የቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ምልዓተ ጉባኤ መጠናቀቁን አስመልክቶ መግለጫ ተሰጠ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!
ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ
በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የሚመራው፣ የሐዋርያት መንበር ወራሽ የሆነው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ
“ወይኩን ጉባኤ ሊቃነ ኤጴስ ቆጶሳት ወኤጲስ ቆጶሳት ክልዔተ ጊዜ በበዓመት ወይትናገሩ በእንተ ግብረ አብያተ ክርስቲያናቲሆሙ ወያሰስሉ ዕቅፍታተ …
የሊቃነ ጳጳሳትና የጳጳሳት ምልዓተ ጉባኤ በዓመት ሁለት ጊዜ ይሁን ስለአብያተ ክርስቲያናት የሚገባውን ሁሉ ይነጋገሩ የሐዋርያዊ ተልእኮ መሰናክሎችንም ሁሉ ያስወግዱ” ተብሎ በመጀመሪያው የሐዋርያት ቀኖና፣ በሁለተኛው ቀሌምንጦስ በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው ከጥቅምት 11 – ጥቅምት 17 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ስለ ቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና የምጣኔ ሀብት ዕድገት፣ ስለ ሀገር ሰላምና አንድነት፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደርና ሐዋርያዊ ተልእኮ መስፋፋት ስለ ሰው ልጅ ሁሉ ደኅንነት ሰፊ ውይይት አድርጓል፡፡
ወቅቱን ያማከሉና ዘላቂ የቤተ ክርስቲያንን ተቋማዊ ሕልውና የሚያረጋግጡ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ልዕልናንን የሚያስጠብቁ፣ ለምእመናን ደኅንነትና ለአገልጋዮች ሕይወት በሚጠቅሙ፣ መንሳፈዊ አስተዳደርንና ማኅበራዊ ጉዳዮችን መሠረት ባደረጉ አጀንዳዎች ላይ በመንፈስ ቅዱስ አንድነት በመወያየት ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን ጠቃሚ የሆኑ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡
በዚሁ መሠረት፡-
1.ሁለንተናዊ ሰላምና መረጋጋት የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሃይማኖታዊ መሠረቷ፥ የሥርዓተ ቅዳሴዋና የምሥጢራት አገልግሎቷ አካል፣ የመንፈሳዊና ማኅበራዊ ሥምሪቷ ማእከላዊ ዐምድ በመሆኑ በግንቦት 2017 ዓ.ም. ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተሠየመው የሀገራዊ ሰላምና የቤተ ክርስቲያን አንድነት ኮሚቴ ሥራውን አጠናክሮ እንዲቀጥል፤ የደረሰበትንም ውጤት ለግንቦት 2018 ዓ.ም ምልዓተ ጉባኤ እንዲያቀርብ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥብቅ መመሪያን አስተላልፏል::
2.በትግራይ አህጉረ ስብከት የሚገኘው ሕዝበ ክርስቲያን ሕዝባችንና ወገናችን ስለሆነ አብያተ ክርስቲያናቱና ገዳማቱም የቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ ሀብቶች በመሆናቸው፣ አህጉረ ስብከቱም የተደራጁት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በመሆኑ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሕግና ቀኖና ተጠብቆ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ልዕልና ተከብሮ፣ የመዋቅር ግንኙነቱን ወደ ቀደመ ቦታው እንዲመለስ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የሰላም፣ የአንድነትና የይቅርታ በር ክፍት መሆኑን ከመግለጽ ጋር ቅዱስ ሲኖዶስ በክልሉ ለሚገኙት አባቶች፣ ካህናትና ምእመናን ያልተቋረጠ የሰላም ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡
የቀድሞዎቹ ቅዱሳን አባቶቻችን ዋጋ ከፍለው፣ ቀኖናዊ ሥርዓቷንና ክብሯን ጠብቀውና አስጠብቀው ፣ አንድነቷን አጽንተው ያወረሱንን አሐቲ ቤተ ክርስቲያን የቀደመ ሉዓላዊ ክብሯ እንደተጠበቀ ለመጭው ትውልድ ማስተላለፍ የበለጠ ዋጋ ያሰጣልና ቀደም ሲል ለዚሁ ጉዳይ የተሠየመው ኮሚቴ ሥራውን አጠናክሮ እንዲቀጥል፣ ሊቃውንቱ፣ ካህናቱና መላው ሕዝባችንም የቤተ ክርስቲያንን አንድነት ለማጠናከር በሚደረገው ጥረት ሁሉ የበኩላችሁን እንድትወጡ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በአጽንኦት ያሳስባል፡፡
