dscn6308

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የሰማዕታቱን ቤተሰቦችንና ምእመናንን አጽናኑ

ሚያዝያ15 ቀን 2007ዓ .ም.

dscn6308ሚያዝያ ፲፫ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. በደብረ ፍሥሓ መካነ ሰማዕት ቅዱስ ቂርቆስ አካባቢ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የሰማዕታቱን ኢያሱ ይኵኖ አምላክና ባልቻ በለጠ ቤተሰቦችንና ምእመናንን ሊያጽናኑ፤ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፣ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፣ ብፁዕ አቡነ ማትያስ ዘካናዳ፣ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፣ ብፁዕ አቡነ ኖክና ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሄደዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ

ልጆቻችን የምንኮራባቸው መጻሕፍቶቻችን ናቸው፡፡ ልጆቻችን ሰማዕታቶቻችን ናቸው፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የውድ ልጆቻችን የሰማዕታቱ፣ የታማኝ ልጆቻችን፣ የጀግኖች ልጆቻችን፣ በኢትዮጵያዊ ባህላቸው፣ በኢትዮጵያዊ ትውፊታቸው፣ በእምነታቸው፣ በሥርዐታቸው፣ በወጋቸው ጸንተው፣ ለማንም ሳይበገሩ እና ለማንም ሳይደለሉ፣ ለሌላ እጃቸውን ሳይሰጡ፣ ሳይቀለበሱ ጀግንነትን ያስተማሩ ልጆቻችን፣ መጻሕፍት የኆኑ ልጆቻችን ወላጆች እና እዚኅየተሰበሰባችሁ ውድ ወገኖቼ፡-

ከክርስቶስ ልደት በፊት ሰባት መቶ ዓመታት ቀድሞ የነበረው ነቢዩ ኤርያስ፣ በዚያን ጊዜዋ ባቢሎን በዛሬዋ ኢራቅ፤ በዚያን ጊዜዋ ፋርስ በዛሬዋ ኢራን እየዘዋወረ ባስተማረበት ዘመን ስለ ኢትዮጵያውን አድናቆት፣ ክብር፣ ጀግንነት፣ አይበገሬነት በትንቢቱ ምዕራፍ 13 ቁጥር 23 ላይ እንዲኽ ብሏል፡-ኢትዮጵያዊ መልኩን ነብር ዝንጉርጉርነቱን ሊለውጥ ይችላልን?

dscn6309ኢትዮጵያዊ ባህሉን፣ ኢትዮጵያዊ እምነቱን፣ ኢትዮጵያዊ አንድነቱን፣ ኢትዮጵያዊ ጀግንነቱን፣ ኢትዮጵያዊ ትውፊቱን በሌላ ሊቀይር ይችላልን? አይቀየርም፡፡ ነቢዩ ቆቃው ኤያስ በተባለ መጽሐፉም ይህን በስፋት እየገለጸ ይናገራል፡፡

ውድ ወገኖቼ፤ ልጆቻችን እኮ ጀግኖች ናቸው፤ ልጆቻችን እኮ እጃቸውን አልሰጡም፤ ልጆቻችን እኮ አልተንበረከኩም፤ ልጆቻችን እኮ መጻሕፍቶቻችን ናቸው፤ ልጆቻችን እኮ አርበኞቻችን ናቸው፤ አልተማረኩም፤ የጀግና እናት አታለቅስም እንደተባለው ሁሉ፣ እናንተም የጀግኖች እናቶች ናችሁ፤ ልትኮሩ ይገባችኋል፤ ስማቸውን ለውጠው፣ ሃይማኖታቸውን ለውጠው፣ ሥርዐታቸውን ለውጠው፣ ተማርከው ቢሆን ኖሮ ነበር ማልቀስ የሚገባን፡፡

ውድ ወገኖቼ፤ የጀግኖች ወላጆች ናችኹና ልትኮሩ፣ ልትጽናኑ ይገባችኋል፡፡ እሰይ ልጄ፤ ተባረክ ልጄ፤ ለመንግሥተ ሰማያት ያብቃኽ ብላችሁ ልትመርቁ፣ ልትጸልዩ፣ ልትጽናኑ ይገባል፡፡ የመጽናኛ ዕለት ነው፤ ልጆቻችን አስተምረውናል፤ ልጆቻችን አኩርተውናል፤ ልጆቻችን አስከብረውናል፤ አስወድደውናል፤ በዓለም ደረጃ አገራችንን አስተዋውቀዋል፡፡

ውድ ወገኖቼ፤ እንዲኽ ላሉት ነው እንዴ የሚለቀሰው? አገር አጥፍቶ ለሔደ፣ በሙስና ተዘፍቆ ለሔደ፣ ሰክሮ ለሔደ፣ አመንዝሮ ለሔደ፣ ቀምቶ ለሔደ በምድር ኑሮው ተበላሽቶ፣ በሰማይ እንዴት ይኾን ከቶ ተብሎ የሚለቀስለት ለዚኽ ነው፡፡ ብዙ ልጆቻችን በየመልኩ ኸሉም አርበኛ ነው፡፡ አካሉን፣ ሕይወቱን፣ ወላጁን፣ ልጁን፣ ዘመኑን፣ ንብረቱን የሰጠ ስንት አለ? ውድ ወገኖቼ፤ እንዴ፣ እነዚኽማ ልጆቻችን የምንኮራባቸው መጻሕፍቶቻችን ናቸው!! የምንማርባቸው ዩኒቨርስቲዎቻችን ናቸው ልጆቻችን!! ብርሃናችን ናቸው ልጆቻችን!! ማዕተቤን አልበጥስም፤ ወደ ሌላ አንለወጥም፤ አንበገርም አሉ፤ ይኼ ነው ወይ የሚያስለቅሰው? የሚለቀስበትን ነገር እንወቅ እንጂ!

ውድ ወገኖቼ፤ ስለዚህ ልጆቻችንን በሰማዕትነታቸው፣ በጀግንነታቸው ልናከብራቸው፣ ልንማርባቸው፣ ምሳሌአቸውን ልንወስድ፣ ልናወድሳቸው ይገባል፡፡ ስለዚኽ ይኼ የመረጋጋት፣ የሰላም የፍቅር ቦታ ነው፡፡ ልጆቻችን የአገር ፍቅር፣ የአገር ሰላም፣ የአገር አንድነት አስተምረውናል፡፡ በልጆቻችን ተምረናል፤ ጠግበናል፤ ረክተናል፤ ኮርተናል፡፡

የልጆቻችንን ነፍስ በገነት በመንግሥተ ሰማያት ያሳርፍልን፤ ይማርልን፤ ወላጆቻቸውን ይጠብቅልን፤ ከክፉ ነገር ይሰውረን፤ መልካሙን ነገር ያምጣልን፤ ልጆቻችንና ወገኖቻችንን በሰላም ወደ ቤታቸው ይመልስልን፡፡ ሁላችንም ተጽናንተን የሚያኮራ ሥራ እንድንሠራ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡ ነፍሰ ገብሩ ኃይለ ኢየሱስ፣ ኃይለ ሚካኤል ሀገረ ሕይወትን መንግሥተ ሰማያትን ያውርስልን፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን የሐዘን ዳርቻ ያድርግልን፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን የቤተሰቡን ሕይወት፣ የቤተሰቡን ሐዘን በመልካም ነገር፣ በፍቅር ነገር ይለውጥልን፡፡ ቤተሰቡን ያለምልምልን፡፡ ቤተሰቡን ያጽናልን፡፡ ደግ ያልኾኑ ሰዎችን ወደ ደግነት፣ ወደ ምሕረት፣ ወደ ቸርነት ይመልስልን፡፡ ለዓለሙ ኹሉ ሰላም መረጋጋትን ያድልልን፡፡ አገራችን ኢትዮጵያን በክብር በረድኤት ይጠብቅልን፡፡

ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ

dscn6312ያለንበት አካባቢ ቤተ መቅደሱ ቂርቆስ ነው፡፡ እንደምታውቁት ቂርቆስ ሕፃን ነው፡፡ በምን መልክ እንደ ዐረፈ ታውቃላችሁ፡፡ ሕፃኑ ቂርቆስ፣ ዓላውያን ነገሥታት በእኛ እምነት እመን፤ እኛ የምናዝዝህን ፈጽም ባሉት ሰዓት አልተቀበላቸውም፡፡ እሳት ነደደ፤ በበርሜል ውስጥ ውኃ ፈላ፡፡ በዚህ ሰዓት እናቱ ደንግጣ ወደ ፈላው ውኃ ለመግባት ስትፈራ ሕፃኑ ቂርቆስ፣ እናቴ ጨክኚ፤ ዛሬ መንግሥተ ሰማያት የምንገባበት ቀን ነው፡፡ አባቶቻችን በሰጡን፣ ባወረሱን፣ ባስተማሩን እምነት ጸንተን ወደ መንግሥተ ሰማያት የምንገባበት ነውና ከዓላዊው ንጉሥ አትፍሪ ብሎ እናቱን ወደ እሳት የጋበዘ ነው፡፡ እስከ መጨረሻው እስከ ዘላለሙ ሰማዕቱ ቂርቆስ ሲባል ይኖራል፤ ታሪክ ሲዘክረው ይኖራል፤ ታሪክ አይደመሰስም፡፡

አሁንም እነዚህ ወንድሞቻችን፣ ወገኖቻችን ሰማዕታት የታሪክ ባለቤቶች ስለኾኑ፣ ታሪክ አትርፈው ስለሔዱ ከእነርሱ በፊት እንደነበሩት ኹሉ ለዘላለም ስማቸው፣ ሥራቸው ሲወሳ ይኖራል፡፡ ሐዘን ሁልጊዜ ሲያነሡት ልብ ይሠቀጥጣል፡፡ ይኼን እያነሡ መናገር በጣም ይከብዳል፡፡ ጭንቅላት ሊሸከመው አይችልም፡፡ እናም እዚህ ያሉትን እያጽናናችኹ፣ እዚያ የቀሩት ደግሞ በሰላም እንዲወጡ ምህላ እያደረግን ልንጸልይ ይገባል፡፡ እኛ እዚኽ ፀሐይ እየሞቅን፣ እየተነጋገርን እናዝለን፤ እዚያ እነርሱ ከወጡበት ሰውነታቸው አልቆ ነፍሳቸው የምትጨነቅ አለችና በሰላም እንዲያወጣቸው ላለፉት ብቻ ሳይኾን ለቀሩትም ጸሎት እያደረጋችኹ በዚኽ እንድትጽናኑ ነው አደራ የምንለው፡፡

ወላጆች ወለዱ እንጂ የሁላችን ልጆች ናቸው፤ ሐዘኑ የኢትዮጵያ ነው፤ እግዚአብሔር ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጽናቱን ይስጥልን፡፡ እዚያ የቀሩትንም በሰላም ያውጣልን፡፡

001 papasat 002

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በሐዘንተኞቹ ቤት ተገኝተው በማጽናናት ላይ ይገኛሉ

ሚያዝያ 13 ቀን 2007 ዓ.ም.

001 papasat 002በዛሬው ዕለት ከቀኑ ዐሥር ሰዓት ጀምሮ ከስድስት በላይ ሊቃነ ጳጳሳት ሰማእቱ ቅዱስ ቂርቆስ ቤተ ክርስቲያን አካባቢ በሚገኘው በሊቢያ በግፍ በአሰቃቂ ሁኔታ የተገደሉትን ወጣቶች ቤተሰቦችን ለማጽናናት በመኖሪያ ቤታቸው ተገኝተዋል፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳቱ በጥልቅ ሐዘን ላይ ለሚገኙት የሰማእታቱ ቤተሰቦችን፤ ዘመድ ወዳጆቻቸውን እንዲሁም ምእመናንን በቃለ እግዚአብሔር በማጽናናት ላይ ይገኛሉ፡፡

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፤ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፤ ብፁዕ አቡነ ማትያስ፤ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፤ ብፁዕ አቡነ እንጦንስ፤ ብፁዕ አቡነ ሔኖክ ተገኝተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ በሰጡት የወንጌል ትምህርት €œልጆቻችን ብርሃን፤ መጻሕፍቶቻችንና ጀግኖቻችን፤ እንዲሁም የሃማኖትም የሀገርም አርበኞች ናቸው፡፡€ ብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ በበኩላቸው የሰማእቱ ቅዱስ ቂርቆስንና የእናቱን የቅድስት ኢየሉጣን ታሪክ መነሻ በማድረግ ሰፊ የማጽናኛ ትምህርት ሰጥተዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ሚዲያ ክፍል አባላትም በቦታው ተገኝተዋል፡፡

005siklet

ሕማማተ እግዚእነ በልሳነ አበው /የጌታችን መከራ በሊቃውንት አንደበት/

ሚያዝያ 1 ቀን 2007 ዓ.ም.

