፳፫-፳፱
ቅዱስ ጳውሎስ ወንጌልን ከአገር አገር እየዞረ ከማስተማሩ በተጓዳኝ 14 መልዕክታትን ጽፏል ቅዱስ ጳውሎስ ወንጌልን በማስተማሩ ተይዞ ወደ ሮም ተወሰደ ኔሮን ቄሣር ቅጥ ባጣ ጥጋቡ የሮምን ከተማ ካቃጠለ በኋላ ሕዝቡ በከተማዋ መቃጠል በመቆጣቱ ፣በማዘኑ ጥፋቱን በክርስቲያኖች ላይ አሳበበ ክርስቲያኖችን ሲያሳድዱ ሲገርፉ ፣ሲገድሉ ቅዱስ ጳውሎስም በ65 ዓ.ም በኒቆልዮን ከተማ ሲያስተምር ተይዞ ወደ ወኅኒ ገባ ለሁለት ዓመታት ከስድስት ወር በጨለማ ቤት ታስሮ ከቆየ በኋላ በሮም ከተማ በተወለደ በ74 ዓመቱ ሐምሌ አምስት ቀን አንገቱን ተቀልቶ በሰማዕትነት አለፈ ፡፡በረከቱ ይደርብን አሜን ፡፡
ውድ ክርስቲያኖች የአባቶቻችንን ገድል ሰማዕትነት ስንሰማ፣ በዓላቸውን (መታሰቢያቸውን) ስናከብር፤ በረከታቸውን ለመቀበል ብቻ ሳይሆን ፈለጋቸውን በመከተል በምገባር ልንጎለብት በእምነት ልንጸና ይገባናል ዓለም ለክርስቲያኖች የድሎት ቦታ ሳትሆን የመከራ ስፍራ ናት፣ ጌታችን ‹‹ በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ…›› በማለት እንደገለጸልን ፣በስሙ በማመናችን ጠላት ዲያብሎስ በተለያየ መልኩ ፈተናዎችን ያመጣልና በእምነታችን ጸንተን በትእግስት ሆነን ልንታገለው ይገባል። ቤተ ክርስቲያን በባህር ላይ እነደሚሄድ ወጀቡ ማዕበሉ እንደሚያንገላታው መርከብ ናት ግን ደግሞ አትሰጥምም ፤‹‹የገሃነም ደጆች አይችሏትም›› ( ማቴ ፲፮፣፲፰ ) ተብላልና ፤ይታገሏታል አያሸንፏትም፣ ቀስታቸውን ያስወንጭፋሉ ግን አይጎዷትም፤ምክንያቱም በጽኑ ዓለት ላይ ተመሠርታለችና፤ በዘመነ ሰማዕታት በዋሻ ውስጥ ሆና አልጠፋችም የመከራው ዘመን ሲያልቅ ዳግመኛ በራች፣ሰፋች፣ ውድቀቷን የሚመኝ ጠላት ዲያስን ድል አደረገች ፡፡ ውድ ክርስያኖች በክርስትና ሕይወት ስንኖር ፈተናው መልኩን ይቀይራል እንጂ አይቀርም፤ አምላካችን ደግሞ መሸከም ከምንችለው በላይ እይሰጠንም ‹‹ ቀንበሬ ልዝብ ሸክሜ ቀሊል…›› ( ማቴ፲፩፣፴ ) ብሎናልና ፤የአበው ቅዱሳን ሰማዕታትን ፈለግ በመከተል በእምነታችን ጸንተን፤ ከሞት በኋላ ላለው ሕይወታችን ‹‹ … ኑ እናንተ የአባቴ ቡሩካን ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ የተዘጋጀላችሁን ምንግሥቴን ውረሱ››( ማቴ ፳፭፣፴፭) የሚለውን ሕይወት ቃል ለመስማት ያብቃን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!
እንኳን ለእናታችን ለእመቤታችን ለቅድስተ ቅዱሳን ለድንግል ማርያም ሰኔ ጐልጐታና ሕንጸተ ቤተ ክርስቲያን (ለመጀመሪያ ጊዜ ቤተ ክርስቲያኗ ለታነጸበት) ክብረ በዓል በሰላምና በጤና አደረሰን አደረሳችሁ፡፡
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ።
“ለዛቲ ቤት ሣረራ አብ ቀዲሙ ለዛቲ ቤት ሐነጻ ወልድ ወፈጸማ መንፈስ ቅዱስ”
(ይችን ቤት አብ ሠራት ወልድ አነጻት መንፈስ ቅዱስ ፈጸማት አከናወናት )
“ቅዱስ ያሬድ “
ክፍል አንድ
ሕንጸተ ቤተ ክርስቲያን
በሐዲስ ኪዳን የመጀመሪያዋ ቤተ ክርስቲያን በሀገረ ቂሣርያ፣ ኬልቄዶንያ አውራጃ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስም ሰኔ ፳ ‹‹ሕንጸታ ቤታ›› ፤ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያለ እንጨት፣ ያለ ጭቃና ያለ ውኀ በሦስት ድንጋዮች ቤተ ክርስቲያኗን ያነጸበት ዕለት ነው።
አናጺውም ደግሞ ራሱ ባለቤቱ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሆን፤ ቦታው በፊልጵስዩስ ነው፤ ቤተ ክርስቲያኗ የተሰየመችው ደግሞ በእመቤታችን ስም ነው።
ቅዱስ ያሬድ እንዲህ ሲል አብራርቶታል –ተቀደሲ ወንሥኢ ኃይለ ኦ ቤተ እግዚአብሔር ፣ እስመ ናሁ ንጉሥኪ፣በጽሐ ዘያበርህ ለኪ በኃይሉ፣
ለዛቲ ቤት ሣረራ አብ ቀዲሙ፣
ለዛቲ ቤት ሐነጻ ወልድ፣
ለዛቲ ቤት ወፈጸማ መንፈስ ቅዱስ፣
የእግዚአብሔር ማደሪያ የሆንሽ ቤተ ክርስቲያን ሆይ በኃይሉ የሚያበራልሽ ንጉሥሽ እነሆ ደርሷልና ክብርሽ ከፍ ከፍ ይበል ኃይልንም ያዥ ይልና
ይችን ቤት አስቀድሞ አብ ሠራት ወልድ አነጻት መንፈስ ቅዱስ ፈጸማት በማለት ይጨርሳል::
ጥንተ ነገሩስ (ታሪኩ) እንደምን ነው ቢሉ፤
ስም አጠራሩ የተመሰገነ ይሁንና አምላካችን መደኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱን ‹‹ሑሩ ወመሐሩ ኵሎ አሕዛበ፤ አሕዛብን ሁሉ ሒዱና አስተምሩ፡፡›› /ማቴ. ፳፰፥፲፱/ ባላቸው ቃል መሠረት ሐዋርያት በወንጌል ያርሷት ዘንድ ይህችን ዓለም በዕጣ ተካፍለዋታል::
የሰው ልጅ ድኅነቱ የሚፈጸመው ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ሲቀበል ነውና (ዮሐ. ፮፥፶፮) አበው ሐዋርያት ቊርባንን በተመረጡ ሰዎች ቤት እያዘጋጁ ቀድሰው ያቆርቡ ነበር::
በመጀመሪያ በጽርሐ ጽዮን፣ቀጥሎም በተለያዩ ሰዎች ቤት እንዲህ ይከናወን ነበር፡፡ ለጸሎት ሥራ ደግሞ አንዳንዴ ምኵራበ አይሁድን ይጠቀሙ ነበር:: እየቆየ ሲሔድ ግን ከአሕዛብ ያመኑ ሰዎች ቊጥር እጅጉን በመብዛቱ ጌታችን በዐረገ በስምንተኛው ዓመት ቅዱስ ጳውሎስና ቅዱስ በርናባስ ወደ ፊልጵስዩስ ገብተው በክርስቶስ ስም አሳምነው ብዙ አሕዛብን ካጠመቁ በኋላ/በተለይ ቅዱስ ዻውሎስ ያሳመናቸው ለጸሎት እያሉ ወደ ጣዖት ቤት መግባት አመጡ::/ በዚህ ምክንያት መምህራን ሕዝቡን ‹‹ካመናችሁ በኋላ እንዴት ወደ ጣዖት ቤት ትገባላችሁ?›› ቢሏቸው ‹‹እኛ ምን እናድርግ! የምንጸልይበት ቤት የለን››ሲሉ መለሱላቸው:: ነገሩ ሲያያዝ ከደጋጉ ሐዋርያት ዻውሎስና በርናባስ ደረሰ::
