ለማእከላት ሓላፊዎች የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና ተሰጠ

 

ሰኔ 12 ቀን 2006 ዓ.ም.

በሕዝብ ግንኙነት አገልግሎት

ማኅበረ ቅዱሳን ለማእከላት፤ ለማስተባበሪያ ጽ/ቤት ሓላፊዎችና አስተባባሪዎች ከሰኔ 10- 11 ቀን 2006 ዓ.ም. ሁለት ቀናት የቆየ የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና ሰጠ፡፡

በሥልጠናው ከሀገር ውስጥና ከውጪ የተውጣጡ የ25 ማእከላት ጸሐፊዎች፤ የማስተባበሪያ ጽ/ቤት ሓላፊዎች፤ የግቢ ጉባኤያት አስተባባሪዎችና መምህራን መካፈላቸውን የማኅበረ ቅዱሳን የሰው ሀብት ሥራ አመራርና ጠቅላላ አገልግሎት ክፍል ሓላፊ አቶ ዳንኤል ተስፋዬ ገልጸዋል፡፡

ለሁለት ቀናት የቆየው ሥልጠና የግንኙነት ክህሎትን ማዳበር፤ የመረጃ አያያዝና አጠቃቀም እና የሕዝብ ግንኙነት አገልግሎትን ያካተተ ሲሆን፤ ሠልጣኞች የተሻለ አገልግሎት ለማበርከት እንደሚረዳቸው አቶ ዳንኤል ተናግረዋል፡፡
ሠልጣኞቹ በበኩላቸው ለሁለት ቀናት የተሰጣቸው ሥልጠና በአገልግሎት ላይ የሚታዩ ክፍተቶችን የሚሞላ ከመሆኑም ባሻገር፤ ከአባቶችና ከምእመናን ጋር ያላቸውን ግንኙነት ለማጠናከር እንደሚያግዛቸው ጠቁመዋል፡፡

ከሥልጠናው ጋር በተያያዘም የልምድ ልውውጥና ውይይት ተደርጓል፡፡

ሥልጠናውን በማኅበረ ቅዱሳን የሰው ሀብት ሥራ አመራርና ጠቅላላ አገልግሎት፤ የሀገር ውስጥ ማእከላትና የግቢ ጉባኤያት ማደራጃና ማስተባበሪያ ዋና ክፍል አዘጋጅተውታል፡፡

 

ለማእከላት ሓላፊዎች የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና ተሰጠ

 

ሰኔ 12 ቀን 2006 ዓ.ም.

በሕዝብ ግንኙነት አገልግሎት

ማኅበረ ቅዱሳን ለማእከላት፤ ለማስተባበሪያ ጽ/ቤት ሓላፊዎችና አስተባባሪዎች ከሰኔ 10- 11 ቀን 2006 ዓ.ም. ሁለት ቀናት የቆየ የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና ሰጠ፡፡

በሥልጠናው ከሀገር ውስጥና ከውጪ የተውጣጡ የ25 ማእከላት ጸሐፊዎች፤ የማስተባበሪያ ጽ/ቤት ሓላፊዎች፤ የግቢ ጉባኤያት አስተባባሪዎችና መምህራን መካፈላቸውን የማኅበረ ቅዱሳን የሰው ሀብት ሥራ አመራርና ጠቅላላ አገልግሎት ክፍል ሓላፊ አቶ ዳንኤል ተስፋዬ ገልጸዋል፡፡

ለሁለት ቀናት የቆየው ሥልጠና የግንኙነት ክህሎትን ማዳበር፤ የመረጃ አያያዝና አጠቃቀም እና የሕዝብ ግንኙነት አገልግሎትን ያካተተ ሲሆን፤ ሠልጣኞች የተሻለ አገልግሎት ለማበርከት እንደሚረዳቸው አቶ ዳንኤል ተናግረዋል፡፡

ሠልጣኞቹ በበኩላቸው ለሁለት ቀናት የተሰጣቸው ሥልጠና በአገልግሎት ላይ የሚታዩ ክፍተቶችን የሚሞላ ከመሆኑም ባሻገር፤ ከአባቶችና ከምእመናን ጋር ያላቸውን ግንኙነት ለማጠናከር እንደሚያግዛቸው ጠቁመዋል፡፡

ከሥልጠናው ጋር በተያያዘም የልምድ ልውውጥና ውይይት ተደርጓል፡፡

ሥልጠናውን በማኅበረ ቅዱሳን የሰው ሀብት ሥራ አመራርና ጠቅላላ አገልግሎት፤ የሀገር ውስጥ ማእከላትና የግቢ ጉባኤያት ማደራጃና ማስተባበሪያ ዋና ክፍል አዘጋጅተውታል፡፡    