005sikletየእስክንድርያው ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ ቄርሎስ እንዲህ አለ

ታመመ፤ ሞትን ከተቀበለበት ከሥጋ ተዋሕዶ በመስቀል ላይ በፈቃዱ ለሥጋውያን ሞተ፣ ባሕርየ መለኮት ሥጋን ተዋሕዶ በማኅፀን ካደረ ጀምሮ ሥጋ ገንዘቡ እንደመሆኑ በሥጋ ይኸንን ሥርዓት ፈጸመ፡፡

ለማይመረመር ለመለኮቱ ባሕርይ እንደሚገባ ደግሞ እርሱ ኅብስት አበርክቶ ሁሉን ያጠግባል፡፡ አይራብም፣ አይጠማም፣ አይደክምም፣ አያንቀላፋም፣ አይታመምም፣ አይሞትም ሕይወትን ለሁሉ ይሰጣል፡፡ ዳግመኛ በዚያ በሲኦል ተገዝተው ያሉ ነፍሳትን ያድን ዘንድ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወረደ በመለኮቱም ሲኦልን በዘበዘ፡፡

ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ጎርጎርዮስ የወልድን ነገር በተናገረበት ድርሳኑ እንዲህ አለ

እጆቹን፤ እግሮቹን በተቸነከረባቸው ችንካሮች መወጋቱንም እናምናለን፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ እርሱ ደዌያችንን ወሰደ ሕማማችንንም ተሸከመ፤ እኛን ለማዳን ኃጢአታችንንም ለማስተስረይ መከራ ተቀበለ እንዳለ፤ በባሕርዩ ሕማም የሌለበት ሲሆን በሥጋ የታመመ ነው፡፡ በእርሱ ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ ድነናል አለ፡፡ በተገረፈና በተቸነከረም ጊዜ በመከራው ሁሉ መለኮትን ሕማም ተሰማው የሚል ሰው ቢኖር የተለየ የተወገዘ ይሁን፡፡

የአንጾኪያው ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ዲዮናስዮስ ከላከው ሲኖዶሳዊ መልእክት የተገኘ

እርሱ መቼም መች ከመለኮቱ ሳይለይ የሰውነትን ሥራ ሁሉ ገንዘቡ አደረገ፡፡ ይኸውም መራብ፣ መጠማት፣ መንገድ በመሔድ መድከም፣ በመስቀል ላይ መሰቀል፣ በብረት ችንካር መቸንከር ነው፡፡ በሰውነቱ መቸም መች ሰው ነው፣ በአምላክነቱም ሰውን የፈጠረ ነው፡፡ ግን ከማይከፈል ተዋሕዶ በኋላ መከፈል የለበትም፡፡ ሰው እንደ መሆኑ ስለ እኛ የታመመው የሞተው እርሱ ነው፡፡ በመለኮቱ ግን መቸም መች አይታመምም አይሞትም፣ ሕማምንና ሞትንም አይቀበልም፡፡ በሞቱ ሞትን ያጠፋው እርሱ ነው፡፡ ሲኦልንም የበዘበዘው እርሱ ነው፡፡

የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ ሐዋርያው ቅዱስ አትናቴዎስ እንዲህ አለ

ነፍሱን ከሥጋው በለየ ጊዜ ያን ጊዜ በሲኦል ፈጥኖ ብርሃን ታየ፡፡ ጌታችን በአካለ ሥጋ ያይደለ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ሔደ፡፡

ሲኦል ተነዋወጠች፣ መሠረቶቿም እፈርስ እፈርስ አሉ፣ ምድርን ያለ ጊዜዋ እንዳታልፍ ክብርት ደሙን በምድር ላይ አፈሰሰ፡፡ ከኅልፈት ጠበቃት በርሷ ያለውንም ሁሉ ጠበቀ፡፡

ስለ ፍጥረት ሁሉ ሥጋውን በመስቀል እንደተሰቀለ ተወው፡፡ ነፍሱ ግን ወደ ሲኦል ወረደች ከዚያ ተግዘው የነበሩ ነፍሳትን አዳነች፤ ሲኦልንም በዘበዘች፤ ፍጥረትንም ሁሉ ገንዘብ አደረገች፡፡ ሥጋውም በመቃብር ያሉ ሙታንን አስነሣ፤ ነፍሱም በሲኦል ተግዘው የነበሩ ነፍሳትን ፈታች፡፡

ሃይማኖታቸው የቀና ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ሊቃውንት በአንድ ልብ እንዲህ አሉ

ከብርሃን የተገኘ ብርሃን፣ ከባሕርይ አምላክ የተገኘ የባሕርይ አምላክ፣ የተወለደ እንጂ የተፈጠረ ያይደለ፣ በባሕርዩ ከአባቱ ጋር አንድ የሚሆን፡፡ ሁሉ የተፈጠረበት ያለ እርሱ ግን ምንም ምን የተፈጠረ የሌለ፣ በሰማይ በምድር ያለውም ቢሆን፡፡

እኛን ስለማዳን ከሰማየ ሰማያት ወርዶ በግብረ መንፈስ ቅዱስ ከቅድስት ድንግል ማርያም ፍጹም ሰው ሆነ፡፡

የሠላሳ ዘመን ጎልማሳ ሆኖ በጶንጦስ ሰው በጲላጦስ የሹመት ዘመን ስለ እኛ ተሰቀለ፣ ስለ እኛም ታመመ ሞተ ተቀበረ፡፡

የቂሣርያ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ባስልዮስ እንዲህ አለ

ምትሐት ያይደለ በእውነት ተራበ፣ ተጠማ እንጂ፡፡ ዳግመኛም ከኃጥአን ከመጸብሐን ጋር በላ ጠጣ፣ ያቀረቡለትንም በላ፡፡ ራሱን አሳልፎ ለመስቀል ሰጠ፣ እጁን እግሩን ተቸነከረ፣ ጎኑን በጦር ተወጋ፣ ከእርሱም ቅዱስ ምስጢር የተገለጠበት ደምና ውኃ ፈሰሰ /ወጣ/፡፡

የኑሲስ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ጎርጎርዮስ እንዲህ አለ

የሚሠዋ በግ እርሱ ነው፣ የሚሠዋ ካህን እርሱ ነው፡፡ ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋርም መሥዋዕት የሚቀበል እርሱ ነው፡፡ በፈቃዱ መከራን በሥጋው የተቀበለ መከራንም ሁሉ የታገሠ እርሱ ነው፡፡ እንደ በግ ሊሠዋ መጣ፣ በግ በሚሸልተው ሰው ፊት እንዳይናገር አልተናገረም፣ በአንደበቱ ሐሰት አልተገኘበትም፡፡

ሰማዕት የሆነ ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ፊልክስ እንዲህ አለ

በሥጋ መወለድ፣ በመስቀል መከራ መቀበል፣ መሞት መነሣት፣ ገንዘቡ የሆነ እርሱ እግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ ስለዚህ በመስቀል ላይ ሳለ ከጥንት ጀምሮ በመቃብር ያሉ ሙታንን ሁሉ አስነሣ፡፡

የሮማ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ አቡሊዲስ እንዲህ አለ

ሙሴም ሞትን ያጠፋ ዘንድ አልቻለም፣ እርሱንም ይዞ ገዛው እንጂ፣ ከእርሱም በኋላ የተነሡ ነቢያትንም ሁሉ ሞት ገዛቸው እንጂ፡፡ ክርስቶስ ግን በቸርነቱ ለሁሉ ሕይወትን ሰጠ፡፡

የሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ አዮክንድዮስ እንዲህ አለ

በመስቀል በሥጋ ተሰቅሎ ሳለ ለመለኮት ከሥጋ መለየት የለበትም፡፡ አንዲት ሰዓትም ቢሆን የዐይን ጥቅሻ ያህል ስንኳ ቢሆንም መለኮት ከትስብእት አልተለየም፣ በመቃብር ውስጥ በሰላም መለኮት ከትስብእት አልተለየም፡፡

የኪስኪስ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ኤራ ቅሊስ እንዲህ አለ

ከአብ ጋር አንድ እንደ መሆንህ ሞት የሌለብህ አንተ ነህ ከእኛ ጋር አንድ እንደመሆንህ በፈቃድህ የሞትክ አንተ ነህ፡፡

በመቃብር ያደርህ አንተ ነህ፣ በኪሩቤል ላይ ያለህ አንተ ነህ፡፡ ከሙታን ጋር በመቃብር የነበርክ አንተ ነህ፣ በአንተ ሕማምና ሞትም ድኅነት ተሰጠ፡፡

ከሙታን ጋር የተቆጠርክ አንተ ነህ፣ ለሙታንም ትንሣኤን የምትሰጥ አንተ ነህ፣ ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በመቃብር ያደርክ አንተ ነህ፣ በዘመኑ ሁሉ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የምትኖር አንተ ነህ፡፡

በመለኮት ሕማም ሳይኖርብህ በሥጋ የታመምክ አካላዊ የእግዚአብሔር ቃል አንተ ነህ፡፡

የኢየሩሳሌም ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ዮሐንስ እንዲህ አለ

ኃጢአታችንን ለማሥተሰረይ በሥጋ እንዲህ ታመመ፣ እንደሞተ ከነፍሱም በተለየ ጊዜ ሥጋውን እንደ ገነዙ እናምናለን፡፡

የቆጵሮስ ደሴት ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ እንዲህ አለ

ነብይ ዳዊትም ነፍሴን በሲኦል አትተዋትም የባሕርይ ልጅህንም ሙስና መቃብርን ያይ ዘንድ አሳልፈህ አትሰጠውም አለ፡፡ ይህም ጌታ በተዋሐደው አካል ያለውን የነፍስና የሥጋ ተዋሕዶ ያስረዳል፣ የቀና ልቡና ዕውቀት በእርሱ ጸንቶ ይኖር ዘንድ፡፡ ዳዊት እንደተናገረው እውነት ሆነ፣ ነፍስ መለኮትን ተዋሕዳ ወደ ሲኦል ወርዳለችና፣ ሥጋም ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በመቃብር ሳለ መለኮት ከሥጋ አልተለየም፡፡ አምላክ ሰው የመሆኑን እውነት ያስረዳ ዘንድ፣ መለኮት ነፍስን ተዋሕዶ በአካለ ነፍስ የሲኦል ምስጢርን ገልጦ ፈጽሟልና በሲኦልም በቁራኝነት አልተያዘምና፡፡

ምንጭ ስምዐ ተዋሕዶ፤ ሚያዝያ 1-5 ቀን 2007 ዓ.ም.

ሆሳዕና በአርያም

መጋቢት 24 ቀን 2007 ዓ.ም.

በዲ/ን ሚኪያስ አስረስ

ሰውን ከወደቀበት የበደል ጉድጓድ ያወጣው ዘንድ እግዚአብሔር ክንዱን ወደ ዓለም ላከ፡፡ ሰው ሆኖ የተገለጠው የእግዚአብሔር ክንድ በጉድጓድ ተጥሎ የነበረን በዚያም በሥጋ በነፍስ፤ በውስጥ በአፍአ ቆስሎ የነበረ አዳምን በትህትና ሁለተኛ አዳም ሆኖ በሥጋ የቆሰለውን በለበሰው ሥጋ ቆስሎ;በነፍስ የታመመውን በትምህርት አዳነ፡፡ ከእርሱ አስቀድሞ ሰውን ከሞት ወደ ሕይወት፤ ከባርነት ወደ ነፃነት የሚያመጣ ባለመኖሩ እርሱ ሁሉን የፈጠረ ሁሉን የሚያኖር እግዚአብሔር ሰው ሆኖ ለሰው መድኃኒት ሆነ፡፡ በሞቱም መድኃኒትነትን አሣየ፡፡ በነቢይ መድኃኒተ ፈነወ እግዚአብሔር ለሕዝቡ፤ እግዚአብሔር ለሕዝቡ መድኃኒትን ሰደደ፡፡ (መዝ.110፡9) ተብሎ የተነገረው ተፈጸመ፡፡

ክርስቶስ ባለ መድኃኒት ሆኖ በኃጢአት ለታመሙ ደቂቀ አዳም ሁሉ ሕይወትን ይሰጥ ዘንድ ወደዚህኛው ዓለም መጣ፡፡ በምድራዊ ሥርዓት እንደምናየው መድኃኒትና ባለ መድኃኒት እንደሚለያዩ አይደለም፡፡ ሁለቱም እርሱ በመምጣቱ (ሰው በመሆኑ) ፈጸ እንጂ፡፡ መድኃኒት አድርጎ ሥጋውን ደሙን የሰጠ እርሱ ነው፡፡ በካህናት አድሮ ሰው በንስሐ ሲመለስ መድኃኒት ወደሆነው ወደ ራሱ የሚመራ እርሱ ነው፡፡

ክርስቶስ መድኃኒት መሆኑ በሕማሙ እና በሞቱ ነው፡፡ በእመቤታችን ማኅፀን የተጀመረው የእርሱ መድኃኒትነት እና ፍቅሩ ፍፃሜውን ያገኘው በሕማሙ እና በሞቱ ነው፡፡ መሐሪ ንጉሥ እርሱ መሆኑን ይገልጥ ዘንድ በፈቃዱ ወደ ኢየሩሳሌም መጣ፡፡ ጌታ ወደ ኢየሩሳሌም ከመግባቱ አስቀድሞ ከኢየሩሳሌም 16 ያህል ምዕራፍ በምትርቀው በቤተፋጌ ከደቀመዛሙርቱ ጋር ነበር፡፡

ከደቀ መዛሙርቱም ሁለቱን (ማለትም ጴጥሮስን እና ዮሐንስን) በፊታችሁ ወዳለችው መንደር ሂዱ ወዲያውም ወደ እርሷ ገብታችሁ ከሰው ማንም ገና ያልተቀመጠበትን ውርንጫ ታስሮ ታገኛላችሁ ፈትታችሁ አምጡልኝ፡፡ (ማር 11፡2) በማለት አዘዛቸው፡፡ ዳግመኛም ሰው ወዳልገባባት የተዘጋች የምሥራቅ ደጅ ወደ ምትባል ወደ ድንግል መጥቶ ዘጠኝ ወር ማኅፀኗን ከተማ አድርጎ እንደኖረ፤ ማኅየዊት ከምትሆን ሕማሙ በኋላም ሰው ባልተቀበረበት መቃብር እንደተቀበረ፤ አሁንም ጌታ ወደ ኢየሩሳሌም ለመግባት ማንም ሰው ያልተቀመጠባቸውን በሌላ መንደር የሚገኙ አህያንና ውርንጫን እንዲያመጡ ደቀመዛሙርቱን አዘዘ፡፡

የፍጥረት ሁሉ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በልደቱ እስትንፋሷን የገበረችለትን አህያ አሁን ደግሞ በፈቃዱ ስለ ሰው ሁሉ ሊሞት ሲል ንጉሥነቱን ሊያስመሰክርባት ወደደ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እስከ ኢየሩሳሌም ድረስ ካለው 16 ምዕራፍ አሥራ አራቱን በአህያ ላይ ሳይቀመጥ በእግሩ ሄደ፡፡ ከዚያም ሁለቱን ምዕራፍ በአህያ ላይ በመቀመጥ ከተጓዘ በኋላ የኢየሩሳሌምን መቅደስ ሦስት ጊዜ በውርጫዋ ላይ በመሆን ዞረ፡፡ በዚህም ለሰው ሁሉ ያለው ቸርነቱ፣ ሕግ የተሰጣቸው አይሁድ እና ሕግ ያልተሰጣቸው አሕዛብ ላይ እኩል ቀንበርን መጫን እንዳይገባ አጠየቀ፡፡