3.ቅዱስ ሲኖዶስ አባት እንዲመደብላቸው ጥያቄ ባቀረቡ አህጉረ ስብከት ዙሪያ የውሳኔ ሐሳብ የሚያቀርቡ ብፁዓን አባቶችን በመሰየምና ተገቢውን ውይይት በማድረግ፡
ሀ) ብፁዕ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ የኢሉ አባቦራ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከትን ደርበው እንዲመሩ፣
ለ) ብፁዕ አቡነ ቶማስ የአዊና መተከል አህጉረ ስብከት ሊቀጳጳስ የምሥራቅ ጎጃምን ሀገረ ስብከት ደርበው እንዲመሩ፣
ሐ) ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የደቡብ ወሎና ከሚሴ አህጉረ ስብከትን ደርበው እንዲመሩ፣
መ) ብፁዕ አቡነ ኒቆዲሞስ የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ጳጳስ የምሥራቅ ወለጋና ሆሮ-ጉድሩ ወለጋ አህጉረ ስብከትን ደርበው እንዲመሩ
ሠ) በተጨማሪም የሸካ ዞን ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ተብሎ ራሱን ችሎ በሀገረ ስብከት ደረጃ እንዲቋቋም፣ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል ሀገረ ስብከቱን እንዲያደራጁና እንዲመሩ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
4.ነባሩና ጥንታዊው የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ገድል እንደተጠበቀ ሆኖ ገድለ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ በሚል ያለአግባብ በአንድ ግለሰብ ተዘጋጅቶ እየተሠራጨ ያለው መጽሐፍ በሊቃውንት ጉባኤ ተመርምሮ ያለበት ግድፈትና የስሕተት ትምህርት በሙሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክሰ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ የማይወክል ሆኖ በመገኘቱ ተወግዟል፤
በውስጡ የያዛቸውም የተሳሳቱ ትምህርቶች በሙሉ ተቀባይነት ስለሌላቸው መጽሐፉ ለጥናትና ምርምርም ሆነ ለማጣቀሻ አገልግሎት እንዳይውል፣ በሥርጭት ላይ የዋለው መጽሐፍ እንዲታገድና በድጋሚም እንዳይታተም፣ ለየአህጉረ ስብከቱ ሠርኩላር እንዲተላለፍ፣ የአፈጻጸም ክትትል እንዲደረግና አጠቃላይ ሁኔታው በሊቃውንት ጉባኤ በኩል በሚዲያ እንዲገለጽ፣ የአስተምህሮ ስሕተትን በማካተት አሳትመው ያሰራጩት ግለሰብ በቋሚ ሲኖዶስ ተጠርተው እንዲጠየቁና የፈጸሙትን ስሕተት ዐውቀው ወደፊት ተመሳሳይ ስሕተት እንዳይፈጽሙ ጥብቅ መመሪያ እንዲሰጣቸው፣
መጽሐፉ እንዲመረመር ያደረገው የደብረ ሊባኖስ አንድነት ገዳምና የገዳሙ የቅኔ መምህር መጋቤ ምሥጢር አባ ክንፈሚካኤል ወልደ ገብርኤል የምስጋና ደብዳቤ እንዲጻፍላቸው ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
5.በሰሜን ካሊፎርኒያ ኔቫዳና አሪዞና ሀገረ ስብከት የኆኅተ ሰማይ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ወቅድስት አርሴማ አንድነት ገዳም መንፈሳዊ ኮሌጅና የአብነት ምስክር ጉባኤ ቤት ለማቋቋም በጠየቀው መሠረት እንዲፈቀድ ሆኖ የትምህርት አሰጣጥ ፖሊሲውና ሥርዓተ ትምህርቱ፣ የሰው ኃይል አደረጃጀቱና መዋቅራዊ ተጠሪነቱ ተዘጋጅቶ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ተጠንቶ ከውሳኔ ሐሳብ ጋር ለግንቦት 2018 ርክበ ካህናት ምልዓተ ጉባኤ እንዲቀርብ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፤
6.በምዕራብና በመካከለኛው ካናዳ የሚገኙት ሁለቱ አህጉረ ስብከት ከአሁን በፊት በ2017 ዓ.ም. በተሰጠው ውሳኔ መሠረት ያለ ጣልቃ ገብነት በየራሳቸው እንዲተዳደሩና የኤድመንተንና አካባቢው ሀገረ ስብከት የመካከለኛው ካናዳ ኤድመንተንና አካባቢው ሀገረ ስብከት በሚል ሥያሜ እንዲስተካከል ምልዓተ ጉባኤው ወስኗል፡፡
