ሕያውን ከሙታን መካከል ስለምን ትፈልጋላችሁ? ሉቃ. ፳፬፥፭

ቀሲስ ሰሎሞን ወንድሙ

በኦሪት ዘፀአት ፲፪፥፳፩-፳፰ እንደተጻፈው ይህ ዕለት በብሉይ ኪዳን ፋሲካ በመባል ይታወቃል፡፡ ትርጉሙም መሻገር ማለት ነው፤ ይህም ሕዝበ እሥራኤል ከግብጽ ባርነት ነጻ ወጥተው ወደ ምድረ ርስት የተሸጋገሩበት ዕለት ነው፤ በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ትንሣኤ ይባላል፡፡ በዓለ ትንሣኤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን በሞቱ ድል ነሥቶ ነጻነትን ለሰው ልጆች ሰጥቶ ከሞት ወደ ሕይወት፤ ከኀሳር ወደ ክብር የተሸጋገርንበት ዕለት በመሆኑ ትንሣኤ እንለዋለን፤ ቅዱስ ሉቃ.  ፳፬፥፭ የጻፈውን ኃይለ ቃል መነሻ በማድረግ ስለ በዓለ ትንሣኤ ጥቂት ዐበይት ነገሮችን እንመልከት፡፡

ሕያውን ከሙታን መካከል ስለምን ትፈልጋላችሁ? ይህንን ጥያቄ የጠየቀው በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር አጠገብ የነበረው የእግዚአብሔር መልአክ ሲሆን ጥያቄው የቀረበላቸው ደግሞ በማለዳ ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር የሄዱት ቅዱሳት አንስት ነበሩ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዋለበት ውለው ባደረበት አድረው የቃሉን ትምህርት የእጁን ተአምራት ያዩት ቅዱሳት እናቶች የሳምንቱ የመጀመሪያ ቀን በተባለች በዕለተ እሑድ በማለዳ የመቃብሩን ጠባቂዎችና የሌሊቱን ጨለማ ሳይፈሩ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሥጋ ሽቱ ለመቀባት ገሰገሡ፡፡ መልአከ እግዚአብሔር ይህንን ጥያቄ  በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መቃብር አጠገብ አቀረበላቸው፤ ቅዱሳት አንስት የመልአኩን ጥያቄ እንደሰሙ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሦስተኛው ቀን ከሙታን እንደሚነሣ የተናገረውን ቃል አስታወሱ፡፡ ከዚያም ቅዱሳት አንስት ወደ ሐዋርያት ሄደው ያዩትንና የሰሙትን ሁሉ ተናገሩ፤ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤውን አበሠሩ፤ ቅዱሳን ሐዋርያትም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሕያዋን እንጂ የሙታን አምላክ አለመሆኑን በግልጽ ተረዱ፡፡ የተሰቀለውን የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ነገረ ሕማሙንና ትንሣኤውን፤ በአባቱ ዕሪና በልዕልና መቀመጡን  ዞረው አስተምረዋል፡፡

በዓለ ትንሣኤ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዐበይት በዓላት አንዱ ነው፤ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስቅለት ተስፋ አበውና ትንቢተ ነቢያት ተፈጽሞ በትንሣኤው የሞት ሥልጣን በመሻሩ የቤተ ክርስቲያን አበው በዓለ ትንሣኤን «የበዓላት በኵር» በማለት ይጠሩታል፡፡ የጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሕማምና ሞት አሳዛኝ ታሪክ ሳይኾን ሕያው እውነት ነው፤ የዓለም መድኃኒት የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ የሐዋርያት ስብከት፤ የቤተ ክርስቲያን መሠረት ነው፡፡ ስለዚህም ዘወትር በጸሎተ ቅዳሴያችን ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር መሞታችንን፤ ከእርሱ ጋር መነሣታችንንና ሕያው መሆናችንን እንገልጻለን፤ ሕማሙንና ሞቱን፤ ትንሣኤውን፤ ዕርገቱንና ዳግም ምጽአቱን እንሰብካለን፡፡ በበዓለ ትንሣኤ በዕለተ ስቅለት የነበረው የኀዘን ዜማ በታላቅ የደስታ ዜማ ይተካል፤ በዚህ ዕለት ቤተ ክርስቲያን ነጭ ልብስ ለብሳ የደስታ ዝማሬ ታሰማለች፡፡

ከነቢያት ወገን ታላቁ ነቢይ ኤልያስ እንዲሁም ደቀ መዝሙሩ ኤልሳዕም በእግዚአብሔር ኃይል ሙታንን እንዳስነሡ ይታወቃል፤ በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ ፰ ቍጥር ፲፬ ታሪኳ የተጻፈው የምኵራብ አለቃ የነበረችው ልጅ፤ በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ ፯ ቍጥር ፲፪ ታሪኩ የተጻፈው ናይን በምትባል ሥፍራ የነበችው የድሃዪቱ ልጅ እንዲሁም በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ፲፩ ታሪኩ የሚነበበው አልአዛር በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተአምራት ከሙታን ተነሥተዋል፡፡ ዳግመኛም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዓርብ በቀራንዮ ኮረብታ ተሰቅሎ ቅድስት ነፍሱን ከቅድስት ሥጋው በለየበት ሰዓት ቍጥራቸው ከስድስት መቶ የሚያንስ ከአምስት መቶ የሚበልጥ ሰዎች ከሙታን ተነሥተዋል፡፡ ነገር ግን ሁሉም ዳግመኛ ሞተዋል፤ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ግን ከሁሉ ይለያል፤ እርሱ ከሙታን ለመነሣት አሥነሽ አላስፈለገውም፣ ከሙታን የተነሣው በራሱ ሥልጣን ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  በማይሞት፤ በማይለወጥ ሥጋ በመነሣቱ እንደሌሎች ዳግመኛ ሞትና ትንሣኤ የለበትም፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ በቀዳማዊ ቆሮንቶስ ምዕራፍ ፲፭ ቍጥር ፳፫ እንደተናገረው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  ሙስና መቃብርን አጥፍቶ(በማይሞትና በማይበሰብስ ሥጋ) በሞቱ ሞትን ድል ነሥቶ፤ የሞት መውጊያን አሸንፎ፤ ሲኦልን በዝብዞ ከሙታን በመነሣቱ የትንሣኤያችን በኵር(መሪ) ተብሏል፡፡ ዳግመኛም ይህ ሐዋርያ በቆላስይስ መልእክቱ ምዕራፍ ፩ ቁጥር ፲፰ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን «የሙታን በኵር» በማለት ጠርቶታል፡፡

የድኅነታችን አለኝታ የእግዚአብሔር ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ በሕማሙና በሞቱ የዲያብሎስን ቁራኝነት በማጥፋት አጋንንትን ድል የመንሣትን ኃይል ሰጥቶናል፡፡ ከጥንት ዠምሮ የሰውን ነፍስ የሚጎዳ የዲያብሎስን ሥልጣን ያጠፋ ዘንድ ፤ የፈጠረውን ዓለም ያድን ዘንድ የሕያው እግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ በእርሱ ፈቃድ፤ በአባቱ ፈቃድና በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ወደዚህ ዓለም መጥቷል፡፡ የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን  ለመስቀል ሞት አሳልፎ በመስጠት በሥጋው ሞቶ በመለኮቱ ሕያው ሆነ፡፡ የሞት አበጋዝን ዲያብሎስን ኃይል ያጠፋ ዘንድ የማይሞተው የሕያው እግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ በመልዕልተ መስቀል ሞተ፤ ሕይወት መድኃኒት በምትሆን ሞቱ ሞትን ያጠፋ ዘንድ፤ ሙታንን ያድን ዘንድ እርሱ የሕያው አምላክ ልጅ ሞተ፡፡ በኪሩቤል ላይ ያለው እርሱ በከርሠ መቃብር ሦስት መዓልትና ሌሊት አደረ፡፡ ያን ጊዜ ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአባታችን በአዳም በደል ተግዘው ወደ ሲኦል የወረዱት ነፍሳት በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ ነጻ አወጥቷቸዋል፡፡ ለቅዱሳን ደቀ መዛሙርቱና ለንጹሐን ሐዋርያቱ እንደተናገረው በሦስተኛው ዕለት በሥልጣኑ ከሙታን ተነሥቷል፤ በዚህም ሙስና መቃብርን(በመቃብር ውስጥ መፍረስ መበስበስን) አጥፍቶልናል፤ ዳግመኛ ሞት የሌለበትን ትንሣኤ አስቀድሞ በመነሣቱ ለትንሣኤያችን በኵር ኾኖልናል፤ ቆላ.  ፩ ፥ ፲፰፡፡ በትንሣኤውም ትንሣኤያችንን ገልጦልናል፤ ከሞት ወደ ሕይወት መልሶናል፤ ፀሐየ ጽድቅ ኢየሱስ ክርስቶስ በትንሣኤው ለሰውነታችን ትንሣኤን፤ ለነፍሳችን ሕይወትን ሰጥቶናል፤ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ፲፩ ቍጥር ፳፭ እንዳስተማረን እርሱ ትንሣኤና ሕይወት ነው፤ እርሱ የሕይወታችን መገኛ ነው፡፡

በዓለ ትንሣኤን ስናከብር ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሕያዋን እንጂ የሙታን አምላክ አለመሆኑን ማስተዋል ይገባናል፤ የእግዚአብሔር መልአክ በመቃብሩ አጠገብ ለተገኙት ሴቶች እንደነገራቸው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሕያዋን መካከል እንጂ በሙታን መካከል አይገኝም፡፡ አባታችን አዳም የማይገባውን አምላክነት ሽቶ ዕፀ  በለስን በመብላቱ ሞተ ሕሊና፤ ሞተ ሥጋ እንዲሁም ሞተ ነፍስ አግኝቶታል፡፡ ዳግመኛም በርደተ መቃብር ላይ ርደተ ሲኦል ተፈርዶበት ነበር፡፡ ሞተ ሕሊና በኃጢአት መኖር ነው፡፡ ንዋይ ኅሩይ ቅዱስ ጳውሎስ በኤፌሶን ምዕራፍ ፪ ቁጥር ፩ «በበደላችሁና በኃጢአታችሁ ሙታን ነበራችኹ» በማለት እንደጻፈው በኃጢአት መኖር ሞት ነው፤ ዳግመኛም ሐዋርያው እንዳስተማረን የኃጢአት ደመወዝ ሞት ነው፤ ሞተ ሥጋ የሥጋ ከነፍስ መለየት ነው፤ ሞተ ነፍስ ደግሞ የነፍስ ከጸጋ እግዚአብሔር መለየት ነው፡፡ በአንጻሩ ትንሣኤም በሦስት ወገን ይታያል፤ ትንሣኤ ሕሊና(ልቡና) በንስሐ ወደ እግዚአብሔር መመለስ፤ ትንሣኤ ዘሥጋ እንደወለተ ኢያኢሮስ፤ እንደአልአዛር ከሞት መነሣት በኋላም በትንሣኤ ዘጉባኤ ከሞት መነሣት ነው፤ ትንሣኤ ነፍስ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ምጽአት በቀኝ መቆም ነው፡፡