   

 

 

Gubae Kana

ጉባኤ ቃና

Gubae Kana

debre libanose

የደብረ ሊባኖስ ገዳምን ለመታደግ ጥሪ ቀረበ

 ሰኔ 10 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

debre libanoseየደብረ ሊባኖስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንድነት ገዳም ያጋጠሙትን በርካታ ችግሮች ለመታደግ ዘላቂ መፍትሔ መሻት እንደሚገባ ሰኔ 8 ቀን 2006 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ በተካሔደ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ጥሪ ቀረበ፡፡

debre libanose 2006 2ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ የሰሜን ሸዋ ሰላሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ገዳሙ ያለበትን ችግር አስመልክቶ ሲገልጹ “የደብረ ሊባኖስ ገዳም የኢትዮጵያዊያን ሁሉ ገዳምና ሀብት ነው፡፡ ገዳምነቱን ሊሸረሽሩ የሚችሉ በርካታ ችግሮች አጋጥመውታል፡፡ እነዚህን ችግሮች ለመፍታትና የአባቶች የጸሎት ቦታ ተጠብቆ እንዲቆይ በርካታ ሥራዎች እየተሠሩ ስለሆነ ምእመናን ድጋፍ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል” ብለዋል፡፡

የገዳሙ አስተዳዳሪ ፀባቴ አባ ወልደ ማርያም አድማሱ የጉዳዩ አሳሳቢነትና ሊወሰድ ስለሚገባው አፋጣኝ መፍትሔ ሲያብራሩ “ገዳሙ ጊዜ የማይሰጥ፤ የቤተ ክርስቲያኑን ሕልውና የሚፈታተኑ በርካታ ችግሮች ከፊት ለፊት ተደቅነውበታል፡፡ ከተራራማው አካባቢ ወደ ታች በሚወርደው ጎርፍ መሬቱ እየተንሸራተተና እየተሰነጠቀ ነው፡፡ የገዳማውያኑና የምእመናን ቦታዎች ያለመለየት፤ ሕገ ወጥ የመሬት ወረራ፤ የገዳሙ ወደ ከተማነት እየተቀየረ መምጣት፤ የአካባቢያዊ ንጽሕና መጓደልና ሌሎችም ችግሮች አሉብን” ሲሉ ገልጸዋል፡፡፡

ገዳሙ ገዳማዊ ሕይወቱን ጠብቆ እንዲዘልቅ በማኅበረ ቅዱሳን ባለሙያዎች ጥናት ተካሒዶ፤ ፕሮጀክቶች ተቀርጸው ሥራዎች እየተሠሩ እንደሚገኙ የሚናገሩት ፀባቴ አባ ወልደ ማርያም፤ በተዘጋጀው ፕሮጀክት መሠረት የመጸዳጃ ቤትና የጎርፍ መከለያdebra libanose 2006 1 ግንባታ በማከናወን ላይ እንደሚገኙ ያስረዳሉ፡፡ ምእመናን ይህንን በመረዳት የታቀዱት ፕሮጀክቶች ጊዜያቸውን ጠብቀው እንዲተገበሩም የበኩላቸውን ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በደብረ ሊባኖስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንድነት ገዳም ሊተገበሩ የታቀዱት 11 ፕሮጀክቶች መሆናቸውን በመጥቀስ ለጉባኤው በዝርዝር ያቀረቡት ኢንጂነር ዮናስ ምናሉ እስካሁን ድረስ ኣፋጣኝ እርምጃ ባለመወሰዱም በጎርፍ ዐራቱ ተግባር ቤቶች፤ የመናንያኑ መኖሪያዎች፤ እንዲሁም ድልድዩ ጉዳት እንደደረሰባቸውና፤ የቤተ ክርስቲያኑንም መሠረት እየቦረቦረው እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡

በገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብሩ ላይ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የአድባራት አስተዳዳሪዎች ተገኝተው የገንዘብ ድጋፍ ያደረጉ ሲሆን፤ ምእመናን የድጋፍ ማድረጊያ ቅጽ እንዲሞሉ ተደርጓል፤ ጨረታም ተካሒዷል፡፡ ይህ ጉባኤ የመጀመሪያ መሆኑንና በቀጣይነት የሚካሄዱ የገቢ ማሰባሰቢያና ሌሎች ዝግጅቶች እንደሚኖሩም ተጠቅሷል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን መዝሙር ክፍል አባላትና የገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራን ያሬዳዊ ዝማሬ፤ እንዲሁም በገጣሚያን ግጥም ቀርቧል፡፡

 

 

Debre libanos Monastary.

