tinat ena miriemer 05 2005

የጥናት መድረክ

tinat ena miriemer 05 2005

kiduse entonse

እንጦንዮስ አበ መነኰሳት

ጥር  22 ቀን 2005 ዓ.ም.

  • ምንጭ፡- የበረሃው ኮከብ ቅዱስ እንጦንዮስ መጽሐፍ

 

ጨለማ በዋጠው በግብፅ በረሃ ውስጥ ለብዙዎች አርዓያ በሆነ የእምነት ገድል የቅድስናን ብርሃን በማብራቱ የበረሃው ኮከብ ብለው ብዙዎች ይጠሩታል፡፡

 

kiduse entonseብፁዐዊ ቅዱስ እንጦንስ በምንኩስና ሕይወት ለመኖር ከጌታችን ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተማረው አብነታዊ ትምህርት (ማቴ.4፥1-10) ከዚህ ዓለም ተድላና ደስታ በመራቅ ከሰዎች ሁሉ ተለይቶ  ፍጹም መንፈሳዊ ተጋድሎን በመጋደል በተወለደ በ106 ዓመቱ ጥር 22 ቀን በ356 ዓ.ም. ከዚች ዓለም በሥጋ ተለይቷል፡፡ “ክቡር ሞቱ ለፃድቅ በቅድመ እግዚአብሔር” “የፃድቅ ሰው ሞቱ በእግዚአብሔር ፊት የከበረ ነው” በማለት ክቡር ዳዊት እንደተናገረው፣ “ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የቅዱሳን የልደታቸውን ጊዜ፣ የተጋድሏቸውን ሁናቴ፣ ቃል ኪዳን የተቀበሉባቸውንና ያረፉባቸውን ዕለታት በክብር ታስባለች፡፡ ይህም በቅዱስ መጽሐፋችን “የፃድቅ መታሰቢያ ለበረከት ነው”(ምሳ.10÷7)፡፡ በመሆኑም “ስለ ፅድቅ የሚሰደዱ ብጹአን ናቸው ÷ መንግሥተ ሰማያት የእነርሱ ናትና” (ማቴ.5÷8) በሚለው በጌታችን ትምህርት የዚችን ዓለም ጣዕም ንቆ በምናኔ በመኖር ለመነኮሳት አብነት የሚሆናቸውን የቅዱስ እንጦንስን ዜና ሕይወት አቅርበናል፡፡ለመሆኑ ቅዱስ እንጦንስ ማን ነው? አስተዳደጉና የፈጸማቸው አገልግሎቶቹ ምን ይመስላሉ?

 

ልጅነት

እንጦንዮስ/እንጦንስ/ ትውልዱ ግብጻዊ ሲሆን ቤተሰቦቹም መልካሞችና ባለጸጎች ነበሩ፡፡ እነርሱም በሕፃንነት ኑሮው ከቤቱና ከወላጆቹ በስተቀር ምንም አላወቀም፡፡ እያደገና ዕድሜው እየጨመረ ሲሄድ ትምህርት ቤት አልገባም ነበር፡፡ ይህም ከሌሎች ልጆች ጋር ጓደኝነት ባለመፈለጉ ነበር፡፡ የእርሱ ፍላጎት በቅዱስ መጽሐፍ ተጠቅሶ እንደሚገኘው እንደ ያዕቆብ በብቸኝነትና በጭምትነት በቤቱ በመቀመጥ ቀላል ሕይወትን መምራት ነበር፡፡ ዘፍ.25፥27 በእርግጥ ከወላጆቹ ጋር ቤተ ክርስቲያን እየሄደ ያስቀድስ ነበር፡፡ በዚህም ከአንድ ልጅ ወይም ከአንድ ወጣት የሚታየው የመሰልቸትና የጥላቻ መንፈስ በጭራሽ አልታየበትም፡፡ ለወላጆቹ በመታዘዝ የሚሰጡትን ትምህርቶችና የሚነበቡትን ቅዱሳት መጻሕፍት በጥሞና ይከታተል ነበር፡፡ ከነዚህም የሚቀስመውን ጥቅም በልቡ በማስተዋል አኖረ፡፡ በሌላም በኩል በልጅነቱ ወራት ምንም እንኳ ያለ አንዳች ችግር ቢኖርም ወላጆቹን ለቅንጦትና ለድሎት ለምግብም ሲል አያስጨንቃቸውም ነበር፡፡ ይህን በመሰሉት ሁሉ አይደሰትም ነበር፡፡ በፊቱ በሚቀርብለት ብቻ ይረካ ነበር፡፡ ተጨማሪም አይጠይቅም፡፡

 

መጠራት

ወላጆቹ ከሞቱ በኂላ እንጦንዮስ ገና ልጅ ከነበረች አንዲት እኅቱ ጋር ብቻኛ ሆነ፡፡ በዚህ ወቅት ዕድሜው ከ18 እስከ 20 ዓመት ገደማ ነበር፡፡ ቤቱንና እኅቱንም ይጠብቅ ጀመር፡፡ እነርሱን ካጣ ከስድስት ወር በኋላ እንደ ልማዱ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲሄድ በመንገድ በኅሊናው ያስብ ጀመር፡፡

 

ሐዋርያት ሁሉን ትተው ጌታን እንደተከተሉት (ማቴ.10፣ 20፣19፣ 27)፤ በግብረ ሐዋርያት ሕዝቡ ያላችውን ሁሉ ሸጠው ለድሆች ይከፋፈል ዘንድ በሐዋርያት እግር ሥር ስለማኖራቸው (ሐዋ.4፡35)፤ ይህን ለመሳሰሉ ሥራዎች በሰማያት እንዴት ያለ ታላቅ ተስፋ እንዳላቸው (ኤፌ.1፡18 ቆላ.1፡15) እኒህን አሳቦች በኅሊናው እያወጣና እያወረደ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገባ፡፡ በዚያም ወቅት ወንጌል ይነበብ ነበር፤ ሲያዳምጥ ጌታ በሀብታሙ ሰው የተናገረውን የሚጠቅሰው ምዕራፍ ተነበበ፡፡

 

“ልትጸድቅ ብትወድድ ሂደህ ያለህን ሁሉ ሽጥና ለድሆች ስጥ፡፡ መጥተህም ተከተለኝ፡፡ በሰማያት መዝገብ ታከማቻለህ፡፡” ማቴ.19፡21 ፡፡ እግዚአብሔር ቀድሞ ስለ ቅዱሳን እንዲያስብ እንዳደረገውና እዚህም የተነበበው በቀጥታ ለእርሱ እንደተነገረ ስለተሰማው እንጦንዮስ በቀጥታ ከቤተ ክርስቲያኑ በመውጣት ከዘመዶቹ የወረሰውን 300 ሄክታር ወይም 12 ጋሻ መሬት ለድሆች አከፋፈለ፡፡ መሬቱ ለምና ለዐይንም ያማረ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ለእርሱም ሆነ ለእኅቱ እንቅፋት እንዲሆንባቸው አልፈለገም፡፡ የተረፈውን ሁሉን ተንቀሳቃሽ ሀብቱን ሸጠ፡፡ አብዛኛውን ለድሃ ሰጥቶ ጥቂቱን ለእኅቱ አስቀመጠው፡፡

 

እንጦንዮስ በሌላ ቀን እንደገና ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ ሳለ ጌታ በወንጌል የተናገረውን ሲነበብ አደመጠ፡፡ “ለነገ አትጨነቁ” ይል ነበር ጥቅሱ ማቴ.6፡34፡፡ ይህንንም ሰምቶ ሳይዘገይ ወደ ቤቱ በመመለስ የተረፈውን ሁሉ ለድሆች ያከፋፍል ጀመር፡፡ እኅቱን ግን የታወቁና የታመኑ ወደሆኑ ደናግል ማኅበር ወሰዳት፡፡ በዚያም ታድግ ዘንድ ለደናግል ትቷት ተመለሰ፡፡ ከዚያ በኋላ ብቻውን በመሆኑ ንቁ ሆኖ ራሱን በመካድ በመኖሪያ ቤቱ አጠገብ ጊዜውን ለብሕትውና ሕይወት ሰጠው፡፡

 

ትሕትና

እንጦንዮስ ራሱን ዝቅ በማድረግና በነፍስ ትሕትና የጸና ነበር፡፡ ምንም እንኳ ታላቅና ዝነኛ ቢሆንም የቤተ ክርስቲያንን ልዑካንና ጸሐፍትን ከእርሱ ይልቅ እንዲከበሩ ይሻ ነበር፡፡ በጳጳሳትና በካህናት ፊት እራሱን ዝቅ አድርጎ እጅ ሲነሣ አሳፋሪ አያደርገውም፡፡ ዲያቆን ወደ እርሱ በመጣ ጊዜ ጠቃሚ ነጥብን ካገኘም ላገኘው ዕውቀት ሳያመሰግን አያልፍም፡፡

 

በገጽታው ሊገለጽ የማይቻልና ታላቅ የሆነ ብሩህ ገጽ ይነበብበታል፡፡ በመነኮሳት ጉባኤ ተቀምጦ ሳለ ቀድሞ የማይተዋወቀውን ሰው ሊያነጋግረው ከፈለገ ማንም ሳያመለክተው በዓይኖቹ እንደተሳበ ሁሉ ሌሎቹን አልፎ በቀጥታ ወደ እንጦንዮስ ይሄዳል፡፡ ከሌሎቹ ልዩ አድርጎ የሚያሳውቀው ቁመናው ምስሉ ሳይሆን የረጋ ባሕርይውና የነፍሱ ንጽሕና ነበር፡፡ ነፍሱ የማትነዋወጽ በመሆንዋ አፍአዊ ገጽታውም የረጋ ነበር፡፡ በመጽሐፍ  “ደስ ያለው ልብ ፊትን ያበራል፡፡ በልብ ኀዘን ግን ነፍስ ትሰበራለች፡፡”ተብሎ እንደተነገረው (ምሳ.15፥13)፡፡ ለምሳሌ ያዕቆብ አጎቱ ደባ ተንኮል እንዳሰበበት ባወቀ ጊዜ ለሚስቶቹ እንዲህ ብሏቸው ነበር የአባታችሁ ፊት ከእኔ ጋር እንደዱሮ እንዳልሆነ አያለሁ፡፡ ዘፍ.31፥5፡፡ ነቢዩ ሳሙኤል ዳዊትን ንጉሥ አድርጎ ይቀባው ዘንድ በተላከ ጊዜ ደስታን የሚያንጸባርቁ ዓይኖቹንና እንደ ወተት የነጡ ጥርሶቹን አይቶ አወቀው፡፡ 1ሳሙ.16፥10፡፡ እንጦንዮስም እንዲሁ ይታወቅ ነበር፡፡ አይነዋወጽም፡፡ ነፍሱ እርጋታ ነበራትና፡፡ አያዝንም፡፡ አዕምሮው ደስታን የተሞላ ነበር፡፡

 

ቅዱስ እንጦንዮስ ፍቅረ ነዋይ ላለቀቀው መነኩሴ ያስተማረው ትምህርት

ዓለመን ንቆ ገንዘብ ስለመውደድ ከመነኮሰ በኋላ ለድሆች ካከፋፈለ በኋላ ለራሱ ጥቂት ያስቀረ አንድ ወንድም ወደ ባሕታዊው ወደ እንጦንዮስ መጣ፡፡ እንጦንዮስም ይህን ካወቀ በኋላ እንዲህ አለው፡፡ “ መነኩሴ ለመሆን ከፈለግህ ወደ መንደር ሂድና ጥቂት ሥጋ ገዝተህ ራቁትህን በሰውነትህ ላይ ተሸክመህ ተመለስና ወደእኔ ና” አለው፡፡ያም ወንድም ይህን ባደረገ ጊዜ ወፎችና ውሾች በሰውነቱ እያንዣበቡ ይታገሉት ጀመር፡፡ በደረሰም ጊዜ እንጦንዮስ እንዳዘዘው ማድረጉን ጠየቀው፡፡ እርሱም የቆሰለውን ሰውነቱን ባሳየው ጊዜ እንጦንዮስ እንዲህ አለው፡-“ዓለምን ከናቁ በኋላ ገንዘብ የሚመኙትም እንደዚሁ በአጋንንት ይገደላሉ፡፡” አለው፡፡

 

ቅዱስ እንጦንስ ስለ ዕረፍቱ በቀደ መዛሙርቱ ፊት የተናገረው የመጨረሻ ንግግር

የአባቶቼን መንገድ እሄዳለሁ

እንደልማዱ መነኮሳትን ይጎበኝ ዘንድ በተራራው ውጭ ሳለ በጌታ ቸርነት አስቀድሞ ስለ ሞቱ ስላወቀ ለወንድሞች እንዲህ ሲል ተናገራቸው፡፡ “ይህ ከናንተ ጋር የማደርገው የመጨረሻው ግንኙነት ነው፡፡ በዚህም ሕይወት ዳግመኛ እንተያይ እንደሆነ እንጃ እጠራጠራለሁ፡፡ ዕድሜዬ አንድ መቶ አምስት ዓመት ገደማ ሆኗልና አሁን እኔ የምሞትበት ጊዜ ነው፡፡” ይህን በሰሙ ጊዜ ሽማግሌውን ሰው አቅፈው እየሳሙ ያለቅሱ ጀመር፡፡ እርሱ ግን ከውጭ ከተማ እንደሚለይ ሁሉ በደስታ ያወጋቸው ነበር፡፡ በጥብቅም መከራቸው፡፡ “ከጥረታችሁ ግዴለሽ አትሁኑ፡፡ በብሕትውና ሕይወት ፍጹም ተስፋ አትቁረጡ፡፡ ዕለት ዕለት እንደምትሞቱ ሆናችሁ ኑሩ፡፡ አስቀድሜ እንደተናገርኩት ነፍስን ከርኩስ አሳቦች ለመጠበቅ በሥራ ትጉ፡፡ ቅዱሳንን ምሰሉ፡፡ ቅድስና የሌለውን የስንፍና ትምህርታቸውን ታውቃላችሁና ወደ መለጣውያን (መናፍቃን) አትቅረቡ ኑፋቄያቸው ለማንም ግልጽ ነውና፡፡

 

በመጽሐፈ መነኮሳት (ፊልክስዮስ) መቅድም ላይ ስለ ቅዱስ እንጦንስ ከተፃፈው የሚከተለው ይገኛል፡-እንጦንዮስ (እንጦንስ) አባቱ ባለጸጋ ነበር፡፡ አገሩም ጽኢድ ዘአምፈለገ አቅብጣ ናት፡፡ …በሕጻንነቱ ከትምህርት ቤት ሄደ፡፡ ተምሮ ሲመለስ አባቱ “ሕግ ግባ” አለው፡፡ እርሱ ግን “አይሆንም” አለ፡፡ምነው ቢሉ ፈቃዱ እንደ ቀደሙ ሰዎች እንደ ኤልያስ፤ እንደ ኋላ ሰዎች እንደ ዮሐንስ ንጽሕ ጠብቆ፣ ከሴት ርቆ በድንግልና መኖር ነውና፤ ግድ አለው፡፡ “ግድማ ካልከኝ …ፍቀድልኝና ለእግዚአብሔር አመልክቼ ልምጣ እንጂ” አለ፡፡ “ደግ አመልክተህ ና” አለው፡፡ሄዶ ባቅራቢያው ካለ ዋሻ ገባ፡፡ ወዲያው አባትህ ታመመ አሉት፡፡ ቢሄድ አርፎ አገኘው፡፡ ገንዘቡን ሦስት ነገር አስቦ አስቀድሞ ይመጸውታል፡፡ መጀመሪያ ያባቴ በድኑ ከመቃብር ሳይከተት መብሉ በከርሰ ርሁባን፤ መጠጡ በጉርኤ ጽሙአን፤ ልብሱ በዘባነ ዕሩቃን ይከተት ብሎ፡፡ ሁለተኛው ወኢይወርድ ምስሌሁ ኩሉ ክብረ ቤቱ /ሀብቱ ንብረቱም ሁሉ አብሮ መቃብር አይወርድም/ ያለውን የነቢዩን ቃል ያውቃልና፤ ሦስተኛ የሚመንን ነውና ልብ እንዳይቀረው፡፡ ሲመጸውትም አየቴ ኀይልከ፤ አይቴ አእምሮትከ አይቴ ፍጥነትከ /ኀይልህ የት አለ እውቀትህስ የት አለ ፍጥነትህስ የት አለ/ እያለ መጽውቶታል፡፡ መጽውቶ አባቱን አስቀብሮ ሲያበቃ ቅዳሴ ለመስማት ከቤተክርስቲያን ገብቶ ቆመ፡፡ ቄሱ ወንጌል ብሎ ወጥቶ ሲያነብ እመሰ ፈቀድከ ትኩን ፍጹመ ሲጥ ኩሉ ንዋይከ ወሀብ ለነዳያነ ወነዓ ትልወኒ ያለውን ቃል ሰማ፡፡ ይህ አዋጅ የተነገረ ለኔ አይደለምን? ብሎ እኅት ነበረችው ከደብረ ደናግል አስጠግቶ ሂዶ ፊት ከነበረባት ዋሻ ገብቶ ተቀመጠ፡፡

