ማኅበረ መነኮሳቱ ድጋፍ እንዲደረግላቸው ጠየቁ

ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሐምሌ ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በምዕራብ ጐጃም ሀገረ ስብከት በሜጫ ወረዳ ቤተ ክህነት በጉታ ቀበሌ ልዩ ስሙ ናዳ በሚባል ቦታ የሚገኘው የፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም ገዳም መነኮሳትና አብነት ተማሪዎች ሰኔ ፳፪ እና ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በጣለው ከባድ ዝናም እና በረዶ ምክንያት ያለሙት ፍራፍሬ ሙሉ በሙሉ በመውደሙ፣ መኖርያ ቤታቸውም በመፍረሱ ድጋፍ እንዲደረግላቸው ጠየቁ፡፡

ምንኵስናን ከሊቅነት፣ አባትነትን ከሥራ ጋር አስተባብረው የያዙት የገዳሙ ዋና አስተዳዳሪ፣ የትርጓሜ መጻሕፍትና የቅኔ መምህሩ ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ በቦታው ተገኝተን ቃለ መጠይቅ ባደረግንላቸው ወቅት እንደ ገለጹልን በገዳሙ አካባቢ የሚገኘውን በጎርፍ የተሸረሸረ ሸለቆ በመከባከብ በ፲፱፻፹ ዓ.ም የተጀመረው የልማት ሥራ ገዳሙን በፌዴራል ሁለተኛ፤ በክልል ደግሞ አንደኛ ደረጃ እንዲያገኝና የክብር ሜዳልያ እንዲሸለም አድርጎታል፡፡

ዳሩ ግን ይህ የልማት ውጤት በበረዶው ምክንያት ከጥቅም ውጪ ኾኗል፡፡ ፍራፍሬውና ደኑም ተጨፍጭፏል፡፡ የጠበል መጠመቂያ ቦታዎች ተናውጠዋል፡፡ ንቦችም ከቀፎዎቻቸው ወጥተው ተሰደዋል፡፡ የመነኮሳቱና አብነት ተማሪዎች መኖርያ ቤቶችም ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡ በአጠቃላይ ከሰባ ሄክታር በላይ የሚገመት ሰብል በበረዶው ናዳ መውደሙን ከገዳሙ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ ‹‹ወደዚህ ገዳም ከመጣሁበት ጊዜ ጀምሮ እንደዚህ ዓይነት ክሥተት ደርሶ አይቼ አላውቅም›› ይላሉ ዋና አስተዳዳሪው የጉዳቱን ከፍተኛነት ሲገልጹ፡፡

በበረዶው ምክንያት የረገፈው ፍራፍሬ በከፊል

ከቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል በደረሰን መረጃ ማኅበረ ቅዱሳን ከገዳሙ ድረስ ልዑካንን በመላክ ለጊዜው የዘር መግዣ ይኾን ዘንድ የሃያ ሺሕ ብር የገንዘብ ድጋፍ አድርጓል፡፡ ማኅበሩ ካሁን በፊት አንድ ትራክተር ገዝቶ በስጦታ ለገዳሙ ያበረከተ ሲኾን፣ ለወደፊትም ገዳሙን በቋሚነት ለመደገፍ አቅዷል፡፡

በመጨረሻም ላደረገው የገንዘብ ድጋፍ ማኅበረ ቅዱሳንን፤ በጉልበት ሥራ በመራዳታቸው ደግሞ የአካባቢውን ሕዝበ ክርስቲያን የገዳሙ ዋና አስተዳዳሪ አመስግነው፣ ሌሎች በጎ አድራጊ ምእመናንም ቀለብ በመስጠት፣ ዘር በመግዛት፣ ልብስ በመለገስ፤ ከፍ ሲል ደግሞ መኖርያ ቤት በማደስ በአጠቃላይ በሚቻላቸው አቅም ዅሉ ድጋፍ እንዲያደርጉ ዋና አስተዳዳሪው በገዳሙ ስም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

በረዶው በአትክልቱ ላይ ያደረሰው ጉዳት በከፊል

የፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም ገዳም ከ፲፱፻፸፱ ዓ.ም ጀምሮ እስካሁን ድረስ የትርጓሜ መጻሕፍት እና የቅኔ ትምህርት የሚሰጥበት ጥንታዊ ገዳም ነው፡፡ ከዚህም ባሻገር ገዳሙ በልማት ሥራ የታወቀ ልዩ ቦታ ነው፡፡ ኾኖም በዘንድሮው ዓመት በወርኃ ሰኔ በአካባቢው በጣለው ከባድ በረዶ የተነሣ ፍራፍሬውና ደኑ በመውደሙ የገዳሙ መነኮሳትና የአብነት ተማሪዎች ኑሯቸው አደጋ ላይ ነው፡፡

ዝግጅት ክፍላችንም የገዳሙን መነኮሳት ከስደት፣ ጉባኤ ቤቱንም ከመዘጋት ለመታደግ፤ እንደዚሁም የልማት ቦታውን ወደ ጥንት ይዘቱ ለመመለስ ይቻል ዘንድ በተቻላችሁ አቅም ዅሉ ድጋፍ በማድረግ ከበረከቱ እንድትሳተፉ ይኹን ሲል መንፈሳዊ መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

ማሳሰቢያ

ገዳሙን በገንዘብ ለመደገፍ የምትፈልጉ ምእመናን በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መርዓዊ ቅርንጫፍ ሒሳብ ቍጥር፡- 10000 6261 1786 ገቢ ማድረግ የምትችሉ መኾኑን የገዳሙ ጽ/ቤት ያሳስባል፡፡ ተጨማሪ መረጃ ለማግኘትም በስልክ ቍጥር፡- 09 18 70 81 36 በመደወል የገዳሙን ዋና አስተዳዳሪ ማነጋገር ይቻላል፡፡

የቅዱስ ቂርቆስ እና ቅድስት ኢየሉጣ ተጋድሎ

በዝግጅት ክፍሉ

ሐምሌ ፲፰ ቀን ፳፻፱ .

በመጽሐፈ ስንክሳር፣ በድርሳነ ገብርኤል እና በገድለ ቂርቆስ ወኢየሉጣ እንደ ተመዘገበው ሐምሌ ፲፱ ቀን ቅዱስ ቂርቆስ እና ቅድስት ኢየሉጣ በሰማዕትነት መከራ የተቀበሉበት፤ ስማቸውን የሚጠሩ፣ ዝክራቸውንም የሚዘክሩ ምእመናን ይቅርታን፣ ምሕረትን እንደሚያገኙ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእነዚህ ቅዱሳን ቃል ኪዳን የሰጠበት ቀን ነው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ የተራዳቸውም በዚሁ ዕለት ነው፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን የሰማዕታቱ ቅዱስ ቂርቆስንና ቅድስት ኢየሉጣን ገድል በአጭሩ እናስታውሳችኋለን፤

ቅድስት ኢየሉጣ በሮም ግዛት በሚገኝ አንጌቤን በሚባል አገር በፈሪሃ እግዚአብሔር፣ በክርስትና ሃይማኖት እና በበጎ ምግባር ጸንታ ትኖር የነበረች ደግ ሴት ናት፡፡ በሥርዓት ያሳደገችው ቂርቆስ የሚባል ሕፃን ልጅም ነበራት፡፡ ይህቺ ቅድስት የዘመኑን አረማዊ መኰንን እለእስክንድሮስን በመፍራቷ ከልጇ ጋር ከሮም ወደ ጠርሴስ በተሰደደች ጊዜ መኰንኑ እነርሱ ከሚገኙበት አገር ገብቶ ክርስቲያኖችን እያሳደደ መግደል ጀመረ፡፡ የንጉሡ ወታደሮችም እግዚአብሔርን እንዲክዱ፤ ለጣዖት እንዲሰግዱ ቅድስት ኢየሉጣንና ቅዱስ ቂርቆስን አስፈራሯቸው፡፡ ቅዱሳኑ ግን ሃይማኖታቸውን ለመለወጥ ፈቃደኛ አልኾኑም ነበር፡፡ በዚህም መኰንኑ ተቈጥቶ በዓይንና በአፍንጫቸው ውስጥ ጨውና ሰናፍጭ በመጨመር፤ በጋሉ የብረት ችንካሮች በመቸንከርና መላ ሰውነታቸውን በመብሳት በብዙ ዓይነት መሣሪያ አሠቃያቸው፡፡ እግዚአብሔርም የጋሉ ብረቶችን እንደ ውኀ ያቀዘቅዝላቸው፤ ሥቃያቸውንም ያቀልላቸው ነበር፡፡

በሌላ ጊዜም በገመድ አሳሥሮ ንጉሡ ሲያስጨንቃቸው ከቆየ በኋላ ራሳቸውን ከቆዳቸው ጋር አስላጭቶ እሳት አነደደባቸው፡፡ ዳግመኛም ከትከሻቸው እስከ እግራቸው ድረስ በሚደርሱ ችንካሮች ቸነከራቸው፡፡ በዚህ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ ከሥቃያቸው አድኗቸዋል፡፡ አሁንም ቀኑን ሙሉ በልዩ ልዩ የሥቃይ መሣሪያዎች ቢያስጨንቃቸውም የእግዚአብሔር ኃይልና የቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት አልተለያቸውም ነበርና ምንም ዓይነት ጉዳት አልደረሰባቸውም፡፡ እንደ ገናም በመጋዝ ሰንጥቀው በብረት ምጣድ በቆሏቸው ጊዜ ጌታችን ከሞት አነሣቸውና በመኰንኑ ፊት ድንቅ ተአምራትን አደረጉ፡፡ ከተአምራቱ መካከልም ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ የመኰንኑን ጫማ በጸሎት ወደ በሬነት እንዲቀየር ማድረጉ ተጠቃሽ ሲኾን፣ መኰንኑ በተአምራቱ ተቈጥቶ የቅዱስ ቂርቆስን ምላስ አስቈርጦታል፤ ጌታችንም ምላሱን አድኖለታል፡፡

ዳግመኛም በፈላ የጋን ውኀ ውስጥ ቅዱሳን ቂርቆስና ኢየሉጣን ሊጨምሯቸው ሲሉ ቅድስት ኢየሉጣ በፈራች ጊዜ ቅዱስ ቂርቆስ ‹‹እናቴ ሆይ አትፍሪ፤ አናንያ፣ ዓዛርያና ሚሳኤልን ከእሳት ነበልባል ያዳናቸው እግዚአብሔር እኛንም ከዚህ የፈላ ውኀ ያድነናል›› እያለ ያረጋጋትና በተጋድሎዋ እንድትጸና ወደ እግዚአብሔር ይጸልይላት ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ተያይዘው ወደ ጋኑ ውስጥ ገቡ፡፡ ያ ውኀም እንደ ውርጭ ቀዘቀዘ፡፡ ደግሞም ወታደሮቹ መንኰራኵር ባለበት የብረት ምጣድ ውስጥ አስገብተው ሥጋቸው እስኪቈራረጥ ድረስ በጎተቷቸው ጊዜ ቅዱስ ገብርኤል አድኗቸዋል፡፡ በመጨረሻም ከእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ተቀብለው በመንፈቀ ሌሊት አንገታቸውን ተቈርጠው በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ እስከ ሞት ድረስ በታመኑበት ተጋድሏቸውም ከእግዚአብሔር ዘንድ የሕይወትን አክሊል ተቀብለዋል፡፡

በአጠቃላይ ቅዱስ ቂርቆስና ቅድስት ኢየሉጣ የዚህን ዓለም ጣዕም በመናቅ ‹‹ሞት ቢኾን፣ ሕይወትም ቢኾን፣ መላእክትም ቢኾኑ፣ ግዛትም ቢኾን፣ ያለውም ቢኾን፣ የሚመጣውም ቢኾን፣ ኃይላትም ቢኾኑ፣ ከፍታም ቢኾን፣ ዝቅታም ቢኾን፣ ልዩ ፍጥረትም ቢኾን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ካለ ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየን እንዳይችል ተረድቼአለሁ፤›› (ሮሜ. ፰፥፴፰-፴፱) በማለት ቅዱስ ጳውሎስ የተናገረውን ቃል በተግባር በማሳየት ለክርስቶስ ፍቅር ሲሉ ራሳቸውን ለመከራና ለሞት አሳልፈው ሰጥተዋል፡፡ ቅዱሳኑ ተጋድሏቸውን እስኪፈጽሙ ድረስም ቅዱስ ገብርኤል አልተለያቸውም፡፡ በቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት ቅድስት ኢየሉጣና ቅዱስ ቂርቆስ ብቻ ሳይኾኑ ብዙ ምእመናንም ተጠቅመዋል፡፡ ስሙ በሚጠራባቸው ገዳማትና አድባራት መልአኩ የሚያደርጋቸው ድንቅ ድንቅ ተአምራት ለዚህ ማስረጃዎች ናቸው፡፡ ይህም ቅዱሳን መላእክት በእግዚአብሔር ስም መከራ የሚቀበሉ ምእመናንን እንደሚጠብቁና ከልዩ ልዩ ደዌ እንደሚፈውሱ የሚያስረዳ ታሪክ ነው፡፡

