“የጽድቅንም ጥሩር ልበሱ”/ኤፌ.፮.፲፬/

ክፍል አንድ

በእንዳለ ደምስስ

መንፈሳዊ ሰው ርስት መንግሥተ ሰማያትን ይወርስ ዘንድ፣ ራስን ለእግዚአብሔር ማስገዛት፣ ትእዛዙንም መፈጸም ይጠበቅበታል፡፡ ከኃጢአት ወደ ጽድቅ ለመሸጋገርም አንድ ክርስቲያን መንፈሳዊ የተጋድሎ መሣሪያዎችን ይዞ መገኘት ይገባዋል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለኤፌሶን ክርስቲያኖች በጻፈው መልእክቱ “እንግዲህ ወገባችሁን በእውነት ታጥቃችሁ ቁሙ፣ የጽድቅንም ጥሩር ልበሱ” እንዲል/ኤፌ.፮.፲፬/፡፡

ሃይማኖትን፣ መልካም ምግባርን፣ ፍቅርን፣ የንስሓ ሕይወትን፣ ወዘተ የያዘ ሰው ራሱን ከዲያብሎስ ውጊያዎች ለመከላከል መንፈሳዊ የተጋድሎ መሣሪያዎችን መያዝ ወይም መታጠቅ ያስፈልገዋል፡፡ እነዚህም፡- ጾም፣ ጸሎት፣ ስግደት፣ ምጽዋት ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ በዚህ ጽሑፍ እነዚህን በቅደም ተከተል በጥቂቱ የምናቀርብ ይሆናል፡፡

ጾም

ጾም ክርስቲያን የሆነ ሰው ሁሉ ከሰባት ዓመት የሕፃንነት ዕድሜው ጀምሮ ለተወሰነ ጊዜና ሰዓት ከእህል፣ ከውኃ ተከልክሎ መቆየት ማለት ነው፡፡ በዚህ ወቅት ከወተት፣ ከሥጋ፣ ከቅቤና፣ ከእንቁላል የአጽዋማቱ ሳምንታት እስኪጠናቀቁ ድረስ የምንከለከልበት ነው፡፡ /ፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ ፲፭/፡፡

ጾም ዓይን ክፉ ከማየት፣ ጆሮ ክፉ ከመስማት፣ አንደበት ክፉ ከመናገር፣ እጅ ክፉ ከመሥራት በአጠቃላይ የኃጢአት ሥራ ከመሥራት መከልከል ማለት ነው፡፡ /ቅዱስ ያሬድ/

ጾም የአዋጅ እና የግል/የፈቃድ/ ጾም ተብሎ በሁለት ይከፈላል፡፡

. የአዋጅ ጾም፡ ይህ ጾም በቤተ ክርስቲያናችን ምእመናን ሁሉ በሥውር ሳይሆን በይፋ የሚጾሙት ጾም ነው፡፡ ይህም መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት ያለው ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኢዩኤል “በጽዮን መለከትን ንፉ፣ ጾምንም ቀድሱ፣ ጉባኤውንም አውጁ” በማለት እንደተናገረው (ኢዩ 2፡፲፭)፡፡

በዚህም መሠረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የደነገገቻቸው የአዋጅ አጽዋማት ሰባት ሲሆኑ፣ እነዚህም እንደሚከተለው ተዘርዝረዋል፡-

፩. የነቢያት ጾም                          ፭. የሐዋርያት ጾምየገሃድ ጾም                ፮. ጾመ ድኅነት (ረቡዕና ዓርብ)

2. የነነዌ ጾም                            ፯. ጾመ ፍልሰታ ናቸው፡፡

፬. ዐቢይ ጾም

. የግል/ፈቃድ/ ጾም፡  የግል ጾም ስንል አንድ ሰው በሠራው ኃጢአት ምክንያት ወደ ንስሓ አባቱ በመቅረብ  በጸጸትና በተሰበረ ልብ ሁኖ ኃጢአቱን በመናገር የሚሰጠው የንስሓ ጾም ነው፡፡ ይህ ጾም በፈቃድ የሚጾም ሲሆን አንድ ሰው ስለ በደሉ፣ ስለደረሰበትና በእርሱ ላይ ስለሆነ ነገር፣ እንዲሁም ስለሚፈልገው ጉዳይ እግዚአብሔር ተገቢውን መልስ እንዲሰጠው የሚጾመው ጾም ነው፡፡ ለምሳሌ ነቢዩ ዳዊት የልጁን መታመም በሰማ ጊዜ ጾሟል፡፡ /2ኛ.ሳሙ.፲2፡፲2/፡፡ ነገር ግን በግል ጾም ጊዜ ጾሙ ይፋ ስላልሆነ ራስን መሠወር እንደሚያስፈልግ ታዟል፡፡ ይህንንም አስመልክቶ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ ሲል ተናግሯል፡፡ “ስትጾሙም እንደ ግብዞች አትጠውልጉ፣ እነርሱ እንደ ጾሙ ለሰው ይታዩ ዘንድ መልካቸውን ይለዋውጣሉና፣ እውነት እላችኋላሁ ዋጋቸውን ተቀብለዋል፡፡ እናንተስ በምትጾሙበት ጊዜ  ራሳችሁን ቅቡ፣ ፊታችሁንም ታጠቡ፡፡ በሥውር ለሚያይ ለአባታችሁ እንጂ ለሰዎች እንደ ጾማችሁ እንዳትታዩ በሥውር የሚያያችሁ አባታችሁም ዋጋችሁን በግልጥ ይሰጣችኋል” ብሏል፡፡(ማቴ.፮፡፲፮-፲፰)፡፡ በዚህ መሠረት የግል ጾምን ከጿሚው ሰው እና ከእግዚአብሔር ውጪ ማንም ሊያወቅ አይገባም፡፡

2. ጾም ለምን ያስፈልጋል?

ጾም ያስፈለገበት ምክንያት የሥጋን ፍላጎት በመግታትና ከኃጢአት ሥራዎች የሚጠብቀን በመሆኑ ነው፡፡ ሰው እንደፈለገው የሚበላና የሚጠጣ፣ ሁል ጊዜ ሳይጾም የሚኖር ከሆነ በኃጢአት ይወድቃል፡፡ ይህንንም አስመልክቶ በፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭ “ሥጋዊ ፍትወትን ያደክም ዘንድ ጾም ታዘዘ” እንዲል፡፡ ጾም ረኀብን፣ ችግርን እንድናውቅ፣ ለተራቡና ለተጠሙ በአጠቃላይ ለተቸገሩ ሁሉ እንድናስብና እንድናዝን፣ ባለን አቅም ሁሉ እንድንረዳ ያደርገናል፡፡ “ጿሚ ሰው የረኀብን ችግር ያውቅ ዘንድና ለተራቡ ይራራ ዘንድ ጾም ታዘዘ” ይላል፡፡(ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፭)

ስለዚህ ጾም ለተራቡ፣ ለጠጠሙ እንዲሁም ለተቸገሩ ሁሉ መራራትን፣ በጎ ማድረግን በማስተማር የምግባር፣ የትሩፋት፣ የትሕርምት ሰዎች ያደርገናል፡፡ ይህም በእግዚአብሔር ፊት የጽድቅ ሥራ ሆኖ መንግሥተ ሰማያትን ያወርሰናል፡፡

ቀድሞ እግዚአብሔር አዳምንና ሔዋንን ካዘዛቸው ትእዛዛት መካከል “መልካምንና ክፉን ከሚያሳየውና ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፣ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና” /ዘፍ.2.፲፮///////// ብሎ ሥርዓት ቢሠራላቸውም አዳምና ሔዋን ግን ከእግዚአብሔር ጋር የገቡትን ቃል አፈረሱ፣ ገነትን ከሚያህል ሥፍራም ተሰደዱ፡፡ ለመሰደዳቸው ምክንያት የሆነው ይጾሙት ዘንድ የተሠራላቸውን ሥርዓት በማፍረሳቸው፣ ዕፀ በለስንም በመብላታቸው ነው፡፡ መብል ከእግዚአብሔር አንድነት የሚለይ ከሆነ ጾም ደግሞ ለእግዚአብሔር ትእዛዛት እንድንገዛ፣ መንግሥቱንም እንድንወርስ ድርሻ እንዳለው ያመለክተናል ማለት ነው፡፡ “ጾምስ በሕግ ውስጥ በታወቀው ጊዜ የሰው ከምግብ መከልከል ነው፡፡ በደሉን ለማስተሥረይ፣ ዋጋውን ለማብዛት፣ እርሱን ወዶ ሕግን ለሠራለት እየታዘዘ የፈቲውን ኃይል ያደክም ዘንድ፣ ለነባቢት ነፍስም ትታዛዝ ዘንድ” እንዲል /ፍትሐ ነገ. አንቀጽ ፲፭/፡፡

አምላካችን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም “ስለ ጽድቅ ብለው የሚራቡና የሚጠሙ ንዑዳን ክቡራን ናቸው፣ እነርሱ ይጠግባሉና” /ማቴ ፭.፮/ ሲል ተናግሯል፡፡ ስለዚህ መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ ጾም ድርሻ እንዳለው ያመለክተናል፡፡

ጾም በሀገር ላይ የታዘዘ መቅሠፍትን ያርቃል፡ መጽሐፍ ቅዱስ በሀገር ላይ ሊመጣ ያለውን መቅሰፍት በጾም አማካይነት እንደሚርቅ ያስተምረናል፡፡ ለዚህም እንደ ምሳሌ የነነዌ ሰዎችን መመልከት እንችላለን፡፡ የነነዌ ሰዎች የዮናስን ትምህርት መሠረት በማድረግ ሕፃናቱን ጨምሮ እንስሳቱ ሁሉ ለሦስት ቀናት ጾመዋል፡፡ እግዚአብሔርም ሊመጣ የነበረውን መቅሰፍት አርቆ ለእነርሱ የታዘዘው እሳት የዛፉን ጫፍ አቃጥሎ ተመልሷል፡፡ (ዮና.፫)፡፡ “አምላካችሁም እግዚአብሔር መሓሪና ይቅር ባይ፣ ቁጣውም የዘገየ፣ ምሕረቱም የበዛ ለክፋትም የተጸጸተ ነውና” እንዲል /ኢዩ.2.፲፫///፡፡

ጾም ሰይጣንን ድል የምንነሣበት መንፈሳዊ መሣሪያ ነው፡- ከላይ እንደተጠቀሰው ጾም ፈቃደ ሥጋችንን ለነፍሳችን የምናስገዛበት፣ ለመልካም ነገር የምንነሳሳበትና ክፉውን የምናርቅበት መሣሪያ በመሆኑ ዲያብሎስ በእኛ ላይ አይሠለጥንም፡፡ ክፉ ከማሰብ፣ ክፉ ከማድረግ እንድንቆጠብም ያደርገናል፣ ለመንፈሳዊ ተጋድሎም ያዘጋጀናል፡፡ ሥጋዊ ፍላጎታችንን እየገታን ለመንፈሳዊ ሕይወታችን እንበረታለን፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ነፍሴ በቅቤና በስብ እንደሚጠግቡ ትጠግባለች፣ ደስተኞች ከንፈሮቼም ስምህን ያመሰግናሉ” በማለት እንደተናገረው፡፡(መዝ.፷፪፥፭)፡፡

በተቃራኒው ደግሞ ባለመጾማችንና ለመንፈሳዊ ተጋድሎ ራሳችንን ባለማዘጋጀታችን ዲያብሎስ እንዲሠለጥንብን፣ ለኃጠአት እንድንሣሣና ከእግዚአብሔር እንድንለይ ያደርገናል፡፡ “እንዲህ ዓይነት አብሮ አደግ ጋኔን ያለ ጾምና ጸሎት አይወጣም” /ማቴ.፲፯፤፳1/ ሲል ጌታችን በቅዱስ ወንጌል እንደተናገረው ሰይጣንን ድል መንሳት የምንችለው በጾምና በጸሎት እንደሆነ ያስረዳናል፡፡

ጾምፈተና እና መከራ ያድናል፡- ፈተና እና መከራ በገጠመን ጊዜ ሱባኤ ይዘን እንጾማለን፣ እንጸልያለን፤ ነገር ግን ብዙዎቻችን ፈተና ወይም መከራ በራቀልን ጊዜ ደግሞ ጾም ጸሎት እናቆማለን፡፡ የምንሻውን ነገር እስክናገኝ፣ ከደረሰብንና ሊደርስ ካለብን ፈተና ለመዳን እንጨነቃለን፣ እንጠበባለን፡፡ ይህ ከክርስቲያኖች የሚጠበቅ አይደለም፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እንጾምባቸው ዘንድ የደነገገችልን የአዋጅ አጽዋማት እንዳሉ ሁሉ የግል/የፈቃድ/ ጾምም እንዳለ ማወቅ ተገቢ ነው፡፡ ክርስቲያን በቀን ውስጥ ሊጸልይባቸው የሚገቡ ሰዓታት እንደተወሰኑ ሁሉ ጾምም አስፈላጊና ዋነኛው ነው፡፡ ሊመጣ ካለው ፈተናም የምንጠበቀው በጾምና ጸሎት ነው፡፡ “ማቅ ለብሼ በአመድም ላይ ሆኜ ስጾም፣ እጸልይና እለምን ዘንድ ፊቴን ወደ ጌታ ወደ አምላክ አቀናሁ” (ዳን.9.፫) እንዲል ነቢዩ፡፡

በጾም ኃጢአት ይሠረያል፡- ቅዱስ ያሬድ “በጾም ወበጸሎት ይሠረይ ኃጢአት፣ በጾምና በጸሎት ኃጢአት ይሠረያል” እንዳለ ጾም ትልቅ ኃይል አለው፡፡ የነነዌ ሰዎች የዮናስን ትምህርት መሠረት በማድረግ ሦስት ቀን ጾመው ጸልየው ኃጢአታቸው ተሠርዮላቸዋል፡፡/ዮና.፫/፡፡ነቢዩ ዳንኤል በጾም ከአፈ አናብስት /ከአንበሶች አፍ/ የዳነው በጾምና በጸሎት ነው፡፡ /ዳን.፮/፡፡  ሶስናም በጾም ከሐሰት ምስክሮች ድናለች፡፡ /ሶስ.1/ ሌሎችም ቅዱሳን በጾም ከፈተና እና ከመከራ ድነዋል፡፡