ወደ ኢየሩሳሌምም ሲሄድ ብዙ ሰዎች ልብሳቸውን በመንገድ ላይ አነጠፉ፣ ሌሎችም ከዛፍ ቅጠሎችን እየቆረጡ ያነጥፉ ነበር፡፡ (ማር. 11፡8)፡፡ ከዚያም ሰዎች ሆሣዕና በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው (ማር. 11፡9) በማለት አመሰገኑ፡፡ ይህም ዛሬ ለቤተ ክርስቲያን እኛ ክርስቲያኖች ቡሩክ ስሙ ለእግዚብሔር ወቡሩክ ዘይመጽእ በስመ እግዚአብሔር፤ የእግዚአብሔር ስሙ ምስጉን ነው፡፡ እግዚአብሔር ነኝ ብሎ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ እርሱ ክርስቶስም ምስጉን ነው በማለት የአብ እና የወልድን መስተካከልን ገልጸን ጌታን እናመሰግናለን፡፡ ጌታን የሚከተሉት ሰዎች ሆሣዕና በአርያም እያሉ ይጮኹ ነበር (ማር.11፡10) ይኸውም በልዕልና፣ በሰማይ ያለ መድኃኒት፣ ከሰማይ የመጣ መድኃኒት ማለት ነው፡፡

የእግዚአብሔር ፍቅር እና መሓሪ መሆን በክርስቶስ ሕማም እና ሞት ከመቼውም ጊዜ በላይ ተገልጧል፡፡ ክርስቶስ የተቀበለው ሕማም እና ሞት የእርሱን አምላክነት እና ንጉሥነት አልሸሸገውም፡፡ እንደውም ዙፋኑን መስቀል በማድረግ ንጉሥነቱን በመድኃኒትነቱ ገልጿል እንጂ፡፡ በነቢይ እግዚአብሔርሰ ንጉሥ ውእቱ እምቅድመ ዓለም ወገብረ መድኃኒተ በማዕከለ ምድር፣ እግዚአብሔር ከዓለም አስቀድሞ ንጉሥ ነው፤ በምድር መካከልም መድኃኒትን አደረገ መዝ. 73፤12 ተብሎ የተነገረው እግዚአብር ድኅነትን በፈጸመበት ማዕከለ ምድር ሲሰቀል በመድኀኒትነቱ ንጉሥነቱን መግለጡን ያመለክታል፡፡ ዳግመኛም አንሰ ተሰየምኩ ንጉሠ በላዕሌሆሙ በጽዮን በደብረ መቅደሱ፤ እኔ ንጉሥ ሆኜ ተሸምኩ በተቀደሰው ተራራ ላይ(መዝ.2፡6) ተብሎ የተነገረው ኦርቶዶክሳውያን አበው እነርሱ (አይሁድ) ሰቅለነው ገድለነው ኋላ ፈርሶ በስብሶ ይቀራል ይሉኛል እንጂ እኔ ደብረ መቅደስ በምትባል በመስቀል ላይ ነግሻለሁ በማለት ይተረጉሙታል፡፡

ጌታ ንግሥናው ክብሩ የተገለጠበት ሆነ እንጂ መታመሙ እና መሞቱ ውርደት ክብሩንም የሚሸሽግ አይደለም፡፡ ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ ይትባረክ እግዚአብሔር ዘሰመየ ሕማማት ወልዱ ክብረ ወስብሐት፣ የልጁን ሕማማት ክብርና ምስጋና አድርጎ የሰየመ እግዚአብሔር ይመስገን አለ፡፡ እኛን ያከበረበት በመሆኑ ሕማሙ ክብር እንደተባለ እናስተውል፡፡ በመስቀል ላይ ሆኖም በቀኝ የተሠቀለው ወንበዴ አቤቱ በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ (ሉቃ 24 ) በማለት ንጉሥነቱ መስክሮለታል፡፡ ለዚህ ነው ጌታ ወደ ኢየሩሳሌም በምስጋና መግባቱ መድኃኒትነቱን እና ንጉሥነቱን ያሳያል ያልነው፡፡ ዳግመኛም ሁሉን የያዘ ጌታ በአህያ ላይ መቀመጡ ትህትናው ያስረዳል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ዘይነብር ዲበ ኪሩቤል ዲባ ዕዋለ አድግ ነበረ፡፡ በማለት ሰማያዊ ልዑል አምላክ ትሑት ሆኖ እንደተገለጠ ተናገረ፡፡

ጌታ ከመድኃኒትነቱ የተነሣ ድንቅ የሆኑ እና ተአምራትን ለሰዎች አሳየ (ገለጠ)፡፡ እም ሆሳዕናሁ አርአያ ተአምረ ወመንክረ (ቅዳ. ጎርጎ.ዘኑሲስ) እንዲል፡፡ ይኸውም በአህያ ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ አእምሮ ጠባይዕ ያልቀናላቸው ሕፃናት ዕውቀት ተገልጾላቸው ሆሳዕና በአርያም እያሉ ጌታ በማመስገናቸው ነው፡፡ ዳግመኛም በከሃሊነቱ መናገር ለማይችሉ ዕውቀት ለሌላቸው ድንጋዮች ዕውቀት ተሰጥቷቸው መናገር ችለው ጌታን አመስግነዋል፡፡ እርሱ የባሕርይ አምላክ መሆኑ በሰውነቱም ቀድሞ በበደል ምክንያት ለሰው ከመገዛት ውጪ የሆኑ ፍጥረታት ዳግመኛ ሥጋዌ ለሰው እንደተገዙ ከዚህ ሁሉ ማስተዋል ይገባል፡፡

ጌታ ከመድኃኒትነቱ የተነሣ ልጅነት እና ተአምራት ማድረግን ገለጸ፡፡ እም ሆሳዕናሁ አርአያ ጸጋ ወኅይለ እንዲል (ቅዳሴ ጎርጎ. ዘኑሲስ)፡፡ የእርሱ ማዳን ከሰው ተወስዶበት የነበረ የጸጋ ልጅነት እንዲመለስለት አድርጋ በልጅነት ላይ ገቢረ ተአምራት (ተአምራትን ማድረግ) ገልጿል፡፡ ይኸውም እርሱ በረድኤት አድሮባቸው ድንቅ ተአምራትን ሚያደርጉ ቅዱሳን መሠረት ነው፡፡ በተጨማሪም ልጅነትን ካገኙ በኋላ በበደል ሲገኙ ለንስሓ የሚሆን እንባን ሠጠ፡፡ እምሆሳዕናሁ ወሀበ ፈልፈለ አንብዕ ለኅጥአን እንዲል (ቅዳሴ ጎርጎ. ዘኑሲስ) ይኸውም የበደሉትን ያከብራቸው ዘንድ፣ ኀጥአንን ከኃጢአታቸው ያነጻቸው ዘንድ እንዲሁም የሳቱትን በንስሐ ይመልሳቸው ዘንድ ነው፡፡

ዳግመኛም ጌታ መድኀኒት ከመሆኑ የተነሣ ለዕውራን ዳግመኛ ብርሃንን ሰጠ፡፡ ይኸውም ለጊዜው በተፈጥሮ ዐይን ተሰጥቷቸው የታወሩትን ፈውሶ በሥጋ ብርሃን መስጠቱ ሲሆን፤ ፍጻሜው ግን በነፍስ ዕውቀትን ከማጣት የተነሣ ዕውራን የነበሩትን ትምህርትን; ዕውቀትን ገለጸላቸው፡፡ ይኸውም የእርሱ ገንዘቡ ስለሚሆን አንድነት ሦስትነት፣ አምላክነቱን መድኃኒት መሆኑን ገለጠላቸው ማለት ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ኒቆዲሞስና አዲሱ ልደት

መጋቢት 20 ቀን 2007 ዓ.ም.

በዲ/ን ታደለ ፈንታው

በቅዱስ ዮሐንስ ወንጌል በምዕራፍ ሦስት ብዙ አሕዛብ ወደ ክርስትና እምነት የተቀላቀሉበት ምዕራፍ ነው፡፡ድኅነትን በትጋት ለመፈጸም የሚታገሉ ክርስቲያኖች ይሄንን ምዕራፍ ሲያነቡ ከኒቆዲሞስ ጎን መቆማቸው የሚያጠራጥር አይሆንም፤ ከጌታ ጋር ምስጢራዊ የሆነ ውይይትን መቀጠል ይፈልጋሉ፡፡ በሕይወታቸው የተከፈተ የአዲስ ኪዳን መንገድን እንዳለ ሲገነዘቡም ጌታን ይከተላሉ፡፡ ከእርሱ ጋር ከቅዱስ መንፈሱም ጋር አንድ ይሆናሉ፡፡ አዲስ ልደትን ያገኛሉ ፤ይህም በጥምቀት የሚገኝ ልጅነት ነው፡፡

ይህ ምዕራፍ መልካም ሥነ ምግባር በነበረው ፈሪሳዊ ሕያውና መንፈሳዊ በሆነው ምንጭ በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ መካከል የነበረውን ውይይት ይዟል፡፡

ኒቆዲሞስ እንደ ፈሪሳዊ በአይሁድ ትውፊትና በብሉይ ኪዳን ትምህርት የታጠቀ ነው፡፡ ጠንካራ ሞራል እንደገነባ ሰው ወደ ጽድቅ የሚወስደውን ትውፊት የሚያውቅ ሰው በፈቃዱ መታዘዝ እንዳለበት የሚያምን ነው፡፡ ይህ የሚሆነው ደግሞ ሰው በሚያደርገው ጠንካራ ትግል እንደሆነ ያምናል፡፡ይህ ትግል በሰው በጎ ፈቃድና ሕጉን በደረቁ በመተርጎም እንደሚገኝ ያምናል፡፡ ኒቆዲሞስ ጌታን ያገኘው ሕጉን የሚቃወም ሆኖ ሳይሆን ሕጉን በጥልቀት የሚተረጉም አይሁዳዊ ሆኖ ነው፡፡

ስለዚህም ነው ወደ መድኀኒታችን ከተሳቡ ወገኖች መካከል ወንጌላዊው የኒቆዲሞስን ጉዳይ በትኩረት የጻፈው፡፡ በዚህ ዐውድ ቅዱስ ዮሐንስ እንዲህ ይላል፡-በፋሲካ በዓልም በኢየሩሳሌም ሳለ ያደረገውን ምልክት ባዩ ጊዜ /ዮሐ.2፡23/፡፡ ኒቆዲሞስ ጌታ ከእግዚአብሔር እንደመጣ አወቀ፤ አመነም /ዮሐ.3፡2/፡፡ ነገር ግን ምናልባት ኒቆዲሞስ ጌታ ትምህርቱን ማኅበራዊ ጉዳይ ላይ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚያስተምር ሊያስብ ይችላል፡፡ የሕጉን ጥሬ ትርጉም እንጂ ፍካሬያዊ ትርጉም አልተገነዘበም፡፡ የአይሁድን ኑሮ ሊያሻሽል የመጣ ነው ብሎም ሊያስብ ይችላል፡፡

የኒቆዲሞስ አመለካከቱና ልምዱ በክርስቶስ ኢየሱስ ያለውን አዲስ ሕይወት ለመቀበል አያበቃውም፡፡ በአዲሱ ልደት የሚገኘው የጸጋ ልጅነት አይገነዘበውም፡፡ የመንፈሳዊው ሕግ ጥቅም ግን ይህ ነበር፡፡ ሥጋዊውን ከመንፈሳዊ ምድራዊውን ከሰማያዊ መለየት ያስችላል፡፡ ጌታ የኒቆዲሞስን አሳቡን፣ ልቡን፣ ስሜቱን፣ ዕውቀቱን ሁሉ ወደ ሰማያዊ ነገር እንዲያሸጋግረው ፈቀደ፡፡ ይህን በማድረግ ከሰማይ የወረደው እርሱም የሰው ልጅ በሰማይ የነበረው€ እንደሆነ ይገነዘባል፡፡ ወደ ሰማይ መውጣትም የሚቻለው እርሱ ነው፡፡ በእርሱ የሚያምኑ ወገኖችን ከፍ ከፍ የሚያደርጋቸው ከፍ ያለውንም ነገር እንዲመለከቱ የሚያደርጋቸው እርሱ ነው፡፡

የኒቆዲሞስና የጌታ ግንኙነት ትኩረታችንን ወደ ክርስቶስ እንድናደርግ ያደርገናል፡፡ ለእያንዳንዱ የሰው ልጅ ነፍስ መዳን ምን ያህል ትኩረት እንደሚሰጥ ከእያንዳንዱም ወገን ጋር ሲነጋገር ያለውን ትህትናም እንገነዘባለን፡፡ ከኒቆዲሞስ ጋር ሲወያይ የአዲሱን ልደት ጠባይ ዘርዝሯል፡፡ ኒቆዲሞስ የእግዚአብሔርን መንግሥት ማወቅ ፈልጓል፤ ይሄንን መንግሥት ለማወቅ በውኃና በመንፈስ ይጠመቅ ዘንድ ግድ መሆኑን ያስረዳል፡፡

ይህ ሁኔታ አስፈላጊ ነው፤ ክርስቲያን ዘወትር የእግዚአብሔር ልጅ ሆኖ እንዲኖር ያስችለዋልና ይጠመቅ ዘንድ የግድ ነው፤ በመንፈሱም እንዲኖር ያደርገዋል፡፡ በዚህ ምዕራፍ ጌታ ከምድራዊ ነገሮች ያወጣና አሳባችን ሰማያዊ በሆነው ጉዳይ እንዲያዝ ያደርጋል፡፡ ይህንን ማድረግ የምንችለው ከሰማያዊው ጋር ሕብረት ስንፈጥር መሆኑን ይነግረናል፡፡

ጌታ ጥምቀቱን ከመስቀሉ ጋር አያይዞታል ፡፡ እግዚአብሔር አብ ለሰው ልጆች ሁሉ ያለውን እውነተኛ ፍቅር የገለጠበት፣ የባሕርይ ልጁን ወደ ዓለም በመላክ ዓለሙ ዘላለማዊ ሕይወትን ያገኝ ዘንድ ልጁ ከፍ ከፍ ያለበትም የነገሠበትም ዙፋኑ ነውና፡፡ አዲሱን ልደትን በማንሣት ጌታ ከፍርሃት ባርነት አውጥቶ መለኮታዊ የሆነውን ብርሃን እንድንመለከት ያደርገናል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ጌታ ሲጠመቅ የነበረውን ሁኔታ ሲነግረን ለሚያምኑ ወገኖች ያለውን አንድምታም ሲገልጽ ደስታው ፍጹም ነበር፡፡ በዚህ ምዕራፍ ውስጥ

