sewa sewe brhan 3

የቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀመዛሙርትን አስመረቀ

 ሰኔ 23 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

sewa sewe brhan 3በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ በመደበኛና በማታ መርሐ ግብር ትምህርታቸውን የተከታተሉ 212 ደቀመዛሙርትን በዲፕሎማ አስመረቀ፡፡

ሰኔ 21 ቀን 2006 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ በተካሔደው የምረቃ መርሐ ግብር ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ዲፕሎማና በትምህርታቸው ከፍተኛ ውጤት ላስመዘገቡ ደቀመዛሙርት የተዘጋጀላቸውን ሽልማት ከሰጡ በኋላ ባስተላለፉት ቃለ ምእዳን “ቤተ ክርስቲያን ከአጽናፈ ዓለም አሰባስባ፤ አስተምራ ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት ልታሰማራችሁ በዝግጅት ላይ ቆይታችኋል፡፡ ይህ ለቤተ ክርስቲያናችን ትልቅ ሐብት በመሆኑ ያገኛችሁትን እውቀት ለወገኖቻችሁ እንድታካፍሉና ቤተ ክርስቲያን የጣለችባችሁን ሓላፊነት እንድትወጡ አደራ እላለሁ” ብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ያሬድ የሰዋሰወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሓላፊ፤ የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ፤ የሶማሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ደቀመዛሙርቱ መንፈሳዊ ትምህርት ሲከታተሉ ቆይተው ቤተ ክርስቲያን ለማገልገል የሚዘጋጁበት ወቅት እንደሆነ አስታውሰው፤ በአባቶች ቡራኬ ለመመረቅ በመብቃታቸው እንኳን አደረሳችሁ በማለት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የኮሌጁ ዲን መጋቤ ጥበብ ምናሴ ወልደ ሃና ባቀረቡት ሪፖርት በመማር ማስተማሩ ሂደት ያጋጠሟቸውን ችግሮች ላይ ትኩረት በማድረግ በዝርዝር አቅርበዋል፡፡ በዚህም መሠረት መምህራን ሲለቁ በቦታቸው ቶሎ ተተኪ ያለመመደብ፤ የሚመሩ ደብዳቤዎች ባልታወቀ ሁኔታ መጥፋት፤ ኮሌጁ ለሚጽፋቸው ደብዳቤዎች ምላሽ ያለማግኘት፤ የሥራ ጣልቃ ገብነት ጎልተው ከሚታዩት ችግሮች ውስጥ እንደሚገኙበት ጠቁመዋል፡፡

ኮሌጁ ምሁራንን እያፈራ የሚገኝ ቢሆንም ዘመኑን ባልተከተለ አሠራር እየተጓዘ ከአባቶች እንደተረከብነው ለተተኪ ትውልድ ማስተላለፍ እንችላለን ወይ? በሚል ጥያቄ ውስጥ እንደሚገኙም መጋቤ ጥበብ ምናሴ ስጋታቸውን ገልጸዋል፡፡ ኮሌጁ በየዓመቱ የሚቀበላቸው ደቀመዛሙርት ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀነሰ መምጣቱም እንደማሳያነት ጠቅሰዋል፡፡

sewa sewe brhan 2ከተመራቂ ደቀ መዛሙርቱ መካከል አባ ኪሮስ ወልደ አብ የትምህርት ቆይታቸውን አስመልክቶ የተሰማቸው ስሜት ሲገለጡ “ትምህርት ጀመርኩ እንጂ አልጨረስኩትም፤ የበለጠ እንድማር አነሳሥቶኛልና እቀጥልበታለሁ፡፡ በኮሌጁ ቆይታዬም በእቅድ መመራት በመቻሌ በጥሩ ሁኔታ ተምሬ በማዕረግ ለመመረቅ ችያለሁ” ብለዋል፡፡

 

ተመራቂ ደቀመዛሙርት ያወጡትን የጋራ መግለጫ በተወካያቸው አማካይነት ያቀረቡ ሲሆን፤ በኮሌጁ ውስጥ አንዳንድ መልካም ሥራዎች ቢኖሩም በኮሌጁ ቆይታቸው በስፋት ይታያሉ ያሏቸውን ችግሮች ዳስሰዋል፡፡ የትምህርት አሠጣጡ ዘመኑን የዋጀsewa sewe brhan 1 ያለመሆን፤ ለመምህራን በቂ ደሞዝ ያለመከፈል፤ ከሌሎች መሰል የቤተ ክርስቲያኒቱ ኮሌጆች ጋር የልምድ ልውውጥ ያለማድረግ፤ በቤተ መጻሕፍቱ ውስጥ የሚገኙ መጻሕፍት በቂ ያለመሆናቸው፤ የመደበኛ ተማሪዎች ቁጥር መቀነስ እንደ ችግር ከጠቀሷቸው ውስጥ ይገኙበታል፡፡

ደቀመዛሙርቱ እንደመፍትሔ ካቀረቧቸው ውስጥ፤ የትምህርት አሰጣጡ በሚመጥን መልኩ ቢቀረጽ፤ ተቋማዊ አቅሙን ወደ ዩኒቨርስቲነት ቢያሳድግ፤ በከፍተኛ ውጤት ለሚመረቁ ደቀመዛሙርት የነጻ ትምህርት እድል ቢመቻች የሚሉት ሐሳቦች ጥቂቶቹ ናቸው፡፡

ከ212 ተመራቂ ደቀ መዛሙርት መካከል 12ቱ በመደበኛነት ትምህርታቸውን የተከታተሉ ሲሆን፤ ከእነዚህ ውስጥ አንድ በብሉያት፤ አንድ በሐዲሳት ትርጓሜ የተመረቁ ናቸው፡፡ 200 ደቀመዛሙርት ደግሞ በማታው የትምህርት መርሐ ግብር ትምህርታቸውን የተከታተሉ ናቸው፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ የኮሌጁ መምህራንና የተመራቂ ደቀመዛሙርት ቤተሰቦች ተገኝተዋል፡፡

 

የሚዛን ተፈሪ ማዕከል 14ኛውን ጠቅላላ ጉባኤ አካሄደ

 

ሰኔ 23 ቀን 2006 ዓ.ም.

በሚዛን ተፈሪ ማዕከል ሚዲያ ክፍል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን የሚዛን ተፊሪ ማዕከል ከሰኔ 13 እስከ 15 2006 ዓ.ም 14ኛውን ጠቅላላ ጉባኤ በአቡነ ተክለ ሃይማኖትና ቅዱስ ኡራኤል የእናቶች አንድነት ገዳም የስብከተ ወንጌል አዳራሽ አካሄደ፡፡

ሦስት ቀናት በፈጀው ጉባኤ የማእከሉ 2006 ዓ.ም ሥራ አፈጻጸም ሪፖርት በማዕከሉ ሰብሳቢ በአቶ መስፍን ደጉ የቀረበ ሲሆን፤ በእቅድ አፈጻጸሙ በተገቢው ሁኔታ የተከናወኑትን፤ ያጋጠሙ ችግሮች ፤ የተወሰዱ የመፍትሄ ሃሳቦች እና ትኩረት የሚሹ ጉዳዮች በሪፖርቱ ተካተዋል፡፡

አብዛኛዎቹ ችግሮች ከአባላት የአገልግሎት ዝለት ጋር የተያያዙ በመሆናቸው ክፍሎች ያቀዷቸውን እቅዶች አባላት የማስፈጸም አቅማቸዉ ያልተመጣጠነ መሆኑም ተጠቁሟል፡፡

በቀረበው ሪፖርት መሠረት የተሻለ የእቅድ አፈጻጸም እንዲሁም ዝቅተኛ የዕቅድ አፈጻጸም ያሳዩ ክፍሎችም ተለይተዋል፡፡ በዚህም መሠረት ለ2007 ዓ.ም. ክፍሎች ራሳቸውን በማጠናከር ያቀዷቸውን እቅዶች ተግባራዊ በማድረግ ጠንክረው እንዲሰሩ ማሳሰቢያ ተሰጥቷል፡፡

የ2007 ዓ.ም ዕቅድ በማዕከሉ የዕቅድ ዝግጅትና ከትትል ክፍል ቀርቦም በውይይት በማዳበር ማስተካከያ ተደርጎበት ጸድቋል፡፡

ከማእከሉ አባላት በተጨማሪም ከሀገረ ስብከት፣ ከወረዳ ቤተ ክህነት፣ ከዋናው ማዕከል፣ ከምዕራብ ማዕከላት ማስተባበርያ፣ ከወረዳ ማዕከላት፣ ከግቢ ጉባኤያትና ከግንኙነት ጣብያዎች ተወክለው የመጡ እንግዶች በጉባኤው ላይ ተሳታፊ ሆነዋል፡፡

 

 

በንባብ ባሕል ላይ ያተኮሩ ጥናታዊ ጽሑፎች ይቀርባሉ

ሰኔ 23 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

የንባብ ባሕልን ለማሳደግ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ያተኮሩ ጥናታዊ ጽሑፎች በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል አዘጋጅነት ሰኔ 28 ቀን 2006 ዓ.ም ከ8፡00-11፡00 ሰዓት በማኅበሩ ሕንፃ ላይ እንደሚቀርቡ ማእከሉ አስታወቀ፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ምሁራን የሚቀርቡት ጥናታዊ ጽሑፎች ሁለት ሲሆኑ፤ “ትርጉም ያለው የንባብ ባሕል”፤ እንዲሁም “የንባብ ባሕልን ለማሳደግ የተለያዩ አካላት ሚና” በሚሉ ርእሰ ጉዳዮች ላይ ትኩረት እንደሚያረጉ የጥናትና ምርምር ማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር አቶ ሰይፈ አበበ ገልጸዋል፡፡

ትርጉም ያለው ንባብ ምንድን ነው? የንባብ ባሕልን ያሳደጉ አገራት ልምድ ምን ይመስላል? የንባብ ልምድ በሀገራችን እና በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ምን እንደሚመስሉ በጥናቶቹ ይዳሰሳሉ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል በየዓመቱ በሀገራችን የንባብ ባሕልን ለማበረታታት ከሚያዘጋጀው የመርሐ ግብር አካል አንዱ ሲሆን፤ ጥናቶቹም የንባብ ባሕላችን ምን ላይ እንደሚገኝ የሚዳስሱና የሚያነብ ትውልድን ለመፍጠር ምን መደረግ እንዳለበት የሚያመላክቱ መሆናቸውን አቶ ሰይፈ ጠቁመዋል፡፡

ይህ የንባብ ጉባኤ ለሦስተኛ ጊዜ የተዘጋጀ ሲሆን፤ በመርሐ ግብሩ በንባብ ባሕል ላይ የሚሠሩ አካላት፣ ምሁራን፤ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት እና ጥሪ የተደረገላቸው አካላት፤ እንዲሁም ምእመናን ተሳታፊ ይሆናሉ፡፡

 

የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት መጽሔት ቊ.፫/፳፻፭ ዳሠሣ

ሰኔ 19 ቀን 2006 ዓ.ም.

