ለቅዱሳን የተሰጠችን ሃይማኖት ትጋደሉላት ዘንድ እማልዳችኋለሁ” (ይሁ.፩፥፫)

“ለቅዱሳን የተሰጠችን ሃይማኖት ትጋደሉላት ዘንድ እማልዳችኋለሁ” (ይሁ.፩፥፫)

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮዋን በመስበክ፣ የሚደርስባቸውን መከራ ሁሉ ታግሰው እስከ መጨረሻው በመጋደል ያሉትን በማጽናት፣ በእግዚአብሔር ቃል መረብነት አሕዛብንና አረማውያንን ካለማመን ወደ ማመን ይመጡ ዘንድ በማጥመድ ወደ ክርስያኖች ኅብረት የሚያስገቡትን ቅዱሳንን ቀን ሰይማ በዓላቸውን ታከብራለች፡፡ ከእነዚህ ቁጥር ስፍር ከሌላቸው ቅዱሳን ሰማዕታት መካከል ደግሞ የሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስና የሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በዓለ እረፍት ሐምሌ ፭ ቀን በየዓመቱ በዓላቸውን በድምቀት ታከብራለች፡፡ የእነዚህ ቅዱሳን ሰማዕታት ሕይወት ምን ይመስል ነበር? እንዴትስ ተጠሩ? አገልግሎታቸውንና ተጋድሏቸው በተመለከተ ቀጥለን እናቀርባለን፡፡

ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ በገሊላ ባሕር ከወንደሙ እንድርያስ ጋር እንደ ልማዳቸው ዓሣ በማጥመድ ሥራ ላይ ሳሉ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወልጌል መረብነት ሰዎችን ወደ ክርስትና በማምጣት ያጠምዱ ዘንድ በቅድሚያ ቅዱስ ጴጥሮስን ቀጥሎም እንድርያስን ጠርቷቸዋል፡፡ “በገሊላ ባሕር ዳር ሲመላለስም ሁለቱን ወንድማማቾች ጴጥሮስ የተባለ ስምዖንና ወንድሙን እንድርያስን መረባቸውን ወደ ባሕር ሲጥሉ አየ፤ ዓሣ አጥማጆችም ነበሩና፡፡ ጌታችን ኢየሱስም ‘ኑ ተከተሉኝ፤ ሰውን የምታጠምዱ እንድትሆኑ አደርጋችኋለሁ’ አላቸው፡፡ ወዲያውኑ መረባቸውን ትተው ተከተሉት” እንዲል (ማቴ. ፬፥፲፰-፳)

የሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አመራረጥ ደግሞ በተአምራት ነው፡፡ ጳውሎስ የተባለው ሳውል ለአይሁድ እምነት ታማኝና ይህንንም የሚቃወሙትን በማሳደድ የሚታወቅ የክርስትና ጠላት የነበረ ሰው ነው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ከድቅድቅ የኃጢአት ባሕር ውስጥ ሰዎችን ማውጣት ይቻለዋልና ሳውል ክርስቲያኖችን ይገድል፣ ያሳድድ ዘንድ በተሰማራበት ጠራው፡፡ “ሳውል ግን ገና አብያተ ቤተ ክርስቲያናትን ይቃወም ነበር፡፡ የሰውንም ቤት ሁሉ ይበረብር ነበር፤ ወንዶችና ሴቶችንም እየጎተተ ወደ ወኅኒ ቤት ያስገባቸው ነበር” በማለት እንደተገለጸው (ሐዋ. ፰፥፫) በዚህ ብቻ ሳይበቃው ሐዋርያትንም ያሳድድና ይገድል ዘንድ ከሊቀ ካህናቱ ዘንድ የፈቃድ ደብዳቤ ይሰጠው ዘንድ እስከመጠየቅ የደረሰ አሳዳጅ ነበር፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ ይህንን ሲገልጽ “ሳውል ግን የጌታን ደቀ መዛሙርት ለመግደል ገና እየዛተ ወደ ሊቀ ካህናቱ ሄደ፡፡ ምን አልባት በመንገድ የሚያገኘው ሰው ቢኖር ወንዶችንም ሴቶችንም እያሰረ ወደ ኢየሩሳሌም ያመጣቸው ዘንድ በደማስቆ ላሉት ምኩራቦች የሥልጣን ደብዳቤ ከሊቀ ካህናቱ ለመነ፡፡” (ሐዋ. ፱፥፩-፪)