 

ከዕለታት አንድ ቀን ወለተ አረሚ ሠናይተ ላህይ ይላታል ከደንገጡሮቿ ጋር በቀትር ጊዜ መጥታ ከዛፉ እግር ከውኃው ዳር አረፈች፡፡ ፊት እሷን አስጠጓት፤ ኋላ እርስበሳቸው ይተጣጠቡ ጀመር፡፡ እሱም እርቃናቸውን እንዳያይ ዓይነ ሥጋውን ወደ ምድር ዓይነ ነፍሱን ወደ ሰማይ አድርጎ ሲጸልይ ቆየ፡፡ ያበቃሉ ቢል የማያበቁለት ሆነ፡፡ ኋላ ደግሞ ቆይተው ነገረ ኀፊር እያነሱ ይጨዋወቱ ጀመር፡፡ ምነው እንግዲህማ አይበቃችሁም? አትሄዱም? አላቸው፡፡ ኦ እንጦኒ! ኦ እንጦኒ!፤ ለእመ ኮንከ መነኮሰ ሑር ኀበ ገዳም እንጦኒ ሆይ መነኩሴ እንደሆንክ ከዚህ ምን አስቀመጠህ ከበረሃ አትሄድም ነበርን?/ አለችው፡፡ ከዚያ አስቀድሞ መነኩሴ አልነበረ መነኮስ ማለት ከምን አምጥታ ተናገረች? ቢሉ ጌት ለአበው ትምህርት የሚሆነውን ነገር በማናቸውም ባልበቃ ሰው አድሮ መናገር ልማዱ ነው፡፡ አንድም እሱ ከመነኩሴ ፊት እንዲህ ያለ ኀፊር ትናገሪያለችን? አላት፡፡ ከሱ ሰምታ ኦ እንጦኒ ኦ እንጦኑ እመሰ ኮንከ መነኮሰ ሑር ሐበ ገዳም አለችው፡፡

 

እንጦኒ ኦ እንጦኒ እመሰ ኮንከ መነኮሰ ሑር ሐበ ገዳም እያለ ራሱን እየገሰጸ ፊቱን እየሰፋ ጽሕሙን እየነጨ ከዚያ ተነሥቶ አናብስት፤ አናምርት፤ አካይስት፤ አቃርብት ካሉበት ነቅዐ ማይ፤ ልምላሜ ዕፅ ከሌለበት ድሩክ ለተአቅቦ ይላል ዘር ተክል ከማይገኝበት ገዳመ አትፊር ሄደ፡፡ የዚህ መንገዱ ፍለጋ የለውም፡፡ አሸዋ ላሸዋ ነው፡፡ ነጋድያን ሲጓዙ የወደቀውን ያህያና የግመል ፋንድያ እያዩ በዚያ ምልክት ይሄዳሉ፡፡ በረሃነቱም ጽኑ ነው፡፡ ከሐሩሩ ጽናት የተነሣ በቀትር ጊዜ ከደንጊያ ላይ ተልባ ቢያሰጡ ይቆላል፡፡ እሱም ከዚያ ሄዶ ሲጋደል አጋንንት ጾር አነሱበት፡፡ ኦ ሕጹጸ መዋዕል እፎ ደፈርከ ዝየ፡፡ /በእድሜ ሕፃን የሆንክ ከዚህ እንደምን ደፍረህ መጣህ?/ አዳም ከወጣበት ገነት እንጂ እገባ ብሎ ነው፡፡ ብለው ዘበቱበት፤ እሱም በትሕትና ይዋጋቸዋል፡፡ መሆንማ ይሆን ብላችሁ ነውን? እናንተ ብዙ አኔ አንድ ብቻዬን፤ እናንተ ረቂቃን እኔ ግዙፍ፡፡ እናንተ ኀያላን እኔ ደካማ በኀይለ ክርስቶስ ብችላችሁ ነው እንጂ ያለዚያስ አልችላችሁም እያለ በትሕትና ሲዋጋቸው ኖረ፡፡

 

ከዕለታት ባንድ ቀን ይኸን ፆር አልቻልሁትም ልሂድ እንጂ ብሎ ሲያስብ አደረ፡፡ ማለዳ በትረ ሆሣዕና ነበረችው ያችን ይዞ ከደጃፉ ላይ ቆመ፡፡ እንዳይቀርም ፆሩ ትዝ እያለው እንዳይሄድም በዓቱ እየናፈቀው አንድ እግሩን ከውስጥ፤ አንድ እግሩን ከአፍአ አድርጎ ሲያወጣ ሲያወርድ መልአኩ የሰሌን ቆብ ደፍቶ፤ የሰሌን መቋረፊያ ለብሶ፤ የሰሌን መታጠቂያ ታጥቆ ብትን ሰሌን ይዞ መጣ፡፡ ምን ሊያደርግ ይሆን? ሲል ፊቱን ወደ ምሥራቅ መልሶ ቆመ፡፡ ወዲያው ጸሎተ ወንጌልን፤ ነአኩቶን፤ ተሠሀለኒን፤ ደግሞ መጀመሪያ ለሥላሴ እጅ ነሳ፡፡ ከዚያ በኋላ አንድ አቡነ ዘበሰማያት ሠላሳ ስድስት ሰጊድ አድርሶ በመጨረሻ አንድ ጊዜ እጅ ነሥቶ ተቀመጠ፡፡ ወዲያው ያን ብትን ሰሌን አቅርቦ ይታታ ጀመር፡፡ እንጦንዮስም እንግዲህማ የዚህን ፍጻሜ ሳላይ እሄዳለሁን? ብሎ ተቀምጦ ይመለከተው ጀመር፡፡ ሠለስት ሲሆን ደግሞ ተነሥቶ አቡነ ዘበሰማያቱንም ሰጊዱንም ያንኑ ያህል አደረሰው፡፡ የቀሩትንም የሰዓቱንም የሠርኩንም እንደዚሁ አድርጎ አሳየው፡፡ በሠርክ ኦ እንጦኒ ከመ ከመዝ ግበር ወለእመገበርከ ዘንቱ ትድኀን እምጸብአ አጋንንት አለው /እንጦኒ ሆይ እንደዚህ እንደዚህ ሥራ፤ ይህንን ከሠራህ ከአጋንንት ጠብ ትድናለህ/፡፡ ማለት ነው፡፡ የንዋሙን የመንፈቀ ሌሊቱን ግን እርሱ ጨምሮታል፡፡ ንዋም ጌታ የጸለየበት፤ ቀትር የተሰቀለበት፤ ሰዓት ነፍሱን ከሥጋው የለየበት፤ ሰርክ መቃብር የወረደበት ነውና ይህን ሁሉ አንድ አድርጎ ዳዊት ሰብአ ለዕለትየ እሴብሐከ ብሏል፡፡ /መዝ.118፥164/

 

ሠላሳ ዓመት ሲሞላው ጌታ በዕለተ ዓርብ የለበሰውን ልብስ አልብሶታል፡፡ ማየት ከመልአክ፤ መቀበል ከአምላክ እንዲሉ ይህም ምሳሌ ነው፡፡ ቆብ የአክሊለ ሦክ፤ ቀሚሱ የከለሜዳ፤ ቅናቱ የሀብል፤ ሥጋ ማርያም የሥጋ ማርያም፤ አስኬማ የሰውነት ወተመሰለነ በአስኬማሁ እንዲል፤እርሱም ይህን ተቀብሎ በዚህ ዓለም እኔ ብቻ ነኝን ሌላም አለ? ብሎ ወደ እግዚአብሔር አመለከተ፡፡ ጌታም አለ እንጂ አንድ ጊዜ ተራምዶ ሁለተኛውን ሳይደግም የሚሠራውን ሥራ ዓለሙ ሁሉ ቢሰበሰብ የማይሠራው፡፡ በጸሎቱ ዝናም የሚያዘንም ፀሐይ የሚያወጣ፤ እንደዚህ ያለ ወዳጅ አለኝ አለው፡፡ ይኸን ሰው ለማየት ልሂድን ልቅር? ቢለው ሂድ አለው፡፡ መልአኩ እየመራ አደረሰው፡፡ ጳውሎስ /ጳውሊ/ ከበዓቱ ወጥቶ ፀሐይ ሲሞቅ ነበር፡፡ ሲመጣ አይቶ ከበዓቱ ገብቶ ወወደየ ማእጾ ውስተ አፈ በዓቱ /ከበዓቱ አፍ ውስጥ መዝጊያ ጨመረ/ ይላል ዘጋበት፡፡ ከደጃፉ ቆሞ አውሎግሶን አውሎግሶን አለ፡፡ ስለ እግዚአብሔር ብለህ ክፈትልኝ ማለት ነው፡፡ ሰው እንደሆንክ ግባ ብሎ ከፈተለት፡፡ ገብቶ ማን ይሉሃል? አለው ስሜን ሳታውቅ እንደምንም መጣህ? አለው፡፡ እንጦንዮስም ፍጹም ነውና ቢጸልይ ወዲያው ተገልጾለት፤ ጎድጎድኩ ወተርህወ ሊተ ሀሰስኩ ወረከብኩ ጳውሎስ ገዳማዊ አለው፡፡

 

ጳውሎስ/ጳውሊ/ ትባላለህ ቢለው አደነቀ፡፡ ተጨዋውተው ሲያበቁ ባጠገቡ ለብቻው በዓት ሰጠው፡፡ እንጦንዮስም ከዚያ ሆኖ ጸሎቱን ሲያደርግ ዋለ፡፡ ወትሮ ለጳውሊ መንፈቀ /ግማሽ/ ኅብስት ይወርድለት የነበረ ማታ ምሉዕ ኅብስት ወረደለት፡፡ በፈቃደ እግዚአብሔር መምጣቱን ያን ጊዜ አወቀው፡፡ ወዲያው ያን ኅብስት ከሁለት ገምሶ እኩሌተውን ለራሱ አስቀርቶ እኩሌታውን ሰጠው፡፡ ያን ተመግበው ሌት ሁሉም በየሥራቸው ክብራቸው ተገልጾ ሲተያዩ አድረዋል፡፡ ጳውሎስ አሥር ጣቶቹን እንደ ፋና ሆነው እያበሩለት አራቱን ወንጌል ሲያደርስ እንጦንዮስም እንደ አምደ ብርሃን ተተክሎ ሲያበራ ተያይተዋል፡፡

 

በዚያች ሌሊት ከዚያ ቦታ ጨለማ ጠፍቶ አድሯል፡፡ በነጋው ሠለስት እላፊ ሲሆን ጸሎታቸውን አድርሰው ሲያበቁ ተገናኝተው ሲጨዋወቱ፤ እንጦንዮስ ያረገውን ቆብ አይቶ፤ ይህማ ከማን አገኘኸው? አለው፡፡ እርሱ ባለቤቱ ስጠኝ አለ፡፡ እርሱም የጌታን ቸርነት ያደንቅ ጀመር፡፡ እንጦንዮስም እስኪ በኔ ብቻ የሚቀር እንደሆነ ለሌላም የሚያልፍ እንደሆነ አመልክትልኝ አለው፡፡ አመለከተ፡፡ ወዲያው ተገለጸለት፡፡ ወአክሞሰሰ ይላል፡፡ ደስ አለው፡፡ ምን አየህ? ቢለው ጽዕድዋን አርጋብ /ነጫጭ ርግቦች/ በጠፈር መልተው አንተ እየመራሀቸው ተከትለውህ ሲሄዱ አየሁ አለው፡፡ ምንኑው ቢለው? እሊህማ በዚህ በቆቡ የምትወልዳቸው ንጹሐን ጻድቃን ልጆችህ ናቸው አለው፡፡  ሁለተኛ አመልክትልኝ አለው፡፡ አመለከተ ወደመነገጹ ይላል፡፡ አዘነ ምነው ቢሉ በክንፋቸው ጥቁር ተቀላቅሎባቸው አየሁ አለው፡፡ ምንድንናቸው ቢለው ጽድቅና ኀጢአት እየቀላቀሉ የሚሠሩ ልጆችህ ናቸው አለው፡፡ ሦስተኛ አመልክትልኝ አለው፡፡ አመለከተ ገአረ ወበከየ ይላል፡፡ ቃሉን ከፍ አድርጎ ጮኸ፡፡ ምነው አለው አርጋብስ አርጋብ ናቸው አለው፡፡ ነገር ግን በመጨረሻ ዘመን የሚነሡቱ እንደ ቁራ ጠቁረው አየሁዋቸው አለ፡፡ ምንድናቸው? ቢለው ሀሳሲያነ ሢመት /ሹመት ፈላጊዎች/፤ መፍቀሪያነ ንዋይ /ገንዘብ የሚወዱ/ እለ ይሠርኡ በነግህ ማዕደ ምስለ መኳንንት /ከመኳንንት ጋር በጥዋት ማዕድ የሚቀመጡ/ ይላቸዋል፡፡ በፍጻሜ ዘመን የሚነሡ ኀጥአን ልጆችህ ናቸው፡፡ አለው፡፡ ያለ ንስሓ ባይጠራቸው እስኪ አመልክትልኝ አለው፡፡ አመለከተ፡፡ የዚህ ምላሽ አልመጣለትም ይላሉ፡፡

 

ከዚህ በኋላ ጳውሊ እንግዲህ ይህን ከራስህ ያደረግኸውን ለኔ ስጠኝ ላንተ ሌላ ሠርተህ አድርግ አለው፡፡ ይህንንስ እንዳልሰጥህ ከባለቤቱ ተቀብዬዋለሁ፡፡ ነገር ግን ሥራውን ለምጄዋለሁ ሌላ ሠርቼ ላምጣልህ አለው፡፡ እንዲያስ አትዘግይ ቶሎ ሠርተህ አምጣልኝ አለው፡፡ ጊዜው እንደደረሰ አውቆታልና ይላሉ፡፡ እንጦንስም ሠርቶ ይዞ ሲመጣ ጳውሊ አርፎ ነፍሱን መላእክተ ብርሃን ይዘዋት ሲያርጉ አየ፡፡ ማነው ብሎ ጠየቃቸው፡፡ ያ ሰው አርፏልና ሂደህ ቅበረው አሉት ይህንሳ የያዝኩትን ቆብ ልተወውን? አላቸው፡፡ አትተው አድርግለት ብለውታል፡፡ ከምንኩስና አስቀድሞ የሠሩትን ሥራ ከንቱ እንዳይደለ ለማጠየቅ ነው፡፡

 

ቢሄድ መጽሐፉን ታቅፎ፤ አጽፉን ተጎናጽፎ፤ ከበዓቱ አርፎ፤ አገኘው፡፡ ከራስጌው ቆሞ ሲያለቅስ ሁለት አናብስት መጡ፡፡ የመቃብሩን ነገር እንደምን ላድርግ ነኝ አያለ ሲጨነቅ በእጃቸው እንደመጥቀስ አድርገው አሳዩት፡፡ ልኩን ለክቶ ሰጣቸው፡፡ ቆፈሩለት እሱን ቀብሮ እንግዲህ ከዚህ እኖራለሁ ብሎ አሰበ፡፡ ጌታ ግን ዛሬ በሱ ቦታ ላይ ሌላ ሰው አላየበትምና አይሆንልህም ሂድ አለው፡፡ አጽፉንና መጽሐፉን ይዞ ሂዶ እስክንደርያ ሲደርስ ሊቀ ጳጳሱ አትናቴዎስ ወዴት ሄደህ ነበር? አለው፡፡ እንዲህ ያለ ሰው ልጠይቅ ሄጄ ነበር፡፡ አርፎ አግኝቼ ቀብሬው መጣሁ፡፡ አለ፡፡ ልሄድና ከዚያ ልኑር? አለው አይሆንልህም አትሂድ እኔም አስቤ ነበር፡፡ የማይሆንልኝ ሆኖ መጣሁ እንጂ አለው፡፡ ባይሆን ለበረከት ያህል አጽፊቱን ጥለህልኝ ሂድ ብሎ ትቶለት ሄደ፡፡ መዓርግ ሲሰጥ ሥጋውን ደሙን ሲለውጥ በውስጥ ያቺን ይለብስ ነበር፡፡

 

