ብፁዕ አቡነ ኤልያስ፣ ቤተ ክርስቲያንን ከነጣቂ ተኩላዎች መጠበቅ እንደሚገባ አሳሰቡ

ታኅሣሥ ፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ከነጣቂ ተኩላዎች መጠበቅ እንደሚገባ ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አሳሰቡ፡፡

ብፁዕነታቸው ይህን መልእክት ያስተላለፉት በጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት በዐርባ ምንጭ ከተማ በደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በተካሔደው የፀረ ተሐድሶ ጉባኤ ላይ ተገኝተው ‹‹እናንተ ግን ክፉውን ከመካከላችሁ አውጡ፡፡ በውጭ ባሉት ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል›› (፩ኛ ቆሮ. ፭፥፲፫) በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል በሰጡበት ወቅት ነው፡፡

የተሐድሶ መናፍቃን ሴራ በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ላይ እየፈጠረ ያለው መለያየት ከፍተኛ መኾኑን የጠቆሙት ብፁዕነታቸው የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮችም ኾኑ ምእመናን ስልታዊ እንቅስቃሴያችንን አጠናክረን በትጋት መቀጠል እንዳለብን አስገንዝበዋል፡፡

የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ለማፋለስ፣ የአገርን አንድነትና የምእመናንን ሰላም ለማደፍረስ የሚንቀሳቀሱ መናፍቃንን አውግዛ በመለየት ቤተ ክርስቲያን ሓላፊነቷን በመወጣት ላይ እንደምትገኝ ያስታወሱት ብፁዕነታቸው መናፍቃኑ ከስሕተታቸው የሚመለሱ ከኾነ መክራ፣ አስተምራ እንደምትቀበላቸውም አስረድተዋል፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ ከኅዳር ፩-፲፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም፤ ገጽ ፩፡፡