1.ስለ አዲሱ ልደት ገለጻ /1፡13/

2.አዲሱ ልደትና የመስቀሉ ሥጦታ /14-17/

3.አብርሆትና እምነት /18-21/

4.በጌታ ጥምቀት ጊዜ የዮሐንስ ሁኔታ /22-36/ ተዘርዝሯል፡፡

ስለ አዲሱ ልደት ገለጻ

ከፈሪሳውያንም ወገን የአይሁድ አለቃ የሆነ ኒቆዲሞስ የሚባል አንደ ሰው ነበረ /ቁ.1/€ ኒቆዲሞስ የአይሁድ ስም ሲሆን ትርጓሜው ሕዝብን ያሸነፈ€ ማለት ነው፡፡ የአይሁድ አካል የሰንሃድሪን አይሁድ ሸንጎም አባል ነው፡፡ መለኮታዊው ጥሪው መላውን የሰው ልጆች ያካተተ ነው፡፡ የመደብ ልዩነት አልተደረገበትም፡፡ ነገር ግን በከፍተኛ ሓላፊነት ከነበሩ የመንግሥትና የሃይማኖት መሪዎች መካከል ለዚህ ጥሪ መልስ የሰጡ ጥቂቶች ነበሩ፡፡ ከፈሪሳውያን መካከል እጅግ ጥቂቶች፤ ከጥቂቶቹ አንዱ ኒቆዲሞስ ነበር፡፡

ጌታን ሊያነጋግር የመጣው ብቻውን ነው፡፡ ምናልባት አንድ ወይም ሁለት አጃቢዎች ሳይኖሩት አይቀሩም፡፡ በአይሁድ ሸንጎ የተከበረ ሰው ነበረ፡፡ ጌታ ግን ይህችን አንዲት ለመዳን የወሰነች ነፍስ ዝቅ አላደረጋትም፤ ሞትን የተቀበለው ስለ እያንዳንዱ ነፍስ ነውና፡፡ ፈሪሳውያን ለመለኮታዊው እውነት የሰጡት መልስ ጥላቻና የዓመጽ መንፈስን የተመላ ነው፡፡ ነገር ግን ከተማሩ አይሁድ መካከል ጌታን ለማግኘት የቸኮሉ በሩም ተከፍቶ የጠበቃቸው ጥቂቶች ነበሩ፡፡ የእግዚአብሔር ጸጋ በተማሩም ባልተማሩም ወገኖች ላይ ይሠራል፡፡ በተራውም ሕዝብ፣ በአለቃውም፣ በየዋኁም፣ በዓመጸኛውም ላይ ይሠራል፡፡

ኒቆዲሞስ ደረጃው ከአመጸኞቹ ቢሆንም ወደ ጌታ መጣ፤ ጊዜው ሲደርስ የቻለውን ያህል ይጠይቅና ያውቅ ዘንድ ሞከረ፡፡ በጥያቄ ላይ እንደነበረ ታሪኩ ያስረዳል፡፡ ጊዜው ሲደርስ ለደቀ መዛሙርቱ ያልተቻለው ለዚህ ሰው ተቻለ፡፡ ከጲላጦስ አስፈቀዶ አዲስ ባሳነጸው መቃብር ላይ እንዲቀበር አደረገ፡፡

ቤን ረጊን በአይሁድ ታሪክ መጽሐፍ ስለ ኒቆዲሞስ ሲናገር ይህ ሰው በጣም ሀብታም ከመሆኑ የተነሣ በኢየሩሳሌም የነበሩ ብዙዎችን ለብዙ ዓመታት ይረዳ ነበር ይላል፡፡

እርሱም በሌሊት ወደ ኢየሱስ መጥቶ መምህር ሆይ እግዚአብሔር ከርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና መምህር ሆነህ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደ መጣህ እናውቃለን /ቁ.2/አለው፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ኒቆዲሞስን በብዙ ቦታዎች ጠርቶታል፡፡ ጌታን ማታ ማታ ይጎበኝ እንደነበረ ተገልጧል፤ ይህ ሁኔታ ሦስት ጊዜ ያህል ተጠቅሷል /ዮሐ.ዮሐ.3፡2፣ 7፡50፣ 19፡39/

ስለምን ወደ ጌታ በምሽት መጣ

1.የመጀመሪያው ምክንያት ጌታችን በአደባባይ የሚያስተምረውን ትምህርት ከሰዎች መስማቱ ብቻውን በቂ አይደለም፡፡ ከምንም በላይ ጌታ በአደባባይ የሚያደርገውን ምልክት በሕዝብ መካከል በግልጽ መጥቶ ማየት አልወደደም፡፡ ድኅነትና ነፍስን የሚመለከቱ ጉዳዮችን በጥሞና ከጌታ ሥር ቁጭ ብሎ መነጋገር ልቡ ፈቅዷል፡፡ቃሌስ በቅንነት ለሚሄድ በጎ አያደርግምን /ሚክ.2፡7/ ተብሎ እንደተጻፈ የቅንነትን መንገድ መርጦ ወደ ጌታ ቀርቧል፡፡

ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር ይነጋገር ዘንድ ወደደ፡፡ ጌታ እንኳን ከሕዝቡና ከደቀመዛሙርቱ ተለይቶ ከአብ ጋር ሲነጋገር የሚያድርበት ጊዜ ነበር፡፡ እኛማ ሌሊቱን በሙሉ ከእግዚአብሔር ጋር እንደምን መነጋገር ይገባን ይሆን፡፡ በተለይ በሌሊት ሁሉንም ነገር ትተን ከጌታ ጋር የግል ጭውውት ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡ አዲሱን ሕይወትና የዚህን ሕይወት ባህርይ፣ በዚህ ሕይወትም ውስጥ ካለች ከመንፈስ ሕብረት ተካፋዮች እንሆን ዘንድ ይገባናል፡፡

2.ሁለተኛው ምክንያት ምናልባት ጥበብን ለመማር የማታው ጊዜ የተሻለ እንደሆነ በመረዳቱ ነው፡፡ ጌታ ቀን ቀን ሕዝቡን በማስተማር ተይዞ እንደሚውል ያውቃል፡፡ ስለዚህ ኒቆዲሞስ ምሽት እስከሚመጣ ድረስ ጠበቀ፡፡ ጌታን ለማግኘትና የድኅነት ጨዋታን ይጨዋወቱ ዘንድ ወደደ፡፡

3.ሦስተኛው ምክንያት አንዳንድ ምልክቶችን ከተመለከተ በኋላ ጌታን ለማግኘት የመጀመሪያውን ዕድል በምሽት አግኝቶ ይሆናል፡፡ ሁሉም ሰው ሲተኛ ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር መንፈሳዊ የሆነች ምሽትን ማሳለፍ ፈልጎ ይሆናል፡፡ ምናልባትም እንዲህ አይነት ዕድል ወደፊት ሊገጥመው እንደማይችል ሥጋት አድሮበት ሊሆን ይችላል፡፡

4.አራተኛው እንደ ነቢዩ ዳዊት ምሳሌውን ሊከተል ፈልጎ ::ዳዊት ሌሊቱን ለምስጋና ይጠቀምበት ነበርና /መዝ.36፡6፤119፡148/

5.አምስተኛው ምናልባትም ኒቆዲሞስ ወደ ጌታ ዘንድ እየሄደ መማሩ ለካህናት አለቆች ወሬው ሊደርስ ይችላል ብሎ ከፍርሃት የተነሣ ሊሆን ይችላል፡፡

6.ስድስተኛው ኒቆዲሞስ ወደ ጌታ ዘንድ መድረሱን አይሁድ ቢያውቁ ጌታችንን ለመዋጋት ቁጣቸውን ይጨምርላቸዋል፡፡ ኒቆዲሞስን ራሱን ለመጉዳት አይሁድ ፈሪሳውያን ሊነሳሡበት ይችላሉ፡፡ ምንም እንኳን በጌታ ትምህርት የተሳበ ቢሆንም በቀን እንዳይሄድ እምነት አንሶት ሊሆን ይችላል፡፡

7.ሰባተኛው ምክንያት ከምንም በላይ ጌታ የዓለም ብርሃን መሆኑን በእርግጠኝነት አለመረዳቱ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ የአይሁድ አለቃ ነው፤ የእስራኤል መምህር ነው፡፡ ሰማያዊውን ደስታ ገንዘብ ያደርግ ዘንድ አዲስ ልደት የሚያስፈልገው ሰው ነው፡፡ በምሽት ሲመጣ ደካማ የሆነ እምነትን ይዞ ነበር የመጣው፤ ነገር ግን የጌታ በር ተከፍቶ አገኘው፡፡ ጌታ ስሜቱን ሊጎዳው አልወደደም፡፡

ሁሉ ነገር የሚቆጠረው እምነት እንደሰናፍጭ ቅንጣት ቀስ በቀስ በልቡ ውስጥ እንደሚያድግ ነበር፡፡ ጌታ የፈለገው ያች ቅንጣት አብባ፣ አፍርታ፣ ጌታ በሚሰቀልበት ጊዜ ትልቅ ዛፍ ትሆን ዘንድ ነበረ፡፡ እንደዚያ ሲሆን ነው በዚያ እምነት ደረጃ ላይ ሲደርስ ነው በድፍረት የጌታን ሥጋ የቀበረው፡፡

ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር በተገናኘ ጊዜ የአይሁድ ድካም በእርሱም ላይ ይንጸባረቅ ነበር፡፡ አስቀድመን እንዳልነው በብርሃን ሳይሆን በጨለማ የመምጣቱም ምክንያት ይህ ነበር፡፡ ነገር ግን መኃሪው አምላክ አልጠላውም፤ ትምህርቱንም አልከለከለውም፡፡ ከዚህ በተቃራኒው ጌታ በጉጉት ከእርሱ ጋር ተነጋገረ፤ ከፍ ያለውንም ምስጢር ገለጠለት፡፡ በርግጥ ለኒቆዲሞስ የተሰወረ ነበረ፡፡ ጌታ ግን አብራራለት፤ ክፉ አሳብ ከነበራቸው ወገኖች አንጻር ሲመዘን ይህ ሰው ይቅርታን ያገኝ ዘንድ እንደሚገባው ጌታ ቆጥሯልና፡፡ ክፉ ሰዎች ይቅርታ የላቸውም፡፡

ምንም እንኳን ኒቆዲሞስ ከአይሁድ የተለየ ቢሆንም ጌታን የቆጠረው ሰው አድርጎ ነው፡፡ ይናገረው የነበረው እንደ ነቢይ ነው፡፡ ያደረገውን ምልክት እያደነቀ ነበር የጠየቀው፡፡

መምህር ሆይ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን /ቁ.2/ አለው፡፡

ታዲያ ኒቆዲሞስ ሆይ ስለምን በምስጢር በምሽት መጣህ? ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣ የእግዚአብሔር የሆነውንም ነገር እንደሚናገር እያወቅህ፡፡ ስለምን ከእርሱ ጋር ነገሮችን በግልጽ አልተወያየህም? ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኒቆዲሞስን እንዲህ ዓይነት ጥያቄዎችን አልጠየቀውም፡፡ አልወቀሰውምም፡፡ ነቢዩ እንዲህ ይላል €œአይጮኸም፤ ቃሉንም አያነሣም፣ ድምፁንም በሜዳ አያሰማም፡፡ የተቀጠቀጠ ሸምበቆን አይሰብርም፣ የሚጨስንም ክር አያጠፋም€ /ኢሳ.42፡3/ ጌታ ራሱ እንዲህ ብሏል፡፡ ዓለሙን ላድን እንጂ በዓለሙ ልፈርድ አልመጣሁም፡፡ /ዮሐ.12፡47/

€œእግዚአብሔር ከርሱ ጋር ከሆነ በስተቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና /ቁ.2/

የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትሕትና ተመልከቱ! እንዲህ አላለም €œእኔ ሁሉን በራሴ ማድረግ ይቻለኛልና የማንም እርዳታ አያስፈልገኝም፡፡ እኔ ራሴ እግዚአብሔር ነኝ፡፡ የያዝኩት ኀይል የአባቴን ኀይል ነው፤ ይህንን ቢል ለሚያዳምጡት ወገኖች ከባድ በሆነ ነበር፡፡

ነገር ግን ድርጊቱን ሲፈጽም በተመሳሳይ መንገድ አልነበረም፤ ምልክትን ሲያደርግ በኀይል ነው፤ ስለዚህም እንዲህ አለ €œልትነጻ እወዳለሁ /ማቴ.8፡3/ ጣቢታ ተነሽ /ማር.5፡4/ እጅህን ዘርጋ /ማር.3፡5/ ኀጢአትህ ተሠረየችልህ /ማቴ.9፡2/ ፀጥ በል /ማር.4፡39/ አልጋህን ተሸከምና ሂድ /ማቴ.9፡6/፤ አንተ ርኩስ መንፈስ ከዚህ ሰው ውጣ /ማር.5፡8/፤ ማንም ስለምን እንዲህ ታደርጋላችሁ ቢላችሁ ለጌታ ያስፈልገዋል በሉት ማር.11፡3/፤ ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትሆናለህ /ማር.23፡43/፡፡ ለቀደሙት አትግደል እንደተባለ ሰምታችኋል የገደለም ሁሉ ፍርድ ይገባዋል እኔ ግን እላችኋለሁ በወንድሙ ላይ የሚቆጣ ሁሉ ፍርድ ይገባዋል፡፡ /ማቴ.5፡21-22/ ተከተለኝ ሰውን አጥማጅ አደርግሃለሁ /ማቴ.1፡17/፡፡

በማንኛውም ሁኔታ ታላቅ ሥልጣኑን እንመለከተዋለን፡፡ ስለዚህ ሲሠራ ማንም ወገን በርሱ ላይ ስህተትን ማግኘት አይቻለውም፡፡ ነገር ግን ሊያጠምዱበት የሚቻላቸው በአንድ መንገድ ብቻ ነው እርሱም በንግግሩ ብቻ ነው፤ ማለት ንግግሩን በተሳሳተ መንገድ በመተርጎም፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ ይላል፡-

ስለዚህ ነው ጌታ ኒቆዲሞስን በግልጥ ያናገረው፤ ነገር ግን የአብ የባሕርይ ልጅነቱን በመግለጽ አልጀመረም፤ ምልክት የሚያደርገው በተመሳሳይ ሥልጣን መሆኑን አልገለጠለትም፡፡