ከዚያ በኋላ በዚህ ቆብ እንጦንዮስ መቃርስን፤ መቃርስ ጳኩሚስን፤ ጳኩሚስ ጳላሞንን፤ ጳላሞን ቴዎድሮስ ሮማዊውን ቴዎድሮስ ሮማዊ አቡነ አረጋዊንና አባ ዳንኤልን ይወልዳል፡፡ አባ ዳንኤል አቡነ አውስጣቴዎስ፤ አቡነ አረጋዊ እስከ አቡነ ተክለሃይማኖት ያሉትን ወልደዋል፡፡ ከዚህ በኋላ መነኮሳቱ እንደ ሳር እንደ ቅጠል በዝተው ተነሥተዋል፡፡ ይሩማሊስ፤ ጳላድዮስ የሚባሉ ሁለት ሊቃውንት መነኮሳት ከግብፅ ተነሥተው አገር ላገር እየዞሩ የአበውን ዜና በሕይወት ያሉትን ከቃላቸው የሞቱትን ከአርድአቶቻቸው እየጠየቁ ቃለ አበው፣ ዜና አበው እያሉ ጽፈዋል፡፡

አምላካችን ከቅዱስ እንጦንስ በረከት ረድኤት ያሳትፈን፡፡

“ሰማዕታት የዚችን ዓለም ጣዕም በእውነት ናቁ፤ ደማቸውን ስለ እግዚአብሔር አፈሰሱ፤ ስለ መንግሥተ ሰማያት መራራ ሞትን ታገሱ፡፡”

ጥር 20 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ሰሎሞን መኩሪያ

ውዳሴ ማርያም ዘሐሙስ ቁ.6

በረከቱ ይደርብንና ይህንን ቃል የተናገረ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ወዳጅ የሆነው ሶሪያዊው ቅዱስ ኤፍሬም ነው፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም በብሉይ ዘመን በቅዱስ ዳዊት ሕይወት የተከወነውን በምስጢር ስቦ አምጥቶ የሰማዕታትን ክብር አጎልቶ ተናግሮበታል፡፡ ታሪኩ እንዲህ ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊትን እግዚአብሔር አምላክ ለእስራኤል አነገሠው፡፡ በዙሪያው የነበሩ ኤሎፍላዊያንን አጥፍቶ ደብረ ጽዮንን /መናገሻ ከተማውን/ አቅንቶ ሲኖር ከዕለታት አንድ ቀን ዳዊት ታመመ፡፡የዳዊትን መታመም ሰምተው፣ ካሉበት ተነስተው የዳዊትን ከተማ በተለይም ቤተልሔምን ከበቧት፡፡ ዳዊት ይህ ሰምቶ “ወይ እኔ ዳዊት! ድሮ ታመምሁና ጠላቶቼ ሰለጠኑ ሲል የኀያላኑን ልቦና ለመፈተን ከቤተልሔም ምንጭ ውኃ ማን ባመጣልኝ?” አለ፡፡ በዚህ ጊዜ የጭፍሮቹ አለቆች ሦስቱ ማለትም አዲኖን፣ ኢያቡስቴ ኤልያና ረዋታቸውን /የውኃ መያዣ/ ይዘው፣ ጦራቸውን አሰልፈው፣ ጠላቶቹን ድል ነስተው፣ ዳዊት ሊጠጣ የወደደውን ውኃ አመጡለት፡፡ቅዱስ ዳዊትም ያንን ውኃ አፈሰሰው “ለምን አፈሰስከው?” ቢሉት “ደማችሁን መጣጠት አይደለምን?” ብሎ፤ ይህም ከጽድቅ ገብቶ ተቆጠረለት፡፡ 2ሳሙ.23፥13-17

 

አባቶቻችን ይህንን ሲያመሰጥሩት የፍጥረት ሁሉ ቁንጮ አባታችን አዳም ከተድላ ገነት ወደ ምድረ ፋይድ፥ ከነጻነት ወደ መገዛት፥ ከልጅነት ወደ ባርነት፥ በወረደና  ፍትወታት እኩያት ኀጣውእ በጠላትነት በተነሱበት ጊዜ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ከተገኘ ከጌታ ጎን የተገኘ ማየ ገቦ ይጠጣ ዘንድ ወደደ፡፡ የትሩፋት አበጋዞች ሃይማኖት፣ ተስፋ፣ ፍቅር፣ ፈጥነው ተነሱ፡፡ በአጋንንት ከተማ ተዋጉለት ይጠጣው ዘንድ የወደደውን ማየ ገቦ አመጡለት፡፡ ማለትም የአዳም ልጅነት በከበረው የክርስቶስ የደሙ ፈሳሽነት የሥጋው መሥዋዕትነት ተመለሰለት፡፡ ይህንን ለአዳምና ለልጆቹ የባህርይ አምላክ ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተቀበለውን ፀዋትወ መከራ እያሰቡ ሰማዕታት በእግዚአብሔር ፍቅር ተቃጥለው “እግዚአብሔርን ካዱ ለጣዖት ሰገዱ” ሲባሉ “እግዚአብሔርን አንክድም ለጣዖት አንሰግድም” ብለው ደማቸውን አፈሰሱ ይህም ጽድቅ ሆኖ ተቆጠረላቸው፡፡ /ውዳሴ ማርያም ትርጓሜ ዘሐሙስ/

 

“ሰማዕት” ማለት ምስክር ማለት ነው፡፡ ይህ ደማቸውን ስለ እግዚአብሔር ፍቅር ብሎ ማፍሰስ ጽድቅ ሆኖ ተቆጠረላቸው፥ የዳዊት ወታደሮች ስለ ዳዊት ፍቅር ብለው “ደማችን ይፍሰስ” እንዲሉ፤ ዳዊትም ያመጡለትን ውኃ መጠጣት ደማችሁን እንደመጠጣት ነው ብሎ በፍቅር ምክንያት ውኃውን እንዳፈሰሰው፥ ይህም ጽድቅ ሆኖ እንደተቆጠረለት፥ የእግዚአብሔር ወዳጆች የሆኑ ቅዱሳን ሰማዕታትም እግዚአብሔርንና የእግዚአብሔር ሃይማኖት የሆነችው እውነተኛይቱን ሃይማኖት ወደው ደማቸውን አፈሰሱ፣ አጥንታቸውን ከሰከሱ፣ ስለዚህ እንደ ፀሐይ አብርተው በሰማያት ዛሬም ስለ እኛ እየማለዱ አሉ፡፡ “ለመሆኑ ከዚህ ክብር የደረሱት እንዴት ነው?” ብሎ ለሚጠይቅ ቅዱስ ኤፍሬም ሲመልስ ሦስት ነገሮችን ያነሣል፡፡

 

1.    “ሰማዕታት የዚችን ዓለም ጣዕም ናቁ” ይላል

ዓለም እንደየዘመኑ የተለያየ ጠባይ አላት፤ ልክ እንደ እስስት ትለዋወጣለች፡፡ ስለዚህ ሁል ጊዜ ከእውነት ይልቅ ሐሰት፥ ከፍቅር ይልቅ በእውነተኞቹ ላይ ጥላቻ፥ በግልጽ ይታይባታል፡፡ የራሷ የሆነውን እጅግ አድርጋ ትወዳለች ስለዚህም በተለያየ መረብ እያጠመደች ለዘለዓለሙ ትጥላለች፡፡ “ሰማዕታት” /ምስክሮች/ ግን የዚችን ዓለም ጣዕም ናቁ፤ ማለትም እውነት እግዚአብሔርን፥በሐሰት ጣዖት አልለወጡም ስለዚህ በእግዚአብሔር ዘንድ በክብር ተቀምጠው ስለ እኛ እያማለዱ አሉ፡፡ ትምህርታችንን የበለጠ ግልጽ እንዲያደርግልን እንደ ሰማይ ከዋክብት እንደ ባሕር አሸዋ ቁጥራቸው ከበዛ በእግዚአብሔር ዘንድ ክብር ካላቸው ቅዱሳን ሰማዕታት መካከል የሰማዕታት አለቃ ተብሎ በፈጣሪው በእግዚብሔር ዘንድ ስለተሾመው ስለ ቅዱስ ጊዮርጊስ የተጋድሎ ሕይወት ጥቂት እንመለከታለን፡፡

 

በረከቱ ይደርብንና ቅዱስ ጊዮርጊስ የአባቱ ስም ዘሮንቶስ የእናቱ ስም ቴዎብስታ ይባላል፡፡ አባቱ በፍልስጥኤም አገር መስፍን ነበር፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሕፃን ሳለ አባቱ በሞት ተለየው ከዚያ 20 ዓመት ሲሞላው የአባቱን ሹመት ለመቀበል ወደ ዱድያኖስ ንጉሥ ዘንድ ሄደ፡፡ ንጉሡም ጣዖት አቁሞ ጣዖትን እንዲያመልኩ ሰዎችን ሁሉ ሲያስገድዳቸው አገኘው፡፡ ይህንን አይቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ እጅግ አዘነ፤ በእርሱ ዘንድ ያለውን ለንጉሡ እጅ መንሻ ያመጣውን ገንዘቡን ለድሆች እና ለምስኪኖች ሰጠ፡፡ ባሮችንም ነጻ አወጣቸው ከዚህ በኋላ በንጉሥ ፊት ቁሞ “በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመኑ በግልጽ እኔ ክርስቲያን ነኝ” አለ፡፡ ያን ጊዜ ንጉሡ ዱድያኖስ በዘመኑ ከነበሩ በሥልጣኑ በሥሩ ከሚተዳደሩ 70 ነገሥታት ጋር ሆኖ አባብለው እግዚአብሔርን እንዲክድ ለጣዖት እንዲሰግድ ይህንን ቢያደርግ ብዙ ብር እና ወርቅ እንደሚሰጠው ከእርሱም በታች ባለ ሥልጣን እንደሚያደርገው ቃል ገባለት፡፡

 

ቅዱስ ጊዮርጊስ ግን ይህንን አልተቀበለም፡፡ በፊቱ ናቀው እንጂ ጌታ በቅዱስ ወንጌል እንደተናገረ “ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጎድል ምን ይጠቅመዋል” ማቴ.16፥26 እንዳለ፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ በወጣትነቱ እግዚአብሔርን ክዶ ለጣዖት ሰግዶ የሚያገኘውን ወርቅ እና ብር እንዲሁም ሥልጣን ናቀ፡፡ ይህ እግዚአብሔር ለማገልገል በሕይወቱ ያሳየውን ቆራጥነት እራስን መካድን ያሳየናል፡፡ ማቴ.16፥24፡፡ ከዚህ ቅዱስ ሕይወት ተምረን እኛም በዓለም ውስጥ ከሚሠራው የኀጢአት ሥራ በንስሐ ሕይወት በጽድቅ ሥራ መለየት ይገባናል በዘመናችንም እንደ ቅዱስ ጊዮርጊስ የዓለምን ጣዕም መናቅ ማለት እውነትን በሐሰት አለመለወጥ ማለትም እውነተኛ ሆኖ መገኘት የሚበላውን ከማይበላው ጋር ቀጥቅጦ አለመሸጥ በሚዛን አለመበደል ፍርድ አለማጉደል ጉቦ ተቀብሎ ድኃ አለመበደል በምንሠራበት መሥሪያ ቤተ ሰነድ አለመሰረዝ አለመደለዝ ባጠቃላይ በሕይወታችን በእግዚአብሔርም በሰውም ዘንድ በእውነት ታምነን መገኘት ይገባናል፡፡ ለዚህም የቅዱስ ጊዮርጊስ ጸሎትና ምልጃ ይርዳን፡፡

 

2.    ደማቸውን ስለ እግዚአብሔር አፈሰሱ

እንግዲህ ከላይ እንደተመለከትነው ዱድያኖስ ንጉሥ የዚችን ዓለም ጣዕም አቅምሶ ቅዱስ ጊዮርጊስ በማባበል ለጣዖት ማሰገድ በተሳነው ጊዜ የወሰደው እርምጃ በዘመኑ በነበረው የተለያየ መሣሪያ ተጠቅሞ የቅዱስ ጊዮርጊስን ደም ማፍሰስ ነበር፡፡ በገድለ ጊዮርጊስ እንደተጻፈ ለቆመው የወርቅ ምስል አልሰግድም እነርሱንም አላመልክም ይልቁንም ዐይን እያላቸው የማያዩ ጆሮ እያላቸው የማይሰሙ እጅ እያላቸው የማይዳስሱ እግር እያላቸው የማይሄዱ በአፋቸው ትንፋሽ የሌለ ግዑዛን ናቸው፡፡ እነርሱን የሚያመልኩ እንደነርሱ ይሁኑ ብሎ በቅዱስ ዳዊት ቃል ንጉሡን እና ጣዖታቱን በዘለፈ ጊዜ መዝ.113፥12-16 ዱድያኖስ ንጉሥ ቅዱስ ጊዮርጊስን አስገረፈው በተገረፈ ጊዜ ደሙ እንደ ውኃ ፈሰሰ፡፡ ከዚያም ጨለማው ጥልቅ ወደ ሆነ የእስር ቤት ጣሉት፡፡ ዱድያኖስና ሰባው ነገሥታት በዚህ መከራ ይሞታል የእርሱን መከራ መቀበል የደሙንም መፍሰስ የተመለከቱ ሌሎች ሰዎችም በመፍራት በእኛ የጣዖት አምልኮ ሥርዓት ፀንተው ይኖራሉ ብለው አስበው ነበር፡፡

 

ነገር ግን የቅዱስ ጊዮርጊስን መከራ መቀበል የደሙንም መፍሰስ የወደደ ይህንንም ለክብር ሊያደርግለት ፈቃዱ የሆነ ቅዱስ እግዚአብሔር በግርፋቱና በደሙ መፍሰስ እንዲሞት አልተወውም ስለዚህ ወደ እስር ቤቱ የጨለማውን ጥልቀት በብርሃን የሚገልጥ ቁስሉንም የሚፈውስ የሚያጽናና መልአክ ላከለት፤ መልአኩም ወደ ቅዱስ ጊዮርጊስ ገብቶ ቁስሎቹን ፈወሰ፤ እርሱንም አጽናንቶ ፣ እግዚአብሔር ለእርሱ ያደረገለት ያለውን ሁሉ በግልፅ ነግሮት በክብር አረገ፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስም እግዚአብሔርን አመሰገነ፡፡ሲነጋ የዱዲያኖስ ወታደሮች ወደ ቅዱስ ጊዮርጊስ በመጡ ጊዜ ምንም የግርፋትና የደም መፍሰስ ምልክት ባላገኙ ጊዜ፣ ይልቁንም ቅዱስ ጊዮርጊስ ደስ ብሎት እግዚአብሔርን ሲያመሰግን  አግኝተው ተደነቁ፡፡ ከዚያም “እኛም በቅዱስ ጊዮርጊስ አምላክ እናምናለን፡፡” ብለው ብዙ ሰዎች ሰማዕትነት ተቀበሉ፡፡አንድ ዛፍ በተቆረጠ ጊዜ ከስሩ ብዙ ችግኝ እንዲገኝ በቅዱስ ጊዮርጊስ መከራ መቀበል ብዙ ሰዎች ወደ ሃይማኖት መጡ፡፡

 

3. ስለ መንግሥተ ሰማያት መራራ ሞትን ታገሱ

ቅዱስ ጊዮርጊስ እንዲህ ያለውን ተአምት በማድረግ ብዙ ሰዎች ወደ እግዚአብሔር እንደተመለሱ የተመለከተ ዱድያኖስ አሁንም በቅዱስ ጊዮርጊስ ላይ የሚደርሰውን የመከራ ስልት በመቀያየር አትናስዮስ የተባለ ጠንቋይ አስመጥቶ መርዝ በጥብጦ እንዲጠጣ አዘዘ፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስም የቀረበለትን መርዝ በሰው ሁሉ ፊት በትእምርተ መስቀል አማትቦ ባጣጣመ ጘራራ የሆነውን የሞት ጽዋ ተጎንጭቶ ከባድ መከራ ተቀብሎ እንዲሞት የእግዚብሔር ፈቃዱ ቢሆንም የቅዱስ ጊዮርጊስን ክብር እርሱን ፍፁም መውደዱን ለመግለጽ አምላካችን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ ቅድስት ድንግል ማርምን ባለሟሎቹ ቅዱሳን መላእክትን ወዳጆቹ ነቢያት ሐዋርያት ቅዱሳንን አስከትሎ አፅሙ ወደ ተዘራበት ወደ ይድራስ ተራራ ወረደ በክብር ወረደ፡፡ ቅዱስ ሚካኤልን አዘዘው የተበተነው የወዳጄን የቅዱስ ጊዮርጊስን አፅም ስብሰባህ አምጣ አለው እርሱም እንደታዘዘው ሰበስቦ ወደ ጌታችን አቀረበ ያን ጊዜ ጌታችን በምሕረት እጁ ተቀብሎ  አዳምን የፈጠሩ እጆቼ አንተንም የፈጠሩ አሁንም ወዳጄ ጊዮርጊስ እኔ አዝዤአለሁ ከሞት ተነሣ አለው፡፡ ያን ጊዜ ከጫጉላ ቤት እንደሚወጣ ሙሸራ አምሮበት ከሞት ተነሣ ጌታችንም በአፍ መሳም ሳመው የሚጸናበትን ቅዱስ መንፈሱን አሳደረበት ከዚያም ሊቀበለው ያለውን መከራ የሚያገኘውን ዋጋ ነግሮት በክብር አረገ፡፡