ከንስሐ ሕይወት ተለይቶ ከቅዱስ ሥጋውና ከክቡር ደሙ ርቆ ስለኃጢአታችን የተሰቀለውን ኢየሱስ ክርስቶስን ማግኘት ከእርሱም ጋር መኖር አይቻልም፡፡ ሞትን ድል አድራጊው የሕይወት ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ ከእኛ ጋር የሚሆነው እኛም ከእርሱ ጋር መኖር የምንችለው ለኃጢአታችን ሥርየት በቀራንዮ አደባባይ የተቆረሰውን ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ተቀብለን ሕያዋን ስንሆን ነው፡፡ ፋሲካን መፈሰክ የሚገባን የዓለምን ኃጢአት ለማስወገድ በተሠዋው በእግዚአብሔር በግ በኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋና ደም እንጂ በእንስሳት ሥጋና ደም ሊሆን አይገባም፡፡ ለትንሣኤ በዓል ሊያስጨንቀን የሚገባው በገንዘባችን የምንገበየው ምድራዊ መብል መጠጡ ሳይሆን በጥበበ እግዚአብሔር ጸጋ ሆኖ የተሰጠን ቅዱስ ሥጋውንና ክብር ደሙን አለመቀበላችን ነው፡፡ በዓለ ትንሣኤ ሕያው አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመካከላችን ይገኝ ዘንድ በትንሣኤ ልቡና ሕያዋን የምንሆንበት መንፈሳዊ በዓል ነው፤ ስለዚህም በዓለ ትንሣኤን ስናከበር በትንሣኤ ሕሊና ሕያዋን ሆነን ቅዱስ ቍርባን መቀበል ይገባናል፡፡

 ተስፋ ትንሣኤን የምናምን ክርስቲያኖች ዘመናችን ሳይፈጸም የምሕረትና የፍቅር እጆቹን ዘርግቶ ወደሚጠራን ሕያው አምላክ በንስሐ እንቅረብ፤ በፈሪሃ እግዚአብሔር በፍጹም ፍቅር የተሰጠንን ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን እንቀበል፡፡ ያንጊዜ ትንሣኤ ልቡና እናገኛለን፤ ያን ጊዜ በምሕረቱና በፍቅሩ በትንሣኤ ዘጉባኤ በክብር ተነሥተን በቀኙ እንቆማለን፤ የሰው ዐይን ያላየውን፤ ጀሮ ያልሰማውን፤ የሰው ልብ ያላሰበውን ዓለም ሳይፈጠር ለወዳጆቹ ያዘጋጀውን ተድላ ነፍስ የሚገኝበትን ገነት መንግሥተ ሰማያትን እንወርሳለን፡፡

 ለመንግሥቱ ጥንት ወይንም ፍጻሜ የሌለው የሕያው አምላክ ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ መድኃኒት በምትሆን ሞቱ የእኛን ሞት ወደ ሕይወት ለውጦ ቅድስት ትንሣኤውን ገልጦልናል፤ ብርሃነ ትንሣኤውን አሳይቶናል፡፡ የቆጵሮሱ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ መልሕቅ በሚባል መጽሐፉ «በትንሣኤውም የትንሣኤያችንንም ተስፋ ምሥጢር እንናገራለን» በማለት እንደተናገረው ዳግመኛም በኒቅያ የተሰበሰቡ አበው «የሙታንን መነሣት የሚመጣውንም ሕይወት ተስፋ እናደርጋለን» በማለት በቀኖና ሃይማኖት እንደጻፉልን ክርስቲያኖች በመቃብር ያሉ፤ በተለያየ አሟሟት የሞቱ ሙታን ሁሉ የሚነሡበት ትንሣኤ ሙታን መኖሩን እናምናለን፡፡

 ሕያው አምላካችን ሕያዋን ሆነን እንኖር ዘንድ በመስቀሉ ወደ ሰማያዊ አባቱ አቅርቦናል፤ በእርሱና በእኛ መካከል የነበረውን የጥል ግድግዳ አፍርሶልናል፤ በቅድስት ትንሣኤው ትንሣኤ ልቡና የንስሐ በር ከፍቶልናል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማኅየዊት በምትሆን ሞቱ የገነት ደጅን ከፍቶልናል፤ ፍሬዋንም ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ሰጥቶናል፤ ስለዚህም ሕያዋን እንሆን ዘንድ ወደ ሕይወት መድኃኒት ቀርበን ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን እንቀበል፡፡ በሕይወታችን ሞተ ሥጋ ሞተ ነፍስ እንዳይሠለጥንብን፤ ትንሣኤ ሕሊና ትንሣኤ ነፍስን እናገኝ ዘንድ የትንሣኤን በዓል በሕያውነት ጸንተን እንኖር ዘንድ ምግባር ትሩፋት በመሥራት እናክብር፡፡

የትንሣኤን በዓል ስናከበር ጽኑ ድቀትን፤ ኀፍረትንና ውርደትን አብዝቶ በመብላትና በመጠጣት፤ በጭፈራና በዳንኪራ፤ በጣፋጭ መብልና መጠጥ ሰውነትን ማድከምና ልዩ ልዩ ኅብረ ኃጢአት ከመሥራት እንራቅ፤ ክብረ በዓልን ምክንያት በማድረግ በኃጢአት በፍዳ እንዳንያዝ እንንቃ፡፡ በኃጢአት የተነሣ ተስፋ ትንሣኤ እንዳናጣ ዛሬ በንስሐ እንታጠብ፤ ትንሣኤ ሕሊና እናገኝ ዘንድ እንፍጠን፤ በትንሣኤ ዘጉባኤ እጥፍ ዋጋ የምናገኝበትን ለሌሎች በጎ ማድረግን፤ ለድሆች ማካፈልን፤ ሕሙማን መጎብኘትን ገንዘብ እናድርግ፡፡

የጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይቅርታውና ቸርነቱ ለዘለዓለሙ ከእኛ ጋር ይሁን፤  የአባቶቻችን ጥርጥር የሌለባት የቀናች ሃይማኖታቸው፤ ድል የማትነሣ ተጋድሏቸው የመንግሥቱ ወራሽ እንድንሆን ያብቃን፤ አሜን፡፡

የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስቅለት

በተክለ አብ

በጲላጦስ ዘመን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጅ በገባለት ቃል ኪዳን መሠረት፤ ትንቢቱም ይፈጸም ዘንድ መከራን ተቀበለ፤ ጲላጦስ በ፫ ሰዓት ይሰቅል ዘንድ ሲፈርድበትም፤ ‹‹መስቀሉንም ተሸክሞ በዕብራይስጥ ጎልጎታ ወደ ተባለው ቀራንዮ ወደሚባል ቦታ ወጣ›› (ዮሐ.፲፱፥፲፯) የራስ ቅል ስፍራ ቀራንዮ-ጎልጎታ አዳም ዐጽም የተቀበረበት ቦታ ነበር፡፡ በዚያም የአዳም መቃብር የሆነች ዋሻ አለች፤ የመስቀሉንም እንጨት በዚያ በምድር መካከል አይሁዶች ተከሉት፡፡ የአዳም አጽም ቀድሞ ከአዳም ትውልዶች ሲተላለፍ ከኖኅ ደርሷል፤ ኖኅም ወደ መርከብ እንደታቦት አስገብቶት በኋላ መልከጼዴቅ ቀብሮታል፡፡ ጌታችንም ከአዳም የራስ ቅል በላይ ሊያድነው መስቀል ተሸከሞ ተንገላታ፤ አይሁዶችም የቀራንዮን ዳገት  እየገረፉ ከወደ ጫፍ አደረሱት፤ሁለቱንም እንጨት አመሳቅለው ዐይኖቹ እያዩ እጆቹንና እግሮቹን ቸነከሩት፤ በዕለተ ዐርብ ቀትር ፮ ሰዓት ላይም ተሰቀለ፡፡

ጌታችን የተሰቀለበት ሰዓት ፀሐይ በሰማይ መካከል በሆነ ጊዜ የጥላ መታየት በሚጠፋበት፤ ወደ ሰው ተረከዝም በሚገባበት ነበር፡፤ ከ፮ ሰዓት ጀምሮ እስከ ፱ ምድር ጨለመች፤ ፀሐይ፤ጨረቃ፤ከዋክብት ብርሃናቸውን ከለከሉ፤ ምክንያቱም የፈጣሪያቸውን ዕርቃኑን ይሸፍኑ ዘንድ ነበር፤ ‹‹ቀትርም በሆነ ጊዜ ፀሐይ ጨለመ፤ምድርም ሁሉ እስከ ፱ ሰዓት ድረስ  ጨለማ ሆነ›› ማር.፲፭፥፴፫፡፡

