የሆሣዕና ምንባብ16(ሐዋ.28÷11-ፍጻ.)

 ከሦስት ወር በኋላም በዚያች ደሴት ወደ ከረመችው ወደ እስክንድርያ መርከብ ወጣን፤ በዚያች መርብ ላይም የዲዮስቆሮስ ምልክት ነበረባት፤ ይኸውም “የመርከበኞች አምላክ” የሚሉት ነው፡፡ ከዚያም ሄደን ወደ ሰራኩስ ደረስን፤ በዚያም ሦስት ቀን ተቀመጥን፡፡ ከዚያም ሄደን ሬቅዩን ወደምትባል ሀገር ደረስን፤ በማግሥቱም ወጣን፤ ከአንድ ቀንም በኋላ ከጐንዋ ነፋስ በነፈሰ ጊዜ በሁለተኛው ቀን ወደ ፑቲዮሉስ ደረስን፡፡ በዚያምም ወንድሞችን አግኝተን ተቀበሉን፤ በእነርሱ ዘንድም ሰባት ቀን እንድንቀመጥ ለመኑን፤ ከዚያም በኋላ ሄደን ወደ ሮሜ ደረስን፡፡ በዚያም ያሉት ወንድሞች ስለ እኛ በስሙ ጊዜ፤ አፍዩስ ፋሩስ እስከሚባለው ገበያና እስከ ሦስተኛው ማረፊያ ድረስ ወጥተው ተቀበሉን፤ ጳውሎስም ባያቸው ጊዜ እግዚአብሔርን አመሰገነ፤ ልቡም ተጽናና፡፡  ወደ ሮሜም በገባን ጊዜ የመቶ አለቃው እስረኞችን ለሠራዊቱ አለቃ አስረከበ፤ ጳውሎስ ግን ከሚጠብቀው አንድ ወታደር ጋር ለብቻው ይቀመጥ ዘንድ ፈቀደለት፡፡

ከሦስት ቀንም በኋላ ጳውሎስ የአይሁድን ታላላቅ ሰዎች ሰበሰባቸው፤ በተሰበሰቡም ጊዜ እንዲህ አላቸው÷ “ወንድሞቻችን ሆይ÷ እኔ በሕዝቡም ላይ ቢሆን÷ በአባቶቻችንም ሕግ ላይ ቢሆን ያደረግሁት ክፉ ነገር የለም፤ ነገር ግን በኢየሩሳሌም እንደ ታሰርሁ ለሮም ሰዎች አሳልፈው ሰጡኝ፡፡ እነርሱም መርምረው ለሞት የሚያበቃ በደል ስለአላገኙብኝ በተነሡ ጊዜ ወደ ቈሣር ይግባኝ ለማለት ግድ ሆነብኝ፤ ነገር ግን ወገኖቼን የምከስበት ነገር ኖሮኝ አይደለም፡፡ ስለዚህም ላያችሁ÷ ልነግራችሁና ላስረዳሁ ወደ እኔ እንድትመጡ ማለድኋችሁ፤ ስለ እሰራኤል ተስፋ በዚህ ሰንሰለት ታስሬአለሁና፡፡” የአይሁድ ታላላቅ ሰዎችም እንዲህ አሉት÷ “ለእኛስ ከይሁዳ ሀገር ስለ አንተ መልእክት አልደረሰንም፤ ከኢየሩሳሌም ከመጡት ወንድሞችም ቢሆን አንድ ስንኳ ከዚህ አስቀድሞ ስለ አንተ ክፉ ነገር ያወራን÷ የነገረንም የለም፡፡ ነገር ግን በዚህ ነገር በየስፍራው ሁሉ እንዲጣሉ በእኛ ዘንድ ታውቋልና የአንተን ዐሳብ ደግሞ ከአንተ እንሰማ ዘንድ እንወድዳለን፡፡” ከዚህም በኋላ ወደ እርሱ የሚመጣበትን ቀን ቀጠሩትና ብዙዎች ወዳረፈበት ወደ እርሱ መጡ፤ ከጥዋትም ጀምሮ እስከ ማታ ድረስ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት እየመሰከረ ስለ ጌታችን ስለ ኢየሱስም ከሙሴ ኦሪትና ከነቢያት እየጠቀሰ ነገራቸው፡፡ ከእነርሱም እኩሌቶቹ የተናገረውን አመኑ፤ እኩሌቶቹ ግን አልተቀበሉትም፡፡ እርስ በርሳቸውም ባልተስማሙ ጊዜ ጳውሎስ አንዲት ቃል ከተናገረ በኋላ ከእርሱ ተመለሱ፤ እንዲህም አላቸው÷ “መንፈስ ቅዱስ በነቢዩ በኢሳይያስ አንደበት ለአባቶቻችን በእውነት እንዲህ ብሎ መልካም ነገር ተናግሮአ፡፡ ‹ወደዚህ ሕዝብ ሂድና እንዲህ በላቸው፡- መስማትን ትሰማላችሁ፤ ግን አታስተውሉም፤ ማየትንም ታያላችሁ፤ ግን አትመለከቱም፡፡ በዐይናቸው እንዳያዩ÷ በጆሮአቸውም እንዳይሰሙ÷ በልባቸውም እንዳያስተውሉ÷ ወደ እኔም እንዳይመለሱና ይቅር እንዳልላቸው የዚህ ሕዝብ ልባቸው ደንድኖአልና÷ ጆሮአቸውም ደንቁሮአልና÷ ዐይናቸውንም ጨፍነዋልና›፡፡ እንግዲህ ከእግዚአብሔር የተገኘች ይህቺ ድኅነት ለአሕዛብ እንደምትሆን ዕወቁ፤ እነርሱም ይሰሙታል፡፡” ይህንም በተናገራቸው ጊዜ አይሁድ እርስ በርሳቸው እጅግ እየተከራከሩ ወጥተው ሄዱ፡፡ ጳውሎስም በገንዘቡ በተከራየው ቤት ሁለት ዓመት ተቀመጠ፤ ወደ እርሱ የሚመጣውንም ሁሉ ይቀበል ነበር፡፡ ማንም ሳይከለክለው የእግዚአብሔርን መንግሥት ይሰብክ ነበር፤ ስለ ጌታችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ እጅግ ገልጦ ያስተምር ነበር፡፡ ጳውሎስም በመጀመሪያ ጊዜ ወደ ኔሮን ቄሣር ገብቶ ነበርና ረትቶ በሰላም ሄደ፤ ከዚህም በኋላ ሁለት ዓመት ኖሮ ከሮም ወጣ፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ ሮም ተመልሶ የኔሮን ቄሣር ዘመዶችን አጠመቀ፤ በኔሮን ትእዛዝም በሰይፍ ተመትቶ መከራውንም ታግሦ ሰማዕት ሆነ፡፡