 

ይህ የሆነው ጥር 18 ቀን ነው፡፡ ይህንን መራራ ሞት በእሳት መቃጠል በመንኮራኩር መፈጨት እንደ እህል መዘራት ታግሶ ከእግዚአብሔር ዘንድ በተደረገለት ተአምራት ከሞትም በመነሣቱ ብዚ ሰዎች በቅዱስ ጊዮርጊስ አምላክ አምነው ወደ እውነተኛይቱ ሃይማኖት ተመልሰዋል፡፡ እንግዲህ በገድሉ መጽሐፍ እንተጻፈ ለ7 ዓመት መራራ መራራ የሆነ ብዙ መከራዎችን ታግሶ በስተመጨረሻ በሰይፍ ተከልሎ /አንገቱን ተቆርጦ ከአንገቱም ደም ውኃ ወተት ፈሶ ለተጋድሎው 7 የድል አክሊል ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቀበለ የከበረ ቃል ኪዳን የተቀበለ ሰማዕት ነው፡፡ እኛም ከዚህ ቅዱስ ገድል ተምረን አሰረ ፍኖቱን በመከተል ኦርቶዶክሳዊ ተዋሕዶ ሃይማኖታችንን እንድናጸና ዘመኑ የሚጠይቀውን ሰማዕትነት ምግባር ማቅናት እንድናቀና የሠማዕቱ የቅዱስ ጊዮርጊስ ጸሎትና ቃል ኪዳን ተራዳኢነት አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች የክብርት እመቤታችን አማላጅነት የቅድስት ሥላሴ ቸርነት አይለየን አሜን፡፡

አስተርእዮ

ጥር 20 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ር ለማ በሱፈቃድ

 

አስተርእዮ ማለት መታየት፣ መገለጥ  የመሳሰሉትን ፍች ይይዛል፡፡ ቃሉ አስተርአየ ታየ፣ ተገለጠ ከሚለው የግዕዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ የጥር ወር በሙሉ ዘመነ አስተርእዮ በመባልም ይታወቃል ምክንያቱም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በገባው ቃል ኪዳን መሠረት በሥጋ የተገለጠበት/የታየበት ወቅት በመሆኑ ከልደት በዓል እስከ ጥር መጨረሻ ዘመነ አስተርእዮ ተባለ፡፡ ይህ ብቻም ሳይሆን አንድነት ሦስትነቱም የተገለጠው  በዚሁ ወር ነውና ዘመነ አስተርአዮ ተብሎ ይጠራል፡፡

 

 

በዚህ ጽሑፍ የምናተኩረው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ልጅ ሥጋ ለብሶ የመታየቱ/የመገለጡ ዋና ዋና መክንያቶቹ ምንድናቸው የሚለው ነው፡፡

 

1.    የገባውን ቃል ኪዳን ይፈጽም ዘንድ

እግዚአብሔር ሰውን ፈጥሮ የሚያስፈልገውን ሁሉ አዘጋጅቶ በክብር ይኖር ዘንድ ገነትን አወረሰው፡፡ በማየት የሚደሰትበትና የሚማርበትንም ሥነ ፍጥረትን ፈጠረለት የሚበላውንና የማይበላውንም ለይቶ ሰጥቶት ነበር ነገር ግን የሰው ልጅ አትብላ ያለውን አምላካዊ ትእዛዝ ሳይጠብቅ የተከለከለውን ዕፀ በለስ በመብላቱ ምክንያት ከገነት ተባረረ፡፡ ዘፍ.2፥16 በዚያን ጊዜ ነው ርህራሄ የባህርዩ የሆነ አምላክ ከአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመናት በኋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለው የሚለው የተስፋ ቃል ኪዳን ሰጠው ሲራ.24፥6፡፡

 

አዳምም ከነ ልጆቹ ለአምስት ሺ አምስት መቶ ዘመናት ይህንን ቃል ኪዳን ሲጠባበቅ ኖሯል፡፡ ነቢያቱም ትንቢት ሲናገሩ ቆይተዋል፡፡ ጌታ ራሱ ምልክትን ይሰጣችኋል እነሆ ድንግል ትፀንሳለች ወንድ ልጅም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች በማለት ተስፋውን በትንቢተ ነቢያት በማስታወስ ቆይቷል፡፡ ኢሳ.7፥14

 

በዚህ ዘመን ደቂቀ አዳም በሙሉ በዲያብሎስ ቁራኝነት ተይዘው ተስፋውን ሲጠባበቁ የነበሩበት ዘመን ከዚሁ የጭለማ ዘመን ለመዳን የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ሁሉ ውጤት ያላመጣ ነበርና ጊዜው/ ቃል ኪዳኑ እስኪፈጸም ድረስ በተስፋ ይጠባበቅ ነበር፡፡ ኢሳ.26፥20 ቁጣው እስኪያልፍ ድረስ ጥቂት ጊዜ ተሸሸግ ተብሎ እንደተጻፈው ይህችን ቃል ኪዳን ይፈጽማት ዘንድ ወልደ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ በተለየ አካሉ በሥጋ ተገለጠ ማለት ሥጋን ተዋሐደ፡፡

 

2.    የዲያብሎስን ሥራ ያፈርስ ዘንድ

ወዘሰ ይገብራ ለኀጢአት እምነ ጋኔን ውእቱ እስመ ቀዳሚሁ ለሰይጣን አበሰ ወበእንተ ዝንቱ አስተርአየ ወልደ እግዚአብሔር ከመ ይሰዐር ግብሮ ለጋኔን” ኀጢአትን የሚሠራትም ከዲያብሎስ ወገን ነው፡፡ ጥንቱንም ሰይጣን በድሎአልና ስለዚህ የእግዚአብሔር ልጅ በሥጋ ተገለጠ የዲያብሎስን ሥራ ይሽር ዘንድ 1ዮሐ.3፥8 በማለት ሐዋርያው እንደገለጸው ሰይጣን የሰውን ልጅ እግዚአብሔርን ያህል ጌታ ገነትን የመሰለ ቦታ እንዲያጣ ከደስታ ወደ ዘለዓለም ሐዘን ከነጻነት ወደ ግዞት ከብርሃን ወደ ጨለማ ይገባ ዘንድ ረቂቅ ሥራ ሠርቶ ነበርና ይህንን የዲያብሎስን ሥራ ያፈርስ ዘንድ በሥጋ ተገለጠ፡፡ ዲያብሎስ በሥጋ ከይሲ/በእባብ ሥጋ ተሰውሮ ነገት ገብቶ አዳምና ሔዋንን እንዳሳተ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም የሰውን ልጅ ሥጋ ተዋሕዶ የደያብሎስን ሥራ አፍርሶበታል፡፡ ዲያብሎስ አዳምና ሔዋንን አስቶ የግብር ልጆቹ ይሆኑ ዘንድ አዳም ገብሩ ለዲያብሎስ ሔዋን አመቱ ለደያብሎስ ብለው የፈረሙትን ደብዳቤ በዮርዳኖስና በሲዖል የቀበረውን የጥፋት የተንኮል ሥራውን ያፈርስ ዘንድ ሰው ሆኖ ተገለጠ፡፡ ይህንን የዲያብሎስ ሥራ በዮርዳኖስ ባሕር የተቀበረውን በጥምቀቱ በሲዖል የተቀበረውን በስቅላቱ በሞቱ ደምስሶበታልና “ወነስተ አረፍተ ማእከል እንተ ድልአ በሥጋሁ” በመካከል የነበረውን የጥል ግድግዳ አፈረሰ፡፡ ኤፌ.2፥14 በማለት ሐዋርያው እንደተናገረው የዲያብሎስን ክፉ ሥራ የጥል ግድግዳ ያፈርስ ዘንድ በሥጋ ተገለጠ፡፡

 

3.    አንድነት ሦስትነቱን ይገልጥ ዘንድ

የምስጢረ ሥላሴ ትምህርት በብሉይ ኪዳን ዘመን በግልጥ አይታወቅም ነበር የተገለጠ የታወቀ የተረዳ የአንድነቱን ሦስትነቱን ትምህርት በሚገባ ለማስተማር የተቻለው ጌታችን ሥጋ ለብሶ ከተጠመቀ ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡ “ወርእየ መንፈሰ እግዚአብሔር እንዘ ይወርድ በአምሳለ ርግብ ወናሁ መጻአ ቃል እምሰማይ ዘይብል ዝንቱ ውእቱ ወልድየ ዘአፈቅር ዘቦቱ ሠመርኩ” የእግዚአብሔር መንፈስ በርግብ አምሳል በራሱ ላይ ሲቀመጥ ለመሥዋዕትነት የመረጥኩት ልጄ ይህ ነው፡፡ ማቴ.3፥17 /ሉቃ.3፥21፡፡ መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል አብ በደመና ሆኖ የምወደው ልጄ ይህ ነው የሚለው ቃል በተገለጸ ጊዜ  የአዳምና የሔዋንን የዕዳ ደብዳቤ ይሽር ዘንድ የአንድነት እና ሦስትነት ምሥጢር ገልጿአል፡፡ ይህንን ምሥጢር ይገልጠ ዘንድ በሥጋ ተገለጠ ታየ፡፡ ይህ ምስጢር ጥንተ ዓለም ሳይታወቅ ሳይገለጥ ተሰውሮ ይኖር ነበር፡፡ በእንተ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘኅቡእ ኅርመቱ እምቅድመ ዓለም፤ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ዓለም ሳይፈጠር ተሰውሮ ነበር ከነቢያት ቃል የተነሣ በዚህ ዘመን ተገለጠ፡፡ ሮሜ.16፥24

 

4.    ፈጽሞ እንደወደደን ለመግለጽ

እግዚብሔር ሰውን ምን ያህል እንደወደደ ለመረዳት እግዚብሔር ዓለምን ከፈጠረበት ጥበቡ ይልቅ ዓለምን ያዳነበት ጥበቡን በሚገባ መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም ዓለምን ከፈጠረበት ጥበቡ ይልቅ ያዳነበት ጥበቡ እጅግ ዕፁብ ድንቅ ነውና ማንም ሳያስገድደው ሰው ሁን ብሎ ሳይጠይቀው በገባው ቃል ኪዳን መሠረት ዘመኑን ጠብቆ ሰው ሆኖ ከኀጢአት በስተቀር ሁሉን ፈጽሞ በገዛ ፈቃዱ መከራ ሥጋን ተቀብሎ ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍሶ የዘለዓለም ሕይወትን መስጠት ምን ያህል ፍጹም ፍቅሩን እንደገለጸልን እንረዳለን፡፡ “አልቦ ዘየዐቢ እምዝ ፍቅር ከመ ዘቦ ዘይሜጡ ነፍሶ ህየንተ አእርክቲሁ” ስለወዳጆቹ ሕይወቱን አሳልፎ የሚሰጥ ያለ እንደሆነ ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር የለም ዮሐ.15፥12 ያጠፋው የሰው ልጅ ይሰቀል ይሙት ሳይል እኔ ልሙት ማለት ፍጹም ፍቅር ነው፡፡ ሰው ሰውን የሚወደው ገንዘቡንና የመሳሰሉትን እስከ መስጠት ሊሆን ይችላል፡፡ ሕይወቱን እስከ መስጠት የሚወድ የለም አልነበረም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የወደደውን የሰውን ሥጋ ለብሶ መኪራ ሥጋን ተቀብሎ ሰውን በሞቱ ያድን ዘንድ ሞትን የሞተው ፈጽሞ እንደወደደን ለመግለጥ ነው፡፡ 1ዮሐ.4፥9፡፡ ይህም ፍቅሩ ይቃወቅ ዘንድ በሥጋ ተገለጠ፡፡ ስለዚህ ሊቃውንቱ አስተርእዮ በማለት ሰይመውታል፡፡

“ወአርአየ ስብሐቲሁ ወአምኑ ቦቱ አርዳኢሁ” ዮሐ. 2፤11

ጥር 12 ቀን 2005 ዓ.ም

መ/ር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ


“ጌትነቱን ገለጠ ደቀ መዛሙርቱም በእርሱ አመኑ” በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የበዐላት አከባበር ቀመር ከበዓለ ልደት ፤ግዝረት፤ ጥምቀት ቀጥሎ ቃና ዘገሊላ ይከበራል፡፡ ምክንያቱም ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን አምላካችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ልጅ ለማዳን ወደዚህ ዓለም በመጣበት ወቅት ልዩ ልዩ የሆኑ ድንቅ ተአምራት አድርጓል፡፡ ከእነዚህም የመጀመሪያው በቃና ዘገሊላ በሰርግ ቤት ተገኝቶ ያደረገው ተአምር ተጠቃሽ ነው፡፡

 

ቅዱስ ዮሐንስ በወንጌሉ እንዲህ ጽፎታል፡፡ “በሦስተኛው ቀን በገሊላ ቃና ሠርግ ሆነ” ምን በሆነ በሦስተኛው ቀን የሚል ጥያቄ በሁላችንም እዕምሮ እንደሚመላለስ አያጠያይቅም፡፡ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በማየ ዮርዳኖስ በእደ ዮሐንስ ጥር 11 ቀን ተጠምቆ ሳይውል ሳያድር ዕለቱን ገዳመ ቆሮንቶስ ገብቶ አርባ መዓልትና አርባ ሌሊት ጾሞ ፤ዲያብሎስን ድል ነስቶ፤ መዋዕለ ጾሙን ፈጽሞ ለእኛም ዲያብሎስን ደል የምንነሳበትን መንገድ አሳይቶን ከገዳመ ቆሮንቶስ መልስ ደቀ መዛሙርቱን መረጠ፡፡ ከጥር አሥራ አንድ እስከ የካቲት ሃያ አርባ ቀን ይሆናል፡፡ መዋዕለ ጾሙን የካቲት ሃያ ፈጽሞ በወጣ በሦስተኛው ቀን ገሊላ አውራጃ ቃና በተባለች መንደር ሰርግ ሆነ፡፡ በዚህ ሰርግ ብዙ ሰዎች የታደሙ መሆኑን የወይን ጠጁ ማለቅ ያስረዳል፡፡ በእርግጥም የተጠሩት ሰዎች ብዙ ቢሆንም ብዙዎች መመገብ የሚችል አምላክ በሰርግ ቤት መጠራቱ ልዩ ያደርገዋል፡፡ በዚህ ሰርግ ከሠዎች በተጨማሪ ሦስት አካላት ተጠርተዋል፡፡

1. እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም

“ወሀለወት ህየ እሙ ለእግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስ” የጌታ እናት ከዚያ ነበረች እንዲል እንዲያው ዝም ብሎ አይደለም፡፡ በደግ ሰው ልማድ ተጠርታ እንጂ እመቤታችን በማኅበራዊ ሕይወት የነበራትን ተሳትፎ እና በሰዎች ዘነድ የነበራትን ተዋቂነት ያመለክታል፡፡ በሌላ መልኩ በቤተ ዘመድ ልማድ ማንኛውም ዘመድ እንደተጠራው ሁሉ እርሷም በገሊላ በነበሩት ሰዎች ዘንድ ታላቅና ተዋቂ ስለበረች እና ቤተ ዘመድ በመሆኗ በዚህ ሠርግ ተጠርታ ነበር፡፡የተገኘችው የሰው ሰውኛው ይህ ቢሆንም በዚያ ሠርግ ቤት ማንም ሊሠራው የማይችል የሥራ ድርሻ ነበራት፡፡ይህ በሰዎች ዘንድ የማይታወቅ በእግዚአብሔርና በእርሷ መካከል ያለ አማላጅነት ነው፡፡ የጎደለውን መሙላት ለሚችል ውድ ልጇ የጎደለውን እንዲሞላ ማማለድ ነው ፡፡ እመቤታችን ከሰው ልጆች የተለየች ክብርት ቅድስት ንፅህት ልዩ በመሆኗ የምታውቀውም ምሥጢር ከሰው የተለየ ነው፡፡ “ወእሙሰ ተአቀብ ዘንተ ኩሎ ነገር ወትወድዮ ውስተ ልበ” ማርያም ግን ይህንን ሁሉ ትጠብቀው በልቧም ታኖረው ነበር ሉ.2፤19 ይህን ሁሉ ያለው ድንግል ማርያም አምላክን በመውለዷ ከሰው ልጆች የራቀ ምስጢር የተገለጠላት መሆኑን ያስረዳል፡፡ ይህንን ሁሉ ብሎ እንደ ሸማ ጠቅልሎ እንደ ወርቅ አንከብሎ የተናገረው የተገለጠላት ምስጢር በሰው አንደበት ተነግሮ የማያልቅ እንደሆነ ነው የሚገልጠው፡፡ ምክንያቱም አንድ ሁለት ብለን የምንቆጥረው አይደለምና መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል እንደዚሁ “ፀጋን የተሞላሽ” በማለት የገለጠው ለእርሷ የተሰጠው ባለሟልነት ልዩ መሆኑን ለማስረገጥ ነበር፡፡ ከዚህ የተነሳ በሠርጉ ቤት የምትሰራውን ሥራ በውል ታውቅ ነበርና፡፡

