ማኅበረ መነኮሳቱ ድጋፍ እንዲደረግላቸው ጠየቁ

ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሐምሌ ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በምዕራብ ጐጃም ሀገረ ስብከት በሜጫ ወረዳ ቤተ ክህነት በጉታ ቀበሌ ልዩ ስሙ ናዳ በሚባል ቦታ የሚገኘው የፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም ገዳም መነኮሳትና አብነት ተማሪዎች ሰኔ ፳፪ እና ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በጣለው ከባድ ዝናም እና በረዶ ምክንያት ያለሙት ፍራፍሬ ሙሉ በሙሉ በመውደሙ፣ መኖርያ ቤታቸውም በመፍረሱ ድጋፍ እንዲደረግላቸው ጠየቁ፡፡

ምንኵስናን ከሊቅነት፣ አባትነትን ከሥራ ጋር አስተባብረው የያዙት የገዳሙ ዋና አስተዳዳሪ፣ የትርጓሜ መጻሕፍትና የቅኔ መምህሩ ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ በቦታው ተገኝተን ቃለ መጠይቅ ባደረግንላቸው ወቅት እንደ ገለጹልን በገዳሙ አካባቢ የሚገኘውን በጎርፍ የተሸረሸረ ሸለቆ በመከባከብ በ፲፱፻፹ ዓ.ም የተጀመረው የልማት ሥራ ገዳሙን በፌዴራል ሁለተኛ፤ በክልል ደግሞ አንደኛ ደረጃ እንዲያገኝና የክብር ሜዳልያ እንዲሸለም አድርጎታል፡፡

ዳሩ ግን ይህ የልማት ውጤት በበረዶው ምክንያት ከጥቅም ውጪ ኾኗል፡፡ ፍራፍሬውና ደኑም ተጨፍጭፏል፡፡ የጠበል መጠመቂያ ቦታዎች ተናውጠዋል፡፡ ንቦችም ከቀፎዎቻቸው ወጥተው ተሰደዋል፡፡ የመነኮሳቱና አብነት ተማሪዎች መኖርያ ቤቶችም ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡ በአጠቃላይ ከሰባ ሄክታር በላይ የሚገመት ሰብል በበረዶው ናዳ መውደሙን ከገዳሙ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ ‹‹ወደዚህ ገዳም ከመጣሁበት ጊዜ ጀምሮ እንደዚህ ዓይነት ክሥተት ደርሶ አይቼ አላውቅም›› ይላሉ ዋና አስተዳዳሪው የጉዳቱን ከፍተኛነት ሲገልጹ፡፡

በበረዶው ምክንያት የረገፈው ፍራፍሬ በከፊል

ከቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል በደረሰን መረጃ ማኅበረ ቅዱሳን ከገዳሙ ድረስ ልዑካንን በመላክ ለጊዜው የዘር መግዣ ይኾን ዘንድ የሃያ ሺሕ ብር የገንዘብ ድጋፍ አድርጓል፡፡ ማኅበሩ ካሁን በፊት አንድ ትራክተር ገዝቶ በስጦታ ለገዳሙ ያበረከተ ሲኾን፣ ለወደፊትም ገዳሙን በቋሚነት ለመደገፍ አቅዷል፡፡

በመጨረሻም ላደረገው የገንዘብ ድጋፍ ማኅበረ ቅዱሳንን፤ በጉልበት ሥራ በመራዳታቸው ደግሞ የአካባቢውን ሕዝበ ክርስቲያን የገዳሙ ዋና አስተዳዳሪ አመስግነው፣ ሌሎች በጎ አድራጊ ምእመናንም ቀለብ በመስጠት፣ ዘር በመግዛት፣ ልብስ በመለገስ፤ ከፍ ሲል ደግሞ መኖርያ ቤት በማደስ በአጠቃላይ በሚቻላቸው አቅም ዅሉ ድጋፍ እንዲያደርጉ ዋና አስተዳዳሪው በገዳሙ ስም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

በረዶው በአትክልቱ ላይ ያደረሰው ጉዳት በከፊል

የፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም ገዳም ከ፲፱፻፸፱ ዓ.ም ጀምሮ እስካሁን ድረስ የትርጓሜ መጻሕፍት እና የቅኔ ትምህርት የሚሰጥበት ጥንታዊ ገዳም ነው፡፡ ከዚህም ባሻገር ገዳሙ በልማት ሥራ የታወቀ ልዩ ቦታ ነው፡፡ ኾኖም በዘንድሮው ዓመት በወርኃ ሰኔ በአካባቢው በጣለው ከባድ በረዶ የተነሣ ፍራፍሬውና ደኑ በመውደሙ የገዳሙ መነኮሳትና የአብነት ተማሪዎች ኑሯቸው አደጋ ላይ ነው፡፡

ዝግጅት ክፍላችንም የገዳሙን መነኮሳት ከስደት፣ ጉባኤ ቤቱንም ከመዘጋት ለመታደግ፤ እንደዚሁም የልማት ቦታውን ወደ ጥንት ይዘቱ ለመመለስ ይቻል ዘንድ በተቻላችሁ አቅም ዅሉ ድጋፍ በማድረግ ከበረከቱ እንድትሳተፉ ይኹን ሲል መንፈሳዊ መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

ማሳሰቢያ

ገዳሙን በገንዘብ ለመደገፍ የምትፈልጉ ምእመናን በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መርዓዊ ቅርንጫፍ ሒሳብ ቍጥር፡- 10000 6261 1786 ገቢ ማድረግ የምትችሉ መኾኑን የገዳሙ ጽ/ቤት ያሳስባል፡፡ ተጨማሪ መረጃ ለማግኘትም በስልክ ቍጥር፡- 09 18 70 81 36 በመደወል የገዳሙን ዋና አስተዳዳሪ ማነጋገር ይቻላል፡፡

ኤጲስ ቆጶሳቱ ሳይለግሙ ምእመናንን እንዲያገለግሉ ፓትርያርኩ አሳሰቡ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሐምሌ ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም  

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የኤጲስ ቆጶሳት ሥርዓተ ሲመት በተፈጸመበት ዕለት በሰጡት ቃለ ምዕዳን ለዚህ በዓለ ሢመት ያደረሳቸውን ልዑል እግዚአብሔርን አመስግነዋል፡፡ ለኤጲስ ቆጶሳቱም የሚከተለውን አባታዊ ምክር ለግሰዋል፤

‹‹እግዚአብሔር የሰጣችሁን ሕዝብ በቀንም በሌሊትም ከእርሱ ሳትለዩ፣ በዅለንተናዊ ሕይወታችሁ ባለ አቅማችሁ ዅሉ ሳትለግሙ አገልግሉት፡፡ ከስደት፣ ከእንግልት ተገላግሎ የልማት ኃይል በመኾን አገሩን እንዲገነባ፤ ሃይማኖቱንና ባህሉን እንዲጠብቅ ያለመታከት አስተምሩት፡፡ ከመንፈሳዊ መሠረተ ትምህርት ጀምሮ እስከ ኤጲስቆጶስነት ድረስ እየመገበና እየተንከባከበ ለታላቅ ክብር ያበቃችሁን ሕዝብ የልቡን ሃይማኖታዊ ትርታ እያዳመጣችሁ በወቅቱ እየደረሳችሁ አስተምሩት፤ አጽናኑት፡፡ ልጆቹን በተኩላዎች ከመነጠቅ አድኑለት፡፡ ወጣቱ ትውልድ ከሐሺሽ፣ ከአደንዛዥ ዕፅ፣ ከሱሰኝነት፣ ከሥራ ፈትነትና ከመጤ ጎጂ ባህል እንዲላቀቅ አድርጉ፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝበ ክርስቲያን በአሁኑ ጊዜ ከሃይማኖት አባቶች የሚፈልገው ይህንኑ ነው፡፡››

የጸሎተ አስኬማ ሥርዓቱ በከፊል

ቅዱስነታቸው በተጨማሪም በየሀገረ ስብከቱ በየመንበራቸው ተገኝተው ከሕዝቡ ጎን ሳይለዩ ተግተው የሚሠሩ፤ ዅሉንም ወገን በእኩል ዓይን የሚያዩና የሚያስተናግዱ፤ በሕዝቡ መካከል ሰላምን የሚሰብኩ፤ ከማናቸውም ርዕዮተ ዓለም ደጋፊነት የተለዩና ከጣልቃ ገብነት የጸዱ፤ ከዅሉም በላይ ለአንዲት ሉዓላዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነት መከበር በጽናት የቆሙ አባቶችን አገራችን ኢትዮጵያ እንደምትሻ ገልጸው፣ ‹‹ዓለሙ በውስጡ ያለና የሌለ ኃይሉን አግበስብሶ እንደሚታገላችሁ አትርሱ፤ ነገር ግን የድል አድራጊው ጌታ ሠራዊት ናችሁና የመጨሻው ድል የእናንተ መኾኑን አትጠራጠሩ›› በማለት ኤጲስ ቆጶሳቱ በምንም ዓይነት ፈተና ሳይበገሩ ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተሰጣቸውን ሓላፊነት በአግባቡ እንዲወጡ መክረዋል፡፡