በ፱ ሰዓት በቀኝ የተሰቀለው ወንበዴ ስለ ጌታችን በሰማይ ፫ት በምድር ፬ት ተአምራትን ሲያደርጉ አይቶ በእውነት አምላክ እንደሆነ አመነ፤ ‹‹አቤቱ በመንግሥት በመጣህ ጊዜ አስበኝ›› ባለ ጊዜ በግራ የተሰቀለው ዳክርስ ግን ‹‹እስቲ አምላክ ከሆነ እራሱን ያድን›› ብሎ ተዘባበተ፡፡ ፍያታዊ ዘየማን ግን ‹‹እኛስ በበደላችን ነው የተሰቀልን፤ እርሱ ግን ምንም ሳይበድል ነው፤ እንዴት በአምላክ ላይ ክፉ ነገርን ትናገራለህ›› ብሎ ገሰጸው ፤ፍያታዊ ዘየማንም ጌታችን በጌትነት መንበረ ጸባዖት(መንግሥት) ሆኖ ታየው፤እርሱንም አይቶ ‹‹ተዘከረኒ እግዚኦ በውስተ መንግሥትከ›› ቢለው ጌታችን ‹‹ዮም ትሄሉ ምስሌየ ውስተ ገነት›› ብሎ ደመ ማኅተሙን ሰጥቶታል፤ በኋላ ገነት ሲገባም መልአኩ አንተ ማነህ፤ አዳም ነህ፤ አብርሃም ወይንስ ይስሐቅ? እያለ ጠይቆታል፡፡ መልአኩ ሳያውቅ የጠየቀ ሆኖ አይደለም፤እንኳን በመጨረሻ የጸደቀ ፍያታዊ ቀርቶ በዘመናቸው የኖሩ ጻድቃንን ያውቃል፤ አዳምን ፤አብርሃምን፤ይስሐቅን ሳያውቅ ቀርቶም አይደለም፡፡ ነገር ግን ሊቃውንት ሲተረጉሙት ‹‹አዳም ነህ›› ማለቱ የአዳምን ያህል ሥራ አለህን? አብርሃም ነህ ሲለው ደግሞ የአብርሃምን ያህል ሥራ አለህን? ለማለት ነው፡፡ ‹‹በጌታችን ኢየሱስ መስቀል አጠገብም እናቱ፤ የእናቱም እኅት፤ የቀለዮጳም ሚስት ማርያም፤መግደላዊትም ማርያም ቆመው ነበር›› (ዮሐ.፲፱፥፳፭) ‹‹እነርሱም ማርያም መግደላዊት፤ የታናሹ ያዕቆብ እና የዮሳ እናት ማርያም፤ የዘብዴዎስም የልጆቹ እናት ሰሎሜም ነበሩ›› (ማር.፲፭፥፵)፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ከተናገራቸው የአደራ ቃላት አንዱ እመቤታችን ለቅዱስ ዮሐንስ መሰጠቷ ነው፤ ለወዳጁ ዮሐንስ ከስጦታ ሁሉ ስጦታ የሆነች እናቱን እናት ትሁንህ ብሎ ሰጠው፤‹‹እነኋት እናትህ፤ እነሆ ልጅሽ›› (ዮሐ.፲፱፥፳፮)፡፡ በኋላ ወደ ቤቱ ወስዷት ፲፭ ዓመት ኖራለች፤ በዚህም የዮሐንስ ቤት በአቢዳራ ቤት ተመስላለች፤እመቤታችንም የሚያጽናናትን ወዳጁ ዮሐንስን ሰጥቷታል፡፡ የእመቤታችን ለዮሐንስ መሰጠት ቀድሞ በሙሴ አንጻር ጽላቷ ለሕዝቡ ሁሉ እንደተሰጠች፤በዮሐንስ አንጻርም እመቤታችን ለሁላችን ለምእመናን ተሰጥታናለች፡፡

፱ ሰዓት በሆነ ጊዜ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ኤሎሄ ኤሎሄ ላማ ሰበቅታኒ፤አምላኬ አምላኬ ለምን ተውከኝ›› ብሎ በታላቅ ቃል ተናገረ፤(ማር.፲፭፥፴፬)፡፡ በዚያም ቆመው የነበሩት ‹‹አምላኬ አምላኬ ለምን ተውከኝ፤›› የሚለውን ድምጽ የሰሙ ኤልያስን ይጣራል እያሉ አሙት፤ ክህደትንም ተናገሩ፤ ያንጊዜ አንዱ ወታደር ሮጦ ሆምጣጤ የመላበት ዕቃ ተቀምጦ ነበርና  በሰፍነግ መልቶ በሂሶጽም አድርጎ በአፉ ውስጥ ጨመረለት፡፡

 በመስቀል ላይ ሳለ ጌታችን ኢየሱስም በታላቅ ድምፅ ሁሉ ተፈጸመ አለ፤ (ማር. ፲፭፥፴፯)፤ ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በፈቃዱ ለየ፡፡ አይሁድም እኒህ ሰዎች እንደተሰቀሉ አይደሩ፤ ምክንያቱም ቀጣዩ ቀን ሰንበት ነውና ጭናቸውን ሰብረው ያወርዷቸው ዘንድ ጲላጦስን ጠየቁት፤ እርሱም ፈቀደላቸው፡፡ የሁለቱ ወንበዴዎች፤ ፈያታይ ዘየማንንና ፈያታይ ዘጸጋምን አብረው አወረዷቸው፤ ከጌታችን ዘንድ ቢቀርቡ ፈጽሞ ሞቶ አገኙት፤ በዚህም ጭኑን ሳይሰብሩት ቀሩ፡፡ ሌላው ግን የተመሰለው ምሳሌ ፍጻሜ ሲያገኝ ነው፤ የፋሲካውን በግ ‹‹አጥንቱን ከእርሱ አትስበሩ›› የተባለው አሁን ተፈጸመ፤(በዘፀ.፲፪፥፲)፡፡ ከጭፍሮቹም አንዱ ቀኝ ጎኑን በጦር ወጋው እንዲል ከወታደሮቹ አንዱ የሆነው ለንጊኖስ የጌታችንን ጎን ቢወጋው ትኩስ ደምና ቀዝቃዛ ውኃ ፈሷል፡፡ ለንጊኖስ ጥንተ ታሪኩ አንድ ዐይኑ የጠፋ ሲሆን ጌታችን በተሰቀለበት ጊዜ ወደ ጫካ ሸሽቶ ርቆ ነበር፤ ምክንያቱም ከዚህ ሰው ሞት አልተባበርም በማለት ነው፡፡ አመሻሹ ላይ የአይሁድ አለቆች ሲመለሱ ከመንገድ አገኘቱ፤ስለምን ከመሢሑ ሞት አልተባበርክም አሉት? እርሱም ምንም ስላላገኘሁበት አላቸው፡፡ ከዚያም በኋላ እንደሕጋቸው እንደሚቀጡት ቢነግሩት እየሮጠ ሔዶ የጌታችንን ጎን ሲወጋው ደሙ በዐይኑ ላይ ፈሰሰ፤ ያን ጊዜ ዐይኑ በራለት፤ከጌታችን ጎን የፈሰሰው ደም እንደ ቅርጽ ሆኖ በሁለት ወገን ደምና ውኃ ሆነ፡፡ ከጌታችንም የፈሰሰውን ትኩስ ደም መላእክት በጽዋ ቀድተው በዓለም ላይ ረጩት፤ ይህ መሠረት ሆኖ ዛሬ ቤተ ክርስቲያን የሚታነጸው የጌታችን ደም የነጠበበት  ነው፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹አሁንም በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔር ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ›› ያለው (ሐዋ.፳፥፳፰)፡፡ ከጌታ ጎን የፈሰሰው ውኃ ደግሞ ምእመናን የልጅነት ጥምቀትን ስንጠመቅ ውኃውን ካህኑ ሲባርከው ማየ ገቦ ይሆናል፡፡

ቅዳሜ ከቀድሞው በተለየ መልኩ የጌታችንን መከራ በማሰብ በጾም ታስባ ስለምትውል የተሻረችው ቅዳሜ ትባላለች፤ ይህ ቅዳሜ ጌታችን ሥጋው በመቃብር የዋለበት በመሆኑ እኛም እንደ ሐዋርያት የትንሣኤውን ብርሃን ሳናይ እህል አንቀምስም በማለት በጾም ስለምናሳልፈው ነው፡፡ ቄጠማውንም ምእመናን እስከ ትንሣኤው ሌሊት በራሳቸው ላይ ያሰሩታል፤ የቄጠማው አመጣጥና ምሥጢርም ከአባታችን ከኖኅ ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፤ ምድር በጥፋት ውኃ በጠፋችበት ወቅት የኖኅ ታማኝ መልእክተኛ ርግብ የውኃውን መጉደል ያበሠረችው ቄጠማ ይዛ በመግባት ነው፡፡ ዛሬም ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች ኃጢአት ጠፋ፤ በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነፃነት ተሰበከና ታወጀ በማለት ካህናቱ ቄጠማ ይዘው ምእመናንን ያበስሩበታል፡፡

በዚህች ቅድስት ቅዳሜ፤ ቅዱስ የሆነ እግዚአብሔር በጥንተ ተፈጥሮ ፍጥረታትን አከናውኖ ከፈጠረ በኋላ፤ በዚህች ዕለት ከሥራው ሁሉ ያረፈባት ዕለት ናት፡፡ ጌታችን የተቀበረበትም ስፍራ ለተሰቀለበት ቦታ አቅራቢያ ነበር፤ ዮሴፍ ከኒቆዲሞስ ጋር ሆኖ ጌታችንን እንደፍጡር በሐዘንና በልቅሶ ሲገንዙት የጌታችን ዐይኖች ተገለጡ ‹‹እንደፍጡር ትገንዙኛላችሁን? በሉ እንዲህ እያላችሁ ገንዙኝ፤ ቅዱስ እግዚአብሔር፤ ቅዱስ ኃያል፤ ቅዱስ ሕያው›› አላቸው፡፡

ጸሎተ ሐሙስ

ሰሙነ ሕማማት (ከዕለተ ሰኑይ እስከ ቀዳሚት ሰንበት)

በመምህር ቸርነት አበበ

መጋቢት ፳፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

መግቢያ

ከአባታችን አዳም በደል ወይም ስሕተት በኋላ በሕማማት፣ በደዌያት፣ በመቅሠፍታት፣ ወዘተ በብዙ መከራ የሰው ልጅ ሊኖርባቸው ግድ የኾነባቸው ዘመናት ጥቂቶች አልነበሩም፡፡ የሰው ልጅ ቢያጠፋ፣ ቢበድል፣ ከሕገ እግዚአብሔር ቢወጣ እንኳን የዋህ፣ ታጋሽ፣ ቸር፣ አዛኝ የኾነው አምላክ የጠፋውን ሊፈልግ፣ የተራበውን ሊያጠግብ የታረዘውን ሊያለብስ፣ ፍቅር ላጣው ፍጹም ፍቅር ሊለግስ፣ ሰላም ለሌለው ፍጹም ሰላም ሊሰጥ፣ ተስፋ ለሌለው ተስፋ ሊያጐናጽፍ ከሰማይ ወረደ፤ ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደ፤ በገዳመ ቆሮንቶስ ዐርባ ቀንና ሌሊት ጾመ፡፡ በጾሙም የኀጢአት ሥሮች ወይም ራሶች የተባሉትን ስስትን፣ ትዕቢትንና ፍቅረ ንዋይን ድል አደረገልን፡፡ እኛ እርሱ የጾመውን ጾም እንድናከብር እንድንጾም ምሳሌ ኾነን፡፡ ዲያብሎስን ድል አድርጐ ድል እንድንነሣው ኃይልና ምሳሌ ኾነን፡፡

ሰሙነ ሕማማት ምንድን ነው?

