merecha

የስድስተኛው ፓትርያርክ ምርጫ ውሎ

የካቲት 21 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

merecha

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስድስተኛውን ፓትርያርክ ለመምረጥ በዛሬው ዕለት ከሌሊቱ 12፡00 ሰዓት ጀምሮ መራጮች የምርጫ ካርዳቸውን ይዘው በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ በመግባት ተጀመረ፡፡ ወደ አዳራሹ ሲገባ ከመድረኩ በስተግራና ቀኝ በምድብ ሀ እና ምድብ ለ በኩል የመራጮችን ዝርዝር የሚመዘግቡ አገልጋዮች መዝገቦቻቸውን ይዘው የተዘጋጀላቸውን ሥፍራ ይዘዋል፡፡ አጠገባቸው መራጮች  የመራጭነት ካርዳቸውን ሲመልሱ የሚያኖሩባቸው ሁለት የታሸጉ ሳጥኖች ይታያሉ፡፡  በተወሰኑ ሜትሮች ርቀት ደግሞ መራጮች በምስጢር ድምፅ የሚሰጡበት የተከለለ ስፍራ ይገኛሉ፡፡ መራጮችም ቀስ በቀስ በመግባት በተዘጋጀላቸው ስፍራ ላይ ዐረፍ ብለዋል፡፡ የምርጫው ታዛቢዎች፤ ምርጫውን የሚያስፈጽሙ አገልጋዮች በተመደቡቡት የሥራ ድርሻ ሁሉም ዝግጅታቸውን አጠናቀው የምርጫውን መጀመር በጉጉት በመጠባበቅ ላይ ናቸው፡፡ አስመራጭ ኮሚቴውም ያዘጋጀውን ስለ አምስቱ እጩ ፓትርያርኮች ማንነት የሚገልጽ መጽሔት ለሁሉም እንዲሰራጭ ተደረገ፡፡

 

ከጠዋቱ አንድ ሰዓት ሲሆን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስን ጨምሮ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ወደ አዳራሹ በማምራት በመድረኩ ላይ በተዘጋጀው ልዩ ስፍራ ላይ ዐረፍ ብለዋል፡፡ ከመድረኩ ወረድ ብሎም ከመራጮች ፊት ለፊት ሁለት ባለ መስታወት የምርጫ ሳጥኖች ይታያሉ፡፡

 

ከጠዋቱ አንድ ሰዓት በኋላ በዐቃቤ መንበረ ፓትርያርኩ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል መሪነት ውዳሴ ማርያም፤ የኪዳን ጸሎትና ጸሎተ ወንጌል ከደረሰ በኋላ መራጮች በብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የአስመራጭ ኮሚቴው ሰብሳቢ አማካይነት ቃለ መሐላ ፈጽመዋል፡፡ ወደ ምርጫው ከመገባቱ በፊትም ለመራጮች ተጨማሪ ግንዛቤ ለመስጠት በምርጫውና በአመራረጡ ዙሪያ ማብራሪያ ከአስመራጭ ኮሚቴው ተሰጥቷል፡፡

 

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ አስመራጭ ኮሚቴው የምርጫ ታዛቢዎች፤ መራጮች ባሉበት ሁለቱ የምርጫ ሳጥኖች እንዲታሸጉ ተደረገ፡፡ የምርጫ ሳጥኖቹ መታሸጋቸው ከተረጋገጠ በኋላ በቀጥታ ወደ ምርጫ ሥነ ሥርዓቱ የተገባ ሲሆን በቅድሚያ በመምረጥ ምርጫውን ያስጀመሩት ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርኩ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ናቸው፡፡ በመቀጠልም ብፀዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የመምሪያ ሓላፊዎች፤ የሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጆችና ሌሎችም በቅደም ተከተል መታወቂያቸውንና የምርጫ ካርዳቸውን በመያዝ ከመዝገባቸው ጋር በማመሳከር ከተረጋገጠ በኋላ የምርጫ ወረቀቱን በመውስድ በምስጢር ድምፅ ወደሚሰጡበት ቦታ በመግባት ወረቀቱን ለአራት በማጠፍ ፊት ለፊት ከሚገኙት የምርጫ ሳጥኖች ውስጥ በግልጽ በመጨመር የምርጫው ሥነ ሥርዓት ቀጠለ፡፡

 

የምርጫው ሥነ ሥርዓት እየተከናወነ ሳለ ከግብፅ ተወከወለው የመጡ በብፁዕ አቡነ ጳኩሚስ የቀድሞው የግብፅ አቃቤ መንበረ ፓትርያርክ የሚመራው አምስቱ ልዑካን ወደ አዳራሽ በመግባታቸው የምርጫው ሥነ ሥርዓት እንዲቆም በማድረግ አቀባበል ተደረገላቸው፡፡

 

ከግብፅ የመጡት አባቶችም፡- ብፁዕ አቡነ ጳኩሚስ፤ ብፁዕ አቡነ ቢሾይ፤ ብፁዕ አቡነ ሄድራ፤ ብፁዕ አቡነ ቢመን፤ እንዲሁም ብፁዕ አቡነ ሩፋኤል የግብፅ ኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ሲሆኑ ምርጫውን ከማካሔዳቸው በፊት ብፁዕ አቡነ ጳኩሚስ ቃለ ምእዳን ሰጥተዋል፡፡ በሰጡት ቃለ ምእዳንም “የመጣነው ከኢትዮጵያውያን ወንድሞቻችን ጋር በአሉን ለማክበር ነው፡፡ ይዘን የመጣነው የግብፅ ቅዱሳንን ቡራኬ ነው፡፡ እኛ የቅዱስ ማርቆስ ቡራኬ ይዘን መጥተናል፤ ከኢትዮጵያ ደግሞ የጻድቁ አባት አቡነ ተክለ ሃይማኖትን ቡራኬ ይዘን እንሄዳለን፡፡ እኅት ለሆነችውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንና ኢትዮጵያውያን ታላቅ ፍቅር አለን” በማለት ተናግረዋል፡፡ግብጻውያን ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ምርጫውን በማከናወን ከተሸኙ በኋላ ምርጫው ቀጥሏል፡፡

የከስዓት በኋላውን ሥነ ሥርዓት እንደደረስ እናቀርብላችኋለን፡፡

የስድስተኛው ፓትርያርክ ቅድመ ምርጫ ሂደቶች

የካቲት 20 ቀን 2005 ዓ.ም.
በእንዳለ ደምስስ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የስድስተኛው ፓትርያርክ ምርጫ የካቲት 21 ቀን 2005 ዓ.ም. የሚካሄድ ሲሆን ከምርጫው በፊት ሊከናወኑ የሚገባቸው ተግባራት በአስመራጭ ኮሚቴው እየተመራ ይገኛል፡፡ ሂደቱንም አስመራጭ ኮሚቴው ባወጣው መርሐ ግብር መሠረት በኢትዮጵያ ውስጥ ከሚገኙ አድባራትና ገዳማት፤ ከቤተ ክርስቲያናት፤ ከሰንበት ትምህርት ቤቶች፤ ከምእመናን፤ እንዲሁም ከውጭ ሀገራት በመራጭነት የተወከሉ መራጮች ከየካቲት 18 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ አዲስ አበባ ገብተዋል፡፡

 

የካቲት 19 ቀን 2005 ዓ.ም. ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት ጀምሮ መራጮች ከየሀገረ ስብከታቸው በመራጭነት መወከላቸውን የሚገልጽ ማስረጃ በመያዝ በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ የተገኙ ሲሆን በአስመራጭ ኮሚቴው በምርጫው ሂደት ላይ ገለጻ ተደርጎላቸዋል፡፡ መራጮችን በአግባቡ መመዝገብ እንዲቻል በምድብ እና በምድብ በመመደብ ምዝገባውን በማካሔድ የመራጭነት ካርዳቸውን ወስደዋል፡፡

የካቲት 20 ቀን 2005 ዓ.ም. ሁሉም መራጮች ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት በጠቅላይ ቤተ ክህነት በመገኘት በምርጫው አካሔድ ላይ ሰፋ ያለ ግንዛቤ እንዲኖራቸው ለማስቻል በአስመራጭ ኮሚቴው ማብራሪያዎች ተሰጥተዋል፡፡ ማብራሪያውን የሰጡት የአስመራጭ ኮሚቴው ጸሐፊ ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጬ እና የአስመራጭ ኮሚቴው ሕዝብ ግንኙነት አቶ ባያብል ሙላቴ ናቸው፡፡

 

ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጬ ባስተላለፉት መልእክትም  “ቤተ ክርስቲያንን የሚመሩ አባት ለመምረጥና ምርጫውን ለማካሔድ አደራ ተሸክማችሁ የመጣችሁ በመሆኑ ምርጫውን በራሳችሁ ፈቃድ ከማንኛውም ተጽእኖ ነጻ ሆናችሁ ቤተ ክርስቲንን ሊመሩ ይችላሉ የምትሏቸውን አባት እንድትመርጡ” ብለዋል፡፡ ለመራጮቹም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ውሳኔ የሆነውንና ከአስመራጭ ኮሚቴው የቀረቡለትን አምስቱን ሊቃነ ጳጳሳት ተወያይቶ በእጩነት ለፓትርያርክነት  ለምርጫ ማቅረቡን የሚገልጸው ውሳኔ አንብበዋል፡፡

 

የአስመራጭ ኮሚቴው ሕዝብ ግንኙነት አቶ ባያብል ሙላቴ በሰጡት ሰፋ ያለ ማብራሪያም ”የምርጫውን ካርድ ካልያዛችሁ ወደ ጠቅላይ ቤተ ክህነት መግባት አትችሉም፡፡ ስለዚህ የምርጫ ካርዱን በጥንቃቄ መያዝ ይገባችኋል፡፡ ቢጠፋም ምትክ አንሰጥም” ያሉ ሲሆን የምርጫ ካርድ የያዙትም ከጠዋቱ አንድ ሰዓት ላይ ተጠቃለው ጠቅላይ ቤተ ክህነት ግቢ ውስጥ በመገኘት እነሱን ለማስተናገድ በተመደቡ አገልጋዮች አማካይነት ካርዳቸውንና ማንነታቸውን ከተመዘገበው መዝገብ ላይ በማመሳከር የምርጫ ካርዱን በማስረከብ በተዘጋጀለት ሳጥን ውስጥ እንዲገባ ከተደረገ በኋላ የምርጫ ወረቀቱን በመቀበል ወደ አዳራሽ ውስጥ እንዲገቡ እንደሚደረግ አብራርተዋል፡፡

