gedamat 11

የኔታ ይቆዩን የገዳማት ዐውደ ርእይ በፓሪስ ከተማ

ሚያዚያ 11 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ደረጄ ግርማ

 

gedamat 11የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል የፈረንሳይ ግንኙነት ጣቢያ ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶችን የሚያስተዋውቅ ዐውደ ርእይ ማዘጋጀቱን ገለጠ።

 

ዐውደ ርእዩም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ታሪክና ለሀገር ያበረከተችውን አስተዋጽኦ፣ በተለይም ጥንታዊ ገዳማት ትናንትና ዛሬ እንዲሁም የአብነት ትምህርት ቤቶችን ነባራዊ ሁኔታ የሚዳስስ፤ እየተደረጉ ያሉ ድጋፎችን የሚጠቁም እንዲሁም ከሕዝበ ክርስቲያኑ የሚጠበቀውን ድርሻ የሚያመላክት ዐውደ ርእይ ይቀርባል።

ከዚህም በተጨማሪ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ስኮላርሸፕ፤ የላይ ቤት ትርጓሜ ፕሮጀክት እንዲሁም የቅዱስ ያሬድ 1500 ዓመት መታሰቢያ የሚያመላክቱ ጹሑፎች ቀርበው ውይይት ይደረግባቸዋል፡፡ ዐውደ ርእዩም ሚያዚያ ፲፰ ቀን ፳፻፭ ዓም ለፓሪስ እና አካባቢ ምእመናን እንደሚቀርብ ተገልጿል። ከፓሪስ ደብረ ም/ቅ/ማርያም ሰበካ ጉባኤ ጋር በመተባበር ሚያዚያ ፲፱ ቀን ፳፻፭ ዓም ልዩ የስብከተ ወንጌል መርሐ ግብር የተዘጋጀ ሲሆን በዕለቱም በገዳማት እና አብነት ትምህርት ቤቶች ወቅታዊ ሁኔታ ላይ ውይይት እንደሚካሄድ ከዝግጅቱ አስተባባሪ ኮሚቴ የደረሰን መረጃ አመልክቷል። ለዚህ ዝግጅት አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ የማኅበረ ቅዱሳን ቅዱሳት መካናትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አንድ ልዑክ እንዲሚልክ ለማወቅ ተችሏል።

 
በአውሮፓ የምትገኙ ሁላችሁም በዝግጅቱ እንድትታደሙ የተጋበዛችሁ ሲሆን በርቀት ያላችሁ ለመርሐ ግብሩ ስኬት በጸሎት እንድታግዟቸው አስተባባሪ ኮሚቴው ጥሪውን አስተላልፏል።

seletena 2 2

ከየማእከላቱ ለተውጣጡ ተጠሪዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና ተሰጠ

ሚያዚያ 9 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ

seletena 2 2በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ከየማዕከላቱ ለተውጣጡ 38 የክፍል ተጠሪዎች ከሚያዝያ 4 ቀን 2005 ዓ.ም. በዋናው ማእከል የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና ተካሄደ፡፡

የሥልጠናውን ዓላማ አስመልክቶ የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ዳይሬክተር ዲ/ን አእምሮ ይሄይስ “የማኅበሩን ስልታዊ ዕቅድ ተጠሪዎቹ ግንዛቤ ኖሮአቸው በቀጣይ በየማእከላቱ የሚሠሩትን ሥራ በተግባር ላይ እንዲያውሉ ለማስቻል  ነው” ብለዋል፡፡

አያይዘውም ሥልጠናው በዚህ ዓመት ለመጀመሪያ ጊዜ የተካሄደ ሲሆን፣ በቀጣይም  በገዳማት ላይ የሚሠራውን የልማት ሥራ በጋለ ሆኖ ከታሰበበት ለማድረስ ያግዛል ሲሉ ሓላፊው ገልጸዋል፡፡

ከሥልጠናው ተሳታፊዎች መካከል የደሴ ማእከል የቅዱስት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል ተጠሪ ወ/ት ስንታየው እሸቱ በሥልጠናው የተለያዩ ግንዛቤዎችን አግኝቻለሁ፡፡ በተለይ የአብነት ትምህርት ቤት ላይ የምንሠራቸውን ሥራ እንዴት ማጠናከርና ገቢ ማሰባሰብ እንዳለብን፣ ፕሮጀክት እንደምንቀርጽና እንደምንተገብር ተንዝቤያለሁ፡፡

ሌላው ከአሰበ ተፈሪ ማእከል የመጣው አቶ ብርሃኑ እንዳለ በሀገራችን በሚገኙአብያተ ክርስቲያናት የአገልጋይ እጥረት ይስተዋላል፡፡ ከዚህ አንጻር የአብነት ትምህርት ቤቶች ተተኪ አገልጋይ የሚፈራባቸው በመሆኑ ብዙ ሊሠራ እንደሚገባ የሚያመለክትና ችግሮችን ለመቅረፍ የሚያስችል ነው ብለዋል፡፡

ለሦስት ቀን በተካሄደው መርሐ ግብር ሉላዊነት እና የቤተ ክርስቲያን የማእከላት ድርሻ ምን መምሰል አለበት፣ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ስኮላር ሺፕ ፕሮግራም አፈጻጸም ማእከላት ድርሻቸው ምን መሆን አለበት፣ ቤተ ክርስቲያን ለልማት ያላት ምቹነትና ተግዳሮቶች፣ የሀብት ምንነት የፕሮጀክት ሠነድ ዝግጅት፣ የንግድ ዕቅድ ዝግጅት (ለገዳማት፣ አብያተ ክርስቲያናት፣ አብነት ት/ቤት ተማሪዎች) በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ሥልጠናና ውይይት ተደርጓል፡፡

በመርሐ ግብሩም ላይ የማኅበሩ ዋና ጸሐፊን ጨምሮ ከሁሉም ማእከላት የተውጣጡ 38 የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ተጠሪዎች ተሳትፈዋል፡፡

“መኑ ውእቱ ገብር ኄር” “ታማኝ አገልጋይ ማነው”? ማቴ.24፥45

ሚያዚያ 4 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ር ምስጢረ ሥላሴ ማናየ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስያሜ የዐቢይ ጾም ስድስተኛው እሑድ ወይም ሳምንት ገብር ኄር ይባላል፡፡ ሰያሜውን የሰጠውም ኢትዮጵያዊ ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ ጾመ ድጓ በተባለው ከአምስቱ መጻሕፍቶቹ አንዱ በሆነው ጾመ ድጓ መጽሐፍ ሳምንቱን የዐቢይ ጾም ሳምንታት ስያሜዎች ከነሥርዓተ ማኅሌቱ አዘጋጅቷል፡፡ ስለዚህ በስድስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ከዋዜማው ቅዳሜ ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን፡- የሚዘመረው ዝማሬ፣ የሚሰበከው ስብከት፣ የሚሰጠው ትምህርት ገብርኄርን የሚያወሳ ነው ማለት ስለ ታማኝ አገልጋይ ነው፡፡ በማቴ.25፥14-25 የተገለጸውና በዕለቱ የሚነበበው ወንጌልም የሚነግረን ይህን ነው፡፡

“አንድ ባዕለ ጸጋ ሰው ባሪያዎችን ጠርቶ ለአንዱ አምስት መክሊት ሰጠው፣ ሁለት መክሊት የሰጠውም አለ፣ አንድ መክሊትም የሰጠው አለ፡፡ ከዚህ በኋላ ወደሩቅ አገር ሄደ፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለውም ወጥቶ ወርዶ ሌላ አምስት አትርፎ አስር አደረገ፡፡ ሁለት የተቀበለውም አትርፎ አራት አደረገ፡፡ አንድ የተቀበለው ግን ሄዶ መሬቱን ቆፍሮ በሻሽ ጠቅልሎ የጌታውን መክሊት ቀበራት፡፡

ከብዙ ጊዜ በኋላ ጌታቸው መጥቶ ተቆጣጠራቸው፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለው ቀርቦ ጌታዬ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር እነሆ አምስት አተረፍኩ አለው፡፡ “ገብርኄር ወምዕመን ዘበሁድ ምዕምነ ኮንከ ዲበ ብዙህ እሰይመከ ባዕ ውስተ ፍስሐሁ ለእግዚእከ” “አንተ ታማኝ ባሪያ በጥቂቱ ታምነሃል በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” አለው፡፡ ሁለት የተቀበለውም ቀርቦ ጌታዬ ሁለት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር እነሆ ወጥቼ ወርጄ ሌላ ሁለት አትርፌ አራት አድርጌአለሁ፡፡ “አንተ ታማኝ በጎ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃል በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” አለው፡፡

አንድ መክሊት የተቀበለው ግን ቀርቦ “ጌታዬ አንተ ክፉና ጨካኝ ካልዘራህበት የምታጭድ ካልበተንህበት የምትሰበስብ እንደሆንክ ስለአወቅሁ መሬቱን ቆፍሬ ቀበርኋት እነኋት መክሊትህ” አለው፡፡ “አንተ ሰነፍ ባሪያ መክሊቴን በጊዜ ልትሰጠኝ በተገባህ ነበር እኔም ወጥቶ ወርዶ ለሚያተርፍ በሰጠሁት ነበር”፡፡

ንዑ የዚህን ሀኬተኛ መክሊት ውሰዱና አስር መክሊት ላለው ስጡት፡፡ ላለው ይሰጡታል ይጨመርለታል ለሌለው ግን ያለውን ይቀሙታል፡፡ ንዑ ይህን ሰነፍና ሃኬተኛ ባሪያ እጅ እግሩን አሥራችሁ ጽኑዕ ጨለማ ወደአለበት ውሰዱት ጩኸትና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ጨምሩት” አለ ማቴ.25፥14-25፡፡

ባዕለ ጸጋ የተባለው ጌታ ነው፡፡ መክሊት የተባለው ልዩ ልዩ የአገልግሎት ጸጋ ነው፡፡ ያተረፉት በሚገባ በታማኝነት ያገለገሉ ቅዱሳን ሰዎች ናቸው መክሊቱን የቀበረው ደግሞ በታማኝነት በተሰጠው ጸጋ ማገልገል ሲገባው ያላገለገለ ነው፡፡ ጌታቸው ሊቆጣጠራቸው መጣ ማለት በዕለተ ምጽአት ለሁሉም በአገለገለው አገልግሎት ዋጋ ለመስጠት እንደሚመጣ ያሳየናል፡፡

ያገለገሉትን ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አላቸው ማለት ታማኝ አገልጋዮች መንግሥተ ሰማያትን ይወርሳሉና፡፡ ሰነፎች ደግሞ ጥርስ ማፋጨት ስቃይ ጽኑዕ ጨለማ ባለበት ሲዖል መግባታቸውን የሚያሳይ ነው፡፡

ከላይ ያነሳነው የቅዱስ ወንጌል ቃል፡- “ታማኝ አገልጋይ ማነው”? ይህ እያንዳንዱ በአርዓያ እግዚአብሔር የተፈጠረ የሰው ልጅ ጥያቄ ነው የዚህን አምላካዊ ጥያቄ መልስ መስጠት ከሰው ልጆች ይጠበቃል፡፡

1.    ታማኝ አገልጋይ ማነው? ሙሴ ነው፡፡
ሙሴ ታማኝ አገልጋይ ነበር ታማኝ አገልጋይ መሆኑን ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሠክራሉ፡፡ “በመካከላችሁ ነቢይ ቢኖር እኔ እግዚአብሔር በራእይ እገለጥለታለሁ ወይም በህልም አናግረዋለሁ ባሪያዬ ሙሴ ግን እንዲህ አይደለም እርሱ በቤቴ ሁሉ የታመነ ነው” ዘኁ.12፥6፡፡ ይህ የፍጡር ምስክርነት ሳይሆን በፈጣሪው የተሰጠ ምስክርነት ነው፡፡ በዕውኑ በዘመናችን እንኳን ፈጣሪ ፍጡራን ታማኝነቱን የሚመሰክሩለት አጋልጋይ ይኖር ይሆን? እንጃ የሙሴን ታማኝ አገልጋይነት በረሃ፣ ስደት፣ መከራ፣ የፈርዖን ግርማ እና ቁጣ ያልበገረው አርባ ዓመት ስለ ወንድሞቹ በመሰደድ አርባ ዓመት ደግሞ የተሰደደላቸው ወንድሞቹን በመምራት ባሕር በመክፈል፣ ጠላት በመግደል፣ መና በማውረድ ደመና በመጋረድ ውኃ ከዓለት አፍልቆ በማጠጣት መከራውን ከወገኖቹ ጋር በመቀበል የቀኑ ሀሩር የሌሊቱን ቁር/ ብርድ/ ታግሶ በታማኝነት አገልግሏል፡፡ ታማኝነቱ እስከሞት ነበር፡፡