ሳውል ለሃይማኖቱ ቀናተኛ ነውና የሚሠራው ሁሉ ከእግዚአብሔር የሚለይ የኃጢአት ሥራ መሆኑን አልተረዳም፡፡ ቀዳሜ ሰማዕት ቅዱስ እስጢፋኖስ በአይሁድ እጅ ሲወገር የገዳዮቹንም ልብስ ጠባቂ የነበረ አሳዳጅ ነበር፡፡ (የሐዋ. ፯፥፶፰-፷) ክርስቲያኖችን እያሳደደ መግደል፣ በወኅኒ ማጎር የዘወትር ሥራው አድርጓልና በዚህም ይደሰት ነበር፡፡ ነገር ግን ወደ ደማስቆ ሲሄድ ድንገት መብረቅ ከሰማይ ብልጭ አለበት፡፡ መቋቋም አልቻለምና በምድር ላይ ወደቀ፡፡ ወዲያውም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ?” የሚለውን ቃል ሰማ፡፡ ሳውልም የሰማውን ድምጽ መቋቋም እየተሳነው በወደቀበት ሆኖ እየተንቀጠቀጠ “አንተ ማነህ?” ሲል ጠየቀ፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም “አንተ የምታሳድደኝ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ፤ በሾተል ብረት ላይ ብትቆም ለአንተ ይብስብሃል” አለው፡፡ ሳውልም ምን እንዲያደርግ እንደሚፈልግ ጌታችንን በጠየቀው ጊዜ ወደ ከተማ እንዲገባና ሊያደርገው የሚገባውን በከተማው እንደሚነግሩት አስረዳው፡፡ ነገር ግን ሳውል ከወደቀበት ሲነሣ ዓይኖቹ ታውረው ስለነበር ማየት አልቻለም፡፡ እየመሩም ወደ ደማስቆ ወሰዱት ሳይበላና ሳይጠጣ ለሦስት ቀናት ቆየ፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐናንያ ለተባለው ደቀ መዝሙር ተገልጦም ሳውልን ይፈውሰው ዘንድ ላከው፡፡ ሐናንያ የሳውልን ኃጢአት አንድ በአንድ እየዘረዘረ ከጌታችን ጋር ተከራክሯል፤ ነገር ግን ጌታችን ”ተነሥና ሂድ በአሕዛብና በነገሥታት በእስራኤልም ልጆች ፊት ስሜን ይሸከም ዘንድ ለእኔ የተመረጠ ዕቃ አድርጌዋለሁና፡፡ እኔም ስለ ስሜ መከራን ይቀበል ዘንድ እንዳለው አሳየዋለሁ” በማለት ነገረው፡፡ ሐናንያም ወደ ሳውል ሄዶ እጁን ጫነበት፤ ፈጥኖም ከዓይኖቹ እንደ ቅርፊት ያለ ነገር ወደቀ፤ ዐይኖቹም አዩ፤ ወዲያውም ተጠመቀ፡፡ ለሳምንታት በዚያ ከቆየም በኋላ በምኩራቦች እየተገኘ የጌታችን መድኃኒታችንን አምላክነት እየሰበከ ዞረ፡፡ አይሁድም ሳውልን ይገድሉት ዘንድ ተማከሩ፡፡ (ሐዋ.፱፥፩-፴፩)

ቅዱስ ጳውሎስም “የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ስላሳደድሁ ሐዋርያ ተብዬ ልጠራ አይገባኝም” በማለት ራሱን በትኅትና ዝቅ በማድረግ ለወንጌል ታማኝ ሆኖ እስከ ሕይወቱ ፍጻሜ በተጋድሎ ኖሯል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ፲፬ መልእክታትን፣ ቅዱስ ጴጥሮስ ደግፖ ሁለት መልእክታትን በመጻፍም ብዙዎችን ከጣዖት አምልኮ፣ ከአሕዛብነትና ከአረማዊነት መልሶ ሐምሌ ፭ ቀን በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡
ቅዱስ ጴጥሮስ የዮና ልጅ ስምዖን ተብሎ ይጠራ ነበር፡፡ (ዮሐ.፳፩፥፲፭) ነገር ግን ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን “እናንተስ ማን ትሉታላችሁ” ብሎ ሲጠይቃቸው ሐዋርያው ተነሣና፡- “አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ” ብሎ መለሰለት፡፡ ያን ጊዜም ጌታችን “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ በሰማያት ያለው አባቴ እንጂ ሥጋና ደም ይህን አልገለጠልህምና ብፁዕ ነህ፡፡ እኔም እልሃለሁ፥ አንተ ጴጥሮስ ነህ፥ በዚችም አለት ላይ ቤተ ክርስቲያኔን እሠራለሁ፥ የገሃነም ደጆችም አይችሏትም” በማለት ጴጥሮስ ብሎ ሰየመው፡፡ (ማቴ.፲፮፥፲፯—፲፰)
ጳውሎስን ደግሞ ጌታችን ለመጀመሪያ ጊዜ ሲጠራው በመጀመሪያ ስሙ ሳውል ብሎ ጠራው፤ በምስክርነቱ ጊዜ ደግሞ “ጳውሎስ ሆይ፥ በኢየሩሳሌም ስለ እኔ እንደ መሰከርህ እንዲሁ በሮሜም ትመሰክርልኝ ዘንድ ይገባሃልና፥ አይዞህ አለው፡፡” (የሐዋ.፳፫፥፲፩)
የቅዱስ ጴጥሮስ አገልግሎቱ በአብዛኛው ሕግ ለተጻፈላቸው፣ ነቢያት ለተላኩላቸው፣ መሥዋዕት ለሚያቀርቡ፣ ግርዛት ለተሰጣቸው ለአይሁድ ነበር፡፡ በአንጻሩ ደግሞ የቅዱስ ጳውሎስ አገልግሎት የነበረው በአሕዛብ መካከል ነበር፡፡
በአገልግሎታቸውም ድንቅ ተአምራትን ፈጽመዋል፡፡ ለምሳሌ ስለ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ተብሎ ተጽፏል፡፡ “እግዚአብሔርም በጳውሎስ እጅ የሚያስገርም ተአምራት ያደርግ ነበር፤ ስለዚህም ከአካሉ ጨርቅ ወይም ልብስ ወደ ድውዮች ይወስዱ ነበር፥ ደዌያቸውም ይለቃቸው ነበር ክፉዎች መናፍስትም ይወጡ ነበር፡፡” (የሐዋ.፲፱፥፲፩-፲፪) በኢዮጴም ጣቢታ የምትባል አገልጋይን ከሞተች፤ አጥበውም በሰገነት ከአኖሯት በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ ካለበት ተጠርቶ ከጸለየ በኋላ ጣቢታ ሆይ ተነሽ ሲላት ዐይኖቿን እንደከፈተች ተጽፏል፡፡ (የሐዋ.፱፥፴፮—፵፪) በተመሳሳይ ቅዱስ ጳውሎስ አውጤኪስ የሚባል ከሦስተኛ ደርብ ወደ ታች ወድቆ የሞተን ጎልማሳ እንዲነሣ አድርጓል፡፡ (የሐዋ.፳፥፯—፲፪)
ሁለቱም ቅዱሳን ሐዋርያት በሮማው ቄሳር ኔሮን ዘመን ፷፯ ዓ.ም. ሰማዕትነትን ተቀብለዋል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ቁልቁል ተሰቅሎ ሰማዕትነት የተቀበለ ሲሆን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ አንገቱን ተቀልቶ ሰማዕትነትን ተቀብሏል፡፡
በረከታቸው ይደርብን፡፡

