Entries by Mahibere Kidusan

ዕቅበተ እምነት በመጽሐፈ ምሥጢር – የመጀመሪያ ክፍል

አባ ጊዮርጊስ ብዙ ድርሳናትን ደርሷል፤ የሚበዙት የምስጋና ድርሰቶች ናቸው፡፡ ከጻፋቸው ብዙ መጻሕፍት መካከል አንዱ መጽሐፈ ምሥጢር ነው፡፡ መጽሐፈ ምሥጢር በቤተ ክርስቲያናችን ከሚጠቀሱ የዕቅበተ እምነት መጻሕፍት ውስጥ አንዱ ሲሆን የአባ ጊዮርጊስ የነገረ ሃይማኖት ሊቅነቱ የተመሰከረበት መጽሐፍ ነው፡፡ መጽሐፉ አባ ጊዮርጊስ በነገረ እግዚአብሔር ላይ ጽርፈት የተናገሩ መናፍቃንን ለመገሠጽና ለእነርሱ መልስ ለመስጠት የጻፈው መጽሐፍ ነው፡፡ በምን ዓይነት ቅንዐተ መንፈስ ቅዱስ ተነሣሥቶ መልስ እንደሰጠ ሲነግረን “… የቅዱሳንን ዜናቸውን ለመናገር ፍቅር ግድ ይለኛል፤ ቅንዐትም ከሐዲዎችን እነቅፋቸው ዘንድ ያስገድደኛል፤ ፍቅር ክርስቶስን እንዳመሰግነው ግድ ይለኛል፤ ቅንዐትም ሰይጣንን አወግዘው ዘንድ ያስገድደኛል፤ ፍቅር የክርስቶስን ሐዋርያት እንድከተላቸው ያስገድደኛል፤ ቅንዐትም ዝንጉዎችን እንድዘልፋቸው ግድ ይለያኛል፤ ፍቅር ሰማዕታትን አወድሳቸው ዘንድ ግድ ይለኛል፤ ቅንዐትም ጠንቋዮችን እንድዘልፋቸው ያስገድደኛል” በማለት ይገልጽልናል፡፡

መጽሐፍ ቅዱስ በቤተ ክርስቲያን ዐይን

መጽሐፍ ቅዱስ የቅዱሳት መጻሕፍት ሁሉ ምንጭና ራስ ነው፡፡ ማንኛውም ትምህርት፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ወይም ሥርዐት በመጽሐፍ ቅዱስ ከተጠቀሰው ጋር የሚጋጭ ከሆነ በቤተ የቤተ ክርስቲያናችን ተቀባይነት የለውም፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን የትምህርተ ሃይማኖት ዋና ምንጭ መጽሐፍ ቅዱስ ነው፡፡ የሥርዐትና የታሪክ ዋና ምንጭም መጽሐፍ ቅዱስ ነው፡፡ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን መጽሐፍ ቅዱስ የሚያዘውን የምትፈጽም፣ የምታስተምርና የምትኖር መጽሐፍ ቅዱሳዊት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ መጽሐፍ ቅዱስንም እንድናነበውና እንድንማርበት አዘጋጅታ የሰጠችን እርሷው ናት፡፡ ይሁንና አንዳንድ መናፍቃን መጽሐፍ ቅዱስን የሚከተሉ መስለው ቤተ ክርስቲያን መጽሐፍ ቅዱስን ያልሰበከች አስመስለው ስለሚያቀርቡ ተንኮላቸውን ተረድተን ልንጠነቀቅ ይገባል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የማይለውን እንደሚል አድርገው በማቅረብና አጣመው በመተርጎም የሚስቱ ብዙዎች ናቸው፡፡ ለዚህም ነው ከሁሉ የምትቀድመውን ቤተ ክርስቲያን እየተቃወሙ እርሷ ለዓለም ሁሉ የሰጠችውን ቅዱስ መጽሐፍ የተቀበሉ የሚያስመስሉት፡፡

