በዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተና

የተከበራችሁ አንባብያን እንደምን ሰነበታችሁ? ባለፉት ተከታታይ ዕትሞች ላይ በዘመናችን ቤተ ክርስቲያን የገጠማትን ፈተና በተለይ የቤተ ክርስቲያንን ቃጠሎና የይዞታ መነጠቅን በተመለከተ መጠነኛ መረጃ የሚሰጥ ጽሑፍ ማቅረባችን ይታወቃል፡፡ ቀጣዩን ደግሞ እንደማከተለው አቅርበነዋል፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያለስሟ ስም፣ ያለ ግብሯ ግብር እየተሰጣትና ለማጥፋት ምክንያት እየተፈለገላት መሆኑ እየታየና እየተሰማ ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከቅዱስ ሲኖዶስ እስከ አጥቢያ በተዘረጋው መዋቅር መሥራት የሚገባትን፣ ማኅበራት፣ ዘማርያንና ሰባክያን መፈጸም የሚኖርባቸውን፣ ምእመናንና ምሁራን ማከናወን የሚጠበቅባቸውን ማሳወቅ ዘመኑ የማጠይቀው ተግባር ነው፡፡ በአንድ በኩል ከሌሎች የእምነት ተቋማት ጋር መተባበር እና መረጃ በመለዋወጥ መሥራት የሚገባንን፣ በሌላ በኩል እየተፈጸመ ያለውን ጥፋት ለመንግሥት በማሳወቅ በአጥፊዎች ላይ እርምት እንዲወሰድ ማገዝ ይገባል፡፡ የአጥፊዎችን የተሳሳተ ትርክታቸውንና ለቤተ ክርስቲያን ያላቸውን ጥላቻ እንዲያስወገዱ እንዲያደርግ ማሳሰብ ሲገባ በሌላ በኩል ደግሞ ከዛሬ ነገ ይማራሉ፣ በመረጃ የተደገፈ ትንታኔ በማቅረብ አስተማሪ የሆነ ጽሑፍ ያቀርባሉ ብለን ብንጠብቅም ዝም ማለታችንን እንደ ፍርሃት፣ አለመጻፋችንን እንደ አላዋቂነት ለሚቈጥሩ ወገኖች ሚዛኑን የጠበቀና ትክክለኛ መረጃ መስጠት ይገባል፡፡

ከትላንት እስከ ዛሬ የፈጸሙትን ጥፋት በማሳየት ማን ጥፋተኛ እንደሆነ አንባብያን የራሳቸውን ፍርድ እንዲሰጡ ማንቃትና ለተጨማሪ ንባብ መቀስቀስ ያስፈልጋል፡፡ ‹‹ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮኻል›› አካሔዳቸውን መግለጥ ባልቻልን ምንም እውነትን ብንይዝ ካልተገለጠ ጠቀሜታው ይደበዝዛል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ከአንዳንድ ባለሥልጣናት እየተጠጉ የሚፈጽሙትን ጥፋትም ማጋለጥ ያስፈልጋል፡፡ ሥራ አጥ ወጣቶች ሠርተው የሚበሉበት፣ ምሁራን ተመራምረው ሀገር የሚያበለጽጉበት ተግባር ከመፈጸም ይልቅ ሀገሪቱን ሁሉ ቤተ እምነት ካላደረግን፣ የሚያዩትን ባዶ ቦታ ሁሉ ካልሠራንበት የሚለው አካሔድ እንደ ሀገር አስማምቶ ሊያኖረን እንደማይችል ማስገንዘብ ይገባል፡፡ እውነት እንነጋገር ከተባለ ሰማንያ በመቶ የሚሆነው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታይ ያለው ቤተ እምነትና ፕሮቴስታንትና እስልምና ቢደመር ሃያ በመቶ ባይሆኑም እያንዳንዳቸው ያላቸው ቤተ እምነት ከኦርቶዶክሱ እጥፍ ሊሆን ምንም አይቀረው፡፡ ይህን እያወቅን እንኳ ያልጠየቅነው ከሁሉ በፊት ለሀገር ማሰብና ለሰላም መስፈን መሥራት ይገባል ብለን ስለምናምን ነው፡፡