እኛም በሃይማኖታችን ምክንያት መከራ ባጋጠመን ጊዜ ቈራጥ ልብ ያለው ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ ‹‹እናቴ ሆይ አትፍሪ›› እያለ እናቱን በመከራ እንድትጸና እንዳረጋጋትና ለሰማዕትነት እንድትበቃ እንዳደረጋት ዅሉ፣ ዘለዓለማዊውን የእግዚአብሔርን መንግሥት በአንድነት ለመውረስ እንድንችል ‹‹አይዞህ! አይዞሽአትፍራ! አትፍሪ›› በመባባል በዚህ ዓለም የሚገጥመንን መከራ ታግሠን፣ እስከ ሞት ድረስ በሃይማኖታችን ጸንተን መኖር ይገባናል፡፡ ክርስትና ለብቻ የሚጸደቅበት መንገድ ሳይኾን በጋራ ዋጋ የሚያገኙበት የድኅነት በር ነውና፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም ቅዱስ ቂርቆስንና ቅድስት ኢየሉጣን የተራዳው የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል በአማላጅነቱ እንዲጠብቀን ‹‹በተአምኖ ንሴፎ ትንባሌ ዚአከ መዓልተ ወሌሊተ፤ በእግዚአብሔር ታምነን በቀንም በሌሊትም የአንተን ልመና ተስፋ እናደርጋለን›› እያልን ዘወትር ልንማጸነው ያስፈልጋል፡፡ እርሱ ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር በተሰጠው ቃል ኪዳን መሠረት ከሚደርስብን ልዩ ልዩ መከራና ሥቃይ ያድነናልና፡፡ ‹‹የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙርያ ይሠፍራል፤ ያድናቸውማል፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (መዝ. ፴፬፥፯)፡፡ ይህን እንድናደርግም የቅዱሳን ተራዳኢነት አይለየን፡፡ የቅዱስ ገብርኤል፣ ቅድስት ኢየሉጣ እና ቅዱስ ቂርቆስ ጸሎታቸው፣ ምልጃቸው ይጠብቀን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዘመነ ክረምት – ክፍል ሁለት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሐምሌ ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች፤ በጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም ሰላምታ እንደምን ሰነበታችሁ? በርኅራኄው እየጠበቀ፣ በቸርነቱ እየመገበ እስከ ዛሬ ድረስ ያቆየን ልዑል እግዚአብሔር የተመሰገነ ይኹን! እንደምታስታዉሱት ሰኔ ፳፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ባስተላለፍነው ክፍል አንድ ዝግጅታችን ከሰኔ ፳፮ እስከ ሐምሌ ፲፰ ቀን ያለው የዘመነ ክረምት ክፍል ስለ ክረምት መግባት፣ ስለ ዘርዕ እና ደመና የሚነገርበት ወቅት እንደ ኾነ በማስገንዝብ ወቅቱን (በዓተ ክረምትን) የሚመለከት አጭር ትምህርት ይዘንላችሁ ቀርበን ነበር፡፡ ስለ ዘር እና ደመና የሚያትተውን ቀጣይ ክፍል ደግሞ እንደሚከተለው አዘጋጅተነዋል፤  

ዘርዕ

ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ ‹‹እለ ይዘርዑ በአንብዕ ወበሐሤት የዐርሩ ሶበሰ የሐውሩ ወፈሩ እንዘ ይበክዩ ወጾሩ ዘርዖሙ ወሶበ የአትዉ መጽኡ እንዘ ይትፌሥሑ ወጾሩ ከላስስቲሆሙ፤ በልቅሶ የሚዘሩ በደስታ ይሰበስባሉ፡፡ በሔዱ ጊዜ ዘራቸውን ተሸክመው እያለቀሱ ተሰማሩ፤ በተመለሱ ጊዜ ግን ነዶአቸውን ተሸክመው ደስ እያላቸው መጡ፤›› በማለት እንደ ተናገረው (መዝ. ፻፳፭፥፭-፮)፣ ይህ ወቅት አርሶ አደሩ በእርሻና ዘር በመዝራት የሚደክምበት፣ የምርት ጊዜውንም በተስፋ የሚጠባበቅበት ጊዜ ነው፡፡ ይህ የአርሶ አደሩ ድካምና ተስፋም የሰውን ልጅ የሕይወት ጉዞና ውጣ ውረድ እንደዚሁም በክርስቲያናዊ ምግባር የሚወርሰውን ሰማያዊ መንግሥት ያመለክታል፡፡

ምድር ከሰማይ ዝናምን፣ ከምድርም ዘርን በምታገኝበት ወቅት ዘሩን አብቅላ ለፍሬ እንዲበቃ ታደርጋለች፡፡ በምድር የምንመሰል የሰው ልጆችም ከእግዚአብሔር ባገኘነው ጸጋ ተጠቅመን፣ ከቅዱሳት መጻሕፍት እና ከመምህራነ ቤተ ክርስቲያን የምናገኘውን ቃለ እግዚአብሔር በተግባር ላይ ማዋል እንደሚገባን ከምድር እንማራለን፡፡ ይህን ካደረግን ዋጋችን እጅግ የበዛ ይኾናል፤ ከዚህም አልፎ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ እንበቃለን፡፡ የተዘራብንን ዘር ለማብቀል ማለትም ቃሉን በተግባር ለማዋል ካልተጋን ግን በምድርም በሰማይም ይፈረድብናል፡፡ ‹‹ምድርም በእርስዋ የሚወርደውን ዝናብ ከጠጣች፣ ያን ጊዜ ስለ እርሱ ያረሱላትን መልካም ቡቃያ ታበቅላለች፡፡ እሾኽን እና ኵርንችትን ብታበቅል ግን የተጣለች ናት፡፡ ለመርገምም የቀረበች ናት ፍጻሜዋም ለመቃጠል ይኾናል፤›› በማለት ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ገለጸው (ዕብ. ፮፥፯-፰)፡፡

ደመና

እግዚአብሔር አምላካችን የውቅያኖስ እና የሐኖስ ድንበር ይኾን ዘንድ በውኃ መካከል ጠፈርን ፈጥሮ ከጠፈር በታች (በዚህ ዓለም) ያለው ውኃ በአንድ ቦታ እንዲወሰን አድርጎታል፡፡ ከዚያም ከምድር እስከ ብሩህ ሰማይ ድረስ የነበረውን ውኃ ከሦስት ከፍሎ ሢሶውን አርግቶ ጠፈር ብሎ ሰይሞታል፡፡ ከጠፈር በላይ ያለውን ሢሶው የውኃ ክፍል ሐኖስ ብሎታል፡፡ ሢሶውንም ይህንን ዓለም ከሰባት ከፍሎ ሰባተኛውን ዕጣ አጐድጕዶ በዚያ ወስኖ ስሙን ውቅያኖስ ብሎ ጠርቶታል፡፡ የብሱን ክፍል ደግሞ ምድር ብሎ ሰይሞታል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ከደረቅ ምድር ደረቅ ጢስን፤ ከርጥብ ባሕር ርጥብ ጢስን አስወጥቶ እንደ ጉበት በለመለመች ምድር ላይ ደመናን አስገኝቷል (ትርጓሜ መዝሙረ ዳዊት፣ መዝ. ፻፴፬፥፯)፡፡

ከላይ እንደ ተጠቀሰው ደመና፣ ዝናምን የሚሸከም የማይጨበጥ፣ የማይዳሰስ ጢስ መሰል ፍጥረት ነው፡፡ በትነት አማካይነት፣ በደመና ተሸካሚነት ከውቅያኖሶች እና ከወንዞች እየተቀዳ ወደ ሰማይ ተወስዶ እንደ ገና ተመልሶ ወደ ምድር የሚጥለው ውኃ ዝናም ይባላል፡፡ ይኸውም በእግዚአብሔር ጥበብ በደመና ወንፊትነት ተጣርቶ ለፍጡራን በሚመችና በሚጠቅም መጠን በሥርዓት ይወርዳል፡፡ ‹‹ያጸንዖ በፍኖተ በድው ከመ ይዝንም ብሔረ ኀበ አልቦ ሰብእ ወኢይነብሮ ዕጓለ እመሕያው፤ ዝናሙን ሰው በሌለበት በምድረ በዳ ያዘንመዋል፤›› እንዳለ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ በቅዳሴው፡፡ ይህ ኃይለ ቃል እግዚአብሔር በረዶውን በምድረ በዳ አፍስሶ የጠራውን ውኃ ሰው ወዳለበት እንዲዘንም ማድረጉን የሚያስረዳ መልእክት የያዘ ሲኾን፣ ምሥጢሩም ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንበለ ዘርዐ ብእሲ (ያለ ወንድ ዘር) በልዩ ጥበቡ ተፀንሶ ከቅድስት ድንግል ማርያም መወለዱንና በለበሰው ሥጋ በምድር ተመላልሶ ወንጌልን ማስተማሩን፤ እንደዚሁም ‹‹ሑሩ ወመሀሩ፤ ሒዱና አስተምሩ›› ብሎ ቅዱሳን ሐዋርያትን በመላው ዓለም ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት ማሠማራቱን ያመለክታል (ትርጓሜ ቅዳሴ ኤጲፋንዮስ፣ ፪፥፭-፮)፡፡

‹‹ዘይገለብቦ ለሰማይ በደመና ወያስተዴሉ ክረምተ ለምድር ዘያበቍል ሣዕረ ውስተ አድባር ወሐመልማለ ለቅኔ እጓለ እመሕያው፤ ሰማዩን በደመና የሚሸፍን፣ ለምድርም ዝናምን የሚያዘጋጅ፣ ሣርን በተራሮች ላይ፣ ልምላሜውንም ለሰው ልጆች አገልግሎት የሚያበቅል … እርሱ ነው፤›› (መዝ. ፻፵፮፥፰) በማለት ቅዱስ ዳዊት እንደ ዘመረው እግዚአብሔር አምላክ ውኃ ከውቅያኖሶች ተቀድቶ፣ በደመና ተቋጥሮ፣ ወደ ሰማይ ሔዶ፣ እንደ ገና ተመልሶ ወደ ምድር እንዲዘንም እያደረገ ዓለምን በልዩ ጥበቡ ይመግባል፡፡ ይህን አምላካዊ ጥበብ በማድነቅ ‹‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር ጸባዖት አምላክነ በተነ ጊሜ ረቂቅ ዘያአቍሮ ለማይ ያዐርጎ እምቀላይ ወያወርዶ እምኑኀ ሰማይ፤ ረቂቅ በኾነ የጉም ተን ውኃውን የሚቋጥረው፤ ከወንዝ ወደ ላይ የሚያወጣው፤ ከሩቅ ሰማይም የሚያወርደው እግዚአብሔር ቅዱስ፣ ልዩ፣ ምስጉን አሸናፊ አምላክ ነው፤›› በማለት ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ልዑል እግዚአብሔርን ያመሰግናል (መጽሐፈ ሰዓታት ዘሌሊት)፡፡

የደመና አገልግሎቱ ዝናምን ከውቅያኖስ በመሸከም ወደ ምድር እያጣራ ማውረድ ነው፡፡ ኾኖም በሰማይ የሚዘዋወርና በነፋስ የሚበታተን ዝናም አልባ ደመናም አለ፡፡ በመልካም ግብር፣ በትሩፋት ጸንተው የሚኖሩ ምእመናን ዝናም ባለው ደመና ሲመሰሉ፣ ያለ ክርስቲያናዊ ምግባር በስመ ክርስትና ብቻ የምንኖር ምእመናን ደግሞ ዝናም በሌለው ደመና እንመሰላለን፡፡ ሐዋርያው ይሁዳ ‹‹… በነፋስ የተወሰዱ ውኃ የሌለባቸው ደመናዎች …›› በማለት የተናገረውም የእንደነዚህ ዓይነት ሰዎችን ሕይወት ይመለከታል (ይሁዳ ፩፥፲፪)፡፡ አንድም ዝናም ያለው ደመና የእመቤታችን የቅድስት ደንግል ማርያም ምሳሌ ነው፡፡ እርሷ ንጹሑን የሕይወት ውኃ (ዝናም) መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አስገኝታልናለችና፡፡ ‹‹አንቲ ዘበአማን ደመና እንተ አስተርአይኪ ለነ ማየ ዝናም፤ የዝናም ውኃን ያስገኘሽልን እውነተኛ ደመና አንቺ ነሽ፤›› እንዳለ ቅዱስ ኤፍሬም (ውዳሴ ዘረቡዕ)፡፡ እኛም ውኃ ሳይኖረው በነፋስ እንደሚበታተን ዝናም አልባ ደመና ሳይኾን፣ ዝናም እንደሚሸከም ደመና በምግባረ ሠናይ ጸንተን ልንኖር ይገባል፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም የእግዚአብሔርን ቃል ሕይወታችን በማድረግ ራሳችንን ከማዳን ባሻገር ለሌሎችም አርአያና ምሳሌ ልንኾን ያስፈልጋል፡፡

ስለ ደመና ሲነገር ዝናምም አብሮ ይነሣል፡፡ ዝናም ያለ ደመና አይጥልምና፡፡ ዝናም የቃለ እግዚአብሔር ምሳሌ ነው፤ ዝናም ለዘር መብቀል፣ ማበብና ማፍራት ምክንያት እንደ ኾነ ዅሉ በቃለ እግዚአብሔርም በድንቁርና በረኃ የደረቀ ሰውነት ይለመልማል፤ መንፈሳዊ ሕይወትን የተራበችና የተጠማች ነፍስም ትጠግባለች፤ ትረካለችና፡፡ ‹‹ሲሲታ ለነፍስ ቃለ እግዚአብሔር፤ የነፍስ ምግቧ የእግዚአብሔር ቃል ነው፤›› እንዲል፡፡ በሌላ በኩል በዚህ ዓለም የሚያጋጥም ልዩ ልዩ ፈተናም በዝናም ይመሰላል፡፡ ጌታችን በወንጌል እንደ ነገረን ቃሉን ሰምቶ በሥራ ላይ የሚያውል ክርስቲያን ቤቱን በዓለት ላይ የመሠረተ ልባም ሰውን ይመስላል፡፡ ቤቱ በጐርፍ ቢገፋ አይናወጥምና፡፡ ቃሉን የማይተገብር ክርስቲያን ግን ያለ መሠረት በአሸዋ ላይ ቤቱን የሠራ ሰነፍ ሰውን ይመስላል፡፡ ቤቱ በዝናብ፣ በጐርፍና በነፋስ ተገፍቶ የከፋ አወዳደቅ ይወድቃልና፡፡ ይህም ሃይማኖቱን በበጎ ልቡና የያዘ ክርስቲያን ከልዩ ልዩ አቅጣጫ በሚደርስበት መከራ ሳይፈራና በሰዎች ምክር ሳይታለል፤ በኢዮብ እንደ ደረሰው ዓይነት ከባድ ፈተና ቢመጣት እንኳን ሳያማርር በምክረ ካህን፣ በፈቃደ ካህን እየታገዘ አጋንንትን ድል እያደረገ በሃይማኖቱ ጸንቶ እንደሚኖር፤ በአንጻሩ ሃይማኖቱን በበጎ ሕሊና ያልያዘ ክርስቲያን ግን ፈተና ባጋጠመው ጊዜ በቀላሉ እንደሚክድና ለአጋንንትም እጁን እንደሚሰጥ የሚያስረዳ ምሥጢር አለው (ትርጓሜ ወንጌል፣ ማቴ. ፯፥፳፬-፳፯)፡፡