“ሙሴም ወደ እግዚብሔር ተመልሶ ወዮ እኒህ ሕዝብ ታላቅ ኀጢአት ሠርተዋል፡፡ ለራሳቸውም የወርቅ አማልክት አድርገዋል፡፡ አሁን ይህን ኀጢአታቸውን ይቅር በላቸው ያለዚያ ግን ከጻፍከው መጽሐፍ እባክህ ደምስሰኝ ከባለሟልነትህ አውጣኝ /ዘጸ.32፥31፡፡ አያችሁ ታማኝ አገልጋይ እኔ ልሙት ሌሎች ይዳኑ የሚል ነው አሁን የምናየው ግን ፈጽሞ ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ሰዎች ይሙቱ እኔ ልኑር ሰዎች ጦም ይደሩ እኔ ልብላ ሰዎች ይራቆቱ እኔ ልልበስ ሰዎች ይዘኑ እኔ ልደሰት ነው፡፡ ይህ ታማኝ አገልጋይ ያለመሆን መገለጫ ነው፡፡ ታማኝ አገልጋይ ለሚያገለግላቸው ሰዎች ጥቅም ቅድሚያ የሚሰጥ እንጂ የራሱን ጥቅም የሚያስቀድም አይደለም፡፡ ዛሬ በዓለማችን የምንመለከተው ግን “ጩኸት ለአሞራ መብል ለጅግራ” የሚባለውን መሰል ነው፡፡ በታማኝ አገልጋዮች ድካም የሚሸለሙ ታማኝ አገልጋዮች በሠሩት ሪፖርት የሚያቀርቡ፣ የሚወደሱ ከጥቅሙ እንጂ ከድካሙ መክፈል የማይሹ እንቅፋት የሚመታው እግርን ነው፡፡ አክሊል የሚቀዳጀው ግን ራስ ነው፡፡ ታማኝ አገልጋይ ማለት እንደራስ አክሊል ዘውድ የሚጸፋ ብቻ ሳይሆን እንደ እግር እንቅፋቱን፣ እሾሁን፣ መከራውን ውጣ ውረዱን ድካሙን የሚቀበል ነው፡፡ በጥቅም ጊዜ ለራሱ በአካፋ የሚዝቅ ሌሎች በጭልፋ የሚቆነጥር አይደለም፡፡ ሙሴ ባሕር የከፈለው መና ያወረደው ደመና የጋረደው ውኃ ያፈለቀው ለራሱ አልነበረም ለሚመራቸው ሕዝብ ነበር እንጂ፡፡ ታማኝ አገልጋይ ያሰኘውም ይኸው ነው፡፡ በዚህ ከብሮበታል ተመስግኖበታልም፡፡

2.    ታማኝ አገልጋይ ማነው? ዳዊት ነው፡፡
ዳዊት ዘመነ መሳፍንት አልፎ ዘመነ ነገሥት ሲተካ እስራኤልን በንጉሥነት እንዲያገለግል እግዚአብሔር ከበግ ጥበቃ መርጦ በተሰጠው ሥልጣን ያልተመነ የሳዖልን በትረ መንግሥት በሳሙኤል እጅ ተቀብቶ ተቀብሏል፡፡

በተሰጠው ሥልጣን በታማኝነት ሕዝበ እስራኤልን መርቷል፡፡ ታማኝነቱንም እግዚአብሔር ለሙሴ እንደ መሰከረለት ለእርሱም መስክሮለታል፡፡
“እግዚአብሔር እንደልቡ የሆነ ሰው መርጧልና” የዘይቱን ቀንድ ሞልተህ በልጆቹ መካከል ለእኔ ንጉሥ አዘጋጅቻለሁና ወደ እሴይ ወደ ቤተልሔም እልክሃለሁ” 1ሳሙ.13፥13፣ 16፥2፡፡

“ወረከብክዎ ለዳዊት ገብርየ ወቀባዕክዎ ቅብዐ ቅዱስ” እንዲል መዝ.88፥20፡፡ “ባሪያዬ ዳዊትን አገኘሁት የተቀደሰ ዘይትንም ቀባሁት” ይህን አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ሰዓታት በተባለው ድርሰቱ፡- “ረከብክዎ ለዳዊት ገብርየ ብዕሴ ምዕመነ ዘከመልብየ” አገልጋዬ ዳዊትን እንደ ልቤ የታመነ ሰውን ሆኖ አገኘሁት ሲል ተርጉሞታል፡፡ የተገኘው በታማኝነት ነበር ከነገሠ በኋላም ታማኝ ነበር አሁን በዚህ ዓለም የምንኖር እኛ ግን በድኅነት ታማኝ እንሆንና ሀብት ሹመት ሥልጣን ሲመጣ ታማኝነትን እናጣለን፤ እንዲያውም ታማኝነትን እንንቀዋለን፡፡ መስረቅ ጀግንነት ይመስለናል፡፡ መዋሸት ሥልጣኔ ይሆንልናል፡፡ ዳዊት ሳይሾም በጎቹን በመጠበቅ ታማኝ ነበር፡፡ በጎቹን የሚነጥቅ ተኩላ አንበሳ ቢመጣ በኋላው ተከትሎ ነብሩን በጡጫ አንበሳውን በእርግጫ ብሎ በጎቹን ያስጥለው ነበር፡፡

“እኔ ባሪያህ የአባቴን በጎች ስጠብቅ አንበሳ ወይም ድብ ይመጣ ነበር ከመንጋውም ጠቦት ይወሰድ ነበር በኋላውም እከተለውና እመታው ነበር ከአፉም አስጥለው ነበር በተነሳብኝም ጊዜ ጉረሮውን አንቄ እመታውና እገድለው ነበር፡፡ ይህም ፍልስጥኤማዊ ከነዚያ እንደ አንዱ ይሆናል እንግዲህ እገድለው ዘንድ ከእስራኤል ተግዳሮትን አስወግድ ዘንድ ዛሬ አልሄድምን? የሕያው አምላክ ጭፍሮችን ይገዳደር ዘንድ ይህ ቆላፍ ምንድን ነው? ከአንበሳና ከድብ ያስጣለኝ እግዚአብሔር ከዚህ ያልተገረዘ ፍልስጥኤማዊ እጅ ያስጥለኛል” አለ 1ሳሙ.17፥34፡፡

ዛሬስ ቢሆን በእስራኤል ዘነፍስ በምዕመናን ላይ የሚገዳደሩ ብዙ ፍልስኤማውያን ተሰልፈዋል እነዚህን ድል የሚነሣ በጎቹን ምዕመናን ከተኩላ ከአንበሳና፣ ከድብ አፍ የሚታደግ ታማኝ አገልጋይ ማነው ከምእመናን ተግዳሮት የሚያርቅ ፈጣሪዬ ከመከራ ያድነኛል ብሎ የሚታመን የኢአማንያን ብዛት የማያስፈራው ማን ነው? ከትንሽነቱ እስከ ታላቅነቱ የታመነ አገልጋይ ማነው? ለተሾመበት ሓላፊነት ታማኝ ማነው? አሁንም ዓለማችን ከሥጋውያን ባለ ሥልጣናትም ሆነ ከመንፈሳዊያን መሪዎች የምትሻው ታማኝ ሰው ነው በሙስና ያልተዘፈቀ ጉቦ አይኑን ያላጨለመበት ለመንጋው አርአያና ምሳሌ የሚሆን ሰው ታማኝ አገልጋይ ማለት ያ ነው፡፡ በመኀላ የተቀበለውን የአገልግሎት ሓላፊነት የማይዘነጋ ጳጳስ፣ ቄስ፣ ዲያቆን፣ ሰባኪ፣ መምህር፣ ሐኪም፣ ዳኛ፣ ነጋዴ፣ ተማሪ፣ ወታደር፣ የቤት ሠራተኛ፣ የቢሮ ሠራተኛ ታማኝ መሆን አለበት፡፡

መንጋው በክህደት ሲጠፋ ዝም ብሎ የሚያይ ጳጳስ፣ ቄስ፣ ዲያቆን፣ መምህር፣ ሰባኪ፣ ታማኝ አይደለም ታማሚው እየተሰቃየ የሚዝናና ቆይ ሻይ ልጠጣና የሚል ሐኪም ታማኝ አይደለም፡፡ ፍርድ የሚያጎድል ድሆችን የሚበድል ለደሃ አደጎች የማይፈርድ ዳኛ ታማኝ አገልጋይ አይደለም፡፡

ቅቤ በሙዝ እና በድንች ቀላቅሎ በርበሬ በገል ጨምሮ ሌሎችን አጭበርብሮ የሚሸጥ ነጋዴ ታማኝ አገልጋይ አይደለም፡፡ እየነገደ ያለው በሰው ሕይወት መሆኑን መዘንጋት የለበትም፡፡ እንደእየ አቅሙ በተሰጠው የአገልግሎት ዘርፍ ታማኝ መሆን አለበት፡፡

3.    ታማኝ አገልጋይ ማን ነው? ዮሴፍ ነው፡፡
ዮሴፍ ለወንድሞቹ ምግባቸውን ተሸክሞ የእርሱ ስንቅ ቢያልቅ የወንድሞቹን ስንቅ ያልበላ በትንሽ የታመነ ሰው ነበር፡፡ ወንድሞቹ ሸጠውት በቤተ ጴጥፋራ በሚያገለግልበት ጊዜም ታማኝ ነበር፡፡ ታማኝነቱ በጲጥፋራ ቤት ጌታ አድርጎታል፡፡

“ዮሴፍ ተሸጠ አገልጋይም ሆነ እግሮቹ በእግር ብረት ስለሰሉ ሰውነቱም ከብረት አመለጠች ቃሉ ሳይደርስ የእግዚአብሔር ቃል ፈተነው ንጉሥ ላከ ፈታውም የሕዝብ አለቃ አድርጎ ሾመው የቤቱም ጌታ አደረገው በገንዘቡ ሁሉ ላይ ገዢ አደረገው፡፡ አለቆቹን እንደ እርሱ ይገስጽ ዘንድ ሽማግሌዎችን እንደ እርሱ ጥበበኞች ያደርጋቸው ዘንድ” መዝ.104፥17፡ በዚህ ሁኔታ የነበረው ዮሴፍ የጌታው ሚስት ሲወጣ ባቱን ሲገባ ደረቱን እያየች ዐይኗን ጣለችበት በዝሙት አይን ተመለከተችው፡፡

“የጌታውም ሚስት በዮሴፍ ላይ ዐይኗን ጣለችበት ከእኔም ጋር ተኛ አለችው እርሱም እምቢ አለ፡፡ ለጌታው ሚስቱ እንዲህ አላት እነሆ ጌታዬ በቤቱ ያለውን ሁሉ ለእኔ በእጄ አስረክቦኛል፡፡ በቤቱ ያለውን ምንም የሚያውቀው የለም በዚህ ቤት ከአኔ የሚበልጥ ሰው የለም፡፡ ሚስት ስለሆንሽ ከአንቺ በቀር ያልሰጠኝ ነገር የለም እንዴት ይህን ትልቅ ክፉ ነገር አደርጋለሁ? እንዴትስ በእግዚአብሔር ፊት ኀጢአትን እሠራለሁ ይህን ነገር በየዕለቱ ለዮሴፍ ትነግረው ነበር” ዘፍ.39፥7፡፡

በዮሴፍ ታማኝነት የጌታው ቤት ተባርኳል፡፡ ሀብቱ በዝቷል፡፡ በታማኝነቱ በቤቱ ያለውን ሁሉ ተረክቦ ነበር የቀረበለት ፈተና ግን ከባድ ነበር፤ ይህን በታማኝነቱ ማለፍ ችሏል፡፡ ዛሬ በእየአንዳንዱ ጓዳ እንደ እሳት የሚያቃጥሉ አገልጋዮች ናቸው ያሉት ልጅ በፈላ ውኃ የሚቀቅሉ ናቸው የሚበዙት እንኳን በሁሉ ገንዘብ ለመሾም አይደለም፡፡ በጥቃቅን ዕቃዎች እንኳን የሚታመን ጠፍቷል፡፡ ዮሴፍ ግን በታማኝ አገልጋይነቱ በመጣበት መከራ ቢታሰር እንኳ ያለ ሹመት አላደረም የእስረኞች አለቃ ነበር፡፡ ከእስር ቤት ሲወጣም ግብፅን በሙሉ መርቷታል፡፡ በግብፃውያን በሙሉ ተሾሟል በጥቂቱ ታምኗልና፡፡ “በጥቂቱ የታመነ በብዙ ይሾማል” እንዲል ማቴ.25፥24፡፡

ጌታውም መልካም አንተ የታመንህ በጎ አገልጋይ በጥቂት የታመንህ ስለሆንህ በብዙ እሾምሀለሁ” ከነዚህ ሦስት ታማኝ አገልጋዮች ሕይወት ሁሉም የሰው ልጅ ታማኝ አገልጋይነት የሚያሰጠውን ክብርና ጸጋ ተመልክቶ በታማኝነት ማገልገል ይገባዋል፡፡ ታማኝ መሆን መጀመሪያ የሚጠቅመው ለራስ ነው ከዚያ በኋላ ለሀገር ለወገን ለቤተ ክርስቲያን ላመኑት ላላመኑት ሁሉ ይጠቅማል፡፡ በመጨረሻም የጽድቅ አክሊልን ያቀዳጃል መንግሥተ ሰማያትን ያወርሳል፡፡ በሰውም በእግዚአብሔርም ፊት ያስከብራል፡፡

ጻድቃን ሠማዕታት ቅዱሳን በታማኝ አገልግሎታቸው ፈጣሪያቸውን ደስ አሰኝተው ከብረዋል፡፡ በሓላፊው ገንዘብ ያልታመኑት ይሁዳ፣ ሐናንያ፣ ሰጲራ፣ የደረሰባቸውን ጉዳት አይተናል፡፡ በአካን ወልደ ከርሚንም ተመሳሳይ ቅጣት ደርሶበታል ሐዋ.5፥1፣ 1፥25፡፡