“እመን እንጂ ተጠራጣሪ አትሁን” (ዮሐ. ፳፥፳፮-፳፱)

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሞቱ ሞትን ሽሮ በትንሣኤው ትንሣኤአችንን ካወጀልን በኋላ በሳምንቱ ሐዋርያት በዝግ ቤት ውስጥ ሆነው ሳሉ መግነዝ ፍቱልኝ መቃብር ክፈቱልኝ ሳይል እንደ ተነሣ እንዲሁ በር ክፍቱልኝ ሳይል በዝግ ቤት ውስጥ ሳሉ በመካከላቸው ተገኝቷል፡፡ ይህንንም ቀን ቅድስት ቤተ ክርስቲያችን “ዳግም ትንሣኤ” በማለት በድምቀት ታከብረዋለች፡፡ ዳግም ትንሣኤ የተባለበት ምክንያትም በአከባበር፥ በሥርዓት የመጀመሪያውን ትንሣኤ ስለሚመስል ነው፡፡ የትንሣኤ ዕለት የሚባለው ቃለ እግዚአብሔር ሳይለወጥ፤ በሙሉ በዚህ ቀን ይደገማል፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በትንሣኤው ዕለት ማታ በዝግ በር ገብቶ፣ በቅዱሳን ሐዋርያት መካከል ተገኝቶ “ሰላም ለሁላችሁ ይሁን!” በማለት ትንሣኤውን ሲገልጽላቸው ሐዋርያው ቶማስ አልተገኘም ነበር፡፡ በኋላ ከሔደበት ሲመጣ ጌታችን እንደ ተነሣ እና እንደ ተገለጸላቸው ሐዋርያት “ጌታችን አየነው” በማለት በደስታ ሲነግሩት እርሱ ግን “የችካሩን ምልክት ካላየሁ፣ ጣቴንም ወደ ተቸነከረበት ካልጨመርሁ፣ እጄንም ወደ ጎኑ ካላስገባሁ አላምንም” አላቸው፡፡ ቶማስ ትንሣኤ ሙታንን ከማያምኑ ከሰዱቃውያን ወገን በመሆኑ ለጥርጥር እንደዳረገው ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ ዲዲሞስ የተባለው ቶማስ በዚህ ብቻ አላበቃም፡፡  “በኋላ እናንተ ‘አየን’ ብላችሁ ልትመሰክሩ፤ ልታስተምሩ፤ እኔ ግን ‘ሰምቼአለሁ’ ብዬ  

ልመሰክር፤ ላስተምር? አይሆንም፡፡ እኔም ካላየሁ አላምንም” አለ፡፡ (ዮሐ. ፳፥፳፬-፳፮)

ቸርነቱ ወሰን የሌለው የባሕርይ አምላክ መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ የሐዋርያው ቶማስን ጥርጥር ለማስወገድ ልክ እንደ መጀመሪያው ትንሣኤ ዕለት አበው ሐዋርያት (ሐዋርያው ቶማስ ባለበት) በተዘጋ ቤት በአንድነት ተሰባስበው እንዳሉ በሩን ሳይከፍት ገብቶ “ሰላም ለሁላችሁ ይሁን!”

በማለት በመካከላቸው ቆመ፡፡ ቶማስንም “ጣትህን ወዲህ አምጣ እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣ ወደ ጎኔ አግባ፤ እመን እንጂ ተጠራጣሪ አትሁን” ብሎ አሳየው፡፡ ቶማስም ጣቱን ወደ ተቸነከሩት እጆቹ፣ እጁንም ወደ ተወጋው ጎኑ ሲጨምር እርር ኩምትር አሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ምልክቱን በማየቱ፣ በመዳሰሱ ትንሣኤውንና አምላክነቱን እንደ ፍላጎቱ በመረዳቱ “ጌታዬ አምላኬም” ብሎ አመነ፡፡ በዚህም ምክንያት የሳምንቱ ዕለተ ሰንበት የትንሣኤው ምሥጢር ለሁለተኛ ጊዜ ለሐዋርያት የተገለጠበት ዕለት በመሆኑ “ዳግም ትንሣኤ” ተብሎ ይጠራል፡፡ (ዮሐ. ፳፥፳፬-፴)፡፡  

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ትንሣኤ ክርስቶስ በሊቃውንት

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

የጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ የድኅነታችን ብሥራት በመኾኑ ለአምሳ ቀናት ያህል በቤተ ክርስቲያን በቅዳሴው፣ በማኅሌቱ፣ በወንጌሉ ወዘተ. ይዘከራል፡፡ በዚህ ሰሙን ‹‹ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን …›› እየተባለ ሞት መደምሰሱ፣ ነጻነት መመለሱ ያታወጃል፡፡ በየጊዜያቱና በየዘመናቱ የተነሡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንም ስለ ክርስቶስ ትንሣኤ ከዚህ ቀጥሎ የተገለጠውን ትምህርትና ምስክርነት ሰጥተዋል፤

