maderaja memreya letter

በሕገወጦች በጨለማ የተዘጋጀው ደብዳቤ ተበተነ፡፡

ግንቦት 7/2004 ዓ.ም.

ከጥቂት ቀናት በፊት ማኅበረ ቅዱሳን ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ማእከላዊ አስተዳደር ተገዥ ካለመሆን አልፎ የተቋሙን ሕልውና ወደ መፈታተን እንደ ደረሰ በማተት የሚከስ ደብዳቤ ለሕግ ተገዢ ባልሆኑ ግለሰቦች በጨለማ ተረቅቆ በመምሪያው ሓላፊ እንዲፈረም ተደርጎ ሊወጣ እንደ ነበር፤ ነገር ግን በመምሪያው ሓላፊው በቆሞስ መልአከ ጽዮን አባ ኅሩይ መታገዱን ገልጸን ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ እስከ አሁን ምክንያቱ ግልጽ ባልሆነ ሁኔታ “ፍጹም ሕገ ወጥ ድርጊት በሕጋዊዋና በእውነተኛዋ ቤተ ክርስቲያን መፈጸም የለበትም፤ ይቁም” ያሉትን የመመሪያ ሓላፊ አስተዳደሩ ከቦታቸው አንሥቷል፡፡ በምትካቸውም ከግብረ አበሮቻቸው ጋር በመሆን ደብዳቤውን በወቅቱ በተገለጠው ሁኔታ በማርቀቅ፣ እንዲፈረምና እንዲሠራጭ የሞት ሽረት ትግል ሲያደርጉ ከነበሩት ግለሰቦች አንዱ የሆኑትን መምህር ዕንቊ ባሕርይ ተከሥተን ሾሟል፡፡

ቆሞስ አባ ኅሩይ በመምሪያ ሓላፊነት ተመድበው ቦታውን ከያዙበት ጊዜ ጀምሮ በማኅበሩ መስተካከል አለባቸው በሚሏቸው ጉዳዮች ላይ ሁሉ የማኅበሩን አመራር አካላት እየሰበሰቡ መመሪያ ሲሰጡ፣ ማኅበሩም መመሪያዎችን እየተቀበለ ወደ ተግባር ሲለውጥ ቆይቷል፡፡ ቆሞስ አባ ኅሩይ ደብዳቤ በማርቀቅ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ልዩ ልዩ ክፍሎች አልፎ እስከ ብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን በሚደርስ ሁኔታ በማብረር የማያምኑ ውይይት ተኮር ዘመናዊ የአመራር ዘዴን የሚከተሉ በመሆናቸው ማኅበሩ መመሪያቸውን ሁሉ እየተቀበለ በማገልገል ላይ ነበር፡፡ ማኅበሩ የሚፈልገው በመጠነ ሰፊ ችግሮች ውስጥ ባለች ቤተ ክርስቲያን ሠርቶ የሚያሠራው ነውና፡፡

የመምሪያ ሓላፊው ቆሞስ አባ ኅሩይ ባላጠፉት ጥፋት ተከሰው ከቦታው መነሣታቸውን በመቃወም ለችግሩ መፍትሔ እንዲሰጥ ማኅበሩ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ደብዳቤ ጽፏል፡፡ ጉዳዩም በቅዱስ ሲኖዶስ በአጀንዳነት ተይዟል፡፡

maderaja memreya letter

ማኅበሩ ለጻፈው ደብዳቤ ምላሽ በሚጠብቅበት በአሁኑ ወቅት፤ በመምሪያ ሓላፊነት የተመደቡት መምህር ዕንቊ ባሕርይ ተከሥተ ለረጅም ዓመታት የታገሉለትን ማኅበሩን የማደናቀፍ እኲይ ተግባር የሚያረጋግጡላቸውን ደብዳቤዎች ማብረር ጀምረዋል፡፡ በትላንትናው ዕለት ካበረሯቸው ደብዳቤዎች አንዱ ለቆሞስ አባ ኅሩይ መነሣት ምክንያት የሆነውንና ራሳቸው መምህር ዕንቊ ባሕርይ ከመሰል ግብረ አበሮቻቸው ጋር ሆነው አርቅቀው እንዲፈረምና እንዲበር የተሯሯጡለት ደብዳቤ ነው፡፡

 

የማኅበሩ አመራር በደብዳቤው ይዘትና በመምሪያችን እየተፈጠረ ስላለው የተጠናና ቤተ ክርስቲያኗን የማዳከም እንቅስቃሴ ላይ ውይይት በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ ጉዳዩን አስመልክቶ ለቅዱስ ሲኖዶስ ያቀረበውን አቤቱታ መልስ ይጠብቃል፡፡ በሒደቱ የሚፈጠሩትን ማናቸውንም ክስተቶች እየተከታተለ ለምእመናን ይፋ ያደርጋል፡፡

mk letter to synodos

የማኅበሩ አባላትም ሆኑ ምእመናን ዛሬ በማኅበራችን ላይ እየደረሰ ያለው ችግር በእናት ቤተ ክርስቲያን ላይ እየደረሰ ካለው ጋር ሲነጻጸር እዚህ ግባ የማይባል በመሆኑ አገልግሎታችንን በተለመደው ሁኔታ አጠናክረን እንድንቀጥል እናሳስባለን፡፡