‹ሰሙን› – ‹‹ሰመነ ስምንት (ሳምንት) አደረገ›› ማለት ነው፡፡ ይኸውም ከዕለተ ሆሣዕና ሠርክ እስከ ትንሣኤ ሌሊት ያለውን ጊዜ ወይም ቀናት የሚያመለክት ነው፡፡ ‹ሕማም (ሕማማት)› – ‹ሐመ ታመመ› ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲኾን ይህም የሰውን ዘር ዂሉ ከዲያብሎስ ባርነት ነጻ ለማውጣት ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፈቃዱ የተቀበላቸውን ጸዋትወ መከራዎች የሚያሳስብ ነው፡፡ ዕለታቱ የዓመተ ኵነኔ ወይም የዓመተ ፍዳ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ክርስቲያኖች የክርስቶስን ውለታ እያሰቡ እጅግ የሚያዝኑበት፣ የሚያለቅሱበት፣ የሚሰግዱበት ቤት ንብረታቸውን ትተው ከሌላው ቀናትና ጊዜያት በተለየ መልኩ ቤተ ክርስቲያናቸውን የሚማጸኑበት፤ ጧት ማታ ደጅ የሚጠኑበት፤ ኀጢአታቸውን በቤተ ክርስቲያን አደባባይ ለካህኑ የሚናዘዙበት በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ የሚገኝ ሳምንት ነው፡፡

በዚህ ሳምንት ብዙ አዝማደ መባልዕት አይበሉም፤ ይልቁን በመራብ በመጠማት በመውጣት በመውረድ በመስገድ በመጸለይ በመጾም በየሰዓቱ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ጸዋትወ መከራዎች በማሰብ አብዝቶ ይሰገዳል፡፡ መከራውን፣ ሕማሙን፣ ድካሙን የሚያስታውሱ ከቅዱሳት መጻሕፍት ኢሳይያስ፣ ኤርምያስ መዝሙረ ዳዊት፣ ግብረ ሕማማት ወዘተ በየሰዓቱ ይነበባል፡፡ መስቀል መሳለም የለም፡፡ ካህናትም ‹‹እግዚአብሔር ይፍታህ›› አይሉም፡፡ ሥርዓተ ፍትሐት አይፈጸምም፡፡ ይኸውም ይህ ሳምንት ከሞት ወደ ሕይወት የተሸጋገርንበት ከጨለማ ወደ ብርሃን የተጓዝንበት የመሸጋገሪያ ወቅት ምሳሌ በመኾኑ ነው፡፡ በዕለተ ምጽአት መላእክት የመለከት ድምፅ በማሰማት የዳግም ምጽአትን ዕለት ለማሳሰብ ምእመናን ጥሪውን ሰምተው ለዚህም አስቀድመው ተዘጋጅተው የበዓሉ ታዳሚዎች መኾናቸውን በማጠየቅ በዚህ ሳምንት ዲያቆኑ ቃጭል እየመታ በየሰዓቱ ምእመናኑን ያሳስባል፡፡ Read more

ሆሣዕና በአርያም

በወልደ አማኑኤል

ሆሣዕና በአርያም ማለት በሰማይ ያለ መድኃኒት ነው፡፡ ጌታችን በአህያ ውርንጫ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም የገባበት ዕለት ከዘጠኙ ዐበይት በዓላት አንዱ ስለሆነ የክብረ በዓሉ ምስጋና በዋዜማው ይጀመራል፡፡ ቅዳሜ ከሰዓት በኋላ ካህናቱ ‹‹በእምርት ዕለት በዓልነ፣ በታወቀ የበዓላችን ቀን ከበሮ ምቱ›› በማለት የዋዜማውን ምስጋና ይጀምራሉ፡፡ የዋዜማው የምስጋና ቀለም እጅግ ሰፊ ስለሆነ በዚህ መዘርዘር አይቻልምና ከዋዜማው ፍጻሜ በኋላ ያለውን ሥርዓት እንመልከት፡፡

በሌሊተ ሆሣዕና ማኅሌት ከመቆሙ በፊት በካህኑ ተባርኮ በሰሙነ ሕማማት ሲነበብ፤ ሲተረጎም የሚሰነብተው ግብረ ሕማማት የተባለው መጽሐፍ ሲነበብ ነው፡፡ ‹‹ስቡሕ ወውዱስ ዘሣረረ ኩሎ ዓለመ››፣ ዓለምን ሁሉ የፈጠረ እግዚአብሔር ፍጹም የተመሰገነ ነው፡፡ የምስጋናዎች ሁሉ ርእስ የዕለቱ የማኅሌቱ ምሥጋና በካህናት በሊቃውንት ይፈጸማል፡፡

ከዐብይ ጾም መግቢያ ጀምሮ በዝምታ የሰነበቱት ከበሮና ጸናጽል የምስጋናው ባለ ድርሻዎች ናቸው፡፡ በዚህ የተጀመረው ማኅሌት ሌሊቱን ሙሉ አድሮ መዝሙር በሚባለው ምስጋና በኩል አድርጎ ሰላም በተባለ የምስጋና ማሳረጊያ ይጠናቀቃል፡፡

ሥርዓተ ዑደት ዘሆዕና

ሥርዓተ ማኅሌቱ ተፈጽሞ፤ ሥርዓተ ቅዳሴው ከመጀመሩ በፊት እስከዚያ ሰዓት ከነበረው ሥርዓት ለየት ያለ ነው፡፡ ይሔውም ሊቃውንቱ የዕለት ድጓ እየቃኙ፣ እየመሩና እየተመሩ፣ ዲያቆኑ ከመዝሙረ ዳዊት የዕለቱን በዓል የተመለከተ ምስባክ በዜማ እያሳመረ፣ ካህናቱም በዓሉን የተመለከተ የዕለቱ ተረኛ ካህን በማቴዎስ ወንጌል ፳፩፡፩-፲፫ ላይ ያለውን ኃይለ ቃል በሚያነብበት ወቅት በአራቱም መዓዘን ቤተ መቅደሱን አንድ ጊዜ ይዞሩታል፡፡

ለምሳሌ ከምዕራቡ ወደ ምሥራቅ ባለው በር ፊት ለፊት በመቆም መምህሩ ‹‹አርእዩነ ፍኖቶ ወንሑር ቤቶ፣ ወደ ቤቱም እንገባ ዘንድ መንገዱን አሳዩን፤››የሚለውን ድጓ ይቃኛሉ፡፡ ካህናቱ እየተከተሉ ያዜማሉ ዲያቆኑ ‹‹ዘምሩ ለእግዚአብሔር ዘየይድር ውስተ ጽዮን፤ በጽዮን የሚገለጥ እግዚአብሔርን አመስግኑ›› እያለ የዕለቱ ተረኛ ካህን ያዜማል፡፡ በዚህ ዐይነት መልክ በአራቱም መዓዝነ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ ዑደቱ ይፈጸማል፡፡

ሥርዓተ ቅዳሴ ዘሆዕና

በዕለተ ሆሣዕና አሁንም የቅዳሴው አገባብ ሥርዓት ከሌሎች ዕለታት ለየት ያለ መሆኑን እንመለከታለን፡፡ ዲያቆናቱ ኅብስቱን በመሶበ ወርቅ ወይኑን በጽዋዕ ይዘው በምዕራብ በር በኩል ይቆማል፡፡ ሠራኢው ዲያቆን በዜማ አሰምቶ ‹‹አርኅው ኖኃተ መኳንንት፣ አለቆች ደጆችን /በሮችን/ ክፈቱ›› ይላል፡፡ ካህኑም በመንጦላዕት ውስጥ ሆኖ ‹‹መኑ ውእቱ ዝንቱ ንጉሠ ስብሐት››፣ ይህን የክብር ንጉሥ የኃያላን አምላክ እግዚአብሔር ነው፤ ብሎ ይመልሳል፡፡ ዲያቆኑ ሦስት ጊዜ የክፈቱልኝ ጥያቄያዊ ዜማውን ካዜመ በኋላ ‹‹ይባእ ንጉሠ ስብሐት››  የክብር ንጉሥ ይግባ ብሎ ፈቅዶለት ይገባል፤መዝ. ፳፫፥፯፡፡

ይህንንም አበው እንደሚከተለው ያመሰጥሩታል፤ አንደኛ ቅዱስ ገብርኤልና ወላዲተ አምላክ በምሥጢረ ብስራት ጊዜ የተነጋገሩት እንደሆነና በመጨረሻም ‹‹ይኩነኒ በከመ ትቤለኒ››፣ እንደ ቃልህ ይደረግልኝ ብላ መቀበሏን ያሳያል፡፡ ሁለተኛው ፈያታዊ ዘየማንና መልአኩ ኪሩብ በማእከለ ገነት የተነጋገሩትን በድርጊት ለማሳየት መሆኑን ያስተምራሉ፡፡ ዋናው ምሥጢር ግን ክርስቶስ ወደ ቤተ መቅደስ ሊገባ ሲል ብዙዎቹ እንዳይገባ ቢፈልጉም ከፊሎቹ ግን እንዲገባ መፍቀዳቸውን ያሳያል፡፡እንደተለመደው ሥርዓተ ቅዳሴው ከተጠናቀቀ በኋላ ‹‹እግዚአ ሕያዋን›› /የሕያዋን ጌታ/ የተሰኘው ጸሎት በካህናት ተደርሶ ለምእመናን ሥርዓተ ፍትሐት ይደረግላቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ሥርዓተ ፍትሐት ስለማይደረግ፤ በሰሙነ ሕማማት የማይከናወኑ ምሥጢራት በዕለተ ሆሣዕና ይከናወናል፡፡

ምእመናኑ ተባርኮ የተሰጣቸውን የዘንባባ ዝንጣፊ በመያዝ ወደ እየቤታቸው ያመራሉ፡፡ የዘንባባው ምሥጢር የተጀመረው በታላቁ አባት በአብርሃም ነው፤ ኩፋ. ፲፫፥፳፩፡፡ ይህን የአባታቸውን ሥርዓት አብነት አድርገው እስራኤል የኤርትራን ባሕር ሲሻገሩ፣ ዮዲት ድል ባደረገች ወቅት ዘንባባ እየያዙ እግዚአብሔርን አመስግነውበታል፡፡ ጌታችን በዕለተ ሆሳሣና ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባም ሽማግሌዎችና ሕፃናት የዘንባባ ዝንጣፊ ይዘው እንደተቀበሉት እናነባለን፡፡‹‹ኢትዮጵያዊያን ምእመናንም ክርስቶስ የሰላም ነጻነት የድኅነት አምላክ መሆኑን ለመመስከር ዘንባባውን ይዘው ወደ ቤታቸው ይገባሉ››፤በእጃቸውም እንደ ቀለበት ያስሩታል፡፡

ለበዓለ ሆሣዕና በሰላም ያደረሰን አምላክ ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም እንዲያደርሰን ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን!