‹‹ከሙታን ተለይቶ ተነሥቶ ሲኦልን ረግጦ፣ በሞቱ ሞትን አጠፋው፤ በሦስተኛው ቀንም ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላአባት ሆይ፤ አመሰግንሃለሁብሎ ሥግው ቃል አመሰገነ፤›› (እልመስጦአግያ ዘሐዋርያት ፭፥፩)፡፡

‹‹እንደ ሞተ እንዲሁ ተነሣ፤ ሙታንንም አስነሣ፡፡ እንደ ተነሣም እንዲሁ ሕያው ነው፤ አዳኝ ነው፡፡ በዚህ ዓለም እንደ ዘበቱበት፣ እንደ ሰደቡት፣ እንዲሁ በሰማይ ያሉ ዅሉ ያከብሩታል፤ ያመሰግኑታል፡፡ ለሥጋ በሚስማማ ሕማም ተሰቀለ፤ በእግዚአብሔርነቱ ኃይል ተነሣ፤ ይኸውም መለኮቱ ነው፡፡ ወደ ሲኦል ወርዶ ነፍሳትን ማረከ፤›› (ቅዱስ ሄሬኔዎስ፣ ሃይ. አበ. ፯፥፳፰፴፩)፡፡

‹‹እንዲህ ሰው ኾኖም ሰውን ፈጽሞ ያድን ዘንድ ታመመ፤ ሞተ፤ ተቀበረ፡፡ በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፤›› (ሠለስቱ ምዕት፣ ሃይ. አበ. ፲፱፥፳፬)፡፡

‹‹ሞትን ያጠፋው፣ ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱ የሞት ሥልጣን የነበረው ዲያብሎስን የሻረው እርሱ ነው፡፡ ሰው የኾነ፣ በሰው ባሕርይ የተገለጠ አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሔር ያደረበት ዕሩቅ ብእሲ አይደለም፤ ሰው የኾነ አምላክ ነው እንጂ፡፡ ፈጽሞ ለዘለዓለሙ በእውነት ምስጋና ይገባዋል፤›› (ቅዱስ አትናቴዎስ፣ ሃይ. አበ. ፳፭፥፵)፡፡

‹‹ሥጋው በመቃብር ያሉ ሙታንን አስነሣ፤ ነፍሱም በሲኦል ተግዘው የነበሩ ነፍሳትን ፈታች፡፡ በዚያም ሰዓት የጌታችን ሥጋው በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ሳለ መቃብራት ተከፈቱ፤ ገሃነምን የሚጠብቁ አጋንንትም ባዩት ጊዜ ሸሹ፡፡ የመዳብ ደጆች ተሰበሩ (ሊቃነ አጋንንት፣ ሠራዊተ አጋንንት ድል ተነሡ)፡፡ የብረት ቁልፎቿም ተቀጠቀጡ (ፍዳ፣ መርገም ጠፋ)፡፡ ቅድስት ነፍሱ በሲኦል ተግዘው የነበሩ የጻድቃን ነፍሳትን ፈታች፤›› (ዝኒ ከማሁ ፳፮፥፳-፳፩)፡፡

‹‹ሥጋ ከመለኮቱ ሳይለይ በመቃብር አደረ፤ ነፍሱም ከመለኮት ሳትለይ በገሃነም ተግዘው ለነበሩ ነፍሳት ደኅነትን ታበስር ዘንድ፣ ነጻም ታደርጋቸው ዘንድ ወደ ሲኦል ወረደች፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ እንደ ተናገረው ቃል ዐፅም፣ ሥጋ ወደ መኾን ፈጽሞ እንደ ተለወጠ የሚናገሩ የመናፍቃንን የአእምሮአቸውን ጉድለት ፈጽመን በዚህ ዐወቅን፡፡ ይህስ እውነት ከኾነ ሥጋ በመቃብር ባልተቀበረም ነበር፡፡ በሲኦል ላሉ ነፍሳት ነጻነትን ያበስር ዘንድ ወደ ሲኦል በወረደ ነበር እንጂ፡፡ ነገር ግን ከነፍስና ከሥጋ ጋር የተዋሐደ ቃል ነው፡፡ እርሱ የሥጋ ሕይወት በምትኾን በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ ለነፍሳት ነጻነትን ሰበከ፡፡ ሥጋ ግን በበፍታ እየገነዙት በጎልጎታ በዮሴፍ በኒቆዲሞስ ዘንድ ነበረ፤ ቅዱስ ወንጌል እንደ ተናገረ፡፡ አባቶቻችን ሥጋ በባሕርዩ ቃል አይደለም፤ ቃል የነሣውሥጋ ነው እንጂ ብለው አስተማሩን፤ ይህንን ሥጋም ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ ቶማስ ዳሠሠው፤ በሥጋው ሲቸነከር ቃል ታግሦ የተቀበለውን የችንካሩን እትራትም (ምልክት) በእርሱ አየ፤›› (ዝኒ ከማሁ ፴፥፴፩-፴፮)፡፡

‹‹አሁን እግዚአብሔር ሞተ ሲል ብትሰማ አትፍራ፤የማይሞተውን ሞተ ሊሉ አይገባምከሚሉ፤ ዕውቀት ከሌላቸው፤ ሕማሙን፣ ሞቱን ከሚክዱ መናፍቃን የተነሣ አትደንግጥ፡፡ እኛ ግን በመለኮቱ ሞት እንደ ሌለበት፤ በሥጋ ቢሞትም በመለኮቱ ሥልጣን እንደ ተነሣ እናውቃለን፡፡ ሞት የሌለበት ባይኾንስ ኖሮ በሥጋ በሞተ ጊዜ ሥጋውን ባላስነሣም ነበር፤ ሥጋው እስከ ዓለም ፍጻሜ በመቃብር በኖረ ነበር እንጂ፤›› (ቅዱስ ባስልዮስ፣ ሃይ. አበ. ፴፬፥፲፯-፲፰)፡፡