ኒቆዲሞስ በሥሙ ከሚያምኑ ከጌታ ጋር ግን ግንኙነት ከሌላቸው ወገኖች አንዱ ነበረ፡፡ ስለዚህ በምሽት ወደ ጌታ ዘንድ መጣ፡፡ የመጣው ወደ ብርሃን ቢሆንም በጨለማ መጣ፡፡

ምንም እንኳን ኒቆዲሞስ የመጣው ወደ ጌታ ቢሆንም የመጣው በምሽትና የሚናገረው በጨለማ ነፍሱ ነበር፡፡ ስለዚህ በሰው ሁሉ ላይ የሚያበራውን ብርሃን የሚናገረውን መልእክት ሊረዳው አልተቻለውም፡፡

ኒቆዲሞስ መምህር ነበረ ወደ እውነተኛው ብርሃን በጨለማ የመምጣቱ ምስጢርም ምናልባት ለክብሩ ተጠንቅቆ ነው፡፡ የሚናገረውን ማንነት ገና አላወቀምና፤ መማሩ እንዲያፍር አደረገው፤ በግሌ እኔ መምህርን ማዳመጥ እንጂ ሰዎች እንደመምህር ሲያዳምጡኝ አይደለም የምጠቀመው፡፡ የመጀመሪያ በመሆን ፍላጎትና ዝንባሌ ያላቸውን ወገኖች ጌታ እንዲህ ብሎ ሲገሥጻቸው አውቃለሁ፡፡ እናንተ ግን መምህር ተብላችሁ አትጠሩ መምህራችሁ አንድ ነውና /ማቴ.23፡8/

በማንኛውም ሁኔታ ኒቆዲሞስ በምሽት ወደ ጌታ የመጣው ለመጠመቅ አልነበረም ለመማርና የጌታ ደቀመዝሙርም ለመሆን አይደለም፡፡

በአይሁድ ትውፊት መሠረት ማንም ወገን በምሽት ወደ አይሁድ እምነት፣ ለመገረዝ ወይም ለመጠመቅ አይመጣም፡፡ ይህ ሕግን መተላለፍ ነው፡፡ እንደ ተማሪ ከጌታ ሥር ቁጭ ብሎ ለመማር ሳይሆን የጌታን አሳብ ለማወቅና በጎዳናውም ይጓዝ ዘንድ ነው፡፡

ለአንድ ቅዱሳት መጻሕፍትን ጠንቅቄ አውቃለሁ ለሚል የአይሁድ መምህር ረቢ ብሎ ጌታን መጥራት ቀላል ነገር አይደለም፡፡ የሕዝብ አለቃ ነኝ ብሎ የሚያስብ ሰው በትህትና ረቢ ብሎ ሲናገር መመልከት በርግጥም ያስደንቃል፡፡€œመምህር ሆይ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን/ቁ.2/ ምንም እንኳን ኒቆዲሞስ የአይሁድ መምህር ቢሆንም የተናገረው ፖለቲካ ወይም የአገር ጉዳይ አይደለም፡፡ ነፍሱ ስለምትድንበት ሁኔታ ብቻ ነው የጠየቀው፡፡

ኒቆዲሞስ ስለ ጌታ አንድ ነገር ያውቃል፤ ጌታ በአይሁድ ምሁራን ወይም በታወቀ የአይሁድ ትምህርት ቤት ገብቶ የተማረ አይደለም፡፡ ትምህርቱ ከሰማይ ነው፡፡ ጌታ የያዘው የእውነትን ኀይል እንጂ የሰይፍን ኀይል አለመሆኑን ተገነዘበ፡፡ የሰውን ጥበብ ባለፈ ፍጹም መለኮታዊ ጥበብ እንደሚናገር ተገንዝቧል፡፡ የሚያደርገው ምልክት በመለኮታዊ ኀይል መሆኑን ተገንዝቧል፡፡

በጣም አስደናቂው ንግግሩ €œእናውቃለን€ የሚለው ነው፡፡ ምናልባት ከርሱ ጋር ሌሎች ሰዎች እንዳሉ ያመለክታል፤ ወይም ፈሪሳውያንን ወክሎ እየተናገረ ይሆናል፡፡ ምክንያቱም ምግባቸውም መጠጣቸውም ወሬአቸውም ክርስቶስ ሆኗልና፡፡ ከእነርሱ መካከል ኒቆዲሞስ የሚያምነውን እምነት የሚያምኑ ፈሪሳውያን ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ከእነርሱ መካከል ጌታን በግልጥ ወይም በስውር ሊያገኘው የፈለገ ወገን የለም፡፡

ኢየሱስም መልሶ እውነት እውነት እልሃለሁ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም አለው /ቁ.3/€

ኒቆዲሞስ ምልክትን ማድረግ ለክርስቶስ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደሆነ ለማመኑ ማሣያ አድርጎ ቆጥሮ ነበር፡፡ ምክንያቱም የአይሁድ ረበናት እምነትን ምልክት ከመሥራት ጋር አያይዘውታልና፡፡ ስለ ክርስቶስ ማንነት ለመመስከር ከዚህ ወንዝ ባሻገር ያቋረጠው የለም፡፡ ስለዚህ ጌታን ዕሤተ በጎነት ያለው መምህር፣ የእግዚአብሔር ሰው አድርጎታል፡፡ እግዚአብሔር ይስሐቅን €œአትፍራ እኔ ከአንት ጋራ ነኝና /ዘፍ.26፡24/ እንዳለው ሰው ዓይነት አድርጎ ገምቶት ነበር፡፡ ወይም እንደ መበለቲቱ ልጅ ኢያሱ ከሙሴ ጋር እንደ ነበርሁ ከአንተም ጋር እሆናለሁ /ኢያ.1፡5/ ያለው ዓይነት ነቢይ ነበር ጌታ ለኒቆዲሞስ፡፡

ሌሎች ብዙ አለቆችና ነቢያት ተመሳሳይ ልምድ ነበራቸው፤ ነገር ግን ኒቆዲሞስ ምንም እምነትን ይዞ ቢመጣም ከፈሪሳውያን ጠባብ አስተሳሰብ ልጓም እንዳይወጣ የሚያደርግ አዕምሮ ነበረው፡፡ የተማረውም ይኼንን እውነታ ነው፡፡ በጌታና በኒቆዲሞስ መካከል የነበረው ውይይት የሚከተሉት ነጥቦች የትኩረት አቅጣጫዎቹ ነበሩ፡፡

1.የዳግም ልደት አስፈላጊነት እርሱም ውስጣዊው ዓለም የተሻለ እንደሆነ የሚያሳይ ነው፤ እርሱም የእግዚአብሔር መንግሥት ነው፡፡ ይህ አባባል በቅብጥ፣ በሶርያ፣ በላቲን በመጀመሪያይቱ ቤተ ክርስቲያን አባቶች ጽሑፍ የተካተተ ነው፡፡ ዮስጢኖስ፣ ቀሌምንጦስ ዘእስክንድርያ፣ ጠርጡለስ፣ አውግስጢኖስና፣ ዠሮም ለአብነት ይጠቀሳሉ፡፡ጌታችን ኒቆዲሞስን እንደገና እንዲወለድ እንደጋበዘው ተረድቷል፡፡ ይህ አስደነቀው፡፡ አሳቡ በልቡ ውስጥ መዳህ ጀምሯል፡፡ ሰው ከሸመገለ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል አለ፡፡

2.አዲሱ ልደት ከላይ ነው ሰማያዊ ነው /3/ ይህ ድርጊት በቅዱሱና በሰማያዊው የእግዚአብሔር መንፈስ ብቻ የሚፈጸም ነው፡፡ የሰውን አሳብ ሁሉ ያለፈ ስጦታ ነው፡፡

3.አዲሱ ልደት የሚፈጸመው በውኃና በመንፈስ ነው /5/

4.ይህ ልደት በኀይል ያለ በነፍስ የተመሰለ ነው፡፡ ስለዚህ ማንም ምስጢሩን ሊገነዘበው አይችለም፡፡

በአይሁድ ጽሑፍ እውነት የሚለው ቃል መደገሙ በእውነት ቅዱስ ከሚለው ጋር ተመሳሳይ ነው፤ ጌታችን የሚናገረው ነገር በጣም ጠቃሚና ትኩረት የሚያሻው መሆኑን ለመናገር ይጠቀምበታል፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱሱ ክርስቶስ በርጋታ ለኒቆዲሞስ የገለጸለት ኢየሱስ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ዘንድ መምህር መሆኑን ማመን ብቻውን በቂ አለመሆኑን፣ ተአምራቱንም ማድነቅና የተለዩ መሆናቸውን ማወቅ በራሱ ግብ አለመሆኑን ነው፡፡ በርግጥም የሚያስፈልገው እንደገና መወለድ ነው፡፡ እርሱም ሰማያዊ የሆነ ልደት ነው፡፡ ሰማያዊ መንፈሳዊ የሆኑ ጉዳዮችን ለማየት ያስችላልና፡፡ በእናቱ ማኅፀን ያለ ፅንስ በዚህ ዓለም እየሆነ ስላለው ነገር የሚያውቀው ነገር የለም፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ አንድ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት መመልከት አይቻለውም፡፡ እንደገና ከተወለደ ብቻ ነው የአዲሱን ዓለም ብርሃን መመልከት የሚችለው፡፡

ሊያይ የሚለው ጌታችን አጽንዖት ሰጥቶ የተናገረው ግሥ ለእውነተኛ ክርስቲያን አስፈላጊ ነው፡፡ አዲሱን ልደት ያጣጥም ዘንድ ስለተወለደ እንዲመካ አይደለም የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊመለከት ለመንግሥቱም እንደሚገባ ሊመላለስ ይገባዋል እንጂ፡፡

ይህ ማለት አዕምሮውና ልቡ ሰማያዊ በሆነ ነገር ላይ ማተኮር አለበት ማለት ነው፡፡ ከሰማያዊ ሕግ ጋር አብሮ የሚሄድ ሕግን ያለማወላወል ሊከተል ይገባዋል፡፡ አዲስ ግብ፣ አዲስ ተስፋ አዲስ ኀይልን ገንዘብ አድርጎ፡፡

በአዲሱ ልደት ክርስቲያን በአይነቱ የተለየ ኑሮን መኖር ይጀምራል፤ አሮጌውን የሰውነቱን ሕንፃ አፍርሶ መሠረቱ ክርስቶስ የሆነውን አዲስ ሕንፃ በማነጽ አሮጌው ሰዋችን ተወግዶ የክርስቶስን መልክ የያዘው አዲሱ ሰው ሊታይ ይገባዋል፡፡

አስቀድመን ኀጢአት ጥንተ ተፈጥሮአችንን ስላጠፋው፣ የልባችንም ጥልቅ በኀጢአት ተይዞ ስለኖረ፣ ሥጋውያን በሥጋ ሕግና ፈቃድም የምንመራ ሆነናል፡፡ የምንመራውም የመልካም ነገር ጠላት በሆነ በዲያብሎስ ነበረ፤ ስለዚህ አዲሱ ልደት ልንሸሸው የማይገባ ጠቃሚ ጉዳይ ሆኖ ቀርቧል፡፡ እውነት እውነት እልሃለሁ የሚለው የጌታ ቃል ለዚህ እውነት ማሣያ ነው፡፡

የእግዚአብሔር መንግሥት ምንድነው? ከሰማያዊው መሲሕ ሌላ መመልከት እንደሌለብን የምታሳስብ መንግሥት አይደለችምን! በእኛ መካከል መንግሥቱን መሥርቶ ይኖራል፡፡ ከእርሱ ጋር አንድነትን ፈጥረን የምናየው፣ የምንኖረው ሁሉ ለዚህ ሕይወት እንደሚገባ ነው፡፡ እርሱ ቅዱስ ስለሆነ እኛም ቅዱሳን እንሆናለን፡፡ በእኛ የሚኖረው የእግዚአብሔር መንግሥት ትክክለኛ ትርጉምም ይኼው ነው፡፡ ጌታ መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንሥሐ ግቡ /ማቴ.4፤17/ አለ፡፡ እንደገናም መንግሥተ ሰማያት በመካከላችሁ ናት /ሉቃ.17፡21/ ብሏል፡፡ በእግዚአብሔር መንግሥት ያለንን ሥፍራ ሲናገር፡፡ ጌታ መንግሥትም ለአምላኩና ለአባቱም ካህናት እንድንሆን ላደረገ /ራዕ.1፡6/ ይላል፡፡

ይህ መንግሥት ከጌታችን ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ኅብረትን የምንፈጥርበት መንግሥት በመሆኑ እንዲህ ተብሏል፡-€œየእግዚአብሔር መንግሥት ጽድቅና ሰላም በመንፈስ ቅዱስም የሆነ ደስታ ናት እንጂ መብልና መጠጥ አይደለችም€ /ሮሜ.14፡17/

ይህ መንግሥት ለዘላለማዊ ሕይወት ዋስትና ነው፡ ወደ ሰማይ እንድንጓዝ ጌታ በጌትነቱ ሲመጣ አስደናቂውን ክብር እንድንካፈል ያደርገናል፡፡ ከምንም በላይ አሳባችንን ከፍ ከፍ አድርጎ ውስጣዊ ነፍሳችንን የመጨረሻውን ቀን እንድትመለከት ጌታ ሲመጣ ሰማያዊ ዘውድን ደፍተን ያለፍርሃት በፊቱ እንቆም ዘንድ የሚያስችለንን ጸጋ እንይዝ ዘንድ ያስችለናል፡፡

የጌታን ቃል እንደገና በሌላ አባባል እንግለጠው ብንል ዳግመኛ ካልተወለድህ ከመንፈስ ጋር ኅብረት ካልፈጠርህ በጥምቀት ልጅነትን ካላገኘህ እኔን በተመለከተ ትክክለኛ የሆነውን አሳብ አታገኝም´የሚል ይሆናል፡፡

€œኒቆዲሞስም ሰው ከሸመገለ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል ሁለተኛ ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ ይወለድ ዘንድ ይችላልን? /ቁ.4/ በማለት ጠየቀ፡፡