‹‹ወአንትሙሰ ተዐቀቡ፤ ወግበሩ ተዝከረ ሕማማቲሁ፤ እናንተስ ተጠበቁ፤ የሕማሙን መታሰቢያ አድርጉ››፤/ትእዛዝ ፴፩/

   በወልደ አማኑኤል

ሰሙነ ሕማማት የሚባለው ከዐቢይ ጾም መጨረሻ ከሆሣዕና ዋዜማ ጀምሮ እስከ ትንሣኤ ባሉት ቀናት ውስጥ ያለው ነው፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ አስቀድሞ የጌታችን የምሥጢረ ሕማማቱን ነገር መንፈስ ቅዱስ ሲገልጽለት ‹‹ውእቱ ነሥአ ደዌነ ወፆረ ሕማመነ፤ እርሱ በእውነት ደዌያችንን ተቀበለ፤ ሕማማታችንንም ተሸከመ››ማቴ. ፰፥፲፯/ኢሳ ፶፫፥፬/ ሲል ተናገረ፤ የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ስለኛ ድኅነት በፍቃዱ ሕማማተ መስቀልን በትዕግስት በመሸከም መከራ መስቀሉ ስለተፈጸመበት፤ እኛም መከራ መስቀሉን የምናስብበት በመሆኑ ሰሙነ ሕማማት ተባለ፤ ኢሳ. ፶፫፥፬፡፡

 ከ፻፹፰-፪፻፴ ዓ.ም የነበረው ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ድሜጥሮስ እግዚአብሔር አምላክ በገለጠለት የጊዜ ቀመር (ባሕረ ሐሳብ) ሰሙነ ሕማማት ከዐቢይ ጾም ቀጥሎ እንዲሆን ተወስኗል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም በቀመረ ድሜጥሮስ ዓመታትን በንዑስ፤ በማዕከላዊና በዐቢይ ቀመር እየቀመረች አጽዋማት የሚገቡበትንና በዓላት የሚውሉበትን ጊዜ ለምእመናን ታሳውቃለች፡፡ ታዲያ ሰሙነ ሕማማትን ጌታችን ለሰው ዘር በሙሉ ያደረገው ትድግና ቅዱሳን መጻሕፍት በየበኩላቸው ቢዘረዝሩትም ቸርነቱ፤ ርህራሄውና በጠቅላላው በአምላካዊ ጥበቡ የሰራቸው ዕፁብ ድንቅ የሆኑ ሥራዎች ጸሐፊ፣ አንባቢና ሰሚ ሊደርስባቸውና ዝርዝራቸውን ሊከተላቸው ሲፈልግ፤ ገና በሀሳቡ ውጥን ላይ ድካም እንዲሰማውና ፍጡርነቱ ፈጣሪን እንዳይመረምር ያስገድደዋል፡፡

መድኃኔዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ዘር በቃሉ ብቻ ዳን በማለት ሊያድነው ሲቻለው የሰውን ባሕርይ ባሕሪዩ አድርጎ በፈቃዱ ሰው የሆነበትን፤ ሰውም ከሆነ በኋላ የተቀበላቸው ልዩ ልዩ መከራ የተቀበለበት ሳምንት ነው፡፡ በዚህ ሰሙነ ሕማማት በቤተ ክርስቲያናችን የሚደረጉ ሥርዓቶች በጥቂቱ እንመልከት፡-

ሥርዓተ ሰሙነ ሕማማት

ሰሙነ ሕማማትን የምናከብረው አባቶች ሐዋርያት የጌታን ጾም ለብቻው እንድናስበው እንዳደረጉን ሁሉ የጌታ ሕማማትም እንዲሁ በተለየ ለብቻው እንድናስበው የሰሩልን ሥርዓት ነው፡፡ ታዲያ ይህን ሳምንት ሊቃወንተ ቤተ ክርስቲያን ዓመተ ፍዳ፤ ዓመተ ኩነኔ (፶፻፭፻ ዘመን) እና የጌታችን ሕማም መከራ እንግልት የሚታሰቡበት ነው ብለው ያስቡታል፡፡ ስለዚህም እነዚህን ሁለት ነገሮች ምክንያት በማድረግ በሰሙነ ሕማማት  የሚተገበሩ ሥርዓቶች አሉ፤ እነርሱም፡-

ጥቁር ልብስ መልበስ 

በሰሙነ ሕማማት ወቅት በተለይ በዕለተ ዐርብ ካህናቱ ጥቁር ልብስ ይለብሳሉ፤ የኃዘንና የመከራ መገለጫ በመሆኑ በዚህ ወቅትም የጌታን ኃዘን መከራ ለማሰብና ለማስታወስ በማሰብ ነው፡፡ ጥቁር ልብስ ባይገኝ ደግሞ የተገኘውን ልብስ ገልብጠው ይለብሱታል፡፡

በጸሎተ ሐሙስ ቃጭሉ ተቀይሮ ጸናጽል ይሆናል

በጸሎተ ሐሙስ በቅዳሴው ወቅት ቃጭሉ ተለውጦ ጸናጽል ይሆናል፤ ምክንያቱም በዘመነ ኦሪት የነበሩ አበው ጸሎታቸው ፍጽም ሥርዓት እንዳላሰጣቸው ለማጠይቅ ነው፡፡ ከቃጭል የጸናጽሉ ድምጽ ከርቀት እንደማይሰማ ሁሉ የአበው ጩኸት አናሳ መሆኑን ለማጠየቅ፤ የይሁዳን ግብር ለመግለጥና ይሁዳ ጌታን ለማስያዝ በድብቅ ያደባ እንደነበር ለማስታወስ ነው፡፡

እርስ በእርሳችን አንሳሳምም፤ መስቀል አንሳለምም

እርስ በእርሳችን አለመሳሳማችን ይሁዳ በመሳም አሳልፎ መስጠቱን ለማሰብና ለማስረዳት ሲሆን መስቀልን ያለመሳለማችን ምክንያቱ ደግሞ፤ መስቀል በዘመነ ኦሪት የኃጥአን መቅጫ እንጂ የሰላም ምልክት እንዳልነበረ ለማጠየቅ ነው፡፡ መጽሐፍትም በመስቀሉ ስለምን አደረገ እንዲሉ መስቀል አዳኝ የሆነ ጌታ ከተሰቀለ በኋላ መሆኑን እንድናስብ ነው፡፡

አብዝተን መጾም አለብን

ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በዚህ ወቅት አብዝተን እንድንጾምና እንድንፀልይ ያዙናል፤ ለምሳሌ በሰሙነ ሕማማት የሚችል በሁለት ቀን ውኃና ጨው ያለበት ምግብ እየተመገበ እንዲጾም ሲያዙን ያልቻለ ግን ፲፫ ሰዓት እየጾመ እየጸለየ ውኃንና ጨው የበዛበት ምግብ እንዲመገብ አዘዋል፡፡

ለሙታን ፍትሐት አይደረግም

በሰሙነ ሕማማት ወቅት ለሞቱ ሰዎች ፍትሐት አይደረግላቸውም፤ ዓመተ ፍዳና ዓመተ ኩነኔን የምናስብበት ወቅት በመሆኑ በዚህ ዘመን ደግሞ የነበሩ ሰዎች ፍትሐት እንደማይደረግላቸው ለማጠየቅ ነው፡፡ ዛሬም ቢሆን ተስፋ ላለውና ለአማኝ እንጂ ለማያምን ትንሣኤ ዘለክብር፤ ለማይነሣ ቢሆን ፍትሐት አይደረግለትም፡፡

በወይራ ቅጠል ጥብጠባ ይደረጋል

በዕለተ ዐርብ ሥርዓቱን ከፈጸምን በኋላ ወደ ካህናት አባቶቻችን እየሔድን በወይራ ዝንጣፊ ጥብጠባ ተደርጎልን ቀኖና እንቀበላለን፤ በዚህ ወቅት የምንቀበለው ቀኖና የሰሙነ ሕማማትን በተመለከተ ብቻ ነው፡፡ ወይራ ጽኑ በመሆኑ የጌታ መከራ ጽኑ መሆኑን ለማጠየቅ ነው፡፡

ሕጽበተ እግር ይደረጋል

በጸሎተ ሐሙስ በካህናት አባቶችን የሚፈጸም እግር የማጠብ ሥርዓት ይፈጸማል፤ በዚህም መነሻ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሐዋርያትን እግር እንዳጠበና እርሱን አብነት ስላደረግን ነው፡፡

በዚህ ወቅት በዋነኝነት ግብረ ሕማማት የተሰኘው መጽሐፍ ይነበባል

የሰሙነ ሕማማት ሥርዓተ ጸሎትና አገልግሎት ሁኔታ ከቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓተ አምልኮት ጋር የተያያዘ ቢሆንም አሁን ያለውን ሥርዓት የያዘ ግብረ ሕማማት የተሰኘው መጻሕፍ ተዘጋጅቶ በሥራ ላይ የዋለው ከጌታ ልደት በኋላ በ፲፬ተኛው ምእት ዓመት ነው፡፡ ከ፲፫፻፵ እስከ ፲፬፻፹ ዓ.ም የነበሩት ብፁዕ አቡነ ሰላማ ብርሃነ ዐዜብ ከዐረብኛ ወደ ግዕዝ እንደተረጎሙት፤ ቀደም ሲል በግዕዝ ብቻ ታትሞ በነበረው የግብረ ሕማማት መጽሐፍ ውስጥ ተገልጧል፡፡

የመጽሐፉ ስያሜም ከጥንት ስሙ ጀምሮ ግብረ ሕማማት እንደሚባል በመጽሐፍ ውስጥ በብዙ ክፍል ተጠቅሶ ይገኛል፡፡ ይህም ቀዳማዊ ቃል እግዚአብሔር ወልድ ከጥንት ፍጥረት ከባሕርይ አባቱ አብ፤ ከባሕርይ ሕይወቱ መንፈስ ቅዱስ ሕልው ሆኖ በረቂቅ ጥበቡ ዓለማትንና ፍጥረታትን ሁሉ በየወገኑ ፈጥሮ እንደባሕርያቸው በቸርነቱ እየመገበና እየጠበቀ ሲገዛ ይኖራል፡፡ አካላዊ ቃል ወልድ በተለየ አካሉ ዓለምን ከፈጠረበት በሚበልጥ ጥበብ ሰው ሆኖ፤ ሥጋን ለብሶ፤ ከድንግል ማርያም ተወልዶ፤ አዳምን ከነዘሩ እንደገና በአዲስ ተፈጥሮ ወደ ቀደመ ክብሩና ቦታው እንደመለሰው ያመለክታል፤ ፪ኛ ቆሮ. ፭፥፲፯/ ዕራ.፳፩፥፭/ ኢሳ. ፵፫፥፲፱/፡፡