‹‹ከመስቀሉ ወደ ሲኦል በመውረዱ አዳነን፤ በአባታቸው በአዳም በደል በሲኦል ተግዘው የነበሩ ጻድቃንን ፈታ፤ ከሙታን ተለይቶ አስቀድሞ በተነሣ በእውነተኛ ትንሣኤውም አስነሣን፡፡ የንስሐንም በር ከፈተልን፤›› (ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ፣ ሃይ. አበ. ፴፮፥፴)፡፡

‹‹በአባታችን በአዳም በደል የተዘጋ የገነት ደጅን የከፈተልን፤ ዕፀ ሕይወትን የሚጠብቅ ኪሩብንም ያስወገደው፤ የእሳት ጦርን ከእጁ ያራቀ፤ ወደ ዕፀ ሕይወት ያደረሰን እርሱ ነው፡፡ ፍሬውንም (ሥጋውን፣ ደሙን) ተቀበልን፡፡ አባታችን አዳም ሊደርስበት ወዳልተቻለው፤ በራሱ ስሕተት ተከልክሎበት ወደ ነበረው መዓርግ ደረስን፡፡ ክፉውንና በጎውን ከሚያስታውቅ፤ ወደ ጥፋት ከሚወስድ፤ በአዳምና በልጆቹም ላይ ኃጢአት ከመጣበት ከዕፀ በለስ ፊታችንን መለስን፤›› (ዝኒ ከማሁ ፴፮፥፴፰-፴፱)፡፡

‹‹የሕይወታችን መገኛ የሚኾን የክርስቶስ ሞት የእኛን ሞት ወደ ትንሣኤ እንደ ለወጠ እናምናለን፤ ክርስቶስም ሞትን አጥፍቶ የማታልፍ ትንሣኤን ገለጠ፤ እንደ ተጻፈ፡፡ ከሰው ወገን ማንም ማን ሞትን ያጠፋ ዘንድ፣ ትንሣኤንም ይገልጣት ዘንድ አይችልም፤ ዳዊትበሕያውነት የሚኖር፤ ሞትንም የማያያት ሰው ማነው? ነፍሱን ከሲኦል፤ ሥጋውን ከመቃብር የሚያድን ማን ነው?› ብሎ እንደ ተናገረ፤›› (ቅዱስ አቡሊዲስ፣ ሃይ. አበ. ፵፪፥፮-፯)፡፡

‹‹በመለኮትህ ሕማም፣ ሞት የሌለብህ አንተ ነህ፡፡ በሥጋ መከራ የተቀበልህ አንተ ነህ፡፡ ከአብ ጋር አንድ እንደ መኾንህ ሞት የሌለብህ አንተ ነህ፡፡ ከእኛም ጋር አንድ እንደ መኾንህ በፈቃድህ የሞትህ አንተ ነህ፡፡ በመቃብር ያደርህ አንተ ነህ፡፡ በኪሩቤል ላይ ያለህ አንተ ነህ፡፡ ከሙታን ጋር በመቃብር የነበርህ አንተ ነህ፡፡ በአንተ ሕማምና ሞትም ድኅነት ተሰጠ፤ ከሙታን ጋር የተቆጠርህ አንተ ነህ፤ ለሙታንም ትንሣኤን የምትሰጥ አንተ ነህ፡፡ ሦስት መዓልት፤ ሦስት ሌሊት በመቃብር ያደርህ አንተ ነህ፤ በዘመኑ ዅሉ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የምትኖር አንተ ነህ፤ በመለኮት ሕማም ሳይኖርብህ በሥጋ የታመምክ አካላዊ እግዚአብሔር ቃል አንተ ነህ፤›› (ቅዱስ ኤራቅሊስ፣ ሃይ. አበ. ፵፰፥፲፪-፲፫)፡፡

‹‹እኛስ ኃጢአታችንን ለማስተሥረይ በሥጋ እንደ ታመመ፤ እንደ ሞተ፤ ከነፍሱም በተለየ ጊዜ ሥጋውን እንደ ገነዙ፤ ከሙታንም ተለይቶ በእውነት እንደ ተነሣ፤ ከተነሣም በኋላ በእውነት ወደ ሰማይም እንደ ዐረገ እናምናለን፡፡ በኋላም በሚመጣው ዓለም እርሱ በሕያዋንና በሙታን ይፈርድ ዘንድ ይመጣል፡፡ የሰውን ወገኖች ዅሉ በሞቱበት፤ በተቀበሩበት ሥጋ ከሞት ያስነሣቸዋል፡፡ ከትንሣኤውም በኋላ ያለ መለወጥ ዅልጊዜ ይኖራል፡፡ እርሱ በዚህ በሞተበት፤ በተገነዘበት ሥጋ ከሙታን አስቀድሞ እንደ ተነሣ፤›› (ቅዱስ ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌም፣ ሃይ. አበ. ፶፪፥፲፩-፲፪)፡፡

‹‹የሥጋን ሕማም ለመለኮት ገንዘብ በአደረገ ጊዜ የእግዚአብሔር አካል በባሕርዩ በግድ ሕማምን አልተቀበለም፤ ሕማም በሚስማማው ባሕርዩ ኃይልን እንጂ፡፡ ሞትም በሥጋ ለእግዚአብሔር ቃል ገንዘብ በኾነ ጊዜ ሞትን አጠፋ፡፡ ከሞትም በኋላ ፈርሶ፣ በስብሶ መቅረትን አጠፋ፤›› (ቅዱስ ቴዎዶጦስ ሃይ. አበ. ፶፫፥፳፯)፡፡