ዝናም ሲጥል የወንዞች ሙላትና ማዕበል ቤት እንዲያፈርስ፤ ንብረት እንዲያወድም በክርስቲያናዊ ሕይወት በሚያጋጥም ፈተናም በእምነት መዛል፣ በመከራ መያዝ፣ መቸገር፣ መውጣትና መውረድ ያጋጥማል፡፡ ዝናም ለጊዜው እንዲያስበርድና ልብስን እንዲያበሰብስ ፈተናም እስኪያልፍ ድረስ ያሰንፋል፤ ያስጨንቃል፤ ያዝላል፡፡ ነገር ግን ዝናም፣ ጐርፍና ማዕበል ጊዜያቸው ሲደርስ ጸጥ እንደሚሉ ዅሉ፣ ምድራዊ ፈተናም ከታገሡት የሚያልፍ የሕይወት ክሥተት ነው፡፡ ስለዚህ ዅላችንም እምነታችንን በጠንካራ መሠረት ላይ በመገንባት በውኃ ሙላትና በማዕበል ከሚመሰል ውድቀት ራሳችንን እንጠብቅ፡፡ ዝናም ሲመጣ የውኆችን ሙላትና ጐርፉን ሳንፈራ ወደ ፊት የምናገኘውን ምርት ተስፋ እንደምናደርግ፣ በሃይማኖታችን ልዩ ልዩ ፈተና ሲያጋጥመንም ከእግዚአብሔር ዘንድ የምናገኘውን ሰማያዊ ዋጋ በማሰብ ዅሉንም በትዕግሥት እናሳልፍ፡፡

ይቆየን

ኤጲስ ቆጶሳቱ ሳይለግሙ ምእመናንን እንዲያገለግሉ ፓትርያርኩ አሳሰቡ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሐምሌ ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም  

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የኤጲስ ቆጶሳት ሥርዓተ ሲመት በተፈጸመበት ዕለት በሰጡት ቃለ ምዕዳን ለዚህ በዓለ ሢመት ያደረሳቸውን ልዑል እግዚአብሔርን አመስግነዋል፡፡ ለኤጲስ ቆጶሳቱም የሚከተለውን አባታዊ ምክር ለግሰዋል፤

‹‹እግዚአብሔር የሰጣችሁን ሕዝብ በቀንም በሌሊትም ከእርሱ ሳትለዩ፣ በዅለንተናዊ ሕይወታችሁ ባለ አቅማችሁ ዅሉ ሳትለግሙ አገልግሉት፡፡ ከስደት፣ ከእንግልት ተገላግሎ የልማት ኃይል በመኾን አገሩን እንዲገነባ፤ ሃይማኖቱንና ባህሉን እንዲጠብቅ ያለመታከት አስተምሩት፡፡ ከመንፈሳዊ መሠረተ ትምህርት ጀምሮ እስከ ኤጲስቆጶስነት ድረስ እየመገበና እየተንከባከበ ለታላቅ ክብር ያበቃችሁን ሕዝብ የልቡን ሃይማኖታዊ ትርታ እያዳመጣችሁ በወቅቱ እየደረሳችሁ አስተምሩት፤ አጽናኑት፡፡ ልጆቹን በተኩላዎች ከመነጠቅ አድኑለት፡፡ ወጣቱ ትውልድ ከሐሺሽ፣ ከአደንዛዥ ዕፅ፣ ከሱሰኝነት፣ ከሥራ ፈትነትና ከመጤ ጎጂ ባህል እንዲላቀቅ አድርጉ፡፡ የኢትዮጵያ ሕዝበ ክርስቲያን በአሁኑ ጊዜ ከሃይማኖት አባቶች የሚፈልገው ይህንኑ ነው፡፡››

የጸሎተ አስኬማ ሥርዓቱ በከፊል

ቅዱስነታቸው በተጨማሪም በየሀገረ ስብከቱ በየመንበራቸው ተገኝተው ከሕዝቡ ጎን ሳይለዩ ተግተው የሚሠሩ፤ ዅሉንም ወገን በእኩል ዓይን የሚያዩና የሚያስተናግዱ፤ በሕዝቡ መካከል ሰላምን የሚሰብኩ፤ ከማናቸውም ርዕዮተ ዓለም ደጋፊነት የተለዩና ከጣልቃ ገብነት የጸዱ፤ ከዅሉም በላይ ለአንዲት ሉዓላዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነት መከበር በጽናት የቆሙ አባቶችን አገራችን ኢትዮጵያ እንደምትሻ ገልጸው፣ ‹‹ዓለሙ በውስጡ ያለና የሌለ ኃይሉን አግበስብሶ እንደሚታገላችሁ አትርሱ፤ ነገር ግን የድል አድራጊው ጌታ ሠራዊት ናችሁና የመጨሻው ድል የእናንተ መኾኑን አትጠራጠሩ›› በማለት ኤጲስ ቆጶሳቱ በምንም ዓይነት ፈተና ሳይበገሩ ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተሰጣቸውን ሓላፊነት በአግባቡ እንዲወጡ መክረዋል፡፡

የጸሎተ አስኬማ ሥርዓቱ በከፊል

ሹመት ማለት የሥራ መገልገያ መሣርያ እንጂ የግል መገልገያ እንዳልኾነ፤ አገልግሎቱም መውጣት መውረድን፣ መንገላታትን፣ ድካምን ከዚያም አልፎ መሥዋዕትነትን እንደሚጠይቅ ያስታወሱት ፓትርያርኩ፣ ‹‹በዚህ ሐዋርያዊ ጉዞ ብዙ መሰናክሎች ሊገጥሟችሁ ቢችሉም ዅሉም ችግሮች ከሞት በታች እንጂ ከሞት በላይ አይደሉምና ከሐዋርያዊ ተልእኳችሁ የሚገታችሁ ምንም ነገር አይኖርም፡፡ ምክንያቱም የገባችሁት ቃል ኪዳን እስከ ሞት ድረስ ለመዳፈር ነውና›› ሲሉ እስከ ሞት ድረስ በመታመን የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ ተልእኮ እንዲያስፋፉ ለኤጲስ ቆጶሳቱ መልእክታቸውን አስተላለፈዋል፡፡

የኤጲስ ቆጶሳቱ ሥርዓተ ሲመት አፈጻጸም በከፊል

ቅዱስነታቸው፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከአኃት አብያተ ክርስቲያናት ጋር ስትነጻጸር በምእመናን ብዛት፣ በሃይማኖት ጽናት፣ በሐዋርያዊ ትውፊት፣ በአበው ቀኖና፣ በሃይማኖታዊ ባህልና በሥርዓተ አምልኮ አፈጻጸም ቀዳሚውን ሥፍራ እንደምትይዝ አውስተው፣ ቤተ ክርስቲያን በአበው ሐዋርያዊ ተጋድሎ ጠብቃ ያቆየችውን ይህን ሀብተ መንፈስ ቅዱስ ለመጭው ትውልድ ለማስተላለፍ ብቃትና ተነሣሽነት ያላቸውን ኤጲስ ቆጶሳት መሾም ተቀዳሚ ተግባሯ እንደ ኾነ፤ የኤጲስ ቆጶሳት ሹመትም ሐዋርያዊ ተልእኮውን ለማስፋፋት ከፍተኛ ሚና እንዳለው አስረድተዋል፡፡

ሥርዓተ ሲመት የተፈጸመላቸው ኤጲስ ቆጶሳት በከፊል

አገራችን ኢትዮጵያ በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅኝት የተቀረፀ፤ ለሃይማኖት፣ ለሥነ ምግባር፣ ለፍትሕ፣ ለልማትና ለአንድነት የተመቸ ሕዝብ እንዳላት፤ ይህን የተቀደሰ ባህልና ሥነ ምግባር ለማስቀጠልም ከቤተ ክርስቲያን አባቶች ብዙ እንደሚጠበቅ የገለጹት ቅዱስ ፓትርያርኩ ‹‹በተለይም ብፁዓን አበው ሊነ ጳጳሳት እና ኤጲስ ቆጶሳት ኢትዮጵያውያንን በአባትነት መንፈስ በማቅረብ ዅሉም በሰላም፣ በወንድማማችነት፣ በመከባበር፣ በመተማመንና በመቻቻል አብረው እንዲኖ፤ እንደዚሁም ትውልዱ እንደ አባቶቹ ደማቅ ታሪክ ሠርቶ እንዲያልፍ ያልተቆጠበ ጥረት ማድረግ ይኖርባችኋል›› ብለዋል፡፡

ሥርዓተ ሲመት የተፈጸመላቸው ኤጲስ ቆጶሳት በከፊል

በመቀጠልም ቤተ ክርስቲያናችን በሃይማኖት አስተምህሮ እና ይዘት፣ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን፣ በሐዋርያዊ ትውፊት፣ በሥርዓተ አምልኮ አፈጻጸም እና በቅዱስ ባህል ምሥረታ እንከን የለሽ ብትኾንም በአስተዳደር፣ በፋይናንስና ንብረት አያያዝ፣ በምእመናን ክብካቤና በሐዋርያዊ ተልእኮ ክንውን፣ በእናቶችና በወጣቶች አያያዝ ከዘመኑ ጋር መራመድ አለማቻሏ የወቅቱ የቤተ ክርስቲያናችን ተግዳሮት መኾኑን ቅዱስነታቸው ጠቅሰው፣ ይህን ተግዳሮት ከሥር መሠረቱ ነቅሎ በመጣል ወደሚፈለገው መልካም አስተዳደር ለመሸጋገር የአሁኖቹ ሥዩማን ኤጲስ ቆጶሳት ከቀደሙት ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በመቀናጀት ጉልህ ሚና እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ

እንደ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ማብራርያ በአሁኑ ጊዜ ሃይማኖት እና ሥነ ምግባር እጅግ ትኩረት የሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች ከመኾናቸው አኳያ፣ የዘመኑ ትውልድ በሃይማኖት የጸና፤ በሥነ ምግባር የቀና፤ ለአገር እና ለወገን ክብር የቆመ እንዲኾን የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮን ማስፋፋት እና የአባቶች አርአያነት ያለው ሕይወት መኖር ቍልፍ መሣርያ ነው፡፡

በተመሳሳይ መልኩ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ እንደዚሁም ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና በክልል ትግራይ ደቡባዊ ማይጨው ዞን፣ ደቡብ ምሥራቅና ምሥራቃዊ አዲግራት አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በዕለቱ ባስተላለፉት መልእክት ለኤጲስ ቆጶስነት መመረጥ የእግዚአብሔር ጥሪ መኾኑን በማስረዳት ኤጲስ ቆጶሳቱ አባታዊ ሓላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲፈጽሙ፤ ሕዝበ ክርስቲያኑም ለአባቶች በመታዘዝ ኦርቶዶክሳዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ አስተምረዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተመረጡት ዐሥራ አምስቱ ኤጲስ ቆጶሳት ቅዱስ ፓትርያርኩ እና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት ሐምሌ ፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ገዳም ጸሎተ አስኬማ ከተደረሰላቸው በኋላ በነጋታው ሐምሌ ፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በቅዱስ ፓትርያርኩ ቡራኬ ሥርዓተ ሢመት ተፈጽሞላቸዋል፡፡

ኤጲስ ቆጶሳቱ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ በመጠበቅና በማስጠበቅ የተሰጣቸውን አባታዊ አደራ በሓላፊነት እንደሚወጡ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትና በሕዝበ ክርስቲያኑ ፊት ሃይማኖታዊ አቋማቸውን ገልጸዋል፡፡

በአቋማቸውም በእግዚአብሔር ዘለዓለማዊ አምላክነት እንደሚያምኑ፤ በኒቅያ፣ ቍስጥንጥንያ እና ኤፌሶን በተወሰነው ውሳኔ መሠረት የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ጠብቀው እንደሚያስጠብቁና እንደሚያስምሩ፤ በሥላሴ አንድነትና ሦስትነት፣ በእግዚአብሔር ወልድ የባሕርይ አምላክነት፣ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክነት፣ ዘለዓለማዊ ድንግልናዋ እና አማላጅነቷ፤ እንደዚሁም በቅዱሳን መላእክት፣ ነቢያት፣ ሐዋርያት፣ ሰማዕታት እና ጻድቃን አማላጅነት አምነው እንደሚያስተምሩ፤ ይህን ትምህርት የሚቃወሙትንና ተሐድሶ ነን የሚሉ መናፍቃንን እንደሚያወግዙም ቃል ገብተዋል፡፡

ኤጲስ ቆጶሳቱ ቃለ መሐላ ሲፈጽሙ

ምሥጢረ ቍርባንን በተመለከተም “ካህኑ ሲባርከው ኅብስቱ ተለውጦ አማናዊ ሥጋ ወልደ እግዚአብሔር፣ ወይኑም ተለውጦ አማናዊ ደመ ወልደ እግዚአብሔር መኾኑን፤ ጥምቀት አንዲት መኾኗን እናምናለን፤ በቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር ያሉ ምእመናን በተዋሕዶ ሃይማኖት ጸንተው፣ ቀኖናዊ ሥርዓቷን አክብረውና ጠብቀው እንዲኖሩ ተግተን እናስተምራለን፡፡ ይህን ዅሉ ለማድረግ እግዚአብሔር ይረዳን ዘንድ እንማጸናለን፤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጉባኤ ፊት ቃል ኪዳን እንገባለን” የሚል ቃለ መሐላ ፈጽመዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በአፋን ኦሮሞ ያሳተማቸው መጻሕፍት በከፊል

ማኅበረ ቅዱሳን በአፋን ኦሮሞ ካሳተማቸው መጻሕፍት መካከል ጥቂቶቹ የሚከተሉት ናቸው፤

የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት በአፋን ኦሮሞ

ሐምሌ ፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ሒዱና አሕዛብን ዅሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው ያዘዝኋችሁንም ዅሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው›› (ማቴ. ፳፰፥፲፱) ሲል በአምላካዊ ቃሉ ያዘዘውን መሠረት በማድረግና የቅዱሳን ሐዋርያትን ፈለግ በመከተል ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በርካታ ሰባክያንን እያስተማረች በየቦታው ስታሰማራ ኖራለች፤ ወደፊትም ይህንን ተልእኮዋን አጠናክራ ትቀጥላለች፡፡ ምክንያቱም ስብከተ ወንጌል ቃለ እግዚአብሔርን ለማስተማር ብቻ ሳይኾን የሰውን አእምሮ ለማልማት (መልካም አስተሳሰብን ለመገንባት) የሚያስችል ዋነኛው የቤተ ክርስቲያን መሣርያ ነውና፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሥራቿ የዅሉም አምላክ፣ የዅሉም ጌታ፣ የዅሉም መድኀኒት የኾነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነውና እንደ ጌታዋ ዘር፣ ጎሣ፣ ቀለም፣ ጾታ ሳትለይ በተዋሕዶ ሃይማኖት ጥላ ሥር የተሰባሰቡ ምእመናንን በአንድነት ተቀብላ ታስተናግዳቸዋለች፡፡ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መፋጠን በልዩ ልዩ የአገልግሎት ዘርፍ የሚሳተፉ ልጆቿም ይህንኑ ዓላማዋን ለማሳካት የመትጋት መንፈሳዊ ግዴታ አለባቸው፡፡ ‹‹ወንድሞች በኅብረት ቢቀመጡ እነሆ መልካም ነው፤ እነሆም ያማረ ነው፤›› (መዝ. ፻፴፪፥፩) ተብሎ በመጽሐፍ ቅዱስ እንደ ተጻፈው፣ በዓለማዊ ብሂልም ‹‹ከአንድ ብርቱ ሁለት መድኀኒቱ›› እንደሚባለው በኅብረት በመሰባሰብ የሚፈጸም መንፈሳዊ ተግባር ውጤታማነቱ የሠመረ ነው፡፡

