በዓታ ለማርያም

ታኅሣሥ በባተ በሦስተኛው ቀን የሚታሰበውና የሚከበረው በዓል ‹‹በዓታ ለማርያም በመባል ይታወቃል፡፡ ከእናቷ ከቅድስት ሐና እና ከአባቷ ቅዱስ ኢያቄም በስዕለት የተወለደችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ዕለት የከበረ እንደመሆኑ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ታከብረዋለች፡፡

በዓት ቃሉ የግእዝ ሲሆን ቤት ማለት ነው፡፡ ደጋጎቹ የእግዚአብሔር ሰዎች ቅዱስ ኢያቄምና ቅድስት ሐና ልጅ አጥተው ለብዙ ዘመናት ከመኖራቸው የተነሣ በኀዘን ፈጣሪያቸውን ሲማጸኑ ቃል በመግባት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሦስት ዓመት ሲሆናት በእግዚአብሔር ቤት ትኖርና ታገለገል ዘንድ በቤተ ክርስቲያን እንድትኖር ስለሰጧት በዓሉም ስያሜውን በዚያ መሠረት አግቷል፡፡

በዚያን ጊዜም በቤተ ክርስቲያን ያገለግል የነበረው ካህኑ ዘካርያስ ስዕለታቸውን አስተውሶ ቅድስት ድንግል ማርያምን ሊቀበላት ሲቀርብ እንደ ፀሐይ የምታበራ ሕፃን ሆና አገኛት፤ በመገረምና በመጨነቅም ከወላጆቿ ጋር ምን ሊመግቧት እንደሚችሉ በመጨነቅ ላይ ሳሉ ሕዝቡ በተሰበሰበበት መካከል መልአኩ ፋኑኤል ኅብስት ሰማያዊ ጽዋዕ ይዞ ከሰማይ ወረደ፡፡ ካህኑ ዘካርያስም ለእርሱ የመጣ መና መስሎት ሲቀረብ ወደ ላይ ተመለሰበት፡፡ በዚያ የተሰበሰቡት ሰዎችም እያንዳንዳቸው ቢሞክሩ በተመሳሳይ መልኩ ተመልሶ ወደ ላይ ራቀባቸው፡፡ ‹‹ምን አልባት ለእንግዶች የመጣ ሀብት እንደሆነ›› ብለው ቅድስት ሐና እና ቅዱስ ኢያቄም እንዲቀርቡ ቢደረግም ለእነርሱም ራቀባቸው፡፡ ካህኑ ዘካርያስም ቅድስት ሐናን ‹‹እግዚአብሔር የሚያደርገውን የሚያውቅ የለምና ልጅቷን ትተሸ ወደዚህ ነይ›› አላት፤ ሆኖም ግን ቅድስት ማርያም እናቷ ትታት ስትሄድ መከተል ጀመረች፤ ምርርም ብላ አለቀሰች፡፡ በዚህም ጊዜ መልአኩ ፋኑኤል ወደ እርሷ ቀርቦ አንድ ክንፉን አንጥፎ አንድ ክንፉን ጋርዶ መገባት፤ ከዚያም በክብር ዐረገ፤ ሊቀ ካህናቱና ሕዝቡም ‹‹የምግቧ ነገር ከተያዘልን በቤት እግዚአብሔር ትኑር›› ብለው ወደ ቤተ መቅደስ አስገቧት፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ሰማያዊ ኅብስትና መጠጥ እየተመገበች  በቤተ መቅደስ  ለ፲፪ ዓመታትም ኖራለች፡፡

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነትና ተራዳኢነት አይለየን፤ በረከቷ ይደርብን፤አሜን!

ምንጭ፡- ነገረ ማርያም