የጸሎተ አስኬማ ሥርዓቱ በከፊል

ሹመት ማለት የሥራ መገልገያ መሣርያ እንጂ የግል መገልገያ እንዳልኾነ፤ አገልግሎቱም መውጣት መውረድን፣ መንገላታትን፣ ድካምን ከዚያም አልፎ መሥዋዕትነትን እንደሚጠይቅ ያስታወሱት ፓትርያርኩ፣ ‹‹በዚህ ሐዋርያዊ ጉዞ ብዙ መሰናክሎች ሊገጥሟችሁ ቢችሉም ዅሉም ችግሮች ከሞት በታች እንጂ ከሞት በላይ አይደሉምና ከሐዋርያዊ ተልእኳችሁ የሚገታችሁ ምንም ነገር አይኖርም፡፡ ምክንያቱም የገባችሁት ቃል ኪዳን እስከ ሞት ድረስ ለመዳፈር ነውና›› ሲሉ እስከ ሞት ድረስ በመታመን የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ ተልእኮ እንዲያስፋፉ ለኤጲስ ቆጶሳቱ መልእክታቸውን አስተላለፈዋል፡፡

የኤጲስ ቆጶሳቱ ሥርዓተ ሲመት አፈጻጸም በከፊል

ቅዱስነታቸው፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከአኃት አብያተ ክርስቲያናት ጋር ስትነጻጸር በምእመናን ብዛት፣ በሃይማኖት ጽናት፣ በሐዋርያዊ ትውፊት፣ በአበው ቀኖና፣ በሃይማኖታዊ ባህልና በሥርዓተ አምልኮ አፈጻጸም ቀዳሚውን ሥፍራ እንደምትይዝ አውስተው፣ ቤተ ክርስቲያን በአበው ሐዋርያዊ ተጋድሎ ጠብቃ ያቆየችውን ይህን ሀብተ መንፈስ ቅዱስ ለመጭው ትውልድ ለማስተላለፍ ብቃትና ተነሣሽነት ያላቸውን ኤጲስ ቆጶሳት መሾም ተቀዳሚ ተግባሯ እንደ ኾነ፤ የኤጲስ ቆጶሳት ሹመትም ሐዋርያዊ ተልእኮውን ለማስፋፋት ከፍተኛ ሚና እንዳለው አስረድተዋል፡፡

ሥርዓተ ሲመት የተፈጸመላቸው ኤጲስ ቆጶሳት በከፊል

አገራችን ኢትዮጵያ በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅኝት የተቀረፀ፤ ለሃይማኖት፣ ለሥነ ምግባር፣ ለፍትሕ፣ ለልማትና ለአንድነት የተመቸ ሕዝብ እንዳላት፤ ይህን የተቀደሰ ባህልና ሥነ ምግባር ለማስቀጠልም ከቤተ ክርስቲያን አባቶች ብዙ እንደሚጠበቅ የገለጹት ቅዱስ ፓትርያርኩ ‹‹በተለይም ብፁዓን አበው ሊነ ጳጳሳት እና ኤጲስ ቆጶሳት ኢትዮጵያውያንን በአባትነት መንፈስ በማቅረብ ዅሉም በሰላም፣ በወንድማማችነት፣ በመከባበር፣ በመተማመንና በመቻቻል አብረው እንዲኖ፤ እንደዚሁም ትውልዱ እንደ አባቶቹ ደማቅ ታሪክ ሠርቶ እንዲያልፍ ያልተቆጠበ ጥረት ማድረግ ይኖርባችኋል›› ብለዋል፡፡

ሥርዓተ ሲመት የተፈጸመላቸው ኤጲስ ቆጶሳት በከፊል

በመቀጠልም ቤተ ክርስቲያናችን በሃይማኖት አስተምህሮ እና ይዘት፣ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን፣ በሐዋርያዊ ትውፊት፣ በሥርዓተ አምልኮ አፈጻጸም እና በቅዱስ ባህል ምሥረታ እንከን የለሽ ብትኾንም በአስተዳደር፣ በፋይናንስና ንብረት አያያዝ፣ በምእመናን ክብካቤና በሐዋርያዊ ተልእኮ ክንውን፣ በእናቶችና በወጣቶች አያያዝ ከዘመኑ ጋር መራመድ አለማቻሏ የወቅቱ የቤተ ክርስቲያናችን ተግዳሮት መኾኑን ቅዱስነታቸው ጠቅሰው፣ ይህን ተግዳሮት ከሥር መሠረቱ ነቅሎ በመጣል ወደሚፈለገው መልካም አስተዳደር ለመሸጋገር የአሁኖቹ ሥዩማን ኤጲስ ቆጶሳት ከቀደሙት ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በመቀናጀት ጉልህ ሚና እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ

እንደ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ማብራርያ በአሁኑ ጊዜ ሃይማኖት እና ሥነ ምግባር እጅግ ትኩረት የሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች ከመኾናቸው አኳያ፣ የዘመኑ ትውልድ በሃይማኖት የጸና፤ በሥነ ምግባር የቀና፤ ለአገር እና ለወገን ክብር የቆመ እንዲኾን የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮን ማስፋፋት እና የአባቶች አርአያነት ያለው ሕይወት መኖር ቍልፍ መሣርያ ነው፡፡

በተመሳሳይ መልኩ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ እንደዚሁም ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና በክልል ትግራይ ደቡባዊ ማይጨው ዞን፣ ደቡብ ምሥራቅና ምሥራቃዊ አዲግራት አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በዕለቱ ባስተላለፉት መልእክት ለኤጲስ ቆጶስነት መመረጥ የእግዚአብሔር ጥሪ መኾኑን በማስረዳት ኤጲስ ቆጶሳቱ አባታዊ ሓላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲፈጽሙ፤ ሕዝበ ክርስቲያኑም ለአባቶች በመታዘዝ ኦርቶዶክሳዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ አስተምረዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተመረጡት ዐሥራ አምስቱ ኤጲስ ቆጶሳት ቅዱስ ፓትርያርኩ እና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት ሐምሌ ፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ገዳም ጸሎተ አስኬማ ከተደረሰላቸው በኋላ በነጋታው ሐምሌ ፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በቅዱስ ፓትርያርኩ ቡራኬ ሥርዓተ ሢመት ተፈጽሞላቸዋል፡፡

ኤጲስ ቆጶሳቱ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ በመጠበቅና በማስጠበቅ የተሰጣቸውን አባታዊ አደራ በሓላፊነት እንደሚወጡ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትና በሕዝበ ክርስቲያኑ ፊት ሃይማኖታዊ አቋማቸውን ገልጸዋል፡፡

በአቋማቸውም በእግዚአብሔር ዘለዓለማዊ አምላክነት እንደሚያምኑ፤ በኒቅያ፣ ቍስጥንጥንያ እና ኤፌሶን በተወሰነው ውሳኔ መሠረት የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ጠብቀው እንደሚያስጠብቁና እንደሚያስምሩ፤ በሥላሴ አንድነትና ሦስትነት፣ በእግዚአብሔር ወልድ የባሕርይ አምላክነት፣ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክነት፣ ዘለዓለማዊ ድንግልናዋ እና አማላጅነቷ፤ እንደዚሁም በቅዱሳን መላእክት፣ ነቢያት፣ ሐዋርያት፣ ሰማዕታት እና ጻድቃን አማላጅነት አምነው እንደሚያስተምሩ፤ ይህን ትምህርት የሚቃወሙትንና ተሐድሶ ነን የሚሉ መናፍቃንን እንደሚያወግዙም ቃል ገብተዋል፡፡

ኤጲስ ቆጶሳቱ ቃለ መሐላ ሲፈጽሙ

ምሥጢረ ቍርባንን በተመለከተም “ካህኑ ሲባርከው ኅብስቱ ተለውጦ አማናዊ ሥጋ ወልደ እግዚአብሔር፣ ወይኑም ተለውጦ አማናዊ ደመ ወልደ እግዚአብሔር መኾኑን፤ ጥምቀት አንዲት መኾኗን እናምናለን፤ በቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር ያሉ ምእመናን በተዋሕዶ ሃይማኖት ጸንተው፣ ቀኖናዊ ሥርዓቷን አክብረውና ጠብቀው እንዲኖሩ ተግተን እናስተምራለን፡፡ ይህን ዅሉ ለማድረግ እግዚአብሔር ይረዳን ዘንድ እንማጸናለን፤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጉባኤ ፊት ቃል ኪዳን እንገባለን” የሚል ቃለ መሐላ ፈጽመዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በአፋን ኦሮሞ ያሳተማቸው መጻሕፍት በከፊል