 

2. ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተጠርቶ ነበር

“ወፀውእዎ ለእግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስ” ጌታ ኢየሱስንም ጠሩት” ዮሐ.2፤2 እናትን ጠርቶ ልጅን መተው ተገቢ አይደለምና እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጠርተው ልጇም ጠርተውታል፡፡ ይህም ፍፁም ሰው መሆኑን ያስረዳል፡፡ ሰው ነውና እንደ ሰውነቱ ወደ ሰርግ ቤት ተጠራ፤አምላክ ነውና ጌትነቱን ገለጠ፡፡

 

ከሚደሰቱት ጋር መደሰት ከሚያዝኑ ጋር ማዘን ተገቢ መሆን በቃል ብቻ ሳይሆን በተግባር አስተማረ፡፡ በቃና ዘገሊላ ከሠርግ ቤት እንደሄደ በአልአዛር ቤት ለለቅሶ መገኘቱን ልብ ይሏል፡፡ወደ ሠርግ ቤት የሄደው በደስታ ነበር፡፡ ቅዱስ ያሬድ እንደገለጠው “ሖረ ኢየሱስ በትፍስህት ውስተ ከብካብ እንዘ ይገብር ተአምረ ወመንክረ በውስተ አህዛብ፤ ኢየሱስ በአህዛብ ፊት ተአምራትንና ድንቆችን እያደረገ በደስታ ወደ ሠርግ ሄደ” ወደ አልአዛር ቤት ሲሄድ ግን “ጌታች ኢየሱስ ክርስቶስም እርሷ (ማርታ) ስታለቅስ ባየ ጊዜ በልቡ አዘነ፡፡በራሱም ታወከ(ራሱን ነቀነቀ፡-የሀዘን ነው) ጌታችን ኢየሱስም እንባውን አፈሰሰ ፡፡አይሁድም ምን ያህል ይወደው እንደነበር እዩ አሉ” ዮሐ.11÷33-38

 

ከዚህ እንደ ምንመለከተው ከኀጢአት በቀር የሰውነትን ሥራ መሥራቱን የሰውን የተፈጥሮ ሕግ ምን ያህል እንደ ከበረ እና እንደፈጸመ ያሳያል በመደሰት እና በማዘን ፍጹም ሰው መሆኑን ሲያስረዳን ፍጹም አምላክ መሆኑን በሰርጉ ቤት ውኃውን የወይን ጠጅ በማድረግ በልቅሶ ቤትም ዓልዓዛርን ከአራት ቀናት በኋላ በማስነሣት አስረዳን፡፡ አምላክ ነኝ ከሠርግ ቤት አልሄድም ከልቅሶም ቤት አልገኝም አላለም በትሕትና ራሱን ዝቅ አድርጎ በሰርግ ቤት እንዲሁም የሚያዝኑትን ለማጽናት በልቅሶ ቤት በመገኘቱ ሁሉንም የሰውነት ሥራ አከናወነ፡፡ አምላክ ነው በሰርግ ቤት የጎደለውን መላ፡፡ አምላክ ነውና የሞተውን አልዓዛርን መግነዝ ፍቱልኝ መቃብር ክፈቱኝ ሳይል እንዲነሣ አደረገ፡፡

 

በዚህ የሰርግ ቤት ባይገኝሰዎች ምን ያህል ሀፍረት ይሰማቸው ይሆን? የእርሱ እንዲሁም የእናቱ በሰርጉ ቤት መገኘት ለባለሰርጉና ለታዳሚዎች ሙላት ነበር እርሱ ባይኖር የሰርጉ ቤት የሃዘን ቤት ሊሆን እንደሚችል ምንም ጥርጥር የለውም በዚህ ሰርግ ቤት ተመላጅነት የአምላክ አማላጅነት ደግሞ የፍጡራን መሆኑን አስተምሯል፡፡

“ወሶበ ሀልቀ ወይኖ ወይትቤሎ እሙ ወይንኬ አልቦሙ” ዮሐ.3÷3 “የወይን ጠጅ ባለቀባቸው ጊዜ እመቤታችን የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም” አለችው አማላጅነት የፍጡራን ገንዘብ ነው፡፡ እርሱ አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ÷ ጊዜዬ ገና አልደረሰም አላት” ከአንቺ ጋር ምን ጠብ አለኝ አንቺ ያልሽውን ልፈጽም አይደለም ሰው የሆንኩት አላት ጊዜ ገና አልደረሰም የሚለው ሥራውን ያለ ጊዜው አይሠራውምና ነው፡፡ ለእግዚአብሔር የሥራ ጊዜ አለው” እንዲል፡፡ መዝ.118÷126 በሌላ መልኩ በአምላክነቱ ማንም የማያዝዘው ግድ ይህን አድርግ ብሎ ማንም ሊያሰገድደው የሚችል የወደደውን የሚያደርግ ቢፈልግ የሚያዘገይ ሲፈልግ በዐይን ጥቅሻ በፈጠነ መልኩ መፈጸም የሚችል በራሱ ፈቃድ እንጂ በሰምች ፈቃድ የማይመራ መሆኑን ያስተምረናል፡፡

 

“ፈቃድ በሰማይ እንደሆነች እንዲሁ በምድር ትሁን” ማቴ.6÷ ብላችሁ ለምኑኝ ያለው ለዚህ ነው በሌላ መንገድ የወይን ጠጅ በሙሉ አላላቀም፡፡

 

ያለውን ቢያበረክተው ተአምራቱን አናደቅም፥ ፈጽሞ ጭል ብሎ እስከሚያልቅ “ጊዜ ገና አልደረሰም” አለ፡፡ሰው ቢለምን ቢማልድ በእርሱ ፈቃድ ጊዜው ሲደርስ ነው የሚፈጸመው፡፡ምልጃው አልተስማም ተቀባይነት አላገኝም ማለት ግን አይደለም ተቀባይነት ያገኘ መሆኑ የሚታወቀው በመደረጉ ነው፡፡

 

አማላጅ ያስፈለገው እርሱ የሚያውቀው ነገር ኖሮት በስምአ በለው ለመንገር አይደለም ለሰው ልጆች ያለው ፍቅር ይታወቅ ዘንድ እና የሰው ልጆችን ከችግር የሚያወጣበት መንገዱ ብዙ መሆኑን ለማስረዳት ነው እንጂ፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሚዜዎችን “ኩሎ ዘይቤለክሙ ግበሩ፤ያዘዛችሁን ሁሉ አድርጉ፡፡” ማለቷ “አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ” የሚለው የጌታችን መልስ “እሺታ ይሁንታን” የሚገልጽ መሆኑን ያስረዳል፡፡ “እሱም ውኃ ቅዱና ጋኖችን ምሏቸው” አለ፡፡ እነርሱም በታዘዙት መሠረት እመቤታችን ያላችሁን አድርጉ እንዳለቻቸው ውኃውን ቀድተው ጋኖችን ሞሏቸው፡፡ ውኃውንም ክብር ይግባውና በአምላካዊ ችሎታው ወደ ወይን ጠጅ ለወጠው፡፡ ለአሳዳሪውም ሰጠው አሳዳሪው የወይን ጠጅ የሆነውን ውኃ ቀምሶ አደነቀ ከወዴት እንደመጣ ግን አላወቀም ድንቅ በሆነ አምላክ ሥራ እንደተለወጠም አልተረዳም፡፡ ያን ምስጢር የሚያቀው ባለሰርጉ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ውኃውን የቀዱ ሰዎች ናቸውና፡፡

 

ታዳሚዎችም “ሰው ሁሉ የተሻለውን ወይን አስቀድሞ ያቀርባል በኋላም ተራውን የወይን ጠጅ በኋላ ያቀርባል አንተስ መናኛውን ከፊት አስቀድመህ ያማረውን ከኋላ ታመጣለህን” ብለው አድንቀዋል፡፡ ድሮም የአምላክ ሥራ እንደዚያ ነው ብርሃን ከመፍጠሩ አስቀድሞ ጨለማን ፈጥሯል ከጨለማ ቀጥሎ “ብርሃን ይሁን” በማለት ብርሃንን ፈጥሯል፡፡ መጀመሪያ ብርሃን ተፈጥሮ ኋላ ጨለማ ቢፈጠር ይከብድ ነበርና መጀመሪያ 21 ፍጥረታት ፈጥሯል፡፡ በመጨረሻም በአርዓያውና በአምሳሉ የሥነ ፍጥረት የሆነውን የሰው ልጅ ፈጥሯል፡፡ ናትናኤልንም እንዲህ ብሎታል፡፡ “ከእንግዲህ ወዲህ ከዚህ የሚባልጥ ታያለህ” ማለቱ የእግዚብሔር ሥራ እየቆየ ውብ ያማረ መሆኑን ያመለክታል ሰው ግን ጥሩ ነው፡፡ ያለውን ያስቀድማል ያ ሲያልቅ የናቀውን ይፈልጋል፡፡ “የወደዱትን ቢያጡ ያጡትን ይቀላውጡ” እንዲሉ እግዚብሔር ልማዱ ነው፡፡ ተራውን ከፊት ታላቁን ከኋላ ማድረግ ለሰው መጀመሪያ የተሰጠው የሚያልፈው ዓለም ነው በኋላ የማያልፈው መንግሥተ ሰማያት ይሰጠዋል ሰው መጀመሪያ ይሞታል በመጨረሻ ትንሣኤ አለው፡፡ ሰው መጀመሪያ ሲወለድ ርቀቱን ነው፡፡ ኋላ ልብስ ያገኛል፡፡ ሁብታም ይሆናል፡፡ ሰው ወደዚህ ዓለም ሲመጣ ዓለምን የሚያገኛት የሚተዋወቃት በልቅሶ ነው፤ ኋላ ግን ይደሰታል በሀሳር በልቅሶ ወደመቃብር ይወርዳል፡፡ በደስታ “መቃብር ክፈቱልኛ፥ መግነዝ ፍቱልኝ” ሳይል ይነሣል ይህን የአምላክ ሥራ አድንቆ መቀበል እንጂ መቃወም አይችልም፡፡

 

3. ቅዱሳን ሐዋርያት በዚህ ሠርግ ነበሩ

“ወለአርዳኢሁ ውስተ ከብካብ” እንዲል፡፡ ዮሐ.2፥2 “ደቀመዛሙርቱንም ጠሯቸው” መምህርን ጠርቶ ደቀ መዝሙርን መተው ተገቢ አይደለምና፤ ደቀ መዛሙርቱ ከመምህራቸው ከክርስቶስ ጋር አብረው በሠርግ ቤት ተገኝተው በተደረገው ተአምር ጌትነቱን አምነዋል፡፡ ተአምራቱን ተመልክተዋል፣ ከዋለበት የሚውሉ፥ ከአደረበት የሚያድሩ፥ ተአምራት የማይከፈልባቸው፥ ይህን ዓለም ለማስተማር የተመረጡ ናቸውና፤ አየን ብለው እንጂ ሰማን ብለው አያስተምሩምና፡፡በጠቅላላው የእነርሱ በሰርጉ ቤት መገኘት የሚያስተምርና ካህናት የሌሉበት ሰርግ ሊደረግ እንደማይገባው ነው፡፡ በሰርግ ቤት የካህናት መገኘት እና ቡራኬ መስጠት አስፈላጊ መሆኑን ያስተምራል፡፡ በፍትሐ ነገሥት አን.24 የተገለጸውም ይህ ነው “ወማዕሰረ ተዋሰቦሶ ኢይትፌጸም ወኢይከውን ዘእንበለ በሀልዎተ ካህናት ወጸሎት ዘለዕሌሆሙ” የጋብቻ አንድነት ካህናት ቢኖሩ እንጂ ያለእነርሱ አይጸናም ጸሎት ቢያደርጉ እንጂ ያለ ጸሎት አይፈጸምም” እን. በቃና ዘገሊላው ሰርግ ጋብቻን በጥንተ ፍጥረት “ሰው ብቻውን ይሆን ዘንድ መልካም አይደለም ረዳት እንፍጠርለት” ዘፍ.2፥19 ያለ አምላክ የሐዲስ ኪዳን ጋብቻ በካህናት ቡራኬና ጸሎት መከናወን እንደሚገባው ሲያስተምረን ቅዱሳን ሐዋርያትን ይዞ ተገኝቷል፡፡ የቃና ዘገሊላ ሰርግ እና በሰርጉ ላይ የታዩ ተአምራት ምልጃዎች ሁሉ ሌላም ምሥጢር ያዘሉ ናቸው፡፡ እመቤታችን “የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም” ማለቷ “ወይን” በተባለው የክርስቶስ ደም ዓለም እንዲድን ያስረዳል፡፡ ደምህን አፍሰህ ሥጋህን ቆርሰህ አጽናቸው ማለቷ ሲሆን “ጊዜዪ ገና ነው” የሚለው የጌታ መልስ “ደሙ በዕለተ ዓርብ የሚፈስበት ጊዜ ገና መሆኑን ያስረዳል” ጥንቱን ዓለምን ለማዳን አይደለምን፣ ሰው የሆንኩት ሥጋ የለበስኩት ለዚህ ዓለምን ለማዳን አይደለምን ሲል ነው፡፡

ይቆየን፡፡

timiket05

የጥምቀት በዓል በድምቀት ተከበረ

ጥር 11 ቀን 2005 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

timiket05

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ የሚከበረው የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ጥምቀት በድምቀት ተከበረ፡፡ ጥር10 ቀን 2005 ዓ.ም. ከዋዜማው ጀምሮ  በተከናወነው የከተራ በዓል ታቦታት ከመንበራቸው በመውጣት ምእመናንን እየባረኩ በብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት፤ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ቀሳውስት፤ በሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎችና ምእመናን ታጅበው ወደ ጥምቀተ ባህር በማመራት በድምቀት ተከብሯል፡፡

በተለይም በአዲስ አበባ የአስራ አንድ አድባራትና ገዳማት ታቦታት በቀሳውስት ሽብሸባና ዝማሬ፤ በሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ዝማሬ፤ በምእመናን እልልታ ታጅበው አመሻሽ ላይ  ጃን ሜዳ ወደሚገኘው ጥምቀተ ባህር ደርሰዋል፡፡

 

በሌሎችም አካባቢዎች ተዘዋውረን እንደተመለከትነው በቅዱስ ራጉኤል፤ በደብረ ገሊላ ቅዱስ አማኑኤል፤ በደብረ አሚን አቡነ ተክለ ሃይማኖትና በጎላ ቅዱስ ሚካአል፤ በገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ  እንዲሁም በቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድኋድ በነበረው ሥነ ሥርዓት ሃማኖታዊ ትውፊቱን ጠብቆ ወጣቶች ታቦታቱ የሚያልፉበትን መንገድ ምንጣፍ በማንጠፍ፤timiket05 youthቄጤማ በመጎዝጎዝ ቀሳውስቱና መዘምራን በዝማሬ ፤ ምእመናን በሆታና በእልልታ አጅበው አቅራቢያቸው ወደሚገኘው ጥምቀተ ባህር አምርተዋል፡፡

ጃንሜዳ በነበረው ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ናትናል፤ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የአድባራትና ገዳማት ተወካዮች ፤ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ፤ በበአሉ ላይ ለመገኘት ከተለያዩ ሀገራት የመጡ የአገር ጎብኚዎች፤ የተዘጋጀላቸውን ቦታ በመያዝ ሥነ ሥርዓቱን የተከታተሉ ሲሆን የ2005 ዓ.ም. ተረኛ የሆነው የገነተ ኢየሱስና ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት እንዲሁም የቤተክርስቲያኑ ሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች በየተራ ያሬዳዊ ወረብ አቅርበዋል፡፡