‹‹ሰላም ለኒቆዲሞስ ለወልደ ማርያም ዘአምኖ››

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዚያ 5/2011 ዓ.ም.
በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት፣ ከዐቢይ ጾም ሳምንታት መካከል ሰባተኛው ሳምንት በኒቆዲሞስ ተሰይሟል፡፡ ሳምንቱ በስሙ ከመጠራቱም ባሻገር በቤተ ክርስቲያን የሚቀርበው ትምህርትም ኒቆዲሞስ ከጌታ የተማረዉን ምሥጢረ ጥምቀት መሠረት ያደረገ ነው፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ ከውኃ እና ከመንፈስ ቅዱስ መወለድ እንደሚገባው ያትታትል፡፡ ቅዱስ ማርቆስ በወንጌሉ ምዕራፍ ፲፮ ቍጥር ፲፮ ላይ ‹‹ያመነ፣ የተጠመቀ ይድናል፤ ያላመነ፣ ያልተጠመቀ ግን ይፈረድበታል፤›› በማለት ያስተማረው ትምህርትም ከዚህ መልእክት ጋር የሚስማማ ነው፡፡ Read more

ገብር ኄር

መምህር ሶምሶን ወርቁ

የዐቢይ ጾም ስድስተኛ ሳምንት ገብር ኄር የተሰየመው በቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ በዚህ ሳምንት ለሰው ሁሉ የማገልገያ ጸጋ መሰጠቱን፣ ሰጪው እግዚአብሔር አምላክ መሆኑን፣ ቅን አገልጋዮች ስለሚቀበሉት ዋጋ ፣ ሰነፍ አገልጋዮች ስለሚጠብቃቸው ፍርድ ይሰበካል፡፡ «ገብር ኄር ወገብር ምእመን ዘአሥመሮ ለእግዚኡ፤ ጌታውን ያስደሰተው አገልጋይ ታማኝና ቸር አገልጋይ ነው፤መኑ ውእቱ ገብር ኄር፤ ቸር አገልጋይ ማን ነው?» እያሉ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይዘምራሉ፤ በቅዳሴው ደግሞ የማቴዎስ ወንጌል ፳፭፤፲፬-፴ ይነበባል።

. የምሳሌው ትርጉም

የመክሊቱ ባለቤት አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ ባለ አምስት፤ ባለ ሁለትና ባለ አንድ መክሊት የተቀበሉት በጥምቀት ጸጋ መንፈስ ቅዱስን የተቀበሉ፤ተምረው የሚያስተምሩ መምህራን ናቸው፡፡ የስጦታው መለያየት መበላለጥን ለማሳየት ሳይሆን የአንዱ ጸጋ ከሌላው እንደሚለይ የሚያጠይቅ ነው፤ «መንፈስ ቅዱስ አንድ ሲሆን ስጦታው ልዩ   ልዩ ነው፡፡ ጌታም አንድ ሲሆን ልዩ ልዩ አገልግሎቶች አሉ» ፩ቆሮ ፲፪፥ ፬፡፡

ባለ አምስትና ባለ ሁለት መክሊት የተባሉት አገልጋዮች ቃለ እግዚአብሔርን ከተማሩ በኋላ መክረው አስተምረውና ራሳቸውን አስመስለው ያወጡ ናቸው፡፡ ባለ አንድ መክሊት የተባለው ዐላውያን ነገሥታት፤ ዐላውያን መኳንንት እሳት ስለት አሳይተው ቢያስክዱኝ፣መናፍቃን ተከራክረው ቢረቱኝ፣ ምላሽ ቢያሳጡኝ፣ ሃይማኖቴን ቢያስቱኝ ብሎ ከማገልገል ይልቅ ሃይማኖቱን የማያስተምርና የማይመሰክር ነው፡፡  «ስለዚህ በሰው ፊት ለሚመሰክርልኝ ሁሉ እኔም በሰማያት በአለው አባቴ ፊት እመሰክርለታለሁ፤ በሰው ፊት የሚክደኝን ግን እኔም በሰማያት በአለው አባቴ ፊት እክደዋለሁ» ብሏል፤ ማቴ ፲፤፴፪ ፡፡ ስለዚህ በተሰጠን መክሊት በተባለ ጸጋ በሰው ሁሉ ፊት በማገልገል ልንመሰክር ይገባል፡፡

አምስትና ሁለት መክሊት የተቀበሉ አገልጋዮች ጠባይ

እነዚህ አገልጋዮች ለጌታቸው ታማኝ የነበሩ፤ በተቀበሉት መክሊት ወጥተው፤ ወርደውና አትርፈው የተገኙ ናቸው፡፡ መክሊታቸውን ከተቀበሉ በኋላ በእምነት ሊሰማሩ ወጡ እንጂ በሥጋት እጅና እግራቸውን አጣጥፈው አልተቀመጡም፡፡ እነርሱም በተሰጣቸው መክሊት መጠን በእምነት በማገልገላቸው ሁለቱም ገብር ኄር (ቸር አገልጋይ) የሚል የክብር ስም ተሰጣቸው፤ «ወደ ጌታህ ደስታ ግባ» የሚለውን የምሥራች ቃል ሰሙ፡፡

. አንድ መክሊት የተቀበለው አገልጋይ ጠባይ

እምነት የጎደለው ተጠራጣሪ ነበረና ማትረፉን ሳይሆን መክሰሩን፣ ማግኘቱን ሳይሆን መድከሙን፣ ብቻ አሰበ፡፡ በተቀበለው መክሊት ባለማትረፉ ራሱን ከመውቀስ ይልቅ ሰጪውን ጌታ አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፤ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው ብሎ የጽርፈት ንግግርን ተናገረ፡፡ ጌታው አስቀድሞ መክሊቱን ሲሰጠው አልቀበልም ሳይል ምን ሠራህና ምን አተረፍህ ሲባል ጌታውን ከሰሰ፡፡ ልቡ የደነደነ፣ጥፋቱን ለማመን የማይፈቅድ፣ለመመለስ የዘገየ ነበረና ወደ ውጭ ልቅሶ፤ ጥርስ ማፏጨት ወዳለበት አውጡት የሚለውን የፍርድ ቃል ሰማ፡፡ ዛሬ መልካም ሥራ ላለመሥራታቸው ምክንያት የሚያበዙ፣ ሃይማኖታቸውን ለመመስከር የሚያፍሩ፣ የሚፈሩና ኀጢአት ለመሥራት ግን የሚደፍሩ ሰዎች ባለ አንድ መክሊቱን አገልጋይ ይመስላሉ፡፡ እንግዲህ «በጎ ነገር ማድረግን የሚያውቅ፤ የማይሠራትም ኀጢአት ትሆንበታለች» ተብሏልና፤ያዕ ፬፥፲፯፡፡

ለአገልግሎት ተፈጥረናል

እግዚአብሔር ሰውን በአርአያው ፈጥሮ፤ በልጅነት ጸጋ አክብሮ፤ ሁሉን አዘጋጅቶ ለአዳም አንድ ልጁን ለመስቀል ሞት ያዘዘው በዓላማ ነው፡፡ ይኸውም «እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ላዘጋጀው በጎ ሥራ በኢየሱስ ክርስቶስ  የፈጠረን ፍጥረቱ ነንና» ኤፌ ፪፥፲፡፡ ለመልካሙ ሥራ ሁሉም ሰው ተጠርቷል፤ በጥምቀት ዳግም የወለደንና በመስቀሉ ያዳነን በመልካም ሥራ እንድናገለግል ነው፡፡

እኛ በመክሊታችን ምን አተረፍን?

ጸጋችንን እናውቃለን? ለማወቅስ እንሻለን? በተሰጠን ጸጋ አትርፈናልን? ካላተረፍን ለምን? በእርግጥ አለማትረፋችን ግድ ይለናል? ከእግዚአብሔር ዘንድ ጸጋ ያልተቀበለ የለም፤ ሰው ጸጋውን አለማወቁ አልተቀበለም፤ ጸጋ የለውም አያሰኝም፡፡ ከሁሉ አስቀድመን ጸጋ እንደ ተሰጠን ማመን ይጠበቅብናል፡፡ የተሰጠንን ጸጋ ለማወቅ ለሕይወታችን በሚጠቅም አገልግሎት  ራሳችንን መፈተን መሞከር ይጠበቅብናል፤ ሳንሰማራና ራሳችንን ሳንፈትን ጸጋችንን ማወቅም ሆነ ማትረፍ አይቻልም፡፡ ጸጋ እንደተሰጠን አምነን ስንረዳና ራሳችንን ለአገልግሎት ስናዘጋጅ ማትረፊያ አገልግሎቱን መመልከት እንችላለን፡፡ በምን ማገልገል እዳለብን አለማወቅ አገልግሎትን ውስን አድርጎ መመልከት፣ለአገልግሎት መዘግየትና እንዴት ማገልገል እንዳለብን አለመረዳት ምክንያቶች ሊሆኑ ይችላሉ። ስለዚህ፡-

ሀ) በምን እናገልግል?

አንዳንዶች ምን ጸጋ ኖሮኝ ነው የማገለግለው? ሲሉ ይሰማሉ፤ ነገር ግን ከጸጋ እግዚአብሔር የጎደለ ሰው የለም፡፡ «መንፈስ ግን አንድ ሲሆን ስጦታው ልዩ ልዩ ነው፤ ጌታም አንድ ሲሆን  ልዩ ልዩ አገልግሎቶች አሉ፡፡ ሁሉን በሁሉ የሚያደርግ እግዚአብሔርም አንድ ሲሆን ልዩ ልዩ አሠራር አለ፡፡ በመንፈስ ቅዱስ የጥበብ ቃል የሚሰጠው አለ፡፡ በመንፈስ ቅዱስም የዕውቀት ቃል የሚሰጠው አለ፡፡ለአንዱም በአንዱ መንፈስ የመፈወስ ስጦታ፤ ለአንዱም ተኣምራትን ማድረግ፤ ለአንዱም ትንቢትን መናገር፤ ለአንዱም መናፍስትን መለየት፤ለአንዱም በልዩ አይነት ልሳን መናገር፤ለአንዱም በልሳኖች የተነገረውን መተርጐም ይሰጠዋል» ይላል፤፩ቆሮ ፲፪፥፬–፲፡፡ ስለዚህ በአለን ጸጋ ማገልገል ይገባናል፡፡

ለ) አገልግሎት ውስን ነውን?