ማኅበረ ቅዱሳን በአፋን ኦሮሞ ካሳተማቸው መጻሕፍት መካከል ጥቂቶቹ የሚከተሉት ናቸው፤

የአዳማ ማእከል በአፋን ኦሮሞ ሥልጠና እየሰጠ ነው

በዝግጅት ክፍሉ

ሐምሌ ፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም  

በማኅበረ ቅዱሳን የአዳማ ማእከል ከምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ልዩ ልዩ ወረዳዎች ለተውጣጡ ሠላሳ ስድስት ሰባክያነ ወንጌል በአፋን ኦሮሞ የስብከተ ወንጌል እና የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና በአዳማ ከተማ እየሰጠ ነው፡፡

ሠልጣኞቹ በሀገረ ስብከቱ፣ በወረዳ ቤተ ክህነቶቹና በአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናቱ ፈቃድ የተመረጡ፣ በክርስቲያናዊ ምግባራቸው የተመሰከረላቸው የቤተ ክርስቲያን ልጆች እንደ ኾኑ፤ የቤተ ክርስቲያን አባልነት፣ ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባርን መላበስ፣ በሰንበት ት/ቤቶች ተሳትፎ ማድረግ፣ ቢቻል መዓርገ ክህነት መያዝ በተጨማሪም አማርኛ ቋንቋ እና አፋን ኦሮሞ መናገር መቻል በምልመላ መሥፈርቱ እንደ ተካተቱ የአዳማ ማእከል ለዝግጅት ክፍላችን አስታውቋል፡፡ ከሠላሳ ስድስቱ ሠልጣኞቹ መካከል አንዱ ቄስ፤ ሰባቱ ዲያቆናት መኾናቸውንም ለመረዳት ችለናል፡፡

በአቀባበል መርሐ ግብሩ የተገኙ እንግዶች እና ሠልጣኞች በከፊል

እንደ ማእከሉ ዘገባ ሥልጠናው የሚሰጠው ለዐሥራ አምስት ቀናት ቀንም ሌሊትም ሲኾን፣ መሠረተ እምነት፣ ነገረ ቅዱሳን፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ የስብከት ዘዴ፣ ኦርቶዶክሳዊ መዝሙር፣ ወቅታዊ ጉዳዮች፣ የጊዜ አጠቃቀም፣ መንፈሳዊ አገልግሎት፣ መሪነትና ውሳኔ አሰጣጥ እንደዚሁም ምክረ አበው ለሠልጣኞቹ የሚሰጡ የትምህርት ክፍሎች፤ አሠልጣኞች ደግሞ በልዩ ልዩ የአገልግሎት ዘርፍ የሚገኙ የቤተ ክርስቲያን መምህራን  ናቸው፡፡

መጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ ቸርነት

ለሠልጣኞቹ ሰኔ ፳፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም የአቀባበል ሥርዓት በተደረገላቸው ጊዜ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ መጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ ቸርነት ተገኝተው ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል፡፡

በትምህርታቸውም መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት ያደላቸውን በልዩ ልዩ ቋንቋ የመናገር ጸጋ ዋቢ በማድረግ ማእከሉ በአፋን ኦሮሞ የስብከተ ወንጌል ሥልጠና መስጠቱ በየገጠሩ በቋንቋ ችግር ምክንያት ወንጌል ባልተዳረሰባቸው አካባቢዎች ሰፊ አገልግሎት ለመስጠት ከፍተኛ አስተዋጽዖ እንዳለው አስረድተዋል፡፡

ሀገረ ስብከቱ ሊደርስ ያልቻለባቸውን የአገልግሎት ክፍሎች በማሟላት የአዳማ ማእከል ለሚሰጠው ዘርፈ ብዙ ተልእኮም ማኅበረ ቅዱሳንን አመስግነዋል፡፡

ሀገረ ስብከታቸው ለወደፊት በአፋን ኦሮሞ የስብከተ ወንጌል ሥልጠና ለመስጠት ማቀዱን የገለጹት ሥራ አስኪያጁ የማእከሉን አገልግሎት እንደሚደግፉም ቃል ገብተዋል፡፡

በትምህርታቸው ማጠቃለያም ‹‹የሚጠብቃችሁ ሕዝብ አለ፡፡ ሥልጠናውን ፈጽማችሁ ድረሱላቸው፡፡ ጕዟችሁ የወንጌል ጉዞ ነው፡፡ እንደ ሐዋርያት ለማታውቁት ሕዝብ ሳይኾን ለወገኖቻችሁ ወንጌልን የመስበክ አደራ አለባችሁ›› በማለት ሠልጣኞቹ የሚጠበቅባቸውን ተልእኮ በትጋት እንዲወጡ መክረዋል፡፡

ሊቀ ካህናት ነጋሽ ሀብተ ወልድ

የሀገረ ስብከቱ ሰበካ ጉባኤ ማደራጃ ክፍል ሓላፊ ሊቀ ካህናት ነጋሽ ሀብተ ወልድ በበኩላቸው ክርስትና የዅሉም ሕዝብ እንጂ የተወሰኑ ሰዎች፤ ቋንቋም መግባብያ እንጂ መለያያ እንዳልኾነ ጠቅሰው ወንጌልን በየቋንቋው ለማዳረስ ማእከሉ የሚያደርገውን ጥረት አጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበዋል፡፡

ለሠልጣኞቹም ‹‹ለዚህ ዕድል በመመረጣችሁ እንኳን ደስ ያላችሁ! ቃለ ወንጌሉን ያልተማሩ፣ በነጣቂዎች የተወሰዱ በየገጠሩ የሚኖሩ ወገኖቻችሁን ታገለግሉ ዘንድ ተመርጣችኋልና ለእነዚህ ወገኖች ልትደርሱላቸው ይገባል›› በማለት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በዕለቱ ከተገኙ በጎ አድራጊ ምእመናን መካከል አቶ ለማ ተፈሪ፣ አቶ ነገሠ ይልማ፣ እና አቶ ተስፋዬ መንገሻ የተባሉ የከተማው ነዋሪዎች ይህን ሥልጠና በመስጠቱ ማእከሉን አድንቀው በአፋን ኦሮሞ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት መሰጠቱ በየቋንቋው ወንጌልን በማስተማር ያመኑትን ለማጽናት፣ በመናፍቃን የተወሰዱትን ለመመለስ እና አዳዲስ አማኞችን ወደ ቤተ ክርስቲያን ለማምጣት የሚኖረውን ጠቀሜታ አብራርተዋል፡፡

የአዳማ ማእከል ሰብሳቢ መምህር ጌትነት ዐሥራት ደግሞ ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያን ተልእኮ የኾነውን የስብከተ ወንጌል አገልግሎት የማሳካት ሓላፊነት እንዳለበት አስታውሰው በመናፍቃን ከሚፈተኑ አካባቢዎች መካከል ኦሮምያ ክልል አንዱ በመኾኑ ምእመናንን በሃይማኖታቸው ለማጽናትና ከነጣቂዎች ለመጠበቅ፤ ያላመኑትንም ለማሳመን ይቻል ዘንድ ማእከሉ በአፋን ኦሮሞ የስብከተ ወንጌል እና የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና ለመስጠት መነሣሣቱን አስታውቀዋል፡፡

መምህር ጌትነት ዐሥራት

በመጨረሻም ለሥልጠናው መሳካት እገዛ ያደረገው የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከትን፤ ለሕክምና፣ ለምግብ፣ ለመጻሕፍትና ለትምህርት መሣርያዎች የሚያስፈልገውን ወጪ በማገዝ ሥልጠናውን የደገፉ በጎ አድራጊ ምእመናንን ሰብሳቢው በማኅበረ ቅዱሳን ስም አመስግነዋል፡፡

ከማእከሉ የደረሰን መረጃ እንደሚያመለክተው የአዳማ ማእከል በአፋን ኦሮሞ የስብከተ ወንጌል ሥልጠና ሲሰጥ አሁን ሁለተኛው ነው፡፡

በመጀመርያው ዙር የሠለጠኑ ሃያ ዘጠኝ ሰባክያነ ወንጌል በክልሉ ገጠራማ ሥፍራዎች ለሚኖሩ ምእመናን ትምህርተ ሃይማኖትን ከማዳረሳቸው ባሻገር ሞጆ አካባቢ አምስት አዳዲስ አማኞችን በማስተማር የሥላሴ ልጅነትን እንዲያገኙ አድርገዋል፡፡