 

አቶ ባያብል ሙላቴ ማብራሪያቸውን በመቀጠል “ከጧቱ 1፡00 ሰዓት ጀምሮ ብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት ከአቃቤ መንበረ ፓትርያርኩ ጋር በመገኘት እንዲሁም ታዛቢዎች በተገኙበት በአቃቤ መንበረ ፓትርያርኩ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል አማካይነት መራጮች ቃለ መሐላ ይፈጽማሉ” ብለዋል፡፡ በተጨማሪም ቃለ መሐላው ከተፈጸመ በኋላ ለመምረጥ ለእያንዳንዱ ቃለ መሐላ ለማስገባት እንደማይቻል ያስገነዘቡ ሲሆን “ደክማችሁ እንዳትመለሱ በሰዓቱ እንድትገኙ” በማለት ገልጸዋል፡፡

 

የምርጫ ወረቀቱ ምን እንደሚመስል ለመራጮች በግልጽ በማሳየት አቶ ባያብል ሙላቴ በሰጡት ማብራሪያም የአምስቱም እጩ ፓትርያርኮች ፎቶ ግራፍና ስም ጵጵስና በተሾሙበት ጊዜ ቅደም ተከተል መቀመጡን፤ መራጮችም በሚፈልጉት  እጩ ፓትርያርክ ፊት ለፊት ከፎቶ ግራፋቸው ትይዩ  ባለው ሳጥን መሰል ቦታ ውሰጥ አንድ ጊዜ ብቻ የ ምልክት በማድረግ ወረቀቱን አራት ቦታ በማጠፍ በተዘጋጀው ባለ መስታወት የምርጫ ሳጥን ውስጥ እንዲከትቱ በማሳሰብ ከ ምልክቱ ውጪ የምርጫ ወረቀቱ ላይ ምንም አይነት ምልክት ወይም ጽሑፍ መጻፍ እንደማይፈቀድና ተጽፎ ቢገኝ የምርጫ ወረቀቱ እንደሚሰረዝ  አሳስበዋል፡፡

 

ምርጫው ከተጠናቀቀ በኋላ ብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የምርጫው ታዛቢዎችና መራጮች ባሉበት በይፋ ሳጥኑ ተከፍቶ ቆጠራ እንደሚካሔድና ከፍተኛ ድምጽ ያገኙት አባት እዚያው አዳራሹ ውስጥ ሁሉም ባለበት ፓትርያርክ ሆነው መመረጣቸውን እንደሚያበስሩ ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም ሁለት አባቶች ተመሳሳይ ድምጽ ቢያገኙ በዕጣ እንደሚለዩ ገልጸዋል፡፡

belaae sebe

በእንተ በላኤ ሰብእ

belaae sebe

ስምዖን/የበላኤ ሰብእ ታሪክ በተአምረ ማርያም ከተመዘገቡትና የእመቤታችንን አማላጅነት ከሚያሳዩት ታሪኮች አንዱ ነው፡፡ ዘወትር በየዓመቱ በየካቲት 16 ቀን ይዘከራል፣ ይተረካል፣ ይተረጎማል፡፡ የስምዖን በላኤ ሰብእ ዘመን በሁለት ይከፈላል፡-

 

ደገኛው የስምዖን/በላኤ ሰብእ ዘመን

በላኤ ሰብእ አስቀድሞ አብርሃማዊ ኑሮ የሚኖር ደገኛ ሰው ነበር፡፡ እንግዳ በመቀበል ዘመኑን የፈጀ ባዕለ ጸጋ ነው፡፡ ነገር ግን የሰውን ልጆች ጽድቅ የማይወደው ዲያብሎስ ሴራ አሴራበት፡፡ በቅድስት ሥላሴ አምሳል እንግዳ ሆኖ ወደ ቤቱ መጣ፡፡ በላኤ ሰብእም እንደ አብርሃም ዘመን ቅድስት ሥላሴ ከቤቱ በመገኘታቸው ተደስቶ ምንጣፍ ጎዝጉዞ ወገቡን ታጥቆ አስተናገደው፡፡ አብርሃም ለሥላሴ ከቤቱ ከብት መርጦ መሥዋዕት እንዳቀረበ በላኤ ሰብእም የሰባውን ፍሪዳ አቀረበ፡፡ ዲያብሎስ ግን የምትወደኝ ከሆነ ልጅህን እረድልኝ ሲል ጠየቀው፡፡

 

በላኤ ሰብእ የዋሕና ደግ ክርስቲያናዊ ስለ ነበር እሺ በጄ ብሎ ልጁን አቅርቦ ሰዋው፡፡ በኋላም “አስቀድመህ ቅመሰው” የሚል ትእዛዝ ሰጠው፡፡ በላኤ ሰብእም ትእዛዙን ፈጸመ፡፡ ዲያብሎስም ተሰወረው፡፡ በላኤ ሰብእ የልጁን ሥጋ በመብላቱ ደሙንም በመጠጣቱ እንዲሁም በዚህ ጊዜ ሥላሴ ነው ብሎ በቤቱ የተቀበለው ዲያብሎስ ምትሐቱን ጨርሶ በመሰወሩ የተፈጠረበት ድንጋጤ ጠባዩ እንዲለወጥ አእምሮው እንዲሰወር አድርጎታል፡፡ ዲያብሎስ ልቡናውን ስለሰወረበት ከዚያ በኋላ ያገኘውን ሰው ሁሉ የሚበላ ሆኗል፡፡

 

አሰቃቂው የስምዖን/በላኤ ሰብእ ዘመን

በላኤ ሰብእ አእምሮውን ካጣ በኋላ አስቀድሞ ቤተሰቦቹን በላ፤ ከዚያ በኋላ የውኃ መጠጫውንና ጦሩን ይዞ ከሀገሩ ወጣ፡፡ በየቦታው እየዞረ በጉልበቱ ተንበርክኮ፤ በጦሩ ተርክኮ ያገኘውን ሁሉ ይበላ ጀመር፡፡ ይኸ ጊዜ በላኤ ሰብእ ፍጹም በዲያብሎስ ቁጥጥር ሥር የዋለበት አሰቃቂው የበላኤ ሰብእ ዘመን ነበር፡፡

የንስሐ ዘመኑ

ያገኘውን ሁሉ እየገደለ የገደለውንም እየበላ ሲዘዋወር ከአንድ መንደር ደረሰ፡፡ በዚያውም የሚበላውን ሲሻ ሰውነቱን በቁስል የተወረረ ሰው ተመለከተ፡፡ ይበላውም ዘንድ ተንደረደረ፡፡ ያ ድኃ ፈጽሞ የተጠማ ነበርና ውኃ ይሰጠው ዘንድ በላኤ ሰብእን ለመነው፣ በእግዚአብሔር ስም፣ በጻድቃን በሰማእታት ሁሉ ለምኖት ሊራራለት አልቻለም፡፡ በመጨረሻም “ስለ እመቤታችን ብለህ” ሲለው ይህቺ ደግ እንደሆነች በልመናዋም ከሲዖል የምታድን እንደሆነች እኔም ከሕፃንነቴ ጀምሮ ሰምቼ ነበር አለው፡፡ በላኤ ሰብእ “ወደ ልቡናው ተመለሰ”፡፡ ጨካኝ የነበረው ልቡ ራርቶ ለድኃው ጥርኝ ውኃ ሰጠው፡፡ በሕይወቱም ከባድ ውሳኔ ወሰነ፡፡ ከእንግዲህ ከዋሻ ገብቼ ስለ ኀጢአቴ ማልቀስ ይገባኛል፣ እህል ከምበላ ሞት ይሻለኛል” ብሎ እየተናገረ ንስሓ ገብቶ እህልና ውኃ ሌላም አንዳችም ሳይቀምስ በእግዚአብሔር ኀይል ሃያ አንድ ቀን ከተቀመጠ በኋላ ይህ በላኤ ሰብእ ሞተ፡፡

 

ድኅነተ ስምዖን/በላኤ ሰብእ

ከዚህ በኋላ ተአምረ ማርያም የሚተርክልን የበላኤ ሰብእ መዳን ነው፡፡ የበላኤ ሰብእ ነፍስ በፈጣሪ ፊት ለፍርድ ቆመች፡፡ የመጀመሪያው ፍርድም ተሰማ፤ “ይህቺን ነፍስ ወደ ሲዖል ውሰዷት” የሚል፡፡ እመቤታችን ማርልኝ ስትል ለመነችው፡፡ በላኤ ሰብእ ያጠፋቸው ነፍሳትና የሰጠው ጥርኝ ውኃ በሚዛን ተመዘነ በመጀመሪያም የበላኤ ሰብእ ጥፋት መዘነ፡፡ ነገር ግን እመቤታችን ቃል ኪዳኗ ባረፈበት ጊዜ ጥርኝ ውኃው ሚዛን ደፋ፡፡ የበላኤ ሰብእ ነፍስ በእመቤታችን አማላጅነት ዳነች ይህም የእግዚአብሔር ቸርነት የሚያሳይ ነው፡፡ “እንበለ ምግባር ባህቱ እመ ኢየጸድቅ አነ ቦኑ ለከንቱ ኪዳንኪ ኮነ” በማለት የመልክአ ኪዳነ ምሕረት ደራሲ የተናገረው አስቀድሞም በወንጌልም በደቀ መዝሙር ስም ብቻ ቀዝቃዛ ውኃ ያጠጣ ዋጋው አይጠፋበትም /ማቴ.10፥42/ የሚለው ቃል ተፈጸመ፡፡

 

በምልጃዋ በላኤ ሰብእን ያስማረች እመ ብርሃን ሁላችንም ታስምረን፡፡ አሜን፡፡

ምንጭ፡-

  • ተአምረ ማርያም ባለ 402 ምዕራፍ፣ 1988 ዓ.ም.

  • ሐመር መጽሔት 1994 ዓ.ም. ነሐሴ እትም

photo 4

የ5ቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እጩ ፓትርያርኮች አጭር የሕይወት ታሪክ

የካቲት 19 ቀን 2005 ዓ.ም.