በማኅበር ተሰባስበው መንፈሳዊ አገልግሎት ከሚሰጡ ማኅበራት መካከል አንዱ የኾነው፤ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልዩ ልዩ ክፍተት ለመሸፈን የሚያስችል መንፈሳዊ ዓላማ እና ርእይን ሰንቆ በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ የተመሠረተው ማኅበረ ቅዱሳንም ለሃያ አምስት ዓመታት ያህል ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በትጋት ሲያገለግል እስከ ዛሬ ድረስ ቆይቷል፡፡ ለወደፊቱም እግዚአብሔር እስከፈቀደለት ጊዜ ድረስ አገልግሎት መስጠቱን ይቀጥላል፡፡ በልዩ ልዩ መገናኛ መንገዶች እንደሚገለጸው ማኅበረ ቅዱሳን ከአመሠራረቱ ጀምሮ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልእኮዋን አስፋፍታ፣ መንፈሳዊ ዓላማዋን ከግብ አድርሳ፣ ከችግሮቿ ወጥታ ለሕዝቦቿ መንፈሳዊና ማኅበራዊ የሕይወት ለውጥ ቀዳሚ ሚናዋን እንድትወጣ ለመደገፍ የሚተጋ መንፈሳዊ ማኅበር ነው፡፡

ማኅበሩ በየግቢ ጉባኤያቱ ትምህርተ ሃይማኖትን ከሚያስተምራቸው ወንድሞችና እኅቶች በተጨማሪ ከአባቶችና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመመካከር በልዩ ልዩ የአገራችን ክፍሎች የሚገኙ ሰባክያነ ወንጌልን በየቋንቋቸው እያሠለጠነ፣ በአባቶች ቡራኬ እያስመረቀ ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት እንዲሠማሩ አድርጓል፡፡ በእነዚህ ሰባክያን አገልግሎትም ከሰማንያ አምስት ሺሕ ሰባት መቶ የሚበልጡ በልዩ ልዩ ጠረፋማ አካባቢዎች የሚኖሩ አዳዲስ አማንያን የሥላሴ ልጅነትን አግኝተዋል፡፡ በዚህ መልኩ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እያገለገለ የሚገኘው ማኅበረ ቅዱሳን በአጠቃላይ በልዩ ልዩ ቋንቋ በርካታ መንፈሳውያን ተግባራትን አከናውኗል፡፡ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ‹‹ይህን ሠርቻለሁ›› ብሎ መናገር ተገቢ ባይኾንም፣ ለቍጥጥር እና ለግምገማ ያመች ዘንድ ማኅበሩ በየጊዜው የአገልግሎት ሪፖርት ያቀርባል፡፡ በዚህ ጽሑፍም በአፋን ኦሮሞ የሚሰጠውን አገልግሎት በሚመለከት አጠር ያለ ግንዛቤ የሚያስጨብጥ መልእክት ይዘን ቀርበናል፡፡

የተወደዳችሁ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባቶች እና ምእመናን!

ማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎቱን ሲጀምር ከነበረበት የሰው ኃይል እና እጥረት አኳያ በአማርኛ ቋንቋ በመጽሔት፣ በጋዜጣ፣ በበራሪ ወረቀት፣ በመጻሕፍት፣ በካሴት፣ በምስል ወድምፅ የሚቻለውን ዅሉ መንፈሳዊ ተግባር ሲያከናውን ቆይቷል፡፡ አሁን አሁን ደግሞ የምእመናን ፍላጎት እየጨመረ፤ ማኅበሩም በሰው ኃይል እየተጠናከረ በመምጣቱ አገልግሎቱን ይበልጥ አሳድጎ በአፋን ኦሮሞ፣ በትግርኛ፣ በወላይትኛ፣ በእንግሊዝኛ፣ በመሳሰሉት የአገር ውስጥ እና የውጭ አገር ቋንቋዎች ወንጌልን ለማስተማር በመፋጠን ላይ ነው፡፡

ከዚህ ቀደም በአፋን ኦሮሞ ከተሠሩ ሥራዎች መካከል ጥቂቶቹን ለመጥቀስ ያህል፡-

  • በግእዝና አማርኛ ቋንቋዎች የታተሙ የትምህርተ ሃይማኖት እና የጸሎት መጻሕፍትን ወደ አፋን ኦሮሞ አስተርጕሟል፤ ከእነዚህ መካከል የዘወትር ጸሎት፣ ውዳሴ ማርያም፣ ውዳሴ አምላክ እና ሰይፈ ሥላሴ ተጠቃሾች ናቸው፡፡
  • ሌሎች አዳዲስ መጻሕፍትንም በቋንቋው አዘጋጅቶ አሠራጭቷል፡፡
  • በሦስት ወር አንድ ጊዜ ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች የምትዘጋጀው ጉባኤ ቃና መጽሔትን ወደ ቋንቋው አስተርጕሞ በየግቢ ጉባኤያቱ አሠራጭቷል፡፡
  • Dhangaa Lubbuu (ዳንጋ ሉቡ) የተሰኘችውን መጽሔት ለዅሉም ክርስቲያን በሚመጥን ዐምድ በየሦስት ወሩ በማዘጋጀት እያሠራጨ ይገኛል፡፡
  • በአፋን ኦሮሞ አራት የመዝሙር አልበሞችን አሠራጭቷል፤ ኦርቶዶክሳዊ የመዝሙር ጥራዝም አሳትሟል፡፡
  • ልዩ ልዩ የቪሲዲ ስብከቶችንና መዝሙሮችን አዘጋጅቶ ለምእመናን እንዲዳረሱ አድርጓል፡፡
  • በክልሉ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናትን አገልግሎትና ታሪክ የተመለከቱ ልዩ ልዩ ጥናታዊ ጽሑፎችን አዘጋጅቶ አሳትሟል፡፡
  • በአፋን ኦሮሞ ለሚያስተምሩ ሰባክያነ ወንጌል በዐሥራ ሦስት ዙር የክረምት ሥልጠና ሲሰጥ ቆይቷል፤ በዚህ ዓመትም ከዘጠና በላይ አገልጋዮችን ለማሠልጠን ዝግጅቱን አጠናቋል፡፡
  • ከአሁን በፊት በአፋን ኦሮሞ የሚተላለፍ ሳምንታዊ መንፈሳዊ የቴሌቭዥን መርሐ ግብር እያዘጋጀ ሲያቀርብ የቆየ ሲኾን፣ ለወደፊቱም ይህንኑ ሥራውን አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡
  • መካነ ድር ከማዘጋጀት ባሻገር ወቅታዊ ትምህርት የሚሰጥበት ወርኃዊ ጉባኤ በማካሔድም ሕዝበ ክርስቲያኑን በአፋን ኦሮሞ ወንጌልን በማስተማር ላይ ይገኛል፡፡
  • በአገራችን ግቢ ጉባኤያት ካሏቸው ዐርባ ሰባት ማእከላት በሠላሳ ስምንቱ የአፋን ኦሮሞ መርሐ ግብር እንዲኖርና ተማሪዎች በቋንቋቸው ኮርስ እንዲማሩ፣ የጽዋ እና ጸሎት መርሐ ግብራት እንዲያካሔዱ፣ መዝሙራትን እንዲያጠኑና እንዲያቀርቡ አድርጓል፤ በማድረግ ላይም ነው፡፡
  • በተጠኑ የክልሉ ቦታዎች አዳሪ የአብነት ትምህርት ቤቶችን በመመሥረት አፋን ኦሮሞ የሚችሉ ዲያቆናትና ካህናትን እንዲሁም ሰባክያነ ወንጌልን አስተምሮ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በማሠማራት ላይ ሲኾን ለዚሁም በምዕራብ ወለጋ የሚገኘውን የቂልጡ ካራ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ እና በጅማ ሀገረ ስብከት ሥር ያለውን የአበልቲ ኪዳነ ምሕረት ገዳማት የአብነት ትምህርት ቤቶችን እንደ ማስረጃነት መጥቀስ ይቻላል፡፡
  • በግቢ ጉባኤያት የምረቃ መጽሔት ላይ ልዩ ልዩ ትምህርታዊ ጽሑፎችና መልእክቶችን በአፋን ኦሮሞ እያቀረበ ነው፡፡
  • በክልሉ ያሉ ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች እንዲጠናከሩ ፕሮጀክቶችን ቀርፆ በመተግበር፣ መምህራንና ደቀ መዛሙርትን በመደጎም፣ ቋንቋውን የሚችሉ ዲያቆናትና ካህናት እንዲፈሩ በማደረግ በርካታ የክልሉ ምእመናን በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ፣ የተዘጉ አብያተ ክርስቲያናት ተከፍተው አገልግሎት እንዲሰጡ የበኩሉን አስተዋጽዖ አበርክቷል፤ የባሌ፣ የምሥራቅ ሐረርጌና የነገሌ ቦረና አህጉረ ስብከት አብነት ትምህርት ቤቶች ተጠቃሾች ናቸው፡፡
  • ከዚሁ ዅሉ ጋርም የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ሲያዘጋጅ ለኦሮምያ ክልል ቅድሚያ በመስጠት፣ የጉባኤው ተሳታፊዎችን በማስተባበር የገቢ እጥረት ላለባቸው የክልሉ አብያተ ክርስቲያናት በመቶ ሺሕ የሚቈጠር የገንዘብ ድጋፍ እንዲያገኙ አድርጓል፡፡ በመርሐ ግብሮቹ የሚቀርቡ ትምህርቶችንም በአፋን ኦሮሞ በማስተርጐም ለአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን አቅርቧል፡፡

ማኅበሩ ለወደፊት በአፋን ኦሮሞ ለመሥራት ካቀዳቸው ተግባራት መካከል ከፊሎቹ

  • መንፈሳዊ የቴሌቭዥን እና የሬድዮ መርሐ ግብር ማዘጋጀት፣
  • ወርኃዊ የሬድዮ መጽሔት ማዘጋጀት፣
  • ዕቅበተ እምነት ላይ ትኩረት ያደረጉ ልዩ ልዩ መጻሕፍትን ማሳተም፣
  • ልዩ ልዩ ቅዱሳት መጻፍትን ወደ አፋን ኦሮሞ ማስተርጐም፣
  • የሕፃናት መጻሕፍትንና መንፈሳዊ ፊልሞችን ማዘጋጀት፣
  • ወጣቶች ምእመናን የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ጠንቅቀው እንዲያውቁ የሚያግዙ ማስተማሪያ አፕሊኬሽኖችን ማዘጋጀት ማኅበሩ በዕቅድ የያዛቸው ተግባራት ናቸው፡፡ በተጨማሪም የሬድዮና ቴሌቭዥን መርሐ ግብሮችን መከታተል ለማይችሉ የገጠር ምእመናን የዘመኑን ቴክኖሎጂ በመጠቀም በሚኖሩበት ቦታ ኾነው ቃለ እግዚአብሔርን እንዲማሩ ለማድረግ የሚያስችል ዕቅድም አለው፡፡

የተወደዳችሁ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባቶች እና ምእመናን!

ቤተ ክርስቲያን የሰጠችውን ሓላፊነትና የአባቶችን አደራ ተቀብሎ ወንጌለ መንግሥትን በመላው ዓለም ለማዳረስ የሚተጋው ማኅበረ ቅዱሳን በቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር ሥር ያለ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተምህሮና መሠረተ እምነት የሚጠብቅና የሚያስጠብቅ፣ በቅዱስ ሲኖዶስ የጸደቀ ደንብ የተሰጠውና በደንቡ መሠረት ብቻ የሚመራ ማኅበር እንጂ ራሱን የቻለ የእምነት ተቋም አይደለም፡፡ አባላቱም ለአንድ መንፈሳዊ ዓላማ ከመላው ኢትዮጵያ የተሰባሰቡ የተዋሕዶ ልጆች እንጂ የአንድ አካባቢ ተወላጆችና አንድ ብቻ ቋንቋ ተናጋሪዎች አይደሉም፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ምእመናን በሚሰሙት ቋንቋ ዅሉ ቃለ እግዚአብሔርን ተምረው ለመንግሥተ ሰማይ ይበቁ ዘንድ የሚጠበቅበትን መንፈሳዊና አገራዊ ድርሻ በአግባቡ ለመወጣት የሚሠራ፤ በአጠቃላይ ለመንፈሳዊ ተልእኮ የሚፋጠን ማኅበር ነው፡፡

ማኅበሩ በግልጽና በይፋ ከሚፈጽመው መንፈሳዊ አገልግሎት ውጪ በስውር የሚሠራው አንዳችም የተለየ ተልእኮ የለውም፡፡ ምእመናን በሚሰሙት ቋንቋ ቃለ እግዚአብሔርን እንዳይማሩም እንቅፋት አይፈጥርም፡፡ እንደዚህ ዓይነት አሠራርም በፍጹም የለውም፡፡ ማኅበሩ የዅሉንም ሕዝበ ክርስቲያን ፍላጎት ሙሉ በሙሉ አሟልቻለሁ ባይልም ምእመናን በየቋንቋቸው ወንልን እንዳይማሩ አለማድረጉን፤ ለወደፊትም እንደዚህ ዓይነት ተልእኮ የሚፈጽም ማኅበር አለመኾኑን ቅዱስ ሲኖዶስ እና መላው ሕዝበ ክርስቲያን እንዲገነዘቡለት ያሳስባል፡፡ በመጨረሻም ማኅበረ ቅዱሳን በኦሮምያ ለሚገኙ ምእመናን ሰፊ አገልግሎት ለመስጠት ካለው ቁርጠኝነት የተነሣ የአፋን ኦሮሞ ሚዲያ ፕሮጀክት በሚል ስያሜ መርሐ ግብር አቋቁሞ፣ በጀት መድቦ በተጠናከረ መልኩ አገልግሎቱን በመፈጸም ላይ መኾኑን በዚህ አጋጣሚ እየገለጸ፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን አገልግሎት ከዚህ በበለጠ መልኩ እንዲቀላጠፍ ለማድረግ ይቻል ዘንድም መላው ሕዝበ ክርስቲያን ማኅበሩ የሚሰጠውን አገልግሎት ቀርባችሁ ደግፉ ሲል በእግዚአብሔር ስም መንፈሳዊ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን!