የሁለተኛው ዙር ሠልጣኞችም ተመርቀው በየቦታው ሲሰማሩ ከዚህ የበለጠ የአገልግሎት ፍሬ ያስመዘግባሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ሠልጣኞቹም ሐምሌ ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ይመረቃሉ፡፡

ከዚህም ሌላ በአዳማ ማእከል የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል አስተባባሪነት በዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም እና የካህናት ማሠልጠኛ ተቋም ለሚገኙ መነኮሳትና አብነት ተማሪዎች ሰኔ ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በነጻ የሕክምና አገልግሎት መሰጠቱን፣ የመድኃኒት ድጋፍም መደረጉን ማእከሉ ያደረሰን ዘገባ ያመላክታል፡፡

ሐኪሞቹ የሕክምና አገልግሎት ሲሰጡ (በከፊል)

ከማእከሉ አባላት እና ከአዳማ ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ ግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የተውጣጡ ሠላሳ አራት ሜዲካል ዶክተሮች በተሳተፉበት በዚህ አገልግሎት ለዐሥራ ስድስት አባቶች መነኮሳት፤ ለስድስት እናቶች መነኮሳይያት እና ለሰባ አምስት አብነት ተማሪዎች የሕክምና ርዳታ፤ የላቦራቶሪ ምርመራ እና የመድኃኒት ድጋፍ ተደርጓል፡፡ በተጨማሪም የግል እና የአካባቢ ጤና አጠባበቅ ትምህርት በጤና ባለሙያዎች ተሰጥቷል፡፡

በመርሐ ግብሩ ማጠቃለያም የሕክምና ባለሙያዎችን በማስተባበር ማእከሉ ላደረገላቸው ክብካቤና ድጋፍ የሕክምና አገልግሎት የተሰጣቸው የገዳሙ አባቶች እና እናቶች ማኅበረ ቅዱሳንን በእግዚአብሔር ስም አመስግነዋል፡፡

ለተተኪ መምህራን ሥልጠና መስጠቱን የአሜሪካ ማእከል አስታወቀ

ሠልጣኞቹ ከአሠልጣኝ መምህራን እና ከኦሀዮ ደ/ሰ/ቅ/ገብርኤል ቤ/ክ የመስተንግዶ ኮሚቴ አባላት ጋር

ሰኔ ፳፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምርያ ማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል በኒውዮርክ ሀገረ ስብከት በኮሎምበስ ኦሀዮ ደብረ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ከሰኔ ፲፮ – ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ለሦስት ቀናት የቆየ የተተኪ መምህራን ሥልጠና መስጠቱን አስታወቀ፡፡

እንደ ማእከሉ ማብራርያ በማእከሉ የትምህርት፣ ሐዋርያዊ ተልእኮ እና የምክር አገልግሎት ዋና ክፍል አዘጋጅነት በተሰጠው በዚህ ሥልጠና በቍጥር ከዐሥር ከሚበልጡ ስቴቶች ከየንዑሳን ማእከላቱ የተወከሉ የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ቀሳውስት፣ ዲያቆናት እና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች የተሳትፉ ሲኾን፣ የሥልጠናው ዓላማም ሠልጣኞቹ በስብከተ ወንጌል ሊያገለግሉ የሚችሉበትን ዕውቀትና ክህሎት እንዲያዳብሩ ለማገዝ ነው፡፡

ትምህርተ ሃይማኖት (ዶግማ)፣ መንፈሳዊ አስተዳደር፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን፣ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን፣ የስብከት ዘዴ እና ክብረ ቅዱሳን በሥልጠናው የተካተቱ የትምህርት ክፍሎች ሲኾኑ፣ መልአከ ጽዮን ቀሲስ በላቸው ወርቁ፣ መልአከ ሰላም ቀሲስ ያሬድ ገብረ መድኅን፣ ቀሲስ ኅብረት የሺጥላ፣ መምህር ሙሉጌታ ኃይለ ማርያም እና መምህር ብርሃኑ አድማስ ሥልጠና በመስጠት የተሳተፉ መምህራን ናቸው፡፡

ለሦስት ቀናት በተሰጠው በዚህ ሥልጠና በወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ጉዳዮች ላይ ሰፊ ውይይት የተደረገ ሲኾን፣ በውይይቱ በቂ ግንዛቤ እንዳገኙ ከሠልጣኞቹ ለመረዳት መቻሉንም ማእከሉ በዘገባው አትቷል።

በሥልጠናው የመፈጸሚያ ዕለት እሑድ ከቅዳሴ በኋላ በተደረገው የምረቃ መርሐ ግብር በመምህር ብርሃኑ አድማስ ትምህርተ ወንጌል የተሰጠ ሲኾን፣ ሠልጣኞቹም ያሬዳዊ ዝማሬ አቅርበዋል፡፡ በማእከሉ የተዘጋጀው የምስክር ወረቀትም በመልአከ ጽዮን ቀሲስ በላቸው ወርቁ አማካይነት ለሠልጣኞች ተበርክቷል፡፡

በመርሐ ግብሩ ማጠቃለያ የደብረ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ቀሲስ ያሬድ ገብረ መድኅን ሥልጠናው በደብራቸው በመሰጠቱ እርሳቸውም ኾኑ ምእመናኑ እጅግ መደሰታቸውን ከገለጹ በኋላ ለወደፊት ሥልጠናው በየጊዜው ሲዘጋጅ ደብራቸው በመስተንግዶ ተባባሪ እንደሚኾን ቃል ገብተዋል።

መልአከ ጽዮን ቀሲስ በላቸው ወርቁ በበኩላቸው ሥልጠናው ተግባራዊ በመኾኑ የተሰማቸው ደስታ ወሰን እንደ ሌለው ገልጸው ሠልጣኞቹ በተሰጣቸው አደራ ቤተ ክርስቲያንን በትጋት እንዲያገለግሉ መክረዋል።

አያይዘውም ለሥልጠናው መሳካት አስተዋጽዖ ያደረጉ የማእከሉ ሥራ አስፈጻሚ አባላትን፣ ሥልጠናውን በትጋት ያስተባበሩ የትምህርት ክፍል ሓላፊዎችን፣ እንደዚሁም የምግብና መኝታ ሙሉ ወጭውን በመቻል በመስተንግዶው ድጋፍ ያበረከቱ ቀሲስ ያሬድ ገብረ መድኅንን፣ በአጠቃላይ የኦሀዮ ደ/ሰ/ቅ/ገብርኤል ሰበካ ጉባኤ አመራር አባላትን እና ሕዝበ ክርስቲያኑን መልአከ ጽዮን ቀሲስ በላቸው ወርቁ ከልብ አመስግነዋል።

የአሜሪካ ማእከል ሰብሳቢ አቶ ማስተዋል ጌጡ በዕለቱ ባስተላለፉት መልእክት ሠልጣኞቹ በሥልጠናው የቀሰሙትን ትምህርት አስፋፍተውና አሳድገው የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ ተልእኮ በማፋጠን የድርሻቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል።

በመጨረሻም የተተኪ መምህራን ሥልጠናው ለወደፊትም በየዓመቱ እንደሚሰጥ ያስታወቁት ሰብሳቢው፣ ከአሁን በፊት የሥልጠና ዕድሉን ያላገኙ ቀሳውስት፣ ዲያቆናት እና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ሥልጠናውን እንዲወስዱ ለማድረግ ማኅበረ ቅዱሳን ቅድመ ኹኔታዎችን በማመቻቸት ላይ እንደሚገኝ አስገንዝበዋል፡፡

‹‹እናንተ የቤተ ክርስቲያን ባለ አደራዎች ናችሁ›› – ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሰኔ ፳፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርቱን ባስመረቀበት ዕለት ተገኝተው በሰጡት ቃለ ምዕዳን ‹‹እናንተ የቤተ ክርስቲያን ባለ አደራዎች ናችሁ›› በማለት ተመራቂዎቹ ወንጌልን ከዳር እስከ ዳር የማዳረስ አደራ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡

‹‹እናንተ ከመልካም ዛፍ የተገኛችሁ መልካም ፍሬዎች እንደ መኾናችሁ ይህን ፍሬያችሁን እንድታካፍሉ ቤተ ክርስቲያን አደራ ትላችኋለች›› ያሉት ቅዱስነታቸው ‹‹መብራታችሁ በሰዉ ዅሉ ፊት ይብራ›› የሚለውን የወንጌል ቃል መነሻ አድርገው በከተማ ብቻ ሳይወሰኑ በየገጠሩ በመዘዋወር በአታላዮች የሚወሰዱ ወገኖችን እንዲጠብቁ እና እንዲያስተምሩ ተመራቂዎቹን አሳስበዋል፡፡