ጾም ከላይ የተዘረዘሩት ብቻ ሳይሆን በርካታ ጥቅሞች አሉት፡፡ ኃጢአት በመብል አማካይነት ወደ ዓለም እንደገባ በጾም ደግሞ ዲያብሎስን ድል እናደርጋለን፡፡ ዲያብሎስም ወደ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀርቦ “አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህስ እነዚህ ድንጋዮች ዳቦ እንዲሆኑ እዘዝ” አለው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም መልሶ “ሰው የሚኖረው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣው ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ እንዳይደለ ተጽፏል” /፬.፬/ አለው እንዲል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዲያብሎስን በገዳመ ቆሮንቶስ አርባ ቀንና ሌሊት ጾሞ ድል ነስቶታልና እኛም እርሱን አርአያ አድርገን በመጾም በመንፈሳዊ ሕይወት በመጽናት ድል ልናደርገው ይገባል፡፡

ይቆየን፡፡

ጾመ ነቢያት

ጾመ ነቢያት ቅዱሳን ነቢያት ጌታ ለአዳም በሰጠው ተስፋ መሠረት ይወርዳል፣ ይወለዳል ብለው ሱባዔ በመቁጠር የክርስቶስን ልደት በመጠበቅ የጾሙት ጾም ነው፡፡

በየዘመናቱ የተነሡ ነቢያት እግዚአብሔር ወደፊት ሊያደርግ ያሰበውን በተሰጣቸው ጸጋ ትንቢት  የራቀው ቀርቦ፣ የረቀቀው ገዝፎ ያዩት ነገር እንዲደርስላቸው ጾሙ፣ ጸለዩ፡፡ ነቢያት ስለ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልደት፣ ጥምቀት፣ ስደት፣ ሞቱና ትንሣኤው፣ እንዲሁም ጨለማ የሆነውን የሰው ልጆችን ልቡና በትምህርቱ ስለ ማብራቱ፣ ጨለማውን ዓለም በብርሃኑ ስለ መግለጡ፣ ስለ ሰው ልጆች ድኅነት ጸዋወ መከራ ስለ መቀበሉና ስለ መሰቀሉ፣ ስለ  ትንሣኤው፣ ስለ ዕርገቱና ዳግም ምጽአቱ ትንቢት ተናግረዋል፡፡

እንደዚሁም ለአዳም የተሰጠው ተስፋ ተገልጦላቸው ለተናገሩት ትንቢት ፍጻሜ እንዲያደርሳቸው ፈጣሪያቸውን በየዘመናቸው “አንሥእ ኃይለከ፣ ፈኑ እዴከ” እያሉ ጮኹ፡፡ በጾምና በጸሎት ሰው የሚሆንበትን ጊዜ በቀናት፣ በሣምንታት፣ በወራት፣ በዓመታት ቆጠሩ፡፡

ነቢያት ተስፋው በዘመናቸው ተፈጽሞ በዓይነ ሥጋ ለማየት ባይችሉም “እግዚአብሔር የማያደርገውን አይናገር፣ የተናገረውን አያስቀር” ብለው አምነው ከወዲሁ ተደሰቱ፡፡ ዘመኑ ሲደርስም በጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ትንቢቱ ተፈጸመ፡፡ ስለዚህ ነቢያት ይወርዳል፣ ይወለዳል እያሉ የጾሙት በመሆኑ “ጾመ ነቢያት” ይባላል፡፡ የወልደ እግዚአብሔርን ሰው መሆን ያስተማሩበት ስለሆነም “ጾመ ስብከት” ይባላል፡፡ ጾመ ነቢያት ከሰባቱ የአዋጅ አጽዋማት መካከል አንዱ ሲሆን፣ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችንም ከኅዳር ፲፭ ቀን ጀምሮ እንዲጾም ደንግጋለች፡፡

ጾም ቃላዊ ትርጉሙ ጾመ፣ ተወ፣ ታረመ ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ቃል ነው፡፡ በታወቀ ጊዜ ከምግብ መከልከል፣ መጠበቅ ማለት ነው፡፡ በአጭሩ ጾም ለሰውነት ከሚያስፈልገው ኃይል ከሚሰጡ ምግቦች፣ ከክፉ ሐሳብና ድርጊት በመከልከል ከእግዚአብሔር ጋር በፍቅር የመኖር ሕይወት ነው፡፡ ለክፉ ሥራ/ኃጢአት ከሚያነሣሱና ሰውነትን ከሚገነቡ ምግቦችና መጠጦች በመከልከል በጾም፣ በጸሎት በመወሰን ልቡናችንን ለእግዚአብሔር ሰጥተን፣ በፍጹም ትኅትና የምንጾመው ጾም ነው፡፡ በዚህ ወቅት በመንፈሳዊ ሕይወታችን የምንበረታበት፣ ንስሓ የምንገባበትና ለቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ የምቀርብበት በመሆኑ ጊዜውን በዋዛ ፈዛዛ ማሳለፍ አይገባንም፡፡ ከቅዱሳን ነቢያት በረከት እንሳተፍ ዘንድ የትሩፋት ሥራዎችን እየሠራን ልናሳልፈውም ይገባል፡፡

አርባዕቱ እንስሳ

ኅዳር ስምንት ቀን “ሥጋ የሌላቸው የአርባዕቱ እንስሳ በዓላቸው ነው፡፡ እነርሱም የእግዚአብሔርን መንበር የሚሸከሙ ሠረገላዎቹ ናቸው” በማለት ከቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ቅዱሳት መጻሕፍት መካከል አንዱ የሆነው መጽሐፍ ስንክሳር ይገልጻል፡፡  ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ይህንኑ በራእይ ያየውን ሲመሰክር እንዲህ ይላል፡- “በዙፋኑም ፊት ብርሌ የሚመስል የብርጭቆ ባሕር ነበረ፤ በዙፋኑም መካከል፣ በዙፋኑ ዙሪያም አራት እንስሶች አሉ፣ እነርሱም በፊትም በኋላም ዐይኖችን የተመሉ ናቸው፡፡ ፊተኛውም እንስሳ አንበሳን ይመስላል፣ ሁለተኛውም እንስሳ ጥጃን ይመስላል፣ ሦስተኛውም እንስሳ ሰውን ይመስላል፣ አራተኛውም እንስሳ የሚበር ንስርን ይመስላል፡፡ ለእነዚህም አራቱ እንስሶች ለእያንዳንዳቸው ስድስት ክንፎች አሏቸው፤ በሁለንተናቸውም ዐይኖችን የተመሉ ናቸው፡፡ “ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ የነበረውና ያለው፣ የሚመጣውም፣ ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክ እያሉ ቀንና ሌሊት አያርፉም፡፡ እነዚህ እንስሶችም በዙፋን ላይ ለተቀመጠው ከዘለዓለም እስከ ዘለዓለም በሕይወት ለሚኖረው ለእርሱ ክብርና ውዳሴን ምስጋናንም ይሰጣሉ”(ራእ.፬.፮-9፣ ስንክሳር ዘኅዳር ገጽ 2፻፸፯) በማለት ገልጿቸዋል፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስም “እግዚአብሔርን በረዥምና ከፍ ባለ ዙፋን ላይ ተቀምጦ አየሁት፣ ምስጋናውም ቤቱን ሞልቶት ነበር፡፡ ሱራፈልም በዙሪያው ቆመው ነበር፣ ለእያንዳንዱም ስድስት ክንፍ ነበረው፣ በሁለቱ ክንፎቻቸው ፊታቸውን ይሸፍኑ ነበር፣ በሁለቱም ክንፎቻቸው እግሮቻቸውን ይሸፍኑ ነበር፣ በሁለቱም ክንፎቻቸውም ይበርሩ ነበር፡፡ አንዱም ለአንዱም ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች፣ እያለ ይጮኸ ነበር፡፡”(ኢሳ.፮.፩-፫፤ ስንክሳር ገጽ 2፻፰) እያለ የእግዚአብሔርን ዙፋን ስለሚሸከሙት አርባዕቱ እንስሳ ተናግሯል፡፡ አገልግሎታቸውም በዙፋኑ ፊት እግዚአብሔርን  ሃያ አራት ሰዓት “ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ” እያሉ ማመስገን ነው፡፡

ከአራቱ ዐበይት ነቢያት መካከል አንዱ የሆነው ነቢዩ ሕዝቅኤል በምርኮ ሳለ ያየውን ራእይ እንዲህ በማለት ይገልጻል፡- “የእግዚአብሔርም እጅ በዚያ በእኔ ላይ ሆነች፣ እኔም አየሁ፣ እነሆም በሰሜን በኩል ዐውሎ ነፋስና ታላቅ ደመና፣ የሚበርቅም እሳት መጣ፣ በዙሪያውም ፀዳል ነበረ፣ በመካከልም በእሳቱ ውስጥ የሚብለጨለጭ ነገር ነበረ፣ ከመካከልም የአራት እንስሶች አምሳያ ወጣ፡፡”(ሕዝ.፩.፫-፭) እንዲል፡፡

ስለ አርባዕቱ እንስሳ ልዕልናቸውና ክብራቸው ከብሉይና ከሐዲስ ብዙ መጻሕፍት መስክረዋል፤ መሐሪና ይቅር ባይ እግዚአብሔርም ስለ ሁሉ የሰው ፍጥረት ይለምኑት ዘንድ ቀራቢዎቹ አደረጋቸው፡፡ ገጸ ሰብእ ስለ ሰው ፍጥረት ይለምናል፣ ገጸ አንበሳ ስለ አራዊት ይለምናል፣ ገጸ ላሕም ስለ እንስሳት ይለምናል፣ ገጸ ንስርም ስለ አዕዋፍ ይለምናል፡፡ ከሠማይ ሠራዊት ሁሉ እነርሱ በእግዚአብሔር ዘንድ በባለሟልነት እጅግ የቀረቡ ናቸውና፡፡

ስለዚህም በዓለሙ ሁሉ በስማቸው አብያተ ክርስቲያን እንዲታነጹ በዚህችም ቀን መታሰቢያቸው እንዲደረግ የቤተ ክርስቲያን መምህራን አዘዙ፣ እነርሱ ስለ ሰው ወገን በእግዚአብሔር ዘንድ ይማልዳሉና፡፡ (ስንክሳር ገጽ 2፻፸9)፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ኪሩቤል አማላጅነት ይማረን፣ በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር፣ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ግቢ ጉባኤያትን ለማጠናከር በጋራ እንሥራ

በእንዳለ ደምስስ

ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልጆቿን በሃይማኖትና በሥነ ምግባር ለማነጽ በምታደርገው ጥረት ውስጥ የእግዚአብሔርን ቃል ማስታጠቅ ዋነኛ ተግባሯ ነው፡፡ ለዚህም ከላይ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት እስከ አጥቢያ ድረስ ባለው መዋቅር ምእመናን ስለ እምነታቸው እንዲረዱ፣ ሕይወቱንም እንዲኖሩት በማድረግ ላለፉት ፳፻ ዓመታት ሐዋርያዊ ተልእኮዋን ስታከናውን ቆይታለች፡፡ በእነዚህ ዘመናት ሁሉ መውደቅ መነሣት ቢያጋጥማትም በክርስቶስ ደም በዐለት ላይ ተመሥርታለችና ፈተናውንና መከራውን ተቋቁማ ዘልቃለች፤ እስከ ዕለተ ምጽአትም ትቀጥላለች፡፡

ወንጌልን መሠረቷ ያደረገችው ቤተ ክርስቲያን የሚገጥሟትን ፈተናዎች ለመቋቋምና አገልግሎቷን ለማስፋፋት ደግሞ የኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች ሚና ከፍተኛውን ድርሻ ይይዛል፡፡ በሃይማኖት የጸኑ፣ በሥነ ምግባር የታነጹ ወጣቶች ለማፍራትም ዘመኑን የዋጀ ትምህርት በየሰንበት ትምህርት ቤቶች ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ ከዚህም አልፎ በሀገር ውስጥና በውጪ የሚገኙ ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ውስጥ የሚማሩ ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች ላይ መሥራት አስፈላጊ በመሆኑ ካለፉት ፳9 ዓመታት ጀምሮ ማኅበረ ቅዱሳን ከቅዱስ ሲኖዶስ በተሰጠው ፈቃድ መሠረት ኃላፊነት ወስዶ መሠረታዊ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በማስተማር ላይ ይገኛል፡፡ በዚህም ከሰባት መቶ ሺሕ በላይ ተማሪዎችን አስተምሮ ለማስመረቅ ችሏል፡፡

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን መንፈሳዊ ትምህርቱን ለመስጠት ጥረት ቢደረግም የሀገራችን የፖለቲካና የመንግሥት መለዋወጥ በዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ውስጥ በሚማሩ ተማሪዎች ላይ ከፍተኛ ያለመረጋገትና ጫና ፈጥሯል፡፡ ከጊዜ ወደ ጊዜ ተማሪዎች በጎሰኝነትና፣ በብሔር በመከፋፈል አንዱ አንዱን ማጥቃት በመበራከቱ የበርካቶች ሕይወት አልፏል፣ እንዲሁም ቆስለዋል፡፡ ለስደትና እንግልት የተዳረጉትም ቁጥራቸው ከፍተኛ ነው፡፡ መደበኛ ትምህርታቸውንም ሆነ መንፈሳዊ ትምህርቱን መከታተል የሚያስችሉ ሁኔታዎች ባለመኖራቸው ብዙዎች ከችግሩ ስፋት አንጻር ወደ ትውልድ ቀዬአቸው ለመመለስ ተገደዋል፡፡

ይህ በዚህ ሁኔታ ውስጥ እያለ ከ፳፻፲2 ዓ.ም አጋማሽ ጀምሮ ዓለምን እያስጨነቀ የሚገኘውና የሰውን ሕይወት እየቀጠፈ ያለው ኮቪድ ፲9 (ኮሮና ቫረስ) በመከሠቱ በመላው ሀገሪቱ የሚገኙ ትምህርት ቤቶች፣ ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ሁሉ ተዘግተው ቆይተዋል፡፡ ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች በኮቪድ ፲9 ሕመም ለተጠቁ ወገኖቻችን ማገገሚያ እንዲሆኑ ተደርጎ ነበር፡፡

በ፳፻፲፫ ዓ.ም መጀመሪያ ግን ትምህርት ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ በማገገሚያ ማእከልነት አገልግሎት ሲሰጡ የነበሩት ተቋማቱ መደበኛ ትምህርት እንዲቀጥል ለማድረግ የዓለም ጤና ድርጅት፣ የኢትያጵያ ጤና ኢንስቲቲዩትና የጤና ሚኒስቴር በሚሰጡት አቅጣጫ መሠረት ዝግጁ የሆኑ ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች የመጨረሻ ዓመት ተማሪዎችን ከመስከረም ፳፭ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም ጀምሮ መቀበል እንደሚችሉ አስታውቋል፡፡