ወዲያውኑ አንዳንድ ወንድሞች የጸሎት ቤት ‹‹ለምን አናንጽም?›› ብለው ነበር:: ቅዱስ ዻውሎስ ግን ‹‹ሊቀ ሐዋርያቱ ሳይፈቅድ አይሆንም›› አለ:: (ለዚህ ነው ዛሬም ሊቀ ዻዻስ ካልፈቀደ ቤተክርስቲያን የማይታነጸው፡፡) ከዚያ ቅዱሳን ዻውሎስና በርናባስ ሐዋርያቱ ወዳሉበት ሔደው ነገሩን ለቅዱስ ዼጥሮስ አስረዱ:: ሊቀ ሐዋርያቱ ቅዱስ ዼጥሮስም ‹‹የጌታችን ፈቃዱ መሆኑን እናውቅ ዘንድ ተያይዘን ሱባኤ እንግባ›› አለ::
በዚህ ጊዜ ሐዋርያት በያሉበት በአንድ ልብ ሱባኤ ገቡ:: በሱባኤያቸው መጨረሻም ክብር ይግባውና ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በኪሩቤል ጀርባ ላይ ሆኖ እልፍ አእላፍ መላአክትን አስከትሎ በግርማ ወደ እነርሱ ወረደ፤እመቤታችንም በቀኙ ነበረች የሞቱትን አስነሥቶ፣ ያሉትንም ጠርቶ ቅዱሳን ሐዋርያትን በፊልጵስዩስ አገር ሰብስቦ ‹‹በእናቴ በድንግል ማርያም ስም ከጽንፍ እስከ ጽንፍ የሚሠራውን የአብያተ ክርስቲያናት ሥራ ላሳያችሁ፤ ሥርዓቱንም ላስተምራችሁ ሰብስቤአችኋለሁ›› ብሎ ወደ ምሥራቅ ይዟቸው ወጣ፡፡ በዚያ ሥፍራ የነበሩትን ሦስት ድንጋዮችንም የተራራቁትን አቀራርቦ፣ ጥቃቅኑን ታላላቅ አድርጎ ቁመቱን በ፳፬፤ ወርዱን በ፲፪ ክንድ ለክቶ ለቅዱሳን ሐዋርያት ሰጣቸው፡፡
ከዚህ በኋላ ቅዱሳን ሐዋርያት ሰም እሳት ሲያገኘው እንዲለመልም፣ ድንጋዩ በእጃቸው ላይ እየተሳበላቸው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑን ሠርተው ፈጽመውታል፡፡ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ የተሠራውም ጌታችን በዐረገ በ፲ኛው፤ እመቤታችን በዐረገች በ፬ኛው ዓመት ሰኔ ፳ ቀን ሲኾን፣ በ፳፩ኛው ቀን (በማግሥቱ) ኅብስት ሰማያዊ፣ ጽዋዕ ሰማያዊ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ወረደ፡፡ ጌታችንም ከእመቤታችን ጋር ከሰማየ ሰማያት መጥቶ እመቤታችንን ታቦት፤ ሐዋርያትን ልዑካን አድርጎ፣ እርሱ ሠራዒ ካህን ሆኖ ቀድሶ ካቈረባቸው በኋላ ‹‹እምይእዜሰ አንትሙኒ ከመዝ ግበሩ፤ ከዛሬ ጀምሮ እናንተም እንደዚህ አድርጉ›› ብሎ አዝዟቸው በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐርጓል፡፡
ይህ ታሪክ ብዙ ምሳሌዎች አሉት፡፡ ይኸውም፡- የሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ቁመት በነገሥታት ዘመን የነበሩ ነቢያት፤ አንድም የ፳፬ቱ ካህናተ ሰማይ አምሳል ሲሆን፣ ወርዱ ደግሞ የ፲፪ቱ ሐዋርያት ምሳሌ ነው፡፡ ሦስቱ ድንጋዮች የሥላሴ አምሳል ሲሆኑ፣ ከታች አቀማመጣቸው ሦስት፤ ከላይ ሕንጻቸው አንድ መሆኑ የሥላሴን ሦስትነትና አንድነት ያመለክታል።
ሊቁ ቅዱስ ያሬድም በድጓው ላይ ስለ ክብረ ቤተ ክርስቲያን፦
“እንተ ተሐንጸት በስሙ፤ ወተቀደሰት በደሙ ወተዐትበት በዕፀ መስቀሉ ጊሡ ኀቤሃ እስመ ኀይለ እግዚአብሔር ላዕሌሃ” (በስሙ ታነጸች፤ በደሙም ከበረች፤ በዕፀ መስቀሉም ተባረከች፤ ወደ ርሷ (ቤተ ክርስቲያን) ሒዱ የእግዚአብሔር ኀይል በእርሷ ላይ ነውና) ይላል፡፡
አባ ጽጌ ድንግል በማሕሌተ ጽጌ መጽሐፋቸው ላይ፡-
“በሠላስ አእባን ገጸ ሥላሴሁ ለአምሮ
ሐኒጸ ቤትኪ ድንግል ድኅረ ፈጸመ ሣርሮ
አመ ወረደ ለበዓል ምስሌኪ በአማኅብሮ
እንዘ ይብላ ቃለ ለዘምሮ
ልዑል ቀደሰ ማኅደሮ
ደናግል ለጽጌኪ ዘበጣ ከበሮ”
(ድንግል በአካል ሦስት መሆኑን ለመግለጽ በሦስት ድንጋዮች ቤትሽን መሥራት ከፈጸመ በኋላ፤ ከአንቺ ጋር ለበዓል በተገለጸ ጊዜ ልዑል ማደሪያውን ቀደሰ እያሉ ልጅሽን ለማመስገን ደናግል በከበሮ ምስጋናን አቀረቡ) በማለት ገልጿታል፡፡
……ይቀጥላል
‘’ከመላእክት አለቆች አንዱ የሆነው ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ።’’ (ት.ዳን. ፲ ፥፱)
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
እንኳን ለቅዱስ ሚካኤል ዓመታዊ በዓል አደረሳችሁ‼
በዓል “አብዐለ” አከበረ÷ አበለጠ÷ ዕለትን በዓል አደረገ ከሚለው ግስ የወጣ ስም ነው። ይህም የደስታ፥የዕረፍት ቀን ፥በዓመት በወርና በሳምንት የሚከበር፥ ያለፈ ድርጊት የሚታወስበትና ምእመናን የበዓሉን ምሥጢር እያሰቡ ሐሴት የሚያደርጉበት ማለት ነው:: ዕለቱም ምእመናን መደበኛ ሥራቸውን ትተው ለበዓሉ ይገባዋል የሚሉትን ተግባር የሚፈጽሙበት የበዓሉን ባለቤት እግዚአብሔርንና የበዓሉን ምክንያት እያሰቡና እያመሰገኑ ደስ የሚሰኙበት ነው። ቅዱስ ዳዊት “….በዓልን የሚያደርጉ ሰዎች በምስጋናና በደስታ ቃል ሲያመሰግኑ ተሰሙ:: ”(መዝ ፵፩፥፬፡፡) እንዳለው። በዓላት የዕረፍት ቀናት ናቸው ማለት ከሥጋዊ ወይም ምድራዊ (ዓለማዊ) ሥራዎች የሚያርፉባቸው ናቸው ለማለት ነው። በአንጻሩ ግን መንፈሳዊ ሥራዎች ሁሉ እንደየችሎታ የሚከናወንባቸው መሆናቸው መረሳት የለበትም፡፡ እነዚህ ዕለታት እግዚአብሔር በራሱ ወይም በቅዱሳኑ አድሮ ለሠራቸው ድንቅ ሥራዎች (ተአምራት) መታሰቢያዎች ናቸው። (መዝ፻፲፥፬)፡፡ ፻፲፩፥፮፡፡ ሉቃ፳፪፥፲፱፡፡)
በበዓሉ ዋዜማ ለዕለቱ የተሠራውን የምስጋና ቃል እየመሩ፣ እየተመሩ፣ እያነሡ፣ እየዘመሙ፣ መስተብቁዕ እየደገሙ፣ እያመረገዱ፣ እያመለጠኑ፣ እየጸፉ ሊቃውንቱ እግዚአብሔርን ያመሰግናሉ። በዚህ መልኩ ከሚከበሩ ዐበይት በዓላትም አንዱ በዓለ ቅዱስ ሚካኤል ነው።