ቅዱስ ፓትርያርኩ፣ በየገጠሩ አንድ ሰባኬ ወንጌል ጠፍቶ በየከተሞች በተለይም በአዲስ አበባ በአንድ አጥቢያ ከሁለት በላይ መምህራን መመደባቸውን ተችተዋል፡፡

ሴቶች በመንፈሳዊ ኮሌጁ ተምረው በመመረቃቸውና ከፊሎቹም ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገባቸው መደሰታቸውን የገለጹት ቅዱስነታቸው፣ ይህን ፈለግ ተከትለው በየኮሌጆቹ የሚሰጠውን ትምህርተ ሃይማኖት እንዲከታተሉና ራሳቸውን በቃለ እግዚአብሔር እንዲያጎለብቱ እናቶችና እኅቶችን መክረዋል፡፡

በመጨረሻም ተመራቂዎቹ በሚሠማሩበት ቦታ ዅሉ በስብከተ ወንጌል ተግተው በማገልገል፤ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ደግሞ የሰባክያነ ወንጌልን አገልግሎት በመቈጣጠር፤ ምእመናኑም ከትክክለኞች መምህራን ትክክለኛውን ቃለ ወንጌል በመማር መንፈሳዊ ሓላፊነታቸውን እንዲወጡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርቱን ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያኩ፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሰባክያነ ወንጌል፣ አባቶች ካህናት፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እና የተመራቂ ቤተሰቦች በተገኙበት ሰኔ ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ በቅዱስ ፓትርያርኩ ቡራኬ አስመርቋል፡፡

ኮሌጁ ደቀ መዛሙርቱን ያስመረቀው በቀን፣ በማታ በተመላላሽ እና በርቀት መርሐ ግብር፤ በልዩ ልዩ የትምህርት ክፍል፤ በማስተርስ፣ በዲግሪ እና በዲፕሎማ ማዕረግ ነው፡፡ በዕለቱ ተመራቂዎቹ ባለ አምስት አንቀጽ የአገልግሎት ቃል ኪዳናቸውን በተወካያቸው አማካይነት አቅርበዋል፡፡ ሴቶች እኅቶቻችንም በልዩ ልዩ ማዕረግ የተመረቁ ሲኾን ከእነርሱ መካከል ጥቂቶቹ ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ መሸለማቸው ቅዱስ ፓትርያርኩን ጨምሮ ብዙዎችን አስገርሟል፡፡

የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ከተመሠረተበት ጊዜ አንሥቶ እስከ አሁን ድረስ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትን ጨምሮ በርካታ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን ሲያፈራ የኖረና በማፍራት ላይ የሚገኝ አንጋፋ የትምህርት ማእከል ነው፡፡

የቤተ ክርስቲያን ባለ አደራዎች ሰባክያነ ወንጌል መፍለቂያ የኾነው ኮሌጁ ከኦርቶዶክሳዊው አስተምህሮ ያፈነገጠ የኑፋቄ ትምህርት ሲያዛምቱ የተገኙ ሰርጎ ገብ ተማሪዎችን ከአሁን በፊት አውግዞ እንደ ለየ፤ ለወደፊትም ኦርቶዶክሳዊው አስተምህሮ ሳይፋለስ ለትውልድ ይተላለፍ ዘንድ ሥርዓቱን የጠበቀ ትምህርት የመስጠት ተልእኮዉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል በኮሌጁ የቦርድ ሥራ አመራር ሪፖርት ተገልጿል፡፡

‹‹ከእናንተ ብዙ ይጠበቃል›› ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሰኔ ፲፱ ቀን ፳፻፱ .

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ የዕለቱን ወንጌል ሲያነቡ (ሉቃ. ፲፥፩-፲፮)

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ በልዩ ልዩ ትምህርት ክፍል ያስተማራቸውን ደቀ መዛሙርት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቤተ ክርስቲያን አባቶች፣ የኮሌጁ መምህራንና ሠራተኞች በተገኙበት ሰኔ ፲፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ በቅዱስ ፓትርያርኩ ቡራኬ አስመርቋል፡፡ ተመራቂዎቹም የስብከተ ወንጌል አገልግሎቱን በሚመለከት ያዘጋጁትን የአቋም መግለጫ በተወካያቸው አማካይነት አቅርበዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በሰጡት ቃለ ምዕዳን ‹‹ታሪካዊቷ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከዘመነ ሐዋርያት ጀምሮ ጠብቃ ያቆየችው ትክክለኛ የኾነ አስተምህሮዋ፣ ባህል እና ትውፊቷ ሳይበረዝና ሳይፋለስ ለትውልደ ትውልድ መሸጋገር ይችል ዘንድ ከእናንተ ብዙ ይጠበቃል›› ሲሉ ተመራቂዎቹን አሳስበዋል፡፡

ዕለቱ፣ ተመራቂዎቹ የቤተ ክርስቲያንን አደራ ተቀብለው በየተሠማሩበት የሥራ መስክ ዅሉ እስከ መጨረሻው በታማኝነት ቃል የሚገቡበት ቀን መኾኑን ያስገነዘቡት ቅዱስነታቸው ‹‹የመንግሥተ እግዚአብሔር መልእክተኛ የኾነ ዅሉ መስቀሉን ተሸክሞ ለማገልገል የተመረጠ ስለ ኾነ በሚያጋጥመው የጕዞ ዐቀበት እና ቍልቍለት ሊቸገር አይገባውም፤ በማን እንደ ተመረጠ ያውቃልና ነው›› በማለት ተመራቂዎቹ ብዙ ፈተና እንደሚጠብቃቸው አውቀው ዅሉንም በትዕግሥት በማሸነፍ የሕይወት አክሊል ባለቤቶች ለመኾን ከወዲሁ እንዲዘጋጁ መክረዋል፡፡

ተመራቂዎቹ በሚላኩበት ቦታ ዅሉ ለቤተ ክርስቲያንና ለትውልድ የሚጠቅም አርአያነት ያለው ሥራ ለመሥራት እንዲችሉ ቤተ ክርስቲያን ስለ እነርሱ ዘወትር እንደምትጸልይም ተናግረዋል፡፡ በቃለ ምዕዳናቸው ማጠቃለያም መንፈሳዊ ኮሌጁ በየጊዜው ተተኪ መምህራንን ለማፍራት እያደረገ ያለውን ጥረት አድንቀው ‹‹ዘመኑ የዕውቀት ነውና የመማር ማስተማር ዘዴው ዘመኑን የዋጀ እንዲኾን ከበፊቱ በበለጠ ተጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ በቤተ ክርስቲያናችን ስም አደራ እንላለን›› በማለት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል የከፋ ሸካ ቤንጂ ማጂ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሓላፊ በበኩላቸው ‹‹በቆያችሁበት የትምህርት ዘመን ከመምህሮቻችሁ ያገኛችሁትን መንፈሳዊ ዕውቀት እግዚአብሔር ሒዱ ብሎ ወደሚልካችሁ ዓለም በመሔድ ሕዝባችሁንና ሃይማኖታችሁን ጠብቃችሁ ሳትታክቱ እንድታገለግሉ ስትል ቤተ ክርስቲያን ሰማያዊ መልእክቷን ታስተላልፋለች›› የሚል ቃለ በረከት ለተመራቂዎቹ ሰጥተዋል፡፡

ሊቀ ኅሩያን መሐሪ አስረስ

መምህር ማሞ ከበደ

በኮሌጁ ተምረው የሚመረቁ መምህራን በልዩ ልዩ የዕውቀት ዓይነት የበለጸጉ ሊቃውንት መኾናቸውን በማውሳት ‹‹ከአሁን በኋላ ዝናብ ዘንቦ መሬትን እንደሚያርሰው ዅሉ ከሞላው የዕውቀት ባሕራችሁ እየቀዳችሁ የምእመናንን አእምሮ እንደምታረሰርሱት ትጠበቃላችሁ›› ያሉት ደግሞ የኮሌጁ ዋና ዲን ሊቀ ኅሩያን መሐሪ አስረስ ናቸው፡፡

‹‹በኮሌጃችን ተምረው የሚመረቁ መምህራን የአብነቱን ትምህርት ከዘመናዊው ጋር አጣጥመው በዕውቀት ላይ ዕውቀት ጨምረው የሚወጡ መንፈሳውያን ሐኪሞች ናቸው፡፡ ትምህርታቸውም ደዌ ሥጋን ብቻ ሳይኾን ደዌ ነፍስንም ይፈውሳል›› ያሉት መምህር ማሞ ከበደ የመንፈሳዊ ኮሌጁ አስተዳደር ምክትል ዲን እና የኮሌጁ መምህርም ኮሌጁ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን ጨምሮ በርካታ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን ሲያፈራ እንደ ቆየ አሁንም በማፍራት ላይ እንደሚገኝ አስታውሰዋል፡፡

