ዜና ዕረፍት

የታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳምና የመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የበላይ ኃላፊ ሆነው በበአታቸው በመወሰን ሲያገለግሉ የቆዩት አባታችን ብፁዕ አቡነ ሰላማ ከዚህ ዓለም ተለይተዋል። ጸሎተኛ፣ ደግ፣ ርኀሩኁና ታጋሽ የነበሩት አረጋዊው አባት ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በአዲስ አበባ ሀሌሉያ ሆስፒታል በሕክምና ሲረዱ ቆይተው መስከረም ፲፰ ቀን ፳፻ ፲ወ፮ ዓ/ም ያረፉ መሆኑ ታውቋል።

የብፁዕ አቡነ ሰላማ አጭር የሕይወት ታሪክ

ዜና ሕይወቱ ለብፁዕ አቡነ ሰላማ (የብፁዕ አቡነ ሰላማ አጭር የሕይወት ታሪክ)

ብፁዕ አቡነ ሰላማ ከአባታቸው ከአቶ ገብረ ሥላሴ ገብረ መድኀንና ከእናታቸው ከወ/ሮ ብዙነሽ ወንድሙ በትግራይ ክፍለ ሀገር በመቀሌ ከተማ ልዩ ስሙ በዓታ  ለማርያም በተባለው ፲፱፴፬ ዓ/ም ተወለዱ።

ዕድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስ በትውልድ ሀገራቸው ንባብና የቃል ትምህርት በሚገባ የተማሩ ሲሆን ለግብረ ዲቁና የሚገባውንም ትምህርት ከየኔታ ክነፈ ርግብ ተምረዋል፤ ዲቁና ከብፁዕ አቡነ ማርቆስ ተቀብለዋል።

ብፁዕነታቸው ለቤተክርስቲያንና ለመንፈሳዊ ዕውቀት ባላቸው ጥልቅ ፍቅር በተለያዩ አካባቢዎች በመዘዋወር የተለያዩ መንፈሳዊ ትምህርቶችን የተማሩ ሲሆን

ዜማ፡- ከየኔታ ተክለ ማርቆስ ማየ አንበሳ ገዳም (ተንቤን)

– ቅኔ፡- ከየኔታ ንጉሤ መነዌ ገዳም (ተንቤን)

– ቅኔ፡- ከየኔታ አክሊሉ ደበጋ (ጐንደር)

  • ትርጓሜ መጻሕፍት- ከየኔታ ኃ/ማርያም ቀረፃ ማርያም ከምትሀባል ገዳም

ቅኔና ትርጓሜ መጻሕፍት፡- እንድባ ጊዮርጊስ ከየኔታ ልሳነ ወርቅ (ጐጃም)

  • ቅኔ፡- ከየኔታ ዲበኩሉ (ጐጃም) በሚገባ ከተማሩ በኋላ ለመምህር ነት በቅተዋል፡፡

ከዚህ በኋላ በጐጃም ክፍለ ሀገር በፈረስ ቤት ሚካኤል፣ በጅጋ ሚካ ኤል ወንበር ዘርግተው ለ፲፪ ዓመታት ቅኔ በማስተማር አያሌ ደቀ መዛሙርትን አፍርተዋል፡

መዝገበ ቅዳሴ ከየኔታ ልዑል (ቦረራ ሚካኤል) ተምረዋል፤ በወቅቱ የጐጃም ሊቀ ጳጳስ ከነበሩት ከብፁዕ አሱነ ማርቆስ የቅስናና የምንኵስና መዐርግ ተቀብለዋል።

ብፁዕ አቡነ ሰላማ በ ፲፱፻፷፬ ዓ.ም ወደ አርሲ ክፍለ ሀገር በመሄድ በወቅቱ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በነበሩት በብፁዕ አቡነ ሉቃስ መልካም ፈቃድ በሀገረ ስብከቱ በማስተማር፣ የአውራጃ ሰባኬ ወንጌል በመሆን፣ የወረዳ ሊቀ ካህናት በመ ሆን በተለያዩ የኃላፊነት ሥራዎች ተመድበው በመሥራት ሰፊ አገልግሎት አበርክተዋል፤ በርካታ ደቀ መዛሙርትንም አፍርተዋል፤ በዚሁ ሀገረ ስብከት ለ፳፪ ዓመታት በማስተማር ቆይተዋል፤ በዚህም ሰፊ ወቅት ብዙ ደቀ መዛሙርትን አውጥተው ለቤተ ክርስቲያን አበርክተዋል፡፡

ብፁዕነታቸው ከአርሲ ሀገረ ስብከት በ፲፱፻፹፮ ዓ.ም ወደ አዲስ አበባ ከመጡ በኋላ ውቅያኖስ በሆነው እውቀታቸውና በቅድስናቸው ቤተ ክርስቲያንንም ሆነ ምእመናንን እንደሚጠቅሙ በማሰብ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በተለያዩ ጊዜያት በቅዱሳን ፓትርያርኮች ፈቃድና ትእዛዝ እየተሾሙ፦-

⇨ በቡራዩ ፄዴንያ ማርያም፣

⇨ በመተሐራ መድኃኔ ዓለም፣

-በቃሊቲ ቅዱስ ገብርኤልና ሳሎ ቅዱስ ጊዮርጊስ፣

⇨ በሰአሊተ ምሕረት፣

⇨ በደብረ አሚን ተክለ ሃይማኖት በአስተዳዳሪነት ተመድበው ለበር ካታ ዓመታት በማስተማር በሚያስመንነው ስብከታቸው ብዙ አማ ንያንን አበርክተዋል፤ ለምናኔም አብቅተዋል፤ በተሰጣቸው ሀብተ ፈውስ በጸሎታቸው አያሌ ሕሙማንን ፈውሰዋል፧ ሰበካ ጉባኤን አጠናክረዋልº ስብከተ ወንጌልን አስፋፍተዋል፤ በተለይም በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሊቀ ሥልጣናት ሆነው ለ ዓመታት ያህል በአስተዳደሩበት ጊዜ ከፈጸሟቸው ተግባራት ዋና ዋናዎቹ ምእመናን በጣዕመ ስብከታቸውና በቅድስናቸው እየተማረኩ ለካቴድራሉ በሚያደርጉት የቦታና የገንዘብ ልግስና በርካታ የሆኑ የልማት ተግባራትን አከናውነዋል።