ሚካኤል ማለት በዕብራይስጥ ቋንቋ ሚ-መኑ፣ካ-ከመ፣ኤል-አምላክ መኑ ከማከ አምላክ? እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው? ማለት ነው።(ኪ.ወ.ክ)።
ቅዱስ ሚካኤል ዲያብሎስ በትዕቢቱ ፈጣሪነትን ሽቶ በዓለመ መላእክት ሁከት ባስነሣ ጊዜ የቅዱሳን መላእክት ፊታውራሪ ሆኖ ዲያብሎስን የተዋጋ ጽኑዕ መልአክ ነው።
“በሰማይም ሰልፍ ሆነ ሚካኤልና መላእክቱ ዘንዶውን ተዋጉት፣ዘንዶውም ከመላእክቱ ጋር ተዋጋ አልቻላቸውም። ከዚያም ወዲያ በሰማይ ሥፍራ አልተገኘላቸውም።”(ራእይ ፳፪:፯)
ቅዱስ ሚካኤል ሊቀ መላእክት ነው። ይሁዳ በመልእክቱ “የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል በማለት ሊቀ መላእክትነቱን ገልጾአል። (ይሁዳ ፱)
ይህችውም ቅሩበ መንበር ተደርጎ የተፈጠረው ዲያብሎስ የተዋት ክብሩ ናት።
ቅዱስ ሚካኤል ይቅር የሚል ከመዓት የራቀ ነው።(ሄኖ፥፲፥፩፪)
ለሰው ባደረገው በጎነት ለሕዝቡ ሁሉ ታዛዥ ነው። የቅዱስ ሚካኤል ሹመት በነገደ መላእክት ላይ ብቻ አይደለም፤ ነገር ግን የእግዚአብሔር ሕዝብ በሆኑት ላይ ጭምር ነው፡፡ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል፣ ለእኛ ለሰዎች አማላጅ ሲሆን ለቅዱሳ ጻድቃንና ሰማዕታት ደግሞ አጋዣቸው ነው፤ በሕይወታቸውና በተጋድሏቸውም እስከ መጨረሻው ይረዳቸዋል፡፡
ይህንንም በቤተ ክርስቲያናችን በመጽሐፈ ስንክሳር እና በድርሳነ ሚካኤል ሰኔ ፲፪ ቀን ተጽፎ እናገኘዋለን። ይህም ቀን መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ተከብሮ የሚውልበት ታላቅ ዕለት ነው፡፡ በእስክንድርያ ከተማ ክላወባጥራ የተባለች ንግሥት የበጥሊሙስ ልጅ ዙሐል በሚባል ኮከብ ስም ያሠራችው ታላቅ ምኲራብ ነበር፤ ሕዝቡም ሰኔ በገባ በዐሥራ ሁለት የዚህን ጣዖት በዓል ያከብሩ ነበር። ይህንንም ግብራቸውን እንዲተው አባታችን እለ እስክንድሮስ ቢነግራቸው አይሆንም አሉት።
በኋላም ጻድቅ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ሲነግሥ አብያተ ክርስቲያናት ይትረኃዋ ወአብያተ ጣዖታት ይትአጸዋ የሚል አዋጅ ስለወጣ በዚህ ምቹ ጊዜም የጣዖት አምልኮ እንደምን ያለ ክፉ ግብር እንደሆነና በጎ ዋጋም እንደሌለው ነግሮ እንዲተዉ ቢጠይቃቸው እኛስ ይህን አንተውም አሉት። እርሱም በጥበብ እንዲህ አላቸው፤ ‹‹ይህን ግብር ብትተው በዚህች ቦታ የሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤልን ቤተ ክርስቲያን እንሠራለን። መሥዋዕታችሁንም በዚያ ለቅዱስ እግዚአብሔር ታቀርባላችሁ አላቸው።›› በዚህ ተደስተው ተመለሱና ያንን የጣዖት ቤት አፍርሰው እጅግ ያማረች ቤተ ክርስቲያንን በመልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ስም ሠሩ። የመልአኩንም በዓለ ንግሥ በዚህች ዕለት አከበሯት። ከዚያን ጊዜም ጀምሮ የከበረ የመላእክት አለቃ የመልአኩ የሚካኤል የመታሰቢያውን በዓል በሰኔ ዐሥራ ሁለት ቀን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይከበራል፡፡ዳግመኛም ንዑድ ክቡር የሚሆን ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ባሕራንን በሰኔ ዐሥራ ሁለት ቀን ያዳነበት ድንቅ ተአምርም ይህ ነው። አንድ ደግ ሰው በዚያች ሀገር ይኖር ነበር። ክፉ ጎረቤትም ነበረው። ይህም ደግ ሰው ነዳያንን እጅግ የሚወድ የቅዱስ ሚካኤልንም ዝክር ሳያስታጉል የሚዘክር ሰው ነው። በዚህ ሥራው ግን ይህ ክፉ ጎረቤቱ ይዘብትበት ነበር። በኋላም ያ ደግ ሰው የሚሞትበት ቀን ሲደርስ ሚስቱን ዝክረ ሚካኤልን እንዳታቋርጥና ነዳያንን እንዳትዘነጋ ነግሯት ያርፋል። እርሷም ፀንሳ ነበርና እርሱ ከሞተ በኋላ የመውለጃዋ ጊዜ ደረሰ። ምጥም ቢጠናባት ወደ መልአኩ ጮኸች፤ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤልም ተራዳትና መልከ መልካም የሆነ ወንድ ልጅ ወለደች። መልአኩም እንዲህ አላት። ‹‹ልጅሽ የዚህ የጎረቤትሽን ሀብት ይወርሳል።›› መልአኩም ለጎረቤታቸው ጆሮውም ከፍቶለት ነበርና ይህን ነገር ሰማ። በዚህም ‹‹በምን ምክንያት ወስጄ ላጥፋው›› ብሎ ሲያስብ ሴቲቱ ልጅዋን ብቻዋን ለማሳደግ ተቸገረች፤ ‹‹ላሳድግልሽ፤ ለአንቺም ይኸው ገንዘብ እሰጥሻለሁ›› ብሎ ብዙ ወርቅ ሰጣት። እርሱም ‹‹ከእንግዲህ አርፋለሁ›› ብሎ ልጁን መጣያ ሳጥን ያዘጋጅና ወደ ባሕር ቢጥለው ባሕሩም ሩቅ ሀገር ወስዶት ከዳር ይጥለዋል።
ከዚህም በኋላ አንድ በጎቹን ያሠማራ ሰው ያገኘዋል። ያንንም ሳጥን ወስዶ ከቤት ያኖረዋል፤ በምን መክፈት እንደሚችል ሲያስብ ዳግመኛ ወደ ባሕሩ እንዲሄድ እግዚአብሔር ሐሳብ ያሳድርበትና ተነሥቶ ይሄዳል። ሲሄድም ዓሣ አጥማጅ ያገኝና ዓሣ ለእርሱና ለቤተሰቡ እንዲያጠምድለት ይነግረዋል። ያም ዓሣ አጥማጅ ሲያጠምድ ታላቅ ዓሣ አገኘና ሰጠው። ዋጋውን ሰጥቶም ወደ ቤት ተመለሰና ሆዱን ቢሰነጥቀው ቁልፉን በዚያ አገኘው። በዚያም ሳጥኑን ቢከፍት መልከ መልካም ልጅ አገኘ። ልጅም ስላልነበረው እጅጉን ተደሰተ። ባሕራን ብሎም ሰየመው።