የኒቆዲሞስ ጥያቄ የእውቀት ድካሙን ይገልጣል፡፡ ጌታ የሚናገረው በመንፈሳዊ ቋንቋ ነው፡፡ የኒቆዲሞስ ልብ ነገሮችን የሚያገናኘው ቁሳዊ ዓለማዊ ከሆኑ ነገሮች ጋር ነው፡፡ ቁሳዊ ነገሮችን ከልቡናው ከአእምሮው ካላወጣ መንፈሳዊና ሰማያዊ የሆኑ ምስጢራትን እንደምን ሊገነዘብ ይችላል? ያኔ ነው ወደ እውነት መድረስ የሚቻለው፡፡ በእግዚአብሔር መንፈስ አዲስ መንፈሳዊ ጉልበትን ይዞ ምስጢርን መረዳት የሚቻለው፡፡

ኒቆዲሞስ ጌታ በተናገረው አዲስ ልደት ተደንቋል፤ ልክ እንደ ሌሎች አይሁድ ዘመዶቹ የአብርሃም ዘር በመሆኑ የሚመካ ነው፡፡ ጌታ ደግሞ እንደገና ተወለድ እያለው ነው፤ አይሁድ ለእግዚአብሔር የተመረጡና የተወደዱ አድርገው ራሳቸውን ይቆጥሩ ነበር፡፡

በነቢያትና በተስፋው ቃል ኪዳን የተቀደሱ ሕዝቦች ነን ይሉ ነበር፡፡ ከምንም በላይ እግዚአብሔር ከእነርሱ አባቶች ጋር ቃል ኪዳን ገብቶ ነበር፡፡ ልዩ መቅደስና መሥዋዕትም ነበራቸው፡፡ ኒቆዲሞስ እስራኤላዊ ብቻ አልነበረም ፈሪሳዊም ጭምር እንጂ፡፡

ምን ዓይነት ከዚህ የበለጠ ልደት ጌታ ይሰጠኛል ብሎ ሊያስብ ይችላል? አይሁድ መሲሑ ሲመጣ የእስራኤል መንግሥት እንደሚያምንበት እንደገናም እንደሚወለዱ ይገምታሉ፡፡ ነገር ግን አስቀድሞ በነበራቸው ኩራትና ትምክህት አንጻር ሲመዝኑት ይህ የሚሆን አይመስላቸውም ነበር፡፡ እነርሱ አሁን ከያዙት የአብርሃም ልጅነት የከበረ ልደት ያለ መስሎ አይታያቸውም ነበር፡፡ ስለ ትውልድ ሀገራቸው ይመኩ ነበር፤ ስለዚህ ሌላ ልደት መስማት የሚሆንላቸው አይደለም፡፡

ይህ ሁሉ ነገር እያለ ኒቆዲሞስ ጀርባውን ለጌታ አልሰጠም፤ እርሱ የጎደለው አንድ ነገር እንዳለ አምኖ ትምህርቱን ቀጥሏል፡፡ በግብሩ ምንም እንኳን መምህርና አለቃ ቢሆንም በትሕትና እውነተኛ የሆነ ነገርን ለመማር የተዘጋጀ መሆኑን ገልጧል፡፡ ነገር ግን ጌታ የሚለው አዲስ ልደት የማይቻል እንደሆነ ገምቷል፡፡ አስደናቂ ሰው ነው፡፡ ረጅም ዘመን የትምህርትና የአመራር ልምድ ያለው ሰው ከጌታ እግር ሥር ተንበርክኮ አዲስ ነገርን ሲማር መመልከት ያስደንቃል፡፡ ለእውነተኛ አለቃ ጌታ የሰጠው ምሳሌ አስቸጋሪ ሊሆንበት ይችላል፡፡ አሁን ኒቆዲሞስ ስለ ትምህርትና ስለ አመራር ልምዱ ሲመካ አንመለከተውም፡፡ እስከመጨረሻው እስትንፋሱ ድረስ ሲማር እንጂ፡፡ አምብሮስ እንዲህ ይላል፡- የኒቆዲሞስ ሁኔታ የሚያሳየን መማር የማያስፈልገው እግዚአብሔር ብቻ መሆኑን ነው ይላል፡፡

ኒቆዲሞስ ወደ ጌታ መጣ፤ ከፍ ያሉ ነገሮችን አዳመጠ፡፡ እንዲህ ዓይነት ጉዳዮች ተራ ሰው የሚገልጣቸው አይደሉም፡፡ ማንም ሰውም ከዚህ አስቀድሞ ሰምቷቸው አያውቅም፡፡ በቅፅበት ኒቆዲሞስ ወደ ከፍታ ወጣ፤ ነገር ግን መረዳቱ ጨለማ ነበር፡፡ ነገር ግን በራሱ ማስተዋል ገና የቆመ በመሆኑ ሊሸከማቸው ስላልቻለ ወደቀ፤ የጌታን ቃል እንዴት ሊሆን ይችላል? በማለት ጠየቀ፡፡ ጌታ የተናገረውን ነገር እንዲያብራራለት ሰው ከሸመገለ በኋላ ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ ይወለድ ዘንድ ይችላልን በማለት ማብራሪያ ጠየቀ፡፡

ኒቆዲሞስ ስለ መንፈሳዊ ልደት ሰምቷል፡፡ ነገር ግን በመንፈስ አልተለማመዳቸውም /አያውቀውም/፡፡ኒቆዲሞስ ትውክልቱን ያደረገው ቁሳዊ መረጃ ላይ ነው ፤ይህንን ትልቅ ትርጉም ለመረዳትና ለመተርጎም ምሳሌ አድርጎ ያቀረበው የሰውን የሥጋ ልደት ነው፡፡ ይህንን ሁኔታ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ በማለት ይገልጠዋል €œለፍጥረታዊ ሰው የእግዚአብሔር መንፈስ ነገር ሞኝነት ነውና አይቀበለውም በመንፈስም የሚመረመር ስለሆነ ሊያውቀው አይችልም€ /1ቆ.2·14/

በዚህ ሁሉ ነገር ኒቆዲሞስ ክብርና ጉጉት ይታይበታል፡፡ ጌታ የነገረው ነገር አላስቆጣውም፡፡ ነገር ግን ይህ ሁኔታ የማይቻል መሆኑን አስቦ ጥያቄ ጠይቆ ዝም አለ፡፡ ሁለት ነገሮችን ተጠራጥሯል፡፡ ምን አይነት እንደገና መወለድ እና የእግዚአብሔር መንግሥት፡፡ አይሁድ በየትኛውም ጊዜ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት የተናገሩት ነገር የለም፡፡ ስለ ዳግም ልደትም እንዲሁ፡፡ ስለነዚህ ነገሮች ሰምተውም አያውቁም፡፡ ኒቆዲሞስን ያስደነቀውም ነገር ይህ ነው፡፡

ቅዱስ አውግስጢኖስ እንዲህ ይላል፡- ይህ ሰው ከአዳምና ከሔዋን የሚደረግ ልደትን ሰምቷል፤ ከእግዚአብሔርና ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስለሚደረገው ልደት ግን አያውቅም፡የሚያውቀው ዘርን የሚተኩ ወላጆች በሞት ፍጻሜያቸውን እንደሚያገኙ ነው፡፡ ነገር ግን ሕይወትን ስለሚሰጠው ስለ አዲሱ ልደት ያለው ግንዛቤ ከመረዳት በታች ነው፡፡ ንብረታቸውን የሚወርሱ ልጆችን የሚወልዱ ቤተሰቦች ያውቃል፡፡ ነገር ግን ዘወትር የሚኖሩ ልጆችን የሚወልዱ የማይሞቱ ወላጆችን በተመለከተ እውቀት የለውም፡፡ ሁለት ዓይነት መወለድ አለ፡፡ አንደኛው በምድር የሚደረግ ሁለተኛው ሰማያዊ፡፡ የመጀመሪያው ከሥጋና ከደም ሁለተኛው ከውኃና ከመንፈስ፤ የመጀመሪያዎቹ ለሞት የተጋለጡ ናቸው የኋለኞቹ ዘላለማውያን ናቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ የተወለዱት ከወንድና ከሴት የኋለኞቹ ከእግዚአብሔርና ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ ኒቆዲሞስን በተመለከተ የሚያውቀው አንድ ልደትን ብቻ ነው፡፡

ኢየሱስም መለሰ እንዲህ ሲል እውነት እውነት እልሃለሁ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡ /5/

ጌታ ይህንን እውነት ዝቅ አድርጎ እንዳይመለከተው በማሰብ አስቀድሞ የተናገረውን ነገር ደገመለት ፡፡ በርግጥ የእግዚአብሔር ቃል አዎ አይደለም ከሚለው አፍአዊ ነገር በዘለለ መልስን የሚጠይቅ ነው፡፡ ምንም እንኳን ኒቆዲሞስ ከመረዳት አቅሙ በላይ ቢሆንም ጌታ እንደገና መወለድ ትምህርቱ ላይ ጠንከር ብሎ ሄዷል፤ ያለዚህ ልደት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየትም ለመግባትም የሚያስችል መንገድ የለም፡፡

ሰው ከውኃና ከመንፈስ መወለድ አለበት ይላል፤ ስለምን ውኃን ይጠቀማል? ውስጣዊ የመንፈስ መታጠብን ለማመልከት ነው፡፡ /ቲቶ.3፡5፣ 1ቆሮ.6፡11፣ ሕዝ.36፡25/ €œ

ይህ ውስጣዊ የመንፈስ መታጠብ በመንፈስ ቅዱስ የሚፈጸም ነው፡፡ እርሱ ብቻ ያጥባል ያነጻል ውስጣዊ ልባችንን አዲስ ያደርጋል፡፡ ጌታ በሰርግ ቤት ተገኝቶ ውኃውን ወደ ወይን በመቀየር በሰርጉ ቤት ለነበሩ ዕድምተኞች ደስታን እንደሰጠ በመንፈሱ የሰጠው ውጫዊ የሰውነት መታጠብ አይደለም፡፡

ይህ ውኃ ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣ ይጠጣ በማለት ለሳምራዊቷ ሴት የነገራት የሕይወት ውኃ ነው፡፡ በያዕቆብ ጉድጓድ ውስጥ እንዳለው ውኃ አይነት አይደለም ያዕቆብ፣ ልጆቹና፣ ከብቶቹ የጠጡት ውኃ የሚያረካው የሥጋን ጥማት ነው፡፡ ጌታችን የሚሰጠን ውኃ ግን የነፍስን ጥማት የሚያረካ ነው፡፡

በአዲሱ ልደት ውኃ አስፈላጊ ሆኗል፤ ጥምቀት የሚፈጸመው በመዘፈቅ ነውና፡፡ ይህም ሞትን የመቀበልና ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር የመቀበር ምልክት ነው፡፡ ከእርሱ ጋር እንነሣ ዘንድ የግድ ያስፈልገናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፡-

እንግዲህ ክርስቶስ በአብ ክብር ከሙታን እንደተነሣ እንዲሁ እኛም በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ፣ ከሞቱ ጋር አንድ እንሆን ዘንድ በጥምቀት ከእርሱ ጋር ተቀበርን€

ከውኃና ከመንፈስ መወለድ የአሮጌውን ሰው መሞትና የአዲሱን ሰው ትንሣኤ ይጠይቃል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ የሆነውን አዲስ ሕይወትም መቀበል ነው፡፡ እርሱም የትንሣኤ መንፈስ ነው፡፡ ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር የሚያደርገንን አዲሱን ሰው የመፍጠር ሂደት ነው፡፡ በፈጣሪያችን መልክ የተፈጠረውን አዲስ ሰው መመልከት ነው፡፡

በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አምነው መስቀሉን ሊሸከሙ የሚወዱ ወገኖች በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም መጠመቅ አለባቸው፡፡ የጌታ ቃል ትርጉም ለኒቆዲሞስ ምንድነው ብላችሁ ብትጠይቁኝ መልሴ የሚሆነው ጌታ ከሥጋ ትውልድ ወጣ ብሎ መንፈሳዊውን ትውልድ እንዲያስብ ሳበው የሚል ይሆናል፡፡

ጌታ እንዲህ በማለት የነገረው ይመስላል፡፡ ኒቆዲሞስ ሆይ እየተናገርሁህ ያለሁት ስለ ሌላ ልደት ነው፡፡ ስለምን ነው ንግግሬን ወደ ምድራዊ ነገር የምታወርደው፡፡ ስለምን የምነግርህ ነገር በተፈጥሮ ሕግ እንዲገዛ ታደርጋለህ? ይህ ትውልድ /ልደት/ በአይነት በሥጋ /በምጥ/ ከሚደረገው ትውልድ የተለየ ነው፡፡ አጠቃላይና የተለመደ ከሆነ ልደት ራስህን አውጣ፤ እኔ ሌላ ልደት ወደሚገኝበት መንፈሳዊ ዓለም ሾሜሃለሁና፡፡ ሰዎች ሁሉ ከዚህ አዲስ ልደት እንዲወለዱ እወዳለሁ፡፡ አዲስ ዓይነት ልደትን ይዤ ወደ ምድር መጥቻለሁ፡፡ ሰውን የፈጠርሁት ከምድር አፈርና ከውኃ ነበር፡፡ ይህ ያገለግለኛል ብዬ የፈጠርሁት ምርጥ ዕቃ የተፈጠረበትን ዓላማ ዘንግቶ አግኝቸዋለሁና እንደገና ከአፈርና ከውኃ ልሠራው አልፈቅድም እንደገና በውኃና በመንፈስ እንዲወለድ እፈቅዳለሁ እንጂ፡፡

ምናልባት ከመካከላችሁ አንዱ እግዚአብሔር ሰውን እንዴት ከውኃ ፈጠረው ብሎ ሊጠይቅ ይችላል፡፡ እኔ መልሼ እጠይቀዋለሁ፡፡ ሰውን እንዴት ከምድር አፈር አበጀው? ጭቃን እንደምን አድርጋችሁ ወደተለያየ ክፍል ትከፋፍሉታላችሁ? አጥንት፣ ነርብ፣ የደም ሥር፣ የደም ቧንቧ ከየት ተሠሩ? ቆዳ፣ ደም፣ ጉበት ከየት ተሠሩ? ይህ ታላቅ ሥራ ለምን የተከናወነ ይመስላችኋል? የተለያየውስ ቀለም? እነዚህ ሁሉ አይነቶች ውሁዶች ከየት ተገኙ? እነዚህ ሁሉ ነገሮች የምድርም የጭቃም አካል አይደሉምና፡፡