በዚህም መሠረት ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ቅድመ ዝግጅት በማድረግ አንዳንዶቹ ተማሪዎችን ለመቀበል ጥሪ እያደረጉ ይገኛሉ፡፡ ነገር ግን ትኩረት ሊሰጥባቸው የሚገቡና ያለፉት ዓመታት ችግሮች መልሰው እንዳያገረሹ ከቤተ ክርስቲያን፣ ከተማሪዎች፣ ከአስተዳደር አካላትና ከመንግሥት የተቀናጀ ሥራ መሥራት ይጠይቃል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ፡-

ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ጽንፈኛ የፖለቲካ ማእከላት እንዳይሆኑ መሥራት፡-

ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች የተቋቋሙበት የራሳቸው የሆነ ዓላማ አላቸው፡፡ በሥነ ምግባርና በዕወቀት የታነጸ የተማረ የሰው ኃይል ማፍራት፣ በተሰማራበት የሥራ መስክም ብቁና የኅብረተሰቡን ችግር መፍታት የሚችል፣ ሀገር ወዳድና ወደ ተሻለ የዕድገት ጎዳና መምራት የሚችል ትውልድን የመፍጠር ኃላፊነት አለባቸው፡፡

ነገር ግን ዩኒቨርስቲዎች ባለፉት ሁለት ዓመታት በተፈጠሩ አደገኛ የሃይማኖትና የፖለቲካ ጎራዎች ምክንያት ተማሪዎች ጠርዝ የረገጠ ስሜታዊነት ውስጥ ገብተው እኔ ያልኩት ካልሆነ በሚል የረብሻና የግድያ ማእከላት እስከመሆን ደርሰው እንደነበር ይታወቃል፡፡ ዓላማቸውን የሳቱ ግብሮችም ሲፈጸሙባቸው ቆይተዋል፡፡

ስለዚህ የሚመለከታቸው አካላት በቅንጅት በመሥራት ዩኒቨርስቲዎችን ለተቋቋሙለት ዓላማ ብቻ በማዋል ብቁ የተማረ የሰው ኃይል በማፍራት ላይ ትኩረት አድርገው ሊሠሩ ይገባቸዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ተፈጥረው የነበሩ ችግሮችን በመለየት፣ በመወያየት፣ በችግሮቹም ላይ ጥልቅ ጥናቶችን በማድረግ፣ የመፍትሔ ሐሳቦችን በማቅረብና ወደ ተግባር በመለወጥ ተማሪዎችም ከሥጋት ውስጥ በመውጣት ጤናማ የተምሮ ማስተማር ሂደቱ ሊቀጥል ይገባል፡፡

ከብሔርና ጎሰኝነት የጸዱ ማድረግ፡-

ላለፉት በርካታ ዓመታት ከኢትዮጵያዊነት ይልቅ በመንደር፣ በብሔርና ጎሰኝት ላይ ያተኮረ እንቅስቃሴ በሀገሪቱ ላይ ጎልቶ በመታየቱ ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ከዚህ ችግር አላመለጡም፡፡ እርስ በእርስ የእኔ እበልጥ የእኔ እበልጥ ሽኩቻ በርካቶች ተጎድተዋል፣ ሕይወታቸውንም አጥተዋል፣ በብሔር ጥላ ሥር በመከለል ኢትዮጵያዊ አንድነትን ዘንግተዋል፡፡

ለተለያዩ ጽንፈኝነት ላይ ያተኮሩ ማኅበራዊ ሚዲያዎች በመጋለጣቸውም በሚያገኙአቸው የተሳሳቱ አመለካከትን ባዘሉ መረጃዎች በመታለል ከትምህርታቸው ይልቅ ሃይማኖትና ብሔር ተኮር እንቅስቃሴ ውስጥ በመግባት የመማር ማስተማሩን ሂደት እንቅፋት እንዲገጥመው አድርገዋል፡፡

እነዚህ ተቋማት በተለያዩ ክልሎች እንደመገኘታቸው ከሌሎች ክልሎች ለሚመጡ ተማሪዎች ስጋት ሲሆኑም ተስተውሏል፡፡ ክልሎች በብሔርና በቋንቋ ላይ የተመሠረቱ በመሆናቸው ለብሔርና ጎሰኝነት ልዩ ትኩረት በመስጠት የእልቂት መነሻ ማእከላትም ሆነዋል፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን ለግቢ ጉባኤያት ሲሰጥ የነበረው መንፈሳዊ ትምህርትም የብሔርና የቋንቋ፣ እንዲሁም አክራሪ የእምነት ተቋማት በሚፈጥሩት ትንኮሳና ጥቃት ምክንያት ተቋርጦ ቆይቷል፡፡

በዩኒቨርስቲዎች ውስጥ የተፈጠሩትን ችግሮች ለማስወገድ በቅድሚያ ሰላምና መረጋገትን ማስፈን ያስፈልጋል፡፡ ከዚያም ከትምህርት ሚኒስቴር ጀምሮ እስከ ተቋማቱ ድረስ የዘለቀ ውይይት በማድረግ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደቱን ለማስቀጠል ችግር ፈቺ አሠራር መዘርጋት ይገባልና ጊዜ የሚሰጠው ጉዳይ አይደለም፡፡ ዩኒቨርስቲዎች ከብሔርና ጎሳ እንዲሁም ከአከራሪ የሃይማኖት እንቅስቃሴ ወጥተው የዕውቀት መገብያ ማእከላት ሊሆኑ ይገባል፡፡

በሃይማኖታቸው ምክንያት ተማሪዎችን ከማግለልና ከማሳደድ መቆጠብ፡-

ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች በመሆናቸው ብቻ እየተመረጡ የተለያዩ አድሎና ጥቃት ሲፈጸምባቸው የቆየ በመሆኑ በአሁኑ ወቅት ይህ ችግር ድጋሚ አገርሽቶ ወደ ግጭትና ጥቃት እንዳያመራ ሁሉም የበኩሉን በመወጣትና ዩኒቨርሲቲዎችን የሰላምና የአንድነት ተምሳሌት ማድረግ ይጠበቃል፡፡ በተለይም በአንዳንድ ዩኒቨርስቲዎች አስተዳደር አካላት በግልጽና በስውር በኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች ላይ ከሚያደርሱት የማግለልና የጥላቻ ዘመቻ መሰል ጥቃት መታደግ ያስፈልጋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ስለ ልጆቿ መብት ልትከራከርና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር መፍትሔ ልታሰጥ ይገባል፡፡

ለዚህም ተማሪዎች ከተለያዩ አካባቢዎች የተለያዩ ቋንቋዎች፣ ባሕልና ሃይማኖት ይዘው ወደ ዩኒቨርስቲዎች ስለሚገቡ አንዱ በአንዱ ላይ ጫና ከማድረግ ይልቅ ተግባብቶና ተፋቅሮ ሰላማዊ እንቅስቃሴን በማስፈን ዓላማቸውን ማሳካት ያስፈልጋል፡፡ በተለይም የሃይማኖት ነፃነታቸው ተጠብቆ በሥነ ምግባር የታነጹና ውጤታማ እንዲሆኑ ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በጋራ መሥራትን ይጠይቃል፡፡

ተማሪዎችን ከሥነ ልቡናዊ ጫና መታደግ፡-

ባለፉት ዓመታት በሀገራችን በተፈጠረው አለመረጋጋት ከተጎዱ አካላት መካከል የዩኒቨርስቲና የኮሌጆች ተማሪዎች ትልቁን ሥፍራ ይይዛሉ፡፡ ተማሪዎች ከቤተሰቦቻቸው ተለይተው ከዚህ ቀደም ወደማያውቁትና አዲስ አካባቢ ሲሄዱ የሚፈጠረው ጫና ቀላል አይደለም፡፡ አዲስ ጓደኛ፣ አዲስ አካባቢ፣ ውጥረት የበዛበት ትምህርት፣ በዚህ ላይ ደግሞ ሰላምና መረጋጋት በማጣት በሚደርሱ ጥቃቶች የባይተዋርነት ስሜት ስለሚሰማቸው ለሥነ ልቡና ቀውስ ይዳረጋሉ፡፡ ፍርሃትና ሁሉንም የመጠራጠር ስሜት ውስጥ ስለሚገቡ ውጤታማ የመማር ማስተማሩ ሂደት በተጠበቀው መንገድ እንዳይጓዝ እንቅፋት ይሆናል፡፡

ተማሪዎችን ከዚህ የሥነ ልቡና ውጥረትና ጫና ለመታደግ ሰላማዊ አካባቢን መፍጠር፣ ከተማሪዎች ጋር ውይይቶችን ማድረግ፣ በተለይም በባለሙያ የተደገፈ ሥልጠና በመስጠት በራስ መተማመናቸውን ማዳበር ያስፈልጋል፡፡

ከሚመለከታቸው አካላት ምን ይጠበቃል?

ከመንግሥት፡-

መንግሥት ሀገርን በሰላም የማስተዳደርና የመምራት ኃላፊነት አለበት፡፡ ችግሮች ከመከሠታቸው በፊት የመፍትሔ እርምጃ የመውሰድ፣ ችግሮች ከተፈጠሩም በኋላ በፍጥነት ፍትሓዊ የማስተካከያ እርምጃ በመውሰድ እንዳይደገም ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡

በተለይም በየክልሉ የሚገኙ አንዳንድ የፖሊስና የመከላከያ ኃይላት ከሚወስዱት ያልተገባና ተመጣጣኝ ያልሆነ ወንጀለኛንና ንጹሐኑን ሳይለዩ በጅምላ እርምጃ ከመውሰድ መቆጠብ ይገባቸዋል፡፡ ባለፈው ዓመት እነዚህ ችግሮች ጎልተው የታዩ በመሆኑ አሁንም እንዳይቀጥሉ መንግሥት አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡

ከአስተዳደር አካላት፡-

የዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች አመራር አካላት ችግር ፈቺ እንጂ የችግሩ አባባሽ ከመሆንና በእሳት ላይ ነዳጅ ከመጨመር መታቀብ ይጠበቅባቸዋል፡፡ በአንዳንድ ተቋማት የተጣለባቸውን ኃላፊነት በመዘንጋት ተማሪዎችን በጎሳና በብሔር በመከፋፈል ኦርቶዶክስ ጠል የሆኑ አመራሮች በፈጸሙት ችግር በርካታ ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች የችግሩ ሰለባ ሆነዋል፡፡

ተማሪዎች ወደ ዩኒቨርስቲዎች በሚገቡበት ወቅት ባለፉት ዓመታት የተፈጠሩት ችግሮች እንዳያገረሹ ሁሉንም ተማሪዎች በእኩል ዓይን በማየትና ሚዛናዊ አስተዳደር በማስፈን ሰላማዊ የማመር ማስተማር ሂደትን መምራት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ስለዚህ መንግሥት የሚመድባቸውን ኃላፊዎች ማንነት በማጥራት የተሻለ አስተዳደር እንዲሰፍን ተግቶ መሥራት ይጠበቅበታል፡፡

ከወላጆች፡-

ወላጆች ልጆቻቸው የግጭት አካል እንዳይሆኑ የመምከር፣ የመገሠጽና ትክክለኛውን ጎዳና የመምራት ኀላፊነት አለባቸው፡፡ ዓላማቸው ትምህርት ብቻ እንደሆነ በማስረዳት ከሁሉም ጋር በሰላም ተግባብተው በመኖር የሚጠበቅባቸውን እንዲያደርጉ አቅጣጫ ማሳየት ይገባቸዋል፡፡ ልጆች መነሻቸው ቤተሰብ ነውና እግዚአብሔርን የሚፈሩ፣ በሃይማኖታቸው የጸኑ ሆነው እንዲያድጉ ቤተሰብ፣ በተለይም የኦርቶዶክሳውያን ወላጆች ሚና ቀላል የሚባል አይደለም፡፡ ስለዚህ ወላጆች ልጆቻቸውን ወደ ዩኒቨርስቲዎች ከመላካቸው በፊትም ሆነ በኋላ የመምከር፣ የመከታተል ግዴታ አለባቸው፡፡ ከጽንፈኛ አስተሳሰብ በመውጣት ለሥነ ምግባር ትልቅ ትኩረት እንዲሰጡ ማበረታታት፣ ከነፈሰው ጋር እንዳይነፍሱና በስሜታዊነት እንዳይነዱ በመቆጣጠር የድርሻቸውን ሊወጡ ይገባል፡፡

ከማኅበረ ቅዱሳን፡-

ማኅበረ ቅዱሳን ላለፉት ፳9 ዓመታት ኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎችን ሃይማኖታቸውን እንዲያውቁ፣ በሥነ ምግባር ታንጸው ቤተ ክርስቲያንን እንዲያገለግሉ፣ በዕውቀት የበለጸጉ፣ በመንፈሳዊ ሕይወት ያደጉ እንዲሆኑ መንፈሳዊውን ትምህርት እንደሚሰጥ ይታወቃል፡፡ ይህን አገልግሎቱን በቀጣይነት በማጠናከር፣ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመወያየት የመፍትሔ አቅጣጫዎችን በመስጠት የድርሻውን ሊወጣ ያስፈልጋል፡፡

ብቁ መምህራንን በመመደብ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች በሁለት ወገን የተሳለ ሰይፍ ሆነው እንዲወጡ፣ ከወጡም በኋላ ሀገርንና ቤተ ክርስቲያንን በማገልገል ለሌሎች አርአያነታቸውን እንዲያሳዩ በማበረታታት የተሰጠውን ኀላፊነት መወጣት ይገባዋል፡፡

ከተማሪዎች፡-

ተማሪዎች ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም ለምን እንደገቡ መረዳት፣ የገቡበትንም ዓላማ ፈጽመው ሀገርንና ቤተ ክርስቲያንን በተማሩበት የትምህርት መስክ በዕውቀታቸው፣ በጉልበታቸውና በገንዘባቸው በመርዳት ያስተማራቸውን ኅብረተሰብ መልሰው የማገልገል ግዴታ አለባቸው፡፡ ዋነኛ ዓላማቸውም ይህ ብቻ ሊሆን ይገባል፡፡