የደብረ ሊባኖስ ገዳም የልማት ፕሮጀክት ትግበራ በመፋጠን ላይ ይገኛል

 

ሰኔ 5 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

  •  ሰኔ 8 ቀን 2006 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ የገቢ ማሰባሰቢያ ጉባኤ ይካሔዳል፡፡

Debre libanos Monastary.በደብረ ሊባኖስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንድነት ገዳም በ2004 ዓ.ም. በገዳሙና በማኅበረ ቅዱሳን ባለሙያዎች ተጠንቶ የቀረበው የገዳሙ ሁለንተናዊ የልማት ፕሮጀክት ተግባራዊ በመሆን ላይ እንደሚገኝ የገዳሙ የልማት ኮሚቴ ገለጸ፡፡

የጥናት ቡድኑ በገዳሙ የሚታዩትን ዋና ዋና ችግሮች በመለየትና ጥናት በማካሔድ፤ የፕሮጀክት ሰነድ በማዘጋጀት ወደ ተግባር ለመሸጋገር በርካታ ሥራዎችን ሲሠራ ቆይቷል፡፡

በጥናቱ ተለይተው የተያዙትን ችግሮች ለመቅረፍ በሦስት ዙር የተከፈሉ ሲሆን፤ በመጀመሪያው ዙር የብዝኀ ሕይወት ጥበቃ፤ የአፈርና የውኃ ጥበቃ፤ የመነኮሳት መኖሪያ ግንባታ፤ የመጸዳጃ ቤትና የአካባቢ ጽዳት ፕሮጀክቶች ተግባራዊ ይደረጋሉ፡፡ በሁለተኛው ዙር የአብነት ትምህርት ቤት ግንባታ (የተማሪዎች መኖሪያና መመገቢያ፤ የመምህራን መኖሪያ፤ ቤተ መጻሕፍትና የምርምር ማእከል) የያዘ ነው፡፡ በሦስተኛ ዙር የጤና ጣቢያ፤ የሁለገብ ሕንፃ፤ የዘመናዊ ትምህርት ቤት ግንባታ ፕሮጀክቶች ተግባራዊ የሚደረጉበት መሆኑ የፕሮጀክት ሰነዱ ያመለክታል፡፡

የጎርፍና የመሬት መንሸራተት፤ የቀብር ቦታና የቀብር ሐውልት መስፋፋት፤ የውስጥ ለውስጥ መንገዶችና የአውቶቡስ መናኸሪያ መስፋፋት በጥናቱ የተካተቱና እንደችግር የታዩ በመሆናቸው በፕሮጀክቱ ተካተዋል፡፡ የመጀመሪያው ዙር ትግበራም በተያዘለት ጊዜ ለማጠናቀቅ ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ ሲሆን፤ የመጸዳጃና የገላ መታጠቢያ ቤቶች ግንባታቸው 60% መድረሱን የገዳሙ የልማት ኮሚቴ አስታውቋል፡፡ በሦስት ዙር የሚጠናቀቀው የልማት ፕሮጀክት ከሁለት ዓመት በፊት በተጠናው ጥናት መሠረት 65,925,976 ብር (ስልሳ አምስት ሚሊዮን ዘጠኝ መቶ ሃያ አምስት ሺህ ዘጠኝ መቶ ሰባ ስድስት ብር) ይፈጃል ተብሎ ይገመታል፡፡

ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅ የገዳሙንና የምእመናን መንደር፤ የአባቶችና የእናቶች መኖሪያ ይለያሉ፤ መናንያን ለጸሎትና ለአገልግሎት የሚመች በዓት ይኖራቸዋል፡፡ ሱባኤ ለመያዝ በሚመጡ ምእመናንና በገዳሙ አባቶች መካከል ያለው ግንኙነት ሥርዓቱን የጠበቀ ምቹ ሁኔታን ይፈጥራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በጥናቱ የተካተቱትን ችግሮች በዘላቂነት ለመፍታት እንዲቻል የልማት ኮሚቴው የተለያየ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር በመንደፍና በማዘጋጀት ፕሮጅክቱን በታቀደለት ሁኔታ ለማጠናቀቅ እየሠራ ይገኛል፡፡ በዚህም መሠረት ሰኔ 8 ቀን 2006 ዓ.ም. ከቀኑ 7፡30 በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ተዘጋጅቷል፡፡ ምእመናን በሥፍራው ተገኝተው ድጋፍ እንዲያደርጉ የገዳሙ ፀባቴ አባ ወልደ ማርያም አድማሱ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በደብረ ሊባኖስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንድነት ገዳም ከ2500 በላይ የአብነት ተማሪዎችና ከ800 በላይ ማኅበረ መነኮሳት እንደሚኖሩ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡

 

abuna abrham 2006

ብፁዕ አቡነ አብርሃም አዲሱን መንበረ ጵጵስና ተረከቡ

 

ሰኔ 3 ቀን 2006 ዓ.ም.