ለዚህ ነበር ቅዱስ ዳዊት “አቤቱ አድነኝ ደግ ሰው አልቋልና ከሰው ልጆችም መተማመን ጎድሏልና” መዝ.11፥1፡፡ ስለዚህ ሁሉም በአለበት ያአገልግሎት መስክ ታማኝ አገልጋይ ሆኖ “አንተ በጎ ታማኝ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃል በብዙ እሾምሀለሁ” የሚለውን የጌታውን የምስጋና ቃል መስማት ይገባዋል፡፡ መልካም አገልግሎት አገልግለን መንግሥቱን እንድንወርስ “ገብርኄር” እንድንባል አምላካችን ይርዳን፡፡

ሐዊረ ሕይወት በሆለታ ደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን

ሚያዚያ 1 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

ሪፖርታዥ

መጋቢት 22 ቀን 2005 ዓ.ም. ሌሊት

ማኅበረ ቅዱሳን ወደ ሆለታ ደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የተዘጋጀው የሐዊረ ሕይወት /የሕይወት ጉዞ/ መርሐ ግብር ላይ ለመሳተፍ ምእመናን ከሌሊቱ 12፤00 ጀምሮ አምስት ኪሎ በሚገኘው በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም እና በማኅበረ ቅዱሳን ጽሕፈት ቤት ዙሪያ በመሰባሰብ ወደ ተዘጋጁት መኪናዎች ለመግባት ይጠባበቃሉ፡፡ እያንዳንዳቸው 61 ሰው የመጫን አቅም ያላቸው 85 አንደኛ ደረጃ አውቶቡሶች ከናዝሬት የልጃገረዶች ትምህርት ቤት እስከ ማኅበረ ቅዱሳን ጽሕፈት ቤት ፤ እንዲሁም ከትንሳኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት እሰከ መንበረ ፓትረያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ሰልፋቸውን ይዘው፤ በሮቻቸውን ከፍተው ምእመናንን በመጫን ላይ ተጠምደዋል፡፡ ትራፊክ ፖሊሶች አካባቢው በመኪናና ሰው እንዳይጨናነቅ ያስተባብራሉ፡፡

ምእመናን በሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር አስተባባሪዎች አማካይነት የጉዞ ቲኬታቸውን እያሳዩ ለጉዞው የተዘጋጀውን ባጅ እየተቀበሉ ወደ ተዘጋጀላቸው አውቶቡሶች ይገባሉ፡፡ ለምእመናን የተዘጋጀው ባጅ ሁለት መልእክቶችን ያዘለ ሲሆን በጽህፈት ቤት ግንባታ አብይ ኮሚቴ የተዘጋጀው ሰረገላ አስክንድር /በማኅበሩ ሕንፃ ላይ አሳንሰር ለመግጠም እንዲቻል  ምእመናን ድጋፍ እንዲያደርጉ ባለ 15፤ 150 እና ባለ 600 ብር ቲኬት በሽያጭ ላይ ስለመሆኑ የሚልገጽ ባጅ/ ፤ እንዲሁም በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባባሪነት የተዘጋጀ ከመጋቢት 25 እስከ ሚያዚያ 11 ቀን 2005 ዓ.ም. የሚቆይ ለአብነት ትምህርት ቤቶች የጽዳት እቃዎች ማሰባሰቢ ሳምንት በሚል ለኣብነት ትምህርት ተማሪዎች የሚሆኑ የተለያዩ ለጽዳትና ለምግብ ማብሰያና መጠጫ፤ ለአካባቢና ለግል ንጽህና መጠበቂያ የሚሆኑ ቁሳቁስ ምእመናን እንዲለግሱ የሚያሳስብ ባጅ ነው፡፡

ከለሊቱ 12፡30 ሰዓት ጀምሮ መኪናዎቹ ጉዟቸውን ጀምረዋል፡፡ ከአዲስ አበባ ውጪ የሚገኙ ማእከላት ተጓዦቻቸውን ይዘው ወደ ሆለታ በመሔድ ላይ ናቸው፡፡
መርሐ ግብሩን በኢንተርኔት በቀጥታ ሥርጭት ለማስተላለፍ በዝግጅት ላይ የሚገኙት የIT ባለሙያዎችና ጋዜጠኞች የተዘጋጀላቸው መኪና በምእመናን በመያዙ ምክንያት ለስርጭቱ የሚያገለግሉትን የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎችን ሌሎች መገልገያ እቃዎች በፒክ አፕ መኪና ላይ ጭነው እነሱም ከእቃዎቹ ጋር /ፍጹም፤ ቴዲ፤ ኤይተነው፤ ብዙአየሁ፤ ሄኖክ/ ተጭነዋል፡፡ እኔና በሥርጭቱ ወቅት ጽሁፎችን በመጻፍ እገዛ የምታደርግልን ጸሐፊያችን የምስራች ገቢና ቦታ ተይዞልናል፡፡ የ30 ኪሎ ሜትሩን መንገድ የመኪናውን ፍጥነትና የንፈሱን ግርፋት ተቋቁመው ወደ ሆለታ በሰልፍ የሚተሙት አውቶቡሶችን በማለፍ፤ አልፎ አልፎም ወርደን በካሜራችን የአውቶቡሶቹን በረድፍ መትመም እየቀረጽን ሆለታ ደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲቲያን ደረስን፡፡

በሰፊ ይዞታ ላይ ያረፈው የሆለታ ደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በማኅበረ ቅዱሳን የሙያ አገልግሎት ክፍል ባለሙያዎች ዲዛይኑ ተዘጋጅቶ በነፃ የተሰጠ ሲሆን ግንባታው በመፋጠን ላይ ነው፡፡ ከአዲሱ ሕንፃ በስተ ምስራቅ አቅጣጫ በ1968 ዓ.ም. የተተከለው አነስተኛ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡ የደብሩ አስተዳደር ጽ/ቤት፤ የሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት፤ የሰንበት ትምህርት ቤት አነስተኛ አዳራሽ፤ ለአጸደ ሕጻናት መማሪያነት የተሰሩ አራት ክፍሎች . . . በቤተ ክርሰቲያኑ ዙሪያ ይገኛሉ፡፡  
ቀድመውን የደረሱት አውቶቡሶች ምእመናንን አውርደው በተዘጋጀላቸው ስፍራ ላይ ተደርድረዋል፡፡ ምእመናን ከአውቶቡሶቹ እየወረዱ ቤተ ክርስቲያን እየተሳለሙ በአስተናጋጆች አማካይነት ወደ ተዘጋጀው የዳቦ መክፈልት እየተቀበሉ ወደ ተዘጋጀው ደንኳን በማምራት ቦታቸውን ይይዛሉ፡፡

ጠዋት
ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ለመርሐ ግብሩ ልዩ ትኩረት በመስጠት ቡራኬያቸውን ለመስጠት በሆለታ በደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ተገኝተዋል፡፡ የደብሩ የአቋቋም የአብነት መምህራንና ተማሪዎች የአቋቋም ትምህርት ሂደት ለማሳየት መምህራቸውን ከብበው፤ በዝማሬ ትምህርታቸውን ይወጣሉ፡፡ መምህሩ ቀለምና ዜማ እንዳይሰበር ይቆጣጠራሉ፡፡ ቀለም የሚስተውን ወይም ዜማ የሚሰብር ካጋጠማቸው አስተካክል በሚል በዓይናቸው ገረፍ ያደርጉታል፡፡

ከጠዋቱ 3፡30 ሰዓት ሲሆን በብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ዑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ መሪነትና ቡራኬ መርሐ ግብሩ በጸሎተ ወንጌል ተከፈተ፡፡

የጸሎት መርሐ ግብሩ እንደተጠናቀቀ ከቀደምት ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ከተመሠረቱት ማኅበራት መካከል የማኅበረ ሰላም የመዝሙር ክፍል አባላት ያሬዳዊ ዝማሬ አቅርበዋል፡፡ 

በሰዋሰው ብርሃን መንፈሳዊ ኮሌጅ የቅኔ መምህር የነበሩና በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በተለያዩ ሓላፊነቶች በመመደብ እያገለገሉ የሚገኙ በመንፈሳዊ ትምህርት የበለጸጉና በዘመናችን ከሚገኙ ሊቃውንት መካከል አንዱ የሆኑት ንቡረ ዕድ ከፍለ ዮሐንስ በተጋባዥ እንግድነት የተገኙ ሲሆን “መንግስተ ሰማያት ሰው ወስዶ በእርሻው የዘራትን የሰናፍጭ ቅንጣት ትመስላለች” /ማቴ.13፡31/ በሚል ርዕስ ሰፋ ያለ የወንጌል ትምህርት ሰጥተዋል፡፡

 
“የእግዚአብሔር መንግሥት የተባለች ቃለ ወንጌል ምሥጢረ ሥጋዌን ሲያመለክት ነው፡፡ሰናፍጭ በመዘራቷ ነው የበቀለችው ትለመልማለችም፤ ብዙም ፍሬ ታፈራለች፡፡ ለእናትነት ከዚህ ዓለም በመረጣት በድንግል ማርያም ትመሰላች፡፡ ከሥጋዋ ሥጋ፣ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ በየጥቂት አድጎና ምስጢረ ጥምቀትን ፈጽሞ እኛን የጠበቀን ያሳደገን መድኀኒታችን ኢየሱሰ ክርስቶስን አስገኝታለችና፡፡ የተበተነውን ሕይወታችንን ሊሰበሰበው ስለፈቀደ ነው፤ ወደ እኛ የቀረበው፡፡ ይህንን ማኅበር የመሠረቱት ጥቂቶች ናቸው፡፡ በሰናፍጭ ቅንጣቱ እንደ ተማርነው በማኅበሩ ጥላ ሥር ብዙዎች በእግዚአብሔር መግቦት ተሰባስበዋል፡፡ እግዚአብሔር እያሠራው ነው፡፡ ይህ ማኅበር ቤተ ክስቲያናችንን፣ አባቶቻችንን እንዲሁም ምእመናንን እንዲያገለግል የእግዚአብሔር ፈቃድ እያሰራው ነው፡፡ ምእመናንም መጠቀም የኛ ፋንታ ነው፡፡ ማኅበሩን ብንጠቀምበት፣ ብንተባበረው መልካም ነው፡፡ ከልጆቻችን ፍቅርን፣ ትሕትናን፣ ራስን ዝቅ ማድረግን፣ በጥሻው ውስጥ የወደቁት አባቶችን መጠየቅ ፤ ማጽናናትን እንማራለን፡፡ በጥምቀት ያገኘነውን ልጅነት አክብረን መኖር አለብን፡፡ ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር የሁል ጊዜ ሥራችንን ሊሆን ይገባል፡፡ በጾም፣ በጸሎት የአጋንንት ክንድ መቁረጥ አለብን ቅዱስ ጳውሎስ ሰይፍን እንድናነሳ የሚነገረን ወንጌልን እንድንጫማ፣ ሥነ ምግባርን ታጥቀን መኖር እንዳለብን ሲያስተምረን ነው፡፡ ዛሬ አስለቃሾች ብንሆን ነገ አልቃሾች እንዳንሆን ልንጠነቀቅ ይገናል፡፡ ወዮባዮች እንዳንሆን በክርስቲየናዊ ሥነ ምግባር ሌሎችን መርዳት ይገባናል፡፡ መዳን ዝም ብሎ ፈረስ ጭኖ፣ መኪና ነድቶ የሚመጣ አይደለም በጎ ሥራ በመሥራት ግን ይገኛል፡፡ ያሰባሰበን እምነታችን ነው፡፡ ለነገ ቀጠሮ መያዝ አያስፈልግም፡፡ ለመዳን የሚፈልግ ሁሉ ይድናል፡፡ እኛም ድነናል፡፡ ልትድን ትወዳለህን የሚለውን አምላካዊ ቃል ሁል ጊዜ የምንጠየቀው ጥያቄ ነው፡፡ አዎ መዳን እንፈልጋለን ብለን የመጣን ነን፤ መዳን ስለምትፈልጉ ትጾማላችሁ፣ ንስሐ ትገባላችሁ፤ ሥጋወ ደሙ ወደሚሰጥበት ቤተክርስቲያን ትገሰግሳላችሁ፡፡ ይህ ሁሉ የሚሆነው መዳን ስለምትፈልጉ ነው፡፡” በማለት ሰፊ ትምህርት ሰጥተዋል፡፡

 

በመቀጠልም በዲ/ን ዘማሪ ቴዎድሮስ ዮሴፍ ዝማሬ የቀረበ ሲሆን በመልአከ ገነት አባ ወ/ጊዮርጊስ አበጀ የደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ የደብሩን ታሪክ በአጭሩ አቅርበዋል፡፡

 

በሆለታ ደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የተደረገው የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር እስከ ምሳ ሰዓት የተካሔደውን ከላይ ያስቃኘናችሁ ሲመስል በመርሐ ግብሩ ላይ በአጠቃላይ 5700 ምዕመናን የአጥቢያው ምእመናንን ሳይጨምር መሳተፋቸውን ከአስተባባሪ ኮሚቴው የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ የምሳ መርሐ ግብሩም
በተሳካ ሁኔታ ተካሒዷል፡፡

