የእግዚአብሔርን እንግዳ ሲጠብቅ እግዚአብሔር እንግዳ ሆነለት!

መምህር ሃይማኖት አስከብር

ሐምሌ ፮ ቀን ፳፻፲፬ ዓ.ም

ወድ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች እንደምን አላችሁ? እንኳን ለቅድስት ሥላሴ ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ!  እንደሚታወቀው ሐምሌ ፯ የቅድስት ሥላሴ ዓመታዊ በዓል ነው፤  የበዓሉን ታሪክ በአጭሩ አቅርበንላችኋል፡፡

ከላይ በርእሱ እንደገለጸው የእግዚአብሔርን እንግዳን ሲጠብቅ እግዚአብሔር እንግዳ የሆነለት ታላቁ አባትን አብርሃምን እናነሣለን፡፡ በዚህ ዕለትም ታላቁ አባት አብርሃም ሥላሴን በቤቱ ያስተናገደበት ዕለት ነው፡፡ ውድ አንባብያን! እግዚአብሔርን በቤታችን እንዴት ማስተናገድ ይቻላል?እንዴትስ ወደ ቤታችን መቀበል እንችላለን? እግዚአብሔርን በቤታችን ማስተናገድ ከአባታችን አብርሃም እንማራለን፡፡

በቅዱሳን መጽሐፍት እንደተጻፈው አብርሃም በተመሳቀለ ጎዳና ድንኳኑን ተክሎ በአራቱም አቅጣጫ የሚመጣውን እንግዳ ይቀበል ነበር፡፡ የደከመውን እግሩን አጥቦ፣ የተራበውን አብልቶና አጠጥቶ የሚልክ እንግዳ የሚወድ ታላቅ አባት ነው፡፡ ሥራው መልካም ሥራ በመሆኑና ሰይጣን በአብርሃም ላይ ቀናበት፤ መልካም ሲሠራ ሰይጣን ደስ ስለማይሰኝ የሚደንቀውም በመልካም ሥራ ሰይጣን የሚደሰት ቢሆን ነበር፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን የደከማቸው ሰዎች ወደ እንግዳ ተቀባዩ አብርሃም ቤት ሲገሰግሱ ሰይጣን ጎዳና ላይ ተቀምጦ እንግዶችን ‹‹ወዴት ትሄዳላችሁ እያለ ይጠይቅ›› ጀመር፡፡ እነርሱም ‹‹ስንደክም የምናርፍበት፣ ሲርበን፣ ሲጠማን የምንበላበትና የምንጠጣበት ወደ ደጉ እንግዳ ተቀባዩ ወደ አብርሃም ቤት እንሄዳለን እንጂ›› አሉት፤ ሰይጣንም ‹‹የድሮው አብርሃም መሰላችሁ! እኔም እንደ እናንተ ደክሞኝና እርቦኝ  ተቀብሎ ያስተናግደኛል ብዬ ብሄድ በድንጋይ እራሴን ፈንክቶ፣ ደሜን፣ አፍስሶ፣ ልብሴን ቀምቶና ገፎ ላከኝ እንጂ፡፡›› እንዲህ እያለ ለሦስት ቀን እንግዳ እንዳይሄድ ከለከለበት፤ አብርሃምም ‹‹ማዕደ እግዚአብሔርን ያለ እንግዳ ምስክርነት አልቆርስም›› ብሎ ለሦስት ቀን ይጠብቅ ነበር፡፡ ታዲያ የአብርሃምን ደግነት የተመለከተ እግዚአብሔር ሰይጣን ሊያስቀረው የማይችል እንግዳ ራሱ እግዚአብሔር እንግዳ ሆኖ በአብርሃም ቤት ተገኘ፤ አብርሃምም የእግዚአብሔርን እንግዳ ሲጠብቅ እግዚአብሔር እንግዳ ሆነለት፡፡ (ቅዳሴ ማርያም ትርጓሜ አንድምታ 4$#2) እግዚአብሔርም በአብርሃም ቤት በአንድነት በሦስትነት ተገለጠለት፡፡