ከውጪም ከውስጥም ለሚነዙ ውዥንብር ለበዛባቸው መረጃዎች ሳይንበረከኩ ከብሔርና ከጎሣ አደገኛ አስተሳሰብ ራሳቸውን በማግለል ሰላማዊ የተምሮ ማስተማር ሂደቱን ማስቀጠል ይጠበቅባቸዋል፡፡

በአጠቃላይ ተማሪዎች ወደ የኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች መመለሳቸው የማይቀር በመሆኑ ሰላማዊ የትምህርት ማእከላት እንዲሆኑ ከጽንፈኛ አስተሳሰብ በመራቅ፣ በዕውቀትና በሥነ ምግባር የታነጸ የተማረ ትውልድ በመፍጠር ረገድ ከሁሉም ኢትዮጵያውያን ይጠበቃል፡፡ ሁሉም የድርሻውን ከተወጣ ደግሞ ለሀገርና ለወገን የሚቆረቆር፣ ለአንድነትና ለሰላም የሚተጋ ማኅበረሰብ መፍጠር ያስችላልና ሊታሰብበት ይገባል፡፡ ለዚህም የግቢ ጉባኤያት ድርሻ ከፍተኛ ነውና ከዚህ በፊት ከነበረው አገልግሎት በተሻለ ተጠናክሮ መቅርብ ያስፈልጋል፡፡ የግቢ ጉባኤያት መጠናከር ሀገርን በመገንባት ሂደት ውስጥ ትልቅ ድርሻ አለውና በተለይም ቤተ ክርስቲያንና ማኅበረ ቅዱሳን ከሌሎች ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በጋራ መሥራት ይጠበቅባቸዋል፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን ለሀገራችንና ለቤተ ክርስቲያናችን ሰላምንና አንድነቱን ያድልልን፡፡ አሜን፡፡

በወለጋና በቤንሻንጉል በግፍ ለተገደሉ ወገኖቻችን ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

በምዕራብ ወለጋ እና ጉራፈርዳ እንዲሁም በቤንሻንጉል ሰሞኑን በተፈጸመ ጥቃት በርካታ ሰዎች በግፍ መገደላቸውን አስመልክቶ የኢትዮጰያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም መግለጫ ሰጥቷል፡፡ መግለጫውን እንደሚከተለው እናቀርባለን፡፡

 

በአገራችን ኢትዮጵያ በምዕራብ ወለጋ እና በጉራፈርዳ እንዲሁም

በቤንሻንጉል በግፍ የተገደሉ ዜጐች አስመልክቶ

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን

ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

ስለ ዓለማት አፈጣጠር ስለሰው ዘር አመጣጥ ስለ ኃጢአትና የስቃይ ኑሮ አጀማመር እግዚአብሔር ከሰው ዘር ጋር ስለአለው ግንኙነት በሚናገረው በኦሪት ዘፍጥረት መጽሐፍ ምዕራፍ አንድ ቁጥር አንድ ላይ በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይና ምድርን ፈጠረ በዚያን ጊዜ ምድር ባዶ ነበረች ይላል፡፡

ከዚህም ጋር ለሰው ልጆች በእጅጉ አስፈላጊ የሆነውን ብርሃን ብርሃን ይሁን በማለት ብርሃንን ከጨለማ ለየ፡፡ በዚህም መሠረት በብርሃን በሞላው ዓለም ይኖር ዘንድ እግዚአብሔር ሰውን በራሱ መልክና በራሱ አምሳያ ፈጠረው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ሰውን ከፈጠረው በኋላ ብዙ ተባዙ ዘራችሁ ምድርን ይሙላ ምድርም በቁጥጥራችሁ ሥር ትሁን በሚል የሰው ልጆች ምንም ዓይነት መልክ ይኑረን የትኛውንም ቋንቋ እንናገር እግዚአብሔር በፈጠረልን ምድር በየትኛውም አቅጣጫ ተከብረንና ተከባብረን እንድንኖር ምድርንም እንድናለማ እግዚአብሔር ፈጥሮናል፡፡

ማለትም የሰው ልጆች በዚህ ዓለም ላይ ስንኖር እንግዶች እንጂ ከመካከላችን አንድም ባለአገር እንደሌለ ሊኖርም እንደማይችል ከላይ የተገለፀው የእግዚአብሔር ቃል ይነግረናል፡፡

እውነታው ይህ ሁኖ ሳለ የሰው ልጅ በእጅጉ በተሳሳተ አመለካከት ውስጥ በመግባት ይሄ የኛ ያኛው የእናንተ አካባቢ እየተባባልን የመለያየት ሁሉ መሠረት የሆነውን የጠላትን መንፈስና አሠራር በመከተል እርስ በርሳችን በመጠላላት ወንድም ወንድሙን ሲያሳድድ እርስ በርሳችን እየተጠፋፋን እንገናለን፡፡

በቅርቡ ጥቅምት 22 ቀን 2013 ዓ.ም. በኦሮምያ ክልል በምዕራብ ወለጋ እና ጉራፈርዳ እንዲሁም በቤንሻንጉል ምንም ዓይነት የፖለቲካ አመለካከት የሌላቸው ማልደው በመነሳት አምሽተው በመግባት ምድርን ቆፍረውና አርሰው፣ ዘርተውና አጭደው፣ በድካም ኑሮአቸውን የሚገፉ ንፁሐን ዜጐች ሽማግሌዎች፣ ሴቶችና ሕጻናት ጭምር ሳይቀሩ ጅምላ ጥፍጨፋ በማካሄድ ሕይወታቸው እንዲያልፍ መደረጉ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤው በዓመታዊ ስብሰባ ላይ እያለ የሰማው ሲሆን ቅዱስ ሲኖዶሱንና ቤተ ክርስቲያናችንን በእጅጉ ያሳዘነ ኢ-ሰብአዊ ድርጊት በመሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስ እንዲህ ዓይነቱን ድርጊት አውግዟል፡፡

መላው ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችንና የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ከላይ በመግቢያው እንደገለጽነው እግዚአብሔር ሰማይና ምድርን ፈጠረ ሰውንም በራሱ መልክና አምሳያ ፈጠረው እንዳለው ሁሉ የሰው ልጆች በዚህ ዓለም ስንኖር ሁላችን የእግዚአብሔር ፍጥረት መሆናችንን ተገንዝበን ሐሳባችንም ሆነ ተግባራችን እንደ እግዚብሔር ሐሳብ ሆኖ ሁላችን የዚህ ዓለም እንግዶች መሆናችን ተገንዝበን በወንድማማችነትና በፍቅር በአንድነት በመተሳሰብ እግዚአብሔር ፈጥሮ በሰጠን ምድር ላይ በፍቅር ልንኖር ይገባል፡፡

በርግጥ እንደ ሥጋ ለባሽነታችን በተለያየ አካባቢ ተወልደን እንደማደጋችን የተለያየ መልክ ሊኖረን የተለያየ ቋንቋ ልንናገር የተለያየ ባሕልና ሥርዓት ሊኖረን የእኔ የምንለው የራስ አመለካከትም ሊኖረን ይችላል፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ሌላው ከእግዚአብሔር የተሰጠን የፀጋ ስጦታ እንጂ ለመለያየት ምክንያት ሊሆነን አይገባም፡፡

ስለዚህ አላስፈላጊ በሆነ ምክንያት በግፍ ለተገደሉትና ሕይወታቸውን ላጡ ወገኖቻችን በቤተ ክርስቲያናችን ስም ልባዊ ሐዘናችንን እየገለጽን ዳግም እንዲህ ዓይነት ኢ-ሰብአዊ ድርጊት እንዳይፈጸም መንግሥት ለዜጐች አስፈላጊውን ጥበቃ እንዲያደርግ ወንጀለኞችንም ለፍርድ እንዲያቀርብ እያሳሰብን መላው ኢትዮጵያውያን ልጆቻችንም በቀጣይ ለጋራ ሰላምና አንድነት እንድትቆሙ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡ የሞቱ ወገኖቻችንን ነብስ ይማርልን፡፡

 

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፤ ይቀድስ፤

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

አሜን!!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም

ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም.

አዲስ አበባ

በስመ አብ ወወልድ ወንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

ከኢትዮጰያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን

ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

     የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው የመክፈቻው ሥርዓተ ጸሎት ከተፈጸመበት ከጥቅምት 11 ቀን 2013 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ጥቅምት 23 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ የተለመደውን ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባ ሲያካሂድ ሰንብቶ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን የሚበጁ ማኅበራዊና መንፈሳዊ ውሳኔዎችን አሳልፎአል፡፡ በዚሁ መሠረት፡-

  1. ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በቀረበው የጉባኤ መክፈቻ ንግግር የበጀት ዓመቱ የሥራ መመሪያ ሆኖ እንዲያገለግል ምልዓተ ጉባኤው ተቀብሎታል፡፡
  2. ለምልዓተ ጉባኤው ቀርቦ ውይይት የተካሄደበት የ39ኛው አጠቃላይ የሰበካ ጉባኤ የጋራ መግለጫ ጉባኤው ተቀብሎ ያፀደቀው በመሆኑ ለሚመለከታቸው ሁሉ ተላልፎ በሥራ እንዲተረጎም ተወስኗል፡፡
  3. የቤተ ክርስቲያን ወቅታዊ ችግሮች አስመልክቶ በጉባኤው ሰፊ ውይይት የተደረገበት ሲሆን ባለፈው አንድ ዓመት በአገራችን በኢትዮጰያ በቤተ ክርስቲያናችንና በቤተ ክርስቲያን ወገኖቻችን ላይ የደረሰው ግፍና መከራ እንዲቆም በየምክንያት በክርስቲያንነታቸው ምክንያት የታሠሩ ካህናትና ምእመናን ጉዳያቸው እየታየ ከታሠሩበት እንዲፈቱ፣ የመንግሥት የበታች ባለሥልጣናትም ለጥፋተኞች ከሚያደርጉት ድጋፍ እጃቸውን እንዲሰበስቡ ጉባኤው አጥብቆ አሳስቧል፡፡ ከዚሁ ጋር በቤተ ክርስቲያንና በቤተ ክርስቲያን ወገኖቻችን ላይ ላለፈው ለደረሰው ጥፋትና ለወደፊትም የሕግ ክትትል በማድረግ ችግሩን የሚከላከሉ የሕግ ባላሙያዎች ኮሚቴ ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አህጉረ ስብከት ድረስ እንዲቋቋም ተወስኗል፡፡
  4. ወቅታዊ አገራዊ ሰላምን በተመለከተ ጉባኤው በሰፊው ተነጋግሯል፡፡ በአገራችን ያለው ወቅታዊ የሰላም እጦት፣ እየታየ ያለው አለመግባባት ለዜጎች ተረጋግቶ አለመኖርና ከሁከት አልፎ ተርፎ ለሰዎች ሕይወት መጥፋት ምክንያት እየሆነ በመሆኑ በቀጣይም አላስፈላጊ ሁከት ውስጥ እንዳይገባ ከወዲሁ እርቅና ሰላም ማምጣት አስፈላጊ መሆኑን ጉባኤው አምኖበታል፡፡ በመሆኑም የእርቅና የሰላም ሂደቱን የሚያስፈጽሙ ብፀዓን አባቶችን በአስታራቂነት ሰይሟል፡፡
  5. በአገራችን ኢትዮጰያ የሕዝባችን የዘመናት የድህነት የኑሮ ጉስቁልና አስወግዶ ለአገራችንም ብልፅግና ሆነ ለሕዝባችን ዕድገት ከፍተኛ ተስፋ የተጣለበት የታላቁ ሕዳሴ ግድብ አስመልክቶ ጥቅምት 13 ቀን 2013 ዓ.ም የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ አካባቢያዊ ጦርነት እንዲነሣ ያስተላለፉት መልእክት አገራችን ኢትዮጵያን በቅኝ ግዛት ወይም በሞግዚትነት ለማስተዳደር የተደረገ ሙከራ በመሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንኦት ተቃውሞታል፡፡ የዓለምም መንግሥታትና ሕዝቦች እንዲህ ዓይነቱን ትንኮሳና የቅኝ ግዛት ፍላጎት እንዲቃወሙ ጥሪውን አቅርቧል፡፡
  6. በሕግ ቤተ ክርስቲያኑ አንቀጽ 50 የሚገኘው በአሁኑ ጊዜ ባለው የሀገረ ስብከቱ አሠራር ላይ አመቺ ሆኖ ስላልተገኘ ከሕገ ቤተ ክርስቲያኑ እንዲወጣና የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት እንደማንኛውም ሀገረ ስብከት ራሱን ችሎ ሊቀ ጳጳስ ተመድቦለት እንዲመራ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡ ከዚህም ጋር አሁን እየተሠራበት ያለው ሕገ ቤተ ክርስቲያን ከወቅቱ ጋር ተገናዝቦ መሻሻል እንዳለበት ስለታመነ ይኸው እየተሠራበት ያለው ሕግ ቤተ ክርስቲያን መርምረውና አጥንተው መሻሻል የሚገባቸውን ነጥቦች አሻሽለው ወደፊት በቋሚ ሲኖዶስ ከሚመረጡ የሕግ ባለሙያዎች ጋር ሕጉን አሻሽለው ለግንቦቱ ርክበ ካህናት እንዲያቀርቡ ሦስት ብፀዓን አባቶችን ጉባኤው መድቧል፡፡
  7. የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ አፈጽረም አስመልክቶ ቀደም ሲል በቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እየተወሰኑ የተፈጸሙና ያልተፈጸሙትን በመለየት ሊፈጸሙ ያልቻሉበትን ምክንያት ተገልጾ ለፊታችን ግንቦት ርክበ ካህናት ውጤቱ እንዲቀርብ መመሪያ ሰጥቷል፡፡
  8. የብፀዓን አባቶች የሥራ ምደባና ዝውውር በማስፈለጉ ቅዱስ ሲኖዶስ ያለውን ሀኔታ ከመረመረ በኋላ በአገር ውስጥና በአገር ውጭ ዝውውርና የሥራ ምደባም ተካሂዷል፡፡
  9. በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት በቆጋ ኪዳነ ምሕረት ገዳም ተከስቶ የነበረውን የዶግማና የቀኖና ጥሰት አስመልክቶ ችግሩ በአጣሪ ልዑካን እንዲጣራ ተደርጎ በቀረበ ሪፖርት ላይ ጉባኤው ተነጋግሮ ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ውጭ በመንፈስ ቅዱስ ጵጵስና ተሹመናል ያሉት መነኮሳት የፈጸሙት ድርጊት አግባብነት የሌለው ከሕገ ቤተ ክርስቲያን ውጭ ሆኖ ስለተገኘ መነኮሳቱ በራሳቸው የለበሱት ልብሰ ጵጵስናና የጵጵስና ቆብ አውልቀው ንስሓ ተሰጥቷቸው በምነኩስናቸው ብቻ ተወስነው በገዳሙ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን እንዲኖሩ ተወስኗል፡፡ ከዚሁ ጋር ተፈጸመ የተባለው ዳግም ጥምቀትና ክህነት ከቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ውጭ የሆነና ቤተ ክርስቲያናችን የማትቀበለው በመሆኑ ይህንን ድርጊት የፈጸሙ ሁሉ ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ ጉባኤው አሳስቧል፡፡
  10. የኦሮሚያ ቤተ ክህነት አደራጅ ኮሚቴ ነን ከሚሉ አባላት ጋር በተደረገ ውይይት መግባባት ደረጃ ላይ በመደረሱ ክህነታቸው የተያዘ ካህናት ክህነታቸው ተለቆ በቤተ ክርስቲያናችን መዋቅር ውስጥ የሥራ መደብ ተሰጥቷቸው እንዲያገለግሉ ተወስኗል፡፡
  11. የቤተ ክርስቲያኒቱ የ2013 ዓ.ም አጠቃላይ በጀት ላይ የተነጋገረው ምልዓተ ጉባኤ ከበጀትና ሂሳብ መምሪያ በቀረበው የበጀት ድልድል ላይ ተነጋግሮ ማስተካካያዎችን በማድረግ በሥራ ላይ እንዲውል አጽድቋል፡፡

    የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ከላይ በተጠቀሱ ነጥቦች እና እንዲሁም በወቅታዊ አገራዊ ጉዳይ ላይ በስፋት ተነጋግሯል፡፡ በአሁኑ ጊዜ በአገራችን በተለያዩ አካባቢዎች የደረሰው ጎርፍ መጥለቅለቅና የአንበጣ መንጋ በበርካታ ወገኖቻችን ላይ ያደረሰው ችግር ከፍተኛ መሆኑን ጉባኤው ተገንዝቧል፡፡ በመሆኑም ሕብረተሰቡ ለተቸገሩ ወገኖቻችን የተለመደ ድጋፉን ከማድረግ ወደ ኋላ እንዳይል ምልዓተ ጉባኤው ጥሪውን አቅርቧል፡፡

     በአገራችን በኢትዮጵያ በዓለማችንም ጭምር እየታየ ያለው አለመግባባት፣ የጎርፍ መጥለቅለቅ፣ የበሽታ ወረርሽኝ የመሳሰሉት ሁሉ እግዚአብሔር አምላክ በምሕረቱ ተመልክቶ ሰላሙንና አንድነቱን ለዓለማችንና ለሕዝባችን ይሰጥልን ዘንድ ከኅዳር 1-7 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ በመላ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማትና አድባራት ጸሎተ ምሕላ እንዲደረግ ተወስኗል፡፡

በመጨረሻም፡-

    አገራዊ ሰላምና አንድነት አስመልክቶ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በወሰነው መሠረት የእርቅ ሂደቱ የሚቀጥልበት ሆኖ ከዚሁ ጋር የፌደራል መንግሥቱ፣ የየክልል መሪዎች እንዲሁም መላው ኢትዮጵያዊ ሁሉ ለአገራችን አንድነትና ሰላም ለልማቱና ለሕዝባዊ አንድነቱ በጋራ እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን እያቀረበ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ከጥቅምት 11 እስከ 23 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ ለ13 ቀናት ሲያካሂድ የቆየውን ጉባኤ በጸሎት አጠናቋል፡፡

ሰላመ እግዚአብሔር ከሁላችን ጋር ይሁን

እግዚአብሔር አገራችንን ኢትዮጵያንና ሕዝባችንን ይጠብቅ፡፡

ታላቁን የሕዳሴ ግድብ አስመልከቶ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

በአገራችን ኢትዮጵያ የሕዝባችን የዘመናት ድህነትና የኑሮ ጉስቁልና አስወግዶ ለአገራችንም ብልፅግና ሆነ ለሕዝባችን ዕድገት ከፍተኛ ተስፋ የተጣለበት የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ሥራው ተጀምሮ በአሁኑ ጊዜ ከፍተኛ የዕድገት ደረጃ ላይ መድረሱ ከዚያም በላይ ከሦስት ወራት በፊት በግድቡ የመጀመሪያ ሙሌት ተደርጎ ለሕዝባችን የብስራት ድምጽ መሰማቱ ኢትዮጵያውያን በአገር ውስጥም ሆነ ከውጭ ደስታቸውን መግለጻቸው ይታወቃል፡፡

በቀጣይም የግድቡ የዕለት ከዕለት ሥራ እየተከናወነ ሕዝባችንም የተለመደ ድጋፉን እያደረገ ከሦስት ዓመታት በኋላ የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ እንደሚደርስ ተስፋ የተጣለበት መሆኑ ይታወቃል፡፡

ይሁን እንጂ ሕዝባችን በዚህ ተስፋ ውስጥ በገንዘቡንም በጉልበቱም በሙያውም የበኩሉን ድጋፍ እየተረባረበ ባለበት ወቅት ጥቅምት 13 ቀን 2013 ዓ.ም የአሜሪካው ፕሬዝዳንት በአገራችን ጉዳይ ጣልቃ በመግባት ግድባችንን አስመለክቶ አገራትን ወደ ግጭትና አለመግባበት ውስጥ የሚከት የጥፋት መልዕክት ማስተላለፋቸውን ቅዱስ ሲኖዶስ በዓመታዊው ጉባኤው ላይ እንዳለ በሐዘን ተመልክቶታል፡፡

የተወደዳችሁ በአገር ውስጥ ሆነ በውጭው ዓለም የምትገኙ ኢትዮጵያውያን ልጆቻችን እና ሌላውም የዓለምም ሕዝብ

ታሪክ እንደሚያስታውሰን አገራችን ኢትዮጵያ በዘመናት ውስጥ ታፍራና ተከብራ የኖረችውና ለመላው የጥቁር ሕዝብ ምሳሌ የሆነችው አገሪቱ አገረ እግዚአብሔር ሕዝቡ ሕዝበ እግዚአብሔር በመሆኑና በዚህም የሰውና የእግዚአብሔር አንድነት አገራችን በእግዚአብሔር ተጠብቃ የኖረች አገር መሆኗ ነው፡፡

ከዚህም ጋር በዘመናት አገሪቱን እንዲመሩ የተጠሩ መሪዎችና ሕዝቧ በአገራችን ላይ ይነሳሱ የነበሩ ወራሪዎች ያሰቡት ሳይሳካለቸው አገሪቱ ድንበሯ ከነክብሯ ተጠብቆ የኖረችና የሕዝባችን አገራዊ አንድነት ተጠብቆ የኖረ በመሆኑ ነው፣

ዛሬም ቢሆን ከአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕም ሆነ ከሌሎች ተመሳሳይ አካላት በአገራችን ላይ እየተላለፈ ያለው የጥፋት ጥሪ መተዛዘቢያ ከሚሆን በስተቀር አገራችን ጠባቂዋ በሆነው እግዚአብሔርና በሕዝባችን አንድነት ተከብራና ተጠብቃ እንደምትኖር ሙሉ እምነታችን ነው፡፡

የተወደዳችሁ በአገር ውስጥ ሆነ በውጭው ዓለም የምትገኙ ኢትዮጵያውያን ልጆቻችን እና ሌላው የዓለምም ሕዝብ

አገራችን ኢትዮጵያ ከአንድ መቶ ሚሊዮን ያላነሱ ልጆቿ እንደየአካባቢያቸውና እንደ አደጉበት አካባቢ የተለያዩ ቋንቋ እየተናገሩ ባሕላቸውንና ሥርዓታቸውን ጠብቀው በመከባበርና በአንድነት መንፈስ እየተረዳዱ የሚኖሩበት እንግዳ በመቀበልና ቤት ያፈራውን ተካፍሎ በመኖር የሕዝባችን ልዩ መታወቂያው እንደሆነ ይታወቃል፡፡

  • ፍትሐዊ
  • የዓለምም ሕብረተሰብ

አሁንም ከኃያላኑ መሪዎችም ሆነ ሌሎች አገራችንን በሩቅ ሁነው ከሚጎመጇት አካላት እየተጎሰመ ያለው የትፋት ጥሪ ኢትዮጵያን እንደ ትናንት አባቶቻችን በአንድነት በመከባበር በመደማመጥም ጭምር መቆም ከቻልን ከአቅማችን በላይ የሚሆን ነገር እንደሌለ ከእኛ ይልቅ የአገራችንን ዕድገት የማይፈልጉ ከእኛ የበለጠ ይገነዘቡታል፣ ያውቁታልም፡፡

ዓለማችን በአሁኑ ጊዜ በከፍተኛ ደረጃ ያጣችው ነገር ቢሆን ሰላም ነው፡፡ ሰላም እንደሚታወቀው ከአንድ አቅጣጫ ብቻ የሚገኝ ሳይሆን በጋራ ለዓለም ሰላም መቆም ሲቻል ብቻ ነው፡፡

ስለዚህ ይህንን የአገራችን ሰላምም ሆነ ጥቅም ሊያሳጣ በሚችል መልኩ ጥቅምት 13 ቀን 2013 ዓ.ም የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በአገራችን ላይ ያስተላለፉት የጦርነት ጥሪ ቅዱስ ሲኖዶስ አጥብቆ ይቃወማል፡፡ መላውም የዓለም መንግሥታትና ሕብረተሰብ ችግሩን በጥልቀት እንዲገነዘቡት ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፡፡

በአገር ውስጥ ሆነ ከአገር ውጭ የምትገኙ ኢትዮጰያውያን ልጆቻችን እንዲሁም አገር የመምራት ኃላፊነት የተጣለባችሁ የፌደራልና የክልል መሪዎች ከዚህም ጋር በአገሪቱ ውስጥ የምትገኙ ተፎካካሪ ፓርቲዎች በአሁኑ ጊዜ ሁላችንም ኢትዮጵያውያን የትኛውንም የየግልና ቡድን አመለካከታችንን ወደ ጎን በመተው አንድነታችንን ልናጠናክርበት የሚገባ ወቅት መሆኑን በመገንዘብ ኢትዮጵያዊ አንድነታችሁን ከምንጊዜውም የበለጠ ጠብቃችሁ ለአገራችን ሕልውና እንድትቆሙ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፣ ይቀድስ፤

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

አሜን!!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአኵሱም

ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ጥቅምት 16 ቀን 2013 ዓ.ም

አዲስ አበባ

ኦርቶዶክሳዊ የአለባበስ ሥርዓት

ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮዋ የሰው ሕይወትን በመልካም ጎዳና በሥጋም ሆነ በነፍስ የሚመራ ነው፡፡ ትምህርትዋም ፍጹም መንፈሳዊ ነው፡፡ የምታስተምረውም የአምላክዋን ቃል በቀጥታ ሳትቀንስ እና ሳትጨምር ሳታስረዝምና ሳታሳጥር ለሚሰማት ሁሉ ታደርሳለች፡፡ የሥርዓትዋም መነሻ እና መድረሻ ከምድር ሳይሆን ከሰማይ ነው፡፡ “ሥርዓተ ሰማይ ተሠርዐ በምድር” እንዲል:: ይህም ሰማያዊውን ሥርዓት ተከትላ በምድር ያሉ አባላቶቹዋ የሰማዩን ሥርዓት በእምነት በመመልከት በምድር የሚኖሩ ሰማያውያን እንዲሆኑ የምታደርግበት ጥበብ ነው፡፡ የዚህች የሰማይ ደጅ የሆነች የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጅ ነኝ የሚል ሁሉ ሀገሩ በሰማይ እንደሆነ ላፍታም እንኳ ቢሆን ሊዘነጋው አይገባም፡፡ በዚህ ዓለም የሚኖረው እስከተፈቀደለት ዕድሜ ብቻ እንደሆነ ያስተውላልና ራሱን በምታልፍ ዓለም ውስጥ ደብቆና ደልሎ ለማይረባ አስተሳሰብ ተላልፎ አይሰጥም፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ልጆቿ ለዘለዓለም ቅዱሳን መላእክትን መስለው የሚኖሩበትን ሥርዓት በምድር ሠርታ እንዲኖሩት በማድረግ ዜግነታቸው ሰማያዊ እንደሆነ በተግባር እያሳየች ታስተምራቸዋለች፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሠራችውን ሥርዓት ሁሉ ከመጽሐፍ ቅዱስ አንጻር ስንመለከተው በቀጥታ ቃሉን በተግባር ወይም በትርጉም የምንተገብርበት ነው፡፡

በዚህ ርእስም የምንመለከተው ኦርቶዶክሳዊ የአለባበስ ሥርዓት ከመጽሐፍ ቅዱስ ቃል እና ከአዋልድ መጻሕፍት፣ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ አንጻር ምን መምሰል አለበት የሚለውን በተለይም ባለንበት ዘመን ያለው የብዙ ወንዶችና ሴቶች አለባበስ ወዴት እያመራ ነው የሚለውን መነሻ በማድረግ ነው፡፡

ነገርን ከሥሩ ውኃን ከጥሩ እንዲሉ አበው አዳምና ሔዋን ከበደሉ በኋላ አካልን በቅጠል፣ በቆዳ፣በጨርቅ መሸፈን ተጀመረ፡፡ ይህም ቅድስናቸው ንጽሕናቸው እንደልብስ ሆኖላቸው እንዲኖር የተሰጣቸው ሀብት ሆኖ ሳለ ሰውነታቸውን  ከአስተሳሰብ ጀምሮ በተግባር በፈጸሙት በደል ምክንያት ጸጋ መንፈስ ቅዱስ ስለራቃቸው ክብር ስለጎደላቸው ራቁታቸውን መሆናቸው ታወቃቸው፡፡ ስለዚህም አካላቸውን መሸፈን አስፈለጋቸው፡፡