በቤተ ክርስቲያኗ ላይ እየተፈጸመ ያለው ጥፋት ያሳሰበው ዜና ቤተ ክርስቲያን በጥቅምት ኅዳር ፳፻፲፩ ዓ.ም ዕትሙ ‹‹ለሁሉም በተሰጠው ገደብ የለሽ የእምነት ነፃነት መሠረት፣ ሁሉም የራሱን እምነት በሰላም ማራመድ ሲገባው በተቃራኒው ፀረ ኦርቶዶክስ ዘመቻ በሁለት ግንባር በመካሔድ ላይ ይገኛል፡፡ በአንድ በኩል ቀደም ሲል በዝርዝር እንደተገለጠው ፀረ ክርስትና አቋም ያለው ቡድን በአንዳንድ አካበቢዎች የሚገኙትን የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያን እያቃጠለ ነው፡፡ ካህናትንና ምእመናንንም እያረደ ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ እነ ፖስተር ኢዩ ጩፋን የመሳሰሉት የእነ ሬንሐርድ ቦነኬ ደቀመዛሙርት በቡድን ተሰማርተው ሕዝቡን በወንጌል ሳይሆን በመናፍስት በማስገደድና በካራቴ በማሳመን የእነርሱ ተከታይ ለማድረግ እየጣሩ ነው›› በማለት በርእሰ አንቀጹ ጽፎ ነበር፡፡

የሚገርመው ይህ ጥፋት በመቀነስ ፈንታ እየጨመረ፣ በመሻሻል ፈንታ እየባሰበት መምጣቱ ነው፡፡ የችግሩ መሞከሪያ፣ የጸጥታው ማስፈጸሚያ ቤተ ክርስቲያንና ክርስቲያኖች እስከሚመስሉ ድረስ በክርስቲያኖች ሞትና መከራ ላይ መከራ እየተደረገ ሀገር ትረጋጋለች ተብሎ ስምምነት ላይ የተደረሰ ያስመስላል፡፡ ይህ ጥፋት ሁል ጊዜ ሰበብ እየተፈለገ እንዲቀጥል አንፈልግም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሲቃጠል በግል የተፈጸመ፣ ክርስቲያኖች ሲገደሉ የግል ጠብ እየመሰለ መነገሩ በጀርባው ሌላ ተንኮል ያለ መሆኑን እየተገለጠልን መምጣቱን መረዳት ይገባል፡፡ ሀገር በጠባጫሪነትና ሁሉ ነገር ለእኔ በሚል መንፈስ መገንባት እንደማትችል የታወቀ ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን መረጃው እያለው እንደ ሌለው፣ ግልጽ አድልዎ እየተፈጸመ መሆኑን እያወቀ ዝም ያለው አጥፊዎችም አደብ ይገዛሉ፣ መንግሥትም እርምት ይወስዳል በማለት ነው፡፡ አሁን ግን የሚፈጸመው ጥፋት እየከፋ መጥቷል፡፡ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስን ማኅበር ለመዘከር የቤት ጉዝጓዝ ሊያጭድ የሔደን ክርስቲያን በገጀራ ከትክቶ ሽንት ቤት መክተት፣ በየቦታው ኦርቶዶክሶች እየተመረጡ አካባቢያቸውን እንዲለቁ መደረጉ የአደባባይ ምሥጢር ነው፡፡ ይህ ሲደረግ መረጃው እንዳይወጣ መደበቁ እንደ ሀገርም እንደ ቤተ ክርስቲያንም መሠራት ያለባቸው ጉዳዮች መኖራቸውን የሚያሳዩ ናቸው፡፡

በቤተ ክርስቲያን እንዳይሠለስ እንዳይቀደስ ከማድረግ በተጨማሪ በደቡብ ክልል ጎፋ ዞን የሚገኘው የመሎላሃ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ጥምቀተ ባሕር ሥልጣን ላይ በተቀመጡ የፕሮቴስታንት ተከታዮች ለአውቶቢስ መናኽሪያ መሰጠቱና ታቦትና ንዋያተ ቅድሳታችሁን ይዛችሁ ውጡ ተብለው በእግራቸው ፻ ኪሎ ሜትር በላይ ታቦትና ንዋያተ ቅድሳት ይዘው መንከራተታቸው በፈጠረው የማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን ጫና የተደናገጡ ባለ ሥልጣናት ታቦቱ ወደ መንበሩ እንዲመለሰ ያደረጉበት ታሪክ የሦስት ወር ትዝታ ነው፡፡ እንዲስተካከል የምንፈልገውም እንዲህ አይነቱ መጥፎ ተግባር ነው፡፡ ሕሊናቸው የመራቸውን፣ መንግሥት የሰጣቸውን ኃላፊነት የሚወጡ የሌላ እምነት ተከታይ ወገኖች እንዳሉ ሁሉ የተሰጣቸውን ኃላፊነት ለጥፋት የሚጠቀሙ መኖራቸው፣ በጥፋት ላይ ጥፋት እያስከተለ በመሆኑ በቶሎ መታረም አለበት፡፡