ሊ/ዲ/ ኤፍሬም የኔሰው

abuna abrham 2006የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ አብርሃም በግንቦት ወር 2006 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ባስተላለፈው ውሳኔ መሠረት የምዕራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው በመዛወራቸው አዲሱን መንበረ ጵጵስና ተረክበዋል፡፡

ሰኔ1 ቀን 2006 ዓ.ም. የሀገረ ስብከቱ ርእሰ ከተማ በሆነችው ፍኖተ ሰላም፣ በፍኖተ ሰላም ቅዱስ ጊዮርጊስ ደብር አቀባበል ተደርጐላቸዋል፡፡ በበዓሉ ላይ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የማይጨው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተገኝተዋል፡፡

በሀገረ ስብከቱ ከተለያዩ አድባራትና ገዳማት የመጡ ካህናት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ምእመናን፣ ከከተማዋ መግቢያ በር ጀምሮ ብፁዕነታቸውን ደመቅ ባለ መንፈሳዊ ሥነ – ሥርዓት ተቀብለዋቸዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ አብርሃም በአቀባበል መርሐ ግብሩ ላይ ባስተላለፉት መልእክት “በእንተ ስማ ለማርያም ብዬ የተማርኩበትን አካባቢ ለማገልገል ዝግጁ ነኝ፡፡ ስለሆነም በርካታ መንፈሳዊ የልማት ሥራዎችን በጋራ እንሠራለን” ብለዋል፡፡ መንበረ ጵጵስናው በብፁዕ አቡነ ቶማስ ዕረፍት ምክንያት ለሁለት ወር ክፍት ሆኖ መቆየቱ ይታወሳል፡፡

በተመሳሳይ ዜና ብፁዕ አቡነ ሰላማ የታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያምና የመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የበላይ ጠባቂ ወደ ምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ተዘዋውረዋል፡፡ መንበረ ጵጵስናቸውንም ግንቦት 29 ቀን 2006 ዓ.ም. ተረክበዋል፡፡

 

senbt 2006 2

የሀገር አቀፍ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ ተጠናቀቀ

 ሰኔ 2 ቀን 2006 ዓ.ም.

senbt 2006 2ከግንቦት 30 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ ለሁለት ቀናት በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ሲካሔድ የቆየው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሀገር አቀፍ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት 3ኛ ጠቅላላ ጉባኤ ሰኔ 1 ቀን 2006 ዓ.ም. የአቋም መግለጫ በማውጣት ተጠናቋል፡፡

senbt 2006 3ጉባኤው በመጨረሻ ቀን ውሎው በየአኅጉረ ስብከቱ የሚታዩ እንቅስቃሴዎችንና ችግሮች አስመልክቶ ተሳታፊዎቹ በቡድን ውይይት በማድረግ ለጉባኤው አቅርበዋል፡፡ የግጭት አፈታት ዘዴን አስመልክቶ በመምህር በለጠ ብርሃኑ ጥናታዊ ጽሑፍ የቀረበ ሲሆን፤ በቀጣይ አንድ ዓመት ተፈጻሚ የሚሆኑ እቅዶች ላይ ውይይት ተካሒዶባቸዋል፡፡

በጉባኤው ማጠናቀቂያ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የበላይ ሓላፊ የስልጤ፤ ጉራጌና ሃዲያ አኅጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ለሁለት ቀናት በጉባኤው ለተገኙና ጉባኤው የተሳካ እንዲሆን ትብብር ላደረጉ አካላት ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ የወላይታ ኮንታና ዳውሮ አኅጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት ቃለ ምእዳን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ውስጥ በርካታ ችግሮች እንዳሉ በመግለጽ፤ በቅድሚያ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ራሳቸውን መመልከት እንደሚገባቸው አሳስበዋል፡፡ ሁሉም የየራሱን ድርሻ ከተወጣ አሁን እየታዩ ያሉ ችግሮች እንደሚወገዱ በመጠቆም ጠንክሮ መሥራት እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል፡፡