ከሰዓት በኋላ
ከሰዓት በኋላ በተያዘው መርሐ ግብር መሠረት የማኅበረ ቅዱሳን የመዝሙር ክፍል አባላት ያሬዳዊ ዝማሬ በማቅረብ የተጀመረ ሲሆን ከጠዋት ጀምሮ በመርሐ ግብሩ ላይ በመገኘት ምእመናንን በመባረክ የቆዩት ብፁዕ አባታችን አቡነ ሉቃስ የሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከስዓት በኋላ ለሌላ አገልግሎት ወደ አዲስ አበባ ስለሚመለሱ ቃለ ምእዳንና ቡራኬ ሰጥተዋል፡፡   

 
ብፅዕነታቸው በሰጡት ቃለ ምዕዳን “የእግዚአብሔር ልጆች  የእግዚአብሔር ሥራ ይሠራሉ፡፡ መመሰባሰባችን ከሁሉም በላይ ፈቃዱ የእግዚአብሔር ነው፡፡ የክርስትና ጉዞ ተምሮ መቅረት ተገንብቶ መፍረስ አይደለም፡፡ የክርስቶስ ልጆች የምንሆነው የክርስቶስን ሥራ ስንሠራ ነው፡፡ መሠረቱ ደግሞ ፍቅር ነው፡፡ የክርስትና ሃይማኖት እውነት እንጂ  ሐቁን አለባብሶ አቆንጅቶ ማስቀመጥ አይደለም፡፡ የክርስቶስ ሥራዎች በእኛ ሕይወት ውስጥ ሊታይ ይገባል፡፡ ይህ የእግዚአብሔር ጉባኤ ነው፡፡ እግዚአብሔር ባይመራው በፀሐይ እየተመቱ አፈር ላይ ተቀምጦ መማር አይቻልም” ብለዋል፡፡ ብፁዕነታቸውም ቡራኬ ሰጥተው ወደ አዲስ አበባ የተመለሱ ሲሆን ጉባኤው ግን ቀጥሏል፡፡
ከስዓት በኋላ ከተያዙት መርሐ ግብራት መካከል ዲ/ን ብርሃኑ አድማስ “በኢየሩሳሌም የሚኖሩ” መ.ኢያሱ.15፥63  በሚል ርዕስ የዕለቱን የወንጌል ትምህርት ሰፋ አድርገው ሰጥተዋል፡፡  

ዲያቆን ብርሃኑ አድማስ በሰጡት የወንጌል ትምህርት “የከነዓንን ምድር የወረሱት የኤፍሬም ልጆች ናቸው፡፡ በጌዝርም የተቀመጡትን ከነዓናዊያንንም አላሳደዷቸውም እሰከ ዛሬም ድረስ ከነዓናዊያን በኤፍሬም ልጆች መካከል ተቀምጠዋል፡፡ ከነዓን ርጉም ፍሬ ቢስ ማለት ነው የተቀደሰውን የሚረግጥ፣ በጎውን እያየ የማይጠቀም፤ እንቁውን የሚረግጥ…. ኤፍሬም ማለት ደግሞ ፍሬያማ ማለት ነው፡፡ ኢያቡሳውያንም ከአፍሬማውያን ጋር አብረው ኖረዋል፡፡  ዛሬም ኢያቡሳውያን  በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በተለያዩ ምክንያቶች አብረውን ይኖራሉ፤ ማጥፋት ባንችልም በግብራቸው ግን ልንተባበር አይገባም፡፡ ኑፋቄውን ማሳደድ መናፍቁን ማዳን፤ የዝሙትን መንፈስ መገሰጽ ዘማዊውን ማንጻት፤ የንፍገት መንፈስን ማሳደድ ንፉጉን ቸር፤ ለጋስ ማድረግ ይገባል፡፡ ይህ ነው መልካም ጦርነት የምንለው፡፡ አንዳንድ ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ መልካም ያልሆኑ ነገሮችን ስንመለከት፤ አንዳንድ መናፍቃንን ስንመለከት፤ በቤተክርስቲያን ውስጥ በምግባር እጅግ የራቁና ባልተገባ ሕይወት ውስጥ ቤተ ክርስቲያንን ለማሽከርከር የሚጥሩ ሰዎችን ስናይ እግዚአብሔር ለምን ዝም ይላል እንላለን፡፡

“በየቤቱ እንደ ጸሎት መጽሐፍ የራሱን ኑፋቄ ይዞ የሚዞር አለ፡፡ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሆኖ መጥፎ ሥራ የሚሰራውን ተመልክቶ ቤተ ክርስቲያን ትክክል አደለችም ማለት፣ በጎውን ደግሞ አይቶ ቤተ ክርስቲያን መጥፎ የለባትም ማለት አይቻልም፡፡ በኢየሩሳሌም ሁለቱም አይነት ሰዎች አሉና፡፡ ዛሬ በገዳማት ውስጥ ሆነው የሚያጭበረብሩ ሰውን  እንዲህ ታገኛላህ እያሉ የሚያታልሉእንዳሉ ሁሉ ሲያዩአቸው ምናምንቴ መስለው ስለ ሕዝብና ስለ ሀገር የሚጸልዩም አሉ” ብለዋል፡፡  

ከዲያቆን ብርሃኑ አድማስ የወንጌል ትምህርት በኋላ ዘማሪ ዲ/ን ዳዊት ፋንታዬ ያሬዳዊ ዝማሬ በመቅረብ የእለቱ መርሐ ግብር ቀጥሏል፡፡

ምእናን እንዲመለሱላቸው የሚፈልጓቸውን ጥያቄዎች በስልክ፤ በኢሜይል፤ እንዲሁም በአካል በመገኘት ለሐዊረ ሕይወት አስተባባሪ ኮሚቴው ያደረሱትን ምላሽ እንዲሰጥባቸው ማድረግ የመርሐ ግብሩ አንዱ አካል ስለነበር ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ በእያንዳንዱ ጥያቄ  ላይ ሰፋ ያለ ትንታኔ በማቅረብ ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡ ከተነሱት ጥያቄዎች መካከልም “በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አርአያ የማደርገው ሰው አጣሁ፡፡ ተስፋ በመቁረጥ ላይ ነኝ፡፡ ምን ትመክሩኛላችሁ?” ለሚለው ዲያቆን ያረጋል ሲመልሱም “ሃይማኖት ከእግዚአብሔር ጋር የሚኖረን ግንኙነት ነው፡፡ ከሰዎች ጋር በተለያየ ምክንያቶች ልንገናኝ እንችላለን፡፡ ከእግዚአብሔር ፍቅር ተነሳ ነው ሰውን የምንወደው እንጂ ስለ ሰዎች ፍቅር ብለን አይደለም እግዚአብሔርን የምንወደው፡፡ መነሻው እግዚአብሔር ነው፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያን ስንመጣ ፤  ክርስትናን ስናውቅ መጀመሪያ ሰዎችን አይደለም ማወቅ ያለብን፡፡ ሰዎች ወደ እግዚአብሔር ሊመሩን ይችላሉ፡፡ እነዚህ መንገዶች ናቸው፡፡ መድረሻው ግን አሁንም እግዚአብሔር ነው፡፡ ስለዚህ መጀመሪያ መተዋወቅ ያለብን ከእግዚአብሔር ጋር ነው፡፡ እኛ ግን ወደ ቤተ ክርስቲያን እንመጣና ከእግዚአብሔር ጋር ሳይሆን ከሰዎች ጋር እንተዋወቃለን፡፡ እግዚአብሔርን ትተን ከሰዎች ጋር እንጣበቃለን፡፡ እነዚያ ሰዎች ሲጠፉ እኛም አብረን እንጠፋለን፡፡ ቤተ ክርስቲያንን በአንዳንድ ወዲህ ወዲያ በሚሉ ሰዎች መለካት የለብንም፡፡ ማሰብ ያለብን የጸኑትን ነው፡፡ ስለዚህ አርአያ የምናደርጋቸው ሰዎች ከእግዚአብሔር እንደማይበልጡ መረዳት አለብን፡፡ ከሰዎች ይልቅ እግዚአብሔርን ማየት ስንጀምር ተስፋ መቁረጥ ከኛ ይርቃል፡፡ አርአያ የምናደርጋቸው ሰዎች ከቤተ ክርስቲያን ቢወጡ እንኳን እኛ ተስፋ ያደረግነው እግዚአብሔር እንዳለን ስለምንረዳ እንጸናለን፡፡” በማለት ምላሻቸውን ሰጥተዋል፡፡

ነብዩ ኤልያስ ከብሔረ ሕያዋን ወደ ምድር ወርዷል፡፡ እኛንም ልኮናል የሚሉ ወገኖች ተነሥተዋልና አስተምህሯቸው ምንድነው? ብታብራሩልን በማለት ለተጠየቀው ጥያቄም ዲያቆን ያረጋል በሰጡት ምላሽ “ሰንበት ቀዳሚት ናት፤ እሁድን ማክበር ስህተት ነው፡፡ ኤልያስ ሰንበትን ወደ ቅዳሜ ይመልሳል፤ እስካሁን እውነተኛው የመልከ ጼዲቅ መሥዋእት ስላልተሰዋ አሁን ኤልያስ እውነተኛውን የመልከ ጼዲቅ መስዋእት ይዞ መጥቷል፤ የጌታችን የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት ታህሣሥ 29 ሳይሆን መስከረም 1 ቀን ነው መከበር ያለበት፤ የዳዊት ኮከብ ተብሎ የሚጠራው ባለ ስድስት ጫፉ ኮከብን ይዛችሁ ጸንታችሁ ቁሙ፤ በቅርቡ በባሕር ዳር ውስጥ ሰውር ጉባኤ ተካሒዷል፡፡ ከኒቂያ፤ ከኤፌሶንና ከቁስትንትኒያ ጉባኤያት በላይ ተካሒዷል፡፡ በዚህ ጉባኤም ከገነትና ከብሔረ ሕያዋን ቅዱሳን መጥተው ተገኝተዋል፤ ካህናትን የገሰጸችና ከነመጻሕፍቶቻቸው ቤተ መቅደሳቸውን ያጠፋች ዮዲት ቅድስት ናት ይላሉ” በማለት ስለ ኤልያስ ወረዷል እያሉ በማስተማር ላይ ስለሚገኙት ሰዎች አስተምህሯቸውን ገልጸዋል፡፡

በመጨረሻም ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ የማኅበረ ቅዱሳን አመሠራረት፤ እያከናወናቸው ስለሚገኙ የአገልግሎት ዘርፎች በአጭሩ በመዳሰስ ለምእመናን ግንዛቤ ያስጨበጡ ሲሆን መርሐ ግብሩንም በማጠናቀቅ በጸሎት ተዘግቶ ምእመናን ወደ መኪናዎቻቸው አምርተው በሰላም ጉዞው እንደተጀመረ በሰላም ተጠናቋል፡፡ 

ለአብነት ትምህርት ቤቶች የጽዳት እቃዎች ድጋፍ ማሰባሰቢያ ሳምንት በመካሄድ ላይ ነው

መጋቢት 26 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባበሪነት ለአብነት ትምህርት ቤቶች የጽዳት እቃዎች ድጋፍ ማሰባሰቢያ ሳምንት ከመጋቢት 21 እስከ ሚያዚያ 11 ቀን 2005 ዓ.ም. በማኅበሩ ሕንፃ ላይ በመካሔድ ላይ ይገኛል፡፡

ተማሪው ምንም ዓይነት የምግብ፤ የመጠለያና የአልባሳት ድጋፍ ሳያገኝ ጥሬ ቆርጥሞ ፤ በሳር ጎጆ ተጠግቶ፤ በእራፊ ጨርቅ ተጠቅልሎ ትምህርቱን ይከታተላል፡፡ በቂ ምግብ ፤ ንፁህ የመጠጥ ውኃ ፤ መጸዳጃ ቤት ባለማግኘቱ ለተለያዩ ተላላፊ በሽታዎችም ይጋለጣል፡፡  በአብነት ትምህርት ቤቶች ውስጥ ጎልቶ የሚታየውን ችግር በተለይም ሰማንያ በመቶ የሚሆነው የበሽታ ዓይነት ከግልና ከአካባቢ ንጽሕና ጉድለት የሚመጣ በመሆኑ ማኅበረ ቅዱሳን ይህንን የጤና ችግር ለመቅረፍ 12000 /አሥራ ሁለት ሺህ/ ተማሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ መርሐ ግብር ነድፏል፡፡     

በተነደፈው ፕሮጀክት መሠረት ለ10 የአብነት ትምህርት ቤቶች የጋራ መጸዳጃ ቤት ግንባታ ፤ ባለ 200 ግራም 12000 የልብስ ሳሙና፤ 10 ባለ 3000 ሊትር የውኃ ማጠራቀሚያ ታንከር፤ የውኃ ማከሚያ ኬሚካሎች፤ ለውኃ መጠጫ፤ ለማብሰያ ፤ ለመመገቢያ ፤ ለገላና ለልብስ ማጠቢያ የሚያገለግሉ የተለያዩ መጠን ያላቸው ቁሳቁስ፤ መርፌና ምላጭ፤ . . . እንደሚያስፈልግ ከማኅበሩ የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡  

የተማሪዎቹን ሕይወት ለማትረፍና ትምህርታቸውን በሚገባ ተምረው ቤተ ክርስቲያንን የሚያገለግሉበት ሁኔታ ለመፍጠር በጎ አድራጊ ምእመናን በማኅበሩ ሕንፃ ላይ እሰከ ሚያዚያ 11 ቀን 2005 ዓ.ም. በሚደረገው የቁሳቁስ ድጋፍ የበኩላቸውን ልገሳ እንዲያደርጉ ተጋብዘዋል፡፡

ደብረ ዘይት

መጋቢት 26 ቀን 2005 ዓ.ም.