በሶማሌ ክልል አሥር አብያተ ክርስቲያን እንዲቃጠሉና ከሃያ ሰባት በላይ ምእመናን እንዲገደሉ፣ ብዙዎችም እንዲቈስሉ የተደረገው በመንግሥት መዋቅር ነው፡፡ የዚህን ድርጊት ተገቢ አለመሆን የተረዳው አዲሱ የሶማሌ መንግሥት አመራር ቤተ ክርስቲያኗን ይቅርታ መጠየቁን ጠቅላይ ሚኒሰትሩ የደሴ ከተማ ነዋሪዎችን ባወያዩ ጊዜ ሲናገሩ ሰምተናል፡፡ አጥፊዎች ከስሕተታቸው ቢመለሱና አስቀድመው ጥፋት ከመፈጸማቸው በፊት ደጋግመው ቢያስቡ መልካም ነው፡፡ ይህም ባይሆን ከተፈጸመ በኋላም ይቅርታ መጠየቃቸው የሚያሰመሰግን ነው፡፡ ይቅርታ መጠየቁ ብቻውን በቂ ባለመሆኑም ተጨማሪ ተግባራትን መፈጸም ይገባል፡፡ በያዘው ሥልጣን የቤተ ክርስቲያንን ይዞታ እየነቀለ፣ ክርስቲያኖችን የገደለ በቃሉ ብቻ ይቅርታ በማለት እንዳይቀጥል ደንብና ገደብ ቢኖረው መልካም ነው፡፡ ይቅርታው ከስሕተት መታረሚያ፣ ዳግም ስሕተት ላለመፈጸም ቃል መግቢያ እንዲሆን መሥራት ይገባል፡፡ ይህንን ጉዳይ ወደ ፊት ሰፋ አድርገን ስላምናቀርበው በዚሁ እናቁምና በተለያዩ ቦታቸው የተፈጸሙ በምእመናን ላይ የደረሱትን ግድያዎች እናስከትላለን፡፡

ሐ. በምእመናን ላይ የደረሰ ግድያ፡-

ቤተ ክርስትያን ባለችበት ሁሉ ምእመናን አሉ፡፡ ምእመናን ቤተ ክርስቲያናቸው እየተቃጠለች ቆመው ማየት ስለማይችሉ ወይ አብረው ይቃጠላሉ ካልሆነም በአጥፊዎች ይገደላሉ፡፡ ይህም ፍርሃታቸውን ሳይሆን ጥብዓታቸውን፣ በመግደል ሳይሆን በመሞት አሸናፊዎች መሆናቸውን ማረጋገጣቸውን ያሳያል፡፡ በሊቢያ የሚገኘው አሸባሪው አይኤስአይኤስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ክርስቲያኖችን ብቻ መርጦ ለመግደል ሲወስዳቸው በሰማዕታቱ ላይ ይነበብ የነበረው በራስ መተማመን ወደ ሞት ሳይሆን ለንግሥና ታጭተው የሚሔዱ ይመስል ነበር፡፡ ብዙዎች የውጭ ሚዲያ ጋዜጠኞችና የማኅበራዊ ብዙኃን መገናኛ ጸሐፊዎች እንዲህ አይነት ምእመናንን በእምነት አንፃ የምታወጣ ቤተ ክርስቲያን አማኝ መሆን የሚያስገኘውን ክብር ሲገልጡ ነበር፡፡ በአንጻሩ በመግደል እናሸንፋለን ብለው ያሰቡ አሸባሪዎች የሚቀናባቸው ሳይሆን የሚጠቋቆምባቸው ቢያተርፉና የሚተቻቸው ቢያገኙ እንጂ የተስተካከለ አእምሮ ካለው ሰው ምስጋና አያገኙም፡፡ አራት ዓመት ቢያልፍም የክርስቲያኖች ጥብዓታቸው፣ ሞትን ለዘለዓለማዊ ሕይወት መውረሻ መሆኑን ስለአወቁ በደስታ መጓዛቸው ዛሬም ድረስ ይተረካል፡፡ ባለፈው ታኅሣሥ የሊቢያ መንግሥት በጅምላ ተገድለው የተቀበሩበትን ቦታ አግኝቶ ለኢትዮጵያ መንግሥት እንደሚመልስ ሲናገር ክብራቸውን በመግለጥ ጭምር ነው፡፡