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዐለም መድረክ የምትታወቀው በጥንታዊነቷ ብቻ ሳይሆን አርቆ አሳቢና ጥበበኛ በሆኑ ሊቃውንት አባቶች አማካኝነት፣ ለዘመናት ተጠብቀው በቆዩ ቁሳዊና ቁሳዊ ባልሆኑ መንፈሳዊ ሀብታት ጭምር ነው፡፡ እነዚህ የቤተክርስቲያን አባቶች በየገዳማቱና አድባራቱ ጠብቀው ያቆዩት የእውቅት ሀብት በዚህ ዘመን ለጥናትና ምርምር ከፍተኛ ምንጭና ገና ያልተነካ የጥናት መዳራሻ ነው፡፡ እነዚህ አባቶች በየድርሳናቱ፣ በየጽሑፉ፤ በሥዕላት እና በቅርሶች ከትበው ያቆዩትን ዕውቀትና ጥበብ ለቤተ ክርስቲያን ልጆችና ለሣይንሱ ማኅበረሰብ ለማስተላለፍ የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የጥናት መጽሔት አሳትሞ ማሠራጨት ከጀመረ ሦስት ዐመታት አልፈዋል፡፡ በዚህ ዐላማ መሠረት ለሦስተኛ ጊዜ ያዘጋጀውን የጥናት መጽሔት በቅርብ ጊዜ አሳትሞ ለሥርጭት አብቅቷል፡፡ ይኽ ሦስተኛ ዕትም ሰባት ጥናታዊ ጽሑፎችን የያዘ ሲሆን ሦስቱ በዐማርኛ ቋንቋ፣ ዐራቱ ደግሞ በእንግሊዘኛ ቋንቋ የተዘጋጁ ናቸው፡፡

የመጀመሪያው ጽሑፍ በሊቀ ኅሩያን በላይ መኮንን የተዘጋጀ ሲኾን ጸሐፊው በቅዱስ ያሬድ ሕይወትና ሥራዎች ዙሪያ የተሠሩ ጥናቶችና ምርምሮች እርስ በርሳቸው ያላቸውን ተዛማጅነትና ልዩነት በጥንቃቄ በመቃኘትና በመረጃ ላይ በመመሥረት የሐሳብ ልዩነታቸውን ለማጥበብ የሞከሩበት ጥናት ነው፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ ጥናቱ በቅዱስ ያሬድ የዜማ መጻሕፍትና ትምህርት የተንጸባረቁትን የቅዱስ ያሬድን ኹለንተናዊ አስተምህሮ ከነገረ መለኮት አንጻር ይተነትናል፡፡ ከጥናቱ ግኝቶች መካከል ለኢትዮጵያ ሊቃውንት የዕውቀታቸው፣ የብቃታቸውና የፍልስፍናቸው ልዩ መገለጫ የሆነው የግእዝ ቅኔ ከዜማ ድርሰት ጋር እንደ ተጀመረ በጥናቱ ታይቷል፡፡ በጥናቱ የታየው ዐዲስ ግኝት ደግሞ የቅዱስ ያሬድ የዜማ ድርሰት ለዐማረኛ የግጥም ምጣኔ /ልኬት/ መሠረት መኾኑን ነው፡፡

ቀጣዩ ጽሑፍ የቤተ ክርስቲያንን አሻራ በሸካቾ ብሔረሰብ ውስጥ የሚዳሥሥ ሲኾን የተጻፈውም በቀሲስ ወንድምስሻ አየለ ነው፡፡ ጸሐፊው በጥናታዊ ጽሑፋቸው በብሔረሰቡ የትበሀል፣ ሥርዐተ አምልኮ፣ የባዐላትና የክብረ ቅዱሳን ዕለታት አካባበር፣ የቦታና የቅዱሳን ስያሜ እንዲሁም የቀን አቆጣጠር አደረጃጀትና ስያሜ ላይ ቤተክርስቲያን ያላትን ጉልህ አሻራ በሰፊው ዳሥሥዋል፡፡ በማጠቃለያም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሌሎች ብሔር ብሔረሰቦች ባህል፣ ታሪክና ቋንቋ ላይ ያላትን አሻራ ለማሳየት በሸካቾ ብሔረሰብ የታየው የቤተ ክርስቲያን አሻራ ጠንካራ ማሳያ ሊኾን እንደሚችል በመጠቆም ጽሑፋቸውን ይቋጫሉ፡፡

በዶ/ር ዐለማየሁ ዋሴ የተጻፈው ሥስተኛው ጽሑፍ የተለያዩ የዕፅዋት ዝርያዎችና እንስሳት እንዲሁም ለሰዎች መገለገያ የሆኑ የአረንጓደ ተፈጥሮ ቦታ መገኛ የሆኑ ተፈጥሯዊ ደኖችን በመጠበቅ ቤተ ክርስቲያን ያላትን ረጅም ታሪክና ልዩ ድርሻ የሚዳሥሥ ነው፡፡ ጸሓፊው አብያተ ክርስቲያናት እግዚአብሔርን ማምለክና ሃይማኖታዊ ተግባር መፈጸም ተቀዳሚ ዐላማቸው /ተግባራቸው/ ቢሆንም በዋጋ ሊተመን የማይቻል ልዩ የኾኑና ጥብቅ ሥነ ሕይወታዊ ቦታዎች መገኛ ማእከል በመኾን እንደሚያገለግሉ ይገልጻሉ፡፡ አጥኝው የቤተ ክርስቲያን ደኖች የሀገር በቀለ ዝርያዎችን ያካተቱ ቀደምትና እየጠፉ ያሉ ዛፎች ቅሪት መኾናቸውን አንክሮ በመሥጠት ያስረዳሉ፡፡ እነዚህ ደኖች ክብር ያላቸው የሃይማኖት ቦታዎች ኾነው እንደሚቀጥሉ ሁሉ ተፈጥሯዊ ጥብቅ ደኖችን በመጠበቅም ቀዳሚ ትኩረት ሊያገኙ እንደሚገባ አበክረው ያስረዳሉ፡፡ የሰሜን ኢትዮጵያ ከፍተኛ ቦታዎችን የጥናት ቦታቸው ወሰን በማድረግ የቤተ ክርስቲያኗ ደኖች ባጋጣሚ ተጠብቀው የቆዩ ሳይኾኑ የጥበቃ ጥረታቸውን ሥነ መለኮታዊና መጽሐፍ ቅዱሳዊ አመክንዮ በሚሠጡ የቤተ ክርስቲያኗ ቁርጠኛ ምእመናን/ተከታዮች/ ጥብቅ ጥበቃና ጥረት መኾኑን ይተነትናሉ፡፡ በመጨረሻም አጥኝው በእነዚህ የቤተ ክርስቲያኗ ደኖች ላይ በዛ ያሉ ሥነ ምኅዳራዊና ማኅበረሰባዊ ተፅዕኖዎች እየተጋረጡባቸው እንደኆነ በመግለጽ የመፍትሔ ሐሳብ አስቀምጠዋል፡፡

ይኽ ጥናት በቤተ ክርስቲያን ደኖች ላይ የተጋረጡትን አደጋዎች የሚገልጽ ሲሆን ቀጣዩ የዶ/ር ጥጋብ በዜ ጥናት ደግሞ ቤተ ክርስቲያን እየገጠማት ያለው ሌላኛውን የተግዳሮት ገጽ ያሳየናል፡፡ የመጀመሪያው ተግዳሮት ውስጣዊ፣ ሁለተኛው ደግሞ ዐለማቀፋዊ ይዘት ያለው ሲኾን የሁለቱም ተግዳሮቶች መነሻ ግን በክብካቤ እና የጥበቃ ጉድለት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከክርስትና መጀመር ጀምሮ በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ስለነበራት ይዞታ በመተንተን ዶ/ር ጥጋብ ብቸኛውንና ዋንኛውን የቤተ ክርስቲያን ይዞታ ማለትም ዴር ሡልጣንን በተመለከተ ስላለው ያልተረጋጋ ሁኔታ በዎፍ በረር ያስቃኙናል፡፡ በጥናቱ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች በቅድስት ሀገር የሚገኙ ይዞታዎቻቸውን እንዴት እንዳጡና ከ፲፱ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ ይኽን ቅዱስ ሥፍራ ለማስጠበቅ ከግብጾች ጋር በምን ዐይነት የተንዛዛ ክርክር እንደተጠመዱ ይተርኩልናል፡፡

ወደ ቀጣዩ ጥናት ሥናልፍ ደግሞ በዝዋይ ሐይቅ በሚገኙ ገዳምና አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ ያሉ ጥንታዊ ቅርሶች ላይ ትኩረት አድርጎ የተሠራውን የአቶ ቡሩክ ወልደ ሰማያትን ጥናት እናገኛለን፡፡ ጥናቱ በዝዋይ ደሴያት ውስጥ በሚገኙ ቅዱሳት መካናት የሚገኙ በዋጋ ሊተመኑ ያማይቻሉ ቅዱሳት መጻሕፍትና ንዋያተ ቅዱሳት ዙሪያ ያጠነጥናል፡፡ የጥናቱ አዘጋጅ በቦታው የሚገኙ ጥንታዊ ቅርሶችን በዝርዝር በማስቀመጥና ቅርሶቹ በቊጥር ብዙ፣ በዐይነት ግን የማይተኩ መኾናቸውንና የአጠባበቅና የአያያዝ ሥርዐቱ በቂ ያለመኾኑን በመግለጽ ሊወሰዱ ይገባቸዋል የሚሏቸውን የመፍትሔ ሐሳቦች በመጠቆም ጥናቱን ይቋጫሉ፡፡