የኮሌጁ ተመራቂዎች በከፊል

በዚህ ዓመትም በብሉይ ኪዳን አንድ፤ በሐዲስ ኪዳን አንድ፤ በቀን አዳሪ ሲሚናር ዐሥራ አንድ፤ በቀን ተመላላሽ ሃያ ሦስት፤ በማታው መርሐ ግብር ሁለት መቶ ዐርባ አምስት በድምሩ ሁለት መቶ ሰማንያ አንድ ደቀ መዛሙርትን ማስመረቁን፤ ከተመራቂዎች መካከልም አካል ጉዳተኞች እና ሴቶች እንደሚገኙ መምህር ማሞ ከበደ አስታውቀዋል፡፡ አራቱን ጉባኤያት ማስተማር፤ በዲግሪ መርሐ ግብር ማስመረቅ እና የርቀት ትምህርት መጀመር ከኮሌጁ የወደፊት ዕቅዶች መካከል የሚጠቀሱ ተግባራት መኾናቸውንም አስረድተዋል፡፡

የኮሌጁ ተመራቂዎች በከፊል

አጠቃላይ የኮሌጁን የማስተማር ተልእኮ በሚመለከት ከዝግጅት ክፍላችን ጋር ባደረጉት ቆይታ ምክትል ዲኑ እንዳብራሩት ኮሌጁ ከኅዳር ወር ፳፻፰ ዓ.ም ጀምሮ ሰርጎ ገብ መናፍቃንን የሚከታተል ኰሚቴ አቋቁሞ ከኦርቶዶክሳዊው የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ያፈነገጠ ባዕድ ትምህርት የሚያስተምሩ ደቀ መዛሙርትን በማጣራት በየጊዜው እንዲወገዙና ከትምህርት እንዲታገዱ ሲያደርግ የቆየ ሲኾን፣ በዘንድሮው ዓመትም እምነቱ ተጣርቶ ውሳኔ እስኪያገኝ ድረስ የሃይማኖት ሕጸጽ የተገኘበት አንድ ደቀ መዝሙር እንዳይመረቅ እገዳ ተጥሎበታል፡፡

ከግራ ወደ ቀኝ፡- ዲያቆን ዳንኤል ታደሰ እና ቀሲስ አድማሱ ሰንበታ

ከዚሁ ዅሉ ጋርም የካህናትና ሰባክያነ ወንጌል እጥረት ካሉባቸው አህጉረ ስብከት መሥፈርቱን የሚያሟሉ ሰባት ደቀ መዛሙርትን በመምረጥ ማኅበረ ቅዱሳን ሙሉ ወጫቸውን ሸፍኖ በመንፈሳዊ ኮሌጁ እያስተማረ መኾኑን፤ ከእነዚህ መካከልም ከምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት የመጡት ሁለቱ ሰባክያነ ወንጌል ቀሲስ አድማሱ ሰንበታ እና ዲያቆን ዳንኤል ታደሰ ለሦስት ዓመታት ተምረው በዘንድሮው ዓመት መመረቃቸውን ከቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የደረሰን መረጃ ያመላክታል፡፡

ዝግጅት ክፍላችን ያነጋገራቸው ሁለቱ ተመራቂዎችም ማኅበሩ ላደረገላቸው ድጋፍ ምስጋናቸውን በእግዚአብሔር ስም አቅርበዋል፡፡ ለወደፊቱም በየቦታው እየተዘዋወሩ ልዩ ልዩ ፈተናዎችን ተቋቁመው በክህነት እና በስብከተ ወንጌል ሰፊ አገልግሎት በመስጠት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሰጣቻቸውን መንፈሳዊ ሓላፊነት ለመወጣት ዝግጁ መኾናቸውን ገልጸዋል፡፡

ዐውደ ርእዩ በአሜሪካ ቀረበ

በዝግጅት ክፍሉ

ሰኔ ፲፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ›› በሚል ርእስ የተዘጋጀው ፭ኛው ዙር የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ ከሰኔ ፲ – ፲፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በአሜሪካ አገር መቅረቡን የአሜሪካ ማእከል አስታወቀ፡፡

ዐውደ ርእዩ በጸሎተ ወንጌል ሲከፈት

በአትላንታ ንዑስ ማእከል አዘጋጅነት በአትላንታ ከተማ በደብል ትሪ ሆቴል በቀረበው በዚህ ልዩ ዐውደ ርእይ የቤተ ክርስቲያን አባቶች፣ የየአጥቢያ ሰንበት ት/ቤቶች እና የመንፈሳውያን ማኅበራት አባላት፣ ታዳጊ ሕፃናትን ጨምሮ በርካታ የአሜሪካ ምእመናን መታደማቸውን የንዑስ ማእከሉንና የዝግጅት ኰሚቴውን ሪፖርት ጠቅሶ ማእከሉ ዘግቧል፡፡

ዐውደ ርእዩ በአባቶች ቡራኬ ሲጀመር

በመኪና ከአራት እስከ ዐሥር ሰዓታት ከሚወስዱ ክፍለ ግዛቶች (ስቴቶች) ጭምር ዐውደ ርእዩን ለመመልከት በአትላንታ ከተማ የተገኙ ምእመናን እንደ ነበሩም ከዝግጅት ኰሚቴው ሪፖርት ለመረዳት ተችሏል፡፡ የተመልካቾች ቍጥር ከመብዛቱ የተነሣ ዐውደ ርእዩ በሁለት ክፍሎች የቀረበ ሲኾን፣ ትዕይንቶቹም በእንግሊዝኛ ቋንቋ እየተተረጐሙ ተመልካቾች በሚረዱት መልኩ ተብራርተዋል፡፡

የብፁዕ አቡነ ፋኑኤል መልእክትና ቃለ ምዕዳን በመጋቤ ሐዲስ ይልማ ቸርነት ሲቀርብ

ዐውደ ርእዩ በጸሎተ ወንጌል በተከፈተበት ዕለት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል መልእክትና ቃለ ምዕዳን በመጋቤ ሐዲስ ይልማ ቸርነት የአትላንታ ዳግማዊ ቁልቢ ደብረ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤል ወአቡነ ተክለ ሃይማኖት አብያተ ክርስቲያናት አስተዳዳሪ ቀርቧል፡፡

በመልእክታቸው እንደ ተጠቀሰው የዐውደ ርእዩ ትዕይንቶች በእንግሊዝኛ ቋንቋ ተተርጕመው እንዲቀርቡ መደረጋቸው ይበል የሚያሰኝ ተግባር መኾኑን ብፁዕነታቸው አድንቀዋል፡፡

የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ለሕዝበ ክርስቲያኑ በስፋት ለማዳረስ ይቻል ዘንድ ይህ መንፈሳዊ አገልግሎት ተጠናክሮ እንዲቀጥልና በሌሎች ከተሞችም እንዲከናወን ያሳሰቡት ብፁዕነታቸው አገልግሎቱን ሀገረ ስብከታቸው እንደሚደግፍም ቃል ገብተዋል፡፡

የዐውደ ርእዩ ታዳሚ አባቶች እና ምእመናን በከፊል

በዐውደ ርእዩ ከተሰሙ መልካም ዜናዎች አንዱ አንድ መቶ ሦስት የአብነት ተማሪዎችን በአንድ ለአንድ የድጋፍ ዘዴ ለመርዳትና ለማስተማር የሚያስችል ቃል መገባቱ ሲኾን፣ በቍጥር ከአራት እስከ ዐሥር የሚደርሱ የአብነት ተማሪዎችን በግል ወጫቸው ለማስተማር አንዳንድ ምእመናን ቃል ገብተዋል፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም ለጎንደር በአታ የቅኔ ጉባኤ ቤት ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የሚውል $2,628 (ሁለት ሺሕ ስድስት መቶ ሃያ ስምንት ዶላር) ምእመናን ለግሰዋል፡፡

የዐውደ ርእዩ ተሳታፊ ምእመናን በከፊል

በመርሐ ግብሩ ማጠቃለያ ዕለት መልእክት ያስተላለፉ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ዐውደ ርእዩ አስተማሪ እንደ ነበር አስታውሰው በዚህም ይህን ሠራን ብሎ መታበይ እንደማያስፈልግ እና ስለ ሥራው ዅሉ እግዚአብሔርን ማመስገን ተገቢ እንደ ኾነ አስተምረዋል፡፡