 senbt 2006 1

senbt 2006 4

የማቴዎስ ወንጌል

ሰኔ 2 ቀን 2006 ዓ.ም

ካለፈው የቀጠለ

  • ይሁዳ የእግዚአብሔር አብ

  • ኤራስ ዓዶሎማዊ የቅዱስ ገብርኤል

  • በግ የእግዚአብሔር ወልድ

ቀለበት፡- የሃይማኖት፤ ባርኔጣ፡- የአክሊለ ሦክ፤ በትር የመስቀል ትዕማር የቤተ አይሁድ፡፡ ትዕማር መያዣ ይዛ ቀረች እንጂ ዋጋዋን እንዳላገኘች ቤተ አይሁድም ትንቢቱን ተስፋውን ሰምተው ቀሩ እንጂ በክርስቶስ አላመኑምና፡፡

ፋሬስ የኦሪት ዛራ የወንጌል ምሳሌ፡፡ ዛራ አስቀድሞ እጁን እንዳወጣ፡፡ ወንጌልም በመልከ ጼዴቅ ታይታ ጠፍታለችና፡፡ ፋሬስ እሱን ወደኋላ ስቦ እንደተወለደ በመካከል ኦሪት ተሠርታለች፡፡ ዛራ በኋላ እንደተወለደ ወንጌል ኋላ ተመሥርታለችና፡፡

“ሰልሞንም ከራኬብ ቦኤዝን ወለደ”

ራኬብ ያላት ረዓብ ዘማን ነው /ኢሳ.6፥1-27/፡፡ ያለውን ተመልከት በዚህ ቦታ በተገለጸው ታሪክ ላይ ያሉት ሁሉ ኋላ ሊሆን ላለው ምሳሌ ናቸው፡፡

  • ኢያሱ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ

  • ኢያሪኮ የምእመናን

  • አሕዛብ የአጋንንት ምሳሌ

ኢያሱ አሕዛብን አጥፍቶ ኢያሪኮን እጅ እንዳደረገ፡፡ ጌታም አጋንንትን ድል ነስቶ ምዕመናንን ገንዘብ ለማድረጉ ምሳሌ፡፡

“ቦኤዝም ከሩት ኢዮቤድን ወለደ”

ትዕማር፣ ራኬብ፣ ሩት እነዚህ ሦስት ሴቶች የተነሡበት ምክንያት ተስፋ ከተሰጣቸው ከእስራአል ወገን ሳይሆን ትንቢት ካልተነገረላቸው ከአሕዛብ ወገን ስለሆኑ ነው፡፡ በዚህም የጌታ ልደት ከእስራኤል ብቻ ሳይሆን ከአሕዛብም መሆኑን መረዳት ይቻላል፡፡

ወንጌላዊው ማቴዎስ ለወገኖቹ ለዕብራውያን ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንቢት የተነገረለት ሱባዔ የተቆጠረለት መሲሕ እርሱ መሆኑን ለማስረዳት የጌታን የዘር ሐረግ በመተንተን ወንጌሉን መጀመሩን ባለፈው እትማችን ተገልጿል፡፡ ከዚያ የሚቀጥለው እነሆ፡-

በጌታችን የትውልድ ቁጥር ውስጥ ከአሕዛብ ወገን የነበሩ ሴቶች የመጠቀሳቸው ምክንያት ባለፈው የተገለጸ ሲሆን ዕብራዊትዋ ቤርሳቤህ /የኦርዮ ሚስት/ ለምን ተነሳች? የሚል ጥያቄ መነሳቱ አይቀርም፡፡ አይሁድ ክርስቶስ በዳዊት ከበረ ይላሉና፡፡ ዳዊት በክርስቶስ ከበረ እንጂ እሱማ ኦርዮንን አስገድሎ ሚስቱን የቀማ አልነበረምን ለማለት እንዲመቸው ነው ሲሉ መተርጉማን ተርጉመውልናል /ወንጌል አንድምታ/፡፡

ጌታ የተወለደው ከንጽሕት ቅድስት ድንግል ማርያም ሆኖ ሳለ ወንጌላዊው ለዮሴፍ የተወለደ ይመስል ቆጥሮ ቆጥሮ ዮሴፍ ላይ ማቆሙ ለምንድር ነው?