ከብዙ ጊዜያት በኋላ ያ ክፉ ሰው ከንግድ ተመልሶ በዚያ መንገድ ሲያልፍ መሸበትና ከዚህ ሰው ቤት አደረ። ባሕራንንም ተመለከተውና ሰውየውን ልጁ እንደሆነ ለማወቅ ታሪኩን ጠየቀው፤ ሰውየውም የሆነውን ሁሉ ነገረው። ክፉ ሰውየውም ልጁ እንዳልሞተ ባወቀ ጊዜ ደነገጠና መልእክት ሊልከው ስለሚፈልግ የባሕራንን አባት ልጁን እንዲሰጠው ጠየቀው። እርሱም ተስማምቶ ሰጠው። በክፋትም ተነሣሥቶ ባሕራንን እንዳገኘው እንዲገድለው ለአገልጋዩ ደብዳቤ ጽፎ አገልጋዩና እርሱ ብቻ የሚያውቁትን ማኅተም አድርጎ ሰጠው። ‹‹ይቺን ደብዳቤ በምታነባት ጊዜ ደብዳቤዋን ይዞ የመጣውን ገድለህ በጉድጓድ ውስጥ ጣለው፡፡ ማንም እንዳያውቅ›› ለባሕራንም ለመንገዱ የሚሆነውን ስንቅ ሰጠው፡፡
የራሱን የሞት ደብዳቤ እንደያዘ ሳያውቅ ባሕራን ወደ ታዘዘበት ሥፍራ ተጓዘ፤ ከዚያ ሰው ቤት ለመድረስ ሲቀርብ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል በንጉሥ ጭፍራ አምሳል በነጭ ፈረስ ላይ ተቀምጦ ‹‹አንተ ጐልማሳ የያዝኸው ምንድነው›› አለው፡፡ ‹‹ወደ ዕገሌ ሀገር ወደ ቤቱ ለማድረስ ከአንድ ባለ ጠጋ የተጻፈች መልእክት ናት›› አለው፡፡ ‹‹ያቺን ደብዳቤ አሳየኝ›› አለው፤ እርሱም ስለ ፈራ ሰጠው፡፡ የሞቱን ደብዳቤ ያቺን የሞት መልእክት ደምስሶ በሕይወት ቀየረለት። በእርሱም ፈንታ በንፍሐት ለውጦ እንዲህ ብሎ ጻፈ፤ ‹‹ይቺን ደብዳቤ ይዞ ለመጣ ባሕራን ለሚባል ሰው ይቺ ደብዳቤ ደርሳ በምትነበብበት ጊዜ ልጄ ዕገሊትን አጋቡት፡፡ በውስጥና በውጭ ያለ ንብረቴንና ጥሪቴን፣ ወንዶችና ሴቶች ባሮቼን፣ ጠቅላላ ንብረቴንም አውርሼዋለሁና የፈለገውንም ሊያደርግ ሥልጣን ሰጥቼዋለሁና እኔን አትጠብቁኝ፡፡ እኔ ብዙ እዘገያለሁ የኔ ሹም እገሌ ሆይ! በእኔና በአንተ መካከል ይቺ ምልክት እነኋት፡፡››
አሽጐ ለባሕራን ሰጠውና ‹‹ወደ ባለ ጠጋው ቤት ሂደህ ይቺን ደብዳቤ ለሹሙ ስጠው፡፡ በጎዳናም እኔ እንደ ተገናኘሁህ አትንገረው፡፡ እንዳይገድልህም ይህን የሞት ደብዳቤ ለውጬልሃለሁ›› አለው፡፡ ባሕራንም ‹‹እሺ ጌታዬ ያዘዝኸኝን ሁሉ አደርጋለሁ›› አለ፡፡
ባሕራንም ወደ ባለ ጠጋው ቤት በደረሰ ጊዜ ያቺን ደብዳቤ ለሹሙ ሰጠው፡፡ ካነበባት በኋላም በመካከላቸው ያለውን ምልክት አገኘ፡፡ አስተውሎም እርግጠኛ እንደ ሆነ ዐወቀ፡፡ ለባሕራን ሰርግ አዘጋጅቶ እንደሚገባ በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በተክሊል የባለ ጠጋውን ልጅ አጋቡት፡፡ ዓርባ ቀን ያህልም ደስታና ሐሴት እያደረጉ ኖሩ፡፡ ሀብቱንም ሁሉ አወረሱት።
ከዚህ በኋላ ባለ ጠጋው ከሄደበት በተመለሰ ጊዜ በደስታ የሆነውን የመሰንቆና የእንዚራ ድምፅ ሰምቶ ‹‹ይህ የምሰማው ምንድነው›› ብሎ ጠየቀ፡፡ እነርሱም ‹‹ስሙ ባሕራን ለተባለ የአንተን ደብዳቤ ላመጣ ጐልማሳ ሰው ልጅህ ዕገሊትን አጋቡት፡፡ እነሆ ዓርባ ቀናት በሰርግ ላይ ነው፡፡ ገንዘብህንና ጥሪትህን ሁሉ ወንዶችና ሴቶች ባሮችህን አንተ እንዳዘዝህ ሰጥተውታል›› አሉት፡፡ ይህንም በሰማ ጊዜ ደንግጦ ከፈረሱ ላይ ወደቀ በድንገትም ሞተ፡፡
ባሕራንም ከዚህ በኋላ የቅዱስ ሚካኤልን ዝክር በሚገባ እየዘከረና ለቤተ ክርስቲያኑም እየታዘዘ የሚያገለግል ሆነ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዓሉን በሚገባ አክብረን በረከት እንድንቀበል ይርዳን፤ የቅዱስ ሚካኤል የረድኤቱ ኀይል በሀገራችን በሃይማኖታቸው ምክንያት ከተሠውት የክርስቲያን ወገኖች ጋር ይሁን፤ለዘለዓለሙ አሜን፡፡
ምንጭ፡– ድርሳነ ቅዱስ ሚካኤል፣ ስንክሳር ዘወርኃ ሰኔ
በዓለ ደብረ ምጥማቅ
የክርስቲያን ወገን ሁሉ አምላክን የወለደች እመቤታችንም ቅድስት ድንግል ማርያም በደብረ ምጥማቅ በስሟ በተሠራች ቤተ ክርስቲያን ጉልላት ላይ በብርሃን መርከብ ተቀምጣ ፊቷ በግልጥ ስለመታየቱ ታላቅ በዓልን ያደርጋሉ፡፡
እመቤታችንም ቅድስት ድንግል ማርያም ብርሃን ተጎናጽፋ በተገለጠችበት ጊዜ በዙሪያዋ የመላእክት ሠራዊት የመላእክት አለቆችም በየማዕረጋቸው ክንፋቸውን ዘርግተው ይቆሙ ነበር፤ ይጋርዷታልም፡፡ ሱራፌል ማዕጠንታቸውን ይዘው ለንግሥትዋ ገናናነት ሰገዱ፤ በየስግደታቸውም እንዲህ እያሉም አመሰገኗት፤ ‹‹አብ በሰማይ ሁኖ ተመለከተ፤ እንዳንቺ ያለ አላገኘም፤ አንድ ልጁንም ልኮ ከአንቺ ሰው ሆነ፡፡›› (መጽሐፈ ስንክሳር ግንቦት ፳፩ ገጽ. ፫፻፲፰)
ሰማዕታትም በየማዕረጋቸው ረቂቃን በሆኑ ፈረሶቻቸው ተቀምጠው ወደ እርሷ ቀርቡ፤ በመጀመሪያ ሊቀ ሰማዕታት ቅዱስ ጊዮርጊስ ከአምባላይ ፈረሱ ወርዶ ሰገደላት፡፡ እንዲሁም ባልንጀሮቹ ሰማዕታት መጥተው ሰገዱላት፤ ለእርሱ በኋላ የመጣው በዱሪ ፈረስ የተቀመጠው ቅዱስ መርቆሬዎዮስ ነው፡፡
ከዚህም በኋላ ሰማዕታት ሁሉ በመከታተል መጥተው ሰገዱላት፤ ምስጋናም አቀረቡላት፤ ጻድቃን በአንድነት መጥተው በፊቷ ሰግደው ተመለሱ፤ ቀጥሎም ሄሮድስ የገደላቸው ሕፃናት መጥተውም ሰገዱ፤ በፊቷም እየዘለሉ አንዱ በአንዱ ላይ እየዘለለ በመተቃቀፍ ተደሰቱ፡፡
በዚያ የተሰበሰቡትም በአዩ ጊዜ ደስታ ሞልቶባቸው በሰማይም ያሉ ይመስላቸው ነበር፡፡ እናትና አባቱም የሞቱበት ቢኖር ወይም ዘመዶቹ ወይም ባልንጀራው ‹‹ቅድስት ድንግል እመቤቴ ሆይ እገሌን አሳይኝ›› ብሎ በሚለምናት ጊዜ ቀድሞ በነበረበት መልኩ ያን ጊዜ ታመጣዋለች፡፡ ደግሞ መሀረባቸውን ወደ ላይ ይወረውሩላታል፤ የወደደችውንም በእጅዋ ተቀብላ መልሳ ትጥልላቸዋለች፤ ለበረከትም በየጥቂቱ ይካፈሉታል፡፡ እንዲህም አምስት ቀን ሁሉ ክርስቲያንም፣ እስላሞችም፣ አረማውያንም ያይዋታል፡፡ ወደ ቤታቸውም ለመሄድ ሲሹ በፊቷ ሰግደው ይሰናበቷታል፤ እርሷም ትባርካቸዋልና ይመለሳሉ፡፡
የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነትና ተራዳኢነት ከእኛ ጋር ይሁን፤አሜን!
ከመጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ ግንቦት
“እግዚአብሔር በመለከት ድምፅ ዐረገ።” (መዝ ፵፮ ፥፭)
ዕርገተ ክርስቶስ (The Ascension of Jesus Christ)
በቀሲስ ኃይሉ ብርሃኑ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ትልቅ ቦታ ካላቸው 9 ዐበይት የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓላት መካከል አንዱ ነው።
“ዕርገት” የሚለው ቃል “ዐርገ” ከሚለው የግእዝ ግስ የወጣ ሲሆን ትርጉሙም ከታች ወደ ላይ መውጣት፣ ከፍ ከፍ ማለት፣ ማረግ ማለት ነው፡፡ ዕርገት (Ascension) ሲባልም ማረግን፣ ወደ ላይ መውጣትን ያመለክታል፡፡ በዓለ ዕርገትም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም የነበረውን የማዳኑን ሥራ ጨርሶ ወደ ላይ መውጣቱና በቀደመ ክብሩ በአብ ቀኝ መቀመጡ የሚከበርበት በዓል ነው፡፡ ለዚህም መሠረት እንዲሆን አርዮስን ለማውገዝ በኒቅያ የተሰበሰቡት ቅዱሳን አበው “ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት ወነበረ በየማነ አቡሁ…/ በክብር ወደ ሰማይ ዐረገ፤ በአባቱም ቀኝ ተቀመጠ…” ብለው ዕርገቱን በቅዱሳት መጻሕፍት ዋቢነት አስረግጠው ደንግገዋል፡፡
የክርስቶስ ጥንተ ዕርገቱ ግንቦት 8 ሐሙስ ቀን በ34 ዓ.ም በዘመነ ማርቆስ ነው፡፡ የዕርገት በዓል አከባበር እስከ 4ኛው ክፍለ ዘመን ድረስ እንደዛሬው ሐሙስን ሳይጠብቅ በጥንተ ዕርገቱ ግንቦት 8 ቀን ብቻ ይከበር ነበር፡፡ በኋላ ግን ትንሣኤ በዋለ በ40ኛው ቀን ብቻ እንዲከበር ቅዱስ ዲሜጥሮስ በባሕረ ሐሳብ ቀመር ስሌት መሠረት ይከናወን ዘንድ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ተወስኖ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም እየተገለገለችበት ይገኛል።
ጌታችን ከተነሣ በኋላ ሐዋርያትን እያስተማረ ስለሚልክላቸው አጽናኝ መንፈስ ቅዱስ ፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት አስፈላጊውን ነገር እያስተካከለ አዕማደ ቤተ ክርስቲያንን በማቆም የሐዲስ ኪዳን ሕግና ሥርዓትን በማጽናት በቀደመው ኪዳን አምሳል ዐርባ ቀን ቆይቷል።
ያስተማራቸው ትምህርትም “ ኪዳን “ይባላል። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለዕርገቱ የመረጠው ቦታ በዓለም ሳለ ዘወትር ይጎበኘው የነበረውን ቦታ ነው። የእግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ከቤተ መቅደስ በመለየት የተመረጠችውን ከተማ እንደተወ ከኢየሩሳሌም በስተምሥራቅ በሚገኘው የደብረ ዘይት ተራራ ላይ ዐረፈ:: ክርስቶስም በተራራዋ ላይ ሆኖ ከተማዋን በርኅራኄ ዐይን ተመለከታት፤ በዚህም ተራራ ላይ የነበሩ ደኖችና ሽለቆዎች በክርስቶስ ተቀድሰዋል:: በዚህ ተራራ ጥግ ላይ በምትገኘው በቢታንያ ከተማ ነዋሪ በሆኑት በእነ አልዓዛር ቤት ብዙ ጊዜ ዐርፎ ነበር። በተራራው ግርጌ በምትገኘው የጌቴሴማኒ የአትክልት ቦታ ውስጥም በብዙ ዕንባና ጩኸት ጸልዮአል:: የአይሁድ አለቆች ለመስቀል ሞት አሳልፈው ሊሰጡት በክፉ አገዳደልም ሊገደሉት ጌታን የያዙት በዚህ ስፍራ ነበር። በዚህ ዕለት ጌታ ተማሪዎቹን እየመራ ወደ ቢታንያ ወሰዳቸው፤ ደቀ መዛሙርቱ ከጌታቸው ጋር የሚገናኙበት ቀን ይህ ብቻ መሆኑን አላወቁም ነበር። ቅዱስ ሉቃስ በወንጌሉ እንዲህ ዘግቦልናል። “ እስከ ቢታንያም አወጣቸው እጁንም አንሥቶ ባረካቸው ።ሲባርካቸውም ከእነርሱ ተለየ ወደ ሰማያ ዐረገ” (ሉቃ ፳፬፥፶)
ቢታንያ ሲደርስ መሄዱን ትቶ ቆመ፤ ደቀ መዛሙርቱም ከበውት ቆሙ ጌታም በፍቅር ዐይን አያቸው።
እጆቹንም አንሥቶ ከባረካቸው በኋላ ከመካከላቸው ተነሥቶ ወደ ሰማይ ዐረገ፤ ደቀ መዛሙርቱም ጌታቸውን ከዐይናቸው እስኪሰወርና ዐይኖቻቸው እስኪፈዙ ድረስ በአድናቆትና በፍቅር ወደ ላይ ተመለከቱ፤ ወዲያውኑ የክብር ደመና ከዐይናቸው ሰወረው የርቀት ያይደለ የርሕቀት ነው፤ ይህ ማለት መርቀቅ ሳይሆን መራቅ ነው። ለምሳሌ አውሮፕላን ከምድር ሲነሣ ቀስ እያለ ወደ ሰማይ በወጣ ጊዜ አካሉ እያነሰ እያነሰ ይሄዳል በመጨረሻም ወፍ እስኪመስለን ድረስ ለዐይናችን ይርቃል፣ አምላካችንም ልክ እንደዚያ የሐዋርያት ዐይን ማየት እስከቻለበት መጠን ድረስ ከፍ ከፍ እያለ ወደ ሰማይ ዐርጓል:: መላእክትም የደመና ሰረገላም መስለው በተቀበሉት ጊዜ ቀደ መዛሙርቱ ጥዑም የሆነውን የመላእክትን ዝማሬ ሰምተዋል:: መላእክትም ትኩር ብለው የጌታን ዕርገት ለሚመለከቱ ሐዋርያት ‹‹እናንተ የገሊላ ሰዎች ወደ ሰማይ ሲወጣ ያያችሁት ተመልሶ ይመጣል›› የሚል ተስፋ አበሠሩአቸው:: ደቀ መዛሙርቱም ‹‹እነሆ እኔ እስከ ዓለም መጨረሻ ድረስ ሁል ጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ, ሲል የሰጣቸውን ተስፋ እያስታወሱ ከቢታንያ ተመለሱ::
ሊቁ እንዲህ አለ “እንዘ ይመስሕ ምስሌሆሙ በዓርብዐ ዕለት ነገሮሙ ወይቤሎሙ ሰላም ለክሙ አዓርግ ሰማየ ኀበ አቡየ ወአቡክሙ ወዘንተ ብሂሎ መሠጦ ደመና ወሠወሮ እምአዕይንቲሆሙ:: ሲመሽ በዐርባኛው ቀን ከእነርሱ ጋር አምሽቶ ነገራቸው እንዲህም አላቸው ሰላም ለእናንተ ይሁን ወደ ሰማይ ወደ አባቴ ወደ አባታችሁ ዐርጋለሁ፤ ይህን ብሎ ደመና ነጥቆ ከዐይኖቻቸው ሠወረው›› በማለት ጌታችን ደመና በተባለች በባሕርይ ክብሩ መቀመጡን ሊቁ መስክሯል:: ክርስቶስ ሲያርግ ያዩት ተማሪዎች ልባቸው አብሮ አርጓል:: ወደ ላይም መንፈሳቸው ተነጥቋል፤ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ሀገራቸው በሰማይ ሆኗል፤ በምድር ላይ ሰማያዊ ኑሮን መኖር ጀምረዋል።
መላእክትም ያን ያህል ያደነቁትና እልል ያሉበት ምክንያት፣ ቀድሞ በምድር ዝቅ ብሎ የነበረው የሰው ሥጋ ዛሬ በመለኮት ክብር ወደ ሰማያት ሲያርግ በመመልከታቸው ነው።