በኦሪት ዘፍጥረት ላይ ተጽፎ እንደምናገኘው እግዚአብሔር ለአብርሃም በአንድነቱና በሦስትነቱ እንደተገለጠለትና በቤቱ እንደተስተናገደ ሲገልጽ ቅዱሱ መጽሐፍ እንዲህ ይለናል፡፡ ‹‹በቀትር ጊዜ አብርሃም በድንኳኑ ተቀምጦ ሳለ እግዚአብሔር በመምሬ ዛፍ ሥር ተገለጠለት፤ ዐይኑንም ባነሳ ጊዜ ሦስቱ ሰዎች በፊቱ ቁመው አየ፤ ሊቀበላቸውም ከድንኳኑ ደጃፍ ተነሥቶ ወደ እነርሱ ሮጠ፤ ወደ እነርሱም ሰገደ፤ አቤቱ በፊትህ ሞገስን አግኝቼ ከሆነ ባርያህን አትለፈው፡፡››  (ዘፍ. 08$1)

ሦስት ቀን ያለ እንግዳ እና ያለ ምግብ የቆየ ሰው በዚያ ላይ እግዚአብሔርን ሲያይ ከደስታው ብዛት የተነሣ ‹‹አብርሃም ወደ ሥላሴ ሮጦ ሰገደ፡፡›› አብርሃም እየጠበቀ የነበረው ሰውን ነበርና፡፡ ሰውን ሰይጣን ቢያስቀርበት ሰውን የፈጠረ እግዚአብሔር በአብርሃም ቤት ተገኘ፤ መባረክ እንዲህ ነው! በትንሹ ሲጠበቅ በብዙ መባረክ እንደዚህም ነው፤ በቅዱስ መጽሐፍ እንግዳ መቀበልን ማዘውተርና ብዙዎች እንግዳዎችን በመቀበል ፈንታ መላእክትን እንደተቀበሉ ተጽፏል፡፡ ሎጥም መላእክትን የተቀበላቸው በእንግዳ አምሳል ነበር፡፡ (ዘፍ.09$3)

ብዙ አባቶች በእንግዳ አምሳል ጻድቃንን፣ መላእክትን እግዚአብሔርን በቤታቸው ያስተናገዱት ለዚህም ነው፤ እንግዳ መቀበል እግዚአብሔርን መቀበል ነውና፡፡ አብርሃምም ‹‹ጥቂት ውኃ ይምጣላችሁ፤ እግራችሁን ታጠቡ፤ ከዚህ ዛፍ በታች እረፉ፤ ቁራሽ እንጀራም ላምጣላችሁ፤ ልባችሁን ደግፉ፤ ወደ ባሪያችሁ መጥታችኋል›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹እንደወደድክ አድርግ›› አሉት። በዚያን ጊዜ ጽንዓ ፍቅሩን ለማጠየቅ ‹‹አዝለህ አስገባን›› አሉት፡፡ እርሱም ከሦስቱ አካል አንዱ ሲያስገባ ሁለቱም ቤት አገኛቸው፤ ይህም አንድነቱን ሦስትነቱን ይገልጻል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ጎርጎርዮስም ‹‹አንሰ እቤ እግዚአብሔር በእንተ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ፤ እኔ እግዚአብሔር ስል ስለ አብ ስለ ወልድ ስለ መንፈስ ቅዱስ ነው›› በማለት ተናግሯል፡፡ ‹‹እግዚአብሔርም ተገለጠለት›› ካለ በኋላ ‹‹ሦስት ሰዎች አየ›› ማለቱ ነው ነው፡፡  እግዚአብሔር የባሕርይ አንድነቱ የሦስቱም ስም ነው፡፡ አንድነቱ በባሕርይ በሥልጣን፣ በአገዛዝ፣ በመለኮቱና በመንግሥቱ ነው፡፡