❖ በዚህም መሠረት በትምህርታቸው በጎ አድራጊዎችንና ምእመናንን በማስተባበር በካቴድራሉ ስም የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤትና ከፍተኛ ክሊኒክ አሠርተው በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፣ ሊቀ ጳጳስ አክሱም፣ ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ተባርኮ አገልግሎት በመስጠት ላይ ነው፡፡

⇨ በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ለ ፭ ዓመታት ካገለገሉ በኋላ በእንጦጦ ሐመረ ኖኅ ኪዳነ ምሕረት ገዳም በአስተዳዳሪነት አገልግለዋል።

⇨ ብፁዕ አቡነ ሰላማ ሙሉ የቤተ ክርስቲያን ትምህርታቸውን አጠናቅቀው በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ከተመደቡበት ጊዜ ጀምሮ ከቦታ ወደ ቦታ በመዘዋወር በአብነት መምህርነታቸው በተለይም በቅኔ መምህርነታቸው በተለያዩ አህጉረ ስብከት ወንበር ዘርግተው በማስተማር እስከ ጵጵስና ደረጃ የደረሱ አያሌ ምሁራንን አፍርተው ለቤተ ክርስቲያን ያስረከቡ፣ በልዩ የስብከት ችሎታቸው የታወቁ ሰባክያነ ወንጌልን ያፈሩና አማንያንን ያበዙ፣ ቅድስናን ከሙያ ጋር አስተባብረው የያዙ፣ የቅዱሳኑ፣ የፍጹማኑ ረድኤት ያልተለያቸው፣ እንደ አባቶቻቸው ቅዱሳን ሐዋር ያት አጋንንትን የማስወጣትና ሌላውንም ደዌ ሁሉ የመፈወስ ሀብተ ፈውስ የተሰጣቸው፣ በጥላቸው ብቻ ሕሙማንን የሚፈ ውሱ፣ የበቁ (ፍጹም) አባት ነበሩ።

ብፁዕ አቡነ ሰላማ ከፈጣሪያቸው የተሰጣቸው ተውህቦ የተወሰነ አይደለም ሀብተ ጸጋቸው ብዙ ነው! ጣዕመ ስብከታቸው ካለ መጠገቡም በላይ በተመስጦ በአካለ ሥጋ ያሳርጋልI ቅኔያቸውም ልዩ ጣዕም አለው ከማር ከወተት ይጣፍጣል! ፈጣሪያቸውን ብቻ አይደለም የሚያከብሩት፣ ሲበዛ ሰው አክባሪ ናቸው፡፡ ምንም ይሁን ምን በአርአያ እግዚአብሔር የተፈጠረውን ትልቁንም ትንሹንም ሁሉ በአክብሮት የሚወዱ አባት ነበሩ።

በአጠቃላይ ብፁዕ አቡነ ሰላማ የቤተ ክርስቲያናችን ጸጋና በረከት ነበሩ።በዚህ ቅድስና ቸው፣ በቤተ ክርስቲያን ትምህርት ሙሉ ችሎታቸው፣ በአብነት መምህርነታቸው በርካታ ምሁራንን በማፍራታቸውና ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናቸው ባበረከቱት ሰፊ የሆነ መንፈሳዊ አገልግሎታቸው ተመዝነው ብቁና ፍጹም አባት ሆነው በመገኘታቸው ሐምሌ ፱ ቀን ፲፱፻፺፯ ዓ.ም በተደረገው የጳጳሳት ምርጫ ከሌሎች ዕጩ ቆሞሳት ጋር ተወዳድረው የድምፅ ብልጫ ስለ አገኙ የአክሱምና ማዕከላዊ ዞን ሃገረ ስብከት ኤጲስ ቆጶስ ሆነው የተመደቡ ሲሆን ከታኅሣሥ ፱/ ፪ሺ፪ ዓ/ም ጀምሮ የሰሜን ምዕራብ ሽሬ እንዳሥላሴ ሀገረ ስብከትን ደርበው እየሰሩ እስከ ግንቦት ፳፰/፪ሺ፭ ዓ/ም ድረስ ሐዋርያዊ ተግባራቸውን ሲፈጽሙ ቆይተዋል።

ግንቦት ፳፰ /፪ሺ ፭ ዓ/ም ከትግራይ ማዕከላዊ ዞን አክሱም ሀገረ ስብከት ወደ አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ተዛውረው የታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም እና የመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የበላይ ኃላፊ ሆነው ሲያገለግሉ ቆይተው በ ፪ሺ፮ ዓ/ም የምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመሆን ለ፮ ዓመታት በምሥራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ከፍተኛ ሐዋርያዊ አገልግሎትን ፈጽመዋል።

ከኅዳር ፳፻፲፪ ዓ/ም ጀምሮ በድጋሚ የታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም እና የመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የበላይ ኃላፊ ሆነው በበአታቸው በመወሰን ሲያገለግሉ ቆይተው ባደረባቸው ሕመም ምክንያት ዐርፈዋል፡፡

በረከታቸው ይደርብን!