በአቶ ሒንጋቡ ሖርዶፋ የተዘጋጀው ስድስተኛው የጥናት ወረቀት በደብረ ሊባኖስ ገዳም ውስጥ በሚገኙ የዕፅዋት ዐይነቶች፣ አጠቃላይ መዋቅርና ብዝኀ ሕይወት ላይ የሚያጠነጥን ነው፡፡ የጽሑፉ ዋና ዐላማም በገዳሙ ውስጥና በአካባቢው ያሉ የዕፅዋት ዘሮችንና አትክልቶችን ዐይነት፣ ስብጥርና መዋቅር መዳሠሥ ነው፡፡ ጥናቱ በገዳሙ ደን ውስጥ ያለው የዕፅዋት ዐይነትና ስብጥር በመንግሥትና በግል ከተያዙት የደን ልማቶች በተሻለ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ አረጋግጧል፡፡ በተጨማሪም በገዳሙ ደን ውስጥ ያሉት የዕፅዋት ዝርያ ልዩ መኾንና ተፈጥሮዊ ስብጥር (መስተጋብር) ጉላ ያለ መኾኑን አሳይቷል፡፡ በመጨረሻም የገዳሙ ደን ከዚህ በተሻለ ትኩረት ቢጠበቅ በውስጡ ያለው ብዝኀ ሕይወት የተፈጥሮን ሚዛን ለመጠበቅና እንደገና ሞተው ሊነሡ የማይችሉ ውድ የዛፍ ዐይነቶች እንዳይጠፉ በመከላከል ረገድ ትልቅ ሚና እንደሚጫወት በመጠቆም ጥናቱን አጠቃልሏል፡፡

በአቶ ዮሐንስ አድገህ የቀረበው የመጨረሻውና ሰባተኛው የጥናት ወረቀት ደግሞ ኦሮምኛ ቋንቋን ለኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ትምህርትና ሃይማኖታዊ አገለግሎት በመጠቀም ረገድ ያሉ ተግዳሮቶችንና ምቹ ኹኔታዎችን ይተነትናል፡፡ ጥናቱ የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ እንደ ተቋም በአጠቃላይ በአፍ መፍቻ ቋንቋ ትምህርት፣ በተለይም በኦሮምኛ ቋንቋ ጠቀሜታ ላይ ያላትን በጎ (አዎንታዊ) አመለካከት አሳይቷል፡፡ ሆኖም ግን የሃይማኖቱን ጽንሰ ሐሳብ የሚሸከሙ አቻ ሙያዊ ቃላት እጥረት፣ የገንዘብና የሰው ሀብት እጥረት፣ ቤተ ክርስቲያን ግልጽ የኾነ የቋንቋ መመርያ የሌላት መኾኑ፣ የተወሰኑ የቤተ ክርስቲያን ሓላፊዎች በአፍ መፍቻ ቋንቋ ትምህርት ላይ ያላቸው የግዛቤ እጥረት፣ የቋንቋ መብዛት ለሀገር አንድነት እንቅፋት ይኾናል የሚል ፍርሃትና የመሳሰሉት የኦሮምኛ ቋንቋ በቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አግልግሎት ላይ በሚጠበቅበት ደራጃ እንዳያገለግል ተግዳሮቶች መኾናቸውን ጥናቱ አመልክቷል፡፡ ይሁን እንጂ ጥናቱ፣ የኦሮምኛ ቋንቋ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ላይ ጥቅም ላይ መዋሉ እየጎለበተ መምጣቱንና በተለይም ማኅበረ ቅዱሳን የኦሮምኛ ቋንቋን በመጠቀም በኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ መገናኛ ብዙኃን የቋንቋውን ተናጋሪዎች ለመድረሥ እየተጋ እንደሚገኝ ጠቁሟል፡፡ በመጨረሻም በአፍ መፍቻ ቋንቋ መጠቀም ያለውን ሥነ ትምህርታዊ፣ ሥነ ልቡናዊና ሥነ ማኅበራዊ ጠቀሜታ በመገንዘብ፣ ቤተ ክርስቲያን ኦሮምኛንም ኾነ ለሌሎችንም የሀገሪቱን ቋንቋዎች በመጠቀም ብዙኃኑን ምእመን ማስተማር እንዳለባት በማሳሰብ ጥናቱን ቋጭቷል፡፡

እንግዲህ ለመነሻ ይህን ያህል ካልን ሙሉውን ጽሑፍ ከጥናት መጽሔቱ እንዲያንቡ መልእክታችን ነው፡፡ ጥናት መጽሔቱን ለማግኘትና ጥያቄ ካልዎት በ mkidusantmaekel@yahoo.com ወይንም በ +251-11-155-99-34 ሊያገኙን ይችላሉ፡፡

 

st mary2

በወርቅ ከተለበጠው በድንጋይ ወደ ታነፀው

ሰኔ 19 ቀን 2006 ዓ.ም.

ሊቀ ሊቃውንት ስምዐኮነ መላክ

በምዕራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት የ፬ቱ ጉባኤያት መምህር

st mary2የመጀመሪያውን የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ለመሥራት ከጥንት ሰዎች የተፈቀደው ለሰሎሞን ነው፡፡ ሰሎሞን የተወለደበት ዘመን በንጉሡ ዳዊትና በእግዚአብሔር መካከል የነበረው ጥል ተወግዶ ፍቅር የተመሠረተበት የፍቅር ወቅት ነበር፡፡ በደለኛነቱ በነቢይ የተረጋገጠበት ንጉሥ ዳዊት በበደለኛነቱ ወቅት ከኦርዮን ሚስት በወለደው ልጁ ሞት ምክንያት የእርሱ ሞት ወደ ልጁ ተዛውሮለት እርሱ ከሞት እንዲድን ሆኗል፡፡ የእርሱን ሞት ልጁ ወስዶለት የልጁ ሕይወት ለእርሱ ተሰጥቶታል፡፡ ከዚህ ልጅ ሞት በኋላ ያለው ዘመን የሰላምና የእርቅ ዘመን በመሆኑ የተወለደው ልጅ ሰሎሞን ተብሎ ተጠራ፤ በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደደ የፍቅር ስም ነው፤1ኛ ነገ12÷24

የንጉሡ ዳዊት ንስሐ ለመጀመሪያው ጊዜ ቤተ መቅደስ በምድር ላይ ለመሥራት ምክንያት ነው፡፡ የምድር ሁሉ ንጉሥ ሆኖ ተሾሞ የነበረው አባታችን አዳም በደለኛ ሳለ በገባው ንስሐ ምክንያት የአምስት ቀን ተኩል (5500 ዘመን) ቀኖናውን ሲፈጽም የተወለደለት አንድ ልጁ ክርስቶስ የእርሱን ሞት ሞቶለት፣ የራሱን ሕይወት ለአዳም ሰጥቶት ባደረገው ካሳ በአዳምና በእግዚአብሔር መካከል ለተፈጠረው ሰላምና ፍቅር መገለጫ የሚሆን ቤተ መቅደስ በሰዎች መካከል ተሠርቷል፡፡ ዘመኑ ከጌታ ልደት በኋላ ሃምሳ አራት ዓመት ገደማ እመቤታችን ባረገች በአራት ዓመት ወንጌልን ለመስማት ከአውሮፓ ከተሞች የሚቀድማት የሌለው እና በመቄዶንያ አውራጃ የምትገኘዋ ግሪካዊቷ የፊልጶስ ከተማ ፊልጵስዩስ፤ በቅዱስ ጳውሎስ ሁለተኛው የወንጌል ጉዞ ወቅት ወንጌልን ሰምታ ካመነች በኋላ የመጀመሪያው የቤተ መቅደስ ሥራ በመካከሏ ተፈጽሞላታል፡፡

ክርስቶስ በምድር ላይ ሰውን የእግዚአብሔር ማደሪያ ቤተ መቅደስ ለማድረግ ሲተጋ ነበር ማደሪያ የሚሆነው ምድራዊ ድንኳን አልሠራም፡፡ ክርስቶስ የመጣው ሰውን ለመሥራት እንጂ በሰማይ ማደሪያ የሌለው ሆኖ ማደሪያ ፍለጋ የመጣ አይደለምና እንዲሁም ጊዜው ገና ስለነበር መጀመሪያ መሠራት ያለበት ሰው ነበር፡፡

ጊዜው ሲደርስ ከላይ በተጠቀሰው ዘመን ቅዱስ ጳውሎስና ቅዱስ በርናባስ አስተምረው ባሳመኗት ከተማ መካከል በጥበበ እግዚአብሔር አዲስ ሕንፃ ለእግዚአብሔር ማደሪያነት ተገነባ፡፡ እስከዚያ ቀን ድረስ ሐዋርያትና ሌሎችም ደቀ መዛሙርት ለመሰብሰቢያነት ይጠቀሙበት የነበረው ካታኮምብ (ግበበ ምድር) ካልሆነ ለክርስቲያኖች ተብሎ የተገነባ ልዩ ሥፍራ አልነበረም፡፡ የአህዛብ መምህር ሆኖ የተመረጠው ቅዱስ ጳውሎስ እስኪነሣ ድረስ ከሐዋርያት አንዳቸውም ለዚህ አገልግሎት አልተመረጡም፡፡ ለእግዚአብሔር ሰዎች የተሰጣቸው ጸጋ ልዩ ልዩ ነውና በአሕዛብ መካከል ቤተ እግዚአብሔር እንዲሠራ የተፈቀደው ለቅዱስ ጳውሎስ ነው፡፡

እርሱ ወንጌልን ሰብኮ ወደ ሌሎቹ ሀገራት ዘወር ሲል ሕዝቡ ተሰብስበው አንድ ጥያቄ ጠየቁ፤ ወደ ቤተ ጣዖት እንዳንሔድ ከልክላችሁናል፤ ሥርዓተ አምልኮ የምንፈጽምበት ቤት ልትሠሩልን ይገባል ብለው ጠየቋቸው፡፡ ጳውሎስና በርናባስ ከሌሎቹ ሐዋርያት ጋር ተማክረው ወደ እግዚአብሔር አመለከቱ፤ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰኔ በሃያ ቀን ወርዶ ሐዋርያትን ባንድ ቦታ ሰብስቦ፣ ከተራራ ላይ የተቀመጡ ሦስት ድንጋዮችን ጠቅሶ ወደ እርሱ በማቅረብ ቅድስት፣ መቅደስ፣ ቅኔ ማኅሌት አድርጎ ሠርቶላቸዋል፡፡

ቤተ እግዚአብሔር ለመጀመሪያ ጊዜ ከቤተ እስራኤል ውጭ ተሠራች፤ ከከበሩ እና ተጠርበው አምረው ከቀረቡ ክቡራን ድንጋዮች ሳይሆን ተራራ ላይ ተቀምጠው ከሚኖሩ ተራ ድንጋዮች ተገነባች፡፡ በወርቅ ከተለበጠው በድንጋይ ወደ ታነፀው ተዛወረች፤ በዝግባና በጽድ የታነፀው አገልግሎት ከመስጠት ተከለከለ፤ በጢሮሳዊ የአልባስጥሮስ ግምጃ የተሸፈነው ተናቀ በነኪራም ብልሃት፣ በነባስልኤልና ኤልያብ ጥበብ የተጌጠው የጸሎት ቤት ክብሩን ለቀቀ፤ ሁሉም ነገር ከተጠበቀው ውጭ ሆነ፡፡

በዚህ ሁሉ ነገር ውስጥ የእግዚአብሔር መልዕክት ምንድነው?