አንቀጸ መድኃኒት ቤተ ክርስቲያን – ካለፈው የቀጠለ

ክርስቲያኖች በዚህች አንዲት ቤተ ክርስቲያን ስንኖር ከእግዚአብሔር ጋር ያለን አንድነት እያደገ እየጠበቀ ይሔዳል፡፡ ይህ አንድነትም በጊዜ ሒደት፣ ወይም በተለያየ ቦታ በመሆን የሚቋረጥ አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያን በውስጧ ቅዱሳን መላእክትን እንዲሁም በብሔረ ሕያዋን፣ በብሔረ ብፁዓን፣ በገነት፣ በዐጸደ ሥጋና በዐጸደ ነፍስ ያሉትን ምእመናን ሁሉ የምትይዝ አንዲት ኅብረት ናት ማለታችንም ስለዚሁ ነው (ዕብ. ፲፪፡፳፪-፳፬)፡፡ በዐጸደ ነፍስ ያሉት ምእመናን በንስሓ የተመላለሱ፣ ሩጫቸውን የጨረሱና ድል ያደረጉ ሲሆኑ፥ በዐጸደ ሥጋ ያለን ደግሞ ሩጫችንን ገና ያልጨረስንና በተጋድሎ ውስጥ የምንገኝ ነን፡፡ ሐዋርያው እንዲህ እንዳለ፡- “እንዲሁ ብዙዎች ስንሆን በክርስቶስ አንድ አካል ነን” (ሮሜ. ፲፪፡፭)፡፡ ይህ ትምህርት የነገረ ሃይማኖት መሠረት ነው፡፡ እንዲህ የተባለበትም ምክንያት በቤተ ክርስቲያን ምንነትና ማንነት ላይ ያለን ልዩነት ለጠቅላላ ነገረ ሃይማኖት መለያየት ምክንያት ስለሚሆን ነው፡፡

አንቀጸ መድኃኒት ቤተ ክርስቲያን  – የመጀመሪያ ክፍል

ቤተ ክርስቲያን ጉባኤ ናት ሲባል ግን አንዳንዶች እንደሚሉት እንዲሁ የሰዎች ስብስብ ሳትሆን የምርጦች ስብስብ ናት፤ የተጠሩ ብዙ የተመረጡ ግን ጥቂቶች ናቸውና (ማቴ. ፳፡፲፮)፡፡ እነዚህ ጥቂትና የተመረጡትም የልጅነት ሥልጣን የተሰጣቸው (ዮሐ. ፩፡፲፫)፣ እግዚአብሔርን በአንድነቱና በሦስትነቱ የሚያመልኩ፣ “ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ” (ማቴ.፲፮፡፲፮) በሚል ጽኑዕ መሠረት የታነፁ ናቸው እንጂ እንዲሁ በአንድ ቤት ውስጥ የተሰበሰቡ ሰዎች አይደሉም፡፡ ቤተ ክርስቲያን አካለ ክርስቶስና ሕያዊት ናት (ኤፌ. ፩፡፳፪-፳፫)፡፡ የክርስቶስ ሙሽራ (መኃ. ፭፡፩፣ ዮሐ. ፫፡፳፱፣ ራእ. ፳፩፡፱)፣  የእግዚአብሔር ሕያው ቤተ መቅደስ (ኤፌ. ፪፡፳፩)፣ የእውነት ዓምድና መሠረት (፩ኛ ጢሞ. ፫፡፲፭) ትባላለች፡፡

የአሜሪካ ማእከል በእንግሊዝኛ ቋንቋ የሚያስተምሩ ሰባክያንን አሠለጠነ

በዋና ክፍሉ ሪፖርት እንደ ተገለጸው የሥልጠናው ዓላማ ሠልጣኞቹ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ወንጌልን ሊያዳርሱ የሚችሉበትን ዕውቀትና ክህሎት እንዲያዳብሩ ለማገዝ ሲኾን፣ ትምህርተ ሃይማኖት (ዶግማ)፣ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን፣ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን፣ ታሪከ ቤተ ክርስቲያን እና የስብከት ዘዴ በሥልጠናው የተካተቱ የትምህርት ክፍሎች ናቸው፡፡ ሥልጠናው የተሰጠውም በዲሲና አከባቢው ሀገረ ስብከት በአትላንታ ጆርጅያ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ወአቡነ አረጋዊ ቤተ ክርስቲያን ከየካቲት ፱-፲፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም ነው፡፡