 

በመቀጠልም እለቱን በማስመልከት በአቃቤ መንበረ ፓትርያርክ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል መልካም ፈቃድ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፤ የደቡብና ምዕራብ አዲስ አበባ እንዲሁም የከፋ ሸካ ቤንች ማጂ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እለቱን በማስመልከት ቃለ ምዕዳን ሰጥተዋል፡፡

ብፁዕነታቸው በሰጡት ቃለ ምዕዳን “የእግዚአብሔር ቸርነት ሰፊ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልዑለ ባሕርይውን ዝቅ6 አድርጎ ወደ ባሕረ ዮርዳኖስ ዮሐንስ ወዳለበት ቦታ ለመጠመቅ መጥቷል፡፡ ዮሐንስን አጥምቀኝ ማለቱ ለእኛ አብነት ለመሆንና ለቤተ ክርስቲያን ሥርዓትን ለመመሥረት ሲል ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ እጅ ተጠመቀ፡፡ ዮሐንስ ወደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሔዶ አጥምቆት ቢሆን ኖሮ ምእመናን ቀሳውስቱን እቤታችን ድረስ መጥታችሁ አጥመቁን እንጂ ወደ ቤተ ክርስቲያን አንሔድም ባሉ ነበር፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት የሌላት እንዳትሆን ሥርዓትን ለማስተማር ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ ባሕር፤ በዮሐንስ እጅ ተጠመቀ” ብለዋል፡፡

 

በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ “ጥምቀትን በየዓመቱ የምናከብረው እግዚአብሔርን ለማመስገን ነው፤ በዝናብ አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ የሚመግብ እርሱ ነውና፡፡ ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍስሶ የሰጠ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የባህርይ አምላክ ነውና ከሦስቱ አካል አንዱ አካል መሆኑን በአደባባይ የገለጠበት ታላቅ የቤተ ክርስቲያናችን በዓል ነው” በማለት እለቱን በማስመልከት የገለጹ ሲሆን በብፁዕነታቸው ቡራኬ የበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል፡፡

 

ከበዓሉ ፍጻሜ በኋላ ካነጋርናቸው የውጪ ዜጎች መካከል፤ “ሚስተር ጆራ እባላለሁ፡፡ የመጣሁት ከስዊድን ነው፡፡ ክርስቲያን ነኝ፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ኢትዮጵያ የመጣሁት ከአስራ አራት አመት በፊት ነው፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ለብዙ ጊዜያት ኢትዮጵያ መጥቼ የኢትዮጵያን የጥምቀት በዓል አክብሬያለሁ፡፡ ይህንን ሥነ ሥርዓት ባየሁ ቁጥር ሁልጊዜ እደነቃለሁ፡፡ ኢትዮጵያ ፍፁም የተለየ ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓት ያላት ሀገር ናት፡፡ በመላው ዓለም እንደዚህ ዓይነት ደማቅ ክብረ በዓል የሚያከብር የለም፡፡ በጣም የተለየ ነው፡፡ ይህንንም በማየቴ በጣም ተደስቻለሁ” በማለት ነበር የተሰማውን ስሜት የገለጸው፡፡

timiket 2005 mezemiran

የበዓሉ ሥነ ሥርዓት ምሽቱን በመቀጠል ትምህርት በተለያዩ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት የተሰጠ ሲሆን በእለቱ ተረኛ በሆኑት በገነተ ኢየሱስና በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ያሬዳዊ ዝማሬ ቀርቧል፡፡ የማኅበረ ቅዱሳን መዝሙር ክፍል አባላትም በተለያዩ ቋንቋዎች ያሬዳዊ ዝማሬ አቅርበዋል፡፡ እንዲሁም በማኅበረ ቅዱሳን የአቡነ ጎርጎርዮስ የአብነትና የዜማ መሳሪያዎች ማሰልጠኛ ክፍል አባለት በገና በመደርደር በዓሉን አድምቀውታል፡፡ በተጨማሪም በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ዜማዊ ድራማ በምሽቱ ለነበረው ምእመን በማቅረብ ሲያገለግሉ አምሽተዋል፡፡ሌሊቱንም በሊቃነ ጳጳሳት እየተመራ ጸሎቱ የቀጠለ ሲሆን የቅዳሴ ሥርዓቱ ተከናውኗል፡፡

 

ከለሊቱ 12፡30 ሰዓት ጀምሮ በብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እየተመራ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የግሪክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ አቡነ ጴጥሮስ፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ተወካይ ክቡር አቶ ታደሰ በንቲ፤ በኢትዮጵያ የግብጽ አምባሳደር፤ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች፤ አገር ጎብኚዎች፤ የየአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎችና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንዲሁም ምእመናን በተገኙበት የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀትን በማስመለከት ጸሎተ ወንጌል በማድረስ መርሐ ግብሩ ተጀመረ፡፡ ጸበሉም ተባርኮ ለምእመናን በመርጨት የበዓሉ ሥነ ሥርዓት ቀጠለ፡፡

 

በዋዜማው ያሬዳዊ ዝማሬ በማቅረብ የበዓሉ ድምቀት የነበሩት የገነተ ኢየሱስና ቅደስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን እንዱሁም የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት ያሬዳዊ ዝማሬ ያቀረቡ ሲሆን የአጫበር ቆሜ ወረብም የመርሐ ግብሩ አንድ አካል ነበር፡፡

ዝማሬው  እንደተጠናቀቀ በብፁዕ አቡነ ናትናኤል አቃቤ መንበረ ፓትርያርክ መልካም ፈቃድ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ዑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እለቱን በማስመልከት ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል፡፡ ባሰተላለፉት ትምህርትም “በዓላችን የሰላማችን ፤የአንድነታችን ምልክት ነው፡፡ መሠረቱም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ አደባባይ ተገኝቶ የእኛን ችግር ያስወገደበት ፤ ነፃነታችንን ያገኘንበት፤ የኀጢዓት ደብዳቤያችን የተቀደደበት፤ዮርዳኖስን ተሻግረን በአንድነት ድኅነት መንግስተ ሰማያትን ያየንበት እለት ነው፡፡ ዛሬ በአንድነት በዘመነ ፍዳ የተዘጋው ጆሯችን የአብ ድምጽ የሰማበት ቀን ነው፡፡” ብለዋል፡፡

 

በመቀጠል የግሪክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንabune petros the greece እየተስፋፋች ነው፡፡ በዓሉ እጅግ የደመቀ ነው፡፡ በጣም ተደስቻለሁ፡፡ እጅግ የደመቀ በዓል ስላዘጋጃችሁ እግዚአብሔር ይባርካችሁ” በማለት ደስታቸውን የገለጹ ሲሆን የግብጽ አምባሳደር፤ አንዲሁም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ተወካይ ክቡር አቶ ታደሰ በንቲ ንግግር አድርገዋል፡፡

 

በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርስ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት ቃለ ምዕዳን “እኛ ኢትዮጵያውያን በየዓመቱ የምናከብረው የጥምቀት በዓል ብሔራዊ በዓላችን ነው፡፡ መገለጫችንም ነው፡፡ ድኅነተ ስጋ ወነፍስ ያገኘንበት ቀን በመሆኑ እንኳን ደስ ያላችሁ” ብለዋል፡፡

 

በብፁዕነታቸው ቡራኬም የበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል፡፡ በጥር 12 ከሚከብሩት የሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ታቦታት በስተቀር ከየአድባራቱና ገዳማት ወደ ጥምቀተ ባሕር መጥተው የነበሩት ታቦታት በመጡበት ሁኔታ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ዘማርያን እንዲሁም በምዕመናን ታጅበው ምዕመናንንና አካባቢውን እየባረኩ በድምቀት እንደወጡ በድምቀት ተመልሰዋል፡፡

 

የጥምቀት በዓል በድምቀት ተከበረ
በእንዳለ ደምስስ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ የሚከበረው የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ጥምቀት በድምቀት ተከበረ፡፡ ጥር10 ቀን 2005 ዓ.ም. ከዋዜማው ጀምሮ  በተከናወነው የከተራ በዓል ታቦታት ከመንበራቸው በመውጣት ምእመናንን እየባረኩ በብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት፤ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ቀሳውስት፤ በሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎችና ምእመናን ታጅበው ወደ ጥምቀተ ባህር በማመራት በድምቀት ተከብሯል፡፡
በተለይም በአዲስ አበባ የአስራ አንድ አድባራትና ገዳማት ታቦታት በቀሳውስት ሽብሸባና ዝማሬ፤ በሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ዝማሬ፤ በምእመናን እልልታ ታጅበው አመሻሽ ላይ  ጃን ሜዳ ወደሚገኘው ጥምቀተ ባህር ደርሰዋል፡፡
በሌሎችም አካባቢዎች ተዘዋውረን እንደተመለከትነው በቅዱስ ራጉኤል፤ በደብረ ገሊላ ቅዱስ አማኑኤል፤ በደብረ አሚን አቡነ ተክለ ሃይማኖትና በጎላ ቅዱስ ሚካአል፤ በገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ  እንዲሁም በቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድኋድ በነበረው ሥነ ሥርዓት ሃማኖታዊ ትውፊቱን ጠብቆ ወጣቶች ታቦታቱ የሚያልፉበትን መንገድ ምንጣፍ በማንጠፍ፤ ቄጤማ በመጎዝጎዝ ቀሳውስቱና መዘምራን በዝማሬ ፤ምእመናን በሆታና በእልልታ አጅበው አቅራቢያቸው ወደሚገኘው ጥምቀተ ባህር አምርተዋል፡፡
ጃንሜዳ በነበረው ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ናትናል፤ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የአድባራትና ገዳማት ተወካዮች ፤ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ፤ በበአሉ ላይ ለመገኘት ከተለያዩ ሀገራት የመጡ የአገር ጎብኚዎች፤ የተዘጋጀላቸውን ቦታ በመያዝ ሥነ ሥርዓቱን የተከታተሉ ሲሆን የ2005 ዓ.ም. ተረኛ የሆነው የገነተ ኢየሱስና ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት እንዲሁም የቤተክርስቲያኑ ሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች በየተራ ያሬዳዊ ወረብ አቅርበዋል፡፡
በመቀጠልም እለቱን በማስመልከት በአቃቤ መንበረ ፓትርያርክ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል መልካም ፈቃድ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፤ የደቡብና ምዕራብ አዲስ አበባ እንዲሁም የከፋ ሸካ ቤንች ማጂ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እለቱን በማስመልከት ቃለ ምዕዳን ሰጥተዋል፡፡
ብፁዕነታቸው በሰጡት ቃለ ምዕዳን “የእግዚአብሔር ቸርነት ሰፊ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልዑለ ባሕርይውን ዝቅ አድርጎ ወደ ባሕረ ዮርዳኖስ ዮሐንስ ወዳለበት ቦታ ለመጠመቅ መጥቷል፡፡ ዮሐንስን አጥምቀኝ ማለቱ ለእኛ አብነት ለመሆንና ለቤተ ክርስቲያን ሥርዓትን ለመመሥረት ሲል ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ እጅ ተጠመቀ፡፡ ዮሐንስ ወደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሔዶ አጥምቆት ቢሆን ኖሮ ምእመናን ቀሳውስቱን እቤታችን ድረስ መጥታችሁ አጥመቁን እንጂ ወደ ቤተ ክርስቲያን አንሔድም ባሉ ነበር፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት የሌላት እንዳትሆን ሥርዓትን ለማስተማር ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ ባሕር፤ በዮሐንስ እጅ ተጠመቀ” ብለዋል፡፡
በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ “ጥምቀትን በየዓመቱ የምናከብረው እግዚአብሔርን ለማመስገን ነው፤ በዝናብ አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ የሚመግብ እርሱ ነውና፡፡ ሥጋውን ቆርሶ ደሙን አፍስሶ የሰጠ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የባህርይ አምላክ ነውና ከሦስቱ አካል አንዱ አካል መሆኑን በአደባባይ የገለጠበት ታላቅ የቤተ ክርስቲያናችን በዓል ነው” በማለት እለቱን በማስመልከት የገለጹ ሲሆን በብፁዕነታቸው ቡራኬ የበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል፡፡
ከበዓሉ ፍጻሜ በኋላ ካነጋርናቸው የውጪ ዜጎች መካከል፤ “ሚስተር ጆራ እባላለሁ፡፡ የመጣሁት ከስዊድን ነው፡፡ ክርስቲያን ነኝ፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ኢትዮጵያ የመጣሁት ከአስራ አራት አመት በፊት ነው፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ለብዙ ጊዜያት ኢትዮጵያ መጥቼ የኢትዮጵያን የጥምቀት በዓል አክብሬያለሁ፡፡ ይህንን ሥነ ሥርዓት ባየሁ ቁጥር ሁልጊዜ እደነቃለሁ፡፡ ኢትዮጵያ ፍፁም የተለየ ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዓት ያላት ሀገር ናት፡፡ በመላው ዓለም እንደዚህ ዓይነት ደማቅ ክብረ በዓል የሚያከብር የለም፡፡ በጣም የተለየ ነው፡፡ ይህንንም በማየቴ በጣም ተደስቻለሁ” በማለት ነበር የተሰማውን ስሜት የገለጸው፡፡
የበዓሉ ሥነ ሥርዓት ምሽቱን በመቀጠል ትምህርት በተለያዩ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት የተሰጠ ሲሆን በእለቱ ተረኛ በሆኑት በገነተ ኢየሱስና በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ያሬዳዊ ዝማሬ ቀርቧል፡፡ የማኅበረ ቅዱሳን መዝሙር ክፍል አባላትም በተለያዩ ቋንቋዎች ያሬዳዊ ዝማሬ አቅርበዋል፡፡ እንዲሁም በማኅበረ ቅዱሳን የአቡነ ጎርጎርዮስ የአብነትና የዜማ መሳሪያዎች ማሰልጠኛ ክፍል አባለት በገና በመደርደር በዓሉን አድምቀውታል፡፡ በተጨማሪም በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ዜማዊ ድራማ በምሽቱ ለነበረው ምእመን በማቅረብ ሲያገለግሉ አምሽተዋል፡፡
ሌሊቱንም በሊቃነ ጳጳሳት እየተመራ ጸሎቱ የቀጠለ ሲሆን የቅዳሴ ሥርዓቱ ተከናውኗል፡፡
ከለሊቱ 12፡30 ሰዓት ጀምሮ በብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እየተመራ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የግሪክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ አቡነ ጴጥሮስ፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ተወካይ ክቡር አቶ ታደሰ በንቲ፤ በኢትዮጵያ የግብጽ አምባሳደር፤ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች፤ አገር ጎብኚዎች፤ የየአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎችና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንዲሁም ምእመናን በተገኙበት የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጥምቀትን በማስመለከት ጸሎተ ወንጌል በማድረስ መርሐ ግብሩ ተጀመረ፡፡ ጸበሉም ተባርኮ ለምእመናን በመርጨት የበዓሉ ሥነ ሥርዓት ቀጠለ፡፡
በዋዜማው ያሬዳዊ ዝማሬ በማቅረብ የበዓሉ ድምቀት የነበሩት የገነተ ኢየሱስና ቅደስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን እንዱሁም የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት ያሬዳዊ ዝማሬ ያቀረቡ ሲሆን የአጫበር ቆሜ ወረብም የመርሐ ግብሩ አንድ አካል ነበር፡፡
ዝማሬው  እንደተጠናቀቀ በብፁዕ አቡነ ናትናኤል አቃቤ መንበረ ፓትርያርክ መልካም ፈቃድ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ዑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እለቱን በማስመልከት ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል፡፡ ባሰተላለፉት ትምህርትም “በዓላችን የሰላማችን ፤የአንድነታችን ምልክት ነው፡፡ መሠረቱም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮርዳኖስ አደባባይ ተገኝቶ የእኛን ችግር ያስወገደበት ፤ ነፃነታችንን ያገኘንበት፤ የኀጢዓት ደብዳቤያችን የተቀደደበት፤ዮርዳኖስን ተሻግረን በአንድነት ድኅነት መንግስተ ሰማያትን ያየንበት እለት ነው፡፡ ዛሬ በአንድነት በዘመነ ፍዳ የተዘጋው ጆሯችን የአብ ድምጽ የሰማበት ቀን ነው፡፡” ብለዋል፡፡
በመቀጠል የግሪክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እየተስፋፋች ነው፡፡ በዓሉ እጅግ የደመቀ ነው፡፡ በጣም ተደስቻለሁ፡፡ እጅግ የደመቀ በዓል ስላዘጋጃችሁ እግዚአብሔር ይባርካችሁ” በማለት ደስታቸውን የገለጹ ሲሆን የግብጽ አምባሳደር፤ አንዲሁም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ተወካይ ክቡር አቶ ታደሰ በንቲ ንግግር አድርገዋል፡፡
በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርስ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት ቃለ ምዕዳን “እኛ ኢትዮጵያውያን በየዓመቱ የምናከብረው የጥምቀት በዓል ብሔራዊ በዓላችን ነው፡፡ መገለጫችንም ነው፡፡ ድኅነተ ስጋ ወነፍስ ያገኘንበት ቀን በመሆኑ እንኳን ደስ ያላችሁ” ብለዋል፡፡
በብፁዕነታቸው ቡራኬም የበዓሉ ፍጻሜ ሆኗል፡፡ በጥር 12 ከሚከብሩት የሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ታቦታት በስተቀር ከየአድባራቱና ገዳማት ወደ ጥምቀተ ባሕር መጥተው የነበሩት ታቦታት በመጡበት ሁኔታ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ዘማርያን እንዲሁም በምዕመናን ታጅበው ምዕመናንንና አካባቢውን እየባረኩ በድምቀት እንደወጡ በድምቀት ተመልሰዋል፡፡