የአትላንታ መካነ ሕይወት አቡነ ገብረ ማንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ ሕይወት ቀሲስ ዕርገተ ቃል ‹‹አሁን ታሪክ ተቀይሯል፡፡ የአገልግሎቱ በር ተከፍቷል፡፡ ስለኾነም ማኅበሩ በአትላንታ ሰፋፊ ራዎችን መሥራት ይጠበቅበታል፡፡ ከሕዝቡ ጥያቄና አስተያየት የተረዳነውም ይህንኑ ነው፡፡ ስለዚህ በርቱ›› በማለት አባታዊ ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡

‹‹ለዚህ ዅሉ ሥራ መሳካት ምክንያቱ እግዚአብሔር ከኛ ጋር ስለ ኾነ ነው›› ያሉት የአትላንታ መካነ ሕይወት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ቀሲስ ያዕቆብ በበኩላቸው፣ ንዑስ ማእከሉ በዚህ ሥራ ብቻ ሳይወሰን ሌሎች መንፈሳውያን ተግባራትንም አጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበዋል፡፡

ምእመናን የዐውደ ርእዩን ትዕይንቶች ሲከታተሉ (በከፊል)

በዝግጅቱ የቤተ ክርስቲያንን አስተዋጽዖ፣ ፈተናዎችንና የምእመናንን ድርሻ በስፋት እንደ ተረዱበት እና የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ የዅሉም ምእመናን ጉዳይ መኾኑን እንደ ተገነዘቡበት የዐውደ ርእዩ ጐብኝዎች በሰጡት አስተያየት ተናግረዋል፡፡

ምእመናን የዐውደ ርእዩን ትዕይንቶች ሲከታተሉ (በከፊል)

በመጨረሻም ለዚህ መርሐ ግብር መሳካት ትብብርና እገዛ ላደረጉ የአብያተ ክርስቲያናት አስተዳዳሪዎች፣ ለሰበካ ጉባኤ አባላትና ማኅበረ ካህናት፤ ለየሰንበት ት/ቤቶች አባላት፤ ድጋፍ በመስጠት (ስፖንሰር በማድረግ) ለተባበሩ የግል ድርጅቶች እና ለልዩ ልዩ መገናኛ ብዙኃን (ሚዲያ) አካላት የዐውደ ርእዩ አዘጋጅ ኰሚቴ ላቅ ያለ ምስጋናውን በማኅበረ ቅዱሳን ስም አቅርቧል፡፡

ከዐውደ ርእዩ ትዕይንቶች ከፊሉ

ዐውደ ርእዩ በሚቀጥለው ቅዳሜና እሑድ (ሰኔ ፲፯ እና ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም) በዋሽንግተን ስቴት ሲያትል ከተማ እንደሚቀርብ የአሜሪካ ማእከል አስታውቋል፡፡

ከዐውደ ርእዩ ክውን ትዕይንቶች አንዱ (የአብነት ተማሪዎች በትምህርት ላይ)

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ‹‹የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ›› በሚል ርእስ ያዘጋጀው ፭ኛ ዙር ዐውደ ርእይ ከግንቦት ፲፯ – ፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በአዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማእከል ቀርቦ በብዙ ሺሕ ሕዝብ እንደ ተጐበኘ የሚታወስ ነው፡፡

ይህን ዐውደ ርእይ በርካታ የአገር ውስጥ እና የውጭ አገር ማእከላት በየጊዜው እያዘጋጁ ትምህርቱ ለምእመናን እንዲዳረስ በማድረግ ላይ ናቸው፡፡

በቅርቡም ከአገር ውስጥ ማእከላት መካከል ባሕር ዳር ማእከል ከግንቦት ፬ – ፲፫፤ ፍኖተ ሰላም ማእከል ከሰኔ ፰ – ፲፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በቅደም ተከተል ዐውደ ርእዩን አዘጋጅተው ለብዙ ሺሕ ሕዝብ እንዳስጐበኙ ከማእከላቱ የደረሰን መረጃ ያመላክታል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የኖላዊነት ተልእኮው ተጠናክሮ እንዲቀጥል አሳሰቡ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሰኔ ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ እና የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

የኢትዮጵያ ኦርቶደክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰባክያነ ወንጌል፤ በተለይ ምእመናንን በቅርበት የመከታተል ሓላፊነት ያለባቸው የእግዚአብሔር እንደራሴዎች፣ የቤተ ክርስቲያን ጠበቃዎች የኾኑ ካህናት የነፍስ ልጆቻቸውን ተግተው በማስተማር የኖላዊነት ተልእኮአቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ እና የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አሳሰቡ፡፡

ብፁዕነታቸው ሰኔ ፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከማኅበረ ቅዱሳን ጋዜጠኞች ጋር ባደረጉት ቆይታ በ፳፻፱ ዓ.ም ርክበ ካህናት በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተላለፉ ውሳኔዎችን መሠረት በማድረግ በተለይ የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴዎችን፣ ዐቂበ ምእመናንን፣ የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎትና የልማት ሥራዎችን በሚመለከት ሰፋ ያለ ማብራርያ ሰጥተዋል፡፡

‹‹ቅዱስ ሲኖዶስን የሚመራውና ሥራውን የሚሠራው መንፈስ ቅዱስ ነው፤ ሰው ምክንያት ነው›› ያሉት ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በቤተ ክርስቲያን ጉዳይ የመጨረሻው ወሳኝ አካል የኾነው ቅዱስ ሲኖዶስ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት፣ ለምእመናን ሕይወት የሚጠቅሙ መመርያዎችን በየጊዜው ሲያወጣ እና ውሳኔዎችን ሲያሳልፍ አክብሮ መቀበል ክርስቲያናዊ ግዴታ መኾኑን አስረድተዋል፡፡ መመርያዎቹና ውሳኔዎቹ በተግባር ላይ እንዲውሉም የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች እና ሕዝበ ክርስቲያኑ የሚጠበቅባቸውን ድርሻ ሊወጡ እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡

በቅዱስ ሲኖዶስ በየጊዜው ተወግዘው ከተለዩ መናፍቃን በተጨማሪ በብፁዕነታቸው ሀገረ ስብከት ደቡብ ምዕራብ ሸዋም ከቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ውጪ የኾኑ ትምህርቶችንና መዝሙሮችንም በስውር ሲያስተምሩ፤ ሲዘምሩ የነበሩ ዘጠኝ የተሐድሶ ኑፋቄ አራማጆችን አውግዘው መለየታቸውን ብፁዕነታቸው አውስተው፣ በሦስት መንገዶች ማለትም አውግዞ በመለየት፤ ከቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በማገድ እና ማስጠንቀቂያ በመስጠት ሀገረ ስብከታቸው በመናፍቃኑ ላይ ርምጃ መውሰዱን አስታውቀዋል፡፡

የኑፋቄ ትምህርት እንደሚሰጡ ሕጋዊ ማስረጃ ቀርቦባቸው ከአሁን በፊትም ኾነ በዘንድሮው የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ተወግዘው ከቤተ ክርስቲያን አንድነት የተለዩ መናፍቃን ጥፋታቸውን አምነው፣ ስሕተታቸውን አርመው በንስሐ ለመመለስ ዝግጁ ከኾኑ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በይቅርታ እንደምትቀበላቸው፤ የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ በመተላለፍ ምእመናንን ማሰናከላቸውን ከቀጠሉ ግን በሕግ እንደምትጠይቃቸው አስረድተዋል፡፡

ሐዋርያዊ ተልእኮን በሚመለከትም ማኅበረ ቅዱሳን በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በማዘጋጀት በአማርኛ ቋንቋ እና አፋን ኦሮሞ ትምህርተ ወንጌል ከመስጠቱ ባሻገር ምእመናንን በማስተባበር ለተቸገሩ አብያተ ክርስቲያናት የገንዘብ ድጋፍ በማድረጉ የአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን መደሰታቸውን ብፁዕነታቸው ገልጸዋል፡፡

አያይዘውም የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ ተልእኮ ይበልጥ ለማፋጠን ይቻል ዘንድ ማኅበሩ ቅዱሳት መጻሕፍትንና መንፈሳውያን መዝሙራትን በልዩ ልዩ ቋንቋዎች በማሠራጨት አገልግሎቱን ይበልጥ አጠናክሮ መቀጠል እንደሚኖርበት ጠቁመዋል፡፡