ዲ/ን ኅሩይ ባየ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስድስተኛውን ፓትርያርክ ለመምረጥ በዝግጅት ላይ እንደምትገኝ ይታወቃል፡፡ በዚህም መሠረት ቅዱስ ሲኖዶስ አስመራጭ ኮሚቴ በመሠየም እጩ ፓትርያርኮችን ለመምረጥ ከብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት፤ ከካህናት፤ ከሰንበት ትምህርት ቤቶች፤ ከማኅበረ ቅዱሳን፤ እንዲሁም ከምእመናን ጥቆማ እንዲያካሒዱ ተደርጓል፡፡ አስመራጭ ኮሚቴው ጥቆማውን በግብአትነት በመጠቀም አምስት ሊቃነ ጳጳሳትን በእጩነት በማቅረብ የካቲት 16 ቀን 2005 ዓ.ም. ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ አቅርቧል፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤም ከየካቲት 16 – 18 ቀን 2005 ዓ.ም. ድረስ ውይይት በማካሔድ አምስቱም ሊቃነ ጳጳሳት በእጩነት እንዲቀርቡ አጽድቋል፡፡ የካቲት 21 ቀን 2005 ዓ.ም. ለሚካሔደው የስድስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የፓትርያርክ ምርጫ የቀረቡት ብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት፡-  ብፁዕ አቡነ ማትያስ በኢየሩሳሌም የኢትዪጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማት ሊቀ ጳጳስ፤ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ  የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል የምዕራብና የደቡብ አዲስ አበባና የከፋ ቤንች ማጂ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፤ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የወላይታና ዳውሮ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ናቸው፡፡ በዚህም መሠረት አጭር የሕይወት ታሪካቸውን እንደሚከተለው እናቀርባለን፡-

 

ብፁዕ አቡነ ማትያስ :- photo 4

የቀድሞው የአባ ተክለ ማርያም ዐሥራት የአሁኑ ብፁዕ አቡነ ማትያስ በ1934 ዓ.ም ተወለዱ፡፡ ቅዳሴ፣ ዜማ፣ ቅኔ፣ ባሕረ ሐሳብ፣ የመጻሕፍተ ሐዲሳት ትርጓሜ ተምረዋል፡፡ በ1948 ዓ.ም ከብፁዕ አቡነ ማርቆስ ዲቁናን ጮኸ ገዳም ተቀብለዋል፡፡ ከመ/ር ዐሥራተ ጽዮን ኰኲሐ ሃይማኖት መርገ ምንኩስናን ተቀብለዋል፡፡ በ1955 ዓ.ም በ1969 ዓ.ም ከብፁዕ አቡነ መቃርዮስ መርገ ቁምስናን ተቀብለዋል፡፡

 

በጮኸ ገዳም በቄሰ ገበዝነት፣ በመጋቢነትና በልዩ ልዩ ገዳማዊ ሥራ አገልግለዋል፡፡ በገዳሙ ውስጥ በነበራቸው ቆይታ ሐዲስ ኪዳንን አስተምረዋል፡፡ ከ1964 — 68 ዓ.ም በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በቅዳሴና በልዩ ልዩ አገልግሎቶች ተመድበው አገልግለዋል፡፡ ከ1968 ዓ.ም ጀምሮ ለሦስት ዓመታት የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አቡነ ቀሲስና ምክትል ልዩ ጸሐፊ በመሆን አገልግለዋል፡፡ ጥር 13 ቀን 1971 ዓ.ም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንብሮተ እድ ብፁዕ አቡነ ማትያስ በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳም ኤጲስ ቆጶስ ሆነው ተሹመዋል፡፡ በአሁኑ ሰዓትም በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ገዳም ሊቀ ጳጳስ ናቸው፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ :-

photo 1የቀድሞው አባ ኅሩይ ወልደ ሰንበት የአሁኑ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ በ1930 ዓ.ም ተወለዱ፡፡ ጸዋትዎ ዜማ፣ ቅኔ፣ ትርጓሜ መጻሕፍት፣ ፍትሐ ነገሥት፣ ባሕረ ሐሳብና ሐዲስ ኪዳንን ተምረዋል፡፡ በ1945 ዓ.ም ከብፁዕ አቡነ ሚካኤል ዲቁና፤ በ1964 ዓ.ም ምንኩስናን በደብረ ሊባኖስ ገዳም ተቀብለዋል፡፡ በ1965 ዓ.ም ከብፁዕ አቡነ ሚካኤል ቅስና በ1969 ዓ.ም ከብፁዕ አቡነ ሰላማ ቁምስናን ተቀብለዋል፡፡ በደብረ ጽጌ ገዳም በመዘምርነትና በቅዳሴ አገልግለዋል፡፡ ጥር 13 ቀን 1971 ዓ.ም  በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንብሮተ እድ የከፋ ሀገረ ስብከት ኤጲስ ቆጶስ ተብለው ተሹመዋል፡፡ በአሁኑ ሰዓት የሰሜን ጎንደር  ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ናቸው፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ :-

ነሐሴ  16  ቀን  1944  ዓ.ም  በሰሜን  ሸዋ  ክፍለ  ሀገር  በሸኖ አውራጃ  ልዩ  ስሙ  ጨቴ  ጊዮርጊስ  በተባለው  ቦታ ተወለዱ፡፡ የቀድሞ ስማቸው photo 2 ቆሞስ  አባ ኀይለጊዮርጊስ ኀይለ ሚካኤል ይባላል፡፡ ፊደል የቆጠሩት፣ ዜማን የተማሩት፣ ቅኔን የተቀኙት በሀፋፍ ማርያም በኢቲሳ ደብረ ጽላልሽ ገዳም ነው፡፡ ቅዳሴን በዳግማዊ ምኒሊክ መታሰቢያ የቀሳውስት ማሠልጠኛ ት/ቤት ተምረዋል፡፡ በሰዋሰወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ት/ቤት ለ4 ዓመታት ተምረው በዲፕሎማ ተመርቀው ዘመናዊ ትምህርታቸውን እስከ 12ኛ ክፍል በማጠናቀቅ በምዕራብ ጀርመን እሸት ኬርከሌ መንፈሳዊ ት/ቤት ስለ ገዳማት አስተዳዳር አጥንተዋል፡፡

 

ሐምሌ 5 ቀን 1991 ዓ.ም. በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ አንብሮተ እድ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ጳጳስ ተብለው ተሹመዋል፡፡ በአሁኑ ሰአት የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ናቸው፡፡

ምንጭ፡- ዜና ቤተ ክርስቲያን 31ኛ የዓመት ቁ.3፣ ጥር 4 ቀን 1971 32ኛ ዓ.ም ቁ.4


ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፡-

photoየቀድሞ ስማቸው መልአከ ምሕረት አባ ሀብተ ማርያም ይባላል፡፡ ግንቦት 7 ቀን 1946 ዓ.ም በደቡብ ወሎ አማራ  ሳይንት ልዩ ስሙ ደብረ ብርሃን ለንጓጥ ሥላሴ ተወለዱ፡፡ አባታቸው ግራ ጌታ መኮንን ኀይሉ እናታቸው ወ/ሮ አታላይ ደርሰህ ይባላል፡፡ ዜማ፣ አቋቋም፣ ቅኔ፣ ፍትሐ ነገሥት ትርጓሜ ተምረዋል፤ የቅኔ መንገድ ከነአገባቡ ተምረው በመምህርነት ተመርቀዋል በ1956 ዓ.ም ከብፁዕ አቡነ ገብርኤል ዲቁና ተቀብለዋል፡፡

 

ጳጉሜን 3 ቀን 1981 ዓ.ም በደብረ ሊባኖስ ገዳም ሥርዓተ ምንኩስና ፈጽመዋል፡፡ ኅዳር 12 ቅን 1982 ዓ.ም የቅስና ማዕረግ ከብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ፤ ከብፁዕ አቡነ ቄርሎስ መዓርገ ቁምስና ተቀብለዋል፡፡  ከ1982 – 87 ዓ.ም በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በደብረ ሰላም ቅዱስ እስጢፋኖስ በጽርሐ ጽዮን ጎላ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን የመጽሐፍ መምህር ሆነው አገልግለዋል፡፡ ከሠኔ 20 ቀን 1987-1990 ዓ.ም በምሥራቅ ሐረርጌ ሐደሬ ጤቆ መካነ ሥላሴ ደብር፣

 

ከየካቲት 1990-93 ዓ.ም የድሬዳዋ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን፣ ከሠኔ 1 ቀን 1993 ዓ.ም – ሐምሌ 1 ቀን 1994 ዓ.ም ጀምሮ ለጵጵስና መአርግ እስከ በቁበት ዘመን በአዲስ አበባ ቦሌ ደብረ ምጽላል እግዚአብሔር አብ ቤተ ክርስቲያን አገልግለዋል፡፡ ከሐምሌ 1 ቀን 1994 ዓ.ም የሰሜን ወሎ ደብረ ሮሐ ቅዱስ ላሊበላ ገዳም አስተዳዳሪ ሆነው አገልግለዋል፡፡ ነሐሴ 22 ቀን 1997 ዓ.ም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ አንብሮተ እድ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል የከፋ ሀገረ ስብከት ጳጳስ ተብለው ተሹመዋል፡፡ በአሁኑ ሰዓት የምዕራብና ደቡብ አዲስ አበባ ፤ የከፋ ሸካ ቤንች ማጂ አህጉረ ስብከት  ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሐፊ ሊቀ ጳጳስ ናቸው፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፡-

በ1955 ዓ.ም በሰሜን ሸዋ በምንጃር ሸንኮራ ወረዳ ልዩ ስሙ ምንታምር ቀበሌ ከአቶ ጌታነህ የኋላሸትና ከወ/ሮ አምሳለ ወርቅ ማሞ ተወለዱ፡፡photo 3 አቋቋም፣ ቅኔ ከነአገባቡ ቅዳሴ ኪዳን አንድምታ፣ ዜማ፣ ሠለስት፣ አርያም፣ ጾመ ድጓ፣ ቁም ዜማ ተምረዋል፡፡ በ1969 ዓ.ም ከብፁዕ አቡነ መቃርዮስ ዲቁና ተቀብለው ቅስና ከብፁዕ አቡነ ሳሙኤል ተቀብለዋል፡፡ በ1975 ዓ.ም በደብረ ዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ሥርዓተ ምንኩስና ፈጽመዋል፡፡ በሰዋሰው ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ለ4 ዓመታት ያህል ተምረው በዲፕሎማ ተመርቀዋል፡፡ በሆላንድ ሆህ እስኩል የነገረ መለኮት ትምህርት ቤት ገብተው ለ4 ዓመታት ተምረው የመጀመሪያ ዲግሪ ተቀብለዋል፡፡