ነቢዩ ቅዱስ ዳዊትም በመዝሙር ፳፫ ፥፯-፰ — “አርኅው ኆኃተ መኳንንት ወይትረኃዋ ኆኃት እለ እም ፍጥረት ወይባእ ንጉሠ ስብሐት” መኳንንት ቅዳሴ መላእክት ኆኃተ ቅዳሴን ክፈቱ ከጥንት ጀምሮ ተከፍተው የማያውቁ ኆኃተ ቅዳሴ ይከፈቱ የክብር ባለቤት ጌታ በየማነ አብ (በአብ ቀኝ) በዘባነ ኪሩብ (በኪሩቤል ጀርባ) ይቀመጥ። በማለት ማር ያዕቆብ ዘሥሩግ መላእክት “ይህ ሥጋ ማን ነው?” ብለው እንደጠየቁ የገለጠውን ቅኔ፣ ይህ ጥቅስ በቀጥታ ያጸናዋል። ሰማያውያን መላእክት የክርስቶስን የሥጋ ዕርገት ሲያዩ በበሮቹ ላይ ያደረጉትን ድንጋጌና መደነቅ ያሳያል።
ቅዱስ ጳውሎስም በ፩ኛ ጢሞቴዎስ ፫፥፲፮ “በሥጋ የተገለጠ፥ በመንፈስ የጸደቀ፥ ለመላእክት የታየ፥ በአሕዛብ የተሰበከ፥ በዓለም የታመነ፥ በክብር ያረገ”በማለት ይገልጻል።
“ለመላእክት የታየ” የሚለው ቃል መላእክት በዕርገቱ ጊዜ አዲሱንና የከበረውን የሰው ልጅ ተፈጥሮ (ሥጋን) አይተው ማድነቃቸውን ያመለክታል።
ቅዱስ ዮሐንስም ይህን ሲያረጋግጥ በዮሐ ፫፥፲፫ — “ከሰማይም ከወረደው በቀር ወደ ሰማይ የወጣ ማንም የለም፥ እርሱም በሰማይ የሚኖረው የሰው ልጅ ነው”ብሏል።
ክርስቶስ ሥጋን ተዋሕዶ ወደ ምድር መውረዱንና ያንኑ ሥጋ ይዞ ሁሉን ይሞላ ዘንድ መዓርጉን ሳያናውጽ ማረጉን ቅዱስ ጳውሎስ በኤፌሶን መልእክቱ በ ፬፥፱-፲ — “ይህም፦ ዐረገ ማለት ከምድር በታች ወደ አሉት ክፍሎች ደግሞ ወረደ ማለት ካልሆነ ምን ማለት ነው? ይህ የወረደው ሁሉን ይሞላ ዘንድ ከሰማያት ሁሉ በላይ የወጣው ያው እርሱ ነው” በማለት ገልጧል።
በአጠቃላይ የክርስቶስን ዕርገት በአራት ዋና ዋና ክፍሎች ማየት ይቻላል።
ሀ) መጽሐፍ ቅዱሳዊ ታሪኩ
ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ (ከትንሣኤ ጀምሮ) ለ40 ቀናት ያህል ለደቀ መዛሙርቱ እየተገለጠ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት አስተምሯቸዋል (ሐዋ. 1፥3)።
ቦታው፦ በ40ኛው ቀን ሐዋርያትን ይዟቸው ወደ ደብረ ዘይት (የወይራ ዘይት ተራራ) ወጣ።
ክስተቱ፦ እየባረካቸው ሳለ ወደ ሰማይ ከፍ ከፍ አለ፤ ደመናም ከዓይናቸው ሰውረችው።
* የመላእክት ብሥራት፦ ሐዋርያት ወደ ሰማይ ትኩር ብለው ሲመለከቱ ሳለ፥ ነጭ ልብስ የለበሱ ሁለት መላእክት ተገልጠው፦ “ይህ ከእግዚአብሔር ወደ ሰማይ የወጣው ኢየሱስ ወደ ሰማይ ሲወጣ እንዳያችሁት እንዲሁ ይመጣል” ብለው የዳግም ምጽአቱን ነገር አረጋገጡላቸው (ሐዋ. 1፥11)።
ለ) ነገረ መለኮታዊ ትርጓሜው (Theological Meaning)
ዕርገት ዝም ብሎ የአንድ ስፍራ መቀየር ሳይሆን የሰው ልጅ ተፈጥሮ ትልቅ ክብር ያገኘበት ምሥጢር ነው።
የሰው ሥጋ ወደ ሰማይ መግባቱ፦
ክርስቶስ ወደ ሰማይ ያረገው በመለኮቱ ብቻሳይሆን በተዋሐደው ሥጋ ነው።
ይህም ለፈራሽና በስባሽ ለነበረ የሰው ልጅ ተፈጥሮ ዘላለማዊ የሰማይ ክብርን ሰጥቷል።
በአብ ቀኝ መቀመጥ፦ “በአብ ቀኝ ተቀመጠ” ማለት ክርስቶስ በሥጋውም ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እኩል ሥልጣን፣ ክብርና ጌትነት እንዳለው ያሳያል።
የመንፈስ ቅዱስ መውረድ ቅድመ–ሁኔታ፦ ክርስቶስ በዮሐንስ ወንጌል 16፥7 ላይ “እኔ ባልሄድ አጽናኙ ወደ እናንተ አይመጣምና፤ እኔ ብሄድ ግን እርሱን እልክላችኋለሁ” እንዳለ፣ ዕርገቱ ለጰራቅሊጦስ (ለመንፈስ ቅዱስ) መውረድ መንገድ የከፈተ ነው።
የቤተክርስቲያን ሊቅ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በድርሳኑ (በተለይም በመዝሙረ ዳዊት ትርጓሜውና በሃይማኖተ አበው ላይ በሰፈረው ትምህርቱ) ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዕርገት የክርስቶስ ዕርገት በገዛ አምላካዊ ሥልጣኑና ኃይሉ የተፈጸመ ፍጹም ልዩ ዕርገት መሆኑን በስፋት ያስተምራል።
የዕርገትን በዓል ታላቅነትና ረቂቅ ምሥጢር ሲያብራራም የሚከተሉትን ዋና ዋና ነጥቦች ያነሳል፡
፩. በገዛ ሥልጣኑ ማረጉ (ከሌሎች ዕርገት መለየቱ)
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የጌታችንን ዕርገት ከነቢያት (ከነቢዩ ኤልያስና ከሄኖክ) ዕርገት ጋር በማነጻጸር የክርስቶስን አምላክነት ያስረዳባቸዋል፦
የኤልያስ ዕርገት፦ ነቢዩ ኤልያስ ወደ ሰማይ የወጣው በመላእክት ረዳትነትና በእሳት ሰረገላ ተጭኖ፣ ወደታዘዘበት ቦታ ተወስዶ ነው።
የጌታችን ዕርገት፦ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን የመላእክት ፈጣሪ በመሆኑ፣ የማንም ርዳታ ወይም መሪ ሳይፈልግ በገዛ አምላካዊ ሥልጣኑ አርጓል።
መዝሙረኛው ዳዊት “እግዚአብሔር በእልልታ ዐረገ” አለ እንጂ “መላእክት አሳረጉት” አላለም በማለት ይተረጉማል። ወንጌላዊው ሉቃስም “ወደ ሰማይ ሲያርግ አዩ” አለ እንጂ “ተሸከሙት” አላለም፤ ምክንያቱም ያረገበት ሰማይ የገዛ ርስቱና ማደሪያው ነው።
፪. በተዋሐደው ሥጋ ማረጉ
ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ
ክርስቶስ ወደ ሰማይ የወጣው ከእኛ በነሣው (በተዋሐደው) እውነተኛ ሥጋ መሆኑን ያረጋግጣል።
ከስቅለቱና ከትንሣኤው አስቀድሞ ግዙፍ ሥጋን እንደ ተዋሕደ በባሕር ላይ በተአምራት እንደተራመደ ሁሉ፣ ዛሬም ነፋሳትን ከፍሎ በተዋሐደው ሥጋ ወደ ሰማይ ሲያርግ ማንም ሊጠራጠር አይገባውም ይላል።
በዕርገቱ ጊዜ የክርስቶስ ሥጋ አልተለወጠም (መለኮት ሥጋን አልተወውም)፤ በዚያው በተዋሕደው ሥጋ ከፍ ከፍ አለ።
ሐ) ለሰው ልጅ የተሰጠ ታላቅ ክብር
በዚህ ድርሳን ላይ እንደተብራራው፣ የክርስቶስ ዕርገት ለሰው ልጅ የዘላለም ተስፋና ክብርን ያጎናጸፈ ነው፦
ቀድሞ በኃጢአት ምክንያት ከገነት ተባሮ የነበረው የሰው ልጅ ተፈጥሮ (ሥጋ)፣ በክርስቶስ ዕርገት አማካኝነት ከሰማያት በላይ ከፍ ብሎ አርጓል።
የሰው ባሕርይ ከጎሰቆለበት ተነሥቶ ከመላእክትና ከኃይላት ሁሉ በላይ የክብር ባለቤት ሆኗል።
መ) በዕርገቱ ሰይጣን ድል ተነሣ
በዕለተ ዕርገት መላእክት ሁሉ ሲዘምሩ፣ አንዳንዶቹ ከፊቱ ሲቀድሙና ከበውት ሲያርጉ፣ ሰይጣን ሙሉ በሙሉ ድል ስለተሣ ለምእመናን የደስታና የሐሴት ምንጭ ሆነ።
- ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለምን ዐረገ?