አገልግሎት በቤተ ክርስቲያን፤ በበዓላትና በአጽዋማት ብቻ የሚመስላቸው፣ ካልቀደሱና ካላወደሱ፣ ካልዘመሩና ካላስተማሩ አገልግሎት የሌለ የሚመስላቸው ሰዎች አይጠፉም፡፡ ነገር ግን አገልግሎት በጊዜና በቦታ፤ በሁኔታም ሆነ በዓይነት አይወሰንም፡፡ «ደግሞ በኢየሱስ ክርስቶስ ለእግዚአብሔር ደስ የሚያሰኝ መንፈሳዊ መሥዋዕትን ታቀርቡ ዘንድ፤ ቅዱሳን ካህናት እንድትሆኑ፤ መንፈሳዊ ቤት ለመሆን ተሠሩ» ፩ጴጥ ፪፥፭፡፡ የእግዚአብሔር ቤተመቅደስ ስንሆን ሕዋሳቶቻችን እግዚአብሔርን የምናገለግልባቸው ንዋየ ቅድሳት ናቸው፡፡ በዐይናችን ቅዱሳት መጻሕፍትን ስናነብ፣ በጆሮአችን የተገፉትንና የተቸገሩትን ሰዎች ጩኸት ስንሰማ፣አፋችንን ለጸሎት ለምስጋና ስንክፈት፣ እጆቻችን ለአሥራት በኩራት ለምጽዋት ሲዘረጉ፣እግሮቻችን ማልደው ወደ ቤተክርስትያን ለጸሎት ሲገሰግሱ፣መንፈሳዊ ቤት ለመሆን እየሠራን እያገለገልን ነው፡፡ በጊዜያችን የታመሙትንና የታሰሩትን ብንጠይቅ፣ በጉልበታችን ደካሞችን ብንረዳ፣ በዕውቀታችን ያላወቁትን ብናሳውቅ ፣ በገንዘባችን የተቸገሩትን ብንጎበኝ፤ በጸጋ ላይ ጸጋና በበረከት ላይ በረከት እናተርፋለን፡፡ ወደ ጌታ ደስታ ግቡ የሚለውን የምስራች ቃል እንሰማለን፤ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንሆናለን፡፡

ሐ) ለአገልግሎት ብንዘገይስ?

አንዳንድ ሰዎች ማገልገል እንዳለባቸው ቢያውቁም ለውሳኔ ይዘገያሉ፡፡ «ዛሬ ወይም ነገ ወደዚያች ከተማ እንሄዳለን ፤ በዚያችም ዓመት እንኖራለን፤ እንነግዳለንም፤ እናተርፋለንም፤ የምትሉ እናንተ ተመልከቱ፤ ነገ የሚሆነውን አታውቁምና» ያዕ ፬፥፲፫-፲፬፡፡ ዛሬ እንኑር ነገ ስለማናውቅ የኛ የሆነውን ተረድተን ልናገለግል ይገባል፡፡ «ማንም ሊሠራ የማይችልባት ሌሊት ትመጣለች» ዮሐ፤፱፥፬፡፡ ሌሊት የተባለው ዕለተ ሞትና ዕለተ ምጽአት  ነው፤ በሞት ከተጠራን በኋላ ልማር ላስተምር፣ ልወድስ ልቀድስ፣ ላጉርስ ላልብስ ማለት የለምና ለአገልግሎት ልንፈጥን ይገባል፡፡

መ) እንዴት እናገልግል?

ማገልገል አንድ ነገር ሆኖ ሳለ እንዴት ማገልገል እዳለብን ካልተረዳን አገልግሎታችን ያለእምነት የተሟላ አይሆንም፡፡ «ያለ እምነትም እግዚአብሔርን ደስ ማሠኘት አይቻልም» ዕብ ፲፩፥፮፡፡ ሰማያዊ ዋጋን እያሰብን እናገልግል፤ «ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየኛል? መከራ ነውን? ኀዘን ነውን? ስደት ነውን? ራብ ነውን? ጭንቀት ነውን? ሾተል ነውን?» ሮሜ.፰፥፴፭፡፡ ሰማያዊውን ዋጋ ስናስብ በፈተና በመከራ እንጸናለን፤ በትሕትና  ሆነን እናገልግል «ከእኔ ተማሩ፤ እኔ የዋህ ነኝና፤ ልቤም ትሑት ነውና» ብሏል፤ ማቴ ፲፩፡፳፱፡፡

እንግዲህ መክሊት የተቀበሉትን አገልጋዮች ስናስብ፤ አምስትና ሁለት መክሊት የተቀበሉ፤ ለጌታቸው ታማኝ የነበሩ፤ በተቀበሉት መክሊትም መከራን ታግሰውና በእምነት በማገልገላቸው ሁለቱም ገብር ኄር (ቸር አገልጋይ) ተባሉ፡፡ አንድ መክሊት የተቀበለው አገልጋይ እምነት የጎደለው ተጠራጣሪ ነበረና ማትረፉን ሳይሆን መክሰሩን ብቻ የሚያስብ ደካማ፤ የተፈጠረበትን  ዓላማና የተሰጠውን ተልእኮውን ያልተረዳ ሰው ነበር። እኛም በጥምቀት ዳግም የተወለድነውና በመስቀሉም የዳንነው ተልእ£ችንን ተረድተን በመልካም ሥራና በታማኝነት እንድናገለግል ነው፡፡ ቀደምት ቅዱሳን አባቶቻችንን አርአያ በማድረግ ለምን፤ በምንና እንዴት ማገልገል እዳለብን ልንረዳ ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ ወወላዲቱ ድንግል፤ ወመስቀሉ ክቡር!

በሰሜን ሸዋ ሰላሌ ሀገረ ስብከት የተሰረቁት የቅዱስ ገብርኤል፤የቅዱስ ዮሐንስና የገብረ ክርስቶስ ጽላቶች መገኘታቸውን ፖሊስ ገለጸ

በሕይወት ሳልለው

ሰኞ መጋቢት ፲፮ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም.፤ የቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ከመቃጠሉ በፊት የቅዱስ ገብርኤልና የበዓለወልድ ጽላቶች በመሰረቃቸው በወቅቱ በአካባቢው ሰዎች መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ለወረዳው ፖሊስ አስተዳደር በማመልከታቸውም በተደረገው ከፍተኛ ርብርብ፤ የቅዱስ ገብርኤል ጽላት ከሂደቡ አቦቴ ወረዳ እንድሪስ ወንዝ ውስጥ ሊገኝ እንደቻለ ፖሊስ ይፋ አድርጓል፡፡ ሆኖም ግን የበዓለወልድ ጽላት እስከአሁን እንዳልተገኘ አያይዞ አስታውቋል፡፡

በተመሳሳይ መልኩም መጋቢት ፲፬ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ከቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን የተሰረቁት የቅዱስ ዮሐንስና የገብረ ክርስቶስ ጽላቶች መገኘታቸውንም ፖሊስ ጨምሮ ገልጿል፡፡በዕለቱ የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎችና የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ከሌሊቱ ፲ ሰዓት ኪዳን ለማድረስ ወደ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን በደረሱበት ወቅት የቤተ መቅደሱ በር ተከፍቶ እንዳገኙትና በመደናገጥ ፍለጋ ቢጀምሩም ማግኘት እንዳልቻሉ ተናግረዋል፡፡ የቅዱስ ዮሐንስና የገብረ ክርስቶስ ጽላት፤ እንዲሁም ንዋያተ ቅድሳት በቦታቸው እንዳልነበሩ ሊገነዘቡም ችሏል፡፡ የማኅበሩ አባላትና የሰንበት ተማሪዎቹም በመደናገጥ ሁሉም በየፊናቸው ከሌሊቱ ፲፩ ሰዓት ጀምሮ ለፍለጋ እንደተሰማሩና እስከ ማግሥቱ ቀን ፲ ሰዓት ድረስ ማግኘት እንዳልቻሉ ጠቅሷል፡፡

ነገር ግን የሰንበት ተማሪ በሆነው ወጣት አብርሃም ታደሰ አማካኝነት በተገኘው ፍንጭ ከተጠረጠሩት ግለሰቦች አንደኛውን በመለየት ወንጀሉን ለፖሊስ አሳውቀዋል፡፡ የቀረበውን ሪፖርት በመመርኮዝ ፖሊስም የተጠረጠሩትን ሦስት ግለሰቦች በመከታተል መኖሪያ ቤታቸውን ከማወቁም በላይ ፍተሻ በማድረግ ከተጠርጣሪዎቹ አንደኛው ቤት ውስጥ የቅዱስ ዮሐንስና የገብረ ክርስቶስ ጽላትን ለማግኘት ችሏል፡፡ የጠፉትንም ንዋያተ ቅድሳት ተራራ ላይ ወስደው ማቃጠላቸውን ወንጀለኞቹ ከሰጡት ሪፖርት አረጋግጧል፡፡ ይህንንም ችግር ለመፍታት የሃይማኖት አባቶች በዚህ ወቅት ስብሰባ በማካሄድ አፋጠኝ የመፍትሔ እርምጃ እንደሚወስዱ ለማኅበራችን አሳውቀዋል፡፡

‹‹ወዕለቱሰ ለእግዚአብሔር ግብተ ትመጽእ ከመ ሰራቂ፤ የእግዚአብሔር ቀን እንደሌባ ድንገት ትመጣለች›› (፪ ጴጥ.፫፥፲)

መጋቤ ሐዲስ ምስጢረ ሥላሴ ማናየ

ደብረ ዘይት ጌታችን ለደቀ መዛሙርቱ ምሥጢረ ምጽአቱን ያስተማረበት፤ የገለጠበት፤ ደቀ መዛሙርቱም የመምጣቱን ምሥጢር የተረዱበት፤ ከኢየሩሳሌም በስተምሥራቅ የሚገኝ በወይራ ዛፍ የተሞላ፤የተከበበ ተራራ ነው፡፡ ጌታችን በመዋዕለ ሥጋዌው አዘውትሮ ከተመላለሰባቸው ቦታዎችም አንዱ ነው፡፡ ቀን በምኩራብ ሲያስተምር ውሎ ሌሊት ሌሊት በደብረ ዘይት ያድር እንደነበር ቅዱስ ወንጌል ምስክር ነው፡፡