በሦስትነቱ በአካል በስም በግብር ነው፡፡ ለዚህም ለአብርሃም በአንድነቱም በሦስትነቱም እግዚአብሔር ተገለጠለት፡፡ አብርሃም ወደ ሣራ ዘንድ በመሄድ ‹‹ሦስት መስፈሪያ ዱቄት ለውሰሽ አንድ እንጎቻ አድርገሽ አዘጋጂ›› አላት፡፡ ሦሰት ማለቱ የሦስትነቱ፣ አንድ አድርጊው ማለቱ የአንድነቱ ምሳሌ ነው፡፡ ወደ ላሞቹ ሄዶ ከላሞቹ መካከል ያማረውን የተዋበውን ንጹሑን ወይፈን አቀረበ፤ እግዚአብሔር ንጹሐ ባሕርይ ነውና ንጹሐ ነገር ይወዳል፡፡ አብርሃም ያዘጋጀውን ተመገቡ፤  ሥላሴ ምግብ የሚበሉ ሆነው አይደለም፤ ተመገቡ ብሎ መናገሩ በሰው አምሳል ስለተገለጡለት ለአብርሃምም የበሉ መስሎት ስለታዩት እንጂ ለሥላሴስ መብልና መጠጥ አይስማማቸውም፡፡ ‹‹ሥላሴ ምግብ በሉ›› ማለት ‹‹እሳት ቅቤን በላው›› እንደማለት ነው፡፡ ቅቤውም ከእሳት ገብቶ አልቀለጠም ማለት ነው፤ መብልና መጠጥ የሥጋ ፈቃድ ነው፡፡ ይህም ይታወቅ ዘንድ የታረደው ወይፈንም ተነሥቶ ‹‹ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ›› ብሎ አመስግኗል፡፡ አንዳንዶች ይህንን ሲሰሙ ላያምኑ ሞኝነት ይችላሉ፤ በመጽሐፍ ቅዱስ ግን እግዚአብሔር የበለዓምን አህያ እና የቢታንያም ድንጋዮችን አናግሯል፤ ስለዚህ በሰው ዘንድ ነው እንጂ በእግዚአብሔር ዘንድ ይቻላል የማይቻል የለም፡፡