በዕብራውያን ሥርዓት የትውልድ ሐረግ የሚቆጠረው በወንድ በኩል እንጂ በሴት አይቆጠርም በዚሁም ላይ አይሁድ ጌታን የዳዊት ልጅ እያሉ ይጠሩት የነበረው በአንዳር በአሳዳጊው በዮሴፍ በኩል ነበርና ዓላማውም የዳዊት ወገን መሆኑን መግለጽ በመሆኑ በዮሴፍ በኩል ቆጠረ፡፡ ዳሩ ግን ጌታ ከእመቤታችን በኅቱም ድንግልና ተፀንሶ በኅቱም ድንግልና መወለዱ የታወቀ ነው፡፡ ማቴ.1፥34-36፣ ኢሳ.7፥14፡፡

ዮሴፍና እመቤታችን ዘመዳሞች መሆናቸውን ወንጌላዊው በእጅ አዙር ገልጿል፡፡ አልአዛር በወንጌሉ እንደተገለጸው ማታንን ብቻ ሳይሆን የወለደው ቅስራንም ነው፡፡ ማታን ያዕቆብን ሲወለድ፡፡ ቅስራ ደግሞ ኢያቄምን ወለደ፡፡ ያዕቆብ ቅዱስ ዮሴፍን /የእመቤታችንን ጠባቂ/ ወለደ፡፡ ኢያቄም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን፡፡ ዝምድናቸው በጣም የቀረበ /ሦስት ቤት/ መሆኑን ማስተዋል ይቻላል፡፡ ሁለቱም የዳዊት ወገን ናቸው፡፡ ዳሩ ግን ክርስቲያኖች ጌታን የዳዊት ልጅ የምንለው በአንጻር በዮሴፍ ሳይሆን በእናቱ በቅድስት ድንግል ማርያም ነው፡፡

ዮሴፍ የእመቤታችን እጮኛ ተብሎ መጠራቱ እንዴት ነው? እመቤታችን ለዮሴፍ በእጮኝነት ስም መሰጠትዋ ስለብዙ ምክንያት ነው፡፡ ከእነዚህም ጥቂቶቹ፡-

ሴት ልጅ ናት ጠባቂ ያስፈልጋታልና በእጮኛ ስም እንዲጠብቃት ነው፡፡ እንዲሁም ዮሴፍ ምክንያት ባይሆን እመቤታችን ጌታን በግብረ መንፈስ ቅዱስ በፀነሰችበት ጊዜ መከራ ላይ በወደቀች ነበር፡፡ ስለዚህ ምክንያት ሆኖ ከመደብደብ ከመንገላታት እንዲያድናት ነው፡፡

ክርስቶስ ያለ ወንድ ዘር መወለዱን ዐይተው እናቱ ቅዱስት ድንግል ማርያምን ከሰማይ የመጣች ኃይል አርያማዊት ናት እንጂ የአዳም ዘር ሰው አይደለችም፡፡ ክርስቶስም ከመልአክ የተገኘ መልአክ ነው የሚሉ መናፍቃን እንደሚነሱ ያውቃልና ከመላእክት ወገን ብትሆንማ ኖሮ እንዴት ለማረጋገጥ ለዮሴፍ ታጨች ለማለትና የአዳም ዘር መሆንዋን ለማረጋገጥ፡፡

በመከራዋ በስደትዋ ጊዜ እንዲያገለግላት እንዲላላክላት ነው፡፡

የእግዚአብሔር ጥበብ ድንግል ማርያም በውጭ የዮሴፍ እጮኛ እንድትባል ማድረጉ ከላይ ስለተጠቀሱት ምክንያቶች ነው እንጂ ዘር ለማስገኘት ሔዋን ለአዳም ረዳት ሁና እንደተሰጠችው ዮሴፍ ልጅ ለማስገኘት ረዳት እንዲሆናት አይደለም፡፡ አያይዞም ወንጌላዊው ድንግል በድንግልና ፀንሳ በድንግልና መውለዷን ሲገልጽ፡፡ “እናቱ ማርያም ለዮሴፍ በታጨች ጊዜ ሳይገናኙ በመንፈስ ቅዱስ ፀንሳ ተገኘች” ብሏል፡፡

ጌታም ልደቱን ያለወንድ ዘር ያደረገበት ምክንያት ቅድመ ዓለም ከአብ ያለ እናት መወለዱን ለማስረዳት ነው፡፡ የመጀመሪያው ልደት በኋላኛው ልደት ታውቋልና፡፡ ቀዳማዊ አዳም ከኅቱም ምድር እንደተገኘ ሁሉ ሁለተኛው አዳም ጌታም ከኅቱም ማኅፀን ተገኝቷል፡፡ እመቤታችን እናትም ድንግልም ስትባል መኖሯ አምላክ ወሰብእ /ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው/ ሲባል ለመኖሩ ምሳሌ ነውና፡፡ ለትውልድ ማኅተመ ድንግልናዋ አለመለወጡ ሰው ሲሆን ባሕርየ መለኮቱ ላለመለወጡ ምሳሌ ናትና፡፡

“የበኲር ልጅዋን እስክትወልድ ድረስ አላወቃትም” ሲል ምን ማለቱ ነው?