በአባ ዘሚካኤል ደሬሳ

የዓለሙ ፍጻሜ ምልክቱ ምንድ ነው?/ማቴ. 24፣3/


በዓቢይ ጾም ውስጥ ካሉት ሳምንታት ደብረ ዘይት 5ኛው ሳምንት ላይ ይውላል፡፡ ደብረ ዘይት ትርጉሙ የወይራ ዛፍ ተራራ ማለት ሲሆን፣ ይህም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በኢየሩሳሌም በሚገኘው በደብረ ዘይት ተራራ ቅዱሳን ሐዋርያት” የዓለሙ ፍጻሜስ ምልክቱ ምንድነው?”/ማቴ. 24፣3/ ብለው ጠይቀውት እርሱም የማይቀረውን የዓለም ፍጻሜና አስቀድመው የሚፈጸሙ ምልክቶችን አስረድቷቸዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ይህንኑ በደብረ ዘይት ሳምንት ታስበዋለች፤ ለምእመናኑም ከዘመኑ ሁኔታ አንጻር በመጻሕፍት የተጠቀሱትን የትንቢት ምልክቶቹን ከተግባራዊ የዓለም ክንዋኔዎች አንጻር በማገናዘብ ታስተምራለች፡፡ በመሆኑም በቤተ ክርስቲያናችን በደብረ ዘይት ሳምንት ምጽአትን አስመልክቶ የሚነገሩ ምስጢራት እጅግ ሰፊ ናቸው፡፡ ነገር ግን በዚህ ጽሑፍ በመጠኑ የምናየው ከቅዱሳት መጻሕፍት አንጻር በዓለም እየተከሰቱ ካሉ ወቅታዊ ምልክቶች ጋር በማገናዘብ ይሆናል፡፡

የሰው ልጅ ከሥነ ፍጥረት መነሻ ጀምሮ ስለ ራሱ መጨረሻና ስለ ዓለም ፍጻሜ ምንነት ማወቅን እንደሚሻ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዱናል፡፡ ከነዚህም በተለይ ቤተ ክርስቲያን በደብረ ዘይት እለት የምታስተምረው፤ ቅዱሳን ሐዋርያት’ የዓለሙ ፍሳሜስ ምልክቱ ምንድነው?/ማቴ. 24፥3/’ በማለት የጠየቁት ጥያቄ ቅድሚያ ይሰጠዋል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያት ከመለሰላቸው ዋናውና ቀዳሚው የምጽአቱ ምልክት የሐሳዊ መሲህ መምጣት ነው፡፡ ሐሳዊ መሲሕ ማለት በቀጥታ ትርጉሙ ሐሰተኛ የሆነ በስሙ ማለትም በኢየሱስ፣ በክርስቶስ፣ በአምላክ ስም የሚመጣ የክርስቶስ ተቃዋሚ ማለት ነው፡፡ ትርጉሙን አስፍተን ስናየው፣ ደግሞ ከሃይማኖት ጋር ተያያዥ የሆኑና ያልሆኑ በዓለም እየተካሄዱ ያሉ ሐሰተኛ ጉዳዮችንና የጥፋት መንገዶችን ያጠቃልላል፡፡ የሐሳዊ መሲሕ የጥፋት ሥራዎች ሳያውቁም ሆነ በተለይ ሆን ብለው በዓለማውያንና በክፉ መናፍስት ተከታዮች እየተፈለሰፉ በሚከሰቱ ሁኔታዎች የሚካሄዱ ናቸው፡፡ ከእግዚአብሔር የተገኙ የሃይማኖት የሥነ ተፈጥሮ የጋብቻና የመሳሰሉ ድንበሮች ማፍለስን ዓላማ ያደረጉ፤ እንዲሁም መንፈሳዊ ባህል፣ ሰብአዊ ክብርና የእድሜ፣ የቅደም ተከተል ትስስርና ክብር እንዲጠፋ የሚሠሩ ሁሉ ከሐሳዊ መሲሕ መደብና ከዓለም ፍጻሜ ምልክትአንጻር የሚታዩ ናቸው፡፡ በዝርዝር ለማየት የሚከተሉትን ነጥቦች እንመልከት፣

 

1. የሃይማኖት ድንበርን ማፍለስ፡- ”አባቶችህ ያኖሩትን /የሠሩትን/ የቀድሞውን የድንበር ምልክት አትፍልስ” ምሳ.22፥28፣ 23፥10 አፈጻጸሙ ሰዎች የእግዚአብሔርን ማንነት እንዳያውቁ ከማድረግ ይጀምራል፡፡ከዚህም አንዱ ሐሳዊ መሲሕ በእግዚአብሔር ስም በተለያየ ሁኔታና መንገድ መገለጥ ነው፡፡ ”እስመ ብዙሃን ይመጽኡ በስምየ እንዘ ይብሉ አነ ውእቱ ክርስቶስ፤ እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ ብዙ ሰዎች በኔ ስም ይነሣሉና” /ማቴ. 24፣5/፡፡ ይህም እንደ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርትና የቅዱሳን ሐዋርያት ስብከት መሠረት፣ ከክርስቶስ ወደ ሰማይ ማረግ በኋላ የሚመጣ፣ ክርስቶስን የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጁ ነው ብሎ የማይሰብክ ሁሉ፤ ሌላ አምላክን የሚሰብክ ሁሉ መደቡ ከሐሳዊ መሲሕ ትምህርት ይመደባል፡፡ በመሆኑም ከዚህ በፊት ያለፉ፣ አምላክ ነን ብለው የተነሡ እንደ ቴዎዳስ ዘግብጽና ይሁዳ ዘገሊላ /ሐዋ. ሥራ. 5፣36-37/ የመሰሉ ሁሉ ከዚያም በኋላ በየጊዜው የተነሡና በዚህም ወቅት የዋሁን ሕዝብ ”ኢየሱስ ነኝ፣ ኢየሱስ በኛ ዘንድ አለ” እያሉ የሚያጭበረብሩ ሁሉ ሐሳውያነ መሲሖች ናቸው፡፡ ከዚህም ሌላ ክርስቶስን ከአብ የሚያሳንሱ፣ ”ሎቱ ስብሐት” ነቢይ ነው ብለው የሚያምኑ፣ በመናፍስት አሠራር የሚጠነቁሉ፣ በማቴሪያሊስት /ቁሳውያን/ ወይም በኢቮሉሽን /በዝግመተ ለውጥ/ ትምህርት አምነው አምላክ የለም የሚሉ ሁሉ፣ ወዘተ የሐሳዊው መሲሕ አካላት ናቸው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በመልእክቱ ”ኢየሱስ ክርስቶስም በሥጋ እንደ መጣ የማይታመን መንፈስ ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደለም፤ ይህም የክርስቶስ ተቃዋሚው መንፈስ ነው፤ ይህም እንደማመጣ ሰምታችኋል፥ አሁንም እንኳ በዓለም አለ።” /1ዮሐ. 4፣3/ በማለት ይመሰክርባቸዋል፡፡

 

ቅዱስ ዮሐንስ አሁንም በመልእክቱ ”ልጆች ሆይ፥ መጨረሻው ሰዓት ነው፥ የክርስቶስም ተቃዋሚ ይመጣ ዘንድ እንደ ሰማችሁ አሁን እንኳ ብዙዎች የክርስቶስ ተቃዋሚዎች ተነሥተዋል፤ ስለዚህም መጨረሻው ሰዓት እንደ ሆነ እናውቃለን።” /1ዮሐ. 2፥18/ ይለናል፡፡ ከዚህ የምንረዳው የክርስቶስ ተቃዋሚ መምጣት የምጽአት ጊዜው መቃረብ ምልክት መሆኑን የማያሻማ ሀሳብ ያደርገዋል፡፡ በተጨማሪም የምጽአትን መቅረብ የሚያመለክቱ፣ ስለ ሐሳዊው መሲሕ እና ከርሱ ጋር ተያያዥ ስለሆኑ ወቅታዊ ጉዳዮች ተዛማጅ የሆኑትን የሚከተሉትን ትንቢቶች እንመልከት፣

ሀ. ”የአውሬው ምስል ሊናገር እንኳ ለአውሬውም ምስል የማይሰግዱለትን ሁሉ ሊያስገድላቸው፥ ለአውሬው ምስል ትንፋሽ እንዲሰጠው ተሰጠው። ታናናሾችና ታላላቆችም ባለ ጠጋዎችና ድሆችም ጌታዎችና ባሪያዎችም ሁሉ በቀኝ እጃቸው ወይም በግምባራቸው ምልክትን እንዲቀበሉ፥ የአውሬውም ስም ወይም የስሙ ቍጥር ያለው ምልክት የሌለበት ማንም ሊገዛ ወይም ሊሸጥ እንዳይችል ያደርጋል። ጥበብ በዚህ አለ። አእምሮ ያለው የአውሬውን ቍጥር ይቍጠረው፤ ቍጥሩ የሰው ቍጥር ነውና፥ ቍጥሩም ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ነው።” /ራእ. ዮሐ. 13፥16-18/ የሚለው የቅዱስ ዮሐንስ ራእይን ሊፈታ ከሚችልበት ትርጉም አንዲት ቅንጣት ብቻ ከዘመኑ አንጻር ብናይ ’የሚናገር የአውሬው ምስል’ ማለትም ለሱ ያልተገዙትን ወይም ቁጥሩን ያልያዙትን የሚናገርባቸው፤ ምልክቱን ያልተቀበሉትን ሊገዙና ሊሸጡ እንዳይችሉ ያደርግል ማለት መኖር፣ መሥራት፣ መሸጥ፣ መለወጥ ወዘተ የሚያግዳቸው ሲል አሁን ባለን ወቅታዊ የዚህ ዓለም አኗኗር አንጻር ሲታይ ተመሳሳይ ጉዳዮች አሉ፡፡ ለምሳሌ፣ መታወቂያ ወረቀት፣ ፓስፖርት፣ ቪዛ፣ የመኖሪያ ፈቃድ ወዘተ በዓለም አጠቃላይ አሠራር እና ባንድ ሰው የመኖር ማንነት ሚና ላይ ተጽእኖ የሚያደርጉ ነገሮች ናቸው፡፡ እነዚህ መታወቂያ ወረቀቶች የሌሉት ሰው ካለበት የትም መንቀሳቀስ አይችልም፡፡ ከዚህም በላይ ጉዳዩን ስናሰፋው በሰለጠኑት ዓለማት አሠራር የእያንዳንዱ ሰው የጣት አሻራ ኮምፒውተራይዝድ በሆነ መንገድ የተደራጀ በመሆኑ፣ እዚያ አደረጃጀት ውስጥ ካልተካተተ በቀር እዚያ ሀገር ሊኖር፣ ሊዘዋወር፣ ሊሠራ፣ ሊነግድ ወዘተ አይችልም፡፡ ለምሳሌ፣ አንድ እዚህ የኮምፒውተር ድር አደረጃጀት ውስጥ ያለ ሰው የትም ዓለም ቢሄድ በጣቱ አሻራ ይታውቃል፡፡ በትንቢቱ” አእምሮ ያለው የአውሬውን ቍጥር ይቍጠረው፤ ቍጥሩ የሰው ቍጥር ነውና፥ ቍጥሩም ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ነው።”  የሚለው ይህን የሚያደራጀው ጉዳዩን የሚያስተሳስረው ሌላ አካል ሳይሆን ሰው መሆኑን የሚያመለክት ነው፡፡ ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት የሚለው ቁጥር የሰው ልጅ የጅማት ቁጥር ነውና፡፡

ለ. ሌላው የምጽአት መቃረብ ምልክት የሐሳዊው መሲሕ ዘመቻን አውቀው በድፍረት፣ ላላወቁት በረቀቀ መንገድ እግዚአብሔርን ያመለኩ አስመስሎ የእግዚአብሔርን ስም፣ እመቤታችንን ቅድስት ድንግል ማርያምን፣ ቅዱሳንን፣ ባጠቃላይ በሰማይ የሚያድሩትን መስደብ ነው፡፡ እነዚህም ተግባራት በተለያዩ ዘመናት ሲፈጸሙ የቆዩ ናቸው ዛሬም ተጠናክረው እየተፈጸሙ ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ፣ ሩቅ ሳንሔድ ዛሬ ቤተ ክርስቲያናችንን እየተፈታተነ ያለው የተሐድሶ ሤራ ዋናው ተቃውሞው የወልድን አምላክነት፣ የድንግል ማርያምን ክብርና አማላጅነት፣ የታቦትንና የመስቀልን ክብር፣ የቅዱሳንን ክብርና አማላጅነት ነው፡፡ በመሆኑም ተሐድሶ በሥራው የአውሬው መንፈስ አራማጅና መንገድ ጠራጊ መሆኑን ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ እንዲህ በማለት ያረጋግጥልናል፡፡ ”ለዘንዶውም ሰገዱለት፥ ለአውሬው ሥልጣንን ሰጥቶታልና፤ ለአውሬውም፡- አውሬውን ማን ይመስለዋል፥ እርሱንስ ሊዋጋ ማን ይችላል? እያሉ ሰገዱለት። ታላቅንም ነገርና ስድብን የሚናገርበት አፍ ተሰጠው፥ በአርባ ሁለት ወርም እንዲሠራ ሥልጣን ተሰጠው። እግዚአብሔርንም ለመሳደብ ስሙንና ማደሪያውንም በሰማይም የሚያድሩትን ሊሳደብ አፉን ከፈተ። ቅዱሳንንም ይዋጋ ዘንድ ድልም ያደርጋቸው ዘንድ ተሰጠው፥ በነገድና በወገንም በቋንቋም በሕዝብም ሁሉ ላይ ሥልጣን ተሰጠው። ከዓለምም ፍጥረት ጀምሮ በታረደው በግ ሕይወት መጽሐፍ ስሞቻቸው ያልተጻፉ በምድር የሚኖሩ ሁሉ ይሰግዱለታል።” /ራእ. ዮሐ. 13፣4.8/ እንዲል፡፡