 

በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት በሰበካ ጉባኤ አደራጅነት፣ በሰ/ት ቤት ሓላፊነት፣ አ/አ ሀገረ ስብከት ሸሮ ሜዳ መንበረ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በሰባኪነት፣ በአ/አ ሀገረ ስብከት በአቃቂ መድኀኔዓለም፣ በቃሊቲ ቅዱስ ገብርኤል፣ በሳሎ ደብረ ፀሐይ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን፣ በመካነ ሰማዕት ቅዱስ ቂርቆስ ደብርና በሐረር ደብረ ገነት መድኀኔዓለም አብያተ ክርስቲያናት በአስሪተዳዳሪነት አገልግለዋል፡፡ በውጭ ሀገር በአሜሪካ ዳላስ ቅዱስ ሚካኤል በአውሮፓ ስዊዘርላንድ በጀኔቫ፣ በሎዛን፣ በዙሪክና በበርንባዝል ከተሞች ባሉ አድባራት በቀዳሽነትና በሰባኪነት አገልግለዋል፡፡

 

ነሐሌ 22 ቀን 1997 ዓ.ም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ አንብሮተ እድ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የዋግ ህምራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው ተሾሙ፡፡ በአሁኑ ሰዓት የየወላይታና ዳውሮ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ናቸው፡፡

ytenaten 058

አምስቱ እጩ ፓትርያርኮች ታወቁ

የካቲት 19 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


ስድስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ÷ አስመራጭ ኮሚቴ ዛሬ የካቲት 18 ቀን 2005 ዓ.ም በሰጠው መግለጫ÷ አምስቱ እጩ ፓትርያርኮችን ይፋ አደረገ፡፡

ytenaten  058ዛሬ ከስዓት በኋላ በቅዱስ ሲኖዶስ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፤ የአስመራጭ ኮሚቴ አባላት፣ እንዲሁም ከልዩ ልዩ የሚዲያ አካላት የተወከሉ ጋዜጠኞች በተገኙበት በተሰጠው መግለጫ ላይ፡-ብፁዕ አቡነ ማትያስ በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ የምዕራብና ደቡብ አዲስ አበባ የከፋ ሸካ ቤንች ማጂ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የወላይታና ዳውሮ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ለፓትርያርክነት እጩ ሆነው መቅረባቸው ተገልጧል፡፡

 

በብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የአስመራጭ ኮሚቴው ሰብሳቢ አማካኝነት የቀረበው መግለጫ “መላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ካህናትና ምእመናን በዕጩነት ከቀረቡት ብፁዓን አባቶች መካከል ለመንጋው እረኛ እግዚአብሔር አምላክ እንዲሰጠን ከምንጊዜውም በላቀ ሁኔታ በጾምና በጸሎት ፈጣሪያቸውን እንዲጠይቁ” አሳስቧል፡፡ ከመግለጫው በኋላ ከጋዜጠኞች ለተነሡ ጥያቄዎች ምላሽ ተሰጥቷል፡፡

hawire ticket

የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ሊካሔድ ነው

የካቲት 18 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

hawire ticket

ማኅበረ ቅዱሳን በ2005 ዓ.ም. የሐዊረ ሕይወት /የሕይወት ጉዞ/ የተሰኘውና ወደ ቅዱሳን መካናት፤ አድባራትና ቤተ ክርስቲያናት የሚያካሄደውን የጉዞ መርሐ ግብር በሆለታ ደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን መጋቢት 22 ቀን 2005 ዓ.ም. እንደሚያካሄድ የማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ዋና ጸሐፊና የጉዞው አዘጋጅ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ግርማ ተሾመ ገለጹ፡፡

hawire 1

 

የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በ2003 ዓ.ም. የተጀመረ ሲሆን ለአራተኛ ጊዜ እንደሚከናወን የገለጹት ምክትል ዋና ጸሐፊው የትኬት ሽያጩንም ከሰኞ የካቲት 18 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ በማኅበሩ የንዋያተ ቅድሳትና የኅትመት ውጤቶች መሸጫ ሱቆች፤ እንዲሁም በማኅበሩ ዋና ጽሕፈት ቤት እንደሚጀመር፤ የቲኬት ሽያጩንም ከጉዞው አሥር ቀን ቀደም ብሎ እንደሚጠናቀቅና በጉዞውም ከዚህ በፊት በተከታታይ ከተደረጉት ጉዞዎች በላቀ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ምእመናን ይሳተፋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም ምእመናን አሳባቸውን ሰብስበው በተረጋጋ መንፈስ ሆነው ከበረከቱ ይሳተፉ ዘንድ የአጽዋማት ወቅቶች የተሻሉ በመሆናቸው ጉዞው መዘጋጀቱን አብራርተዋል፡፡

 

የጉዞውን ጠቀሜታ ሲገልጹም “ትልቁ ጠቀሜታው  ምእመናን በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ዙሪያ ያሏቸው ጥያቄዎች ከታላላቅ ሊቃውንት መልስ የሚያገኙበት፤ እንዲሁም  የወንጌል ትምህርት ለምእመናን በስፋት የሚሰጥበት ነው” ብለዋል፡፡

 

hawire 2ከ2003 ዓ.ም. ጀምሮ  በደብረ ጽጌ ቅድስት ማርያም ገዳም፤ በፍቼ ቅዱስ ጴጥሮስ ቤተ ክርስቲያን፤ እንዲሁም በበኬ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር መካሄዱ የሚታወስ ሲሆን ምእመናን ከወዲሁ ትኬቱን በብር 120፡00 /አንድ መቶ ሃያ/ በመግዛት በጉዞው እንዲሳተፉ የማኅበሩ ምክትል ዋና ጸሐፊና የጉዞው አዘጋጅ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ግርማ ተሾመ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ፍርድ ለነነዌ÷ ሥልጣን ለነነዌ

የካቲት 18 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኩኖአምላክ


ኮናኔ በርትዕ÷ ፈታሄ በጽድቅ÷ የሆነው መድኀኒዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ጻፍት ፈሪሳውያንን በቋንቋቸው በዕብራያስጥ ቢያስተምራቸው “እንደ ሙሴ፡- ባሕር ከፍለህ÷ ጠላት ገድለህ÷ ደመና ጋርደህ÷ መና አውርደህ፣ እንደ ኢያሱ፡- በረድ አዝንመህ÷ ፀሐይ አቁመህ÷ እንደ ጌዴዎን፡- ፀምር ዘርግተህ ጠል አውርደህ፣ እንደ ኤልያስ ሰማይ ለጉመህ እሳት አዝንመህ ልታሳየን እንወዳለን” የሚል ጥያቄ በቀረበለት ጊዜ የሰጣቸው ምላሽ “ክፉና አመንዝራ ትውልድ ምልክት ይሻል÷ ከነቢዩ ከዮናስ ምልክት በቀር ምልክት  አይሰጠውም፡፡ ዮናስ በዓሣ አንበሪ ሆድ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት እንደ ነበረ÷ እንዲሁ የሰው ልጅ በምድር ልብ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት ይኖራል፡፡ የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነሥተው ይፈረዱበታል፤ በዮናስ ስብከት ንስሐ ገብተዋልና÷ እነሆም ከዮናስ የሚበልጥ ከዚህ አለ” የሚል ነው፡፡ ጻፍት ፈሪሳውያንን ምልክት ያስፈለጋቸው ዋነኛ ምክንያት በጌታችንና በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት ለማመን አልነበረም፤ ይልቅስ እንደ ዘማ ሴት ምልክት በምልክት እየተደራረበ ማየትን በመናፈቅ ነው፡፡

 

በመጽሐፍ ቅዱሳችን በተደጋጋሚ እንደተገለጠው የአይሁድ ማኅበረሰብ ሁሉ የጌታችንን የባሕርይ አምላክነቱን አይተው ይረዱ ዘንድ ከሌሎቹ ይልቅ በእነርሱ መኖሪያና መንደር እየተዘዋወረ ድንቅ ሥራን ሠርቷል÷ ድውያነ ሥጋን በተአምራት÷ ድውያነ ነፍስን በትምህርት አድኗል፣ ሙታንን አንሥቷል (ማቴ.8÷28-34፣ ማቴ.9÷18-26፣ ዮሐ.9÷1 እስከ ፍጻሜ ምዕራፍ )፡፡ ነገር ግን ቤተ አይሁድ የእጁን ሥራ አይተው፣ የቃሉን ትምህርት ሰምተው ሊያምኑበት እየተገባቸው አላመኑበትም፡ አሁንም አሁንም እየመላለሱ ምልክትን ታሳየን ዘንድ እንወዳለን ይሉ ነበረ(ማቴ.12÷38)፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ምእመናን በላካት ክታቡ “መቼም አይሁድ ምልክትን ይለምናሉ” በማለት የአይሁድን መሻት (ፈቲው) ምን እንደሆነ ገልጦ ተናግሯል፡፡(1ኛ.ቆሮ. 1÷22)፡፡ ነባቤ መለኮት የተሰኘው ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ በወንጌሉ “ለሰው ሁሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃንስ ወደ ዓለም የመጣው ነው፡፡በዓለም ነበረ፤ ዓለሙም በእርሱ ሆነ፤ ዓለሙ ግን አላወቀውም፡፡ ወደ ወገኖቹ መጣ፤ ወገኖቹ ግን አልተቀበሉትም፡፡ ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑት የእግዚአብሔር ልጆች እንዲሆኑ ሥልጣንን ሰጣቸው፡፡” በማለት መናገሩ የሚታወቅ ነው(ዮሐ.1÷9-12)፡፡የቃሉን ትምህርት ሰምተው፣ የእጁን ተአምር አይተው ሊያምኑበት እየተገባቸው በአንጻሩ ከሀገራችን ውጣልን የሚል ቃል ይናገሩት እንደነበር መጽሐፍ ቅዱስ ይመሰክራል፡፡ ጌታችንም “ ነቢይ ከገዛ አገሩና ከገዛ ዘመዶቹ ከገዛ ቤቱም በቀር ሳይከበር አይቀርም አላቸው።”(ማር.6÷4) በአይሁድ መካከል እየተመላለሰ ማስተማሩ፣ ተአምር ማድረጉ÷ጌታችንን እንዲያምኑትና እንዲያከብሩት አላደረጋቸውም፡፡ ይልቁንም በገዛ ወገኖቹ ተይዞ ባልተገባ ፍርድ ለሞት ተላልፎ እንዲሰጥ ሆነ እንጂ፡፡