ቤተ መቅደሱ በድንጋይ ለምን ተሠራ? ከመሠረት እስከ ጣራና ጉልላት ሌላ ነገር አልተጨመረበትም፤ ድንጋዮቹም ሦስት ብቻ ናቸው፡፡ እግዚአብሔር በአዲስ ኪዳን ዘመን በድንጋይ ላይ የሠራቸው አስደናቂ ነገሮች የተለዩ ናቸው፤ የቃና ዘገሊላውን ተአምር የተመለከትን እንደሆነ፤ የቢታንያ ድንጋዮችንም ያነሣን እንደሆነ በእነርሱ የተደረገው ነገር ድንቅ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ያልተደረገ፣ ወደፊትም የማይደረግ ድንቅ ተአምር በነዚህ ድንጋዮች ውስጥ ሲደረግ እናያለን፡፡ እግዚአብሔር ሊሠራ ከወደደ በድንጋይ ልብ ውስጥም ሥራ መሥራት እንደሚችል አሳየን፡፡ ቀድሞ በነቢያቱ ዘመን ዮናስን በባሕር ልብ ውስጥ አስገብቶ እንዲዘምር አደረገ፣ ኢያሱ ሥራውን እስኪጨርስ ፀሐይን አቆመ፣ በእኛም ዘመን የአቡነ ዘርዐ ቡሩክን የጸሎት መጻሕፍት እስከወደዱት ዘመን ድረስ በዐባይ ውኃ ጉያ ውስጥ ደብቆ አቆየ፡፡

ድንጋይ ሲፈልጡት ይፈለጣል፣ ሲረግጡት ይረገጣል እንጂ መች ቀድሶ ያውቃል? መች ወንጌል ሰብኮ ያውቃል? በቢታንያ የቆመው የድንጋይ ምሰሶ ግን ይሁዳ ንስሐ እንዲገባ ተግቶ የሰበከ ብቸኛ ሐዋርያ ነው፡፡

የክርስቶስ ወደ ዓለም የመምጣት ምክንያት ይህ ነበር፡፡ እንደ ድንጋይ ኃጢአት ያፈዘዘው አዕምሯችንን ሕይወት እንዲኖረው ማድረግ! ድንጋይ ከውጪ እንጂ ከቤት ውስጥ ምን ሙያ አለው? እኛ ሁላችንም በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ሙያ ታጥቶልን በውጭ እንድንጣል የተደረግን ሰዎች ነበርን፤ እንዲህ እንደ ድንጋይ ያለ ፈዛዛ ታሪክ በነበረን ወራት የተወለደው የማዕዘኑ ራስ ክርስቶስ በእኛ በድንጋዮች አድሮ ሥራ እንደሚሠራ ለማስረዳት ለልዩ ልዩ አገልግሎት ድንጋይን ሲጠቀም እንመለከተዋለን፡፡ የበረሃው ሰባኪ ቃለ ዓዋዲ ዮሐንስ እስራኤልን ሲገስጽ ‹‹እብለክሙ ከመ ይክል እግዚአብሔር እምዕላንቱ አዕባን አንሥኦ ውሉድ ለአብርሃም፤ እግዚአብሔር ከነዚህ ድንጋዮች ለአብርሃም ልጅ ማሥነሳት እንደሚችል በእውነት እነግራችኋለሁ›› ማቴ3÷9 እያለ አብርሃም አባት አለን በማለት ብቻ ሊጸድቁ የሚያስቡትን ይዘልፋቸው ነበር፡፡ ሲጀመር ለአብርሃም የተገባው ቃል ኪዳን እንደ ሰማይ ከዋክብት ለሆኑት ልጆቹ ብቻ መች ሆነና! እንደ ባሕር አሸዋ በምድር ላይ ለተነጠፉት ልጆቹም ነው እንጂ፡፡

በእውነት ድንጋዮችን ልጅ አድርጎ ለአብርሃም የሚያስነሣበት ዘመን እንደደረሰ እንዲታወቅ በእነዚህ ድንጋዮች ቤቱን ሠራ፡፡ እኒህ ድንጋዮች እኮ የአሕዛብ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ የሰሎሞን ቤተ መቅደስ በከበሩ ድንጋዮች የተሠራ፣ በዋንዛ፣ በጽድ፣ በዝግባ የተዋበ፣ በወርቅ የተለበጠ ነበር 1ኛነገ. 6÷7፡፡ ለዚህ ግን እነዚህ ሁሉ ጌጣ ጌጦች አላስፈለጉትም፤ ድንጋዮች በቂ ነበሩና፡፡ ለክርስትና የጥንቶቹ ሊቃነ ካህናት ሌዋውያንና ፈሪሳውያን አያስፈልጉትም፤ እግዚአብሔር ከመረጣቸው አሕዛብ ቤተ መቅደሱን ለመሙላት አላስቸገረም፡፡

ከድንጋይስ ምን አለበት የከበሩ ድንጋዮችን ቢመርጥ ኖሮ ሊባል ይቻል ይሆናል፤ ተራራው ላይ ሥራ አጥተው የተቀመጡትን ድንጋዮች ሥራ መስጠትኮ ነው የክርስቶስ ዓላማ፡፡ በማለዳም፣ በሦስት ሰዓትም፣ በቀትርም፣ እስከ ማታ ለወይኑ ቦታ ሠራተኞችን ሊስማማ በወጣ ጊዜ የተዋዋላቸው ሰዎች ሥራ ፈቶች አልነበሩምን? ማቴ20÷1 አሁንስ ለቤቱ የመረጣቸው ድንጋዮች በሰው ዘንድ ያልታሰቡ ቢሆኑ ምን ይገርማል፤ ለክርስቶስ ማደሪያነት ከቤተ አይሁድ ቀድሞ የሚገኝ አለ ተብሎ በሰው ዘንድ ታስቦ ያውቅ ነበር? አሕዛብን እግዚአብሔር ከውሻነት አውጥቶ ልጆች ያደርጋቸዋል ብሎ ማን አስቦ ኖሯል? እግዚአብሔር ብቻ ነው እንጂ፤ ማቴ15÷26፡፡

ዳሩ ግን ሰው እንዳሰበው አልሆነም፤ በቃሉ የጠራቸውን ሦስቱን ድንጋዮች እንዲበቁ አደረጋቸው፤ እርሱ ይበቃል ያለው ይበቃል፤ የከለከለው ደግሞ ወርቅም ቢሆንም ተልጦ ይወድቃል፡፡ ሲፈቀድለት ጣዖት አጣኙ የሞዓብ ልጅ የእግዚአብሔር ካህን ሆኖ ተሾመ፤ ባይፈቀድለት የወርቁን ማዕጠንት በእጁ ይዞ የቃል ኪዳኑን ታቦት ሲያጥን የኖረው የአሮን ልጅ ተከለከለ፤ የእግዚአብሔር ሥራው ድንቅ ነው፡፡

የመጀመሪያው ቤተ መቅደስ ለምን በአሕዛብ ከተማ ተሠራ? አሕዛብ አማልክቶቻቸው ብዙ፣ አጋንንቶቻቸው ብዙ ናቸው፤ ቅዱስ ኤፍሬም እንደተናገረው ኃጢአት ብትበዛባቸው፤ ጸጋ እግዚአብሔር በዝታላቸው ብዙ ነገሮችን ከእስራኤል ቀድመው አግኝተዋል፡፡ ከአዳም ቀድሞ ገነት የገባው ፈያታዊ ዘይማን ከአሕዛብ ወገን ነበር፤ እስራኤል ሞትን ለፈረዱበት ጌታ ምንም እንኳን ማዳን ባይቻለውም ብቻውን የተከራከረለት ጲላጦስም ከአሕዛብ ወገን ነበር፡፡ የመጀመሪያውን የቡራኬ ሥራም የጀመረው በአሕዛብ ሀገር በግብፅ ገዳማት በገዳመ አስቄጥስ ነው፡፡ ለአሕዛብ ምን ያልተደረገ ምን አለ? ይህን ታሪካዊ ቤተ መቅደስም በቤተ አይሁድ መካከል የሠራው አይደለም፤ በአሕዛብ መካከል እንጂ፡፡

ቤተ ክርስቲያን በምኩራብ ማኅፀን ውስጥ ተፀንሶ የቆየ ፅንስ እንጂ አዲስ አይደለም፡፡ ሆኖም ግን የፀነሰችው ምኩራበ አይሁድ ወልዳ መሳም ሳትችል ቀረች፤ ምክንያቱም እንደ ተወለደ በእስራኤል እንቢተኝነት ምክንያት ወደ አሕዛብ ስለገባ ነው፤ ሕንፃው በቅድስቲቷ ምድር ኢየሩሳሌም ሳይሆን ቀረ፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው በረከቱን ከእስራኤል እንዳራቀ፣ ክብራቸውን ወደ አሕዛብ እንደተነጠቀ ለማሳየት ነው ፡፡