የበኲር ልጅ ለመባል የግዴታ ተከታይ ሊኖረው አይገባም፡፡ አንድ ብቻ ቢሆንም በኲር ይባላል፡፡ ከእርሱ በፊት የተወለደ የለምና፡፡ ዘጸ13፡1-2፡፡ የጌታ በኲር መባል የመጀመሪያም የመጨረሻም ብቸኛ ልጅዋ ስለሆነ ሲሆን ከድንግል የተወለደውም ተቀዳሚ ተከታይ የሌለው አንድያ የአብ ልጁ መሆኑን ለመግለጽ ነው፡፡ ዕብ.1፡6፡፡

በሌላም በኩል ከፍጥረታት በፊት ያለና የነበረ፡፡ ፈጣሬ ኲሉ ዓለም መሆኑን ለማስገንዘብ ነው፡፡ ይህንንም የቤተ ክርስቲያን የንጋት ኮከብ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ሲል ገልጾታል “….. ከፍጥረት ሁሉ በፊት በኲር ነው ሁሉ በእርሱና ለእርሱ ተፈጥሮአል እርሱም ከሁሉ በፊት ነው፡፡” ቆላ.1፡17፡፡

“እስከ” የሚለውን ቃል አገባብ በተለያየ ቦታ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እንዴት እንደገባ በሚከተሉት ምሳሌዎች እንመልከት፡፡

  1. “የሳኦል ልጅ ሜልኮል አስከ ሞተችበት ቀን ድረስ ልጅ አልወለችም” 2ሳሙ.6፡23፡፡ አባባሉ ከሞተች በኋላ ልጅ ወለደች የሚል ይመስላል፡፡ ዳሩ ግን ሰው ከሞተ በኋላ ሊወልድ ስለማይችል ትክክለኛው ትርጉም ሳትወልድ መሞትዋን ለመግለጽ የተጠቀሰ መሆኑን ይገነዘቧል፡፡

  2.  “ከአዳም ጀምሮ እስከ ሙሴ ድረስ ሞት ነገሠ” ሮሜ.5፡7፡፡ የሞት ንግሥና ከሙሴ በኋላ አለመቅረቱ የታወቀ ነው፡፡ ስለዚህ አነጋገሩ መቀጠሉን የሚገልጽ ነው እስከ ጌታ ሞት ድረስ፡፡

  3. “እግዚአብሔር ጌታዬን ጠላቶችህን ለእግርህ መረጋገጫ እስካደርግልህ ድረስ በቀኜ ተቀመጥ አለው” መዝ.110፡1፡፡ ጠላቶቹን ካሸነፈ በኋላ በቀኝ መቀመጡ ቀረን ቅዱስ እስጢፋኖስ ጌታ በመስቀሉ ላይ ዲያብሎስን ድል ካደረገ በኋላ /ቆላ.2፡14ና 15/ በእግዚአብሔር አብ ቀኝ ሆኖ ያየው መሆኑን ተናግሮአል፡፡ የሐዋ ሥራ 7፡55፡፡ የእስከ አገባብ በዚህ ላይ ፍጻሜ የሌለው ሆኖ እናገኛለን፡፡

  4. “እነሆ እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁል ጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ” ማቴ.28፡20፡፡ ከዓለም ፍጻሜ በኋላ ከእናንተ እለያለሁ ማለቱ አይደለም፡፡ ከላይ በተገለጸው መሠረት “እስከ” የሚለው ቃል ፍጻሜ ላለው ነገር እንደሚገባ ሁሉ ፍጻሜ ለሌለው ነገርም ይገባል፡፡ ስለሆነም ወንጌላዊው ማቴዎስ “እስከትወልድ ድረስ አላወቃትም” በማለት ዮሴፍ ጌታን ከወለደች በኋላ በሴትና በወንድ ግብር ፍጹም አላወቃትም ማለቱ ነው፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 3ኛ ዓመት ቁጥር 1 ታኅሥሥ 1988 ዓ.ም.