 

እንግዲህ የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን በአይሁድ ላይ ተነስተው ይፈርዱባቸው ዘንድ ሥልጣንን ያሠጣቸው ዋነኛው ምክንያት በነቢዩ በዮናስ ስብከት ንስሐ ገብተው  ከእግዚአብሔር ጋር ስለታረቁ ነው (ዮና.3÷10) ፡፡ ቁጥራቸው ከመቶ ሃያ ሺህ በላይ የነበሩና ግራና ቀኛቸውን የማይለዩ ተብሎ የተጻፈላቸው በአሁኑ ጊዜ ኩዌት ቀድሞ ነነዌ ትባል በነበረችው ከተማ የሚኖሩ ሰዎች እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ባለመመላለሳቸው ምክንያት የሚመጣባቸውን መቅሰፍት በንስሐ፣ በጾምና በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ተመልሰው እንዲያርቁት እንዲያስተምራቸው ነቢዩ ዮናስን አዘዘው (ዮና.1÷2) ፡፡ በአጭር ቃል በነቢዩ ዮናስ አማካኝነት የተላለፈውን መንፈሳዊ ትእዛዝና መመሪያ ተቀብለው ተግባራዊ በማድረጋቸው የሚመጣባቸውን መዐት ማራቅ ቻሉ፡፡ “እግዚአብሔርም ከክፉ መንገዳቸው እንደተመለሱ ሥራቸውን አየ እግዚአብሔርም ያደርግባቸው ዘንድ በተናገረው ክፉ ነገር ተጸጽቶ አላደረገውም”(ዮና.3÷10) መምህረ ዮናስ፣ የዮናስ ፈጣሪ ልዑለ ባሕርይ እግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ በአይሁድ መካከል እየተመላለሰ በሠራው ሥራ አለማመናቸው፣ በኀጢአታቸው ተጸጽተው ንስሐ አለመግባታቸው እንደሚስፈርድባቸው ነገራቸው፡፡ በዕለተ ምጽአት (በፍርድ ቀን) በአይሁድ ላይ ለመፍረድ የነነዌ ሰዎች ተነስተው “እኛ እግዚአብሔርን ባለመወቅ÷ እርሱንም በማሳዘን፡- በኀጢአትና በበደል ሥራ ተጠምደን ስንኖር ነቢዩ ዮናስን ልኮልን ባስተማረን ጊዜ ንስሐ ገብተን ምሕረት ቸርነቱ ተደረገልን፤ እናንተ ግን የዮናስ አምላክ፣ የዮናስ ፈጣሪ በመከከላችሁ እየተመላለሰ ያስተማረውን ትምህርት ባለመቀበላችሁ÷ የእጁን ተአምራት አይታችሁ ባለማድነቃችሁ ሊፈረድባችሁ ይገባል፤” ብለው ይፈርዱባችኋል አላቸው፡፡ በእግዚአብሔር ቸርነት ሕዝበ እግዚአብሔር እየተባሉ ይጠሩ የነበሩት እስራኤላውያን የተደረገላቸውን ቸርነት ማድነቅ ሲገባቸው ነገር ግን አልተጠቀሙበትም፡፡ ወደ እነርሱ ከእግዚአብሔር ተልከው የሄዱትን ነቢያት፣ መምህራን  የእግዚአብሔር ሰዎችን ቃላቸውን ከመስማት ይልቅ÷ እኩሌቶቹን አሳደዱ፣ እኩሌቶቹን ደበደቡ፣ እኩሌቶቹን ገደሉ፡፡ቀዳሜ ሰማዕታት ሊቀ ዲያቆናት ቅዱስ እስጢፋኖስ እንደተናገረው ፡-“ከነቢያትስ አባቶቻችሁ ያላሳደዱት ማን ነው? የጻድቁንም መምጣት አስቀድሞ የተናገሩትን ገደሉአቸው፤ በመላእክት ሥርዓት ሕግን ተቀብላችሁ ያልጠበቃችሁት እናንተም አሁን እርሱን አሳልፋችሁ ሰጣችሁት ገደላችሁትም።” (የሐዋ.ሥራ.7÷52-53)፡፡

 

ከነነዌ ሰዎች  የምንማረው ምንድር ነው?

1ኛ. የእግዚአብሔርን ቃል መስማትና ለመፈጸም መነሣትን፤ ሰብአ ነነዌ አስቀድመው ፈቃደ እግዚአብሔርን የማያውቁ እንደነበሩ ይታወቃል፡፡ በትእዛዘ እግዚአብሔር ለመኖር የሚያስችላቸው ቃሉን እንኳ የሚነግራቸው ነቢይ ስላልነበራቸው በኃጢአት ተጠምደው መኖራቸው ታውቋል፡፡ “እኔስ ቀኛቸውንና ግራቸውን የማይለዩ  ከመቶ ሀያ ሺህ የሚበልጡ ሰዎችና ብዙ እንስሶች ላሉባት ለታላቂቱ ከተማ ለነነዌ አላዝንምን?” የሚለው የእግዚአብሔር ቃል የሚያስረዳን እኒህ የነነዌ ሰዎች ቃለ እግዚአብሔርን አለማወቃቸውን ነው፡፡ ይህንኑ አለማወቃቸውን ያሳውቃቸው ዘንድ ነቢዩ ዮናስ ያስተማራቸውን  የእግዚአብሔርን ቃል በመስማት ፈጽመዋል፡፡(ዮና.3÷4)

 

በዚህ ዘመን ያለን ሰዎች ከምንቸገርባቸው ምክንያቶች አንዱ ቃሉን ለመስማትና ለመፈጸም ያለን ትጋት ደካማ መሆን ነው፡፡ አምላካችን “ይሰሙኝስ ዘንድ ለማን እናገራለሁ? ለማንስ አስጠነቅቃለሁ? እነሆ፥ ጆሮአቸው ያልተገረዘች ናት ለመስማትም አይችሉም እነሆ፥ የእግዚአብሔር ቃል ለስድብ ሆኖባቸዋል፥ ደስም አያሰኛቸውም” ብሎ የተነገረው ቃል እንዳይፈጸምብን ልናስብ ይገባናል፡፡ (ኤር.6÷10) ከዚህ ላይ አብሮ መታየት የሚገባው ዐቢይ ጉዳይ ቃሉን ከመስማት ባሻገር እንደቃሉ መኖር የሚገባ መሆኑን ነው፡፡ ብዙዎቻችን የመጽሐፍ ቅዱስን ቃላት በማወቅ ደረጃ እናውቃቸው ይሆናል፤ ነገር ግን ማወቃችን ወደ ሕይወት (ወደ ተግባር) የተሻገረልን ስንቶቻችን እንሆን? እንጃ እግዚአብሔር ይወቀው፡፡ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ በመልእክቱ “ቃሉን የምታደርጉ ሁኑ እንጂ ራሳችሁን እያሳታችሁ የምትሰሙ ብቻ አትሁኑ” በማለት የሰጠንን መንፈሳዊ ምክር ተግባራዊ ማድረግ ያሻናል፡፡(ያዕ.1÷22) ንስሐን የሚቀበል ልዑል እግዚአብሔር ኀጥአን ልጆቹን ከርኩሰታቸው ያጠራቸው ዘንድ በነቢዩ ኢሳይያስ አድሮ ባስተላለፈው የንስሐ ጥሪ ውስጥ “…እሺ ብትሉ ለእኔም ብትታዘዙ…” የሚል ቃል ተናግሯል(ኢሳ.1÷19)፡፡ እንግዲህ ልብ እናድርግ “እሺ” ብሎ ለቃሉ ምላሽ መስጠትና መታዘዝ የተለያዩ ነገራት ናቸው፡፡ ብዙዎቻችን “እሺ” እንል ይሆናል፤ ነገር ግን ታዝዘናል? እንደ ፈቃዱስ ኖረናል? የነነዌ ሰዎች ግን ከዮናስ አንደበት የተላለፈውን መመሪያ (ቃለ እግዚአብሔር) ሰምተው ተግባራዊ አድርገዋል÷ እንዲህ ተብሎ እንደተጻፈ ፡-“ዮናስም የአንድ ቀን መንገድ ያህል ወደ ከተማይቱ ውስጥ ሊገባ ጀመረ ጮኾም፡፡ በሦስት ቀን ውስጥ ነነዌ ትገለበጣለች አለ፡፡ የነነዌም ሰዎች እግዚአብሔርን አመኑ ለጾም አዋጅ ነገሩ÷ ከታላቁም ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ማቅ ለበሱ፡፡”(ዮና.3÷4-5)፡፡ እንግዲህ “ዛሬ ድምፁን ብትሰሙት፥ አባቶቻችሁ እኔን የፈተኑበት የመረመሩበትም አርባ ዓመትም ሥራዬን ያዩበት በምድረ በዳ በፈተና ቀን በማስመረር እንደ ሆነ፥ ልባችሁን እልከኛ አታድርጉ” (ዕብ.3÷8-9) ተብሎ እንደተነገረ፤ ቃሉን በሰማን ጊዜ ልቡናችንን ከጥርጥር፣ ከትዕቢት አንጽተን ለንስሐ እንድንበቃ ፈጣሪያችን ይርዳን!