አብርሃም በራዕይ የተመለከታቸው በምድራዊ አሸዋ የተመሰሉ ልጆቹ የሰማዩን ተስፋ፣ የቃል ኪዳኑን ምድር እንዲወርሱ የተወለዱለት በዚህ ጊዜ ነው፤ ዘፍ 22÷17፡፡ እንደ ባሕር አሸዋ የመንፈስ ቅዱስ ሙቀት የሌላቸው ቀዝቃዞች፣ በምድር እንጂ በሰማይ እንዳሉት ከዋክብት በላይ ለመኖር ያልታደሉ ብርሃን አልባ ድንጋዮች ናቸው፡፡ ዛሬ ግን ከከበረ የአልማዝ ድንጋይ ይልቅ ያበራሉ፤ ድንጋይነታቸውን እንዳልናቀባቸው ለማስረዳትም በመካከላቸው የመጀመሪያውን ቤተ መቅደስ በድንጋይ ሠርቶ አሳየ፡፡ ለካ ድንጋይም አናጢዎች የናቁት ድንጋይም ለአገልግሎት ይፈለጋል ብለው እምነታቸው እንዲፈጸምላቸው ነው እንጂ ሌላ ምንድነው? ያልታሰቡትን ድንጋዮች ባንድ ቀን ለቤቱ እንዲበቁ አደረጋቸው::

በዚያውም ላይ እግዚአብሔር ሲፈቅድ የቀደሙት ኋለኞች፣ ኋለኞች ደግሞ ፊተኞች ይሆናሉ፤ ቀድመን ወንጌሉን ማወቃችን፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከፍተኛውን የሥልጣን ሥፍራ መያዛችን፣ በቤተ መቅደሱ ማደጋችን ብቻውን ያጸድቀናል የሚመስላቸው ብዙ ወገኖቻችን ናቸው:: በወንጌል ውስጥ ብዙ ኋለኞች ፊተኞች የሆኑ ሲሆን ብዙ ፊተኞች ደግሞ ኋለኞች ሆነዋል፡፡

ቤተ መቅደሱ በእመቤታችን ስም ለምን ተሰየመ? የመጀመሪያው የመላዕክት የምስጋና መሥዋዕት በምድር ላይ የቀረበበት ቤተ መቅደስ ማኅፀነ ማርያም ለመሆኑ ብዙ ማስረጃ መጥቀስ ይቻላል፡፡ አረጋዊ መንፈሳዊ የተባለው የቤተ ክርስቲያናችን ሊቅ “ድንግል አጽነነት ርዕሳ መንገለ ከርሣ ከመ ትስማ ቃለ እመላዕክት፤ ድንግል ከመላዕክት ቅዳሴን ልትሰማ ራሷን ወደ ሆዷ ዘንበል ታደርግ ነበር” በማለት የእመቤታችንን ማኅደረ ቅዳሴነት ይናገራል፤ ጌታችን የሚፀነስበት ወራት በደረሰ ጊዜስ እመቤታችን ከቤተ መቅደስ እንድትወጣ መደረጉ ለምን ይመስላችኋል፤ ቤተ መቅደስ በቤተ መቅደስ ውስጥ መኖር ስለሌለበት እኮ ነው፡፡ በዚያውም ላይ ያኛው ቤተ መቅደስ የሌቦች ዋሻ የወንበዶች መዳረሻ ሆኗል፤ ብቸኛዋ የእግዚአብሔር ከተማ ድንግል ከዚያኛው ጋር ምን ሕብረት አላትና በዚያ ሳለች ትፅነሰው?

ከአይሁድ ቤተ መቅደስ አውጥቶ ቤተ መቅደስ አደረጋት፤ በቤተ መቅደስ ትሰማው የነበረውን የመላእክት ዜማ አሁንም በሆዷ ውስጥ ትሰማው ነበር የምድራውያኑን ካህናት ቅዳሴ በሰማዩ ካህናት ቅዳሴ ለውጣዋለች:: ይህን ለመግለጽ ነው እንግዲህ ቤተ መቅደሱን ከሦስት ድንጋዮች ሠርቶ ሲጨርስ በሰኔ በሃያ አንደኛው ቀን ከሰማያት ወርዶ ቤቱን በእናቱ ስም ሰይሞ ቆርቦ እሷንም እነሱንም አቁርቧቸዋል::

አሕዛብ በሥላሴ ለማመናቸው ምክንያት የሆነች እርሷ ናት እንጅ ሌላ ማን አለ፤ ቅዱስ ኤፍሬም እንደ ተናገረው “ለሥላሴ ስግደትን የምታስተምርላቸው” ድንግል ማርያም ናት በኦሪትና በነቢያት ከተገለጠው ይልቅ የእግዚአብሔር ምሥጢር በዝቶ የተገለጠው ጌታ ከእመቤታችን ከተወለደ በኋላ ነውና፤ በዚያውስ ላይ አሕዛብን ማን ፈልጓቸው ያውቅ ነበር፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ጌታን በእቅፏ ይዛላቸው በከተሞቻቸው መካከል የተገኘች እርሷ እኮ ናት፡፡ ድንጋዮቹ አሕዛብ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንዲሆኑ እመቤታችን ምክንያታቸው ናት፤ ስለዚህ ቤቱ በእርሷ ስም ተሰየመ፡፡ አሁን ሁላችንም እንደ ሐዋርያው ቃል የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ለመሆናችን ምንም ጥርጥር የለንም 1ኛ ቆሮ3÷16፡፡ እግዚአብሔር “መንፈሴ በሰው ላይ ለዘለዓለም አይኖርም እርሱ ሥጋ ነውና” ዘፍ6÷3 ብሎ የማለውን መሀላ እንዲረሳና በሰው ላይ እንዲያድር ሰውም ቅዱስ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ወደ መሆን እንዲያድግ ከእመቤታችን በስተቀር ሌላ ምን ምክንያት አለው፡፡

አምላካችን በድንጋይ ልብ ውስጥም ይመሰገናል ማለትም በአሕዛብም ዘንድ ቅዳሴው አይቋረጥበትም፤ ይህን ስጦታዋን በሰዎች መካከል ሲገልጽላት እግዚአብሔር ቤተ መቅደሱን በስሟ ሰይመላት፤ ከዚያም በኋላ የተነሡ መምህራን ይሄን መነሻ በማድረግ በዐራቱም መዐዝን ወንጌልን ሰብከው ብዙ የመታሰቢያ ቤቶችን በስሟ ከመሥራታቸውም በተጨማሪ ስሟን ለምዕመናን ስም እንዲሆን ፈቅደውላቸው እንዲጠሩበት አድርገዋል፡፡ በነቢይ ስለ እርሷ የተባለውም በዚህ ተፈጽሞላታል “ወይዘክሩ ስመኪ በኩሉ ትውልደ ትውልድ፤ ስምሽን ለልጅ ልጅ ያሳስቡልሻል” መዝ 44÷17፡፡

 

ልሳነ አርድእት

 ሰኔ 19 ቀን 2006 ዓ.ም.

በመ/ር ደሴ ቀለብ
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፊሎሎጂ መምህር

ክፍል ፩

የግእዝ ቋንቋ እድገት ከየት ወዴት?

አንዲት ሀገር የራሷ የሆነው ባህሏ /ሥርዓቷ/ የሚያኮራትና ማንነቷንም የሚያንጸባርቅ በመሆኑ ልትጠብቀውና ከትወልድ ወደ ትውልድ ልታስተላልፈው የባለቤትነት ግዴታዋ ነው፡፡ በመሆኑም ሀገራችን ኢትዮጵያን ለጥቁር ሕዝቦች መኩሪያ እንድትሆን ያደረጋት የልጆቿ ሀገር ወዳድነትና ጀግንነትን የተመላው ባህሏ ብቻ ሳይሆን የሃይማኖት፤ የሥነ ፊደል ሀገር መሆኗም መጻሕፍተ ታሪክን ባነበቡ ሊቃውንት አንደበት ብቻ ሳይሆን በማዳመጥ ትውፊት /ርክክብ/ ለኅብረተሰቡ ኀቡእ ያልሆነ ነገር መሆኑ ነው ፡፡

በተጨማሪም ሀገራችን ኢትዮጵያ የዘመናት ዑደት ስፍር ቀምራ የራሷን አኀዝ ያደላደለች አፍሪካዊት እመቤት ናት ብንል ጽልመት ሊጋርደው የማይችለው ገሀድ ነው፡፡

ይሁን እንጂ እኛ ልጆቿ የትናንቱን ለዛሬ ማበርከት ያልቻልን ይመስላል፡፡ ለዚህም ነው ትናንት የኢትዮጵያ መሠረተ ቋንቋ የነበረው የግእዝ ቋንቋ ከነበረበት የብሔራዊና የውል ቋንቋነት ይቅርና ዛሬ ዛሬ የት ገባ ሊባል የሚያሳፍር ሆኗል፡፡ አበው ለብዙ ዘመናት ይህን ቋንቋ በዜማ ቤቱ፣ በቅኔ ቤቱና በመጻሕፍት ቤቱ እንዳልተጠቀሙበት ሁሉ ዛሬ ግን የአበው ያለህ ብንል፤ አይደለም መግባባት ይቅርና ገና ተማሪው እንኳን ከማለዳው “ኦኾ” /እሽ/ በማለት ፈንታ “ኦኬ” ቢል ይቀድመዋል ፡፡ ይህ ግን “የቆጡን አወርድ ብላ የብብቷን ጣለች” ሳያሠኝ አይቀርም ፡፡

እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ ታሪክ መረጃ ሥነ ሐውልቶች የተሸከሙት የግእዝ ቋንቋ ሥነ ጽሑፍ የሀገራችንን ጥንተ ታሪክ የሚያስረዳ መሆኑን ታሪክ ይመሰክራል፡፡ የግእዝ ተፎካካሪ የነበረው የሳባዊያን ቋንቋም በግእዝ ተልቆ /ተበልጦ/ ግእዝ የኢትዮጵያ ነገሥታት ሊቃውንት ኅብረተሰብ መግባቢያ ከመሆኑም አልፎ ከሀገር ውጭም ኢትዮጵያ ሀገረ ፊደል፣ ሀገረ አሚን መሆኗን ያስመሰከረ ልሳን ነበር፡፡ የሆነው ሆኖ ቀድሞ ከ፯ ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ እየተጠናከረ መሄዱ በሚነገርለት በአማርኛ ቋንቋ መሆኑ ቀርቶ በቤተ ክርስቲያንና በተወሰነው የኅብረተሰብ ክፍል ዘንድ እየተገደበ መጣ፡፡ እንዲያውም በተለይ በዘመነ ዓምደጽዮን / ከ፲፫፻፯-፲፫፻፴፯ ዓ.ም./ የንጉሡ ገድል ሁሉ የሚጻፈው በተሰባበረ አማርኛ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ለአብነት ያህል የሚከተለውን ማየት ይቻላል፡፡ 

  • ሐርልኛ ዓመደ ጽዮን
  • መላለሸ የወሰን
  • ወሀ እንዳመሰን መላላሽ የወሰን
  • ከወጅ ዜብደናን ከገንዝጠጠን
  • ምንቀረህ በወሠን ከድያ አምኖን