የሀገር አቀፍ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ በመካሔድ ላይ ነው

ግንቦት 30 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሀገር አቀፍ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት 3ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ግንቦት 30 ቀን 2006 ዓ.ም. ተጀምሯል፡፡

ጠቅላላ ጉባኤው ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት፤ በኮተቤ ኪዳነምህረት ቤተ ክርስቲያን ልዑካን አማካይነት በጸሎተ ወንጌል የተጀመረ ሲሆን፤ በብፁዕ አቡነ ሉቃስ የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሐፊ የሰቲት ሁመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ቡራኬ ቀጥሏል፡፡

ብፁዕነታቸው በሰጡት ቃለ ምእዳን “ነብዩ ሕዝቅኤል ወጣቶችን ሰብስቦ ልጆቼ ሆይ እግዚአብሔርን ታገለግሉት፤ በፊቱም ትቆሙ ዘንድ መርጧችኋልና ችላ አትበሉ እንዳለው ከእናንተ ወጣቶች ብዙ ይጠበቃል፡፡ አባቶቻችን ነብያት፤ ሐዋርያት፤ ሊቃውንት ከራሳቸው በፊት እግዚአሔርን አስቀድመዋል፡፡ እኛም የእነሱን መንገድ ልንከተል ይገባናል፡፡ ዛሬ ከእግዚአብሔር ይልቅ ገንዘብን በማስቀደም ብዙ ነገሮች ሲሰሩ እንመለከታለን፡፡ እናንተ ግን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረው ዘመኑን ዋጁ፤ በሃይማኖት ቁሙ፡፡ከፊታችን ብዙ ሥራ ይጠበቅብናልና መቀራረብ፤ መተራረም፤ መወያየት ያስፈልገናል” ብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የበላይ ሓላፊ የስልጤ፤ ጉራጌና ሃዲያ አኅጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ለተሳታፊዎች የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክት ሲያስተላልፉም “አባቶቻችን የዚህች ጥንታዊት፤ ታሪካዊትና ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን ዶግማ፤ ቀኖና፤ ሥርዓትና ትውፊት በሚገባ ጠብቀው ዘመን ተሸጋሪ የሆነ ወርቃማ ታሪክ ሰርተው ክርስትናን እስከነ ሙሉ ክብሩ በአግባቡ አስረክበውናል፡፡ እናንተም የአባቶቻችሁን ፈለግ ተከትላችሁ እየተመካከራችሁና እየተናበባችሁ መመሪያውንና ሕጉን አክብራችሁ በመንቀሳቀስ አሁን ካለው መልካም አገልግሎታችሁ የተሻለ ታሪክ እንድትሰሩ አደራ እንላችኋለን” በማለት ጉባኤው ቤተ ክርስቲያንን የሚጠቅም ውይይት እንደሚካሔድ እምነታቸው እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

በቀጣይነትም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የ2006 ዓ.ም የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት በማደራጃ መምሪያው ዋና ሓላፊ በመምህር እንቁባሕርይ ተከስተ አማካይነት ለጉባኤው ቀርቧል፡፡
በቀረበው ሪፖርት በ2006 ዓ.ም. የተከናወኑ አበይት ክንውኖችን በመዳሰስ ያጋጠሙ ችግሮች፤ ችግሮቹን ለመፍታት የተወሰዱ መፍትሔዎችም ተብራርተዋል፡፡ በቀረበው የአፈጻጸም ሪፖርት መሠረት ከተሳታዎች ጥያቄዎችና አስተያየቶች የቀረቡ ሲሆን ለጥያቆዎቹም ከመምሪያው ሓላፊ ምላሽ ተሰጥቷል፡፡

ከስዓት በኋላ ቀጥሎ በዋለው ጉባኤም በሰንበት ትምህርት ቤቶች የአንድነት ጉባኤ ውስጠ ደንብና ሀገራዊ አደረጃጀት፤ አፈጻጸምና ፈተናዎቹን አስመልከቶ በመምህር ሙሴ ኃይሉ በማደራጃ መምሪያው ምክትል ኃላፊ ገለጻ ተደርጓል፡፡ ከተሳታፊዎች ለቀረቡ ጥያቄዎችም ምላሽ ተሰጥቷል፡፡ በየአኅጉረ ስብከት የሚገኙ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ውስጥ እየተከናወኑ ያሉ አበይት ተግባራትና ያጋጠሙ ችግሮች አስመልክቶም የቡድን ውይይት ተካሂዷል፡፡

በአንድነት ጠቅላላ ጉባኤው ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ሓላፊዎች፤ ከ50 አኅጉረ ስብከት የተውጣጡ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ሓላፊዎች፤ ከመላው ሀገሪቱ የተወከሉ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ጠቅላላ ጉባኤ ተቀዳሚና ምክትል ሰብሳቢዎች፤የአዲስ አበባ አድባራትና ገዳማት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ሊቃነ መናብርት ተገኝተዋል፡፡ ጉባኤው በነገው እለትም ቀጥሎ ይውላል፤ ውሳኔዎችንም ያሳልፋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