 

2ኛ. ነቢየ እግዚአብሔር ዮናስን  አክብረው መገኘታቸው፤  ከነነዌ ሰዎች ከምንማራቸው ተግባራት ሁለተኛው ነገር የእግዚአብሔር ሰዎችን አክብሮ መቀበልን ነው፡፡ “ከየት መጣህ? ዘርህ ምንድር ነው?…” የሚሉና እነዚያን የመሳሰሉ ጥያቄዎችን በመጠየቅ ነቢዩን አላስጨነቁም፡፡ ከእግዚአ ነቢያት፣ ከእግዚአ ካህናት የተላከ መሆኑን በመረዳት አክብረው፣ ተግሳፁንም ተቀብለው እንዳስተማራቸው ሆነው ተገኙ እንጂ፤ “ነነዌ ትጠፋለች፣ ነነዌ ትገለነጣለች፣ ትጠፋላችሁ የምትለን የምታሟርትብን አንተ ማነህ” በማለት ለሰይፍ ለእሳት አልዳረጉትም፡፡  “ኢየሩሳሌም ኢየሩሳሌም ሆይ÷ነቢያትን የምትገድል ወደ እርስዋ የተላኩትንም የምትወግር÷…”(ማቴ.23÷37) በማለት መድኀኔዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ የተናገረባት የኢየሩሳሌም ሰዎች እንኳ ፊት፡- ነቢያትን፣ የእግዚአብሔርን ሰዎች፤ ኋላም ሐዋርያትን ያሳደደችና የወገረች መሆኗን ገልጦ ተናግሯል፡፡

 

በዳዊት መዝሙር ውስጥ “እግዚኦ መኑ የኀድር ውስተ ጽላሎትከ፡፡ ወመኑ ያጸልል ውስተ ደብረ መቅደስከ…ዘያከብሮሙ ለፈራሀያነ እግዚአብሔር፤ አቤቱ በድንኳንህ ውስጥ ማን ያድራል? በተቀደሰውም ተራራህ ማን ይኖራል?”(መዝ.14÷1-4) የሚል ቃል ይገኛል፡፡ ከዚህ የምንረዳው ቅዱሳን ነቢያትን፣ ሐዋርያትን ካህናትን በአጠቃላይ ከእግዚአብሔር የተላኩትን ማክበር እነርሱን የላከ ፈጣሪን ማክበር ነው፡፡ እነርሱን መቀበል የላካቸውን መቀበል ነው፡፡ ይህም ሊታወቅ ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱሳን ሐዋርያቱ በሰጣቸው ሐዋርያዊ ተልእኮ ውስጥ፡-“እናንተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል÷ እኔንም የሚቀበል የላከኝን ይቀበላል” በማለት የተናገረውን ልብ ይሏል፤(ማቴ. 10÷40) በሐዋርያት ሥራ ላይ እንደተጠቀሰው ያ ከእናቱ ማኅጸን ጀምሮ ሲወጣ አንካሳ ሆኖ የተወለደውና በቤተ መቅደስ ተቀምጦ ምጽዋት ይለምን የነበረውን ሰው÷ ብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ዮሐንስ “ወደ እኛ ተመልከት” በማለት ባዘዙት ጊዜ ወደ እነርሱ ተመልክቶ ከደዌው ለመፈወስ ችሏል፡(የሐዋ.ሥራ.3÷4-6) እኛም ወደ ቅዱሳን ገድል፣ ቃል ኪዳናቸው… ብንመለስ ወደ እግዚአብሔር መመለሳችን እንደሆነ አስበን÷ በቅዱሳኑ ጸሎት ምልጃና ቃል ኪዳን ለመጠቀም እንችል ዘንድ የእግዚአብሔር ቸርነት አይለየን፡፡

 

3ኛ ኃጢአት በደልን አምኖ ንስሐ መግባትን ከነነዌ ሰዎች ልንማረው የሚገባን ክርስቲያናዊ ተግባር ነው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ሰዎችን በኀጢአት በበደል እንዲጸኑ ከሚያደርጓቸው ሁኔታዎች አንዱ ምክንያተኝነት ወይም ለራስ ይቅርታ ማድረግ ነው፡፡ በኀጢአታችን ንስሐ መግባት እየተጠበቀብን ነገር ግን ለፈጸምነው ስህተት ሌላ ምክንያት ስናቀርብ እንሰማለን፡፡ ይህ ነገርም ቅጣታችንን ያበዛው እንደሆነ እንጂ በበደል ከመጠየቅ ነጻ አያደርገንም፡፡ በመጽሐፍ እንዲህ ተብሎ እንደተገለጠው “ኀጢአቱን የሚሰውር አይለማም የሚናዘዝባትና የሚተዋት ግን ምሕረትን ያገኛል፡፡”(ምሳ.28÷13) የነነዌ ሰዎች የሚያተምሩን አንዱ ነገር ኀጢአት በደልን መታመንን ነው፡፡ ስለሆነም ለበደላችን ምክንያትን የምንደረድር ሰዎች ምን ያህል ከጸጋ እግዚአብሔር እንደተራቆትን ልናስብ ልንጸጸትም ይገባናል፡፡ ንጉሥ ዳዊት ቤርሳቤህን አስነውሮ÷ ኦርዮንን ባስገደለ ጊዜ እግዚአብሔር በነቢዩ በናታን አድሮ ስለኀጢአቱ ሲወቅሰው፡-“ዳዊትም ናታንን፦ እግዚአብሔርን በድያለሁ አለው።” ተብሎ ነው የተጻፈው(2ኛ.ሳሙ12÷13)፡፡ ኃጢአት በደላችንን ብናምን እንደ ቅዱስ ቃሉም በካህናትም ፊት ቀርበን ብንናዘዝ አምላካችን ከኀጢአታችን ሊያነጻን የታመነ ነው፡፡ “በኀጢአታችን ብንናዘዝ ኀጢአታችንን ይቅር ሊለን ከዓመፃም ሊያነጻን የታመነና ጻድቅ ነው፡፡”ተብሎ እንደ ተጻፈ፡(1ኛ.ዮሐ.1÷8-9) እንግዲህ ከዚህ በመማር እንደ ሰብአ ነነዌና እንደ ዳዊት ኀጢአታችንን በማመንና ንስሐ በመግባት ምሕረት እንድናገኝ አምላካችን ይርዳን፡፡ዳዊት ኀጢአቱን በታመነ ጊዜ “ናታንም ዳዊትን፦ እግዚአብሔር ደግሞ ኀጢአትህን አርቆልሃል አትሞትም” ብሎታል፡፡ “የነነዌ ሰዎችም ከክፉ መንገዳቸው እንተመለሱ ሥራቸውን አየ፤ እግዚአብሔርም ያደርግባቸው ዘንድ በተናገረው ክፉ ነገር ተጸጽቶ አላደረገውም፡፡” (2ኛ.ሳሙ12÷13፤ዮና.3÷10)

 

4ኛ ፍጹም የሆነ የጾም የጸሎት ሕይወትን እንማረለን፤ ሰብአ ነነዌ ባለማወቅ ሠርተውት ሊመጣባቸው ካለ መአት ለመዳን፣ ወደ እግዚአብሔርም ለመመለስ የተጠቀሙበት የጾም የጸሎት መንገዳቸው ፍጹም ሊያስተምረን ይገባል፡፡ በትንቢተ ኢዩኤል ላይ ፈጣሪያችን  እግዚአብሔር፥ “በፍጹም ልባችሁ፥ በጾምም፥ በልቅሶና በዋይታ ወደ እኔ ተመለሱ።” (ኢዩ.2÷12)ብሎናል፡፡ ስለሆነም በፍጹም ልባችን (ያለ ተከፍሎ ልቡና) ወደ ፈጣሪይችን ተመልሰን ቸርነት ምሕረቱን ደጅ ልንጠና ይገባናል፡፡ የነነዌ ሰዎች ለሦስት ቀንና ለሦስት ሌሊት  በፍጹም ልቡናቸው ተጸጽተው፣ ጹመው ጸልየው  ምሕረትን አግኝተዋል፡፡ እኛ በቁጥር ከዚያ የበለጠውን ጾመን፣ ጸልየን ልመናችን ምላሽ ያላሰጠን ለምንድር ነው? በእርግጥ ጾም ጸሎታችን በፍጹም ልቡና የቀረበ ነው? በትንቢተ ኢሳይያስ እንዲህ የሚል ቃልተጽፎ እናነባለን፡- “ስለ ምን ጾምን አንተም አልተመለከትኸንም? ሰውነታችንንስ ስለ ምን አዋረድን÷ አንተም አላወቅህም? ይላሉ፡፡እነሆ÷ በጾማችሁ ቀን ፈቃዳችሁን ታደርጋላችሁ÷ ሠራተኞቻችሁንም ሁሉ ታስጨንቃላችሁ፡፡ እንሆ÷ለጥልና ለክርክር ትጾማላችሁ በግፍ ጡጫም ትማታላችሁ ድምፃችሁንም ወደ ላይ ታሰሙ ዘንድ ዛሬ እንደምትጾሙት አትጾሙም። እኔ የመረጥሁት ጾም ይህ ነውን?ሰውስ ነፍሱን የሚያዋርደው እንደዚህ ባለ ቀን ነውን? በውኑ ራሱን እንደ እንግጫ ዝቅ ያደርግ ዘንድ ማቅንና አመድንም በበታቹ ያነጥፍ ዘንድ ነውን? በውኑ ይህን ጾም፥ በእግዚአብሔርም ዘንድ የተወደደ ቀን ትለዋለህን?እኔስ የመረጥሁት ጾም ይህ አይደለምን? የበደልን እስራት ትፈቱ ዘንድ፥ የቀንበርንስ ጠፍር ትለቅቁ ዘንድ፥ የተገፉትንስ አርነት ትሰድዱ ዘንድ፥ ቀንበሩንስ ሁሉ ትሰብሩ ዘንድ አይደለምን?እንጀራህንስ ለተራበ ትቈርስ ዘንድ፥ ስደተኞቹን ድሆች ወደ ቤትህ ታገባ ዘንድ፥ የተራቈተውንስ ብታይ ታለብሰው ዘንድ፥ ከሥጋ ዘምድህ እንዳትሸሽግ አይደለምን?የዚያን ጊዜ ብርሃንህ እንደ ንጋት ይበራል፥ ፈውስህም ፈጥኖ ይበቅላል፥ ጽድቅህም በፊትህ ይሄዳል፥ የእግዚአብሔርም ክብር በኋላህ ሆኖ ይጠብቅሃል።”(ኢሳ.58÷3-9)

 

እንግዲህ ከነነዌ ሰዎች ተምረን ጾም ጸሎታቻንን÷ ከቂም፣ ከበቀል፣ ከአመጻና…ይህን ከመሳሰለው የሥጋ ፈቃድ ሁሉ ለይተን በፍጹም ልባችንና በፍጹም ሰውነታችን ወደ እግዚአብሔር በመመለስ÷ ንጹህ መስዋእት አድርገን ልናቀርበው ይገባናል፡፡  ፈጣሪያችን ልኡል እግዚአብሔር ወርሃ ጾሙን የንስሐ የምሕረት ያድርግልን! ለሰብአ ነነዌ የተለመነ ለእኛም ይለመነን! አሜን!!