 ‹‹መዓልተ ይሜህር በምኩራብ ወሌሊተ ይበይት ውስተ ደብረ ዘይት፤ ዕለት ዕለት በመቅደስ ያስተምር ነበር፤ ሌሊት ግን ደብረ ዘይት ወደሚባል ተራራ ወጥቶ ያድር ነበር›› እንዲል ሉቃ፤ ፳፩፥፴፯። ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን በደብረ ታቦር እንደገለጠ ምሥጢረ ምጽአቱን በደብረ ዘይት ገልጧል፡፡ ይህንንም ሲገልጥ ሦስቱ የምሥጢር ደቀ መዛሙርት ተብለው የሚጠሩት ያዕቆብ፣ ዮሐንስ፣ ጴጥሮስ የዚህ ምሥጢር መደበኞች እንደነበሩ መተርጒማን አስተምረዋል፡፡ ከእነዚህ ደቀ መዛሙርት አንዱ የነበረው ቅዱስ ጴጥሮስ ማን ያርዳ የቀበረ፤ ማን ይንገር የነበረ እንዲሉ አበው ያን ጊዜ የተገለጠለትን የጌታችንን የመምጣት ቀን ‹‹የእግዚአብሔር ቀን እንደሌባ ድንገት ትመጣለች›› በማለት በዘመኑ፣ ኅልፍተ ሰማይ ወምድር፣ በዘመኑ ሙታን ትንሣኤ ሙታን የለም የሚል የስንፍና ትምህርት ይዘው ክርስቲያኖችን ያወናብዱ ለነበሩ ቢጽ ሐሳውያን ትንሣኤ ሙታን እንዳለ ገልጾ ጽፏል፡፡

ታዲያ ከእኛ ቀድመው የሞቱት ለምን ቀድመውን ተነሥተው አናይም? መከር አንድ ጊዜ ይካተታልን? ከሰማይስ ከፊሉ ታንጾ፣ ከመሬቱስ እኩሌታው ተጐርዶ ሲወርድ ለምን አናይም? እያሉ ሲያስቸግሩ ትምህርቱን ሲነቅፉ የክርስትናውን ትምህርት ሲያጐድፉ ለነበሩት በክሕደት ለሚመላለሱ ሰዎች ነው ይህን የጻፈው፡፡ የእግዚአብሔር ቀን ማን ናት? የሚለውን ማየት ጥሩ ነው፤ የእግዚአብሔር የተለየች ቀንስ አለችው? ቀናት በሙሉ የማን ሆነው ነው? የሚል ሐሳብ በውስጣችን መመላለሱ አይቀርም፤ እውነት ነው! ቀናቱ ሁሉ የእርሱ ናቸው፡፡ እርሱ ያለ ቀንና ያለ ጊዜ ከዘመን በፊት የነበረ ‹‹ያለና የሚኖር›› አምላክ ሲሆን ቀናትን የሰጠን ዘመናትን በልግስና የቸረን እርሱ ነው፤ ሁሉ ቀናት የእርሱ ገንዘቦች መሆናቸውን መጻሕፍት ያስተምራሉ፤ ‹‹ዚኣከ ውእቱ መዓልት ወዚኣከ ውእቱ ሌሊት – አቤቱ ቀኑ ያንተ፤ ሌሊቱም የአንተ ነው›› መዝ.፸፫፥፲፮። ሁሉም ባሪያዎችህ ናቸው፤ ቀኑ በትእዛዝህ ይኖራል፤ መዝ ፻፲፱፥፲፮፡፡

ዕለተ ምጽአት

የቀናት ሁሉ ማጠቃለያ፤ የሁሉም ፍጻሜ ዕለተ ምጽአት፣ ዳግም ምጽአት፣ የመጨረሻዋ ዕለት ናት፡፡ ቀን የምትባለው ከዕለተ ፍጥረት ጀምሮ ያለው ሥጋዊና ደማዊ ፍጥረት ሁሉ ፍጻሜውን የሚያገኝባት፤ ክፉም ደጉም የሠራው እንደየሥራው መጠን ዋጋውን የሚቀበልባት፤ የጭንቅ፣ የመከራ ቀን፤ ይህ ዓለም የሚያልፍባት፤ የሁሉም ፍጻሜ የሆነች ቀን ናት፡፡ ጌታችን ስለሚመጣባት የጌታ ቀን ተብላም ትጠራለች፡፡ ስለዚህ የመጨረሻዋ ቀን ዕለተ ምጽአት ወይም  በሌላ አነጋገር የፍርድ ቀን ስለተባለችው ነቢያት፣ ራሱ ጌታችንና ቅዱሳን ሐዋርያት አስተምረዋል፡፡ ቀዳማዊ ምጽአቱን እንደ ዘር ደኃራዊ ዳግም ምጽአቱን እንደ መከር አድርጐ ዓለም ይጠብቀዋል፤ በመጀመሪያው ምጽአቱ ትሕትናውን በዳግም ምጽአቱ ግርማውን ዓለም ሁሉ ያያል፤ መጀመሪያ በትሕትና መጣ ዓለምን አስተማረው፤ በኋላ በግርማ መንግሥት በክበበ ትስብእት ይመጣል፤ ይህ የጌታ ቀን ተበሎ ይጠራል፡፡ ‹‹እነሆ እንደ ምድጃ እሳት የሚነድ ቀን ይመጣል፤ ትዕቢተኞችና ኃጢአትን የሚሠሩ ሁሉ ገለባ ይሆናሉ፤ የሚመጣውም ቀን ያቃጥላቸዋል፤ ሚል.፬፥፩፡፡

ታላቁና የሚያስፈራው የእግዚአብሔር ቀን ሳይመጣ ነቢዩ ኤልያስን እልክላችኃለሁ››ሚል.፬፥፭፡፡ ‹‹የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጉብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ መክ.፲፪፥፩። ያ ቀን የመዓት፤ የመከራ፤ የጭንቀት፤ የመፍረስ፤ የመጥፋት፤ የጨለማ ፤ የጭጋግ፤ የደመናና፤ የድቅድቅና ጨለማ ቀን ነው›› ሶፎ. ፩፥፲፭።

‹‹እግዚአብሔር በግልጥ ይመጣል፤ መጥቶም ዝም አይልም፤ እሳት በፊቱ ይነድዳል›› መዝ. ፵፱፥፫። በዚያች ቀን ለእያንዳንዱ እንደየሥራው መጠን የሚከፍል መሆኑን አስረድቷል፤ እንደ ቀድሞው በትሕትና ሳይሆን በግርማ መንግሥቱ እንደሚመጣም ያሳያል፡፡ ‹‹ጌታ እግዚአብሔር እንደ ኃይል ይመጣል፤ እነሆ ዋጋው ከእርሱ ጋር ደመወዙም በፊቱ ነው›› ኢሳ. ፵፥፲።

‹‹እነሆ የእግዚአብሔር ቀን ይመጣል፤ በዚያም ቀን እግሮቹ በኢየሩሳሌም ትይዩ በምሥራቅ በኩል ባለው በደብረ ዘይት ተራራ ይቆማሉ›› ዘካ. ፲፬፥፩‐፭።  ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህችን ዕለት ከእነምልክቶቿ ያስተማረው በደብረ ዘይት ነው፤ ይህች ዕለትና የጌታ ምጽአት ምሥጢር ናቸው፤ ምሥጢረ ምጽአቱን በደቀ መዛሙርቱ አማካኝነት ለዓለም ገልጧል፤ አስረድቷልም፡፡

የምጽአት ምልክቶች

‹‹ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉ፤ ብዙዎችን ያስታሉ፡፡ ጦርነትን፤ የጦርነትንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠንቀቁ፤ አትደናገጡ፤ ዳሩ ግን መጨረሻው ገና ነው፡፡ ሕዝብ በሕዝብ ላይ፤መንግሥትም በመንግሥትም ላይ ይነሣሉ፤ በየሀገሩም ረሀብ፣ ቸነፈርም፤ የምድር መናወጥም ይሆናል፡፡ እነዚህም ሁሉ የምጥ ጣር መጀመሪያ ናቸው፡፡ ያንጊዜም ለመከራ አሳልፈው ይሰጡአችኋል፤ ይገድሉአችኋልም፤ ስለ ስሜም በሰዎች ሁሉ ዘንድ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ፡፡ ያንጊዜም ብዙዎች ሃይማኖታቸውን ይለውጣሉ፤ እርስ በእርሳቸውም አሳልፈው ይሰጣጣሉ፤ እርስ በእርሳቸውም ይጣላሉ፡፡ ብዙዎች ሐሰተኞች ነቢያትም ይመጣሉ፤ ብዙዎችንም ያስታሉ፡፡ ከዐመፅም ብዛት የተነሣ ፍቅር ከብዙዎች ዘንድ  ትጠፋለች፡፡ እስከ መጨረሻው የሚታገስ ግን እርሱ ይድናል፡፡ በሕዝብ ሁሉ ምስክር ሊሆን ይህ የመንግሥት ወንጌል በዓለም ይሰበካል፤ ያንጊዜም ፍጻሜ ይደርሳል›› ማቴ. ፳፬፥፭‐፲፬።

በዚያን ጊዜ የሰው ልጅ በክብሩ ከቅዱሳን መላእክት ጋር  በዙፋን ይቀመጣል፤ አሕዛብ ሁሉ በፊቱ ይሰበሰባሉ፤ እረኛም በጐችን ከፍየሎች እንደሚለይ እርስ በእርሳቸው ይለያቸዋል፤ በጐችን /ጻድቃንን/ በቀኝ ፍየሎችን /ኃጥኣንን/ በግራ ያቆማቸዋል፡፡ ‹‹ሙታንን ያስነሣቸዋል፤ ሙታን ይነሣሉ፤ በመቃብር ያሉ ሬሳዎችም ሕያዋን ይሆናሉ፤ ከአንተ የሚገኝ ጠለ ረድኤት ሕይወታቸው ነውና››፤ ኢሳ. ፳፮፥፲፱።

የዘለዓለም ሕይወት ይሰጣል፤ ሕይወት ለማይገባቸውም የዘለዓለም ቅጣት ይፈርድባቸዋል፡፡ በመቃብር ያሉት ድምፁን የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል መልካም ያደርጉ ለሕይወት ትንሣኤ ክፉ ያደርጉ ለፍርድ ትንሣኤ ይመጣሉ፤ ዮሐ.፭፥፳፰-፳፱። ከላይ እንዳየነው ጻድቃን በቀኝ ኃጥአን በግራ ይቆማሉ ማለት ጻድቃን በክብር መንግሥተ ሰማያትን ይወርሳሉ ኃጥኣን በውርደት ወደ ገሃነመ እሳት ይሄዳሉ፤ ‹‹እነዚያም ወደ ዘለዓለም ቅጣት ይሄዳሉ ጻድቃን ግን ወደ ዘለዓለም ሕይወት ይሄዳሉ›› እንዲል፤ ማቴ.፳፭፥፵፮፡፡

የእኛንም እድል ፈንታ ከጻድቃን ጋር ያድርግልን፤አሜን!