የክርስቲያኖች መገደል ተገቢ አለመሆኑን የምንገልጠው በዐዋጅ የሚፈጸም ስለሚመስል እንጂ እንደ ዘመነ ሰማዕታት ክርስቲያኖችን የሚፈጅ መንግሥት ቢሆን ለምን ለማለት አይደለም፡፡ መንግሥት በውጭና በሀገር ውስጥ የነበሩትን አባቶች ማስማማቱ፣ የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሀገር መሆኗን መግለጡ፣ በደርግ ተወስደው የነበሩ ቤቶችን መመለሱ መልካም ነው፡፡ ይህ ብቻ ግን በቂ አይደለም መሬታችን ኦርቶዶክስ ሃይማኖትን እየሰበከ ሕዝቡ የሌላ እምነት ተከታይ እንዲሆን የሚሠሩ ስለአሉ ቆመን ማየት የለብንም፡፡ የአጥፊዎችን ድርጊት ይህንንም በገሀድም ሆነ በስውር የሚደግፉ ስለአሉ መንግሥት መፍትሔ እንዲሰጥ ለማሳሰብ ነው፡፡ መንግሥትን ስናሳስብ የሰማዕትነትን ዋጋ ዘነግተን፣ ሰማዕትነትን ፈርተን ሳይሆን ዕለት ዕለት ሰማዕትነት እንደምንቀበል አምነን ዘመኑ የሚጠይቀውን ለመፈጸም የምንችለውን ሁሉ ለማድረግ ነው፡፡ ይህንንም መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹አይሁድ ስለ ጳውሎስ ከፊት ይልቅ አጥብቀህ እንደምትመረምር መስለህ ነገ ወደ ሸንጎ ታወርደው ዘንድ ሊለምኑህ ተስማምተዋል፡፡ እንግዲህ አንተ በጄ አትበላቸው፤ እስኪገድሉት ድረስ እንዳይበሉና እንዳይጠጡ ተማምለው ከእነሱ ከዐርባ የሚበዙት ሰዎች ያደቡበታልና፤ አሁንም የተዘጋጁ ናቸው፣ የአንተንም ምላሽ ይጠብቃሉ አለው፡፡›› (ሐዋ.ሥ ፳፫፥፳‐፳፪) በማለት የተገለጠውን ማስተዋል ይገባል፡፡ ጥፋትን የሚፈጽሙና የግል ጥቅማቸውን የሚያሳድዱ አካላት ፍትሐዊና ቀና የሆነውን አሠራርና ሕግ ለራሳቸው በሚመች መንገድ የሚጠቀሙበት መሆኑን ይህ ቃል ያስረዳል፡፡ ልንነቃ የሚገባው የአካሔዳቸውን መሠሪነት ነው፡፡ እነሱ ሐሰትን ታሪክ አስመስለው ሲጽፉ ሕሊናቸውን አየቆጠቁጠውም እንዲያውም ለአምላካቸው መብዓ ያቀረቡ የሚመስላቸው አካሔዳቸው ተገቢ አለመሆኑን የሚያስገነዝብ መልስ ሲሰጣቸው ደግሞ መረጃ ይዞ ተከራክሮ እውነቱን ከማውጣት ይልቅ ትክክለኛ ጉዳይ የጻፉትን አካላት ስም በማጥፋትና ጉዳዩን ሌላ መልክ በመስጠተ ሌሎች እንዳይጽፉ ለማድረግ ይሞክራሉ፡፡ የተቀመጡበትን ወንበር መከታ አድርገው ሕዝብን በሕዝብ ላይ እንደማነሣሣት፣ ሃይማኖትን ከሃይማኖት እንደማጋጨት ይቈጥሩታል፡፡ መታወቅ የሚኖርበት ኦርቶዶክሳውያን ሲጽፉ ብቻ ጠብ አጫሪ መባል የማይገባቸው መሆኑን ነው፡፡ የሕዝብ ሰላም የሚያሳጣ፣ ከልማት ጥፋትን የሚያመጣ ተግባር ከፈጸሙ ለዚህ የጥፋት ተልእኮአቸው መልስ መስጠታችን፣ ሕዝበ ክርስቲያኑን ማንቃታችን የማይቀር ነው፡፡ እውነተኞች ከሆኑ የምንለያይበትንና የምንጋጭበትን እየፈለፈሉ በማውጣት ተአማኒነት ያለው ጽሑፍ ማቅረብ ነው፡፡ በዚህ ፈንታ የሚመርጡት በለመዱበት መንገድ መንግሥት በተቀየረ ቊጥር እየተጠጉ ኦርቶዶክሳውያንን ማስጠላት ነው፡፡ ይህን የምንለው እየተፈጸመ ያለው ጉዳይ ለሀገር አንድነት የማይጠቅም በመሆኑ በሌላ በኩል እነሱ በሔዱበት መንገድ መሔድ የሚያደርሰውን ጥፋት በመገንዘብ ነው፡፡

ይቆየን

 ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ፳፮ ዓመት ቁጥር ፲፮