በተጨማሪም በዐፄ ይስሐቅ /ከ፲፬፻፯-፲፬፻፳፪ ዓ.ም./ ጊዜ ለንጉሡ የሚቀርቡት መወድሶች ከአማርኛው ላይ ያተኮሩ ይምስላሉ፡፡ ለምሳሌ ያህል፡-

  • ገጽዥን ይስሐቄ ገጽ
  • አርያም ይመስል አንቀጽ
  • እሳት ይመስል ብቁጽ
  • ከመ መደልው ልጽሉጽ
  • ገጹ እንዲያስደነግጽ
  • እስራኤላዊ መደንግጽ
  • ማን አየህ ገጽ በገጽ

 

እነዚህ ግጥሞች ግን እንደምናያቸው ሙሉ በሙሉ አማርኛ አልነበሩም፡፡ ለዚህም ነው ግዊዲ የተባለው የታሪክ ተመራማሪ “ግእዝ -አማርኛ” ጽሑፎች ብሎ የሚጠራቸው፡፡ በእርግጥ ከአማርኛው ላይ ግእዝ መደመር ለአሁኑ ትውልድም የቋንቋ ጣዕም የሥነ ጽሑፍ ቃና መሆኑ አወንታዊ ምላሽ አለው፡፡

ያም ሆኖ ግን ብዙ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የጽሕፈት ሥራቸውን ብራና ዳምጠው ቀለም በጥብጠው ይጠቀሙበት የነበረው በዚህ ቋንቋ መሆኑን አላገደውም፡፡ እንዲያውም በዘመነ ዘርዓያዕቆብ /፲፬፻፳፮-፲፬፻፷ ዓ.ም./ መስፋፋት የነበረበት የሥነ ጽሑፍ እድገት ግእዙን የሙጥኝ ያለ ነበር፡፡ በኋላም ቢሆን በዐፄ ሱስንዮስ / ከ፲፭፻፱፱-፲፮፻፳፬ ዓ.ም./ የሃይማኖት መለወጥ ምክንያት ጋር ተያይዞ ኢየሱሳውያን (Jesuites) ጉልህ ችግር ደርሶባት የነበረችውን የሮማ (ስፔን) ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ተከታዮችን ቁጥር ለማበርከት ሲሉ በአማርኛ በመጻፍ ወረቀቶችን ለመበተን ቢሞክሩም የአንድ ባሕርይ አማኝ የሆነው ዐፄ ፋሲል / ከ፲፮፻፳፬ -፲፮፻፸፬ ዓ.ም/ በመንገሥ የምእመናኑን ፍጹም ቀናዒነት ብሎም የኢየሱሳውያን ከኢትዮጵያ ምድር መውጣት ለልሳነ ግእዝ እንደገና መወለድ መስፋፋት ሆነለት፡፡ ብዙም መጻሕፍተ ግእዝ ተደረሱ፡፡ የቅኔ እድገትም ታየ፡፡ ከዐፄ ፋሲል በኋላም ነገሥታቱ ታላቅ ተሳትፎአቸውን አበርክተዋል፡፡ ስለሆነም ዐፄ ኢያሱ አድያም ሰገድ /ከ፲፮፻፸፬ -፲፮፻፱፱ ዓ.ም./ እና ሌሎችም ነገሥታት የማይጠፋ ስማቸውን በልቡናችን ቀረጸው አልፈዋል፡፡

ዳግመኛ የ፲፮ኛው እና የ፲፯ኛው ክፍለ ዘመናት ቁስር አልሽር ብሎ እንደገና በመሳፍንቱ ዘመን /ከ፲፯፻፸፯-፲፰፻፵፭ ዓ.ም/ ሀገሪቱ እርስ በርሷ በፖለቲካና በሃይማኖት ድልቅልቅ ስትዋጥ ሀገርን አንድ ማድረግ ይችል የነበረውን ነገረ-ሃይማኖት ለመረዳትና ለመወሠን ሊቃውንቱ የግእዝን መጻሕፍት ማገላበጥ ግድ ሆነባቸው፡፡ የመነጋገሪያ /የመከራከሪያ/ ምሥጢራቸው የሆነው ቅኔም ለልሳነ ግእዝ መስፋፋት ጠቀመ፡፡ የአብነት ትምህርት ቤቶችም ተስፋፉ፡፡ ፍጹም የሆነ አንድነትም ታዬ፡፡ ዛሬስ የሃይማኖት ውዝግቡን የሚፈቱት የትኞቹ እውን መጻሕፍት ይሆኑ? በእርግጥ ዛሬ ግእዝ ያወቀው ሁሉ ነገረ ሃይማኖትን ተረዳ ማለት አይደለም፡፡ የሚማረውም ለሕይወት /ለፍቅር/ ወይም ታሪክን ለማወቅ ላይሆን ይችላል፡፡ ነበርኩ ለማለትና ክዶ ለማስካድ እንዲመቸው የሚያስብም አይጠፋምና፡፡ በየዋህነት መማር ግን በአማናውያኑ አበው ቀርቷል፡፡

እንግዲህ ለግእዝ ቋንቋ መዳከም ዐቢይ ምክንያት የአማርኛ መተካት ብቻ ሳይሆን ለቋንቋው የሚሰጠው ትኩረት መላላቱ የማያወላውል ምክንያት መሆኑ ነው፡፡ ዝም ብሎ ግን ቅርስ ቅርስ ማለት ብቻ ዋጋ የለውም፡፡ “ባዶ ብራና” ካልተነበበ ምን ሊሠራልን፡፡ በተጨማሪም መንግሥትም ሆነ ማንኛውም አካል ግእዝ የቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ ቅርስ መሆኑን ሊገነዘበው ይገባል፡፡ ቤተ ክህነትም ብትሆን የእነ ቅዱስ ያሬድ የዜማ መጻሕፍት እነ ድጓ፣ የዚቅ ቀለማት፤ የእነ አባ ጊዮርጊስ መጻሕፍት ፣ እነ ሰዓታት በሌላ ቋንቋ ሊዜሙ “ይቻል” ይመስል ለግእዝ የሚሰጠው እንክብካቤ ያሳዝናል፡፡

ድሮ ድሮ የቆሎ ተማሪ ለምኖ አኮፈዳውን፤ ዳዊቱን አንግቦ የሚነጋገረው በዚህ ቋንቋ ነበር፡፡ እንደዛሬው ግን ለወደፊቱ አይደለም የሚነጋገር አባባሉን የሚያጠና /የሚቀጽል/፣ በደንብ ቅኔ የሚቀኝ ይቅርና ዳዊቱን አጣርቶ መድገሙም ራሱ ያጠራጥራል፡፡ በእርግጥ በአንዳንድ የገጠር ቦታዎች የሚያስተምሩ ብዙ የሊቃውንት በረከቶች ቢኖሩም፤ ነገ የሚተካው ግን ከግእዝ ይልቅ ጣሊያንኛ፣ እንግሊዝኛ፣ ፈረንሳይኛ ብቻ ቢማር የሚያተርፈው ይመስለዋል፡፡ ይህ ግን “አባቱን አያውቅ አያቱን ይናፍቅ” ያሠኛል፡፡

ምንጭ መጻሕፍቱ በግእዝ የሆነው የሀገራችን ታሪክንስ አንባቢና ተርጓሚ ማን ይሆን? በዚህ እኮ ነው የሀገራችንን ታሪክ ለማወቅ የውጭ መጻሕፍት ላይ ጥገኛ የምንሆነው፡፡ አንባቢውና ተርጓሚው አላዋቂ ከሆነ ደግሞ ታሪከ ሀገር ቅድምና ሀገር በምልዑ ልብ የማይመሰከርበት ይመስላል፡፡ የሚገርመው ግን ብዙዎቹ የግእዝ መጽሐፎቻችን በፈርንጆቹ ላይ የማያልቅ ፍቅርን አሳድረውባቸው ቋንቋውን እስከ ሃምሳ ዓመት ድረስ ሲያጠኑ እኛ ግን “የሞተ ቋንቋ” እንለዋለን፡፡ ቋንቋው ሞተ ከማለት ግን ታሪከ ሀገር ቅድምና ሀገር ሞተ ብንል ሳይሻል አይቀርም፡፡ ቢያንስ ቢያንስ በቤተ ክርስቲያን ለካህናቱ የምስጋናቸው አንደበት ግእዙ ነውና፡፡

እንግዲህ እናጠቃለውና ማንኛውም ክፍል /አካል/ ይህ ቋንቋ በጥንቱም ሆነ በአዲስ መልክ እንዲያድግ ጥረት ቢያደረግ፤ የቅኔ መምህራኑም የግእዝ መምህራኑም ምንም እንኳን የኑሮ ችግር ቢኖርም ለራስ የሚስማማ ቦታን ከመምረጥ ለተማሪዎች የሚስማማ ቦታን መርጦ በገጠርም ቢሆን ማስተማር ይኖርባቸዋል፡፡ የቋንቋ ምሁራንም ለዚህ እድገት አስተዋጽዖ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን በመካከለኛው ክፍለ ዘመን ላይ የጥንቱ ሰዋስው (Classical Grammar) ይምጣልን፣ ይመለስልን፤ መካከለኛው ክፍለ ዘመን የጨለማ ዘመን ነው እያሉ እንዳማረሩት ሮማውያንና ግሪካውያን እንዳንሆን ያስፈራል፡፡ ስለሆነም ሥርወ ቃላትን ለመመርመር ሰዋስውን ለመለየት ግእዝ ማወቅ ይጠበቅብናል፡፡ ለዚህም ታላላቅ ደራሲያን ምስክሮች ናቸው፡፡ በተረፈ ግን ሁላችንም የታሪክ፣ የሀገር፣ የወገን፣ የቅርስ ባለአደራዎች መሆናችንን አንዘንጋ፤ እንቅልፉም ይብቃን፡፡

ይቆየን

 

የደብረ ሊባኖስ ገዳም አምስቱ ስያሜዎች

 ሰኔ 17 ቀን 2006 ዓ.ም.