ማዕከሉ ዐውደ ጥናት ሊያካሂድ ነው

የካቲት 18 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


የጥናትና ምርመር ማዕከል በሁለት ታላላቅ ርእሶች ላይ ያዘጋጀውን ዐውደ ጥናት  የካቲት 23 ቀን 2005 ዓ.ም በብሔራዊ ሙዚየም አዲሱ አዳራሽ ውስጥ እንደሚያካሂድ አስታወቀ፡፡

 

የጥናትና ምርምር ማዕከሉ ምክትል ዳይሬክተር የሆኑት አቶ ሰይፉ አበበ  ለመካነ ድራችን በሰጡት መገለጫ “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን፣ የዓድዋ ድልና አንድምታው፤ እንዲሁም በጦርነቱ የተዘረፉ ቅርሶችን ከማስመለስ አንጻር የቤተ ክርስቲያኒቷ ድርሻ በሚሉ ሁለት ርዕሶች ላይ ትኩረት አድረጎ የሚቀርብ ነው፡፡” ካሉ በኋላ የዐውደ ጥናቱ የትኩረት አቅጣጫዎችን ሲጠቁሙ “ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ኢትዮጵያ በቅኝ ግዛት እንዳትገዛ፣ ነጻነቷ የተጠበቀ ሉአላዊት ሀገር እንድትሆን ከጦርነቱ ጀምሮ እስከ ድሉ የነበራትን ሚና፣ እንዲሁም በዓድዋና በማይጨው በልዩ ልዩ ጊዜያት በወራሪዎች የተዘረፉ ቅርሶችን ከማስመለስ አንጻር የቤተ ክርስቲያኒቱ ድርሻን ማመላከት የጥናቱ ዋነኛ የትኩረት አቅጣጫዎች ናቸው፡፡” ብለዋል፡፡

 

በስተመጨረሻም ምክትል ዳይሬክተሩ ሁሉም ምእመናን ቅዳሜ የካቲት 23 ቀን 2005 ዓ.ም ከቀኑ ስምንት ሰዓት ጀምሮ በሚከናወነው በዚሁ ዐውደ ጥናት ላይ ተሳታፊ ይሆኑ ዘንድ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

KidaneMihret

ኪዳነ ምሕረት

የካቲት 15 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ኀይለ ኢየሱስ ቢያ

KidaneMihret

“ኪዳነ ተካየድኩ ምስለ ኅሩያንየ ከመረጥኋቸው ጋር ቃል ኪዳን አደረግሁ” 88፥3 በማለት በነቢዩ ቅዱስ ዳዊት አድሮ ራሱ እግዚአብሔር ከመረጣቸው አበው ነቢያት ጻድቃን ቅዱሳንና ሰማዕታት ጋር ቃል ኪዳን እንደ ገባና እንደሚገባ ተናግሯል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም እግዝአብሔር እንደሚጠራ እንደሚያከብር እንደሚቀድስ ቃል ኪዳን እንደሚሰጥ ነግሮናል፡፡ /እንግዲህ እርሱ ራሱ ከጸደቀ እግዚአብሔር የመረጣቸውን ሰዎት የሚቃወማቸው ማን ነው? ብሏል፡፡ ሮሜ.8፥33

 

ቅዱስ ዳዊትም “ነኪር ነገሩ በእንቲአኪ ሀገረ እግዚአብሔር የእግዚአብሔር ከተማ ሆይ ስለ አንቺ የተነገረው ነገር ድንቅ ነውብሏል፡፡ መዝ.86፥3 ስለዚህ ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም የገባው ቃል ኪዳን ከቅዱሳን ቃል ኪዳን ሁሉ ልዩ ነው፡፡

 

ቃል ኪዳን መሐላ የሚለው መዝገበ ቃላዊ ፍች እንደሚከተለው ተገልጿል፡-

ኪዳነ ምሕረት የካቲት 16 ቀን እመቤታችን ከልጇ የምሕረት ቃል ኪዳን /ውል / ስምምነት፣ የተቀበለችበት ዕለት የበዓል ስም ነው፡፡ ኪዳን ማለት ኪዳን፡- ውል፣ መሐላ፣ ቃል ኪዳን፣ የውል ቃል ማለት ነው፡፡ ተካየደ፡- ተዋዋለ፣ ቃል ኪዳን ተጋባ፣ ተማማለ ማለት ነው፡፡ ዘዳ.29፥1፣ ኤር.31፥31-33፣ መዝ.88፥3 በሌላ በኩል ኪዳን፡- የጸሎት ስም ነው፡፡ ጌታችን ሞትን ድል አድርጎ ከተነሣ በኋላ ከማረጉ በፊት ለሐዋርያት ያስተማራቸው ጸሎት “ኪዳን” ይባላል፡፡

 

በየዓመቱ የካቲት 16 ቀን የምናከብረው በዓል እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በጎልጎታ በልጇ በመቃብር ላይ ሁና ከወትሮው ለየት ባለ መልኩ “ኦ ወልድየ ወፍቁርየ እስእለከ በእንተ ዘተሰባእከ እምኔየ ወበማሕፀንየ ዘጸረተከ፤ ልጄ ወዳጃ ሆይ ከሥጋዩ ሥጋ ከነፍሴ ነፍስ ነሥተህ ሰው በመሆንህ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በቻለችህ ማኅፀኔ ከአንተ ጋር ሀገር ለሀገር ስለመሰደዴ መጥተህ ልመናዬን ትሰማኝ ዘንድ እለምንሃለሁ” እያለች ስትጸልይ÷ ጌታ እልፍ አእላፍ መላእክቱን አስከትሎ መጥቶ “ሰላም ለኪ ማርያም እምየ፤ እናቴ ማርያም ሰላም ላንቺ ይሁን እንዳደረግልሽ የምትለምኚኝ ምንድን ነው?” አላት፡፡

 

  • ኩሉ ዘጸውአ ስምዬ፤ በስሜ የተማጸነውን

  • ወዘገብረ ተዝካርየ፤ መታሰቢያዬን ያደረገውን

  • ስለስሜ ለችግረኛ የሚራራውን

  • በስሜ ቤተ ክርስቲያን ያነጸውን

  • በስሜ ለቤተ ክርስቲያን ዕጣንና ዘይት መብአ የሰጠውን

  • ከሃይማኖት ፍቅር ጽናት፣ ልጁን በስሜ የጠራውን ሁሉ ማርልኝ ከሞተ ነፍስ አድንልኝ” አለችው፡፡

 

ጌታም “ይህን ሁሉ እንዳደርግልሽ መሐልኩ ለኪ በርእስየ ወበአቡየ ወበመንፈስ ቅዱስ ሕያው” ብሎ ቃል ኪዳን ገብቶላት ዐርጓል፡፡

 

ከዚህ የተነሣ ነው ያዕቆብ ዘሥሩግ በቅዳሴው “ዳግመኛም በእናትህ በማርያም ተማፅነናል÷ ይህችውም አንተን በመውለድ እመቤታችንና የባሕርያችን መመኪያ ናት÷ አንተ መታሰቢያሽን ያደረገ÷ ስምሽንም የጠራ ÷የዘላለም ድኅነትን ይድናል ብለሃታልና፡፡” ያለው (ገጽ 242)

 

በዚህ ዕለት የሚታሰብ በተአምረ ማርያም መጽሐፍ….. የተገለጸ ሁለት ተአምር አለ፡፡

  1. ስምዖን የሚባል እንግዳ ተቀባይ ደግ ሰው ነበር፡፡ ሰይጣን ለምቀኝነት አያፍርምና ከዕለታት አንድ ቀን በእንግድነት እቤቱ ገብቶ “ልጅህን አርደህ ካላበላኸኝ÷ ሌላ ምግብ አልበላም” አለው፡፡ በዚህ ጊዜ ስምዖን ወደ እርሱ የመጣውን “የእግዚአብሔር እንግዳ” ላለማሳዘን አወጣ አወረደ፤ በዚያውም ላይ “አብርሃም ልጁን ሰውቶ ነው፡ የእግዚአብሔር ሰው የተባለው፣” በማለት÷ ልጁን አርዶ ሰጠው፡፡ “በግድ ቅመስልኝ” አለው፡፡ ስምዖን አርዶ የቀቀለውን የልጁን ሥጋ በቀምሰ ጊዜ ተዋሕዶት፤ ቤተሰቦቹን ጎረቤቶቹን መንገደኛውን ሁሉ ይበላ ጀመር፡፡ በዚህም 78 ሰው በልቶ አንድ በቁስል የተመታ ሰው ሊበላው ሲል፡- “በሥላሴ ስም፣ በቅዱስ ሚካኤል ስም፣ በቅዱስ ገብርኤል ስም ውኃ አጠጣኝ” ብሎ ለመነው፤ ዝም አለው፡፡ በመጨረሻም “በድንግል ማርያም ስም” አለው፡፡የእመቤታችንን ስም በሰማ ጊዜ በላኤሰብእ ወደ ልቡናው ተመልሶ “እስኪ ድገመው” አለው፤ “ስለ ድንግል ማርያም ውኃ አጠጣኝ” ብሎ ለመነው፡፡ ያን ጊዜ “ይህችስ እንደምታስምር በልጅነቴ ሰምቻለሁ” ብሎ ጥቂት ውኃ ሰጠው፣ ጉሮሮ እንኳን ሳይርስለት ጨረስህብኝ ብሎ ነጥቆት ሄደ፡፡ “ገበሬው በላኤ ሰብ የምትባል አንተነህ?” አለው፡፡ ያን ጊዜ “ለካስ ሰው ሁሉ አውቆብኛል” ብሎ ዋሻ ገብቶ በመጸጸት በዚያው ሞተ፡፡ ነፍሱን መላእክተ ጽልመት መጥተው ሲወስዷት እመቤታችን “መሐር ሊተ ዛተ ነፍሰ ኦ ወልድየ ዘይትሔሰው ቃልከ፤ ልጄ ይህችን ነፍስ ማርልኝ ቃልህ ይትበላልን” አለችው፡፡ “ሰባ ስምንት ነፍስ ያጠፋ÷ ፈጣሪውን የካደ ይማራልን?” አላት፤ እመቤታችንም “በስሜ የተጠማውን ውኃ አጥጥቶ የለምን?” ብላ አስምራዋለች፡፡ ነፍሱንም መላእክተ ብርሃን መጥተው ወደ ገነት አስገብተዋታል፡፡