እግዚአብሔርም አብርሃምን ጠርቶ ‹‹ሚስትህ ሣራ ወዴት ናት›› አለው፡፡ እግዚአብሔር ስለ ሣራ አብርሃምን መጠየቁ ያለችበት ጠፍቶት አልነበረም፤ ልጅ እንደምትወልድ ሊነግረው ነው እንጂ፤ አብርሃምም ‹‹በድንኳን ውስጥ አለች›› አለ፡፡ ‹‹ወይቤሎ ሶበ ገባእኩ እመጽዕ ኀቤከ አመ ከመ ዮም ትረክብ ሣራ ወልደ፤ የዛሬ ዓመት እንደ ዛሬው ጊዜ ወደ አንተ እመለሳለሁ፤ ሚስትህ ሣራ ልጅ ትወልዳለች›› ብሎ ለአብርሃም ነገረው፡፡ (ዘፍ 08$0) ሣራም በአብርሃም በኋላ ቁማ ነበርና ሰማች፤ አብርሃምና ሣራ ፺፱ ሣራ ፹፱ ዓመታቸው ስለነበር አርጅተዋልና መውለድ አይችሉም፡፡ ሣራ ብቻዋን ሳቀች፤ ይህም ሣራ አርጅቻለሁ የሴቶች ልማድም አቁማለች እንዴት ሰው ካረጀ በኋላ ልጅ ይወልዳል፡፡ ‹‹ሲያረጁ በአምባር ይዋጁ›› እንዲሉ እስከ ‹‹ዛሬ ድረስ ገና ቆንጆ ነኝ›› ብላ ተጠራጠረች፤ ‹‹ትወልጃለሽ›› መባሏ አሳቃት፤ ‹‹ወይቤሎ እግዚአብሔር ለአብርሃም ምንት አስሐቃ ለሣራ እግዚአብሔር፤ አብርሃምን ሣራን ምን አሳቃት›› አለው፤ ሣራም ‹‹አልሳቅሁም›› አለች፤ እግዚአብሔር መሳቋን እንዳወቀም ከነገራት በኋላ ‹‹በድጋሚ በዓመት እንደ ዛሬው እመጣለሁ›› አለው፤ ወንድ ልጅም እንደምትወልድም አበሠራት፤ ‹‹ጌታዬም አርጅቷል እኔስ ገና ነኝ?›› ብላም ሣራ ጠየቀች፤ ‹‹ቦኑ ነገር ዘይሰአኖ ለእግዚአብሔር፤ በእውነት ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር አለ?››  እግዚአብሔርም አለ ‹‹እኔ የማደርገውን ከአብርሃም እሰውራለሁ፤ አብርሃም በምድር ላይ ትልቅ ብርቱ ሕዝብ ይሆናል፡፡›› መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል እመቤታቸንን ለማብሠር በመጣ ጊዜ ‹‹ልጅ ትወልጃለሽ›› ባላት ጊዜ ‹‹ወንድ ሳላውቅ እንደምን ይሆናል›› በማለት ስትጠይቀው መልአኩ ያስረዳት ዘንድም ከእርሷ በፊት ስለ ፀነሱችውን ኤልሳቤትን ነገራት፤ ለእግዚአብሔር የሚሣነው ነገር እንደሌለም አስረዳት፡፡ (ሉቃ. 1$@6-#7) ይህም እግዚአብሔር በዘመን ብዛት የማይለወጥ መሆኑን ያስረዳል፡፡ በአብርሃም ድንኳን እግዚአብሔር ተገኝቶ ለአብርሃምና ለሣራ የምሥራች ነገሯቸው፡፡ በአማናዊት ድንኳን እመቤታችን ተገኝቶ የምሥራችን ነገራት፤ ከዚህ አያይዞ ለአብርሃም እንዲህ ብሎት ነበር፤ ‹‹በዘርህ አሕዛብ ይባረካሉ፡፡›› ከአብርሃም ዘር ከተገኘችው እመቤታችን የረከሰው ዓለም ሁሉ እንዲባረክ ሆነ፤ ምክንያቱም ከእመቤታችን የተገኘው መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ስለሆነ፡፡

በአብርሃም ድንኳን ሥላሴ ተስተናግደውበታል፤ ይህች ድንኳን በእመቤታችን ትመሰላለች፤ በአብርሃም ድንኳን ‹‹አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ›› እንደገቡ ሁሉ አምስት ሽህ አምስት መቶ  ዘመን ሲፈጸም በእመቤታችን እግዚአብሔር አብ ለአጽንዖ እግዘአብሔር መንፈስ ቅዱስ፣ ለአንጽሖ አግዚአብሔር ወልድ፣ በተለየ አካሉ ሥጋን ለመልበስ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም አድረዋልና እመቤታችን በአብርሃም ድንኳን መመሰልዋ እንዲህ ስለሆነ ‹‹አብና መንፈስ ቅዱስ ተዋሐዱ አይባልም ወልድ በተለየ አካሉ እንጂ፤

በአጠቃላይ በዚህ ዕለት በአብርሃም ቤት እግዚአብሔር የተስተናገደበት፣ አንድነቱና ሦስትነቱ የተገለጠበት፣ አብርሃም እና ሣራ ካረጁ በኋላ ልጅ እንደሚወልዱ የተበሠረበት፣ ይሰሐቅንም እንደሚወልድ የተነገረበት እንዲሁም አብርሃም በእግዚአብሔር ፊት ቆሞ ስለ ገሞራ ሰዎች የማለደበት ዕለት ነው፡፡

ለአብርሃም ምሥጢሩን የገለጠ እግዘአብሔር ለሁላችን ይግለጥልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!