የደብረ ሊባኖስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንድነት ገዳም ገዳማዊ ሥርዓቱ እንደተጠበቀ ቢሆንም የጎርፍ አደጋ፤ የብዝኅ ሕይወት መመናመን፤ የሕገ ወጥ የመሬት ወረራና ሌሎችም ችግሮች እየተፈታተኑት ይገኛል፡፡ ይህንን ችግር ለመቅረፍና ዘላቂ መፍትሔ ለማምጣት በገዳሙና በማኅበረ ቅዱሳን ባለሙያዎች ፕሮጀክቶች ተቀርጸው ወደ ሥራ ተገብቷል፡፡ 

 

ፕሮጀክቶቹንም በተያዘላቸው እቅድ መሠረት ለማስፈጸም በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ሠኔ 8 ቀን 2006 ዓ.ም. የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ላይ ፕሮጀክቶቹንና ገዳሙን አስመልክቶ የተዘጋጀ መጽሔት ለምእመናን ተሰራጭቷል፡፡ ከመጽሔቱ ያገኘናቸውን ጥቂት መረጃዎች እናካፍላችሁ፡-

የደብረ ሊባኖስ አቡነ ተክለ ሃማኖት አንድነት ገዳም በኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ከአዲስ አበባ ወደ ጎንደር- ጎጃም መውጫ በ104 ኪሎ ሜትር ርቀት፤ ወደ ምሥራቅ አቅጣጫ 4.5 ኪሎ ሜትር ተገንጥሎ የሚገኝ የአንድነት ገዳም ነው፡፡
ገዳሙ በጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በ1296 ዓ.ም. የተቆረቆረ ሲሆን፤ 710 ዓመታትን አስቆጥሯል፡፡ በገዳሙ አስተዳደር ሥር ከአቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን በተጨማሪ የቅዱስ አማኑኤል እና የቅዱስ ፊልጶስ አብያተ ክርስቲያናት ይገኛሉ፡፡

በገዳሙ ውስጥ የሚጎበኙ የተለያዩ የነገሥታት ሥጦታዎች፤ ቅዱሳት መጻሕፍት፤ ንዋየ ቅድሳት፤ የቅዱሳን አጽም፤ ፈውስ የሚገኝባቸው የጸበል ቦታዎችም ይገኛሉ፡፡

የደብረ ሊባኖስ ገዳም አምስቱ ስያሜዎችን ስንመለከት፡-

ምድረ ግራሪያ፡-
ግራሪያ የሚለውን ስያሜ የሰጠችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከልጇ ከወዳጇ ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ወደ ምድረ ግብጽ ስትሰደድ በኢትዮጵያ ውስጥ ከቆየችባቸው ቦታዎች አንዱ ይህ ቅዱስ ቦታ ነው፡፡ ለአንድ ሳምንት ቆይታ አድርጋ የቦታውን ስም ምድረ ግራሪያ ስትል ሰይማዋለች፡፡ ግራሪያ ማለት ኩሉ ይገርር ሎቱ፤ ሁሉ ይገዛላታል ማለት ነው፡፡ አንድም ግራር በቁሙ ለሁሉ ጥላ፤ መሰብሰቢያ እንደሆነ ደብረ ሊባኖስም የሁሉ ጥላ መሰብሰቢያ ነውና ምድረ ግራሪያ ተብሏል፡፡

ደብረ አስቦ፡-
ደብረ አስቦ ማለት የዋጋ ተራራ ማለት ሲሆን፤ የሰየመውም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ አባታችን ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በዚህ ቅዱስ ሥፍራ ሃያ ዘጠኝ ዓመታት ከጸለዩ በኋላ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡ ቦታውንም ደብረ አስቦ፤ የድካምህ ዋጋ፤ የስምህ መጠሪያ ይሁንልህ በማለት ሰይሞታል፡፡

ኤላም፡-
ኤላም ማለት የእግዚአብሔር ክብር መገለጫ ማለት ነው፡፡ ይህ ቦታ የአባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት አጽም ለአርባ ዓመታት የቆየበት ቅዱስ ሥፍራ ነው፡፡ ስያሜውም የአቡነ ዮሐንስ ከማ ነው፡፡ ዮሐንስ ከማ የጻድቁ አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት የመንፈስ ልጅ ናቸው፡፡ ኤላም የበረከት ቦታ፤ የሰላም ሠፈር ነው፡፡ የመድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ተሰውሮ ይገኝበታል፡፡

ደብረ ሊባኖስ፡-
ደብረ ሊባኖስ ማለት የሊባኖስ ተራራ ማለት ነው፡፡ ጻድቁ አቡነ ሊባኖስ የተባሉት ሮማዊ አባት ለአርባ ዓመታት የጸለዩበት፤ ብዙ ገቢረ ተአምራት ያደረጉበት፤ ከእግዚአብሔር ጋር የተገናኙበት ነው፡፡ “ትትሌአል ወትከብር እምነ ኲሎን አድባራት ወገዳማት እሞን ለአህጉር፤ ከአድባራትና ገዳማት ትከብራለች፤ ከፍ ከፍም ትላለች፤ ለሀገራትም እናት ትባላለች” ሲል፡፡

አባ ሊባኖስ በጌታ የተወደደውንና የቅዱሳን ከተማ ደብረ ሊባኖስን በጣም ይወዱት ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ይህ ቦታ ከአንተ በኋላ ለሚመጣው ለተክለ ሃይማኖት ነውና አንተ ወደ ትግራይ ሀገር ሒድ፤ እድል ፈንታህ በዚያ ነው አላቸው፡፡ እርሳቸውም አርባ ዓመታት የደከምኩበት ለከንቱ ነውን? አሉት ቅዱሳን አጽንኦተ በዓት ይወዳሉና፡፡ መልአኩም ስለ ድካምህ ይህ ቦታ ደብረ ሊባኖስ ይባላል እንጂ ደብረ ተክለ ሃይማኖት አይባልም አላቸው፡፡ እሳቸውም ፈቃድህ ይሁን ብለው ወደ ትግራይ ሀገር ሔዱ፡፡ እስከ ዛሬም ድረስ ደብረ ሊባኖስ እየተባለ ይጠራል፤ ስመ ተፋልሶም አላገኘውም፡፡

ዜጋዎ አመል፡-
ዜጋዎ አመል ማለት የአየር ንብረቱ የተመቸ፤ የሚያስደስት፤ ተስማሚና ለኑሮ የሚመች ማለት ነው፡፡ በዚህ ምክንያት ዜጋዎ አመል ተብሏል፡፡

ምንጭ፡- ልሳነ ደብረ ሊባኖስ፤ ቅጽ-1፤ ቁጥር-1፤ ሠኔ 2006 ዓ.ም.

 

 

 

 

 

 

የማቴዎስ ወንጌል

ሰኔ 16 ቀን 2006 ዓ.ም.

ምዕራፍ ሁለት 

በዚህ ምዕራፍ ውስጥ የምንረዳውና የምንገነዘበው ጌታ በይሁዳ ቤተልሔም በንጉሥ ሄሮድስ ዘመን እንደተወለደ እንረዳለን፡፡ ቤተልሔም ማለት ቤተ ኅብስት ማለት ነው፡፡ ስምዋም የተሰየመው ካሌብ ኤፍራታ የተባለች ሚስት አግብቶ ወንድ ልጅ ከኳ በወለደ ጊዜ እንጀራ እገባ እገባ ብሎት ስለነበር የልጁን ስም ልሔም /ኅብስት/ አለው፡፡ በልሔም ቤተልሔም ተብላለች፡፡

የጥበብ ሰዎች ከሩቅ ምሥራቅ መጥተው የበረከት ሳጥናቸውን ከፍተው ለጌታ ገጸ በረከት አበርክተውለታል፡፡

  • ወርቅ-ለመንግሥቱ

  • ዕጣን ለክህነቱ

  • ከርቤ- ለመራራ ሞቱ፡፡ ምሳሌ ናቸው፡፡

ሰብዓ ሰገል ከሄዱ በኋላ ጌታ ሄሮድስ ሊገድለው ስለሚፈልገው አስቀድሞ በነብያት በተነገረው መሠረት ወደ ግብፅ ተሰደደ ሆሴ.11፡1፡፡

ንጉሡ ሄሮድስም ጌታን ያገኘ መስሎት 144ሺ የቤተልሔም ሕፃናትን አስፈጅቷል፡፡ ከሔሮድስ ሞት በኋላ ጌታ ከስደት ተመለሰ የስደት ዘመኑ 3 ዓመት ከመንፈቅ ነበር፡፡ ራዕይ 12፡7፡፡

እድገቱንም በነቢያት አስቀድሞ እንደተነገረው በናዝሬት ከተማ አደረገ፡፡ ናዝሬት የወንበዴዎች የቀማኞች የተናቁ ሰዎች ከተማ ነበረች፡፡ ጌታም ወደ ተዋረድነው ወደ እኛ መጥቶ ከውርደት ሊያድነን መሆኑን ሊያስገነዝበን በናዝሬት ኖረ፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 3ኛ ዓመት ቁጥር 1 ታኅሥሥ 1988 ዓ.ም.

ማኅበረ ቅዱሳን በኦሮምኛ ቋንቋ የድረ – ገጽ አገልግሎት ሊጀምር ነው

ሰኔ 13 ቀን 2006 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

በማኅበረ ቅዱሳን የኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ዋና ክፍል የኦሮምኛ ድረ ገጽ አገልግሎት በቅርቡ እንደሚጀምር የዋና ክፍሉ ሓላፊ ዲያቆን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ ገለጹ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ዶግማ፤ ቀኖና እና ትውፊት የጠበቁ ትምህርቶችን በኦሮምኛ ቋንቋ በተለያዩ የመገናኛ ብዙኀን ዘዴዎች ለምእመናን ለማሰራጨት እቅድ ከያዘ መቆየቱን የገለጹት ዲያቆን ዶ/ር መርሻ፤ የድረ ገጽ አገልግሎቱ ቅድሚያ ተሰጥቶት ለምእመናን ተደራሽ እንደሚሆን አስታውቀዋል፡፡

በዚህም መሠረት “በጥቂት ሳምንታት ውስጥ የኦሮምኛ ድረ ገጽ አገልግሎት መስጠት የሚጀምር ሲሆን፤ ወደፊት የኅትመትና የብሮድካስት ዝግጅቶችን ለምእመናን ለማዳረስ ማኅበሩ ፕሮጀክቶችን ቀርጾ ተግባራዊ ያደርጋል” ብለዋል፡፡