የስብከተ ወንጌል አገልግሎቱን በስፋት ማዳረስ፣ የአብነት ት/ቤቶችን ማስፋፋት፣ የተዘጉ አብያተ ክርስቲያናት አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረግ እና ገቢ የሚያስገኙ ፕሮጀክቶችን መተግበር ወደፊት ሊከናወኑ የታቃዱ ተግባራት መኾናቸውን ያስታወቁት ብፁዕነታቸው፣ በሀገረ ስብከቱ ሥር የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናትን በዘላቂነት ለመደገፍ ሲባል በወሊሶ ከተማ ለሚገነባው ባለ አራት ፎቅ ዅለገብ ሕንጻ ግንባታም መላው ሕዝበ ክርስቲያን ድጋፍ እንዲያደርግ መንፈሳዊ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

በመጨረሻም ‹‹ዘመኑ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ ፈተና የበዛበት፤ ከውስጥም ከውጪም ጠላቶች የበረከቱበት ወቅት ነው፡፡ በተለይ ትክክለኛ ሰባኪ እና የቤተ ክርስቲያን ልጅ መስለው በቅዱሳን ስም የሚሰበሰበውን ገንዘቧን እየበሉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እየጎዱ ያሉ አፅራረ ቤተ ክርስቲያንም እየበዙ ነው፡፡ ስለኾነም ሰባክያነ ወንጌል፣ ቀሳውስት እና ዲያቆናት፣ እንደዚሁም የሰንበት /ቤት ወጣቶች ምእመናኑን በሥርዓት ሊያስተምሩ፤ ሕዝበ ክርስቲያኑም ከኑፋቄ ትምህርት አራማጆች ሊጠነቀቅ፤ በቃለ እግዚአብሔር በመጎልበትም ራሱን ከስሕተት ሊጠብቅ ይገባል›› በማለት ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ስዊድናዊው ፕሮፌሰር አምሳ ሁለት መጻሕፍትን አበረከቱ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በስዊድን አገር የሉንድ ዩኒቨርሲቲ መምህርና ተመራማሪ የኾኑት ፕሮፌሰር ሳሙኤል ሮቢንሰን በልዩ ልዩ ባለሙያዎችና በተለያዩ አርእስት በእንግሊዝኛ ቋንቋ የተዘጋጁ አምሳ ሁለት መጻሕፍትን ለማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል በስጦታ መልክ አበረከቱ፡፡

ፕ/ር ሳሙኤል ሮቢንሰን መጻሕፍታቸውን ሲያስረክቡ

‹TAITU Empress of Ethiopia; Lake Tana and The Blue Nile an Abyssinian Quest; Education in Ethiopia Prospect and Retrospect; The Abyssinian Difficulty the Emperor Tewodross and the Magdala Campaign 1867-68; Slavery, Slave Trade and Abolition Attempts in Egypt and Sudan› የሚሉት ከአምሳ ሁለቱ መጻሕፍት መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡

ዶ/ር ዮሐንስ አድገህ መጻሕፍቱን ሲረከቡ

ወላጅ አባታቸው ፕሮፌሰር ሮቢንሰን፣ ከሌላ እምነት ወደ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት የተመለሱ የቤተ ክርስቲያን ልጅ እንደ ነበሩና በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ (የአሁኑ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ) ለበርካታ ዓመታት በመምህርነት አገልግሎት እንደ ሰጡ ያስታወሱት ፕሮፌሰር ሳሙኤል፣ ማኅበሩ የሚያከናውነውን የጥናትና ምርምር ተግባር ለመደገፍና ለማበረታታት በውድ ገንዘብ የገዟቸውን እነዚህን መጻሕፍት በወላጅ አባታቸው ስም ለማእከሉ ማበርከታቸውን ተናግረዋል፡፡

በምጣኔ ሀብት፣ በታሪክ፣ በኅብረተሰብና አካባቢ ሳይንስ፣ በፖለቲካ እና ሌላም የትምህርት መስክ የተዘጋጁት መጻሕፍቱ በተለይ ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መምህራን፣ ተመራማሪዎችና ተማሪዎች የጎላ ጠቀሜታ እንዳላቸው ፕሮፌሰሩ ገልጸዋል፡፡

ፕሮፌሰሩ መጻሕፍቶቻቸውን ለማኅበሩ ያበረከቱት በስዊድን አገር የፒኤችዲ ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ በሚገኙት የቀድሞው የጥናትና ምርምር ማእከሉ ዳይሬክተር ቀሲስ መንግሥቱ ጎበዜ አስተባባሪነት መኾኑን የጥናትና ምርምር ማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር አቶ ጌታቸው ሞላ ለዝግጅት ክፍላችን አስታውቀዋል፡፡

አቶ ጌታቸው እንዳስታወቁት መጻሕፍቱ በተበረከቱበት ሚያዝያ ፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከልዩ ልዩ ዓለማቀፍ የትምህርት ተቋማት የመጡ የውጭ አገር ዜጎች ከፕሮፌሰር ሳሙኤል ጋር በማኅበሩ ሕንጻ ተገኝተዋል፡፡

የመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች በከፊል

በዕለቱ በነበረው መርሐ ግብር፣ ፕሮፌሰር ሽፈራው በቀለ (ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ) የኢትዮጵያን ታሪክ፤ ዶክተር ዮሐንስ አድገህ (የጥናትና ምርምር ማእከሉ ዋና ዳይሬክተር) የማኅበረ ቅዱሳንን አመሠራረትና የማእከሉን ተግባር በአጭሩ ለእንግዶቹ አቅርበዋል፡፡ ቀሲስ መንግሥቱ ጎበዜም ማኅበሩ በጥናትና ምርምር ማእከሉ አማካይነት ለቤተ ክርስቲያን የሚሰጠውን አገልግሎት አስረድተዋል፡፡

ከግራ ወደ ቀኝ፡- ቀሲስ መንግሥቱ ጎበዜ፣ ፕ/ር ሽፈራው በቀለ እና ፕ/ር ሳሙኤል ሮቢንሰን

መጻሕፍቱ አንባብያን ይጠቀሙባቸው ዘንድ በሕጋዊ ደረሰኝ ወደ ማኅበሩ ቤተ መጻሕፍት ገቢ መደረጋቸውን የጠቆሙት አቶ ጌታቸው ሞላ፣ ማኅበረ ቅዱሳን ምሁራንን በማሳተፍ የሚያከናውነውን የጥናትና ምርምር ሥራ የውጭ አገር ዜጎች ለመደገፍ መነሣሣታቸው ‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በውጩ ዓለም ዘንድ ያላትን ልዩ ቦታ ያመላክታል፡፡ መጻሕፍት ልገሳውም የጥናትና ምርምር ማእከሉን ወደ ተቋም ለማሳደግ የሚደረገውን ጥረት ከግብ ለማድረስ ያግዛል›› ብለዋል፡፡

አቶ ጌታቸው ሞላ የጥናትና ምርምር ማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር

በመጨረሻም ፕሮፌሰር ሳሙኤልንና ሌሎች የትምህርት ባልንጀሮቻቸውን በማስተባበር መጻሕፍቱ ለማኅበሩ ቤተ መጻሕፍት ገቢ እንዲኾኑ ያደረጉትን ቀሲስ መንግሥቱ ጎበዜን የማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር በቤተ ክርስቲያን ስም አመስግነው ‹‹ማኅበረ ቅዱሳን የሚሰጠውን መንፈሳዊ አገልግሎት ለመደገፍ ፈቃደኛ የኾናችሁ አጋሮቻችን! እንደ ፕሮፌሰር ሳሙኤል ሮቢንሰን ልዩ ልዩ መጻሕፍትን ለቤተ መጻሕፍታችን በማበርከት መንፈሳዊ ድርሻችሁን እንድትወጡ ይኹን›› ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በጥናትና ምርምር ማእከሉ ሥር የሚገኘው የማኅበረ ቅዱሳን ቤተ መጻሕፍት ቅዱሳት መጻሕፍትን ብቻ ሳይኾን በልዩ ልዩ የትምህርት መስክና ቋንቋ የተዘጋጁ በርካታ ዓለማቀፍ የጥናትና የምርምር ሥራዎችን ለንባብ እንደሚያቀርብ፤ ዘወትር ከሰኞ እስከ ቅዳሜ ከጠዋቱ 2፡3 – ምሽቱ 1፡00 ሰዓት (የምሳ ሰዓትን ጨምሮ) አገልግሎት እንደሚሰጥ ያስረዱት የማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር፣ ‹‹መንፈሳዊም ኾነ ዘመናዊ ዕውቀታችሁን ለማዳበር የምትፈልጉ ዅሉ ከማኅበሩ ሕንጻ ስድስተኛ ፎቅ ድረስ በመምጣት በአገልግሎቱ ተጠቃሚ ኹኑ›› ሲሉ መንፈሳዊ ጥሪአቸውን አቅርበዋል፡፡