በዋልድባ ገዳምና በወልቃይት ስኳር ልማት ፕሮጀክት መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት አስመልክቶ ማኅበረ ቅዱሳን ያደረገው ጥናት ዘገባ

 

ግንቦት 10/2004 ዓ.ም.

ካለፉት ሁለትና ሦስት ወራት ወዲህ ከዋልድባ ገዳም ጋር በተያያዘ በመንግሥትና በገዳሙ መካከል አለመግባባት ተከስቷል፡፡ አለመግባባቱም ብዙዎችን አነጋግሯል፣ አከራክሯል፡፡ ከጉዳዩ መግዘፍ የተነሣ በርካቶችን ሲያስጨንቅና ሲያሳስብ ቆይቷል፡፡ የበርካታ ኢትዮጵውያንን ትኩረት የሳበ ሀገራዊ ጉዳይም ሆኗል፡፡ አለመግባባቱን ለማወቅ ከመጓጓት አንጻርም፤ የጉዳዩን ምንጭና መፍትሔ ነጣጥሎ ማየት እስከ ሚከብድ ድረስ በሰው ልቡና ሲመላለስ ቆይቷል፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳንም እውነታውን ለማጣራት ከመጋቢት 25-30 ቀን 2004ዓ.ም አምስት አባላት ያሉት የልዑካን ቡድን ወደቦታው ልኮ ነበር፡፡ ቡድኑ በቦታው በመገኘት ሁሉንም አካላት ማለትም የገዳሙን አባቶች (የገዳሙ አባቶች ስማቸው እንዲጠቀስ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው፤ በጽሑፉ ውስጥ የገዳሙ መነኮሳት በሚል የወል ስም ተገልጸዋል)፣ የፕሮጀክቱን ሓላፊዎች፣ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች በማነጋገር ያገኘውን ምላሽ ከልዑካኑ ዕይታ ጋር በመጨመር ሰፋ ያለ ሪፖርት ይዞ ተመልሷል፡፡ የዚህ ጽሑፍ ዓላማ የልዑኩን ሪፖርት የማኅበሩ አመራር አካል ከሰማ በኋላ፤ ከልዩ ልዩ አቅጣጫዎችና ተጨማሪ መረጃዎች ጋር በመመርመር ያጸደቀውን ሪፖርት ማቅረብ ነው፡፡