የኦሮምኛ ዝግጅት ንዑስ ክፍል አስተባባሪ ዲ/ን መዝገቡ ከፍያለው ለኦሮምኛ ድረ ገጽ መከፈት ምክንያት ናቸው ያሏቸውን ሲገልጹ “በኦሮሚያ ክልል ምእመናን ስለ እምነታቸው በቋንቋቸው መማር አለመቻላቸው፤ በቋንቋው የተዘጋጁ ሃይማኖታዊ የኅትመትና የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ውጤቶች አለመኖር እና ምእመናን በሌሎች የእምነት ተቋማት መወሰዳቸው ነው” በማለት ጠቅሰዋል፡፡

እነዚህን ዘርፈ ብዙ ችግሮች ለመፍታት እና ያሉትን ምእመናን ለማጽናት፤ የጠፉትንም ለመመለስ እንዲቻል ከዐውደ ምሕረት ስብከት በተጨማሪ በመገናኛ ብዙኀን ዘዴዎች ወደ ምእመናን ለመድረስ አዲስ የተዘጋጀው ማኅበራዊ ድረ ገጹ አስተዋጽኦ ከፍተኛ እንደሆነ ታምኖበታል፡፡

በድረ ገጹም ትምህርተ ሃይማኖት፤ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፤ ነገረ ቅዱሳን፤ ስብከት፤ ለጥያቄዎች ምላሽ /ከምእመናን ለሚጠየቁ ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጥበት/፤ መዝሙር እና ኪነጥበብ ወዘተ. . . የተካተቱበት ሥራዎች እንደሚቀርቡ ዲ/ መዝገቡ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

የድረ ገጹ አድራሻ፡- www.eotcmk.org/afaanoromo

በተያያዘ ዜና ከዚህ ቀደም ተቋርጦ የነበረው የእንግሊዝኛ ድረ ገጽ በቅርቡ የሚጀምር ሲሆን፤ የድረ ገጹ አድራሻ፡- www.eotcmk.org/site-en መጎብኘት ይቻላል፡

 

 

ቅድስት አፎሚያ

ሰኔ 12 ቀን 2006 ዓ.ም.

በመ/ር ፍቃዱ ሣህሌ

በወርኃ ሠኔ መታሰቢያ ከሚደረግላቸው ቅዱሳን መካከል እግዚአብሔርን የሚፈራ የአስተራኒቆስ ሚስት የሆነች የቅድስት አፎምያን ታሪክ በአጭሩ እንዳስሳለን፡፡

 

ቅድስት አፎምያ በትዳር በነበረችባቸው ዘመናት እግዚአብሔርን ከሚወድ ባለቤቷ ጋር እግዚአብሔርን ስታገለግለው የኖረች ሴት ነበረች፡፡ በየወሩ በ29 ቀን የጌታችንን የልደቱን፣ ወር በገባ በ21 የእመቤታችንንና ወር በገባ በ12 የቅዱስ ሚካኤልን መታሰቢያ እያደረጉ ነዳያንን ይጎበኙ እንደነበር ታሪካቸው ይነግረናል፡፡

 

ባለቤቷ አስተራኒቆስ ከዚህ ዓለም የሚያርፍበት ጊዜ እንደደረሰ ባወቀ ጊዜ ይሰጡት የነበረውን ምጽዋት እና የሦስቱን በዓላት መታሰቢያ ማድረግ እንዳታስታጉል ከአደራ ጋር አዘዛት፡፡ እሷም የመልአኩን የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕል ያሥልላት ዘንድ ባለቤቷን ጠይቃ አሠርቶ ሰጣት፡፡ በከበረ ቦታም አኖረችው፡፡

 

ባሏ ካረፈ በኋላ ያዘዛትን መንፈሳዊ ሥራ ከወትሮው አስበልጣ መሥራት ቀጠለች፡፡ የሰው ልጆች ጠላት የሆነው ሰይጣንም በመልካም አገልግሎት ስትበረታ ባያት ጊዜ ዝም ብሎ ሊተዋት አልወደደም፡፡ በመጀመሪያ ባል ሳታገባ ማገልገሏን ትታ፣ ሌላ ባል አግብታ፣ ልጅ ወልዳ እንድትኖር በብዙ ማባበል ጠየቃት፡፡ ባሏ መንግሥተ ሰማያትን ስለወረሰ ምንም ምጽዋት እንደማይሻ አስመስሎ ነገራት፡፡

 

ቅድስት አፎምያ ግን ዳግመኛ ትዳር ላለመመሥረት ቃል ኪዳን እንደገባች ርግብንና ዖፈ መንጢጥን አብነት አድርጋ፤ እነሱ እንኳ በሕይወት ዘመናቸው ከአንድ ባል ውጪ ሌላ ባል እንደማያውቁ በመጥቀስ አሳቡን እንደማትቀበለው ገለጸችለት፡፡ ሰይጣንም አስመሳይ መሆኑ አላዋጣ ሲለው ማንነቱን ቀይሮ ሊያንቃት ቢሞክር የእግዚአብሔርንና የቅዱስ ሚካኤልን ስም ጠርታ አባረረችው፡፡ እሱም ተመልሶ መጥቶ እንደሚያጠፋት ዝቶባት እንደአቧራ በኖ፤ እንደ ጢስም ተኖ ጠፋ፡፡

 

በሠኔ ፲፪ ቀን የቅዱስ ሚካኤልን መታሰቢያ እያዘጋጀች ሳለች ሰይጣን ብርሃናዊ መልአክ መስሎ መጣ፡፡ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል እንደሆነ ገልጾ የመጀመሪያውን የመሰለ ከንቱ ምክሩን አሰማምሮ አቀረበላት፡፡ አሳቡንም የእግዚአብሔር ፈቃድና አሳብ እንደሆነ አድርጎ ለማሳመን ሞከረ፡፡ ሰይጣን አስቀድሞ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በገዳመ ቆሮንቶስ መጻሕፍትን እየጠቀሰ እንደተፈታተነው ሁሉ ቅድስት አፎምያንም ለማሳመንም አብርሃምን፣ ይስሐቅን፣ ያዕቆብን፣ ዳዊትን የመሳሰሉ ደጋግ አባቶችን ታሪክ እየጠቀሰ ወደ ትዳር እንድትገባ ደጋግሞ ወተወታት፡፡

 

ቅድስት አፎምያም በእግዚአብሔር ኃይል ጸንታ በቅዱስ ሚካኤልም ተራዳኢነት ታምና “የእግዚአብሔር መልአክ ከሆንክ መንፈሳዊ ማረጋገጫህ የሆነው የመስቀል ምልክት የታለ?” በማለት በምድራዊ ንጉሥና በጭፍራው መካከል የሚኖርን የጋራ መግባቢያ መንገድ ዋቢ አድርጋ ጠየቀችው፡፡

 

ለጊዜው “በኛ በመላእክት ዘንድ እንዲህ አይደለም” ብሎ ሊሸነግላትና አቋሟን ሊያስቀይራት ሞከረ፡፡ ከቤቷ ያለ የቅዱስ ሚካኤል ሥዕል ላይ ያለውን ምልክት አብራርታ የእሱ ግን ከዛ ጋር አንድነት እንደሌለው አረጋገጠችበት፡፡ ከቤቷ ላለው ለቅዱስ ሚካኤል ሥዕል እጅ እንዲነሣ ጠየቀችው፡፡ በዚህ ጊዜ መልኩ ወደ ትክክለኛ ማንነቱ ተለወጠና ጨለማ ለብሶ እየዛተ አነቃት፡፡ ቅድስት አፎምያም የከበረ መልአክ ቅዱስ ሚካኤልን “ድረስልኝ” እያለች በጠራችው ጊዜ መልአኩም ፈጥኖ በመድረስ ከሰይጣን እጅ አዳናት፡፡

 

የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልም ለሰይጣኑ ተገቢውን ቅጣት ሰጥቶ ቅድስት አፎምያን ባረካት፡፡ የዕረፍት ቀኗ በዚህ ቀን መሆኑን ነግሮ ቤቷን እንድታዘጋጅ አዘዛት፡፡ የበዓሉን ዝግጅት አከናውና ሥጋ ወደሙን ተቀብላ ኤጲስ ቆጶሱንና ካህናቱን እንደየመዓርጋቸው ጠርታ በቤቷ አክብራ ተቀበለቻቸው፡፡ ለነዳያንና ለጾም አዳሪዎች በኤጲስ ቆጶሱና በካህናቱ እጅ ገንዘቧን መጽውታ መንገዷን አሳመረች፡፡ ስለ ኃጢአቷ እንዲጸልዩላት ተማፅና በፊታቸው ተንበርክካ ጸለየች፡፡ ባሏ ያሠራላትን የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕል አቅፋ ስማ ከተማጸነች በኋላ ሠኔ ፲፪ ቀን በሰላም ዐረፈች፡፡

 

ይህች የታመነች ቅድስት አፎምያ በሰላም እስክታርፍ ጊዜ ድረስ የተጓዘችበትን መንፈሳዊ ጎዳና አስተውለን ይሆን? አስቀድማ ከባሏ ጋር አንድ ሆና በታማኝነት ፈጣሪዋን አገለገለችው፡፡ በኋላም የባሏን ኑዛዜ አክብራ ምንም እንኳን ኃጢአት ባይሆንባትም በሁለተኛ ትዳር ራስዋን ማጠላለፍ አልፈለገችም፡፡ በጎ ሥራ አብልጣ በመሥራት እግዚአብሔርን ደስ ለማሰኘት ተፋጠነች እንጂ፡፡

 

ሰይጣን ልጅ አለመውለዷን ተጠቅሞ ያቀረበላትን የጋብቻ ጥያቄ ውድቅ በማድረግ “መንፈስን ሁሉ አትመኑ፤ መናፍስት ከእግዚአብሔር እንደሆኑ መርምሩ” ተብሎ በቅዱሳት መጻሕፍት የታዘዘውን መመሪያ ተጠቅማ ሰይጣንን በተወክሎ እግዚአብሔር ተቃውማ አሸነፈችው፡፡ የቅዱስ ሚካኤልን ርዳታ ያገኘችውና በሰላም ዐርፋ ወዳገለገለችው እግዚአብሔር በክብር የሔደችው በጽናት ተጋድላ ነው፡፡

 

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፤ እኛንም በጸሎቷ ይማረን፤ የቅዱስ ሚካኤል የረድኤቱ ኃይል ሁላችንንም ይጠብቀን፣ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡ 

ምንጭ፡- ስንክሳር ዘወርኃ ሰኔ፣ ድርሳነ ሚካኤል ዘወርኃ ሰኔ