ሐ. ሌላው በዓለም ላይ የሚታየው በሰዎች ዘንድ ክብር፣ ዝናና ታዋቂነትን ለማግኘት ሲባል ራስን ከፍ ማድረግና እንደ አማልክት መቁጠር ከሐሳዊው መሲሕ ያስመድባል፡፡ ከዚህ በተመሳሳይ ሊቀ ነቢያት ሙሴ እንደገለጸው የሰናዖር ሰዎችን ኀጢአት ስናሰተውል የተነሡበት ዋናው ነጥብ ’ስማችንን እናስጠራ’ የሚለው ነበር፡፡” ኑ ለእኛ ከተማና ራሱ ወደ ሰማይ የሚደርስ ግንብ እንሥራ፤ በምድር ላይ ሳንበተንም ስማችንን እናስጠራው አሉ።” /ዘፍ. 11፥4/ ነው የሚለን፣ በዚህ እኩይ አሳብ ምክንያት እግዚአብሔር ቋንቋቸውን ደባለቀባቸው፡፡ የሰናዖር ሰዎች ያሰቡትናየተመኙት ትውልዱ እግዚአብሔርን ማድነቅ ትቶ፣ ለዘለዓለም ስማቸውን ሲጠራቸው፣ ሲያደንቃቸው መኖርን ነበር፡፡ ዛሬም ብዙዎቹ ይህንን የሰናዖርን ኀጢአትና የጥፋት ጉዞ እንደ ዓላማ ይዘው በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛሉ፡፡

2. የሥነ ተፈጥሮ ሕግ ድንበር መጣስ አንዱ የጊዜው መቃረብ ምልክት ነው፡፡ እግዚአብሔር የፈጠረው ፍጥረት ፍጹም በመሆኑ፣ ይህ ቀረህ፣ ይህ ይጨመርልህ የሚባል አይደለም፡፡ ነገር ግን በዚህ ወቅት፣ ሰው ለተለያየ ጥቅም በሚል ሰበብ ዝርያቸው የተለያዩ የሆኑትን ፍጥረታት ማዳቀልንና ማደበላለቅን ተያይዞታል፡፡እንስሳትና ተክሎችን ለማባዛት የማያደርገው ጥረትና  የማዳቀል ዘዴ የለም፡፡ በተቃራኒውም የሰውን ቁጥር ለመቀነስ የማያደርገው ሩጫ የለም፡፡ በመሆኑም ውጤቱ የሰውን ቁጥር ለመቀነስ ሲባል በሚደረጉ ሕክምናዎች ሰዎች ለተለያዩ በሽታዎች ተዳርገዋል፡፡ በሚደረገውም ማበረታታት በሠለጠኑት ዓለም ብዙዎቹ የግብረ ሰዶም ፈጻሚና አስፈጻሚ ሆነዋል፡፡ ይህ አሠራር አምላክ የሠራውን የፍጥረት ሕግ በማጣጣል ሰው ላሻሽል ወደሚል ያዘነበለ በመሆኑ የሰውን ልጅ ቅጥ ያጣ ድፍረት ያሳያል፡፡ እግዚአብሔር ግን ሥነ ፍጥረቱን እንዲያደባልቁበት አይፈልግም፡፡እግዚአብሔር ለሊቀ ነቢያት ሙሴ ”ሥርዓቴን ጠብቁ። እንስሳህ ከሌላ ዓይነት ጋር አይደባለቅ፤ በእርሻህም ሁለት ዓይነት ዘር አትዝራ” /ዘሌ. 19፣ 19፤/ ማናቸውም ሰው ከሴት ጋር እንደሚተኛ ከወንድ ጋር ቢተኛ ሁለቱ ጸያፍ ነገር አድርገዋል፤ ፈጽመው ይገደሉ፤ ደማቸው በላያቸው ነው።” /ዘሌ 20፣ 13/ በማለት ያሰተምረናል፡፡

3.    በጋብቻ ላይ የሚደረግ ርኩሰትን ስንመለከትም በየትኛውም ዓለም የፍርድ ቤቶች ትልቁ ሥራ ማፋታት ሆኗል፡፡ ምክንያቱም ተጋቢዎች ባንድ ላይ እንዳይኖሩ አውሬው /አስማንድዮስ/ የጋብቻ ጠላት በመሆን ስለነገሠ ፈተናውን መቋቋም አልቻሉምና ነው፡፡ ስለዚህ አስማንድዮስ ከዛ ይልቅ ግብረ ሰዶምን እያበረታታ በአንዳንድ ሀገሮች እንደሚታየው ወንድ ከወንድ፣ ሴት ከሴት ጋር እያቆራኘ በቤተ ክርስቲያኖቻቸው” ጋብቻ እስከ መፈጸም አድርሷቸዋል፡፡ ስለዚህም ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፣” ስለዚህ እርስ በርሳቸው ሥጋቸውን ሊያዋርዱ እግዚአብሔር በልባቸው ፍትወት ወደ ርኵሰት አሳልፎ ሰጣቸው፤ ይህም የእግዚአብሔርን እውነት በውሸት ስለ ለወጡ በፈጣሪም ፈንታ የተፈጠረውን ስላመለኩና ስላገለገሉ ነው፤ እርሱም ለዘላለም የተባረከ ነው፤ አሜን። ስለዚህ እግዚአብሔር ለሚያስነውር ምኞት አሳልፎ ሰጣቸው፤ ሴቶቻቸውም ለባሕርያቸው የሚገባውን ሥራ ለባሕርያቸው በማይገባው ለወጡ፤ እንዲሁም ወንዶች ደግሞ ለባሕርያቸው የሚገባውን ሴቶችን መገናኘት ትተው እርስ በርሳቸው በፍትወታቸው ተቃጠሉ፤ ወንዶችም በወንዶች ነውር አድርገው በስሕተታቸው የሚገባውን ብድራት በራሳቸው ተቀበሉ። እግዚአብሔርን ለማወቅ ባልወደዱት መጠን እግዚአብሔር የማይገባውን ያደርጉ ዘንድ ለማይረባ አእምሮ አሳልፎ ሰጣቸው፤ ዓመፃ ሁሉ፥ ግፍ፥ መመኘት፥ ክፋት ሞላባቸው፤ ቅናትን፥ ነፍስ መግደልን፥ ክርክርን፥ ተንኰልን፥ ክፉ ጠባይን ተሞሉ፤ የሚያሾከሹኩ፥ ሐሜተኞች፥ አምላክን የሚጠሉ፥ የሚያንገላቱ፥ ትዕቢተኞች፥ ትምክህተኞች፥ ክፋትን የሚፈላለጉ፥ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፥ የማያስተውሉ፥ ውል የሚያፈርሱ፥ ፍቅር የሌላቸው፥ ምሕረት ያጡ ናቸው፤ እንደነዚህ ለሚያደርጉት ሞት ይገባቸዋል የሚለውን የእግዚአብሔርን ሕግ እያወቁ እነዚህን ከሚያደርጉ ጋር ይስማማሉ እንጂ አድራጊዎች ብቻ አይደሉም።” /ሮሜ.1፥24-ፍጻሜ

4.    መንፈሳዊ ባህል፣  የክህነት ክብር፣ ሰብአዊ ክብርና የእድሜ፣ የቅደም ተከተል ትስስርና  ክብር እንዲጠፋ የሚሠሩ፣ በሚለው ዙሪያ ስንመለከት በቀላሉ ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ ያለውን ማየት እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡ነገር ግን በመጨረሻው ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንዲመጣ ይህን እወቅ። ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱ ይሆናሉና፥ ገንዘብን የሚወዱ፥ ትምክህተኞች፥ ትዕቢተኞች፥ ተሳዳቢዎች፥ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፥ የማያመሰግኑ፥ ቅድስና የሌላቸው፥ ፍቅር የሌላቸው፥ ዕርቅን የማይሰሙ፥ ሐሜተኞች፥ ራሳቸውን የማይገዙ፥ ጨካኞች፥ መልካም የሆነውን የማይወዱ፥ ከዳተኞች፥ ችኩሎች፥ በትዕቢት የተነፉ፥ ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይሆናሉ፤ የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል፤ እነዚህ ደግሞ ራቅ። ወደ ቤቶች ሾልከው እየገቡ፥ ኃጢአታቸው የተከመረባቸውን በልዩ ልዩ ምኞትንም የሚወሰዱትን ሁል ጊዜም እየተማሩ እውነትን ወደ ማወቅ ሊደርሱ ከቶ የማይችሉትን ሞኞችን ሴቶች የሚማርኩ፥ ከእነዚህ ዘንድ ናቸውና። ኢያኔስና ኢያንበሬስም ሙሴን እንደተቃወሙት፥ እንዲሁ እነዚህ ደግሞ አእምሮአቸው የጠፋባቸው ስለ እምነትም የተጣሉ ሰዎች ሆነው፥ እውነትን ይቃወማሉ። ዳሩ ግን የእነዚያ ሞኝነት ደግሞ ግልጥ እንደሆነ፥ ሞኝነታቸው ለሁሉ ይገለጣልና ከፊት ይልቅ አይቀናላቸውም።” / 2ጢሞ. 3፥1.7/ በማለት በመጨረሻው ዘመን የሚነሡ ሰዎችን ፀባይን ይነግረናል፡፡ ይህንን ትምህርተ ጥቅስ ለማገናዘብ  እግዚአብሔርን የማያምነውን ህዝብ ትተን፣ አሁን በዓለም ሁሉ ካለው የቤተ ክርስቲያንዋ አማኞች ብቻ አንጻር በመጠኑ እንይ ደግሞ፤

ሀ. መንፈሳዊ ባህል ማፍረስን ስንመለከት፣ የሁሉንም ባይሆን፣ የአንዳንዶቹ አማኞች ሰዎች ጸባይ ቅ. ጳውሎስ ”ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይሆናሉ፤ የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል” የሚያሰኝ ሕይወት የያዙ እንደሆነ ያስረግጥልናል፡፡ እንደ አማኝ ቤተ ክርስቲያን የሚገኙ፣ ነገር ግን መንፈሳዊ አምልኮ የማይፈጽሙና የራሳቸውን አሳብ ቤተ ክርስቲያን ላይ ሊጭኑ የሚፈልጉትን ነው ’የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደዋል’ ያላቸው፡፡ የእግዚአብሔር ቤት መታዘዝ፣ መከባበርና ሰላም የነገሠበት መሆን ነው ያለበት፡፡ ነገር ግን በአንዳንድ ቦታ እንደሚስተዋለው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ብዙዎቹ በመንፈሳዊው ባህል የጠነከሩ እንዳሉ ሁሉ አንዳንዶቹ ሥራ ፈቶች ሆነው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ፖለቲካ፣ዘረኝነት፣አሉባልታ፣ ወዘተ በማምጣት ቤተ ክርስቲያንን ሲያውኩአት ይታያል፡፡ ቅ. ሉቃስ በተመሳሳይ አይሁድ ቀንተው በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረጉትን ”አንዳንዶቹ ተረድተው ከሚያመልኩም ከግሪክ ሰዎች ብዙ ከከበሩትም ሴቶች ጥቂቶች ያይደሉ፥ ከጳውሎስና ከሲላስ ጋር ተባበሩ።  አይሁድ ግን ቀንተው ከሥራ ፈቶች ክፉ ሰዎችን አመጡ ሕዝብንም ሰብስበው ከተማውን አወኩ፥” /የሐዋ. ሥራ 17፣ 5/ በማለት እንደገለጸው ያሉ ናቸው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ”ወደ ቤቶች ሾልከው እየገቡ፥ ኃጢአታቸው የተከመረባቸውን በልዩ ልዩ ምኞትንም የሚወሰዱትን ሁልጊዜም እየተማሩ እውነትን ወደ ማወቅ ሊደርሱ ከቶ የማይችሉትን ሞኞችን ሴቶች የሚማርኩ፥ ከእነዚህ ዘንድ ናቸውና።” ይላቸዋል፡፡