 

gubae

የሥነ ጽሑፍ ውድድር

gubae

ጥምቀት በቅዱስ ኤፍሬም

ጥር 9 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ


ቅዱስ ኤፍሬም በጥምቀት ላይ እጅግ ጥልቅ የሆነ አስተምህሮ ያለው አባት ነው፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም በጥምቀት የገሃነም እሳት ይጠፋል ይለናል፡፡ “የሰውነት ትኩሳት ከሰውነታችን በሚመነጨው ላቦት እንዲቀዘቅዝ እንዲሁ በጥምቀት የገሃነም እሳት ይጠፋል፡፡”

 

ከዚህ ተነሥተን እንደ ቅዱስ ኤፍሬም ምልከታ የገሃነም ቦታዋ ከሰውነታችን ውስጥ ናት ማለት ነው፡፡ እሳቱ የማይጠፋ መባሉም ከእኛ ዘለዓለማዊነት ጋር የተቆራኘ መሆኑን መረዳት እንችላልን ፡፡ እኛ ዘለዓለማውያን ሆነን ስለተፈጠርን እሳቱም በሰውነታችን ውስጥ ዳግም አይቀጣጠልም፡፡ ይህ የሚያስረዳን ከጥምቀት በኋላ በራሳችን ፈቃድና ምርጫ በድርጊትም ይሁን በቃል ጌታችንን እስካልካድነው ድረስ የገሃነም እሳት በሰውነታችን ውስጥ እንደማይኖር ነው፡፡

 

ስለዚህ መዳን አለመዳን በእጃችን እንደተያዘች መረዳት እንችላለን፡፡ ነገር ግን ይህን መብታችንን የማንጠቀምበት ጊዜ ይመጣል፡፡ እርሱም በምጽአትና በሞት ወደ እግዚአብሔር ለፍርድ የተወሰድንበት ወቅት ነው፡፡ እስከዛው ድረስ ግን የገሃነምን እሳት በሰውነታችን ላይ ማቀጣጠልም ይሁን ማጥፋት ወይም ሰውነታችንን የጌታ ቤተመቅደስ ማድረግ ወይም አለማድረግ የእኛ ፈንታ ይሆናል፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም ጥምቀትን ወደሰማያት የምንወጣጣበት መሰላል ብሎም ይጠራዋል፡፡

 

“እርሱ ወደ ጥምቀት በመውረድ ጥምቀትን መሠረተልን እርሱም በሠራልን ጥምቀት ወደ ሰማየ ሰማያት ተነጠቅን ፡፡”

¨ ቅዱስ ኤፍሬም መጠመቂያ ገንዳውን በክርስቶስ መስቀል ይመስለዋል፡፡ በውስጡም ክርስቶስን

 

ለብሰን እንወለዳለን ሲለን እንዲህ ይላል፡፡

“የክርስቶስ መንጎች እጅግ ደስ ተሰኝተው የእርሱን አርዓያ የነሡበትን ሕያውና ቅዱስ የሆነውን መስቀል ከበው ቆመዋል፡፡ በዚያ ውስጥ ፍጥረታት እንደገና ተፈጥረው ይታያሉ፡፡ ሁሉም ሕያውና ቅዱስ በሆነው መስቀሉ ታትመዋል፡፡”

 

¨ ቅዱስ ጴጥሮስ በጌታ ትእዛዝ በቀኝ በኩል የጣለው መረብ ፻፶፫ ዓሣት ይዞለት ነበር፡፡ ይህ የጥምቀት ምሳሌ ነው፡፡

 

“ከባህር ውስጥ በቅዱስ ጴጥሮስ መረብ ፻፶፫ ዓሣት ተሠግረው ነበር፡፡ እንዲሁ በእርሱ ስብከት በጥምቀት እቅፍ ዐሥር ሺሕና ከዚያም በላይ የሆኑትን በማጥመድ የእግዚአብሔር ልጆች እንዲሆኑ ማረካቸው” ይለናል፡፡

 

¨ “በምድር ላይ እሳትን ልጥል መጣሁ አሁን የእነደደ ከሆነ ዘንድ ምን እፈልጋለሁ” (ሉቃ.፲፪፥፵፰) የሚለውን የጌታ ቃል ለመንፈስ ቅዱስ በመስጠት እንዲህ ብሎ ያስተምራል፡፡

 

“ጌታችን “በምድር ላይ እሳትን ልጥል መጣሁ” ሲል እኔ የማጠምቀው ጥምቀት በዚህ ነው ሲለን ነው፡፡ እሳት ያለውም መንፈስ ቅዱስን ነው፡፡”

 

“በጥምቀት እሳት በክፉው ሰይጣን የተቀጣጠለውን እሳት አጠፋለሁ፡፡ ንጹሕ የሆነው በተጠማቂያን ነፍስ ውስጥ የተቀጣጠለው መለኮታዊው እሳት መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ በእርሱ እሳትነት በኀጢአታችንና በመተላለፋችን ምክንያት የተቀጣጠለውን የገሃነም እሳትን ይጠፋልናል፡፡

 

“ይህ እሳት በምሳሌ በሲና ምድረ በዳ በእሾኽ ቁጥቋጦ ውስጥ ለሙሴ የታየው እሳት ነው ፡፡ ሙሴ ያየው እሳት እሾኹንና ቁጥቋጦውን አላቃጠለውም ነበር፡፡ ነገር ግን በጥምቀት በእናንተ ውስጥ የተቀጣጠለው መለኮታዊ እሳት የኀጢአት ቁጥቋጦውን አቃጥሎ ያጠፋዋል ፡፡ ስለዚህም እርሻው እስከሰማይ የሚደርስ ፍሬን ያፈራል፡፡

 

¨ ቅዱስ ኤፍሬም ጥምቀትን ነቢዩ ኤርምያስን በፀነሰችው ማኅፀን መስሎ ያስተምራል፡፡

“ነቢዩ ኤርምያስ ገና ከእናቱ ማኅፀን ሳለ ተቀደሰ ተማረ፡፡ ደካማ የሆነችው ማኅፀን የፀነሰችውን ቀድሳ የወለደች ከሆነ እንዴት ጥምቀት ከእርሷ ማኅፀን የተፀነሱትን ይበልጥ ቀድሳ አትወልዳቸው ይሆን? ጥምቀት ተጠማቅያንን ንጹሐንና መንፈሳውያን አድርጋ ትወልዳቸዋለች፡፡”

 

የውኃንም ተፈጥሮ በማንሣት ጥምቀትን በውሃ ተፈጥሮአዊ ጠባይ መስሎ ያስረዳል፡፡ “ውኃ በተፈጥሮው እንደመስታወት ነው ፡፡ አንድ ሰው በውኃው መስታወትነት እርሱ ምን እንደሚመስል ተረድቶ እራሱን ያስተካክላል ፡፡ ወደ ጥምቀት ተመልከት በእርሱ ውስጥ ያለውን ውበትን ልበሰው፡፡”

 

በሥነ ፍጥረት የመንፈስ ቅዱስ በውኃ ላይ መስፈፍን ለጥምቀት ሰጥቶ ይተረጉመዋል “በሥነ ፍጥረት መንፈስ ቅዱስ በውኃ ላይ በመስፈፉ ምክንያት ውኃ ፀንሳ ዓሣትንና አእዋፋትን እባብንም አስገኝታ ነበር፡፡ እንዲሁ በጥምቀት መንፈስ ቅዱስ ውኃ ላይ በመስፈፉ ምክንያት በንስር የሚመሰሉትን ደናግላንንና ጳጳሳትን ወለደች፡፡ በዓሣት የተመሰሉትን ራሳቸውን ለመንግሥተ ሰማያት ጃንደረቦች ያደረጉትንና ቅዱሳንን ወለደች፡፡ አስቀድሞ ተንኮለኞች የነበሩትን በእባብ የሚመሰሉትን ወገኖች ደግሞ የዋሃን ርግቦች እንዲሆኑ አድርጋ ወለደቻቸው፡፡”

 

ቅዱስ ኤፍሬም አዳም በክርስቶስ አካል ተጠምቆአል ብሎ ያስተምራል፡፡

“በጌታ ጥምቀት አዳም በገነት ዛፎች መካከል ያጣውን የጸጋውን ልብስ አገኘው፡፡ እርሱ ወደ ውኃ ውስጥ በመጥለቅ በውኃ ውስጥ ያንን የጸጋ ልብስ ለብሰው በእርሱም አጌጦና ተውቦ ወጣ፡፡ ምኅረቱን ሙሉ ለሙሉ የሰጠን አምላካችን እርሱ የተመሰገነ ይሁን፡፡”

 

በጥምቀት የምንለብሰው መንፈስ ቅዱስን ቅዱስ ኤፍሬም ያዕቆብ በፎኖተ ሎዛ በሕልም ባየው መሰላል መስሎ ይገልጸዋል፡፡

 

“ወንድሞች ሆይ ዐይኖቻችሁን ክፈቱና ተመልከቱ ልክ ያዕቆብ እንደተመለከተው መሰላል ዓይነት በአየሩ ላይ በዐይን የማይታይ አምድ ተተክሎ ይታያችኋል፡፡ የዚህ አምድ መሠረቱ በመጠመቂያው ውኃው መካከል ሲሆን ጫፉም የሰማይን ደጆች ይነካል፡፡ በእርሱም ወደ መጠመቂያው ገንዳ ብርሃን ይወርዳል ፡፡ በእዚህም አምደ ብርሃን በኩል ተጠማቂያን ወደ ሰማያት ይነጠቃሉ ፡፡ በዚያም በአንድ ፍቅር ይገለጣሉ፡፡”

 

ስለጌታ ጥምቀት አስፈላጊነት ሲያስተምር እንዲህ ይላል ፡-

“ ውኆች በእኔ ጥምቀት ይቀደሳሉ፡፡ ከዚህ ውኃ የሚጠመቁ በእኔም ምክንያት እሳታውያንና መንፈሳውያን ይሆናሉ፡፡ ከዚህ ካልተጠመቁ በቀር ፍጹማን አይሆኑም፤ እኔም ከመሠረትኩት ጥምቀት የሚጠመቅ ሰውም የሲኦል ሞት አይኖርበትም”

 

“እኔ በመሠረትኩት ጥምቀት እስረኞች ነጻ ይወጣሉ፡፡ የተጻፈውም የእዳ ደብዳቤ ይሰረዛል፡፡ በጥምቀት ውኃ ውስጥም ተጠማቅያን እኔን ለማገልገል ሥልጣንን ይረከባሉ፡፡ ነገር ግን ይህ ሁሉ የሚሆነው እኔ ተጠምቄ ጥምቀትን ከባረኩዋት በኋላ ነው፡፡”

 

ጥምቀትን ሲያመሰግናትም እንዲህ ይላል፡፡

“ በልቡናችን ዐይኖች ጥምቀት እንዴት ውብ ናት ፡፡ ሁላችን ወደ እርሱዋ እናስተውል፡፡ ማኅተም እንዲቀረጽ እንዲሁ እኛም በጥምቀት አርዓያውን እንመስል ዘንድ ተቀርጸናል፡፡ የበጎቹ ልብ እንደ ወተት ነጭ ነው፡፡”

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የጥምቀት በዓል በዮርዳኖስ ወንዝ /ለሕፃናት/

ጥር 9 ቀን 2005 ዓ.ም.
ከወልደ ኢየሱስ /ቤካ ፋንታ/

 

ልጆችዬ እንኳን ለጥምቀት በዓል በሰላም አደረሳችሁ! ዛሬ ስለ ታላቁ በዓል ስለ ጥምቀት ብዙ የምነግራችሁ ነገር አለኝ፡፡ በደንብ ተከታተሉኝ እሺ፡፡

 

በገዳም ውስጥ ለሠላሳ ዓመት ለብቻው ሆኖ እግዚአብሔርን እያመሰገነ የሚኖር የእግዚአብሔር አገልጋይ ነበር፡፡ ስሙም ቅዱስ ዮሐንስ ይባላል፡፡ ልጆችዬ የቅዱስ ዮሐንስ ልብስ ምንድር መሰላችሁ የግመል ቆዳ ነበረ፣ የሚበላው ደግሞ በበረሃ የሚገኝ ማር ነው፡፡ በገዳም ሲኖር ሁል ጊዜ እግዚአብሔርን በደስታ እየዘመረ ያመሰግነው ነበር፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን ከሚኖርበት ገዳም ተነሥቶ ዮርዳኖስ ወደሚባል ወንዝ እያስተማረ መጣ፡፡ ትምህርቱም “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ፡፡” የሚል ነው፡፡ ያን ጊዜ ይህንን ትምህርት የሰሙ በጣም ብዙ ሕፃናት፣ ወጣቶች እና ትልልቅ ሰዎች ወደ ቅዱስ ዮሐንስ ተሰብስበው መጡና ያጠፉትን ጥፋት፣ የበደሉትን በደል፣ የሠሩትን ኃጢአት ሁሉ እየነገሩት /እየተናዘዙ/ በጸበል አጥምቀን አሉት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም የዮርዳኖስን ወንዝ በእግዚአብሔር ስም ሲባርከው ጸበል ሆነ፡፡ ከዚያም የተሰበሰቡትን ሁሉ ወንዶችን ሴቶችን እና ሕፃናትን በጸበሉ አጠመቃቸው፡፡

 

ልጆችዬ ከዚያም ምን ሆነ መሰላችሁ? ፈጣሪያችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ ሊጠመቅ መጣ፡፡ አጥማቂው ቅዱስ ዮሐንስም ኢየሱስ ክርስቶስን ሲያየው ፈጣሪዬ ሆይ አጥምቀኝ አለው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን አይሆንም አንተ አጥምቀኝ ብሎት በጥር 11 በቅዱስ ዮሐንስ እጅ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠመቀ፡፡ ስለዚህም አምላካችን በዚህች ቀን ስለተጠመቀ ዛሬ የምናከብረው የጥምቀት በዓላችን የተባረከ ሆነ፡፡

 

ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ ከውኃ ሲወጣ  በጣም የሚያስደንቅ ተአምር ታየ፡፡ ሰማያት ተከፈቱ፤ ከሰማዩ ውስጥም መንፈስ ቅዱስ በነጭ ርግብ ተመስሎ መጣና በጌታችንነ በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  በራሱ ላይ ተቀመጠ፡፡ ከዚያም አንድ ታላቅ ድምፅ ከሰማይ ውስጥ ተሰማ፡፡ እንዲህ የሚል “በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፡፡”

 

ልጆችዬ ዛሬም እኛ ክርስቲያኖች ከጥር ዐሥር ጀምረን ነጭ የሀገር ልብስ ለብሰን ቅዱሱን ታቦት አጅበን እየዘመርን፣ እልል እያልን የምንዘምረውና በጸበል የምንጠመቀው በመስቀልም በአባቶቻችን ካህናት የምንባረከው አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተጠመቀበት ቀን ስለሆነ ነው፡፡

 

አገራችን ኢትዮጵያ ደግሞ በሁሉም ቤተ ክርስቲያን ያሉት ታቦታት ጥር አሥር ቀን ከየቤተ ክርስቲያኑ ወጥተው ወደ ጥምቀተ ባሕር /ጸበሉ ቦታ/ ሄደው እየተዘመረ፣ እየተጸለየ በምስጋና ይታደራል፡፡ በነጋታው ጥር 11 በጠዋት ውኃው ተባርኮ ጸበል ይሆናል፡፡ በሥፍራው የተሰበሰቡትን ክርስቲያኖች ሁሉንም በጸበሉ እየረጩ ያጠምቋቸዋል፡፡ በመጨረሻም የእግዚአብሔር ማደሪያ ቅዱስ ታቦቱ በካህናቱ ዝማሬ በምእመናን እልልታ ታጅቦ ወደ ቤተ ክርስቲያን ይመለሳል፡፡

አሁን ደግሞ ጥያቄ ልጠይቃችሁ፡-

  1. ቅዱስ ዮሐንስ የሚኖረው በየት ነበር?