 ማኅበረ ቅዱሳን

ሥላሴ በአብርሃም ቤት

ሥላሴ በአብርሃም ቤት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሐምሌ ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ሐምሌ ፯ ቀን እግዚአብሔር አምላክ በአብርሃም ቤት የገባበትና ሣራ ይስሐቅን እንደምትወልድ የተናገረበት ዕለት ነው፡፡ ይህ የቅድስት ሥላሴ ክብረ በዓል በቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ በደማቅ ሥርዓት ይከበራል፡፡ ታሪኩም በአጭሩ እንዲህ ነው፤

አባታችን አብርሃም ከተመሳቀለ ጐዳና ላይ ድንኳን ሠርቶ መንገደኞችን ዅሉ በእንግድነት እየተቀበለ ሲያስተናግድ ይኖር ነበር፡፡ ጥንተ ጠላታችን ሰይጣን ለተንኮል አያርፍምና ይህንን መልካም ግብሩን ለማሰናክል አሰበ፡፡ አስቦም አልቀረ፤ የተጐዳ ሰው መስሎ ከጐዳና ቆሞ አብርሃም እንግዳ መቀበል እንደ ተወ፤ እርሱ ሊበላ ሊጠጣ ከቤቱ ቢሔድ ራሱን ፈንክቶ፣ ደሙን አፍሶ፣ አጥንቱን ከስክሶ፣ ልብሱን ገፎ እንደ መለሰው ወደ አብርሃም ቤት ለሚሔዱ ሰዎች ይናገር ጀመር፡፡ በዚህ የተነሣም እንግዳ ወደ አብርሃም ቤት አልመጣ አለ፡፡ በዚህ ጊዜ አብርሃምም ማዕደ እግዚአብሔርን ያለ ምስክር (ያለ እንግዳ) አልመገብም ብሎ ሦስት ቀን ሳይመገብ ጾሙን አደረ፡፡ በሦስተኛው ቀን ይህን ደግነቱን እግዚአብሔር ተመልክቶ በሦስት ሰዎች አምሳል አንድም በሥላሴው (በሦስትነቱ) ከአብርሃም ቤት ገብቷል (ቅዳሴ ማርያም አንድምታ ትርጓሜ፣ ፬፥፴፪)፡፡

በኦሪት ዘፍጥረት ፲፰፥፩-፲፱ ተጽፎ እንደምናገኘው በቀትር ጊዜ አብርሃም በድንኳኑ ደጃፍ ተቀምጦ ሳለ እግዚአብሔር በሦስት ሰዎች አምሳል በመምሬ አድባር ዛፍ ተገልጦለታል፡፡ አብርሃምም ሦስት ሰዎች ቆመው ባየ ጊዜ ሊቀበላቸው ከድንኳኑ ደጃፍ ተነሥቶ ወደ እነርሱ ሮጠ፡፡ ወደ ምድርም ሰገደና ‹‹አቤቱ በፊትህስ ሞገስ አግኝቼ እንደ ኾነ ባርያህን አትለፈኝ?›› ብሎ ተማጸነ፡፡ በመቀጠል አብርሃም ‹‹ጥቂት ውኃ ይምጣላችሁ፤ እግራችሁን ታጠቡ፤ ከዚህችም ዛፍ በታች ዕረፉ፡፡ ቍራሽ እንጀራም ላምጣላችሁ፤ ልባችሁንም ደግፉ፡፡ ከዚያም በኋላ ትሔዳላችሁ፡፡ ስለዚህ ወደ ባርያችሁ መጥታችኋልና›› ሲላቸው እነርሱም ‹‹እንዳልህ አድርግ›› ብለውታል፡፡

የኦሪት ዘፍጥረት አንድምታ ትርጓሜ እንደሚያስረዳው አብርሃም ሥላሴን ‹‹ጌቶቼ ከቤት ገብታችሁ ዕረፉ›› ሲላቸው ‹‹ደክሞናልና አዝለህ አስገባን›› አሉት፡፡ እርሱም እሺ ብሎ አንዱን አዝሎ ቢገባ ሁለቱ በግብር አምላካዊ (በአምላካዊ ጥበብ) ከቤቱ ገቡ፡፡ አብርሃምም ወደ ሣራ ዘንድ ፈጥኖ ሔደና ‹‹ሦስት መሥፈሪያ ዱቄት ፈጥነሽ አዘጋጂ፤ ለውሺውም፤ እንጎቻም አድርጊ›› አላት፤ እርሷም እንዳዘዛት አደረገች፡፡ አብርሃምም ወይፈን አርዶ አወራርዶ አዘገጅቶላቸው ተመግበዋል፡፡ ወይፈኑም ተነሥቶ ‹‹ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ፤ ለአብ ምስጋና ይገባል፤ ለወልድ ምስጋና ይገባል፤ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይገባል፤›› ብሎ እግዚአብሔርን አመስገኗል፡፡

ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር አብርሃምን ጠርቶ ‹‹ሚስትህ ሣራ ወዴት ናት?›› አለው፡፡ አብርሃምም ከድንኳኑ ውስጥ እንዳለች ነገረው፡፡ እግዚአብሔርም ‹‹የዛሬ ዓመት እንደ ዛሬው ጊዜ ወደ አንተ በእውነት እመለሳለሁ፤ ሚስትህ ሣራም ልጅን ታገኛለች›› ብሎ ለአብርሃም አበሠረው፡፡ ሣራ ይህንን ቃል በሰማች ጊዜ ባለቤቷም አርጅቶ፤ እርሷም የሴቶች ግዳጅ ትቷት ነበርና ‹‹‹ሲያረጁ አምባር ይዋጁ› እንዲሉ ‹‹እስከ ዛሬ ድረስ ቆንጆ ነኝን? ጌታዬ አብርሃምስ ገና ጐረምሳ ነውን?›› ብላ በማሰቧና መውለዷን በመጠራጠሯ ሳቀች፡፡ እግዚአብሔርም ምሥጢሩን በአጽንዖት ለማስረዳትና አስረግጦ ለመንገር አብርሃምን ‹‹ሣራ ለምን ትስቃለች? በውኑ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር አለን?›› አለው፡፡ ሣራም ስለፈራች ‹‹አልሳቅሁም›› አለች፡፡ እግዚአብሔርም መሳቋን እንዳወቀባት ከነገራት በኋላ በድጋሜ በዓመቱ ወደ አብርሃም ቤት እንደሚመጣና ሣራ ወንድ ልጅ (ይስሐቅን) እንደምትወልድ አብሥሯቸዋል፡፡

በዚህ ትምህርት ብዙ ምሥጢራት ይገኛሉ፤ ጥቂቶቹን በመጠኑ ለማስታወስ ያህል፦ ‹‹… ሦስት ሰዎች … ሊቀበላቸው … ወደ እነርሱ …›› የሚሉትና ሌሎችም በብዙ ቍጥር የተገለጹ ተመሳሳይ ሐረጋት የእግዚአብሔርን ሦስትነት፤ ‹‹… በፊትህስ ሞገስ አግኝቼ እንደ ኾነ ባሪያህን አትለፈኝ? …›› የሚለው ዐረፍተ ነገር ደግሞ አንድነቱን ያመለክታል፡፡ ሣራ ዳቦ ያዘጋጀችበት ሦስቱ መሥፈሪያ የሦስትነቱ፤ ዳቦው አንድ መኾኑ ደግሞ የአንድነቱ ምሳሌ ነው፡፡ ሥላሴ አብርሃም ያዘጋጀውን እንስሳ ተመገቡ ተብሎ መነገሩም በሰው አምሳል ስለ ተገለጡና ለአብርሃም የበሉ መስለው ስለ ታዩት ነው እንጂ ለሥላሴ መብል መጠጥ አይስማማቸውም (አይነገርላቸውም)፡፡ መምህራነ ቤተ ክርስቲያን እንዳስተማሩን ሥላሴ ምግብ በሉ (እግዚአብሔር ምግብ በላ) ማለት ቅቤ ከእሳት ገብቶ አልቀለጠም እንደ ማለት ነው፡፡ መብላት፣ መጠጣትን የመሰሉ የሥጋ ተግባራት የመለኮት ባሕርያት አይደሉምና፡፡ ከዚህ በተለየ ምሥጢር ሥላሴ ‹‹ሣራ ለምን ትስቃለች? በውኑ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር አለን?›› ብለው ከጠየቁበት ኃይለ ቃል መካከል ‹‹ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር አለን?›› የሚለውን እመቤታችንን በድንግልና ፀንሳ በድንግልና እንደምትወልድ ሲያበሥራት ‹‹ወንድ ሳላውቅ ይህ እንዴት ሊኾን ይችላል?›› (ሉቃ. ፩፥፴፯) ብላ በጠየቀችው ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ደግሞ መናገሩ የእግዚአብሔር ቃል በዘመን ብዛት የማይለወጥ ሕያውና እውነተኛ መኾኑን ያጠይቃል፡፡

እግዚአብሔር አብርሃምን ‹‹ሣራ ወዴት ናት?›› ሲል መጠየቁም ያለችበት ጠፍቶበት ሳይኾን የሚነግራት ታላቅ የምሥራች እንዳለ ለማጠየቅ ነው፡፡ ሰውን ያለበትን ጠይቆ፣ ጠርቶ፣ አቅርቦ አስደሳች ዜና መንገር የተለመደ ነውና፡፡ ይኸውም ‹‹አዳም ወዴት ነህ?›› ከሚለው ጥያቄ ጋር ተመሳሳይነት አለው (ዘፍ. ፫፥፱)፡፡ እግዚአብሔር አምላክ አባታችን አዳምን ‹‹ወዴት ነህ?›› ሲል የጠየቀው ያለበትን ዐላውቅ ብሎ ሳይኾን ቃል በቃል ሊያነጋግረው፣ ‹‹ከልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ›› የሚለውን የድኅነት ቃል ኪዳን ሊሰጠው ፈቅዶ ነበር፡፡ እንደ አዳም ዅሉ ለሣራም ለጊዜው ይስሐቅን እንደምትወልድ፤ ለፍጻሜው ደግሞ ከአብርሃም ዘር ከምትኾን ቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር ሥጋ ለብሶ እንደሚገለጥና ዓለሙን እንደሚያድነው ለመንገር አብርሃምን ‹‹ሚስትህ ሣራ ወዴት ናት?›› ሲል ጠይቆታል፡፡ ከዚያም የይስሐቅን መወለድ አብሥሯቸዋል፡፡ ይኸውም አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዓመት ሲፈጸም እግዚአብሔር ከአብርሃም የልጅ ልጅ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እንደ ተወለደ (በአካለ ሥጋ ወደ ምድር እንደ መጣ)፤ በዚህ ጊዜም በሣራ የተመሰለች ወንጌል በይስሐቅ የሚመሰሉ ምእመናንን እንዳስገኘች ማለትም ሐዲስ ኪዳን ተመሥርታ ብዙ ክርስቲያኖችን እንዳፈራች የሚያመለክት ምሥጢር አለው፡፡

የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት እንደ ተረጐሙልን የአብርሃም ድንኳን የእመቤታችን ምሳሌ ነው፤ ‹‹ተናግዶቱ (ተአንግዶቱ) ለአብርሃም፤ ለአብርሃም የሃይማኖቱን (የእንግዳ ተቀባይነቱን) ዋጋ የምታሰጪው አንቺ ነሽ፤›› እንዳሉ አባ ሕርያቆስ፡፡ በአብርሃም ድንኳን አላፊ አግዳሚው ይመግብበት፣ ያርፍበት እንደ ነበረ ዅሉ በእመቤታችንም አማላጅነትም መንገደኞች ማረፍያ፤ እንግዶች መጠለያ፤ ስደተኞች ተስፋ ያገኛሉና፡፡ ከዅሉም በላይ የነፈስ የሥጋ መድኀኒት፤ የዘለዓለም ማረፍያ፤ እውነተኛ መብልና መጠጥ የኾነውን ኢየሱስ ክርስቶስን የወለደች እርሷ ናትና በአብርሃም ድንኳን ትመሰላለች፡፡ ቀትር በኾነ ጊዜ ማለትም በስድስት ሰዓት አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ወደ አብርሃም ድንኳን እንደ ገቡ ዅሉ፣ አምስት ሺሕ አምስት መቶው ዓመት ተፈጽሞ በስድስተኛው ሺሕ ዓመት እግዚአብሔር አብ ለአጽንዖ፤ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ለአንጽሖ፤ እግዚአብሔር ወልድ በተለየ አካሉ ሥጋን ለመልበስ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አድረዋልና እመቤታችን በአብርሃም ድንኳን ትመሰላለች፡፡ ‹‹በስድስተኛው ወር ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ወደ እመቤታችን ተላከ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሉቃ. ፩፥፳፮)፡፡ በዚህ ቃለ ወንጌል ‹‹ስድስተኛው ወር›› የሚለው ሐረግ አምስት ሺሕ አምስት መቶው ዘመን ተፈጽሞ በስድስተኛው ሺሕ ዘመን ቅዱስ ገብርኤል ወደ እመቤታችን ለብሥራት መላኩን ያመለክታል፡፡

በአብርሃም ቤት (በድንኳኑ) ውስጥ ወይፈኑ ‹‹ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ›› ብሎ እንዳመሰገነ ዅሉ እግዚአብሔር አምላክ ከእመቤታችን በተወለደ ጊዜም ቅዱሳን መላእክትና የሰው ልጆች ‹‹ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ሥምረቱ ለሰብእ፤ ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይኹን፤ ሰላምም በምድር፤ ለሰውም በጎ ፈቃድ›› እያሉ እግዚአብሔርን በአንድነት አመስግነዋል (ሉቃ. ፪፥፲፬)፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ለአብርሃም የይስሐቅን መወለድ እና በሥጋ ማርያም መገለጡን ከነገረው በኋላ ተመልሶ ሔዷል፡፡ ‹‹ሔዷል›› ስንልም ሥላሴ ከአብርሃም ቤት በሰው አምሳል ሲወጡ መታየታቸውን ለማመልከት እንጂ እግዚአብሔር መሔድ መምጣት የሚነገርለት ኾኖ አይደለም፡፡ እርሱ በዓለሙ ዅሉ ሰፍኖ የሚኖር አምላክ ነውና፡፡ ነገር ግን በልዩ ልዩ ምሳሌ እየተገለጠ ጸጋውን፣ በረከቱን ማሳደሩን ለመግለጽ መጣ፤ ሔደ፤ ወረደ፤ ዐረገ እየተባለ ይነገርለታል፡፡