‹‹መለኮት በሥጋ አካል በመቃብር ሳለ የሥጋ ሕይወት በምትኾን በነፍስ አካል ወደ ሲኦል ወረደ፤ እንደዚህ ባለ ተዋሕዶ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡ ከትንሣኤ በኋላ አይያዝም፤ አይዳሰስም፡፡ በዝግ ቤት ገብቷልና፡፡ ነገር ግን ምትሐት እንዳይሉት ቶማስ ዳሠሠው፡፡ የተባለውን ከፈጸመ በኋላ ቶማስ አመነበት፤›› (ቅዱስ ኤጲፋንዮስ፣ ሃይ. አበ. ፶፮፥፴፯-፴፰)፡፡

‹‹ክርስቶስ የሙታን በኵር እንደምን ተባለ? እነሆ በናይን ያለች የደሀይቱን ልጅ አስቀድሞ አስነሣው፤ ዳግመኛም አልዓዛርን በሞተ በአራተኛው ቀን አስነሣው፡፡ ኤልያስም አንድ ምውት አስነሣ፡፡ ደቀ መዝሙሩ ኤልሣዕም ሁለት ሙታንን አስነሣ፤ አንዱን ሳይቀበር፣ ሁለተኛውን ከተቀበረ በኋላ ሥጋውን አስነሣ፡፡ እነዚያ ሙታን ቢነሡ ኋላ እንደ ሞቱ፤ እነርሱ ኋላ አንድ ኾነው የሚነሡበትን ትንሣኤ ዛሬ ተስፋ ያደርጋሉ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን የሙታን ትንሣኤያቸው በኵር ነው፡፡እንግዲህ ወዲህም ሞት የሌለበትን ትንሣኤ አስቀድሞ የተነሣ እርሱ ነው፤ ዳግመኛም ሞት አያገኘውምተብሎ እንደ ተጻፈ፤›› (ቅዱስ ኤጲፋንዮስ፣ ሃይ. አበ. ፶፯፥፫-፮)፡፡

‹‹ቃል ሥጋውን በመቃብር አልተወም፤ በሲኦልም ካለች ከነፍሱ አልተለየም፡፡ ከነፍስ ከሥጋ በአንድነት ነበረ እንጂ፡፡ ለዘለዓለም ክብር ምስጋና ይግባው፤›› (ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘእንዚናዙ ሃይ. አበ. ፷፥፳፱)፡፡

‹‹ጌታ ለደቀ መዛሙርቱበትንሣኤ ከእናንተ ጋር እስከምመጣበት ቀን ድረስ ከዚያ ወይን ጭማቂ አልጠጣም፤ በሐዲስ ግብር በምነሣበት ጊዜ የምታዩኝ እናንት ምስክሮቼ ናችሁያለውን የማቴዎስን ወንጌል በተረጐመበት አንቀጽ እንዲህ አለ፤ ሐዲስ ያለው ይህ ነገር ምንድን ነው? ይህ ነገር ድንቅ ነው! መዋቲ ሥጋ እንዳለኝ ታያላችሁ፤ ነገር ግን ከትንሣኤ በኋላ የማይሞትነው፤ አይለወጥም፤ ሥጋዊ መብልንም መሻት የለበትም፤ ከትንሣኤ በኋላ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ቢበላም ቢጠጣም መብልን ሽቶ አይደለም፤ እርሱ ከሙታን ተለይቶ እንደ ተነሣ ያምኑ ዘንድ በላ ጠጣ እንጂ፡፡ ይህ ድንቅ ሥራ ነው! ያለ መለወጥ ሰው የኾነ ቃል የተቸነከረበትን ምልክት (እትራት) አላጠፋምና፡፡ በሚሞቱ ሰዎች እጅ እንዲዳሠሥ አድርጎታልና፡፡ አምላክ የኾነ ሥጋ የሚታይበት ጊዜ ነውና አላስፈራም፡፡ እርሱ በዝግ ደጅ ገባ፤ ግዙፉ ረቂቅ እንደ ኾነ ሥራውን አስረዳ፡፡ ነገር ግን በትንሣኤው ያምኑ ዘንድ የተሰቀለው እርሱ እንደሆነ የተነሣውም ሌላ እንዳይደለ ያውቁ ዘንድ ይህን ሠራ፡፡ ስለዚህም ተነሣ፤ በሥጋውም የችንካሩን ምልክት (እትራት) አላጠፋም፤ ዳግመኛም ከትንሣኤው አስቀድሞ ደቀ መዛሙርቱ ጧት ማታ ከእርሱ ጋር ይበሉ እንደ ነበረ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር በላ፤ ስለዚህም በአራቱ መዓዝነ ዓለም ትንሣኤውን አስረዱ፡፡ ከትንሣኤውም በኋላያየነው ከእርሱም ጋር የበላን የጠጣንም እርሱ ነውብለው አስረዱ፤›› (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሃይ. አበ. ፷፮፥፯-፲፪)፡፡

ትንሣኤ ምንድን ነው?

ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን…….በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን

አሰሮ ለሰይጣን……..አግዓዞ ለአዳም

ሰላም….….እምይእዜሰ

ኮነ…….ፍሥሓ ወሰላም

እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ

ትንሣኤ፡– ትንሣኤ ተንሥአ ተነሣ ከሚለው የግእዝ ቃል የወጣ ሲሆን ትርጉሙ መነሣት ማለት ነው፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ ሞቶ ሥጋው ፈርሶ በስብሶ እንደማይቀር እና በዳግም ምጽአት ጊዜ እንደሚነሣ የሚያመለክት ነው፡፡ የሰው ልጅ ከፈጣሪ የተሰጠውን ትእዛዝ ባለመጠበቁ ምክንያት የሞት ሞት ተፈርዶበት ነበረ፡፡ “እንዳትሞቱ ከእርሱ አትብሉ፣ አትንኩትም” ተብሎ ነበርና፡፡ (ዘፍ.፫፣፫) በዚህም ምክንያት ከአቤል ጀምሮ እስከ እለተ ምጽአት ድረስ የሰው ልጅ በሥጋ የሚሞት ሆኗል፡፡ ነገር ግን እንደሞትን አንቀርም፡፡ ሁላችንም ትንሳኤ አለን፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ በመነሣት የትንሣኤያችን በኩር ሆኖናልና፡፡(፩ኛ ቆሮ.፲፭፣፳፩)፡፡

“ሞት በሰው በኩል ስለመጣ ትንሳኤ ሙታን በሰው በኩል ሆኗል›› እንዲል፡፡ ዘለዓለማዊ ሞታችን እና ፈርሶ በስብሶ መቅረት የቀረልን አካላዊ ቃል ሥጋችን ተዋሕዶ ሰው ሆኖ ሞትን በሞቱ ድል ከነሣልን በኋላ ነው፡፡ ሊቁ ሱኑትዩ በሃይማኖተ አበው “ሞተ ክርስቶስ በሞተ ዚኣነ ከመ ይቅትሎ ለሞት በሞቱ፤ ሞትን በሞቱ ያጠፋልን ዘንድ ክርስቶስ በተዋሐደው ሥጋ የእኛን ሞት ሞተ ብሎ እንደገለጠው፡፡ (ዮሐ.፲፩፣፳፭)

“ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ” ያለ ጌታ በጥንተ ትንሣኤ መጋቢት ፳፱ ቀን በዕለተ እሑድ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡ ማር.(፲፮፣፮) መልአኩም “አትደንግጡ የተሰቀለውን የናዝሬቱን ኢየሱስ ትሻላችሁን? ተነሥቷል” ብሎ ለቅዱሳት አንስት ነግሯቸዋል፡፡ (ሉቃ.፳፬፣፮)፡፡

የክርስቶስ ትንሣኤ ከአልዓዛር ትንሣኤ የተለየ ነው፡፡ አልዓዛርን ያስነሣው ራሱ ክርስቶስ ሲሆን ትንሣኤውም መልሶ ሞት ነበረበት፡፡ ክርስቶስ ግን የተነሣው በራሱ ሥልጣን ነው፡፡ ዳግመኛ ሞትም የለበትም፡፡(ዮሐ.፪፥፲፱፤ ፲፥ ፲፰)”ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት በሦስት ቀንም አነሧዋለሁ” ካለ በኋላ እርሱ ግን ይህንን የተናገረው ቤተ መቅደስ ስለተባለ ሰውነቱ ነበር ይለዋል፡፡ በሌላም የወንጌል ክፍል “እናንተ በሰቀላችሁት እግዚአብሔርም ከሙታን ባስነሣው በናዝሬቱ ኢየሱስ ክርስቶስ ሥም… ይላል፡፡(ሐዋ.፬፣፲) በሃይማኖተ አበው ደግሞ መንፈስ ቅዱስ አስነሳው የሚል ይገኛል፡፡ ይህን ቢል ሦስቱ አካላት አንዲት ግብረ ባሕርይ ስላላቸው ያችን ለእያንዳንዱ አካላት አድሎ መናገሩ ነው፡፡ አብ አምላክ፣ ወልድ አምላክ፣ መንፈስ ቅዱስ አምላክ ቢል ሦስት አምላክ አንልም፡፡ አንድ አምላክ እንላለን እንጂ፡፡ (ዮሐ.፲፥፴) “እኔና አብ አንድ ነን”(ዮሐ.፲፥፱) እንዲል፡፡ ማስነሣት ሦስቱ አካላት አንድ የሚሆኑበት ግብር ስለሆነ አብ አስነሣው፣ በራሴ ሥልጣን ተነሣሁ፣ መንፈስቅዱስ አስነሣው ቢል አንድ ነው፡፡

የትንሣኤ ዓይነቶች

በዳግም ምጽአት ጊዜ ሙታን ሲነሡ ሁለት ዓይነት ትንሣኤ ይነሣሉ፡፡ አንደኛው ትንሣኤ ዘለክብር ሲሆን ሁለተኛው ትንሣኤ ዘለኀሣር ነው፡፡ ትንሣኤ ዘለክብርን የሚነሡ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ የፈጸሙ ቅዱሳን ናቸው፡፡ ትንሣኤ ዘለኀሣርን የሚነሡት ደግሞ የእግዚአብሔርን ሕግ ያልፈጸሙ ኃጥአን ናቸው፡፡ (ማቴ.፳፭፥፵፮) “እነዚያም (ኃጥአን) ወደ ዘለዓለም ቅጣት ጻድቃን ግን ወደ ዘለዓለም ሕይወት ይሄዳሉ” ተብሎ እንደተገለጠ፡፡ ትንሣኤ ዘለክብርን የተነሡ ጻድቃን ለዘለዓለም በመንግሥተ ሰማያት በተድላ በደስታ ይኖራሉ፡፡ ትንሣኤ ዘለኀሣርን የተነሡ ኃጥአን ደግሞ ለዘለዓለም በገሃነመ እሳት በሥቃይ በሰቆቃ ይኖራሉ፡፡

