‹‹እግዚአብሔርም የፈጠረው ሁሉ እጅግ ያማረ እንደሆነ ተመለከተ›› (ዘፍ.፩፥፴፩)
በባሕርዩ ክቡር የሆነው እግዚአብሔር የፈጠረው ሁሉ ክቡር ነው። ይሁን እንጂ አበው በብሂላቸው ‹‹ከጣትም ጣት ይበልጣል›› እንዲሉ እጅግ የከበሩ ፍጥረታትም አሉ። ከእነዚህ እጅግ የከበሩ ፍጥረታት ከሚባሉት መካከል በቀዳሚነት የሚገኘው የሰው ልጅ ነው። ስለዚህ የሥነ ፍጥረትን ታሪክ የጻፈልን ሊቀ ነቢያት ሙሴ ሁሉንም ፍጥረታት ከፈጠረ በኋላ ‹‹መልካም እንደሆነ አየ›› እያለን ይመጣና ሰው ላይ ሲደርስ ግን ‹‹እጅግ መልካም እንደሆነ አየ›› በማለት ይደመድማል። ሊቁ ቅዱስ ያሬድም ‹‹ሰንበት ተዐቢ እምኵሉ ዕለት ወሰብእ ይከብር እምኵሉ ፍጥረት፤ ከዕለታት ሰንበት ትበልጣለች፤ ከፍጥረታትም ሁሉ ሰው ይበልጣል›› በማለት እንደነገረን የሰውን ልጅ እጅግ ክቡር ፍጥረት መሆኑን ያስረዳናል። የሰው ልጅ ክቡርነት በተመለከተ መጻሕፍት አምልተውና አስፍተው ይናገራሉ። (ዘፍ.፩፥፴፩)