ትምህርታችንን ለማጠቃለል ያህል ሐምሌ ፯ ቀን እግዚአብሔር በአብርሃም ቤት ተገኝቶ የይስሐቅን መወለድና የእግዚአብሔርን ሰው መኾን የተናገረበት ዕለት ከመኾኑ ሌላ የአብርሃምን ዘሩን እንደሚያበዛለትና አሕዛብ ዅሉ በእርሱ እንደሚከብሩ ማለትም ከአብርሃም ዘር በተገኘው በኢየሱስ ክርስቶስ አሕዛብ እንደሚቀደሱ፤ ይህንን ምሥጢርም እግዚአብሔር ከወዳጁ ከአብርሃም እንደማይሠውር ቃል ኪዳን የገባበት ቀን ነው፡፡ በተጨማሪም እግዚአብሔር በኀጢአታቸው ብዛት የተነሣ ሰዶምንና ገሞራን ያጠፋው፤ አብርሃምም በአማላጅነት በእግዚአብሔር ፊት ቆሞ የተማጸነው በዚሁ ዕለት ነው፡፡

ቅዱሳን በእግዚአብሔር ፊት ቆመው ዘወትር ስለ ሰው ልጅ ድኅነት እንደሚጸልዩ እና እንደሚያማልዱ፤ እንደ አብርሃም ልቡናቸው ቅን በኾነና በለጋሾች ማለትም ምጽዋትንና እንግዳ መቀበልን የዘወትር ተግባራቸው አድርገው በሚኖሩ ሰዎች ቤት እግዚአብሔር እንደሚገኝ፤ እግዚአብሔር በረድኤት ወደ ሰው ቤት ሲገባም የተዘጋ ማኅፀን እንደሚከፍትና ቤቱን በበረከት እንደሚሞላ፤ እንደዚሁም የተሠወረ ምሥጢር እንደሚገልጽ ከዚህ ታሪክ እንረዳለን፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም እግዚአብሔር አምላክ በአንድነቱም በሦስትነቱም እየታየ አምላክነቱን ለዘመናት እንደሚገልጥና የቸርነቱን ሥራ እንደሚሠራም ከታሪኩ እንማራለን፡፡

በአጠቃላይ ይህ የእግዚአብሔር በአብርሃም ቤት የመገለጥ ትምህርት በአንድ ወቅት ብቻ የተፈጸመና ‹‹ነበር›› እየተባለ የሚነገር ያለፈ ታሪክ ሳይኾን፣ ለዘለዓለሙ ሲነገርና ሲፈጸም የሚኖር ሕያው ቃል ነው፡፡ ይህንም እግዚአብሔር ለቅዱሳኑ በልዩ ልዩ መንገድ እየተገለጠ ለዘመናት በሚያደርገው ድንቅ ሥራና ተአምር መገንዘብ እንችላለን፡፡ ዛሬም ሀብት ንብረት ያለን ምእመናን በትሩፋት ሥራ በመሠማራት ማለትም እንግዶችን በመቀበል፣ ለተራቡ በማብላት፣ በመመጽወት እና በመሳሰለው ተግባር ከኖርን፤ በቂ ንብረት የሌለን ደግሞ ልቡናችንን ንጹሕ ከማድረግና ከኀጢአት ከመለየት በተጨማሪ ለተቸገሩ በመራራት፣ በደግነት፣ በቀና አስተሳሰብ ከተጓዝን እግዚአብሔር በሕይወታችን ውስጥ ያድራል፡፡ አድሮም ይባርከናል፤ ይቀድሰናል፡፡ እርሱ ያደረበት ሰውነት ይባረካል፤ ይቀደሳልና፡፡ ደግሞም ልጅ ለሌለን ልጅ፤ ዘመድ ላጣን ዘመድ በመስጠት ዘራችንንም ይባርክልናል፡፡ በጥቅሉ የልባችንን መሻት ዐውቆ የምንሻውን መልካም ነገር ዅሉ ይፈጽምልናል፡፡ ይህ ዅሉ የእግዚአብሔር ጸጋ ይበዛልን ዘንድ እኛም በርትዕት የተዋሕዶ ሃይማኖት እንጽና፤ በክርስቲያናዊ ምግባርም እንትጋ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የብርሃናተ ዓለም ጴጥሮስ እና ጳውሎስ ዕረፍት

ቅዱሳን ጴጥሮስ እና ጳውሎስ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሐምሌ ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በየዓመቱ ሐምሌ ፭ ቀን በአንድ በኩል የጾመ ሐዋርያት ፋሲካ የሚከበርበት ዕለት ሲኾን፣ በሌላ በኩል ደግሞ የብርሃናተ ዓለም ቅዱሳን ጴጥሮስ እና ጳውሎስ በዓለ ዕረፍትም በዚሁ ዕለት ይዘከራል፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን የእነዚህን ቅዱሳን ታሪክ በቅደም ተከተል በአጭሩ ይዘንላችሁ ቀርበናል፤

ቅዱስ ጴጥሮስ

ቅዱስ ጴጥሮስ በአባቱ የሮቤል፣ በእናቱ የስምዖን ነገድ ሲኾን፣ የተወለደውም በገሊላ አውራጃ በቤተ ሳይዳ ነው፡፡ ወላጆቹ ያወጡለት ስም ‹ስምዖን› ነበር፡፡ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹ጴጥሮስ› ብሎ ጠርቶታል፡፡ ትርጕሙም በግሪክ ቋንቋ ዓለት (መሠረት) ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ የሚተዳደረው በዓሣ አጥማጅነት የነበረ ሲኾን፣ ሰዎችን በወንጌል መረብ እያጠመደ ወደ ክርስትና ሕይወት ይመልስ ዘንድ ጌታችን ለሐዋርያነት ጠርቶታል (ሉቃ. ፭፥፲፤ ማር. ፩፥፲፮)፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ በመንፈሳዊ ቅንዓቱና ለጌታችን በነበረው ፍቅር የሐዋርያት አለቃ ኾኖ ተሹሟል፡፡ ለአገልግሎት ከተጠራበት ጊዜ ጀምሮም በእስያ፣ በሮም፣ በሰማርያ፣ በልዳ፣ በኢዮጴ፣ በአንጾኪያ፣ በገላትያና በሌሎችም አገሮች እየተዘዋወረ ወንጌልን ሰብኳል፡፡ በስብከቱ ምክንያትም ልዩ ልዩ መከራን ተቀብሏል፡፡ በክርስቶስ ኀይል አጋዥነት ብዙ ድንቆችንና ተአምራትን አድርጓል፡፡ ከተሰጠው ጸጋ ብዛት የተነሣ በጥላው ሕሙማን ይፈወሱ ነበር (ሐዋ. ፭፥፲፭)፡፡ ሐዋርያው በቃል ካስተማረው ትምህርት በተጨማሪ በመጽሐፍ ቅዱስ በስሙ የተመዘገቡ ሁለት መልእክታትን ጽፏል (፩ኛ እና ፪ኛ ጴጥሮስ)፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ ቁልቁል ተሰቅሎ በሰማዕትነት ሲያርፍ

የቅዱስ ጴጥሮስ ምድራዊ የአገልግሎት ዘመኑ ሊፈጸም ሲቃረብም እንዲህ ኾነ፤ በዘመኑ የክርስቲያኖች ጠላት የነበረው የሮም ንጉሥ ወደ አካይያ ዘምቶ ድል አድርጎ በደስታ ወደ ሮሜ ሲመለስ መኳንንቱን ለማስደሰት፤ ጣዖታቱንም ለማክበር ሲል በቅዱስ ጴጥሮስና በሌሎችም ክርስቲያኖች ላይ የሞት ፍርድ ዐወጀ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም በሮም ሲያስተምር ቆይቶ የሮም መኳንንት እንዳይገድሉት ትጥቁን ለውጦ ከሮም ሲወጣ ጌታችን መስቀል ተሸክሞ ተገለጸለት፡፡

በዚህ ጊዜ ‹‹አቤቱ ጌታ ሆይ ወዴት ትሔዳለህ?›› ሲል ቢጠይቀው ጌታችንም ‹‹ልሰቀል ወደ ሮም እሔዳለሁ›› አለው፡፡ ‹‹ዳግመኛ ትሰቀላለህን?›› ባለው ጊዜም ‹‹አንተ ስትፈራ ጊዜ ነው እንጂ›› ሲል መለሰለት፡፡ ያን ጊዜም ‹‹ጐልማሳ ሳለህ ወገብህን ታጥቀህ ወደ ወደድኸው ትሔድ ነበር፡፡ ስትሸመግል ግን እጅህን ታነሣና ሌላ ሰው ያስታጥቅሃል፤ ወደማትወደውም ይወስድሃል፤›› (ዮሐ. ፳፩፥፲፰) በማለት ጌታችን የነገረው ቃል አሟሟቱን የሚያመለክት መኾኑን አስታውሶ ወደ ሮም ተመልሶ ስብከቱን ቀጠለ፡፡

በሮማውያን ሕግ ቅጣት የተፈረደበት ወንጀለኛ የሮም አገር ተወላጅ ከኾነ የወንጀሉ ክብደትና ቅለት እየታየ ግርፋት ወይም ሞት ይፈረድበታል እንጂ በአንድ ወንጀል ሁለት ቅጣት አይቀጣም ነበር፡፡ ወንጀለኛው የውጪ አገር ዜጋ (ከሮም ውጪ) ከኾነ ግን ለምሳሌ ቅጣቱ ግርፋት ከኾነ ከተገረፈ በኋላ እስራት ይጨመርበታል፤ ቅጣቱ ሞት ከኾነም ከገረፉት በኋላ በመስቀል ወይም በሌላ መሣርያ ይገድሉት ነበር፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ዜግነቱ ሮማዊ አልነበረምና በግርፋትም፣ በእስራትም በሞትም እንዲቀጣ ተፈረደበት፡፡

እንደ ሥርዓታቸውም ቅዱስ ጴጥሮስን ከገረፉት በኋላ ሊሰቅሉት ሲሉ ወታደሮቹን ‹‹እንደ ክብር ንጉሥ እንደ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ አቁማችሁ ሳይኾን፣ ዘቅዝቃችሁ ስቀሉኝ›› አላቸው፡፡ እነርሱም እንዳላቸው አድርገው ሐምሌ ፭ ቀን ዘቅዝቀው ሰቅለውታል፡፡ በመስቀል ላይ ሳለም ተከታዮቹን በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ ካዘዛቸው በኋላ ነፍሱን ለእግዚአብሔር ሰጠ፡፡ ሥጋውንም መርቄሎስ የሚባለው ደቀ መዝሙሩ ሽቱ ቀብቶ፣ በነጭ ሐር ገንዞ ዛሬ ቫቲካን በምትባለዋ ስፍራ በክብር ቀብሮታል፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ

ቅዱስ ጳውሎስ ለአገልግሎት ከመጠራቱ በፊት ‹ሳውል› ይባል ነበር፡፡ ከኦሪቱ ምሁር ከገማልያል ሕገ ኦሪትንና መጻሕፍተ ነቢያትን ተምሯል፡፡ ለሕገ ኦሪት ቀናኢ ከመኾኑ የተነሣም የክርስቶስ ተከታዮችን ዅሉ ያሳድድ ነበር፡፡ ቅዱስ እስጢፋኖስ በድንጋይ ተደብድቦ በሰማዕትነት በሞተ ጊዜ ቅዱስ ጳውሎስ የገዳዮቹ ልብስ ጠባቂ ነበር (ሐዋ. ፯፥፶፰፤ ፳፪፥፳)፡፡ ክርስቲያኖችን ለማሳደድ ወደ ደማስቆ ሲሔድ ከመንገድ ላይ ለሐዋርያነት ተጠርቷል (ሐዋ. ፱፥፩-፴፩፤ ፳፪፥፩-፳፩)፡፡

ለሐዋርያነት ከተጠራበት ጊዜ ጀምሮም በመላው ዓለም እየተዘዋወረ ወንጌልን በመስበክ ብዙዎችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አሳምኗል፡፡ ሲሰብክም ጣዖት አምላኪ፣ ሕመምተኛ፣ ችግረኛ፣ አረማዊና አይሁዳዊ እየመሰለ ብዙዎችን አስተምሮ ለእግዚአብሔር መንግሥት አዘጋጅቷል (፩ኛ ቆሮ. ፱፥፲፱-፳፫)፡፡ ዐረብ፣ አንጾኪያ፣ እልዋሪቆን፣ ሊቃኦንያ፣ ሦርያ፣ ግሪክና ልስጥራን ካስተማረባቸው አገሮች ጥቂቶቹ ናቸው፡፡

ወንጌልን በመስበኩ ምክንያትም ከአይሁድና ከአረማውያን ዘንድ ብዙ መከራና ስቃይ ደርሶበታል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ከእግዚአብሔር በተሰጠው ጸጋ ብዙ ድንቆችንና ተአምራትን አድርጓል፡፡ በልብሱ ቅዳጅም ሕሙማን ይፈወሱ ነበር (ሐዋ. ፲፱፥፲፩)፡፡ ሐዋርያው በቃል ካስተማረው ሌላ በመጽሐፍ ቅዱስ በስሙ የተመዘገቡ ፲፬ መልእክታት አሉት፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ በሰይፍ ተቈርጦ በሰማዕትነት ሲያርፍ

አገልግሎቱን ሊፈጽም ሲልም የሮም ንጉሥ ኔሮን ቄሣር የክርስቲያኖች ቍጥር እየጨመረ የመጣው በቅዱስ ጳውሎስ ትምህርት በመማረካቸው ምክንያት መኾኑን ተረድቶ፤ ይልቁንም የቤተ መንግሥቱ ሰዎች ሳይቀር በቅዱስ ጳውሎስ በመማረካቸው ተቈጥቶ ቅዱስ ጳውሎስን ወደ ፍርድ ሸንጎው አስቀረበው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም በቀኝ እጁ ከሰንሰለቱ ጋር መስቀሉን ይዞ ንጉሡንና ወታደሮችን ሳይፈራ የኢየሱስ ክርስቶስን የእግዚአብሔር ልጅነትና አምላካዊ ሥልጣን ይመሰክር ነበር፡፡