ዕርገቱ ከምድር መለየት ብቻ ሳይሆን የተከናወኑበት ዋና ዋና ምክንያቶች የሚከተሉት ናቸው፡
፩.የመዳን ሥራ ለማጠናቀቅ: ምሥጢረ ሥጋዌን (ሰው መሆኑን) እና የቤዛነት ሥራውን ፈጽሞ ወደ ቀደመ ክብሩ፣ ወደ አባቱ ቀኝ ለመቀመጥ።
፪.መንፈስ ቅዱስን ለመላክ: ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን እንደማይተዋቸው ተስፋ የሰጠ ሲሆን፣ እርሱ ካላረገ በስተቀር አጽናኙ መንፈስ ቅዱስ ወደ ምድር አይመጣም ነበርና።
፫.ትንቢትን ለመፈጸም: «አምላክ በእልልታ፥ እግዚአብሔር በመለከት ድምፅ ዐረገ» ተብሎ በመዝሙረ ዳዊት (መዝ. ፵፮፥፭) የተነገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ነው。
፬.ቦታን ለማዘጋጀት: ምእመናን ከእርሱ ጋር ለሚኖሩበት ክብርና መንግሥት ስፍራን ለማዘጋጀት (ዮሐ. ፲፬፥፪) ዐረገ።
- ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዕርገቱን ለምን በተነሣ በ40ኛው ቀን አደረገ?
፩. አዳም በ40ኛ ቀን አግኝቶ ያጣትን ልጅነት እንደተመለሰለት ለማጠየቅ።
፪. አንድም ጌታ በረቀቀ ጥበቡ ተሸብሮ የነበረውን የሐዋርያትን ልቡና እያረጋጋና እያጽናና ለመቆየት።
፫. አንድም ለአይሁድ ምክንያት ለማሳጣት ነው፡፡ ዕርገቱን ከትንሣኤ አስከትሎ ወዲያው ቢያደርገው ዕርገቱን ምትሐት ናት እንዳይሉ በእርግጥ በሞቱ ሞትን ድል አድረጎ የተነሣው ወልደ እግዚአብሔር መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እርሱ መሆኑን እንዲረዱ እንዲገነዘቡ የጥርጣሬ መንፈስ በአእምሯቸው እንዳይሰርጽ ።
፬. አንድም ላላመኑት ለእስራኤላውያን (ለአይሁድ) የንስሐ ጊዜ ሲሰጣቸው ነው፡፡ ብዙዎች በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት አምነው የተመለሱ አሉና፡፡
ስለዚህ እኛም ዕርገቱን መሠረተ ሃይማኖታችን በሆነው ጸሎተ ሃይማኖት ”በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ በአባቱም ቀኝ ተቀመጠ” ብለን ዘወትር እንጸልያለን፤ እንመሰክራለን።
ከሊቁ ከአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ጋር “አሁንም ከኛ ጋር በዓልን እንዲያደርጉ አባቶችን እንጥራቸው። ከሁሉ በፊት አዳምን እንጥራው፤ እነሆ እግዚአብሔር ከገነት በወጣህ ጊዜ ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ ያለው ተፈጸመ፤ እግዚአብሔር ሥጋን ከሴት ልጅህ ለበሰ፤ በአባቱም ቀኝ በሰማያት ተቀመጠ፤ ይህን የወደድኸውን አምላክነት ከሴት ልጅህ በተወለደ በመለኮት ሰው መሆን አገኘኸው እንበለው። የሕያዋን እናታቸው ስለሆንሽ ሕይወት የተባልሽ ሔዋን ሆይ በሴትልጅሽ ደስ ትሰኚ ዘንድ ነዪ፤ ሕይወትን አምጥተሻልና፤ በታተመ አፈ ማኅፀኗ የወለደችው እርሱ በረከትን ካገኙ ደቀ መዛሙርቱ ጋር ቆማ እያየችው ወደ ሰማያዊው አባቱ ዐረገ” (መጽሐፈ ምሥ. ፳፰፥፲፬) እያልን እናክብር እናመስግን;
ከበዓለ ዕርገቱ ረድኤት በረከት ያሳትፈን!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።
“ዮም ፍሥሐ ኮነ በእንተ ልደታ ለማርያም፤ በማርያም ልደት ምክንያት ዛሬ ደስታ ሆነ!” (ድጓ ዘቅዱስ ያሬድ)
በመምህር ብንያም
“አነ ጽጌ ገዳም ጽጌ ደንጎላት ዘውስተ ቄላት ወከመ ጽጌ ደንጎላት በማእከለ አስዋክ-እኔ የምድረ በዳ አበባ ነኝ በቆላ ውስጥ ያለ በሾህ መካከል የበቀለ የሱፍ አበባ ነኝ።” (መኃ.፪፥፩) ብሎ ነቢዩ ሰሎሞን እንደተናገረ ግንቦት አንድ ቀን በምድረ በዳ በአድባረ ሊባኖስ የበቀለችውን አማናዊት ንጽሕት የሱፍ ፣ የጽጌረዳ አበባ የሆነችውን በመዓዛዋ ጣዕም የዓለምን የኀጢአትን ሽታ ያስወገደችውን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ልደት እናከብራለን፡፡
ጠቢቡ ሰሎሞን አስቀድሞ በመንፈሰ እግዚአብሔር ተቃኝቶ በመዝሙሩ ፮፥፲ ላይ “መኑ ይእቲ ዛቲ እንተ ትሔውጽ ከመ ጎሕ ሠናይት ከመ ወርኅ ወብርህት ከመ ፀሐይ” (ይህቺ እንደ ማለዳ ብርሃን የምትጐበኝ፣ እንደ ጨረቃ የተዋበች፤ እንደ ፀሐይም የጠራች፣ ዓላማ ይዞ እንደተሰለፈ ሠራዊት የምታስፈራ ማን ናት?) በማለት እንደ ፀሐይ የሞቀ፣ እንደ ጨረቃ የደመቀ፣ ንጽሕናዋና ቅድስናዋ የመልኳ ደም ግባት በነቢያት ትንቢት አስቀድሞ የተጐበኘላት የእውነት ፀሐይ የክርስቶስ እናት የቅድስት ድንግል ማርያምን ክብርና ደም ግባቷን እንደተናገረ፤ በሊባኖስ ተራራ በግንቦት ፩ በተወለደች ጊዜ ፊቷ በእጅጉ ያበራ ነበር፤ መዓዛዋም ከሽቱ ሁሉ ይበልጥ ነበር፡፡ የእመቤታችን ዜና ልደት እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውኃ ፈሳሽ አይደለም ፡፡በብዙ ሕብረ አምሳል እና ትንቢት ሲነገርላት የመጣች ምልዕተ ምሥጢር ናት እንጂ፡፡
ይኸውም ልደቷ በሦስት ክፍል ተነግሮላታል ፡፡
ሀ. በልበ ሥላሴ
