የሆሣዕና ምንባብ15(1ኛጴጥ.4÷1-12)

 ክርስቶስ ስለ እኛ በሥጋው ከተሰለቀ÷ እናንተም ይህቺን ዐሳብ ጋሻ አድርጋችሁ ኑሩ፤ በሥጋዉ መከራ የተቀበለ ከኀጢአት ድኖአልና፡፡ ከእንግዲህ ወዲህ በሥጋው ከሕይወቱ ዘመን የቀረውን÷ በሰው ፈቃድ ሳይሆን በእግዚአብሔር ፈቃድ እንዲፈጽም ነው እንጂ፡፡ የአሕዛብን ፈቃድ፡- ዝሙትንና ምኞትን÷ ስካርንና ወድቆ ማደርን÷ ያለ ልክ መጠጣትንና ጣዖት ማምለክን ያደረጋችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃችኋልና፡፡ እንግዲህ ወደዚህ ሥራ እንዳትሮጡ ዕወቁ፤ ከዚች ጎዳናና መጠን ከሌለው ከዚያ ሥራም ተለዩ፤ እነሆ÷ ከእነርሱም መካከል ሰዎች ስለ እናንተ ያደንቃሉ፤ በዚያም በቀድሞው ሥራ ሳትተባበሩአቸው ሲያዩአችሁ ይሰድቡአችኋል፡፡ እነርሱም በሕያዋንና በሙታን ይፈርድ ዘንድ ተዘጋጅቶ ላለው መልስ ይሰጣሉ፡፡ ስለዚህም በሥጋቸው በሰው ሕግ አንዲቀጡ÷ በነፍሳቸውም በእግዚአብሔር ሕግ እንዲድኑ ለሙታን ወንጌልን ሰበኩላቸው፡፡

የሁሉ ፍጻሜው ቀርቦአልና ልባችሁን አንጹ፤ ለጸሎትም ትጉ፡፡ ከሁሉ አስቀድሞ በፍጹም ልቡናችሁ እርስ በርሳችሁ ተዋደዱ፤ ፍቅር ኀጢአትን ሁሉ ይሸፍናልና፡፡ ሳታንጐራጒሩ እርስ በርሳችሁ እንግዳ መቀበልን ውደዱ፡፡ ሁላችሁም በየራሳችሁ ከእግዚአበሔር የተሰጣችሁን ዕድል እንደ ተቀበላችሁ መጠን እንደ ደግ መጋቢ አገልግሉ፤ ለአያንዳንዱ ከእግዚአብሔር ስጦታው እየራሱ ነውና፡፡ የሚያስተምርም÷ እንደ እግዚአብሔር ቃል ያስተምር÷ የሚያገለግልም እግዚአብሔር በሚሰጠው ኀይል ያገልግል፤ ክብርና ኀይል እስከ ዘለዓለም ድረስ ገንዘቡ በሚሆን በኢየሱስ ክርስቶስ እግዚአብሔር በሁሉ ነገር ይመሰገን ዘንድ፡፡

ወዳጆች ሆይ÷ በእናንተ መካከል እንደ እሳት ሊፈትናችሁ ስለሚሆነው መከራ÷ ድንቅ ነገር እንደመጣባችሁ አትደነቁ፡፡