ምክንያቱም በእግዚአብሔር ፊት ለመቆምም ሆነ በሰው ፊት ለመታየት እንደ መላእክት ንጹሕ በመሆን መንፈስ ቅዱስን ጸጋ እግዚአብሔርን መልበስ የግድ አስፈላጊ ስለነበር ነው፡፡ ከውድቀት በኋላ ግን የቀድሞው ንጽሐ ጠባይ ስላደፈብን ገነት ደግሞ ባደፈ በጎሰቆለ ማንነት የማይኖሩባት ሰማያዊት ሀገር ናትና ወደ እዚህ ዓለም ተሰደድን፡፡ በዚህ ዓለም እየኖርን ለሰማያዊት ርስት የምንበቃበትን ሥራ፣በመሥራት የገነት ምሳሌ በሆነች በቤተ ክርስቲያን ስንኖር የአለባበስ ሥርዓት ተሠርቶልናል፡፡ ሥርዓቱም በጾታ ተለይቶ እንደየ ተፈጥሮአችን የወንድ ልብስ፣የሴት ልብስ፣የሕፃናት ልብስ፣ የመነኮሳት ልብስ፣የካህናት እና  የዲያቆናት ልብስ፣የኤጲስ ቆጶሳት  የሊቃነ  ጳጳሳት  ልብስ  ተብሎ  እንደየ  መልኩና አስፈላጊነቱ የመጽሐፍ ቅዱስን ቃል በጠበቀ መልኩ፣ሰማያዊውን ሥርዓት መሠረት ባደረገ መልኩ ቅድስት ቤተ ክርስቲን ሥርዓት ሠርታለች፡፡

አሁን አሁን የምንመለከተውና የምንታዘበው ግን ብዙዎቻችን ከዚህ ሥርዓት ወጣ ብለናል፡፡ ወንዱ የሴቷን፣ሴቷም የወንዱን፣ምእመኑ የካህኑን፣ካህኑም የመነኮሳትን በመልበስ ሥርዓት አልበኝነት በብዙዎቻችን ላይ ይታያል፡፡

በተለይም ደግሞ በከተሞቻችን እጅግ ገዝፎ የሚታየው የሴቷ  እና የወንዱ አለባበስ ቅጥ ያጣ ፍትወተ ሥጋን መሠረት ያደረገ ነው፡፡ ሴት በወንድ ልብስ ስታጌጥ ከማየት የበለጠ የስነ ምግባር ዝቅጠት የለም፡፡ አስቀድሞ እግዚአብሔር ለሙሴ የወንድም ሆነ የሴት የአለባበስ ሥርዓት መጠበቅ እንዳለበት በሕጉ መጽሐፍ አስፍሮታል፡፡

“ሴት የወንድ ልብስ አትልበስ ወንድም የሴት ልብስ አይልበስ ይህን የሚያደርግ በአምላክህ በእግዚአብሔር ዘንድ የተጠላ ነውና”(ዘዳ.፳፪፥፭)፡፡ ሴት የወንድን ልብስ አትልበስ ማለት በራሷ በሴቷ ስም የተሰፋ ሱሪ ትልበስ ማለት አይደለም፡፡ ያማ ከሆነ የመጥበብና የመስፋት አልያም የማነስና የማጠር እንጂ ቅርጹ ያው ሆነ ማለት ነው፡፡ ነገር ግን ተፈጥሮ እንደሚያስተምረን ሱሪ መልበስ ለሴት የተፈቀደ አለመሆኑን ነው፡፡ ሴት ሱሪ አለመልበስ ብቻ ሳይሆን አካሏ ተገላልጦ መታየት ስለ ሌለባት ከልብስ በመራቆትዋ ምክንያት ወንዱ በእርስዋ እንዳይሰነካከል በምኞት ኃጢአት እንዳይወድቅ አካሏን የሚሸፍን ልብስ መልበስ ስለሚገባት ነው፡፡

ተፈጥሮ አያስተምራችሁምን በማለት ቅዱስ ጳውሎስ ያስተማረን ሴቷ ይህንን የአለባበስ ሥርዓት ባለመጠበቅዋ ምክንያት ለሚሰናከልባት ወንድ ሁሉ ተጠያቂ ናት፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የሚነግረን ኃጢአትን ያደረጋት ብቻ ሳይሆን ለኃጢአት ምክንያት የሆነው ሁሉ ከተጠያቂነት አይድንም፡፡

“በእኔ ከሚያምኑ ከእነዚህ ከታናናሾች አንዱን የሚያሰናክል  የወፍጮ ድንጋይ በአንገቱ ታስሮ ወደ ጥልቅ ባሕር ቢሰጥም ይሻለዋል”(ማቴ.፲፰፥፮)፡፡

ለስም አጠራሩ ክብር ምስጋና ይድረሰውና ጌታችን መድኃኒታችን ኢሱስ ክርስቶስ “ከታናናሾቹ አንዱን” ያለው በምግባር ደከም ያሉትን ይባሱኑ በሚያዩት ወይም በሚሰሙት ነገር ተስበው ኃጢአትን እንዲያደርጉ ምክንያት የሚሆን ይፈረድበታል ሲል ነው፡፡

አንዳንድ እኅቶች ሌላውን የሚያሰናክል ልብስ ለምን ትለብሳላችሁ? ሲባሉ እኔን ከተመቸኝ ስለ ሌላው ምን አገባኝ የሚል መልስ መመለሳቸው ያሳዝናል፡፡ እውነት ግን ለነሱስ ቢሆን የአካልን ቅርጽ የሚያሳይ ጥብቅ ያለ ታይት መሰል ለብሶ በአደባባይ መታየቱ፣ባታቸውን እያሳዩ አጭር ጉርድ ለብሰው ብዙዎችን ለኃጢአት መሳባቸው፣ለወንድ የተፈቀደ ሱሪ ለብሰው የሴትነት ወጉን እርግፍ አድረገው መጣላቸው ምን አይነት ስሜት ይሆን የሚሰማቸው? ምቾቱስ ምን ላይ ነው? አጭር ጉርዳቸውን ጨብጠው ዝቅ ለማድረግ የሚገጥሙት ትግልና መሸማቀቅ በሚዲያዎቻችን ሳይቀር የምንታዘበው አይደል፡፡ ቁራጭ ከመሆኑም አልፎ ከስስነቱ የተነሣ የአካል ቅርጽን ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ልብስ ከሰውነታቸው ጣል አድርገው  ነፋስ ሲመጣ ጭራሹኑ ከላያቸው በኖ እንዳይጠፋ ጨብጦ መያዝ፣የአየሩ ሁኔታ በተቀየረ ቁጥር በብርድ መጠበሱ የቱ ላይ ነው ምቾቱ? ወይንስ ደግሞ ሌላውን በማሰናከል የሚያገኙት ደስታ፣ጥቅም አለ ማለት ነው? ከሆነ ይህ ሰይጣናዊ ሥራ ነው ለማለት ያስደፍራል፡፡

እኛ ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ቅዱሳን አባቶቻችን እንዳስተማሩን ከአለባበሳችን ጀምሮ ንግግራችን፣አረማመዳችን፣አኗኗራችን፣አመጋገባችን ሁሉ በጥንቃቄ ሊሆን ይገባል፡፡ “አለባበስህ በጥንቃቄ ይሁን”እንዲል (ሃይ.አበው ዘሠለስቱ ምዕት ፳፩፥፲፪) ጥንቃቄያችንም ለእኔስ እንዲህ አይነት ይፈቀድልኛል? ወይስ አይፈቀድም? ለሌላውስ መሰናክል አልሆንበትም? ብሎ አስቦ በጥንቃቄ መልበስ እንዳለብን ነው አበው ቅዱሳን ያስተማሩን፡፡

አንዳንድ እኅቶችማ በዓለም ጫጫታ ውስጥ የሚለብሱት ቅጥ ያጣ አለባበስ ሳያንሳቸው በሱሪ ተወጣጥረው፣አጫጭር ጉርዶችን ለብሰው ቤተ እግዚአብሔር ሳይቀር ለጸሎት የቆመውን ወጣት ቀልብ በመስረቅ መሰናክልነታቸው ጎልቶ የሚታይ  መሆኑ ሐቅ ነው፡፡ በውኑ ቤተ ክርስቲያን የሥጋ ገበያ የሚሸመትባት፣በምንዝር ጌጥ ራሳችንን አታለን ርካሽ የሆነውን ጠባያችን የምናንጸባርቅባት ናትን? አንድ ክርስቲያን የትም ቦታ ይሁን ምንም አይነት ሁኔታ ውስጥ ይሁን ክርስቲያናዊ ሕይወቱን የሚያስነቅፍ የስንፍና ሥራ ሊሠራ አይገባውም፡፡ ድንገት ተሳስቶ ቢወድቅ እንኳ በንስሓ መነሣት አለበት፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንኳንስ በሕግ የተከለከለውን ሴት የወንድን ወንድም የሴትን ልብስ መልበስ ይቅርና በሕግ የተፈቀደውን መብል መብላት ወንድምንየሚያሰናክል ከሆነ አለመብላትን እንደሚመርጥ አስተምሮናል፡፡ “ነገር ግን በመብል ምክንያት ወንድሜ የሚሰናከል ከሆነ ወንድሜን እንዳላሰናክል ለዘላለም ሥጋ አልበላም(፩ኛቆሮ.፰፥፲፫)

ይህው ሐዋርያ “እስኪ እናንተ ራሳችሁ ፍረዱ ሴት ወደ እግዚአብሔር በምትጸልይበት ጊዜ ልትከናነብ አይገባምን? ተፈጥሮዋስ አያስረዳችሁምን? ወንድ ግን ጠጉሩን ቢያሳድግ ነውር ነው  ለሴት ግን ጠጉርዋን ብታሳድግ ክብርዋ ነው ለሴት ጠጉርዋ እንደ ቀጸላ ሆኖ ተሰጥቶአታልና”(፩ኛቆሮ.፲፩፥፲፫)፡፡

እነዚህንና በዚህ ያልጠቀስናቸውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል መሠረት በማድረግ የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአለባበስ ሥርዓታችን በማያስነቅፍና ለውድቀት ምክንያት በማይሆን ይልቁንም እኛ የእግዚአብሔር ልጆች ነንና በክርስቶስ ደም የከበረ አካላችንን በማያራቁት ሌላውንም  በማያሰናክል  መልኩ  መልበስ  ክርስቲያናዊ  ግዴታችን  መሆኑን  መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ከቀደሙት እናቶቻችንና አባቶቻችን መልካም የሆነውን የአለባበስ ሥርዓት እንውረስ እነርሱ ኢትዮጵያዊነትን ከኦርቶዶክሳዊነት አንጻር አዋሕደው ሀገራዊ እሴታቸውን ጠብቀው ሃይማኖታዊም ግዴታቸውን ተወጥተው ማለፋቸው ሊያስቀናን ይገባልና፡፡

በኢት/ኦ/ተ/ቤተ ክርስቲያን 39ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ መካሔድ ጀመረ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን 39ኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በጸሎተ ወንጌልና በቅዱስ ፓትርያርኩ የመክፈቻ መልእክት ጥቅምት 3 ቀን 2013 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነት በዛሬው ዕለት ተጀምሯል፡፡

በመክፈቻው መርሐ ግብርም ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዮስ እና ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ጀምሮ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት የልዩ ልዩ መምሪያ ኃላፊዎች፣ የአህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳሚዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ባስተላለፉት መልእክትም በአሁኑ ወቅት በቤተ ክርስቲያንና ኦርቶዶክሳውያን ላይ እየደረሰ ያለውን ግፍና መከራ፣ በእጅ አዙር ቤተ ክርስቲያንን ለመከፋፈልና ለማዳከም እየሠሩ የሚገኙ አካላት እንዳሉ በተለይም በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ከቀኖና ውጪ እየተደረገ ያለው ድርጊት ድፍረት የተሞላበት ስሕተት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ አስከፊውን የወጣቶች ስደት፣ የአንበጣ መንጋና ልዩ ልዩ መቅሠፍት እያስከተሉት ያለውን ችግር በተመለከተም በመልእክታቸው ያነሱ ሲሆን ችግሮቹንም ለመፍታት ጥረት መደረግ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡ በሀገራችን እየታዩ ያሉትን አለመግባባቶችም በጠረጴዛ ዙሪያ በውይይት መፍታት እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤው እስከ ጥቅምት 7 ቀን 2013 ዓ.ም ቀጥሎ የሚካሄድ ሲሆን ልዩ ልዩ ጉዳዮች ተነስተው ውይይት እንደሚካሔድባቸውና ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ግብአት የሚሆኑ ነጥቦችን እንደሚያቀርብ ይጠበቃል፡፡

የቅዱስነታቸው መልእክት ሙሉ ቃል እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡-

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

– ብፁዕ አቡነ ያሬድ

የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና 

የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣

– ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና

የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

   – ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፣

   –  የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት የየመመሪያውና የየድርጅቱ ኃላፊዎች፣

   –  የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ልዩ ልዩ ኃላፊዎች፣ የገደማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣

   – በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር ከሚገኙ ልዩ ልዩ አህጉረ ስብከት የመጣችሁ ሥራ  አስኪያጆች፣

በልዩ ልዩ የሥራ ዘርፍ ተወክላችሁ በዚህ ዓመታዊና ዓለም አቀፋዊ ጉባኤ የተገኛችሁ ክቡራንና በአጠቃላይ፤

ሁሉንም ማድረግ የሚችል እግዚአብሔር አምላካችን መከራውንና ፈተናውን አስችሎ በዚህ ታላቅ ጉባኤ ስለሰበሰበን ስሙ የተመሰገነ ይሁን፡፡

‹‹ወይኩን ቅኑተ ሐቈክው ወኅተው መኃትቂክሙ፤ ወገባችሁ የታጠቀ፣ መብራታችሁም የበራ ይሁን፡፡›› (ሉቃ.12፡35)

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህንን ኃይለ ቃል የተናገረውና ያስተማረው ለቅዱሳን ሐዋርያት እንደሆነ ሁላችንም እናውቃለን፡፡ ትምህርቱ ለጊዜው አጠገቡ ለነበሩት ሐዋርያት የተነገረ ቢሆንም ፍጻሜው እስከ ዕለተ ምጽአት ለሚነሡ ደቀ መዛሙርት ሁሉ እንደሆነም እናውቃለን፡፡ ከነሱ ውስጥ በአሁኑ ጊዜ በየደረጃው በኃላፊነት የምንገኝ ደቀ መዛሙርትም ቃሉ በቀጥታ እንደሚመለከተን አንዘነጋውም፡፡