ለ. የክህነት ክብርን ማፍረስ በተመለከተ፣ ቅ. ጳውሎስ ”ኢያኔስና ኢያንበሬስም ሙሴን እንደ ተቃወሙት፥ እንዲሁ እነዚህ ደግሞ አእምሮአቸው የጠፋባቸው ስለ እምነትም የተጣሉ ሰዎች ሆነው፥ እውነትን ይቃወማሉ። ዳሩ ግን የእነዚያ ሞኝነት ደግሞ ግልጥ እንደ ሆነ፥ ሞኝነታቸው ለሁሉ ይገለጣልና ከፊት ይልቅ አይቀናላቸውም።” እንዳለው ሁሉ ካህናት ነን ከሚሉት ጀምሮ እስከ ምእመናን ድረስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያት ሰጥቷቸው በአንብሮተ እድ እየተሾሙ ሲወርድ መጥቶ ለኛ የደረሰውን ታላቁን የድኅነት መፈጸሚያ ክህነት እንደ ኢያኔስና ኢያንበሬስ ዛሬ በብዙዎች ተንቆና ተዋርዶ ይገኛል፡፡ ለምሳሌ ከሚፈጸሙ ስህተቶች ጥቂቶቹን ቀጥለን እንመለከት፣

 

  • ቅዱስ ማቴዎስ ”በዚያን ዘመን ብዙዎች ይሰናከላሉ፣ እርስ በርሳቸውም አሳልፈው ይሰጣጣሉ፣ እርስ በርሳቸው ይጣላሉ” /ማቴ. 24፣10/ እንዳለው ሁሉ፤ለዘመናት በአንድነት የኖረችውን ቤተክርስቲያን ”ከዓመጻም ብዛት የተነሣ የብዙዎች ፍቅር ትቀዘቅዛለች” እንዲል፣ በዚህ ዘመን በድፍረት አስተዳደሩዋን በመከፋፈል ”ኢያኔስና ኢያንበሬስም ሙሴን እንደ ተቃወሙት” እንዲሁ አሳድጋ፣ አስተምራ፣ ክህነት የሰጠቻቸውን እናታቸውን ቤተ ክርስቲያን እስከ ማውገዝ የድፍረት ኀጢአት የተደረሰበት ዘመን ነው፡፡በመወጋገዙ ሂደት ያለው ጉዳትን ማን አስተዋለው? እግዚአብሔር ይማረን እንጂ እንደ ሰውኛው ከሆነ፣ በጭካኔ፣ ውስጥ ያለው ውጪውን፣ ውጭ ያለው ደጋግሞ ውስጥ ያለውን አውግዞትአንዲት ነፍስ ወደ እግዚአብሔር እንዳትደርስ ተቆላልፎ ቁጭ ብሏል፡፡ ነገር ግን ኢያኔስና ኢያንበሬስ ሙሴን ቢቃወሙትም ሙሴ ክህነቱ ከእግዚአብሔር በመሆኑ የእግዚአብሔር ክብር በርሱ ላይ ተገልጦ እግዚአብሔርን የተቃወሙት በደላቸው እንደ ተገለጠ ሁሉ፣ ዘለዓለማዊዋ ቤተ ክርስቲያን ክህነታዊ ክብርዋ በእግዚአብሔር ዘንድ ክቡር ነው፡፡  ”ሁሉ ለንጹሖች ንጹሕ ነው፤ ለርኵሳንና ለማያምኑ ግን ንጹሕ የሆነ ምንም የለም፥ ነገር ግን አእምሮአቸውም ሕሊናቸውም ረክሶአል።  እግዚአብሔርን እንዲያውቁ በግልጥ ይናገራሉ፥ ዳሩ ግን የሚያስጸይፉና የማይታዘዙ ለበጎ ሥራም ሁሉ የማይበቁ ስለ ሆኑ፥ በሥራቸው ይክዱታል።” / ቲቶ. 1፥15/ እንዳለ፡፡
  • ” ሰለስቱ ምእት በኒቂያ ጉባኤ ’ያለ ኢጲስ ቆጶስ ፈቃድ ቤተ ክርስቲያንን የመሠረተ ከክህነቱ ይሻር’ብለው ደንግገዋል፡፡ ነገር ግን በተለይ በውጭ አገር እየተለመደ የመጣው ጉዳይ የትኛውንም ኤጲስቆጶስ ሳያስፈቅድ አንድ ካህን፣ ከዚያም አልፎ በሚገርም ሁኔታ ዲያቆን ወይም ምእመን ከፈለገ ቦርድ አቋቋምኩ እያለ ቤተ ክርስቲያን አስተምራ አጥምቃ ያሳደገችውን ምእመን ከሥርዓተ ቤተክርስቲያን በማውጣት እንደ ማንኛውም ድርጅት ቤተ ክርስቲያን ከፈትኩ የሚባልበት የድፍረት ኀጢአት በጠራራ ፀሐይ ከሚፈጸምበት ዘመን ደርሰናል፡፡ በተጨማሪም በዚህ ዓይነት ለተቋቋሙ ሁሉ የሚገለገሉበት ታቦት ከየት መጣ? ሜሮን ከየት ተገኘ? የሚሉ ጥያቄዎች ምላሽ የላቸውም፡፡ ”ብዙዎች ይስታሉ” እንደተባለ በድፈረትና በስሕተት መሠረት ላይ የስሕተትና የድፍረትን ግድግዳ ማቆም፣ የስሕተትና የድፍረት ጣሪያንም ማዋቀር እንደ ሕጋዊ ሥራ ከተቆጠረ ሰነባበተ፡፡
  • የጥፋት ርኩሰት በተቀደሰው ስፍራ ቆሞ ስታዩ አንባቢው ያስተውል” /ማቴ 24፣15/ በየአጥቢያው የሚሰማውን ክፉ ወሬ ስናስተውል የዚህ ትንቢት ተፈጻሚነት እንዳገኘ ያረጋግጥልናል፡፡ የተሐድሶ ሴራ፣ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚፈጠሩት ጭቅጭቆች፣ በመነኮሳትና በካህናት የሚነሱ ሐሜቶች፣ ሙሰኝነት፣ዘረኝነት ምን ይነግሩናል?በውጭ አገር በየቦታው አቋቋምን የሚሉት ሰበካ ጉባኤ ሳይሆን ራስ ገዝ የቦርዶቹ አስተዳደር ግፍ ደግሞ በሚገርም ሁኔታ የሚያገለግለው ካህንን የሚያዩት እንደ እግዚአብሔር ካህን ሳይሆን ከአንድ ቅጥር ሠራተኛቸው በታች ነው፡፡ ስለ አስተዳደሩ እንዲያውቅ አይፈልጉም፣ እነሱ ያዘዙትን ብቻ ይሰብካል/ ይናገራል፣ ካህኑም ሲፈልጉ የሚያኖሩት ሲፈልጉ የሚያባርሩት ሆኗል፡፡ ይህን አሠራር ለዘመናት ቤተ ክርስቲያን ከኖረችበት አንጻር ስናየው እጅግ የራቀና አስጸያፊ የሚባል ነው፡፡ ጌታችን ቤተ ክርስቲያንን የመሠረተው በሥልጣነ ክህነት እንድትተዳደር ሲሆን ይህኛው በተቃራኒ የቆመ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ምእመኑን አስተምራ አጥምቃ አሳድጋ እንደገና በተንኮለኞች ሤራ ልጆቹዋን ቀስጠው በስዋ ላይ እንዲያምጹ ማድረግ የጥፋት ርኩሰት መሆኑን ስንቱ ተረድቶት ይሆን?፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ”ማንም ልዩ ትምህርት የሚያስተምር ከጌታችንም ከኢየሱስ ክርስቶስ በሆነው ጤናማ ቃልና እግዚአብሔርን ለመምሰል በሚስማማ ትምህርት የማይጠጋ ቢሆን፥ በትዕቢት ተነፍቶአል አንዳችም አያውቅም፥ ነገር ግን ምርመራን በቃልም መዋጋትን እንደ በሽተኛ ይናፍቃል፤ ከእነዚህም ቅንዓትና ክርክር ስድብም ክፉ አሳብም እርስ በርስ መናደድም ይወጣሉ፥ አእምሮአቸውም በጠፋባቸው እውነትንም በተቀሙ፥ እግዚአብሔርን መምሰል ማትረፊያ የሚሆን በመሰላቸው ሰዎች ይገኛሉ። እንደነዚህ ካሉት ራቅ።” /1 ጢሞ.6፥3-5/ እንዳለ፡፡

ሐ. ሰብአዊ ክብርና የዕድሜ፣ የቅደም ተከተል ትስስርና  ክብር እንዲጠፋ የሚሠሩ ለሚለው ሌላ ብዙ ከማለት ይልቅ ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ ”ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱ ይሆናሉና፥ ገንዘብን የሚወዱ፥ ትምክህተኞች፥ ትዕቢተኞች፥ ተሳዳቢዎች፥ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፥ የማያመሰግኑ፥ ቅድስና የሌላቸው፥ ፍቅር የሌላቸው፥ ዕርቅን የማይሰሙ፥ ሐሜተኞች፥ ራሳቸውን የማይገዙ፥ ጨካኞች፥ መልካም የሆነውን የማይወዱ፥  ከዳተኞች፥ ችኩሎች፥ በትዕቢት የተነፉ” በማለት የዘረዘረው ለርእሰ ጉዳዩ ተስማሚና በቂ ነው፡፡/1ጢሞ.3፥1-3/

ባጠቃላይም የምጽአት ምልክቶች የሚያሳዩት ሁኔታዎች ከመንፈሳዊው እስከ ዓለማዊው፣ ከተማረው እስከ መሀይሙ፣ ከትልቅ እስከ ትንሽ፣ ያላገባው፣ ያገባው፣ መነኩሴው ሳይቀር ሁሉም ሁሉም ባንድ ላይ ከቅድስና ርቀት፣ ከጥፋት ርኩሰት፣ ከመከራ ሕይወት፣ ተቋደሽ መሆናቸውን ነው የሚያሳየው፡፡ ነገር ግን ቅዱሳት መጻሕፍት ተባብረው እንደመሰከሩልን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ድንገት ይመጣል አይዘገይም፡፡ ቅዱስ ዳዊት ”ከክብሩ ውበት ከጽዮን እግዚአብሔር ግልጥ ሆኖ ይመጣል።  አምላካችን ይመጣል ዝምም አይልም፤ እሳት በፊቱ ይቃጠላል፥ በዙሪያውም ብዙ ዐውሎ አለ።” /መዝ.49፥2-3/ ብሎ እንደተናገረው፡፡ ከላይ እንደተዘረዘረው የሰው ልጆች ሁለ ጊዜ ከመንፈሳውያን እስከ ዓለማውያን ድረስ በተጠመዱበት የዓለማዊ ሥራ እንደ ተወጠሩ ነው ያሉት፡፡ ከዚህም በኋላ የበለጠ በሥጋ ሥራ እየተወጠሩ ይሄዳሉ እንጂ መንፈሳዊ ወደ ሆነው የተጋድሎ ሕይወት የሚያዘነብል ይኖራል ለማለት ያስቸግራል፡፡ እንዲያውም በዐመጽ እየበረታ እስከ መቅደስ ድፍረቱን ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይገልጸዋል፤”ማንም በማናቸውም መንገድ አያስታችሁ፤ ክህደቱ አስቀድሞ ሳይመጣና የዓመፅ ሰው እርሱም የጥፋት ልጅ ሳይገለጥ፥ አይደርስምና። እኔ እግዚአብሔር ነኝ ብሎ አዋጅ እየነገረ በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እስኪቀመጥ ድረስ፥ አምላክ ከተባለው ሁሉ፥ ሰዎችም ከሚያመልኩት ሁሉ በላይ ራሱን ከፍ ከፍ የሚያደርገው ተቃዋሚ እርሱ ነው።” /2ተሰ.2፥3-4/ ይለናል፡፡ ነገር ግን ክርስቲያኖች ነን የምንል ሁሉ የጥፋት ትንቢቱ እኛ ላይ እንዳይፈጸም አሁኑኑ ሳናመነታ ንስሐ መግባትና በትንቢት ከተገለጡት ርኩሰቶች ጨክነን መራቅ ይገባናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን፡፡

“መራሔ ፍኖት” መንፈሳዊ ጉዞ ለግቢ ጉባኤያት ተዘጋጀ

መጋቢት 25 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በማኅበረ ቅዱሳን አዲስ አበባ ማእከል አስተባባሪነት በ60 ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሥር ለሚገኙ 5000 /አምስት ሺህ/ ግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች  “መራሔ ፍኖት” /መንገድ መሪ/ የተሰኘ መንፈሳዊ ጉዞ ወደ ሱሉልታ ደብረ ምሕረት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በዕለተ ሆሣዕና ሚያዚያ 20 ቀን 2005 ዓ.ም. መዘጋጀቱን የአዲስ አበባ ማእከል ዋና ጸሐፊ አቶ ካሳሁን ኃይሌ ገለጹ፡፡