7.በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት በምንጃር ሸንኮራ ወረዳ በአረርቲ ደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን በዓል ለማክበር ሄደው አዲሱን ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን በመጐብኘት ላይ እያሉ አደጋ በደረሰባቸው ምዕመናን የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተሰማውን ሐዘን እየገለጸ እግዚአብሔር አምላካች ላረፉት ወገኖቻችን ዕረፍተ ነፍስ እንዲሰጥልን ከመጸለይ ጋር አካላዊ ጉዳት የደረሰባቸውን ወገኖች ለማሳከምና የተጎጂ ቤተሰቦችን ለመርዳት የገንዘብ ድጋፍ እንዲደረግ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡ ለወደፊቱም በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ዙሪያ በሚገነቡ ሕንጻ ግንባታዎች አደጋ ከመድረሱ በፊት ከፍተኛ ጥንቃቄ እንዲደረግ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንዖት ያሳስባል፤
8.በመላው ኢትዮጵያ በሚገኙ ገዳማት ያሉት መነኰሳትና መነኰሳይያት ለአገልግሎትና ጉዳይ ለማስፈጸም ወደ አዲስ አበባ ሲመጡ ክብራቸውና ገዳማዊ ሕይወታቸው ተጠብቆ ጉዳያቸውን እስከሚፈጽሙ ድረስ የገዳማት ኅብረቱ ባቀረበው ጥያቄ መሠረት በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት በኩል ማረፊያ የሚሆን ቦታ እንዲዘጋጅላቸው፣
የአንድነት ገዳማት ኅብረቱ መተዳደሪያ ደንብ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሕግ አገልግሎት መምሪያ በኩል ታይቶና ተመርምሮ እንዲቀርብ፣
በአጠቃላይ በአንድነት ገዳማት ኅብረት የቀረበው የገዳማውያንና ገዳማውያት ማረፊያ እና የገቢ ማስገኛ ሁለገብ ሕንጻ ግንባታ የትግበራ ዕቅድ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት በኩል በዘርፉ ባለሙያዎች ታይቶና ተገምግሞ ከባለሙያ አስተያየቶችና የውሳኔ ሐሳብ ጋር ተጠንቶ ለግንቦት 2018 ርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ እንዲቀርብ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ወስኗል፡፡
9.በበዓላት አከባበር፣ በመንፈሳዊ አገልግሎት አፈጻጸም ዙሪያ የሚታዩ ግድፈቶች፣ ያልተገቡ እንቅስቃሴዎችና ከሥርዓት የወጡ የአገልግሎት አፈጻጸሞች መታረም ስላለባቸው በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት በሚሰየሙ ሊቃውንትና ባለሙያዎች ለመመሪያና ለማስተማሪያ የሚሆን ሰነድ ተዘጋጅቶ እንዲቀርብ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ተገቢውን ውሳኔ ያስተላለፈ መሆኑን እየገለጽን ያለጠባሳ የሚያድኑ ሐኪሞች፣ ያለቅሬታ የሚያስታርቁ ሽማግሌዎች በነበሩባትና ባሉባት ሀገር ተመካክሮ ችግርን አለመፍታት ተገቢ አይደለምና ሀገራችንን እንወዳለን፣ ሕዝባችንን እናከብራለን የምትሉ፣ የዜጎችን ደኅንነት የማስጠበቅ ኃላፊነት ያለባችሁ ሁሉ ክቡር የሆነው የሰው ልጅ ሕይወት በከንቱ እንዳይጠፋ፣ አካሉ እንዳይጐድል የሀገር ልማትና መልካም ገጽታ እንዳይበላሽ ጠላት መባባሉ ቀርቶ፣ የጦር መሣሪያ ትግል ተወግዶ፣ በእኩልነትና በመስማማት ሰላማዊ የችግር አፈታት መንገድን ተከትላችሁ በውይይትና በጥበብ ልዩነቶችን በመፍታት የተሟላ ሀገራዊ ሰላም እንዲሰፍን ታደርጉ ዘንድ ቅዱስ ሲኖዶስ ከአደራ ጭምር ሐዋርያዊ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡
በመጨረሻም የሀገራችን ኢትዮጵያና የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን ሕልውና ስለማይነጣጠሉ፣ ሀገራችን በሉአላዊነቷ እንድትቀጥል የቤተ ክርስቲያናችን የአንድነት መዋቅሯ የበለጠ ተጠናክሮ፣ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮዋ ሰፍቶ፣ ለትውልድ እንድትሻገር፣ ሕዝባችን ደኅንነቱና ሰላሙ ተጠብቆ እንዲኖር ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ጀምሮ ሁሉም የቤተ ክርስቲያናችን መምህራን፣ ካህናትና ሕዝባውያን፣ መነኰሳትና መነኰሳይያት በሙሉ በፍቅርና በአንድነት ዘወትር በመጸለይ ዘመኑ ከደረሰበት አሠራርና ጥበብ በላቀ ሁኔታ ከፍ ብለን ትውልዱን ለመዋጀት እንድንችል የበኩላችሁን እንድትወጡ በማሳሰብ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ዓመታዊ ስብሰባውን አጠናቋል፡፡
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ አሜን!
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም
ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
ጥቅምት ፲፯/፳፻፲፰ ዓ.ም
አዲስ አበባ – ኢትዮጵያ