ንጉሡም በቍጣ ይሙት በቃ ፈረደበት፡፡ ከላይ እንደ ተገለጸው ሮማውያን የሞት ፍርድ ሲፈርዱ የሚቀጣው ሰው የሌላ አገር ዜጋ ከኾነ ከፍርዱ ውጪ ተጨማሪ ቅጣት ይቀጡትና ይገድሉት ነበር፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ግን የሮም ዜግነት ስለ ነበረው ሳይገርፉ በአንድ ቅጣት ብቻ በሰይፍ እንዲገደል ወስነውበታል፡፡ ወደሚገደልበት ስፍራ ሲወስዱትም በንግግሩና በአስተያየቱ ዅሉ ምንም ፍርኀት አይታይበትም ነበር፡፡ እንዳውም በጦርነት ድል አድርጎና ማርኮ እንደ ተመለሰ ወታደር ይደሰት ነበር እንጂ፡፡ ለሚገድሉትም ይቅርታን ይለምን ነበር፡፡

በገዳዮቹና በተከታዮቹ ፊትም የክርስትና ሽልማቱ የእግዚአብሔር መንግሥት መኾኑን የሚያስገነዝብ ቃል እያስተማረ እግዚአብሔር የሚሰጠውን የጽድቅ አክሊል ለመቀበል ይቻኮል ነበር (፪ኛ ቆሮ. ፬፥፮-፲፰)፡፡ ወታደሮች ሊገድሉት ሲወስዱትም ከንጉሥ ኔሮን ወገን የኾነችውን የአንዲት ብላቴና መጐናጸፊያ ‹‹ዛሬ እመልስልሻለሁ›› ብሎ ከተቀበላት በኋላ ‹‹መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ፤ ሩጫዬን ጨርሻለሁ፡፡ ሃይማኖቴን ጠብቄአለሁ፤ ወደፊትም የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል፤›› በማለት ራሱ በመልእክቱ እንደ ተናገረው (፪ኛ ጢሞ. ፬፥፯-፰)፣ ፊቱን በብላቴናዋ መጐናጸፊያ ተሸፍኖ አንገቱን በሰይፍ ተቀልቶ አገልግሎቱን በሰማዕትነት ፈጽሟል፡፡

ደቀ መዛሙርቱም ራሱን ከአንገቱ ጋር ቢያደርጉት እንደ ቀድሞው ደኅና ኾኖላቸው በክብር ገንዘው ቀብረውታል፡፡ ሰያፊው ቅዱስ ጳውሎስን እንደ ገደለው ለመናገር ወደ ንጉሡ ሲመለስም ያቺ መጐናጸፊያዋን የሰጠችው ብላቴና ‹‹ጳውሎስ ወዴት አለ?›› አለችው፡፡ እርሱም ‹‹ራሱን ተቈርጦ በመጐናጸፊያሽ ተሸፍኖ ወድቋል›› ሲላት ‹‹ዋሽተሃል፤ እነሆ ጴጥሮስና ጳውሎስ በእኔ በኩል አልፈው ሔዱ፡፡ እነርሱም የመንግሥት ልብስ ለብሰዋል፡፡ በራሳቸውም በዕንቍ ያጌጡ አክሊላትን አድርገዋል፡፡ መጐናጸፊያዬንም ሰጡኝ፡፡ ይህችውም እነኋት፤ ተመልከታት›› ብላ ሰጠቸው፡፡ ከእርሱ ጋር ለነበሩትም አሳየቻቸው፡፡ አይተውም አደነቁ፤ ስለዚህም በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ፡፡

ቅዱሳን ጴጥሮስ እና ጳውሎስ በስብከተ ወንጌል አገልግሎታቸው ጨለማውን ዓለም በማድመቃቸው ‹ብርሃናተ ዓለም› ተብለው ይጠራሉ፡፡ የቅዱሳኑ አገልግሎት፣ ገድላቸው እና ተአምራቸው በመጽሐፈ ስንክሳር፣ በዜና ሐዋርያት እና በገድለ ሐዋርያት በሰፊው ተጽፎ ይገኛል፡፡ እኛም በዓለ ዕረፍታቸውን ለማስታወስ ያህል ታሪካቸውን በአጭሩ አቀረብን፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት ያቆዩልንን የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ጠብቀን፣ በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተን እንድንኖር፤ በመጨረሻም የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ እንድንበቃ የቅዱሳኑ ጸሎት ይርዳን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡-

  • መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሐምሌ ፭ ቀን፤
  • ዜና ሐዋርያት፤
  • ገድለ ሐዋርያት፡፡

የአዳማ ማእከል በአፋን ኦሮሞ ሥልጠና እየሰጠ ነው

በዝግጅት ክፍሉ

ሐምሌ ፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም  

በማኅበረ ቅዱሳን የአዳማ ማእከል ከምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ልዩ ልዩ ወረዳዎች ለተውጣጡ ሠላሳ ስድስት ሰባክያነ ወንጌል በአፋን ኦሮሞ የስብከተ ወንጌል እና የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና በአዳማ ከተማ እየሰጠ ነው፡፡

ሠልጣኞቹ በሀገረ ስብከቱ፣ በወረዳ ቤተ ክህነቶቹና በአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናቱ ፈቃድ የተመረጡ፣ በክርስቲያናዊ ምግባራቸው የተመሰከረላቸው የቤተ ክርስቲያን ልጆች እንደ ኾኑ፤ የቤተ ክርስቲያን አባልነት፣ ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባርን መላበስ፣ በሰንበት ት/ቤቶች ተሳትፎ ማድረግ፣ ቢቻል መዓርገ ክህነት መያዝ በተጨማሪም አማርኛ ቋንቋ እና አፋን ኦሮሞ መናገር መቻል በምልመላ መሥፈርቱ እንደ ተካተቱ የአዳማ ማእከል ለዝግጅት ክፍላችን አስታውቋል፡፡ ከሠላሳ ስድስቱ ሠልጣኞቹ መካከል አንዱ ቄስ፤ ሰባቱ ዲያቆናት መኾናቸውንም ለመረዳት ችለናል፡፡

በአቀባበል መርሐ ግብሩ የተገኙ እንግዶች እና ሠልጣኞች በከፊል

እንደ ማእከሉ ዘገባ ሥልጠናው የሚሰጠው ለዐሥራ አምስት ቀናት ቀንም ሌሊትም ሲኾን፣ መሠረተ እምነት፣ ነገረ ቅዱሳን፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ የስብከት ዘዴ፣ ኦርቶዶክሳዊ መዝሙር፣ ወቅታዊ ጉዳዮች፣ የጊዜ አጠቃቀም፣ መንፈሳዊ አገልግሎት፣ መሪነትና ውሳኔ አሰጣጥ እንደዚሁም ምክረ አበው ለሠልጣኞቹ የሚሰጡ የትምህርት ክፍሎች፤ አሠልጣኞች ደግሞ በልዩ ልዩ የአገልግሎት ዘርፍ የሚገኙ የቤተ ክርስቲያን መምህራን  ናቸው፡፡

መጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ ቸርነት

ለሠልጣኞቹ ሰኔ ፳፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም የአቀባበል ሥርዓት በተደረገላቸው ጊዜ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ መጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ ቸርነት ተገኝተው ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል፡፡

በትምህርታቸውም መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት ያደላቸውን በልዩ ልዩ ቋንቋ የመናገር ጸጋ ዋቢ በማድረግ ማእከሉ በአፋን ኦሮሞ የስብከተ ወንጌል ሥልጠና መስጠቱ በየገጠሩ በቋንቋ ችግር ምክንያት ወንጌል ባልተዳረሰባቸው አካባቢዎች ሰፊ አገልግሎት ለመስጠት ከፍተኛ አስተዋጽዖ እንዳለው አስረድተዋል፡፡

ሀገረ ስብከቱ ሊደርስ ያልቻለባቸውን የአገልግሎት ክፍሎች በማሟላት የአዳማ ማእከል ለሚሰጠው ዘርፈ ብዙ ተልእኮም ማኅበረ ቅዱሳንን አመስግነዋል፡፡

ሀገረ ስብከታቸው ለወደፊት በአፋን ኦሮሞ የስብከተ ወንጌል ሥልጠና ለመስጠት ማቀዱን የገለጹት ሥራ አስኪያጁ የማእከሉን አገልግሎት እንደሚደግፉም ቃል ገብተዋል፡፡

በትምህርታቸው ማጠቃለያም ‹‹የሚጠብቃችሁ ሕዝብ አለ፡፡ ሥልጠናውን ፈጽማችሁ ድረሱላቸው፡፡ ጕዟችሁ የወንጌል ጉዞ ነው፡፡ እንደ ሐዋርያት ለማታውቁት ሕዝብ ሳይኾን ለወገኖቻችሁ ወንጌልን የመስበክ አደራ አለባችሁ›› በማለት ሠልጣኞቹ የሚጠበቅባቸውን ተልእኮ በትጋት እንዲወጡ መክረዋል፡፡

ሊቀ ካህናት ነጋሽ ሀብተ ወልድ

የሀገረ ስብከቱ ሰበካ ጉባኤ ማደራጃ ክፍል ሓላፊ ሊቀ ካህናት ነጋሽ ሀብተ ወልድ በበኩላቸው ክርስትና የዅሉም ሕዝብ እንጂ የተወሰኑ ሰዎች፤ ቋንቋም መግባብያ እንጂ መለያያ እንዳልኾነ ጠቅሰው ወንጌልን በየቋንቋው ለማዳረስ ማእከሉ የሚያደርገውን ጥረት አጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበዋል፡፡

ለሠልጣኞቹም ‹‹ለዚህ ዕድል በመመረጣችሁ እንኳን ደስ ያላችሁ! ቃለ ወንጌሉን ያልተማሩ፣ በነጣቂዎች የተወሰዱ በየገጠሩ የሚኖሩ ወገኖቻችሁን ታገለግሉ ዘንድ ተመርጣችኋልና ለእነዚህ ወገኖች ልትደርሱላቸው ይገባል›› በማለት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በዕለቱ ከተገኙ በጎ አድራጊ ምእመናን መካከል አቶ ለማ ተፈሪ፣ አቶ ነገሠ ይልማ፣ እና አቶ ተስፋዬ መንገሻ የተባሉ የከተማው ነዋሪዎች ይህን ሥልጠና በመስጠቱ ማእከሉን አድንቀው በአፋን ኦሮሞ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት መሰጠቱ በየቋንቋው ወንጌልን በማስተማር ያመኑትን ለማጽናት፣ በመናፍቃን የተወሰዱትን ለመመለስ እና አዳዲስ አማኞችን ወደ ቤተ ክርስቲያን ለማምጣት የሚኖረውን ጠቀሜታ አብራርተዋል፡፡

የአዳማ ማእከል ሰብሳቢ መምህር ጌትነት ዐሥራት ደግሞ ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያን ተልእኮ የኾነውን የስብከተ ወንጌል አገልግሎት የማሳካት ሓላፊነት እንዳለበት አስታውሰው በመናፍቃን ከሚፈተኑ አካባቢዎች መካከል ኦሮምያ ክልል አንዱ በመኾኑ ምእመናንን በሃይማኖታቸው ለማጽናትና ከነጣቂዎች ለመጠበቅ፤ ያላመኑትንም ለማሳመን ይቻል ዘንድ ማእከሉ በአፋን ኦሮሞ የስብከተ ወንጌል እና የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና ለመስጠት መነሣሣቱን አስታውቀዋል፡፡

መምህር ጌትነት ዐሥራት

በመጨረሻም ለሥልጠናው መሳካት እገዛ ያደረገው የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከትን፤ ለሕክምና፣ ለምግብ፣ ለመጻሕፍትና ለትምህርት መሣርያዎች የሚያስፈልገውን ወጪ በማገዝ ሥልጠናውን የደገፉ በጎ አድራጊ ምእመናንን ሰብሳቢው በማኅበረ ቅዱሳን ስም አመስግነዋል፡፡

ከማእከሉ የደረሰን መረጃ እንደሚያመለክተው የአዳማ ማእከል በአፋን ኦሮሞ የስብከተ ወንጌል ሥልጠና ሲሰጥ አሁን ሁለተኛው ነው፡፡

በመጀመርያው ዙር የሠለጠኑ ሃያ ዘጠኝ ሰባክያነ ወንጌል በክልሉ ገጠራማ ሥፍራዎች ለሚኖሩ ምእመናን ትምህርተ ሃይማኖትን ከማዳረሳቸው ባሻገር ሞጆ አካባቢ አምስት አዳዲስ አማኞችን በማስተማር የሥላሴ ልጅነትን እንዲያገኙ አድርገዋል፡፡

የሁለተኛው ዙር ሠልጣኞችም ተመርቀው በየቦታው ሲሰማሩ ከዚህ የበለጠ የአገልግሎት ፍሬ ያስመዘግባሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ሠልጣኞቹም ሐምሌ ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ይመረቃሉ፡፡

ከዚህም ሌላ በአዳማ ማእከል የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል አስተባባሪነት በዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም እና የካህናት ማሠልጠኛ ተቋም ለሚገኙ መነኮሳትና አብነት ተማሪዎች ሰኔ ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በነጻ የሕክምና አገልግሎት መሰጠቱን፣ የመድኃኒት ድጋፍም መደረጉን ማእከሉ ያደረሰን ዘገባ ያመላክታል፡፡

ሐኪሞቹ የሕክምና አገልግሎት ሲሰጡ (በከፊል)

ከማእከሉ አባላት እና ከአዳማ ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ ግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የተውጣጡ ሠላሳ አራት ሜዲካል ዶክተሮች በተሳተፉበት በዚህ አገልግሎት ለዐሥራ ስድስት አባቶች መነኮሳት፤ ለስድስት እናቶች መነኮሳይያት እና ለሰባ አምስት አብነት ተማሪዎች የሕክምና ርዳታ፤ የላቦራቶሪ ምርመራ እና የመድኃኒት ድጋፍ ተደርጓል፡፡ በተጨማሪም የግል እና የአካባቢ ጤና አጠባበቅ ትምህርት በጤና ባለሙያዎች ተሰጥቷል፡፡

በመርሐ ግብሩ ማጠቃለያም የሕክምና ባለሙያዎችን በማስተባበር ማእከሉ ላደረገላቸው ክብካቤና ድጋፍ የሕክምና አገልግሎት የተሰጣቸው የገዳሙ አባቶች እና እናቶች ማኅበረ ቅዱሳንን በእግዚአብሔር ስም አመስግነዋል፡፡

ቅዱስ ታዴዎስ ሐዋርያ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሐምሌ ቀን ፳፻፱ .