የጉዞውን መሠረታዊ ዓላማ አስመልከቶ አቶ ካሳሁን ኃይሌ ሲገልጹ “በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ የሚገኙ ግቢ ጉባኤያት የአንድነት መንፈስ እንዲኖራቸው ለማድረግ፤ እንዲሁም በግቢ ጉባኤያት የማይሳተፉ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆችን በግቢ ጉባኤያት ውስጥ የሚሰጠውን መንፈሳዊ ትምህርት እንዲማሩ ለማነሳሳት ታስቦ የተዘጋጀ መርሐ ግብር ነው” ብለዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ የተለያዩ መንፈሳዊ ዝግጅቶች የሚቀርቡ ሲሆን በዋነኛነት ተማሪዎች በቀለም ትምህርታቸው፤ በመንፈሳዊ ሕይወታቸውና አገልግሎታቸው እንዴት ስኬታማ መሆን ይችላሉ? በሚል ርዕስ ከዚህ በፊት በግቢ ጉባኤት ውስጥ በመማርና በማገልገል ላይ የነበሩ ወንድሞችና እኅቶች ተሞክሯቸውን ያካፍላሉ፡፡ እንዲሁም ተማሪዎች ለሚያቀርቧቸው በቀለም ትምህርታቸውና በመንፈሳዊ ሕይወታቸው የሚያጋጥሟቸውን ፈተናዎችና ተያያዥነት ያላቸው ጥያቄዎቻቸው በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ምላሽ ይሰጥባቸዋል፡፡

በዚህም መሠረት ተማሪዎች ያሏቸውን ጥያቄዎች እስከ ሚያዚያ 10 ቀን 2005 ዓ.ም. ድረስ በኢሜይል አድራሻ Mfenot2005@gmail.com ፤ በስልክ  09 11 89 89 90 / 09 11 36 16 92 መላክ እንደሚችሉ  አቶ ካሳሁን ኃይሌ ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም የቲኬት ሽያጩ በሁሉም ግቢ ጉባኤያት ሥራ አስፈጻሚዎች፤ በማኅበረ ቅዱሳን ንዋያተ ቅድሳት መሸጫ ሱቆችና መዝሙር ቤቶች እንዲሁም በአዲስ አበባ ማእከል ጽሕፈት ቤት ውስጥ ማግኘት እንደሚቻል አስታውቀዋል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የሚተላለፈው ቴሌቪዥን ዝግጅት የሰዓት ለውጥ ተደረገ

መጋቢት 25 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በማኅበረ ቅዱሳን የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ሬድዮና ቴሌቪዥን ዝግጅት ክፍል እየተዘጋጀ በNilesat/EBS የሚቀርበው የ30 ደቂቃ መርሐ ግብር በየሳምንቱ እሑድ ከጧቱ 3፡30-4፡00 ሲተላለፍ መቆየቱ ይታወሳል፡፡ ሆኖም ሰዓቱ በቅዳሴ መጠናቀቂያ ላይ ይተላለፍ ስለነበር ለመከታተል አስቻጋሪ እንደሆነ ለክፍሉ ከሚደርሱት መልእክቶች ለመረዳት ተችሏል፡፡

በዚህም መሠረት ከፊታችን እሑድ ከመጋቢት 28 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ በየሳምንቱ እሑድ ከቀኑ 5፡30-6፡00 ሰዓት የሚተላለፍ መሆኑንና የተላለፉ መርሐ ግብሮችን eotc.tv ላይ እንዲሁም በyoutube ላይ Mahibere kidusan Tv Program ብሎ በመፈለግ ማግኘት እንደሚቻል የሬድዮና ቴሌቪዥን ክፍሉ አስተባባሪ የሆኑት ዲ/ን ሄኖክ ኀይሌ ገልጸዋል፡፡

“ተማሪ በሞተ በሰባት ዓመቱ ተምሮ ይመጣል ትላለች እናቱ”

ይህ ሥነ ቃል ከሞቀ ከደመቀ ቤቱ የላመ የጣመን ትቶ የነገው ካህን፣ መምህር፣ ሊቅ የመሆን ህልሙን ለማሳካት ቃለ እግዚአብሔር ፍለጋ የተሰደደው ተማሪ በረሃብ፣ በእርዛት፣ በሽታን መቋቋም ተስኖት ወደ ቤቱ አለመመለሱን ፤ወጥቶ መቅረቱን የተማሪውን መከራ ለማዘከር በሰፊው በማኅበረሰቡ ዘንድ የተነገረ ቃል ነው።



ተማሪው በተማሪ ቤት ምንም ዓይነት የምግብ፣ የመጠለያ፣ የአልባሳት የመሳሰለውን ድጋፍ አያገኝም።

ጥሬ ቆርጥሞ፣ ኮቸሮ አኮችሮ በአንድ እራፊ ጨርቅ ተጠቅልሎ፤ ማደሪያ ሳያምረው በሳር ጎጆ ተጠግቶ የመማርያ አዳራሽ ሳይኖረው በዛፍ ጥላ ሥር ትምህርቱን በትጋት በንቃት ይከታተላል።

ተማሪው ከምግብ እጥረት የተነሳ ሰውነቱ ቀጥኖና አጥሮ በዳፍንት በሽታ በማታ ማየት እየተሳነው የትምህርት ቤቱን ኑሮ በመከራ ይገፋል።

ተማሪው በቂ ንፁሕ የመጠጥ ውኃ ፣ የመጸዳጃ ቤት ካለማግኘቱ የተነሣ ለልዩ ልዩ ተላላፊ በሽታዎች ይጋለጣል። በዚህም ሰውነቱ በምግብ እጥረት የተጎዳ በመሆኑ በሽታን መቋቋም ስለማይችል ለሞት በቀላሉ ይጋለጣል። 

ብዙዎችም ከትምህርት ቤት ያተረፉት በሽታ በዕድሜአቸው ሙሉ በአገልግሎታቸው ሲያውካቸው ይገኛል። 

ዛሬ በዓለም ብሎም በኢትዮጵያ በግልና በአካባቢ ንጽሕና ጉድለት የሚመጡ በሽታዎችን ለመቀነስና የተሻለ ዓለምን ለመፍጠር የሚረባረቡ አካላት ቢኖሩም የአብነት ተማሪዎች ግን ዛሬም የችግሩ ተጠቂዎች እንደሆኑ ይገኛሉ።

በተማሪ ቤት ጎልቶ የሚታየውን ችግር በተለየም ሰማንያ በመቶ የሚሆነው የበሽታ ዓይነት ከግልና ከአካባቢ ንጽሕና ጉድለት፤ ከንጹሕ ውኃ መጠጥ አለማግኘት፤ ከምግብ እጥረት ጋር ተደምሮ የሚመጣ ነው። ማኅበረ ቅዱሳን ይህንን የጤና እክል ለመታደግ 12 ሺህ ተማሪዎችን ተጠቃሚ ሚያደርግ መርሐ ግብር ነድፎ የሁሉንም ተሳትፎ እየጋበዘ ይገኛል። የመርሐግብሩ ሥያሜ ተማሪ በሞተ……..የሚል መሪ ቃል እዲኖረው ተደርጓል። ምክንያቱም እውቀትን ለመሻት መራራውን ሞት የተጎነጩ ሊቃውንትን ለማዘከርና አሁን ያሉትን ተማሪዎች ሕይወት ለመታድግ ገላጭ ቃል ሆኖ በመገኘቱ ነው።

• የመርሐ ግብሩ አስፈላጊነት

  • የግልና የአካባቢን ንጽሕና መጠበቅ አምላካዊ ትዕዛዝ መሆኑን ለማስገንዘብና ተፈጻሚ ለማድረግ (ኦሪት ዘዳግም 23፣13) 
  • በአብነት ትምህርት ቤት በግልና በጋራ የንጽሕና አጠባበቅ ችግር የሚፈጠረውን የሕመምና የሞት አደጋ ለመቀነስ 
  • ተማሪዎቹ ትምህርታቸው ላይ እንዲያተኩሩ በማድረግ ምቹ የሆነ የመማርና የማስተማር ሁኔታ መፍጠር
  • በአብነት ትምህርት ቤቶች ዙሪያ ያለውን ዝቅተኛ የጤናና የንጹሕ መጠጥ ውኃ ተደራሽነት ትኩረት እንዲያገኝ ማድረግ 
  • የአብነት ተማሪው ስለጤና አጠባበቅ ምንነት ተረድቶ እርሱም ለኅበረተሰቡ እውቀቱን እንዲያስፋፋ ለማገዝ 

• ከእርሶ ምን ይጠበቃል

  • ፕሮግራሙ እውን እንዲሆን የሙያ የገንዘብና የቁሳቁስ ድጋፍ እንዲያደርጉ ተጋብዘዋል።
  • ፕሮግራሙን ተግባራዊ ለማድረግ 
  • 200 ግራም የሆነ 12,000 የልብስ ሳሙና 
  • 10 ባለ 3,000 ሊትር የውኃ ማጠራቀሚያ የፕላስቲክ ታንከር 
  • የውኃ ማከሚያ ኬሚካሎች
  • ለውኃ መጠጫ፣ ለማብሰያ፣ ለመመገቢያ የሚሆኑ የተለያዩ መጠን ያላቸው ቁሳቁስ
  • ለገላና ለልብስ ማጠቢያ የሚያገለግሉ ቁሳቁሶችን 
  • የግል ንጽሕና መጠበቂያ የሚያገለግሉ (መርፌ፣ ምላጭ)
  • በ10 ትምህርት ቤቶች የጋራ መጸዳጃ ቤት ሥራ እንዲሁም 
  • የጤና አጠባበቅ ሥልጠና 

የድጋፍ ማሰባሰቢያ 
ጊዜ፦ ከመጋቢት 21 እስከ ሚያዝያ 11 ቀን 2005 ዓም 
ቦታ፦ በማኅበረ ቅዱሳን ሕንፃ
ለበለጠ መረጃ ስልክ፦ 0911 751529 / 0913 102621

ምኲራብ

መጋቢት 18ቀን 2005 ዓ.ም.

በዳዊትደስታ

የዐብይ ጾም ሦስተኛው ሰንበት ምኲራብ ይባላል፡፡ ይህም ምኲራብ ከክርስቶስ ልደት በፊት እግዚአብሔርን ለማመስገን የእግዚአብሔር አማኞች ለጸሎት የሚሰባሰቡበት ቤት ስም ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብዙ ጊዜ ወደ ምኲራባቸው በመግባት ሰዎችን አስተምሯል፡፡ ሰዎች የእግዚአብሔር መመስገኛ የሆነውን ምኲራብ ገበያ አድርገውት ስላገኘም “ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል ተብሎ ተጽፏል እናንተ ግን የሌባና የቀማኛ ዋሻ አደረጋችሁት” /ማቴ.21፥12-13/ በማለት ገሥጾ በዚያ የሚሸጡትንና የሚለውጡትን ሁሉ በትኗቸዋል፡፡ ይህንን ምክንያት በማድረግ ሦስተኛው የዐብይ ጾም ሳምንት ምኩራብ በሚል ሰያሜ ይጠራል፡፡ በምኲራብ ገብቶ እንዳስተማረ የሚያሳስብ ዕለት የሚነበበው የወንጌል ክፍልም ዮሐ.12 እስከ ፍጻሜው ያለው ነው፡፡

ቅድመታሪክ
ስለምኲራብ /ሲናጎግ/
ምኲራብ ማለት የአይሁድ የጸሎት ቤት ማለት ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን የአይሁድ አምልኮ በኢየሩሳሌም በነበረው ቤተ መቅደስና እንደ ሥርዓቱ የተመሠረተ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ በዚሁ መቀጠል አልቻለም፡፡ ምክንያቱም ሃይማኖት የሚያጠፋ ቤተ መቅደስ የሚያፈርስና የሚያቃጥል አረማዊ ንጉሥ ተነሣ፡፡ 

አረማዊው ንጉሥ ናቡከደነጾር ቤተ መቅደሱን አፍርሶ ሕዝበ እስራኤልን ወደ ባቢሎን አፍልሶ ስለነበር ከዚያን ጊዜ ጀምሮ አይሁዶች በሚገኙባቸው ሥፍራዎች ሁሉ ለጸሎትና በማኅበር ለማመስገን ቤቶችን ሊሠሩ እንደጀመሩ ይነገርላቸዋል ሕዝ.11፥16፡፡

በምኩራቦችም የብሉይ ኪዳን ማምለኪያ አምልኮታቸውን ይፈጽሙ ስለነበረና ምኲራቦቻቸውም ብዙ ስለ ነበሩ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋዌ ምስጢር ተገልጾ በተዋሕዶ ከብሮ ወደ ዓለም በመጣ ጊዜም ተከታዮቹን ሐዋርያትን እየላከ በምኲራቦቻቸው ያስተምራቸው ነበር፡፡ /ማቴ.4፥23፣ ሐዋ.6፥9፣ 13፥5፣ 14፥1፣ 17፥16-18/፡፡ በብሉይ ኪዳን ታሪክና ለአይሁዳውያን ሕግ አሥር የሚያህሉ ወንዶች በአንድ ማኅበር ቢገኙ ምኲራብ ለመሥራት ይፈቀድላቸዋል፡፡ እንዲሁም በሚያንጹት ምኲራብ ውስጥ ሕግና ነቢያት የተጻፈባቸው የብር ጥቅልሎች /Scroll/ በአንድ ሳጥን ወይም ማኅደር ውስጥ ይቀመጣሉ፡፡ /ፅላትበታቦት፣ ዳዊት በማኅደር እንደሚቀመጥ/ ማለትነው፡፡ ምኲራብ እንደ ደብተራ ኦሪት ሁሉ አምልኮተ እግዚአብሔር የሚፈጽምበት ሕንፃ ነው፡፡