  2. ጌታችን መድኃኒጻችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተጠመቀው የት ነው?

  3. ኢየሱስ ክርስቶስን ያጠመቀው ማን ነው?

  4. ቅዱስ ዮሐንስ ያጠመቃቸው  ወገኖች እነማን ናቸው?

ልጆችዬ ከመሰናበቴ በፊት ለዛሬ የምታነቡትን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ልንገራችሁ፡፡ ይኸውም የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ ሦስት ነው፡፡ ስለተከታተላችሁኝ የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር ይስጥልኝ፡፡ እመቤታችን ድንግል ማርያም ታሳድግልኝ፡፡ መልካም የጥምቀት በዓል ይሁንላችሁ፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ጥምቀት

ጥር 9 ቀን 2005 ዓ.ም

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


በሰው ልጅ ዘላለማዊ ድኅነት ውስጥ ትልቁን ድርሻ የሚይዘው ሥርዓተ ጥምቀት ከሌሎቹ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን በቀዳሚነት የሚፈጸምና የማይደገም ሥርዓት ነው፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ “አንዲት ጥመቀት” በማለት የሥርዓተ ጥምቀትን አለመደገምና አለመሠለስ ገልጦ ተናግሯል /ኤፌ.4፥5/፡፡ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ተመዝግቦ እንደሚገኘውና፥ የታናሽ እስያ ክፍል በሆነችው ቁስጥንጥንያ በ381 ዓ.ም. የተሰበሰቡ 150 የሃይማኖት አባቶቻችን “ወነአምን በአሐቲ ጥምቀት ለሥርየተ ኀጢአት፣ ለኀጢአት ማስተሥረያ /ኀጢአትን በምታስተሠርይ/ በአንዲት ጥምቀት እናምናለን” በማለት የጥምቀትን አንድ መሆንና ኀጢአትን በደልን የምታርቅ፣ የምታስወግድ ስለመሆኗ በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ተመርተው ተናግረዋል፡፡ ሃይማኖታቸውንም ገልጠዋል፡፡

 

ጥምቀት የሚለውን ቃል አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ሲተረጉሙ “ጥምቀት” በቁሙ፡- “ማጥመቅ፣ መጠመቅ፣ አጠማመቅ፣ ጠመቃ፣ የማጥመቅና የመጠመቅ ሥራ፣ ኅፅበት፣ በጥሩ ውኃ የሚፈጸም” በማለት ተርጉመውታል፡፡ ምሥጢረ ጥምቀትን የመሠረተው ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ጌታችን ሥርዓተ ጥምቀትን የመሠረተው በሦስት ዓይነት መንገዶች እንደሆነ መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡

 

ሦስቱ መንገዶች የሚባሉትም ትምህርት፣ ትዕዛዝና ተግባር ናቸው፡፡ ይኸውም ሊታወቅ በዮሐንስ ወንጌል ምዕ.3 ቁጥር 5 ላይ “እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡ ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፥ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነው፡፡ ዳግመኛ ልትወለዱ ያስፈልጋችኋል ስላልሁህ አትደነቅ፡፡” በማለት የአይሁድ አለቃ ለነበረው ለኒቆዲሞስ ጌታችን ያስተማረውን ትምህርት ልብ ላለው ጥምቀት በጌታችን ትምህርት መመሥረቷን ይረዳል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በትዕዛዝም ጭምር ጥምቀትን መሥርቷል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ በወንጌሉ የጌታችንን ትዕዛዝ እንዲህ ያስነብበናል፡- “እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፡፡” /ማቴ.28፥19/ መምህረ ትሕትና የሆነው መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተግባር መምህር ነውና ተጠመቁ ብሎ ካስተማረውና ካዘዘው በተጨማሪ ሥርዓተ ጥምቀትን በተግባር ጭምር መሥርቷል፡፡ በማቴዎስ ምዕራፍ 3 በማርቆስ ምዕራፍ 1 እና በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ 3 ላይ በስፋት እንደተመዘገበው ጌታችንና አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ባሕረ ዮርደኖስ ሄዶ ከባሪያው ከዮሐንስ እጅ ሥርዓተ ጥምቀትን ፈጽሟል፡፡ በዚህም ትሕትናንና የትሕትናን አሠራር ፈጣሪያችን አሳይቷል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በበዓላት አከባበር ሥርዓት መሠረት በየዓመቱ ጥር 10 ቀን /የከተራ ዕለት/ ታቦታተ ሕጉ ከመንበረ ክብራቸው በመነሣት ወደ ጥምቀተ ባሕሩ ይጓዛሉ፡፡ ይህም ጌታችን በኪደተ እግሩ እየተመላለሰ ምድርን እንደቀደሳት በማሰብና እርሱኑ አርዓያ በማድረግ ሀገሩን መንደሩን ለመቀደስና ለመባረክ የሚፈጸም ዑደት ነው፡፡

 

ሥርዓተ ጥመቀት በአጋጣሚ ወይም በድንገት የተጀመረ /የተመሠረተ/ አይደለም፡፡ በዘመነ ብሉይ በርካታ ምሳሌዎች የተመሰሉለት፣ በርካታ ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት ነው እንጂ፡፡ በነቢዩ ሕዝቅኤል እግዚአብሔር አምላካችን አድሮ ሲናገር “ጥሩ ውኃንም እረጭባችኋለሁ፣ እናንተም ትጠራላችሁ ከርኲሰታችሁም ሁሉ ከጣዖቶቻችሁም ሁሉ አጠራችኋለሁ፡፡” ብሏል፡፡ /ሕዝ.36፥25/ ከኀጢአት የሚያነጻ ከርኲሰት የሚቀድስ ለመንግሥተ ሰማያት የሚያዘጋጅ የሚያበቃ ጥሩ ውኃ ተብሎ የተገለጸ ጥምቀት መሆኑን ልብ ይሏል፡፡

 

ሥርዓተ ጥምቀትን የመሠረተው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለመሆኑ በአጭሩ ከገለጽን፤ ጌታችን የተጠመቀው ለምንድር ነው? የሚል ጥያቄ ቢነሣ፡-

 

ጌታችን እርሱ ባወቀ ጥምቀትን የፈጸመበት ዋነኛ ምክንያቶች እንደ ሊቃውንት አባቶቻችን አስተምህሮ በሦስት መንገዶች ይታያል፡፡ እነዚህም

 

1ኛ ምሥጢረ ሥላሴን /ሦስትነቱን ያስረዳን ዘንድ ነው/ ማቴ.3፥13-17 በዘመነ ብሉይ በነበሩ ሰዎች በረቂቅና በምሳሌ ይታወቅ የነበረውን የልዩ ሦስትነቱንና አንድነቱን ምሥጢር በተረዳ በታወቀና በጎላ ሁኔታ እንረዳ ዘንድ ጌታችን ተጠምቋል፡፡ በቅዱስ ወንጌላችን በግልጽ እንደሚታየው አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ የስም፣ የአካል፣ የአካለ ግብር ሦስትነት እንዳላቸው በጊዜ ጥምቀቱ ለክርስቶስ እንረዳለን፡፡ ይኸውም እግዚአብሔር አብ በሰማይ ሆኖ፡- “በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው” በማለት እኔ ባይ አካል እንዳለው ገልጿል፡፡ እግዚአብሔር ወልድ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በነሣው ሰውነት በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ በዮሐንስ እጅ በመጠመቅ እርሱም እንደ ባሕርይ አባቱ የራሱ እኔ ባይ አካል እንዳለው ገልጦ አሳይቶናል፡፡ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል ሆኖ ከሰማይ በመውረድ ታይቷል፤ በዚህም መንፈስ ቅዱስ እንደ አብና ወልድ እኔ ባይ አካል እንዳለው ተረድተናል፡፡ ስለሆነም ጌታችን ጥምቀትን የፈጸመው የሦስትነቱን ምሥጢር ይገልጽልን ዘንድ ነው፡፡

 

2ኛ ለትምህርት ለትሕትና ለአርዓያነት

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥርዓተ ጥምቀትን የፈጸመው እንደእኛ የሰው ልጆች የልጅነትን ጸጋ ለማግኘት አይደለም፡፡ እርሱ አብን በመልክ የሚመስለው በባሕርይ የሚተካከለው፤ ተቀዳሚም ተከታይም የሌለው የአብ የባሕርይ ልጁ ነውና፡፡ /ዮሐ.1፥18፣ ዮሐ.3፥16/ እንዲሁም እንደ ንዑስ ክርስቲያን ሥረየት ኃጢአትንም ለማግኘት አይደለም፡፡ ነውርም ኀጢአትም በደልም ምንም ምን ክፋት የሌለበት ንጹሐ ባሕርይ ነውና ነቢዩ በአፉም ተንኮል አልተገኘበትም እንዳለ /ኢሳ.53፥9፤ ማር.2፥10፣ ሉቃ.7፥49/ ነገር ግን በርዕሳችን እንደተገለጠው ጌታችን ሥርዓተ ጥምቀትን የፈጸመው ለትምህርት፣ ለትሐትናና ለአርአያነት ነው፡፡ ንጉሠ ነገሥት ኢየሱስ ክርስቶስ ሕይወትን የሚሰጥ እርሱ እንደ ደካማ ሰው ወደ ባሕረ ዮርዳኖስ ሄዶ ከዮሐንስ ዘንድ ሲጠመቅ ትሕትናን አስተምሮናል፡፡ ዮሐንስን መጥተህ አጥምቀኝ ሳይል ፤ ከዮሐንስ ዘንድ ሄዶ ተጠመቀ፡፡ የቱንም ያህል ክብር ሥልጦን…. ቢኖረን እኛም ከካህናት ዘንድ መሄድ እንዳለብን ሲያስተምረን ነው፤ /ዮሐ.131-17 እና 1ኛ ጴጥ.2፥26/

 

3ኛ. ጥምቀታችንን ይባርክልን ዘንድ

እንፈጽመው ዘንድ የሚገባንንና የሚያስፈልገንን ሥርዓት ሁሉ የሠራልን ፈጣሪያችን ነው፡፡ በገዳመ ቆሮንቶስ አርባ ቀን አርባ ሌሊት በመጾም ጾማችንን እንደባረከልን /ማቴ.4፥1-10/ በጥምቀቱ ጥምቀታችንን ይባርክልን ዘንድ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዘመነ ሉቃስ በወርኀ ጥር በ11ኛው ቀን ማክሰኞ ሌሊት 10 ሰዓት ተጠምቋል፡፡

 

እኛ የሰው ልጆች ሥርዓተ ጥምቀት እንዲፈጸምልን የሚያስፈልገው፡-

የልጅነት ጸጋን እናገኝ ዘንድ ነው፡፡ ዮሐ.1፥5

አስቀድመን ከሥጋ እናት አባታችን በዘር በሩካቤ እንደተወለድንና የሥጋ ልጅነትን እንዳገኘን ሁሉ በማየ ገቦ ስንጠመቅ ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ እንወለዳለን፡፡ ይህንን አስመልክቶ ጌታችን “ከሥጋ የሚወለድ ሥጋ ነው፥ ከመንፈስ የሚወለድ መንፈስ ነው” ብሎ ከማስተማሩ በፊት “ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም” ያለው፡፡ /ዮሐ.3፥3 እና 6/ በምሥጢረ ጥምቀት ሀብተ ወልድና ስመ ክርስትና ስለመገኘቱ አስተምሯል፡፡ ሐዋርያውም በጥምቀት ስላገኘነው የልጅነት ጸጋ አስመልክቶ ሲናገር “አባ አባት ብለን የምንጮኸበትን /የምንጣራበትን/ የልጅነትን መንፈስ ተቀበላችሁ እንጂ እንደገና ለፍርሃት የባርነትን መንፈስ አልተቀበላችሁምና፡፡ የእግዚአብሔር ልጆች መሆናችንን ያ መንፈስ ራሱ ከመንፈስ ጋር ይመሰክራል፡፡” ብሏል፡፡ /ሮሜ.8፥15-16/ ጌታችንንም ለተቀበሉት ሁሉ በስሙም ላመኑበት በጠቅላላው የእግዚአብሔር ልጆች ይሁኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጥቷቸዋል፡፡ እነርሱም ከእግዚአብሔር ተወለዱ እንጂ ከደም ወይም ከሥጋ ፈቃድ ወይም ከወንድ ፈቃድ አለመወለዳቸው ተገልጿል፡፡ /ዮሐ.1፥11-13/

 

እንግዲህ እኛ ክርስቲያኖች ሁለት ልደታት እንዳሉን እናስብ፡፡ ይኸውም መጀመሪያው ከሥጋ እናትና አባታችን የተወለድነው ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ ከእግዚአብሔር የምንወለደው ነው፡፡ ከተወለድን በኋላ እድገታችን በሁለቱም ወገን መሆን ያስፈልጋዋል፡፡ ሰው ሥጋዊም መንፈሳዊም ነውና፡፡

 

ሥርየተ ኀጢአትን ለማግኘት

በአምልኮ ባዕድና በልዩ ልዩ ሁኔታዎች ከጥምቀት በአፍአ ሆነው የቆዩ ሰዎች ከነበረባቸው ኀጢአት ይነፁ ዘንድ ሥርዓተ ጥምቀት ተሠርታለች፡፡ ጌታችን ሞትን ድል አድርጎ በተነሣ በ50ኛው ቀን የመንፈስ ቅዱስ ጸጋና ሀብቱ በቅዱሳን ሐዋርያት ላይ ማደሩን የሰሙ አይሁድ፤ ከቅዱሳን ሐዋርየት ዘንድ ቀርበው የሚናገሩትን ቃለ እግዚአብሔር መስማት ጀመሩ፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን የባሕርይ አምላክነቱን፣ በኃይለ ሥልጣኑ ሞትን ድል አድርጎ መነሣቱንና ወደ ሰማይ ማረጉን ነገሯቸው፡፡ አይሁድም ይህንን በሰሙ ጊዜ ልባቸው ተነካ ጴጥሮስንና ሌሎችንም ሐዋርያት “ወንድሞች ሆይ ምን እናድርግ?” አሏቸው፡፡ ጴጥሮስም “ንስሐ ግቡ ኀጢአታችሁም ይሰረይ ዘንድ እያንዳንዳችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ፤ የመንፈስ ቅዱስንም ስጦታ ትቀበላላችሁ፡፡….” አላቸው /ሐዋ.2፥37-38/ ይህ የሐዋርያው ቃል የሚያስረዳን የጥምቀትን መድኀኒትነት ነው፡፡ አስቀድመን እንደገለጥነው አባቶቻችን በሃይማኖት መግለጫቸው “ወነአምን በአሐቲ ጥምቀት ለሥርየተ ኀጢአት፥ ኀጢአትን በምታስተሠርይ በአንዲት ጥምቀት እናምናለን” ማለታቸው ጥምቀት ከደዌ ነፍስ የምታድን መሆኗን መመስከራቸው ነው፡፡ /ጸሎተ ሃይማኖት/

 

ዘላለማዊ ድኅነት

የሰው ልጅ ድኅነት ቅጽበታዊ አለመሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ይሁንና የድኅነት በር ከፋችና ሌሎችን ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ለመፈጸም የሚያበቃን ምሥጢር ምሥጢረ ጥምቀት ነው፡፡ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱሳን ደቀ መዛሙርቱ በሰጣቸው ሐዋርያዊ መመሪያ ውስጥ “ሑሩ ውስተ ኩሉ ዓለም ወስብኩ ወንጌለ ለኲሉ ፍጥረት፡፡ ዘአምነ ወዘተጠምቀ ይድኅን ወዘሰ ኢአምነ ይደየን፡፡ ወደ ዓለም ሂዱ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ፡፡ ያመነ የተጠመቀ ይድናል ያላመነ ግን ይፈረድበታል፡፡” በማለት ተናግሯል፡፡ /ማር.16፥15-16/

 

እንግዲህ በጥምቀት ያገኘነውን ጸጋና ክብር ሁላችን ልናስብ ያስፈልገናል፡፡ ይህንንም ክብራችንን መጠበቅ ያሻናል፡፡

ፈጣሪያችን በዓሉን የበረክት የረድኤት ያድርግልን፡፡