ከ፲፪ቱ ሐዋርያት አንዱ የኾው ቅዱስ ታዴዎስ የዕረፍቱ መታሰቢያ በዓል በየዓመቱ ሐምሌ ፪ ቀን በቤተ ክርስቲያናችን ይከበራል፡፡ የቅዱስ ታዴዎስን ታሪክ በአጭሩ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሐዋርያት አስቀድሞ ቅዱስ ታዴዎስን እንደ መረጠው መጽሐፈ ስንክሳር ይናገራል፡፡ ቅዱስ ታዴዎስ አባቱ እልፍዮስ ይባላል (ማቴ. ፲፥፫)፡፡ ሐዋርያው – ‹ልብድዮስ›፣ ‹የያዕቆብ ልጅ ይሁዳ› እየተባለም ይጠራል (ሉቃ. ፮፥፲፮፤ ዮሐ. ፲፬፥፳፪፤ ሐዋ. ፩፥፲፫)፡፡  ቅዱስ ታዴዎስ በየአገሩ እየተዘዋወረ ወንጌልን በመስበክ ከአይሁድ እና ከአረማውያን ወገን ብዙዎችን በክርስትና ሃይማኖት አሳምኖ በክርስቶስ ስም አጥምቋል፡፡ አንድ ቀን ወደ ሀገረ ስብከቱ ወደ ሦርያ ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት ሲሔድ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጐልማሳ አምሳል ተገልጦ ‹‹ወዳጄ ታዴዎስ ሆይ፣ እኔ ከአንተ ጋር ነኝና አትፍራ›› በማለት ሰላምታ ሰጥቶት ወደ ሰማይ በክብር ዐረገ፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም የሐዋርያት አለቃ ነውና እንደ አባትነቱ ወደ ሦርያ ለማድረስ ከቅዱስ ታዴዎስ ጋር ሔደ፡፡ ከከተማዋ አጠገብ ሲደርሱም አንድ ሽማግሌ በሮችን ጠምደው ሲያርሱ አገኙ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ሽማግሌውን ምግብ በለመናቸው ጊዜ ‹‹በሮቼን ጠብቁ›› አሏቸውና ምግብ ሊያመጡላቸው ወደ ቤታቸው ሔዱ፡፡ ሽማግሌው እስኪመለሱ ድረስም ቅዱስ ጴጥሮስ በሮችን ጠምዶ ሠላሳ ትልም አረሰ፡፡ ቅዱስ ታዴዎስም በዚያ የነበረውን የሥንዴ ዘር መዝራት ጀመረ፡፡ የተዘራው ዘርም ወዲያዉኑ በቅሎ፣ አድጎ፣ እሸት ኾነ፡፡ ሽማግሌው ምግብ ይዘው ከቤታቸው ሲመለሱም ቅዱሳን ሐዋርያት ያደረጉትን ተአምር አይተው ደነገጡ፡፡ ከእግራቸው ሥር ወድቀውም ለሐዋርያት ሰገዱላቸው፡፡ በኋላም ‹‹እናንተ ከሰማይ የወረዳችሁ አማልክት ናችሁን?›› አሏቸው፡፡ እነርሱም ‹‹እኛ የእግዚአብሔር ባሮች እንጂ አማልክት አይደለንም›› አሉ፡፡

ሽማግሌውም ‹‹ስላደረጋችሁልኝ በጎ ሥራ በምትሔዱበት ቦታ ዅሉ ልከተላችሁን?›› ባሏቸው ጊዜ ሐዋርያት ‹‹ይህንን ልታደርግ አይገባም፤ ነገር ግን በሮችን ለጌታቸው መልስና በቤትህ የምንበላውን ታዘጋጅልን ዘንድ ለባለቤትህ ንገራት፡፡ እኛ ወደዚህች ከተማ ገብተን እግዚአብሔር እስከሚጠራን ጊዜ ድረስ እንቆያለንና›› ብለው መለሱላቸው፡፡ ሽማግሌውም የሥንዴውን እሸት ይዘው በሮችን እየነዱ ወደ ከተማ ሲሔዱ ወቅቱ የእርሻ እንጂ የእሸት ጊዜ አልነበረምና እሸት ይዘው በመመልከታቸው የከተማው ሰዎች ተገረሙ፡፡ ሽማሌውንም ‹‹ይህንን እሸት ከወዴት አገኘኸው?›› ብለው ጠየቋቸው፡፡ እርሳቸው ግን ምላሽ አልሰጧቸውም ነበር፡፡ ሽማግሌው ሐዋርያት እንዳዘዟቸው በሮቹን ለጌታቸው መልሰው ቤታቸውን አሰናድተው ራት እንድታዘጋጅላቸው ለሚስታቸው ነገሩ፡፡

ወሬውን የከተማው መኳንንት በሰሙ ጊዜም ‹‹በክፉ አሟሟት እንዳትሞት እሸቱን ከወዴት እንዳገኘኸው ንገረን›› ብለው በሽማግሌው መልእክተኞችን ላኩባቸው፡፡ ሽማግሌውም ‹‹ሕይወት ከእኔ ጋራ ሳለ ሞትን አልፈራም!›› አሉ፡፡ ከዚያም ሐዋርያት ያደረጉትን ዅሉ ነገሯቸው፡፡ መኳንንቱም ‹‹ሐዋርያቱን አምጣቸው›› አሏቸው፡፡ ሽማግሌውም ወደ እርሳቸው ቤት ሲመጡ ማግኘት እንደሚችሉ ነገሯቸው፡፡ ሰይጣን የልቡናቸዉን ዐሳብ ወደ ክፋት ለውጦታልና ከመኳንንቱ ከፊሎቹ ቅዱሳን ሐዋርያትን ለመግደል ተነሣሡ፡፡ ከፊሎቹ ግን ‹‹አምላካቸው ኢየሱስ የሚሹትን እንደሚያደርግላቸው ሰምተናልና ልንገድላቸው አንችልም፡፡ ነገር ግን አመንዝራ ሴት ወስደን በከተማው በር ርቃኗን እናስቀምጣት፡፡ እርሷን ሲያዩ ወደ ከተማችን አይገቡም፤›› አሉ፡፡ ይህን ማለታቸውም ቅዱሳን ሐዋርያት ንጹሐን እንደ መኾናቸው በዓይናቸው የሴት ልጅን ርቃን እንደማይመለከቱ መመስከራቸው ነበር፡፡

መኳንንቱ እንደ ተነጋሩት ሴትዮዋን በከተማው በር ርቃኗን አስቀመጧት፡፡ ሐዋርያው ታዴዎስ ባያት ጊዜም ‹‹ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! ወደ ከተማው ገብተን በከበረ ስምህ እስክንሰብክ ድረስ ይህቺን ሴት በአየር ላይ ይሰቅላት ዘንድ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልን ላክልን›› ብሎ ጸለየ፡፡ ጌታችንም ጸሎቱን ተቀበለውና ሴትዮዋ አየር ላይ ተሰቀለች፡፡ በዚህ ጊዜ የከተማው ሰዎችና መኳኳንንቱ ዅሉ እያዩአት ‹‹አቤቱ ፍረድልኝ›› እያለች ትጮኽ ጀመር፡: መኳንንቱ ግን ሰይጣን ልቡናቸውን አጽንቶታልና የሐዋርያትን ትምህርት አልተቀበሉም፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ታዴዎስ ወደ እግዚአብሔር በጸለዩ ጊዜም ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤልን ልኮ የሰዎቹን ልቡና የማረኩ መናፍስትን ርኩሳንን አባረረላቸው፡፡

ሰዎቹም የሐዋርያትን ትምህርት ተቀብለው በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ፡፡ ሐዋርያው ታዴዎስም በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ካጠመቃቸው በኋላ ኤጲስ ቆጶሳትን፣ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው፡፡ በአየር ላይ የተሰቀለችውን ሴትም አውርዶ ዲያቆናዪት አደርጎ ሾማት፡፡ በዚያች ከተማ በሐዋርያት እጅ ብዙ ድንቆችና ተአምራት ተደረጉ፡፡ ዕውሮች አዩ፤ ሐንካሶች ቆመው ሔዱ፤ ዲዳዎች ተናገሩ፤ ደንቆሮዎች ሰሙ፤ ለምጻሞች ነጹ፤ አጋንንትም ካደሩባቸው ሰዎች እየወጡ ተሰደዱ፤ ሙታንም ተነሡ፡፡ የከተማው ሰዎችም ይህንን ተአምር አይተው በቅዱሳን ሐዋርያት አምላክ በእግዚአብሔር አመኑ፡፡

አንድ ሰይጣን ያደረበትና ገንዘብ የሚወድ ጐልማሳ ባለ ጠጋም ወደ ሐዋርያው ታዴዎስ መጥቶ ሰገደለትና ‹‹የእግዚአብሔር አገልጋይ ሆይ! እድን ዘንድ ምን ላድርግ?›› ሲል ጠየቀው፡፡ ሐዋርያውም ‹‹እግዚአብሔርን በፍጹም ልብህ፣ በፍጹም ኀይልህ ውደደው፡፡ አትግደል፤ አትስረቅ፤ አታመንዝር፡፡ በአንተ ሊደረግብህ የማትሻውን በሌላው ላይ አታድርግ፡፡ ደግሞም ገንዘብህን ሸጠህ ለድኆችና ለምስኪኖች ብትሰጥ በሰማያት ለዘለዓለም የሚኖር ድልብ ታገኛለህ›› በማለት ሕገ ወንጌልን አስተማረው፡፡ ጐልማሳውም ትምህርቱን በሰማ ጊዜ ተቈጥቶ ሐዋርያውን አነቀው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ‹‹የክርስቶስን አገልጋይ እንዴት ደፍረህ ታንቃለህ?›› ባለው ጊዜ ጐልማሳው ቅዱስ ታዴዎስን ለቀቀው፡፡ የእግዚአብሔር ኀይል በይረዳው ኖሮ ሐዋርያው ከመታነቁ ጽናት የተነሣ ዓይኖቹ ሊወጡ ነበር፡፡

ያን ጊዜም ቅዱስ ታዴዎስ ‹‹ጌታችን ሀብታም መንግሥተ ሰማያት ከሚገባ ይልቅ ግመል በመርፌ ቀዳዳ ቢያልፍ ይቀላል› ሲል በእውነት የተናገረው እንዳንተ ላለው ሀብታም ነው›› አለው፡፡ ጐልማሳውም ‹‹ይህ ሊኾን አይችልም!›› ባለ ጊዜ ሐዋርያው ታዴዎስ በመንገድ ሲያልፍ ያገኘውን ባለ ግመል አስቁሞ መርፌ ገዝቶ ሊያሳየው ወደደ፡፡ መርፌ ሻጩ ሐዋርያውን ለመርዳት ፈልጎ ቀዳዳው ሰፊ የኾነ መርፌ አመጣለት፡፡ ቅዱስ ታዴዎስም ‹‹እግዚአብሔር ዋጋህን ይክፈልህ፤ ነገር ግን በዚህች አገር የእግዚአብሔር ክብር ይገለጥ ዘንድ ቀዳዳው ጠባብ የኾነ መርፌ አምጣልን›› አለው፡፡ ቀዳዳው ጠባብ የኾነውን መርፌ ቅዱስ ታዴዎስ ተቀብሎ ‹‹ኀይልህን ግለጥ›› ብሎ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፡፡ እጁንም ዘርግቶ ባለ ግመሉን ‹‹በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ከግመልህ ጋር በመርፌ ቀዳዳው ውስጥ እለፍ›› አለው፡፡ ሰውየውም እስከ ግመሉ ድረስ በመርፌ ቀዳዳው አለፈ፡፡

ዳግመኛም ‹‹ሕዝቡ የፈጣሪያችንን የክርስቶስን ኀይል ይረዱ ዘንድ ዳግመኛ ገብተህ እለፍ›› አለው፡፡ ሰውየውም እንደ ታዘዘው ሦስት ጊዜ በመርፌ ቀዳዳው አለፈ፡፡ ሕዝቡም ይህንን ተአምር አይተው ድምፃቸውን ከፍ አድርገው ‹‹ከቅዱሳን ሐዋርያት አምላክ ከሕያው እግዚአብሔር ልጅ ከኢየሱስ በቀር ሌላ አምላክ የለም›› እያሉ ተናገሩ፡፡ ያ ጐልማሳ ባለ ጠጋም ከሐዋርያው ታዴዎስ እግር በታች ወድቆ ሰገደና ‹‹ኀጢአቴን ይቅር በለኝ፡፡ ገንዘቤንም ዅሉ ወስደህ ለድኆችና ለምስኪኖች አከፋፍልኝ›› ሲል ተማጸነው፡፡ ሐዋርያውም እንደ ለመነው አደረገለት፡፡ የክርስትናን ሃይማኖትን ሕግ አስተምሮ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አጠመቀው፡፡ ሥርዓተ ቅዳሴ አከናውኖም ሥጋውን፣ ደሙን አቀበለው፡፡ በዚያች አገር አካባቢ የነበሩትን ዅሉንም በቀናች የክርስትና ሃይማኖት አጸናቸው፡፡ ከዚያ በኋላም ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ታዴዎስ ከዚያች ከተማ ወጡ፤ ሕዝቡም በሰላም ሸኟቸው፡፡

ቅዱስ ታዴዎስ በየአገሩ እየተዘዋወረ ወንጌልን ሲሰብክ ቆይቶ ከአይሁድና ከአረማውያን ዘንድ ብዙ መከራ ከደረሰበት በኋላ አገልግሎቱን ፈጽሞ ሐምሌ ፪ ቀን በሰማዕትነት ዐርፏል፡፡ በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ዘመንም ሐምሌ ፳፱ ቀን የከበረ ዐፅሙ ከሦርያ ፈልሶ በቍስጥንጥንያ ከተማ በስሙ በታነጸች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በክብር እንዲቀመጥ ተደርጓል፡፡ ከዐፅሙም ብዙ ድንቆችና ተአምራት ተገልጠዋል፡፡ ዅላችንንም የሐዋርያው ጸሎት ይጠብቀን፤ በረከቱም ይደርብን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡

  • መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሐምሌ እና ሐምሌ ፳፱ ቀን፤
  • ገድለ ሐዋርያት፣ ፲፱፻፺፬ .ም፤ አዲስ አበባ፣ ገጽ ፻፷፭ – ፻፸፩፡፡