ታቦተ እግዚአብሔርን ከጣዖት ጋር አንድ የሚያደርግ ማን ነው? (፪ኛ ቆሮ. ፮፥፲፮)

በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ታቦት ማለት ለዓለም ራሱን መሥዋዕት አድርጎ የሰጠ ለአምላካችንና ለመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋ እና ክቡር ደም የክብር ዙፋን (መሠዊያ) ነው፡፡ በታቦቱ ላይ የሚጻፈውም ቃልም ‹‹አልፋ ዖሜጋ›› (ፊተኛውና ኋለኛው፤ መጀመሪያውና መጨረሻው የዘላለም አምላክ) የሚለው ቅዱስ ስሙ ነው (ራእ. ፳፪፥፲፫)፡፡ በታቦቱ ፊትም የሚሰገደው ለዚህ ቅዱስ ስም ነው፡፡ ‹‹በላይ በሰማይ፣ በታች በምድር የማናቸውንም ምሳሌ እና ቅርፅ በፊትህ አታድርግ፤ አትስገድላቸውም፤›› (ዘፀ. ፳፥፬-፭) የመሳሰሉትን ኃይለ ቃላት በመጥቀስ ታቦት፣ ሥዕል፣ መስቀል አያስፈልግም የሚሉ ሰዎች አሉ፡፡ ኾኖም ይህ ኃይለ ቃል በእግዚአብሔር ፈንታ ለሚመለክ ጣዖት እንጂ የክብሩ መገለጫ ለኾነው ታቦትና እርሱ ፈቅዶ ለሰጠን የቅዱሳን ሥዕልና መስቀል የሚጠቀስ አይደለም፡፡

የክህነት አገልግሎት

የኤልያስ መንፈስ በኤልሳዕ፤ የሙሴ መንፈስ በኢያሱ እንዳደረ የሐዋርያት መንፈስ ያደረበት እግዚአብሔር የመረጠው የገለጠው ክህነት በአበው ጳጳሳት ቅባትና ጸሎት አማካይነት ይታደላል፡፡ አባቶች ጳጳሳት በአንብሮተ እድ ባርከው በንፍሐት እፍ ብለው በእግዚአብሔር ስም ክህነቱን ካላሳደሩበት በቀር ማንም ካህን መኾን አይችልም፡፡ እግዚአበሔር የሾመው ሐዋርያትን ብቻ አይደለም፤ ጳጳሳትንም የሾመው እርሱ ነውና፡፡ ‹‹በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ዂሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሐዋ. ፳፥፳፰)፡፡ ጌታችን ‹‹እውነት እላችኋለሁ፤ በምድር የምታስሩት ዂሉ በሰማይ የታሰረ ይኾናል፡፡ በምድርም የምትፈቱት ዂሉ በሰማይ የተፈታ ይኾናል›› በማለት ለቅዱሳን ሐዋርያት የማሰር የመፍታት ሥልጣን እንደ ሰጣቸው በማያሻማ ኹኔታ በቅዱስ ወንጌል ተቀምጧል (ማቴ. ፲፰፥፲፰፤ ሉቃ. ፳፬፥፶፤ ዮሐ. ፳፥፳፪-፳፬፤ ሐዋ. ፱፥፲፯፤ ፩ኛ ጢሞ. ፬፥፲፭)፡፡

ምልጃ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን

‹‹በዐፀደ ሥጋ ያለውን ምልጃ እንቀበላለን፤ በዐፀደ ነፍስ ግን አይደረግም›› ለሚሉ መጽሐፍ ቅዱስ በዐፀደ ነፍስ ስላለው ምልጃ እንደሚከተለው ያስተምረናል፤ ነፍስ ከእግዚአብሔር የተሰጠች ተመልሳም ወደ እግዚአብሔር የምትሔድ፤ እንድናስብ እንድንናገርና ሕያው ኾነን እንድንኖር ያስቻለችን ረቂቅ ፍጥረት ነች (ዘፍ. ፪፥፯፤ መክ. ፲፪፥፯)፡፡ ስለዚህ ቅዱሳን ዂሉን የሚያውቁት፣ ከሞት (የሥጋ ሞት) በኋላ ሕያው የሚኾኑት፣ የምናናግራቸውና የሚያናግሩን በዚህች ነፍስ ነው፡፡ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም የሙታን ሳይኾን የሕያዋን አምላክ መኾኑን የነገረን ለዚሁ ነው (ማቴ. ፳፪፥፴፪)፡፡ ወደ እግዚአብሔር የሔዱ ቅዱሳን ከዚህ ዓለም ዕረፍታቸው በኋላ በዚህ ዓለም ስለሚኾነው ነገር እግዚአብሔር በገለጠላቸው መጠን እንደሚያውቁ እና እንደሚያማልዱ መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡

ነገረ ድኅነት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን

ቅዱሳት መጻሕፍት የመዳንን መንገድ የሚነግሩን እንድናየው አይደለም፤ እንድንጓዝበት ነው እንጂ፡፡ “… ‹ጌቶቼ፥ እድን ዘንድ ምን ላድርግ?› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እመን፤ አንተ እና ቤተሰቦችህ ትድናላችሁ› አሉት፡፡ የእግዚአብሔርንም ቃል ለእርሱና በቤቱ ላሉት ዂሉ ነገሩአቸው … በዚያው ጊዜ ከቤተ ሰቡ ዂሉ ጋር ተጠመቀ፤” (ሐዋ. ፲፮፥፴-፴፬)፡፡ ከዚህ ላይ ‹‹ድናችኋል›› ሳይኾን ‹‹ትድናላችሁ›› የሚለውን ቃል ልብ ይሏል፡፡ “ዳግመኛ ከውኃ እና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ሰው ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም” እንዳለ (ዮሐ. ፫፥፭)፡፡ ስለዚህ ሰው አምኖ ይጠመቃል፤ ከእግዚአብሔርም ይወለዳል፤ በዚህ ድኅነትን ገንዘብ ያደርጋል፡፡ ከእግዚአብሔር ካልተወለደ በፍጹም ሊድን አይችልም፡፡ መዳን ማለት የእግዚአብሔርን መንግሥት ወርሶ ስሙን ቀድሶ መኖር ነው፡፡ ስለዚህ የሕይወት እና የድኅነት ወንጌል ለዓለሙ ዂሉ ይሰበካል፤ ዂሉም ይድን ዘንድ (ማር. ፲፮፥፰)፡፡

አውጣኪ፣ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ እና የኬልቄዶን ጉባኤ – ካለፈው የቀጠለ

በጉባኤው ፓትርያርክ ዲዮስቆሮስ እምነቱን እንዲገልጽ ተጠይቆ ሁለቱ ባሕርያት (የመለኮትና የሥጋ) ያለ መቀላቀልና ያለ ትድምርት፣ ያለ መለወጥና ያለ መለያየት በአንድ አካል እንደተዋሐዱ በሚገባ አስረዳ፡፡ እንዲሁም በቅዱስ ቄርሎስ ትምህርት መሠረት ‹‹አአምን በአሐዱ ባሕርይ (ህላዌ) ዘቃለ እግዚአብሔር ሥግው፤›› ብሎ አስረዳ፡፡ ጉባኤውም በዚህ በዲዮስቆሮስ እምነት ላይ ምንም እንከን፣ ምንም ስሕተት አላገኘም፡፡ ጉባኤው በሌላ መንገድ ‹‹አውጣኪ በጽሑፍ ካቀረበው የተለየ በቃል ቢናገር ምን ትፈርድ ነበር?›› ብለው በጠየቁት ጊዜ፣ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ‹‹አውጣኪ የጻፈውን ትቶ ሌላ የክህደት ነገር ቢናገር፣ እሱን ማውገዝ ብቻ ሳይሆን በእሳትም እንዲቃጠል እፈርድበት ነበር፤›› ብሎ መለሰ፡፡ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ በእንደዚህ ያለ ነጐድጓዳዊ አነጋገር ሁሉን ግልጥልጥ አድርጎ በተናገረ ጊዜ፣ ኬልቄዶናውያን ጸጥ አሉ፡፡ ዲዮስቆሮስን በመቃወም የተናገሩ የምሥራቅ አህጉር ጳጳሳት ግን ንግግሩ ልባቸውን ነክቶት ‹‹በድለናል፤ ይቅርታ እንጠይቃለን!›› በማለት ጮኹ፡፡