“እግዝእትነ ማርያም ነበረት እምቅድመ ዓለም በኅሊና አምላክ-እመቤታችን ዓለም ሳይፈጠር አስቀድማ በአምላከ ኅሊና ታስባ ትኖር ነበር” ተብሎ ተነግሮላታል። እግዚአብሔር ይህን ዓለም ሳይፈጥረው ግብሩን ያውቀው ነበር እና የሚድንበትንም ከፍጥረት አስቀድሞ በኅሊናው ያውቅ ነበር። እንዲህ ሲባል ግን ማወቅ እና ማሠራት ይለያያል። አወቀው ማለት አዳምን ክፉ አሠራው ማለት ግን አይደለም፡፡ ስንኳን እመቤታችንን ስለእኛ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲናገር፦ “ዓለም ሳይፈጠር አስቀድሞ መረጠን።” (ኤፌ.፩፥፬) ብሎ ተናግሯል፡፡ “እስመ እግዚእ ኀረያ-ጌታ መርጧታልና” እንድትመረጥ ሁና ብትገኝ ተመረጠች ብሎ ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬምም ተናግሮላታል፡፡
ለ.በሥነ ፍጥረት ተነግሮታል፦ እመቤታችን በበርካታ ሥነ ፍጥረት ምሳሌ ተመስላለች።
ከረቂቁ እስከ ግዙፉ ዓለም ድረስ ፡፡
ግብር እምግብር (ከተፈጠረ ነገር የተገኙ) ከተፈጠሩ ፍጥረታት በሰዓት እስከ ሚቆጠሩ ዕለታት ድረስ ፡፡
ከባሕር እስከ የብስ፣ ከየብስ እስከ ባሕር ድረስ፡፡
ከዓለመ መላእክት እስከ ዓለመ ሰብእ ድረስ፡፡
ለዚህ ነው ሊቁ አባ ሕርያቆስ፦
“በመኑ በአምሳለ መኑ ናስተማስለኪ-በምን እና በምን እንመስልሻለን?” በማለት የተናገረው።
ሐ.በሕገ ልቡና እና በሕገ መጻሕፍት ተነግሮላታል።
ይህም በብዙ ኅብረ አምሳል እና በብዙ ኅብረ ትንቢት የተነገረው ነው።
ኅብረ ትንቢት እንደሚከተለው ነው፦
“በአንተና በሴቲቱ በዘርህ እና በዘሯ መካከል ጠላትነትን አደርጋለው።” (ዘፍ.፫፥፲፭)
“ቀስቴን በደመና አደርጋለሁ” (ዘፍ.፱፥፲፫)
“እግዚአብሔርም በሴም ድንኳን ይደር።” (ዘፍ.፱፥፳፯)
“በድንግልና ፀንሳ በድንግልና ትወልዳለች።” (ኢሳ.፯፥፲፬)
“ከእሴይ በትር ትወጣለች” …(ኢሳ.፲፩፥፩) ወዘተ በማለት ትንቢት ተናግረዋል።
በተለይም በጠቢቡ ሰሎሞን “ሙሽራዬ ሆይ ከሊባኖስዩ” (መኃ ፬፥፰ ) ብሎ በአድባረ ሊባኖስ እንደምትወልድ በሚደንቅ ትንቢት ተናግሯል።
በብዙ ኅብረ አምሳል ደግሞ እንደሚከተለው ሲሆን በአምሳለ ሰዋስው (መሰላል) ለያዕቆብ (ዘፍ.፳፯፥፲፯)…በአምሳለ ሐመልማል ለሙሴ (ዘጸ .፫፥፫)
“በአምሳለ መሶበ ወርቅ፤ በአምሳለ ተቅዋመ ወርቅ፤ በአምሳለ ማዕጠንተ ወርቅ፤በአምሳለ ታቦት”ለሙሴ፡፡
በጠቅላለው በኦሪት ውስጥ የተመሰሉ ምሳሌዎች ለእመቤታችን አምሳል ናቸው፡፡
በዘመነ መሳፍንት እና በዘመነ ነገሥትም በብዙ ተመስላለች።
“በአምሳለ ጸምር ለጌዴወን” (መሳ.፮፴፭)
“በአምሳለ መሶብ ለኤልያስ” (፩.ነገ.፲፱፥፮)
“በአምሳለ ንግሥት ለዳዊት”(መዝ.፵፬፥፱)
“በአምሳለ መርዓት ‹ሙሽራ›ለሰሎሞን (መኃ፬፥፰)
“በአምሳለ ፈጣን ደመና ለኢሳይያስ” (ኢሳ.፲፱፥፩) ወዘተ በመሳሰሉ ምሳሌያት እየተመሰለች እየተነገረች ዘመነ አበውን በምሥጢር እያለፈች አበውን በተስፋ እያጽናናች የመጣች እርሷ ናት፡፡
“ይእቲኬ መድኃኒት እንተ ኀሠሥዋ ወዖድዋ ነቢያት-ነቢያት የሿት እና የፈለጓት መድኃኒት ይህች ናት።” (፩.ጴጥ.፩፥፲) ብሎ ቅዱስ ጴጥሮስ እንደነገረን፡፡ ራሱ ባለቤቱ እግዚአብሔር ለአባታችን ለአዳም የሰጠው ዘለዓለማዊ ተስፋ የሚፈጸመው በእርሷ በኩል ነው።”ተስፋ ሕይወት ተሠርዐ-የሕይወት ተስፋ ተሠራልን።” ቅዱስ ያሬድ የሕይወት ተስፋም በድንግል ማርያም ተፈጽሟል።
“ተፈጸመ ተስፋ አበው በማርያም ድንግል-የአበው ተስፋ በድንግል ማርያም ተፈጸመ።”እንዲል ደራሲው ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴ ማርያም. ስለሆነም ቀን ሲደርስ አንባ ይፈርስ እንዲሉ፦
አማናዊ ቃል ኪዳን ሊጻፍባት አማናዊት ብራና ፤
አማናዊ ካህን ሊያገለግልባት አማናዊት መቅደስ፤
አማናዊ ፀሐየ-ጽድቅ ክርስቶስ ለሚወጣባት አማናዊት ሰማይ፤
አማናዊ ስንዴ ሊበቅልባት አማናዊት ምድር።
ግንቦት አንድ ቀን ከቅድስት ሐናና ከቅዱስ ኢያቄም በፈቃደ እግዚአብሔር በብሥራተ መልአክ በሊባኖስ ተራራ ተወለደች፡፡ ባሕርየ ሰብእን የፈጠረ ባሕርይዋን ሊዋሐድ ንጽሕት እናቱን ፈጠረ ፡፡ ፅንሰቷ በዘር በሩካቤ ቢሆንም ባሕርይዋ ሳያድፍ ጥንተ በደል ሳይደርስባት ተወለደች፡፡”እምጽቡር ጽሩየ ገብራ-ንጽሕት አድርጎ ሠራት።” “ከፈጠራት ጀምሮ በምንም በምን ከድንግልናዋ አልተለወጠችም።” (ሃይ.፶፫፥፳፪) ብሎ ሊቁ ቅዱስ ቴዎዶጦስ እንደተናገረ ፡፡አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም፦”ዐቀባ መንፈስ ቅዱስ እምከርሠ እማ-መንፈስ ቅዱስ ከእናቷ ማሕፀን ጀምሮ ጠበቃት።” (መ.ምሥ.፳፥፲)
ቀዳማዊት ሔዋን ያጣችውን ንጽሕና እመቤታችን ግን ሳይጎድልባት ይዛ ተወለደች፡፡
ስለዚህም ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም፦ ወመሠረተ ንጽሕነ ኮነ በማርያም ድንግል-የንጽሕናችን የቅድስናችን መሠረትስ በማርያም ድንግል ተደረገልን” አለ፡፡
አምላካችን ከበረከተ ልደቷ ያሳትፈን፡፡አሜን፡፡ይቆየን