ምድር ዘርን ስትቀበል እንዴት አድርገው ሥር ይሰድዳሉ? ነገር ግን በእኛ አካል ውስጥ ሲሆኑ እነዚህ ዘሮች ይፈጫሉ፡፡ ምድር ዘርን ምን መግባ ዘር ፍሬ እንዲያፈራ ታደርጋለች? እንደገናስ ሰውነታችን እንዴት በእነዚህ ዘሮች ይገነባል? ምድር ውኃን ትቀበላለች ወደሚያፈራ ወይንም ትቀይረዋለች፡፡ የእኛ ሰውነት ግን ወይንን ተቀብሎ ወደ ውኃ ይቀይረዋል፡፡ በአሳብ የምትሰጠው ፍሬ ሁሉ የእርሷ ውጤት መሆኑን በምን በምን በምን መንገድ ነው የሚለውን ግን ማስረዳት ቀላል ነገር አይደለም፡፡ ምድር በፍሬዋ ሰውነታችንን ታጠግባለች፤ በእግዚአብሔር ላይ ያለኝ እምነት ብቻ ነው እነዚህ ሁሉ ነገሮች የምድር ውጤቶች ናቸው ብዬ እንድቀበል የሚያደርገኝ፡፡

አሁን እነዚህ ሁሉ ዓይነት ተጨባጭ ነገሮች በየቀኑ የሚከሰቱ ስለሆነ እምነት የሚይጠይቁ ስለሆነ መንፈሳዊ የሆነው ጉዳይ በቂ የሆነ ትኩረትና ቅድምና ማግኘት እንደሚኖርበት ትገነዘባላችሁ፡፡ የማይንቀሳቀሰው ምድር ለእግዚአብሔር ፈቃድ መልስ ይሰጣል ምድር የምትሸከመው ይህ ሁሉ ነገር የተገኘው ለዚህ ፈቃድ ነውና፤ በተመሳሳይ ሁኔታ ከመረዳታችን በላይ የሆነ ጽንፍ የያዘ ብዙ ምልክት ይፈጠራል፤ መንፈስ ቅዱስ በውኃ ላይ በኖረ ጊዜ ምን ተከሰተ?

ምናልባት ከመካከላችሁ አንዱ ውኃ ለዚህ ልደት ለምን ያስፈልጋል? ብሎ ቢጠይቀኝ መልሴ የሚሆነው ይህ ልደት አምላካዊ ጠቀሜታ አለው የሚል ነው፡፡ መቃብር፣ መቀበር እምነት፣ ሕይወትና፣ ትንሣኤ እነዚህ ሁሉ ምሥጢራት በጥምቀት ጊዜ የሚከናወኑ ናቸው፡፡ጭንቅላታችንን ውኃ ውስጥ እንነክራለን፤ ወደመቃብር እንደምንወርድ ሁሉ አሮጌውን ሰዋችን እንቀብር ዘንድ ጭንቅላታችንን ስናነሣ አዲሱ ሰው በተመሳሳይ ሁኔታ ይገኛል፡፡

ከመንፈስ የሚወለድ እርሱ ማነው €œእንደሚያታልል ምኞት የሚጠፋውን አሮጌውን ሰው አስወግዶ በአእምሮው መንፈስ ከሚታደስ ሰው በስተቀር€ /ኤፌ.4፡23/ በእርግጥ ይህ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ እንደገና የተወለደ ሰው ነው፡፡

ይህ በዘላለማዊ ሕይወት የመተማመን ውጤት ነው፡፡ ይህም በጥምቀት አማካኝነት የሚፈጸም ነው፡፡ በእርግጥም እንዲህ ዓይነት ሰው እንደምሕረቱ መጠን በአዲስ ልደት በሚሆነው መታጠብም በመንፈስ ቅዱስ በመታደስ /ቲቶ.3፡5/ መንፈሳዊ ልጅነትን የተቀበለ ነው፡፡ በሌላ ንባብ ቅዱስ ጴጥሮስ እንዲህ ይላል €œበመንፈስ ቅዱስ ስም ትጠመቃላችሁ€ /ሥራ.11፡16/፡፡ ከውኃና ከመንፈስ ከተወለደ ወገን ውጭ በመንፈስ ቅዱስ የተጠመቀ ማነው? እውነት እውነት እላችኋለሁ ከውኃና ከመንፈስ ከተወለደ ወገን ውጭ በመንፈስ ቅድስ የተጠመቀ ማነው? እውነት እውነት እላችኋለሁ ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለዳችሁ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት አይቻላችሁም፡፡

የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ በተጠመቀ ሰው ላይ ያደረ መንፈስ ቅዱስ የሚናገረውን ምስጢር ይናገራል፡፡ ጥምቀት €œለአዲስ ልደት የሚሆን መታጠብ /ቲቶ.3፡5/ ተብሏል በመንፈስ ቅዱስ የሚሆን መታደስ ነው፡፡

በምስጢረ ጥምቀት የኀጢአት እሥራት ይፈታል ስለዚህ ምክንያት ሕፃናት ሳይቀሩ ይጠመቃሉ፡፡€

€œሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ይገባ ዘንድ አይቻለውምና፡፡

ጥምቀት ኀጢአታችን ሁሉ ያጥባል፡፡ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ መቅደስ እንድንሆን ያደርገናል፡፡ ሰማያዊ ተፈጥሮአችንን ያድሳል ይህም በመንፈስ ቅዱስ ግብር የሚፈጸም ነው፡፡

በቅዱስ ጥምቀት ሰው ከሰይጣን ኀይል ነጻ ይሆናል፤ እንደ አርባ ቀን ሕፃንም ይሆናል፡፡ ይህም በመንፈስ ቅዱስ የሚከናወን ነው፡፡ የተጠመቀውን ሰው የሚቀድስና የሚያነጻ መንፈስ ነው፡፡ በእንደዚህ ዓይነት ሰው ላይ ሰይጣን የወደደውን ያደርግበት ዘንድ አቅሙ አይኖረውም፡፡

ሰው በጥምቀት ከክርስቶስ ጋር አንድነትን ሲፈጥር እንደገና ከመወለዱ ባሻገር ክርስቶስን በሁለንተናው ይለብሰዋል /ገላ.3፡27/ ይህን በንባብ ብቻ የምንረዳው አይደለም፡፡የፍቅር መግለጫ ነውና፡፡ይህንን የምንረዳው ጌታ ሥጋችንን ተዋሕዶ በእኛ መጠን መወለዱና ስለእኛም ሲል ለአብነት በመወለዱ ነው፡፡

002 olonkomi

የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ቅድመ ዝግጅት በኦሎንኮሚ ደብረ ብስራት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን

â€Â¢ መርሐ ግብሩ በማኅበሩ ድረ ገጽ ከጠዋቱ 3:00 ሰዓት ጀምሮ በቀጥታ ይተላለፋል፡፡

መጋቢት 11 ቀን 2007 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

002 olonkomiማኅበረ ቅዱሳን መጋቢት 13 ቀን 2007 ዓ.ም. በምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት በደንዲ ወረዳ ቤተ ክህነት ኦሎንኮሚ ደብረ ብስራት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የሚካሔደው የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ቅድመ ዝግጅት በመጠናቀቅ ላይ ነው፡፡

አዘጋጅ ኮሚቴው ከቤተ ክርስቲያኑ ሰበካ ጉባኤና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት በመሥራት መርሐ ግብሩን የተሳካ ለማድረግ በእንቅስቃሴ ላይ ይገኛል፡፡ ኮሚቴው ወደ ስፍራው በመጓዝም ክንውኑን ገምግሟል፡፡

 

የድንኳን ተከላው እየተፋጠነ ሲሆን፤ ጊዜያዊ የመጸዳጃ ቤቶች ዝግጅት ሙሉ ለሙሉ መጠናቀቁን አረጋግጧል፡፡ የተግባር ቤት፤ የመኪና ማቆሚያ፤ የምግብ መስተንግዶ ስፍራዎች ተለይተዋል፡፡ በምእመናን አቀባበል ሁኔታም ዝግጅቶችን በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡

የማኅበሩ ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ክፍል በማኅበሩ ድረ ገጽ ላይ የቀጥታ ሥርጭት ለማድረግ ባለሙያዎችን ስፍራው ድረስ በመላክ ማስተላለፍ እንደሚችል ሙከራ አድረጎ ተመልሷል፡፡ በዚህም መሠረት በእለቱ ከጠዋቱ 3:00 ሰዓት ጀምሮ መርሐ ግብሩን በቀጥታ ያስተላልፋል፡፡

001 olonkomiየኦሎንኮሚ ደብረ ብስራት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በ1907 ዓ.ም. የተተከለ ሲሆን፤ 100ኛ ዓመቱን ጥር 16 እና 17 ቀን 2007 ዓ.ም. በድምቀት አክብሯል፡፡ ታቦቱም በ1906 ዓ.ም. ከወሎ ክፍለ ሀገር ወረኢሉ እንደመጣ፤ አሁን ባለበት ቦታ ላይ ከመተከሉ በፊት በኤጄርሳ ለፎ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ለአንድ ኣመት በደባልነት ቆይቷል፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ የተተከለው በከፍታ ቦታ ላይ በመሆኑ ቀድሞ የአካባቢው ልጆች በየዓመቱ የደብረ ታቦርን በዓል ያከብሩበት ነበር፡፡ ቦታውም “የልጆች ተራራ” እየተባለ ሲጠራ ቆይቷል፡፡

በአሰቦት ገዳም ደን ተቀስቅሶ የነበረው እሳት ሙሉ ለሙሉ ጠፍቷል

መጋቢት 11 ቀን 2007 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በአሰቦት ገዳም ደን ላይ ተቀስቅሶ የነበረው እሳት ሙሉ ሙሉ መጥፋቱን ከገዳሙ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

ማኅበረ መነኮሳቱ፤ የፌደራል ፖሊስ አባላት እና ምእመናን ባደረጉት ከፍተኛ ጥረት በአሁኑ ስዓት ሙሉ ለሙሉ ለማጥፋት በመቻሉ በገዳሙ ውስጥ ማኅበረ መነኮሳቱ የተለመደውን አገልግሎታቸውን ቀጥለዋል፡፡ 

beg madleb 02

የመምህር አካለ ወልድ የሐዲስ ኪዳን የመጻሕፍት ትርጓሜ ት/ቤት የበግ ማድለብ ፕሮጀክት ተግባራዊ ሊደረግ ነው

መጋቢት 9 ቀን 2007 ዓ.ም

ከደሴ ማእከል

beg madleb 02የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ከ20 በላይ የወረዳ ቤተ ክህነት ሲኖሩት፤ እነዚህም ብዛት ያላቸው ጥንታውያን ገዳማትና አድባራትን እንዲሁም የአብነት ት/ቤቶችን አቅፎ የያዘ ነው፡፡ ሀገረ ስብከቱ ካሉት ጥንታውያን የአብነት ት/ቤቶች የቦሩ ሥላሴ የመምህር አካለ ወልድ የሐዲስ ኪዳን የመጻሕፍት ትርጓሜ ት/ቤት አንዱ ነው፡፡

ት/ቤቱ በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት በደሴ ወረዳ ቤተ ክህነት ቦሩ በሚባል ቀበሌ በቦሩ ደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚገኝ ሲሆን፤ ከደሴ የ10 ኪ.ሜ መንገድ ነው፡፡ ይህ ትምህርት ቤት በ18ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጨረሻ የቀለም ቀንድ ተብለው በሚጠሩት በዐራት ዓይናው በመ/ር አካለ ወልድ የተቋቋመ ለሀገርና ለቤተ ክርስቲያን የጠቀሙ ሊቃውንትን ሲያፈራ የነበረ ነው፡፡

በአሁኑ ወቅት 16 የሚደርሱ የሐዲሳት ትርጓሜ መጻሕፍት ተማሪዎችን ተቀብሎ በሀገረ ስብከቱ፣ በማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል እና በጎ አድራጊ ምእመናን ድጋፍ እየተደረገላቸው እያስተማረ ይገኛል፡፡ ት/ቤቱ በአቅም ማነስና ተያያዥ ችግሮች ምክንያት ለብዙ ዓመታት ተዘግቶ የነበረ ሲሆን፤ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ቀናኢ በሆኑት በብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከፍተኛ ጥረት ካለፉት 9 ዓመታት ወዲህ እንደገና ተከፍቶ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መፋጠን የሚያግዙ ተተኪ አገልጋዮችን እያፈራ ይገኛል፡፡

beg madlebት/ቤቱ ቀድሞ ለብዙ ዓመታት እንዲዘጋ ያደረገውና አሁንም አገልግሎቱን እየተፈታተነው ያለውን መሠረታዊ የኢኮኖሚ ችግር ቀርፎ የተማሪዎችን ቁጥር እና የጉባኤያቱን ዓይነት በመጨመር ለቤተ ክርስቲያን ተተኪ አገልጋዮችን በማፍራት ሐዋርያዊ አገልግሎትን ለማጠናከር ይቻል ዘንድ በማኅበረ ቅዱሳን የደሴ ማእከል የቅዱሳት መካናት ማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ክፍል ከበጎ አድራጊዎች በተገኘ ድጋፍ የበግ ማድለብ ፕሮጀክት ቀርጾ ከደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ጋር የፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የውል ሰነድ መጋቢት 3 ቀን 2007 ዓ.ም ተፈራርሟል፡፡

በእለቱ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መምህር ቆሞስ አባ ገብረ ሥላሴ በላይ እና የሀገረ ስብከቱ ሰራተኞች የተገኙ ሲሆን፤ ገንቢና ስጋት ሊሆኑ የሚችሉ ሀሳቦች ተነስተው ውይይት ከተደረገባቸው በኋላ ከሀገረ ስብከት፣ ከማኅበረ ቅዱሳን ደሴ ማእከል፣ ከት/ቤቱ፣ ከደብሩ ሰበካ ጉባኤና ከምእመናን የተውጣጡ ስድስት አባላት ያሉት ኮሚቴ ተቋቋሟል፡፡

በአሁኑ ወቅት የመገልገያ ቁሳቁሶች ተገዝተው የበጎች ማድለቢያና ማቆያ ቤት መሠራቱን የደሴ ማእከል ጸሐፊ ዲ/ን ሰለሞን ወልዴ በውይይቱ ወቅት ገልጸዋል፡፡