በመሆኑም ከዚህ እውነታ ተነሥተን፣ ጌታችን ‹‹ወገባችሁ የታጠቀ፣ መብራታችሁም የበራ ይሁን›› ሲል እኛን ያዘዘበትና ያስተማረበት ምክንያት ምን ይሆን? የሚለውን ጥያቄ አንሥተን ማየት ከሁላችንም ይጠበቃል፤ ሁላችንም እንደምንገነዘበው የትጥቅ ነገር የሚነሣው ተቃራኒ ኃይል ራስን ወይም ወገንን ለማጥቃት እንደተዘጋጀ ሲታወቅ ነው፤ መብራትን ማብራት የሚያስፈልገው ጨለማ መኖሩ ሲታወቅ ነው፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አፅራር ምንጊዜም የማይተኙ መሆናቸውን በአምላክነቱ ኃይል የሚያውቅ እግዚአብሔር አምላካችን ሁሌ ወገባችንን ታጥቀን መንጋውን እንድንጠብቅ አዞናል፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ብርሃናዊት፣ ሰማያዊትና ዘለላለማዊት ብትሆንም ለጊዜው ያለችው ጠላት በብዛት ባለበትና በጨለማው ዓለም ውስጥ ነውና በጠላት እንዳትጠቃ በጨለማውም እንዳትዋጥ ሁልጊዜ መብራት እንድናበራላት ታዘናል፤ ይህ የእኛ የክርስቲኖች ቀዋሚና መደበኛ ሥራችን ነው፡፡

– ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤

– ክቡራንና ክቡራት የጉባኤው ተሳታፊዎች፤

በአሁኑ ጊዜ በቤተ ክርስቲያኖች ላይ እየደረሰ ካለው መከራ አንጻር ከምንም ጊዜ በላይ ታጥቀን ለቤተ ክርስቲያን ህልውና መቀጠልና ለሕዝበ ክርስቲያኑ የሕይወት ዋስትና መረጋገጥ በአንድነት የምንቆምበት ነው፤

ለሦስት ሺሕ ዘመናት ሀገርን የገነባችና የጠበቀች ሁሉንም በእኩልነት ያስተናገደች በማንም ላይ ግፍን ያልፈጸመች ቤተ ክርስቲያናችን ዛሬ ከገጸ ምድር እናጥፋሽ የሚሉ በምሥራቅም በምዕራብም እየተበራከቱ መጥተዋል፡፡ ከዛሬ ነገ ይሻል ይሆናል፤ ፍትሕም ይገኝ ይሆናል እያልን በተስፋ ብንጠባበቅም ሲሆን አናይም፤ ይልቁንም ከጊዜ ወደ ጊዜ ነገሩ እየተባባሰ፣ ክርስቲያን ልጆቻችንም ለተደጋጋሚ ጥቃት እየተዳረጉ በክርስቲያንነታቸው ብቻ የግፍ ግፍ እየተፈጻመባቸው ይገኛሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በተለያዩ ጊዜያት ባደረገችው ጥሪ ከልዩ ልዩ በጎ አድራጊዎችና ከሕዝብ ክርስቲያኑ ለተጎዱ ምእመናን የተወሰኑ ድጋፍ ለማድረግ ቢሞከርም ከችግሩ ስፋት የተነሣ የሚያረካ አልሆነም፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤

ክቡራንና ክቡራት የጉባኤው ተሳታፊዎች፤

አበው ሲናገሩ ‹‹ከራስ በላይ ነፋስ›› እንደሚሉት ቤተ ክርስቲያናችን እየገጠማት ያለውን ችግር ለመቋቋም ልጆችዋን አስተባብራና አደራጅታ ራስዋን በራስዋ ወደመጠበቅ አማራጭ ካልተሻገረች ዕጣ ፈንታዋ እጅግ አስጊ እየሆነ መጥቶአል፤ ክርስቲያን ልጆቻችን ተሸማቅቀው፣ ነጻነታቸው ተገፎ፣ በሀገራቸውና በወገናቸው መካከል የመኖርና ሃይማኖታቸውን የመከተል መብት አጥተው ባለቡት ሁኔታ ቤተ ክርስቲያንን እየጠበቅን ነው ማለት አይቻልም፡፡

ስለሆነም ሕዝበ ክርስቲያንን የመጠበቅና የማጽናናት ኃላፊነት ከሁሉ በፊት በቅዱስ ሲኖዶስ ጫንቃ ላይ ያረፈ እንደመሆኑ መጠን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ የሚዘንበውን መከራ ለመግታት ቅዱስ ሲኖዶስ በዚህ ጉባኤ ተገቢውን መፍትሔ ማስቀመጥ ይጠበቅበታል፤

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤

ክቡራንና ክቡራት የጉባኤው አባላት፤

‹‹በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ›› እንደሚባለው ሁከት፣ ለዘመናት ታይቶና ተሰምቶ የማይታወቅ የአንበጣ መንጋና ልዩ ልዩ መቅሠፍት በበዛበት በአሁኑ ጊዜ አንድ ላይ ሆነን በመቆም ሕዝበ ክርስቲያኑን በመጠበቅ ፈንታ ሌላ ተቀጥላና የቤተ ክርስቲያንን ዓቅም በመከፋፈል ለማዳከም በውስጣችን የሚደረጉ ሤራዎችም ለቤተ ክርስቲያን አንድነትና ጥንካሬ ከባድ ዕንቅፋቶች እየሆኑ መምጣታቸው ሌላ የጥፋት ገጽታ ሆኖ እየታየ ነው፡፡

እንደ እውነቱ ከሆነ እንደዚህ ያለው ድርጊት ለዘመናት ቤተ ክርስቲያናችንን ሲፈታተኑ የነበሩ የውጭ ኃይሎች በረቀቀ ስልትና በእጅ አዙር ቤተ ክርስቲያናችንን ሊያፈራርሱ የጠነሰሱት ተልእኮ እንጂ ላይ ላዩ አጥባቂ የኦርቶዶክስ ተከታይ መሳይ ውስጡ ግን ኦርቶዶክስን በመከፋፈል ማዳከምና ማፍረስ የሆነ ድርጊት የንጹሐን ኦርቶዶክሳዊያን ተግባር ይሆናል ብለን አናምንም፤ ይህንን ደባ ሁላችንም ልናጤነው ይገባል፡፡

ለዚህ ማሳያ የሚሆነው በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት የተፈጸመው ሕገ ወጥና ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ውጭ የሆነ የኤጲስ ቆጳሳት ሢመት ይገኝበታል፡፡ እንደዚህ ያለ ድርጊት የሁለት ሺሕ ዘመን ሐዋርያዊ ቀኖና እና ሥርዓት ባላት በቤተ ክርስቲያናችን ቀርቶ በየትኛውም ቦታና ጊዜ ተደርጎ የማያውቅ ድፍረትና ስሕተት ነው፡፡ በመሆኑም ለዚህ ድርጊት መነሻ የሆኑት ምክንያቶችና የምክንያቶች ሰለባ የሆኑ፣ እንደዚሁም ሳይላኩና ሥልጣኑ ሳይኖራቸው ዳግም ጥምቀትን ዳግም ክህነትን በማወጅ ለዚህ አደጋ መከሠት ምክንያት የሆኑ ሁሉ በማያዳግም ሁኔታ ይህ ጉባኤ የማስቆሚያ መፍትሔ እንዲያበጅላቸው በዚህ አጋጣሚ አጥብቀን እናሳስባለን፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤

ክቡራንና ክቡራት የጉባኤው ተሳታፊዎች፤

የቤተ ክርስቲያናችን ልጆች ዛሬ በብዙ መልኩ እንግልት ላይ ወድቀው ማየት የተለመደ ሆኗል፤ ብዙ ወጣት ልጆች ለእንጀራ ፍለጋ ሲሉ ሃይማኖታቸው ወደማይወደድበት ሰብአዊ መብታቸው ወደማይከበርበት፣ የንብረትም ሆነ የሕይወት ዋስትና ወደሌለበት ሀገር በመሰደድ የምድር ሲኦል እየለበለባቸው እንደሆነ እያየን ነው፤ ይህንን እየተመለከትን ተኝተን የምናድር ኢትዮጵያውያን ካለን ክርስቲያንነቱም ሰብአዊነቱንም ዘንግተዋል የሚያሰኝ ነው፤ ስለሆነም ልጆቻችን በባዕድ ሀገር ራቁታቸው እንደቅጠል እየረገፉ ከማየት የበለጠ (የከፋ) አንገትን የሚያስደፋ ውርደት ስለሌለ ሀገር አቀፍና ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተቅዋማት፣ የኢፌድሪ መንግሥትና መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚገባውን ሁሉ በማድረግ ልጆች ወደ ሀገራቸውና ወደ ቤተሰቦቻቸው በአስቸኳይ እንዲመለሱ ያደርጉ ዘንድ ቤተ ክርስቲያን ድምጽዋን ከፍ አድርጋ ማሰማት አለባት፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤

ክቡራንና ክቡራት የጉባኤው ተሳታፊዎች፤

የሰው ልጅ በተፈጥሮው ምግብና መጠጥ፣ ልብስና መጠለያ እንደሚሻ ሁሉ ከዚህ ባልተናነሰ ሁኔታ የእኩልነት፣ የመብትና የፍትሕ ፍላጎቱም የላቀ ነው፤ እነዚህ ፍላጎቶቹን ባጣ ጊዜ ያላስፈላጊ ሁከትና ግጭት ይፈጠራሉ፤ በዓለማችንም በሀገራችን የሚታዩ አለመግባባቶች ይብዛም ይነስ ከዚህ የሚመነጩ ከመሆን አያልፍም፤ እነዚህ ነገሮች በተቻለ መጠን ካልተከበሩ ውጤቱ ጥሩ እንደማይሆን እያየን ነው፤ በመሆኑም በሀገራችን ያለው ያልተረጋጋ ሁኔታ ያልሆነ መልክ እንዳይዝ መንግሥታችንና የሀገራችን ተፎካካሪ ፓርቲዎች ወንድማማቾች እንደመሆናቸው መጠን ምንም ልዩነት ሳይኖር በክብ ጠረጴዛ ሆነው በመመካከር ችግሮችን ሁሉ እንዲፈቱ እንጂ ወደ አስፈላጊ ሁኔታ እንዳይገቡ ቤተ ክርስቲያናችን በገለልተኝነትና በእናትነት መንፈስ ማገዝ አለባት፤ ማስታረቅም ማስተማርም አለባት፤ ሁሉም ነገር በሰላምና በውይይት ብቻ እንጂ ከዚህ ባፈነገጠ መልኩ የሚደረግ አማራጭ ከጉዳት በቀር ውጤት አናገኝበትም፤ ከዚህ ጎን ለጎንም ፍትሕና ርትዕ እንዲሰፍን፣ ፍትሕ የተነፈጋቸው ወገኖች ካሉ ፍትሕ እንዲያገኙ ቤተ ክርስቲያን በማእከል ሆና የመምከር ሥራ መሥራት አለባት፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤

ክቡራንና ክቡራት የጉባኤው ተሳታፊዎች፤

ከዚህ በላይ የጠቃቀስናቸው ችግሮች በሀገራችን ሥር እየሰደዱ የመጡበት ምክንያት በርከት ያለ ቢሆንም የድህነት ጉዳይ የአንበሳውን ድርሻ እንደሚወስድ አያጠራጥርም፤ ወጣት ልጆቻችን ሥራና ዳቦ ባጡ ቁጥር ሌላውን አማራጭ በመከተል ሲታክቱ እነሆ በጣም በርካታ የሆኑ ዓመታት ተቈጠሩ፤ ስያሜውና አቀራረቡ ቢለያይም ከሕገ ንጉሣዊ ሥርዓት ማክተም ማግሥት ጀምሮ የተደረጉ እንቅስቃሴዎች ሁሉ ፀረ ድህነት የሚል አንድምታ ይዘው የተደረጉ ናቸው፤ ሆኖም ይቀረፋል የተባለው ድህነት ባላመቀረፉ፣ በዚያም ላይ ሌሎች ነገሮች በመካከሉ እየተሰነቀሩ ጉዞአችንን የኋልዮሽ አድርገውታል፡፡

ስለሆነም ድህነትን በዕድገት በመቀየር ረገድ ቤተ ክርስቲያን በልማቱ፣ በድህነት ማጥፋቱና በሰላም ማረጋገጡ ዙሪያ በርትታ መሥራት ይጠበቅባታል፤ ሰበካ ጉባኤ የተቋቋመውም ሕዝቡ በየአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን በአንዱ ወጥ አደረጃጀት ተሰብስቦ አረጋዊያንን በመጦር፣ ሕፃናትን በማስተማርና በመንከባከብ፣ የራስ አገዝ ልማትን በማስፋፋት፣ ለወጣቱ ትውልድ ሥራ በመፍጠርና የተሟላ መንፈሳዊ አገልግሎት ለመስጠት እንደሆነ ይታወቃል፤ ከዚህ አንጻር ሰበካ ጉባኤ ከተቋቋመበት ዘመን አንሥቶ የተገኘው ዕድገት የማይናቅ ቢሆንም መጓዝ የሚገባውን ያህል እንዳልተጓዘ፣ ያለውም ሀብት በአግባቡ እንዳልተያዘ የአደባባይ ምሥጢር ነው፤ ከዚህም ሌላ ሌሎች ደባል ቡድኖች በየአካባባው ሲፈጠሩ ለቤተ ክርስቲያን አንድነትና ለምጣኔ ሀብት መባከን ያለው አደጋ ሳይጤን በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ፈቃድ እየተሰጠን በየፊናው ያሰማራቸውና ሁሉ በስመ ቤተ ክርስቲያን እየተሰበሰቡና ገንዘብ እየሰበሰቡ በርከት ያለ የምእመናን ሀብት እንደሚባክን መረጃዎች አሉ፤ ይህም የሚከናውነውን በሀገር ውስጥና በውጭ ጭምር ነው፤ ቅዱስ ሲኖዶስና ሕዝበ ክርስቲያኑ ይህንን ድርጊት አርሞና አስተካክሎ መልክ ካላስያዘ በቀር ጉዳቱ የቤተ ክርስቲያንን ምጣኔ ሀብት ብቻ ሳይሆን አንድነትዋንና ህልውናዋንም ጭምር ከባድ አደጋ ላይ የሚጥል ይሆናል፤ በታሪክም ተወቃሽነትን ያስከትላል ስለዚህ እኛ የምንለው አሁንም መፍትሔ እናበጅለት ነው፡፡