  2. ከክርስቲያን ወገን የሆነ ሀብት አግኝቶ ያጣ አንድ ሰው ነበር፡፡ “ከብሬ በኖርሁበት ሀገር÷ተዋርጄ አልኖርም” ብሎ ጓዙን ጠቅልሎ ሲሄድ፣ ሰይጣን ያዘነ መስሎ÷ ደንጊያውን፡- በምትሐት ወርቅ አስመስሎ÷ “አብን ወልድን መንፈስ ቅዱስን፣ ጻድቃን፣ ሰማዕታትን፣ መላእክትን ካድልኝና ይህን እሰጥሃለሁ” አለው፡፡ ካደለትና ተቀብሎ ዞር ሲል፤ “ምእመናን የሚመኩባት ድንግል ማርያም `የአምላክ እናት አይደለችም` ብለህ ካድልኝ” አለው፡፡ “እሷንስ አልክድም” አለው፡፡ በደንጊያ ቀጥቅጦ ገደለው፡፡ መላእክተ ጽልመት ነፍሱን እጅ አደረጉ፤ መላእክተ ብርሃንም አብረው ቀረቡ እመቤታችንም ቀርባ፤ “ልጄ ይህችን ነፍስ ማርልኝ” አለችው፡፡ “ከልብኑ ይታመሐር እምየ፤ እናቴ ውሻ ይማራልን” አላት፡፡ “ስምሽን የጠራውን መታሰቢያሽን ያደረገውን እምርልሻለሁ ያልኸው ቃል ይታበላልን” አለችው “ምሬልሻለሁ” አላት፡፡

 

እግዚአብሔር ከመረጥኳቸው ጋር ቃል ኪዳን አደረግሁ ባለው መሠረት ከቅዱሳን ጋር ያደረጋቸው ቃል ኪዳኖች ብዙዎች ናቸው (መዝ.88፥3)፡፡ ከእነዚህም መካከል አንዱ የእመቤታችን ኪዳን/አማላጅነት/ ነው፡፡

 

አማላጅነትዋ

እንደሚታወቀው ማማለድ ማለት ስለሌላው መጸለይ፣ መለመን፣ የደረሰውን ችግር እንዲወገድ ማስደረግ፣ ማስማር ማለት ነው፡፡ በዚሁ መሠረት ከእግዚአብሔር በታች ከቅዱሳን ሁሉ በላይ ከፍ ከፍ ያለችና የከበረች ቅድስት ድንግል ማርያም ከእግዚአብሔር በተሰጣት የማማለድ ሥልጣን “ሰአሊ ለነ ቅድስት፤ ቅድስት ሆይ ለምኚልን” እያሉ ለሚለምኑአት ሁሉ ከእግዚአብሔር እያማለደችና እየለመነች ምሕረትን እንደምታሰጥ ቀናውንና የተመሰገነውን ሃይማኖት የሚከተሉ ሁሉ ያምናሉ፡፡ ምክንያቱም ቅድስት ድንግል ማርያም የእግዚአብሔር እናትና አገልጋይ በመሆንዋ ከሁሉም ቅዱሳን በበለጠ ለእግዚአብሔር ቅርብ ናትና፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድም ሆነ በሰው ዘንድ ባለሟልነት ወይም ቅርብ መሆን ጉዳይን ያስፈጽማል፡፡

 

ለምሳሌ

  • መልአኩ ቅዱስ ገብርአል በእግዚአብሔር ፊት የሚቆም ባለሟል በመሆኑ የድኅነትን ምሥጢር አብሣሪ ሆኗል፡፡ ሉቃ.1፥19፣ 1፥26

  • አስቴር የንጉሡ አርጤክስስ ሚስት በመሆኗ በወገኖቿ አይሁድ የታወጀውን የሞት አዋጅ አስለውጣለች፡፡ መጽሐፈ አስቴር.3፥10

  • ነቢዩ ሙሴ በእግዚአብሔር ፊት ባለሟል በመሆኑ ለእስራኤላውያን ምሕረት አሰጠ፡፡ ዘጸ.32፥14 “ይህንን ኀጢአታቸውን ይቅር በላቸው ያለዚያ ግን እኔን ከጻፈከው መጽሐፍህ እባክህ ደምስሰኝ አለው እግዚአብሔርም ራራላቸው፡፡”

  • የቅድስት ድንግል ማርያምም አማላጅነት እንደ ፀሐይ የበራ ሐቅ ነው፡፡ ይህንን እውነት ቅዱስ ያሬድ ሲመሰክር “ወታስተሠርዪ ኀጢአተ ሕዝብኪ ተበውሀ ለኪ እም አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ወከመ ትኩኒ ተንከተመ ለውሉደ ሰብእ ለሕይወት ዘለዓለም” ማለት “ለሕዝብሽ ለወገኖችሽ የኃጢአት ይቅርታን ታሰጪ ዘንድ ዘለዓለማዊ ሕይወትንም ለሚወርሱ ሁሉ መሸጋገሪያ ድልድይ ትሆኚ ዘንድ ከአብ ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ÷ከአንድ አምላክ ሥልጣን አግኝተሻል በማለት አመስግኗታል፡፡” /አንቀጸ ብርሃን ተመልከት/

 

በአባ ጽጌ ድንግልም በማኅሌተ ጽጌው “ሶበሰ ኪዳንኪ ምክንያተ ድኂን ኢሀሎ ፈለገ እሳት ወደይን እም አሰጠመ ኩሎ፤የድኅነት ምክንያት ቃል ኪዳንሽ ባይኖር ኖሮ የጥፋት እሳት ፤መርገም /ኀጢአት/ ባጠፋን ነበር” ብሏል፡፡

 

በሥርዓተ ቅደሴአችንም

  • ድኅነትን የምንለምንሽ ክብርን የተመላሽ ቅድስት ሆይ ደስ ይበልሽ

  • ሁል ጊዜ ድንግል የምትሆኚ አምላክን የወለድነሽ የክርስቶስ እናት ሆይ ኀጢአታችንን ያስተሠርይልን ዘንድ ወደ ልጅሽ ወደ ወዳጅሽ ወደ ላይ ጸሎታችንን አሰርጊ፣

  • በእውነት የጽድቅ ብርሃን የሚሆን አምላካችንን ክርስቶስን የወለድሽልን ንጽሕት ሆይ ደስ ይበልሽ፣

  • ንጽሕት ድንግል ሆይ ለነፍሳችን ይቅርታን ያደርግ ዘንድ ኀጢአታችንንም ያስተሠርይልን ዘንድ ወደ ጌታችን ለምኚልን፡፡

  • በእውነት ለሰው ወገን አማላጅ የምትሆኝ አምላክን የወለድሽ ንጽሕት ቅድስት ድንግል ማርያም ሆይ ደስ ይበልሽ፡፡

  • የኀጢአታችንን ሥርየት ይሰጠን በልጅሽ በክርስቶስ ፊት ለምኝልን፣

  • በእውነት ንግሥት የምትሆኝ ንጽሕት ድንግል ሆይ ደስ ይበልሽ

  • የባሕርያችን መመኪያ ሆይ ደስ ይበልሽ

  • አምላካችን አማኑኤልን የወለድሽልን ሆይ ደስ ይበልሽ

  • በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ፊት እውነተኛ አስታራቂ ሆነሽ ታስቢን ዘንድ እንለምንሻለን፡፡

  • ለነፍሳችን ይቅርታን ያደርግልን ዘንድ ኀጢአታችንንም ያስተሰርይልን ዘንድ” በማለት እንማጸናታለን፡፡

አባ ሕርያቆስም በቅዳሴው

  • ጥፋትን ያይደለ ይቅርታን አሳስቢ

  • ማዓትን ያይደለ ምሕረትን አሳስቢ

  • ለጻድቃን ያይደለ ለኀጥአን አሳስቢ

  • ለንጹሐን ያይደለ ለተዳደፉት አሶስቢ ብሏል፡፡ ቁ.165-171

 

የእመቤታችን ክብር ከቅዱሳን ክብር ሁሉ የተለየ ነው፤ ይህም እንደምን ነው ቢሉ

  • ለአምላክ እናትነት የተመረጠች ልዩ እናት በመሆኗ ሉቃ.1፥26

  • አምላክ ከሥጋዬ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ ከእርሷ በመወለድ

  • ከመለለዷ በፊት በወለደች ጊዜ ከወለደች በኋላ ምን ጊዜም ድንግል በመሆኗ ኢሳ.7፥14

  • በሁለቱም ወገን /በአሳብም በገቢርም/ ድንግል በክልኤ በመሆኗ

  • አማላጅነቷ የወዳጅነት ሳይነሆን የእናትነት በመሆኑ ዮሐ.2፥5

  • ዓለም ይድን ዘንድ የድኅነት ምክንያት አድርጎ አምላክ የመረጣት ስለሆነ የእመቤታችን ክብር /ቃል ኪዳን/ ከቅዱሳን ክብር ፈጽሞ የተለየ ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊትም በመዝሙሩ

“እግዚአብሔር ጽዮንን መርጧታልና ማደሪያውም ትሆነው ዘንድ ወዷታልና ይህች ለዘለዓለም ማረሪያዬ ናት መርጫታለሁና በዚህች አድራለሁ፡፡” በማለት ነግሮናል፡፡ እግዚአብሔር የመረጠውንና የከበረውን መቃወም እንደሣይቻ ሐዋርያውቅ ቅዱስ ጳውሎስም “እንግዲህ እርሱ ራሱ ከጸደቀ እግዚአብሔር የመረጣቸውን ሰዎች የሚቃወመቸው ማን ነው” ብሏል፡፡ ስለዚህ ብዙ ከንቱ አሳቦችን ትተን እንደበላኤሰብ በቃል ኪዳኗ ተጠቅመን ንስሐ ገብተን ቅዲስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ተቀበልን የስሙ ቀዳሽ የመንግሥቱ ወራሽ ለመሆን ያብቃን፡፡

የእግዚአብሔር ቸርነት የእመቤታችን አማላጅነት የቅዱሳን ተራደኢነት አይለየን፡፡

ዋቢ መጻሕፍት

  • ተአምረ ማርያም

  • ስንክሳር

  • መዝገበ ታሪክ

  • ክብረ ቅዱሳን

  • አማርኛ መዝገበ ቃላት