እንደ ጸሐፊው ገለጻ የፕሮጀክቱ ሙሉ ሥራ በሁለት ዙር የሚጠናቀቅ ሲሆን የመጀመሪያውን ዙር ቀሪ ሥራዎች በአጭር ቀናት ውስጥ በማጠናቀቅ የበግ ማድለቡ ሥራ እንዲጀመር ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡የፕሮጀክቱን የመጀመሪያ ዙር ሥራ አጠናቆ አገልግሎት ለማስጀመርም ብር 135,993 /አንድ መቶ ሰላሳ አምስት ሺህ ዘጠኝ መቶ ዘጠና ሶስት/ ብር እንደሚያስፈልግ ለማወቅ ተችሏል፡፡

abune gm 003

በዝቋላ ገዳም የተቀሰቀሰው እሳት ለማዳፈን ጥረት እየተደረገ ነው

የካቲት 26 ቀን 2007 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

abune gm 003ከማክሰኞ የካቲት 24 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ በዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም የተቀሰቀሰው እሳት በትናንትናው እለት ተባብሶ የነበረ ቢሆንም ወደ ሌላ ቦታ ሳይዛመት ከሸለቆው ውስጥ ለማዳፈን ጥረት የተደረገ መሆኑን የገዳሙ አበምኔት አባ ገብረ ማርያም ዛሬ ጠዋት በስልክ ገልጸዋል፡፡

በሸለቆው ውስጥ የተዛመተው እሳት ማኅበረ መነኮሳቱ፤ ምእመናንና የፖሊስ ኃይል ባደረጉት ርብርብ ከሸለቆው ሳይወጣ ለማቆም ተችሏል፡፡ ነገር ግን ከተዳፈነው እሳት ከፍተኛ ጭስ እየወጣ በመሆኑ እሳቱ እንዳይቀጣጠል ጥረት በማደረግ ላይ እንደሚገኙም አበምኔቱ ገልጸዋል፡፡

በገዳሙ ደን ላይ ለተከሰተው እሳት ቃጠሎ መንስኤ ከሰል በማክሰል ላይ በነበረ አንድ ግለሰብ እንደሆነ ከገዳሙ ያገኘነው መረጃ አመልክቷል፡፡

ግለሰቡ በድብቅ ከሰል በማክሰል ላይ ሳለ እሳቱ ከቁጥጥሩ ውጪ በመሆኑ ሲገለገልበት የነበረውን አካፋና ሹራብ ጥሎ እንደተሰወረ ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡

የካቲት 25 ቀን 2007 ዓ.ም. የእሳቱን መንስኤ ለመጣራት በወንበር ቀበሌ ጽ/ቤት ከወረዳና ከዞን ከመጡ የፖሊስ ባለሥልጣናት ጋር በተደረገ ውይይት የግለሰቡ ማንነት ታውቋል ሲሉ በስብሰባው የተሳተፉ መነኮሳት ገልጸዋል፡፡ ፖሊስ ግለሰቡን ለመያዝ ክትትል እያደረገ ሲሆን፤ እሳቱ ዳግም እንዳይነሳም ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፤፤

 

ምኩራብ(የዐቢይ ጾም ሦስተኛ ሳምንት)

የካቲት 20 ቀን 2007 ዓ.ም.

የዕለተ ሰንበት መዝሙር (ከጾመ ድጓ)

ቦአ ኢየሱስ ምኩራበ አይሁድ ወመሐረ ቃለ ሃይማኖት ወይቤሎሙ ምጽዋተ አበድር እመሥዋዕት አነ ውእቱ እግዚኣ ለሰንበት ወአቡሃ ለምሕረት እግዚኣ ውእቱ ለሰንበት ወልደ እጓለ እመሕያው ኢትግበሩ ቤተ አቡየ ቤተ ምስያጥ ቤትየሰ ቤተ ጸሎት ይሰመይ ቦአ ምኩራቦሙ ወገሠፆሙ ያርምሙ አንከሩ ምህሮቶ ሞገስ ቃሉ ወጣዕመ ነገሩ ወሣዕሣዓ አፉሁ፡፡

 

ትርጉም:- ጌታችን ኢየሱስ ወደ አይሁድ ምኩራብ ገባ፤ የሃይማኖት ቃልን አስተማረ፤ ከመሥዋዕት ይልቅ ምሕረትን እወዳለሁ፤የሰንበት ጌታዋ የምሕረት አባቷም እኔ ነኝ፤ የሰው ልጅም የሰንበት ጌታዋ ነው ፡፡ያባቴን ቤት የንግድ ቦታ አታድርጉት፤ቤቴስ የጸሎት ቤት ይባላል (እያለ የሃይማኖትን ቃል አስተማራቸው፡)፡ ወደ ምኩራባቸውም ገብቶ ዝም ይሉ ዘንድ ገሠፃቸው፤ እነርሱም ትምህርቱን፣ የቃሉን ግርማ፣ የአነጋገሩን ጣዕምና፣ የአንደበቱን ቅልጥፍና አደነቁ።

 

ምንባባት

መልዕክታት

(ቆላ. 2÷16-ፍጻ.)፡- እንግዲህ በመብልም ቢሆን÷ በመጠጥም ቢሆን÷ በልዩ ልዩ በዓላትም ቢሆን÷ በመባቻም ቢሆን÷ በሰንበትም ቢሆን የሚነቅፋችሁ እንዳይኖር ተጠንቀቁ፡፡ ይህ ሁሉ ይመጣ ዘንድ ላለው ጥላ ነውና። አካሉ ግን የክርስቶስ ነው፡፡ በመታለልና ራስን ዝቅ በማድረግ ለመላእክት አምልኮ ትታዘዙ ዘንድ ወድዶ÷ በአላየውም በከንቱ የሥጋው ምክር እየተመካ የሚያሰንፋችሁ አይኑር፡፡ ሥጋ ሁሉ ጸንቶ በሚኖርበት÷ በሥርና በጅማትም በሚስማማበት÷ በእግዚአብሔርም በሚያድግበትና በሚጸናበት በሚሞላበትም በራስ አይጸናም፡፡

 

ከዚህ ዓለም ኑሮ ከክርሰቶስ ጋር ከሞታችሁ እንደገና በዓለም እንደሚኖሩ ሰዎች እንዴት ትሠራላችሁ? እንዴትስ ይህን አትዳስስ÷ ይህን አትንካ÷ ይህንም አትቅመስ ይሉአችኋል? ይህ ሁሉ እንደ ሰው ትእዛዝና ትምህርት ለጥፋት ነውና፡፡ ይህም ስለ ልብ ትሕትናና እግዚአብሔርንም ስለ መፍራት÷ ለሥጋም ስለ አለማዘን ጥበብን ይመስላል፤ ነገር ግን ከሥጋ በላይ ነው እንጂ ምንም ክብር የለውም፡፡

(ያዕ. 2÷14-ፍጻ.)፡- ወንድሞቻችን ሆይ÷ እምነት አለኝ፤ ምግባር ግን የለኝም የሚል ሰው ቢኖር÷ ምን ይጠቅመዋል? በውኑ እምነቱ ልታድነው ትችላለችን? ከወንድሞቻችን÷ ወይም ከእኅቶቻችን÷ የታረዙ ወይም የዕለት ምግብ ያጡ ቢኖሩ÷ ከእናንተም አንዱ÷ “በሰላም ሂዱ÷ እሳት ሙቁ÷ ትጠግባላችሁም” ቢላቸው÷ ለችግራቸውም የሚሹትን ባይሰጣቸው ምን ይጠቅማቸዋል? እንዲሁም ሥራ የሌለው እምነት ቢኖር በራሱ የሞተ ነው፡፡

 

ነገር ግን አንድ ሰው÷ “አንተ እምነት አለህ÷ እኔም መልካም ሥራ አለኝ፤ እስቲ ሃይማኖትህን ከሥራህ ለይተህ አሳየኝ፤ እኔም እምነቴን በሥራዬ አሳይሃለሁ” ይላል፡፡ አንተም እግዚአብሔር አንድ እንደ ሆነ ታምናለህ፤ መልካምም ታደርጋለህ፤ እንዲህስ አጋንንትም ያምናሉ፤ ይንቀጠቀጣሉም፡፡ አንተ ሰነፍ ሰው÷ እምነት ያለ ምግባር የሞተች እንደ ሆነች ልታውቅ ትወዳለህን? አባታችን አብርሃም ልጁን ይስሐቅን ወደ መሠዊያው ባቀረበው ጊዜ÷ በሥራው የጸደቀ አይደለምን? እምነት ለሥራ ትረዳው እንደ ነበር÷ በሥራውም እምነቱ እንደ መላችና ፍጽምት እንደ ሆነችም ታያለህን?

 

መጽሐፍ÷ “አብርሃም በእግዚአብሔር አመነ፤ ጽድቅ ሆኖም ተቈጠረለት” የሚለው ተፈጸመ፤ የእግዚአብሔርም ወዳጅ ተባለ፡፡ ሰው በሥራ እንደሚጸድቅ በእምነት ብቻም እንዳይደለ ታያለህን? እንዲሁ ዘማይቱ ረአብ ደግሞ ጒበኞችን ተቀብላ÷ በሌላ መንገድ ባወጣቻቸው ጊዜ በሥራ አልጸደቀችምን? ከነፍስ የተለየ ሥጋ የሞተ እንደ ሆነ÷ እንዲሁ ደግሞ ከሥራ የተለየ እምነት የሞተ ነው፡፡

 

ግብረ ሐዋርያት

(የሐዋ.10÷1-8)፡- በቂሳርያም ቆርኔሌዎስ የሚባል አንድ ሰው ነበር፤ ኢጣሊቄ ለሚሉት ጭፍራም የመቶ አለቃ ነበር፡፡ እርሱም ጻድቅና ከነቤተሰቡ እግዚአብሔርን የሚፈራ ነበር፤ ለሕዝቡም ብዙ ምጽዋት ይሰጥ ነበር፤ ዘወትርም ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ ነበር፡፡ የእግዚአብሔር መልአክም በራእይ ከቀኑ በዘጠኝ ሰዓት በግልጥ ታየው፤ ወደ እርሱም ገብቶ÷ “ቆርኔሌዎስ ሆይ÷” አለው፡፡ ወደ እርሱም ተመልክቶ ፈራና÷ “አቤቱ÷ ምንድን ነው?” አለ፤ መልአኩም እንዲህ አለው÷ “ጸሎትህም ምጽዋትህም መልካም መታሰቢያ ሆኖ ወደ እግዚአብሔር ዐርጎአል፡፡ አሁንም ጴጥሮስ የሚባለውን ስምዖንን ይጠሩልህ ዘንድ ወደ ኢዮጴ ከተማ ሰዎችን ላክ፡፡ እርሱም ቤቱ በባሕር አጠገብ ባለው በቊርበት ፋቂው በስምዖን ቤት እንግድነት ተቀምጦአል፡፡ልታደርገው የሚገባህን እርሱ ይነግርሃል፡፡” ያነጋገረውም መልአክ ከሄደ በኋላ ከሎሌዎቹ ሁለት÷ ከማይለዩት ጭፍሮቹም አንድ ደግ ወታደር ጠራ፡፡

 

ምስባክ

መዝ.68፡9፡- እስመ ቅንዐተ ቤትከ በልዐኒ፤ ትዕይርቶሙ ለእለይትዔየሩከ ወድቀ ላዕሌየ፤ ወቀጻዕክዋ በጾም ለነፍስየ፡፡

ትርጉም፦ የቤትህ ቅንዓት በልታኛለችና የሚሰድቡህም ስድብ በላዬ ወድቆአልና ነፍሴን በጾም አስመረርኋት፡፡

 

ወንጌል

(ዮሐ. 2÷12-ፍጻ.)፡- ከዚህም በኋላ እርሱና እናቱ÷ ወንድሞቹና ደቀ መዛሙርቱም ወደ ቅፍርናሆም ወረዱ፤ በዚያም ብዙ ያይደለ ጥቂት ቀን ተቀመጡ፡፡ የአይሁድም የፋሲካቸው በዓል ቀርቦ ነበር፤ ጌታችን ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ፡፡ በቤተ መቅደስም በሬዎችንና በጎችን÷ ርግቦችንም የሚሸጡትን÷ገንዘብ ለዋጮችንም ተቀምጠው አገኘ፡፡ የገመድም ጅራፍ አበጀ፤ በጎችንና በሬዎችን÷ ሁሉንም ከቤተ መቅደስ አስወጣ፤ የለዋጮችንም ገንዘብ በተነ፤ ገበታዎቻቸውንም ገለበጠ፡፡ ርግብ ሻጮችንም÷ “ይህን ከዚህ አውጡ፤ የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉ” አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም÷ “የቤትህ ቅናት በላኝ” የሚል ቃል ተጽፎ እንዳለ ዐሰቡ፡፡

 

አይሁድም መልሰው÷ “ይህን የምታደርግ ምን ምልክት ታሳያለህ?” አሉት፡፡ ጌታችን ኢየሱስም÷ “ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት፤ በሦስተኛውም ቀን አነሣዋለሁ” ብሎ መለሰላቸው፡፡ አይሁድም÷ “ይህ ቤተ መቅደስ በአርባ ስድስት ዓመት ተሠራ፤ አንተስ በሦስት ቀኖች ውስጥ ታነሣዋለህን?” አሉት፡፡ እርሱ ግን ይህን የተናገረው ቤተ መቅደስ ስለ ተባለ ሰውነቱ ነበር፡፡ ከሙታን በተነሣ ጊዜም ደቀ መዛሙርቱ ስለዚህ እንደ ነገራቸው ዐሰቡ፤ በመጻሕፍት ቃልና ጌታችን ኢየሱስ በነገራቸውም ነገር አመኑ፡፡

 

ጌታችን ኢየሱስም በፋሲካ በዓል በኢየሩሳለም ሳለ ብዙ ሰዎች ያደረገውን ተአምራት ባዩ ጊዜ በስሙ አመኑ፡፡ እርሱ ጌታችን ኢየሱስ ግን አያምናቸውም ነበር፤ ሁሉን እያንዳንዱን ያውቀዋልና፡፡ የሰውንም ግብሩን ሊነግሩት አይሻም፤ እርሱ በሰው ያለውን ያውቅ ነበርና፡፡