በመጨረሻም፤ ይህ ዓመታዊና ዓለም አቀፋዊ የጠቅላላ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ፣ የቀረቡትን ዓበይት ጉዳዮች በጥልቀትና በማስተዋል ተመልክቶ ለወሳኙ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ግብአት የሚሆን የውሳኔ ሐሳብ እንዲያስተላልፍ በማሳሰብ አባታዊ መልእክታችን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ጉባኤያችንን ይባርክልን፤ ይቀድስልን

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ፤ ይቀድስ፤

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ አሜን!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም

ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ጥቅምት 3 ቀን 2013 ዓ.ም

አዲስ አበባ፤ ኢትዮጵያ

 

ሰቆቃወ ድንግል፣ የድንግል ልቅሶ

በእንዳለ ደምስስ

ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፮ ቀን ድረስ ዐርባውን ቀናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልጇን ጌታችን መድኃኒታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ታቅፋ፣ ይረዷት ዘንድ ሰሎሜንና አረጋዊው ዮሴፍን አስከትላ ወደ ግብፅ የተሰደደችበትን፣ የተመለሰችበትን የመከራ ወቅት የምታስብበት ጊዜ ነው፡፡

እመቤታችን ልጇን ይዛ ለምን ተሰደደች ስንል፡- በሄሮድስ ዘመን በይሁዳ ክፍል በቤተልሔም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደ ጊዜ ሰብአ ሰገል ይሰግዱለት ዘንድ ከምሥራቅ ወደ ኢየሩሳሌም በመጡ ጊዜ ንጉሡ ሄሮድስ አግኝቷቸዋል፡፡ “ኮከቡን በምሥራቅ ዐይተን እንሰግድለት ዘንድ መጥተናልና የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው?” ሲሉ ጠየቁ፡፡ ሄሮድስ ይህንን በሰማ ጊዜም እጅግ ደነገጠ፡፡ ሄሮድስ ብቻ አይደለም መላዋ ኢየሩሳሌም መደንገጧን ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ በወንጌሉ ይነግረናል፡፡ ሄሮድስ የካህናት አለቆችንና ጻፎችን ሰብስቦም “ክርስቶስ በየት ይወለዳል?” ሲል ጠይቋቸዋል፡፡ እነርሱም በይሁዳ ክፍል በቤተልሔም እንደሚወለድ በነቢይ እንዲህ ተብሎ ተጽፏልና አሉት፡- “የይሁዳ ምድር አንቺ ቤተልሔም ከይሁዳ አለቆች ከቶ አታንሺም፣ ሕዝቤን እስራኤልን የሚጠብቅ ከአንቺ ይወጣልና” የሚለውን በኢሳይያስ የተነገረውን የትንቢት ቃል ነገሩት፡፡ በዞህም ምክንያት ይገድለው ዘንድ ፈለገ፡፡ ዓመት፣ ዓመት ከመንፈቅ፣ ሁለት ዓመት የሞላቸው ሕፃናትንም አስገደለ፡፡

በዚህ ወቅት ነበር የእግዚአብሔር መልአክ ወደ አረጋዊው ዮሴፍ በሕልም መጥቶ “ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይሻዋልና ተነሣ፣ እናቱንና ሕፃኑን ይዘህ ወደ ግብፅ ሽሽ፣ እስክነግርህም ድረስ በዚያ ኑር” ያለው፡፡ ወደ ምድረ ግብጽም ተሰደዱ፡፡ በዚያም ለሦስት ዓመት ከስድስት ወራት ያህል ረኀብ፣ ጥሙንና እንግልቱን ሁሉ ታግሰው አልፈዋል፡፡ (ማቴ.2.፩-፲፭)፡፡

በዚህም ምክንያት የእመቤታችንን ስደት፣ የደረሰባትን እንግልትና መከራ በማሰብ በረከት ለማግኘት በርካቶች በፍቅር ይጾሙታል፡፡ በቤተ ክርስቲያንም ሊቃውንትና ምእመናን በ፲፬ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተነሡት ኢትዮጵያዊው የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሊቅ አባ ጽጌ ድንግል በደረሱት “ማኅሌተ ጽጌ” በተባለው የምስጋና ክፍል እመቤታችንን ያመሰግኑዋታል፡፡

በዘመነ ጽጌ እመቤታችን የምትመሰገንበት ምስጋና የመጀመሪያው ማኅሌተ ጽጌ ሲሆን ሁለተኛው ሰቆቃወ ድንግል ይባላል፡፡ ሰቆቃወ ድንግል የተጻፈው በግጥም ሲሆን ብዛቱ $፮ ነው፡፡ የእመቤታችንን ሰቆቃና ዋይታ በስፋት ይናገራል፡፡

ሊቁ አባ ጽጌ ድንግል እመቤታችን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይዛ መሰደዷን፣ በስደቷም ያጋጠማት መከራ እጅግ ለመራራ ሐዘን ስለዳረገው ድርሰቱን በቀለም ሳይሆን ዕንባውን እያፈሰሰ መጻፉን “የድንግልን ልቅሶ ታሪክ የምጽፈው በዕንባ ቀለም ነው፣ የሚያነበውም ዕንባና ዕዥ ነው ይበል” ይላል/ሰቆቃወ ድንግል/፡፡
ሰዎች መሪር የሆነ ሐዘን ሲገጥማቸው ከዐይናቸው ውኃ መሳይ ዕንባ ብቻ ሳይሆን ደም የተቀላቀለበት ዕንባ የሚያፈሱበት ወቅት አለ፡፡ ውኃ ከደም ጋር ሲቀላቀል ዕዥ ይሆናል፡፡ እስራኤላዊቷ ራሔል ሁለቱን ልጆቿ ከጭቃው ጋር እርገጫቸው ስትባል ሳትወድ በግድ የማሕፀኗን ክፋዮች ከረገጠቻቸው በኋላ ከዐይኖቿ ዕንባና ደም ተቀላቅለው ፈሰዋል፡፡ ደም የተቀላቀለበት ዕንባዋን ወደ ሰማይ ብትረጨው ከመንበረ ጸባኦት ደርሳል፡፡ “በግብፅ ያለውን ሕዝቤን መከራ በእውነት አየሁ፡- ከአሠሪዎቻቸውም የተነሣ ጩኸታቸውን ሰማሁ፣ ሥቃያቸውንም ዐውቄያለሁ” (ዘፀ.፫.7) እንዲል፡፡

ድንግል ማርያም ሕፃናት እንዲገደሉ የሚለውን አዋጅ ስትሰማ ከልጇ ሞት ይልቅ የእርሷ ሞት እንዲቀድም መመኘቷን ሊቁ እንዲህ ሲል ያስረዳል፡፡ “የልጄ ደሙ ሲፈስ ከምመለከት እኔን አስቀድመው ይግደሉኝ አለች” እያለ የሐዘኗን ጥልቀት ይገልጸዋል፡፡ የሄሮድስ ጭካኔ የተሞላበት አዋጅ ድንግል ማርያምን ከልጇ ሞት ይልቅ የራሷን ሞት እንድትመርጥ አድርጓታል፡፡/ማኅሌተ ጽጌ/

አባ ጽጌ ድንግል በማኅሌተ ጽጌ ድርሰቱ ድንግል ማርያም የተሰማትን ጥልቅ ሐዘን ስለተሰማው እንደ ልብ ወዳጅ በሐዘን ስሜት በድርሰቱ እንዲህ ሲል ይጠይቃል፡፡ “ድንግል ማርያም ወዴት ሄደች? በቤተልሔም ፈልግኋት ግን አላገኘኋትም፣ እናንተ የገሊላ ሰዎች ዐይታችኋት እንደሆነ እጠይቃችኋለሁ ወሬዋን ንገሩኝ፣ ወደሄደችበትም በልቅሶ እከተላት ዘንድ መንገዱን አሳዩኝ” እያለ ድንግል ማርያምን በእግረ ሕሊናው ሊከተላት ይፈልጋል፡፡

ስለ ግብፅ ስደቷና የደረሰባት መከራ ሲገልጽም “ልጅሽን አንድ ጊዜ በጀርባሽ፣ አንድ ጊዜ በጎንሽ ስትይዢ ብዙ ደከምሽ፡፡ በእግሩ ድክድክ እያለ ይሄድና እንድታዝይው ደግሞ ያለቅሳል፣ ከሰሎሜ በቀር የሚያግዝሽ፣ ከዮሴፍ በቀር ስንቅሽን የሚሸከም ረዳት አልነበረሽም” ይላል የግብፁ በረሃ ክብደት፣ የአሸዋው ግለት፣ የፀሐዩ ሙቀትበዓነ ኅሊና እየታየው፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በግብፅ በረሃ ያልደረሰባት ጸዋትወ መከራ የለም፡፡ የውቅያኖስ ውኃ በመዳፉ የያዘውን አምላክ አዝላ ተጠምታለች፡፡ ገበሬ በማያርስበት ምድረ በዳ ከሰማይ መና አውርዶ የመገበውን አምላክ ይዛ ተርባለች፡፡

ጌታችን በዚያን ክፉ ጊዜ እንደ ሰውነቱ በግእዘ ሕፃናት ይጠማ ይራብ እንጂ እንደ አምላክነቱ ደግሞ ድንቅ ተአምራቱንም አድርጓል፡፡ ሊቁም በዘመድ እጦት ምክንያት በሐዘን ትንገላታ የነበረችውን የድንግል ማርያምን መሪር ሐዘን ከገለጠ በኋላ በልጇ ሁሉን ቻይነት ለሐዘኗ መጽናናትን ለጥሟ ቀዝቃዛ ውኃ እንዳዘጋጀላት ይነግረናል፡፡

አባ ጽጌ ድንግል በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን የተከናወነውን ታላቅ መሥዋዕትነት የተከፈለበትን የድንግል ማርያምን ሐዘን፣ ስደትና መከራ ቀጥተኛ ተካፋይ ባይሆንም በመንፈሰ ኅሊና ግን ሰቆቃወ ድንግል ብሎ በደረሰው ድርሰት ሐዘኑን ገልጿል፣ አብሯት እንደነበረ ሁኖ አልቅሷል፣ አብሯት እንደነበረ ሁኖም ተሰዷል፣ በዚህም የመከራዋ ተካፋይ ሆኗል፡፡

ምእመናንም የእመቤታችንን ስደት ለማስታወስ የፈቃድ ጾም በመጾም፣ በቤተ ክርስቲያን ተገኝተው ማሕሌተ ጸጌን ከሊቃውንቱ ጋር በመሆን እየዘመሩ የደረሰባትን መከራና እንግልት ያስባሉ፡፡ በማኅበር በመሆንም ዝክር እየዘከሩ፣ በንስሓ አባቶቻቸው አማካይነት ሌሊቱን ያለ ዕረፍት በያሬዳዊ ዝማሬ ሲያመሰግኑ ያደሩትን ሊቃውንቱንና ካህናቱን በማብላት በማጠጣት የትሩፋት ሥራ ይሠራሉ፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከጽንሰቱ እስከ ዳግም ምጽአቱ ስለሚሠራው ሥራ አስቀድሞ በነቢያቱ አድሮ ትንቢት አናግሯል፡፡ ስለምን ወደ ግብፅ ተሰደደ ስንል በርካታ ምክንያቶችን ማንሳት እንችላለን፡፡ ከእነዚህም ውስጥ፡- ለፍቅሩ ይሳሱለት ስለነበር፣ ኪዳነ መልከ ጼዴቅን ለመፈጸም፣ አጋንንትን ከግብጽና ከሰው ልቡና አስወጥቶ ለመስደድ፣ አዳም ከዚህ ዓለም አፍኣ በምትሆን ከገነት ተሰዶ ነበርና ለመካስ፣ ለሰማዕታት ስደትን ለመባረክ እንደሆነ ቅዱሳት መጻሕፍት ያብራራሉ፡፡ በተጨማሪም ግንቦት ፳፬ ቀን በሚነበበው ስንክሳር “ሔሮድስ ቢያገኘው ሊገድለው እንዳይችል፣ ሌሎች ሰዎች ትስብእቱ ምትሐት ነው ብለው እንዳያስቡ፣ የግብፅ ሰዎች በመካከላቸው በመመላለሱ ጸጋውን እንዲያገኙ፣ ጣዖትንም ቀጥቅጦ ለማጥፋት፡፡ ‘እነሆ እግዚአብሔር በፈጣን ደመና ተቀምጦ ወደ ግብፅ ይወርዳል፣ ጣዖታትም በፊቱ ይወድቃሉ’ ያለው ይፈጸም ዘንድ” የሚሉት በዋናነት ይጠቀሳሉ፡፡

አባ ጽጌ ድንግል በዘመኑ ቢኖር ኖሮ የስደቷና የመከራዋ ተፋካይ ይሆን እንደነበረ በገለጸበት አንቀጹም “እመቤቴ ሆይ በመንገድ ያገኘሽን የቀኑን የፀሐይ ቃጠሎና የሌሊቱን የዱር ቅዝቃዜ ሁሉ ስንቱን እናገራለሁ፡፡ ከዚህ ሁሉ ጋር ሽፍቶች አስቸገሩሽ፣ እኔ ባሪያሽ በእነዚያ ዓመታት ብኖር ከአንቺ ጋር እንድሰደድ በፈለግሁ ነበር፡፡ ሲድህም በድንጋይ የተፈገፈገውን የእጁን አሠር በአፌ በሳምኩት ነበር፣ በማርያም ልጅ ፍቅር ልቤ ቆሰለ” በማለት ፍቅሩን ይገልጻል፡፡/ማኅሌተ ጽጌ/፡፡
በመሆኑም በዚህ በወርኃ ጽጌ የድንግል ማርያምን የስደትና የመከራ ወራት ስናስታውስ ስደተኞችን፣ የሚበሉት፣ የሚጠጡት አጥተው የሚሰቃዩትን፣ ዘመድ ጠያቂ የሌላቸውን በየጸበል ቦታ የወደቁትን በመደገፍ፣ በማብላትና በማጠጣት ሊሆን ይገባል፡፡ ከእመቤታችን ስደት በረከት ይከፍለን ዘንድ የአምላካችን ቅዱስ ፈቃዱ ይሁን፡፡ አሜን፡፡

ምንጭ፡- መጽሐፍ ቅዱስ፣፳፻
ስንክሳር፣ ግንቦት ፳፬፣ ገጽ ፫፻፳፯
ሐመር መጽሔት ጥቅምት ፳፻፲፩ ዓ.ም
ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከጥቅምት ፩-፲፭ ቀን ፳፻፭ ዓ.ም