የትንሣኤ ምሳሌዎች

. ፀሐይ፡-

ፀሐይ የመውጣቷ የመወለዳችን ምሳሌ ነው፡፡ ፀሐይ ጠዋት ወጥታ ስታበራ እንድትውል እኛም ተወልደን በዚች ምድር ለመኖራችን ምሳሌ ነው፡፡ በሠርክ ፀሐይ መግባቷ የመሞታችን ምሳሌ ነው፡፡ መልሳ ጠዋት መውጣቷ የትንሣኤያችን ምሳሌ ናት፡፡ (ሃይ.አበ.፶፰፥፭)

. ዖፈ ፊንክስ፡-

ይህ ወፍ የሚሞትበት ቀን እንደደረሰ ባወቀ ጊዜ ብዙ ጭቃ ሰብስቦ ወደ ግብጽ ይሄዳል፡፡ በጭቃው ላይ ቆሞ ክንፉን በደረቱ ባማታው ጊዜ ከአካሉ እሳት ወጥቶ ሥጋውን አጥንቱን ሁሉ ያቃጥለዋል፡፡ በእግዚአብሔር ትእዛዝ ዝናም የያዘ ደመና መጥቶ ዝናም ይዘንማል፡፡ እሳቱንም ያጠፋዋል፡፡ ከዚያ ከአመዱ ትንኝ ይገኛል፡፡ክንፍም ይበቅልለታል፡፡ ቡላል አህሎ ያድራል፡፡ በሦስተኛው ቀን እንደቀደመ አካሉ ይመለስለታል፡፡

የራሳችን ፀጉርም ከተላጨ በኋላ መልሶ ሌላ አዲስ ፀጉር ይበቅልልናል፡፡ የእጅ ጥፍርም እንዲሁ ከተቆረጠ በኋላ አዲስ ጥፍር ይወጣል፡፡ ይህ ሁሉ ምሳሌ ዘየሐጽጽ ነው፡፡ እኛ በምንነሣበት ጊዜ ይዘነው የምንነሣው ሥጋ የማይራብ የማይጠማ ሥጋን ነው፡፡ በምስጋና እና በጸጋ ላይ ጸጋ እየተጨመረለት የሚሄድ ሥጋን ይዘን ነው የምንነሣው፡፡ ሌላው እና ዋናው ግን በኃጢአት የወደቅን ሰዎች በንስሓ ተነሥተን አዲስ ልብን ገንዘብ ማድረግ ይገባናል፡፡ ይህም ትንሣኤ ልቡና ይባላል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ቀዳም ሥዑር

በሰሙነ ሕማማት በስቀለት ማግስት የሚውለው ቅዳሜ ቀዳም ሥዑር በመባል ይጠራል፡፡ በዚህ ዕለት ከድሮው በተለየ መልኩ ጌታችን መድኂታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዳምና ልጆቹን ከዲያብሎስ አገዛዝና እስራት ነጻ ለማውጣት የተቀበለውን መከራ፣ እንዲሁም ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በከርሠ መቃብር ማደሩን በማሰብ በጾም ታስቦ ስለሚውል ቀዳም ስዑር ወይም የተሻረው ቅዳሜ ተብሏል፡፡ የማይጾመው ቅዳሜ ስለሚጾም ስዑር /የተሻረ/ ተብሏል፡፡

ቀዳም ሰዑር ሌሎችም ስያሜዎች ያሉት ሲሆን እንደሚከተለው ቀርቧል፡-

ለምለም ቅዳሜ፡

ካህናቱ ሌሊት ለምእመናን ለምለም ቄጤማ ስለሚያድሉ ዕለቲቱ በዚህ ስያሜ ተሰይሟል፡፡ ቀጤማውንም ምእመናን እስከ ትንሣኤ ሌሊት በራሳቸው ላይ ያስሩታል፡፡

በቀዳም ስዑር ቀሳውስቱና ዲያቆናቱ ቃጭል /ቃለ ዓዋዲ/ እየመቱ “ገብረ ሰላመ በመስቀሉ ትንሣኤሁ አግሃደ” የሚለውን ያሬዳዊ ዜማ በመዘመር፤ ጌታ በመስቀሉ ሰላምን እንደሰጠን እና ትንሣኤውንም እንደገለጠልን በማብሰር፤ ቄጤማውን ለምእመናን ይሰጣሉ፡፡ ምእመናኑም በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚውል ገጸ በረከት ያቀርባሉ፡፡ ቄጤማውንም በራሳቸው ያስራሉ፡፡ ይህም አይሁድ ጌታችንን እያሰቃዩ ሊሰቅሉት ባሉ ጊዜ የእሾህ አክሊል ጭንቅላቱ ላይ ያሠሩበትን ድርጊት የሚያስታውስ ነው፡፡

የቀጤማው አመጣጥና ምስጢርም ከአባታችን ከኖኅ ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ምድር በማየ አይኅ /በጥፋት ውኃ/ በጠፋችበት ወቅት የኖኅ ታማኝ መልእክተኛ ርግብ የውኃውን መጉደል ያበሰረችው ቄጤማ ይዛ በመግባት ነው፡፡

ዛሬም ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች የኃጢአት ውኃ ጐደለ፣ የኃጢአት ውኃ ጠፋ በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነጻነት ተሰበከ ታወጀ በማለት ካህናት ቄጠማ ይዘው ምእመናንን ያበሥሩበታል፡፡

ቅዱስ ቅዳሜ

ቅዱስ ቅዳሜ መባሉ ቅዱስ የሆነ እግዚአብሔር በጥንተ ተፈጥሮ ፍጥረታትን አከናውኖ ከፈጠረ በኋላ በዚህ ቀን ከሥራው ሁሉ ያረፈበት ነው፡፡ በዘመነ ሐዲስ ደግሞ የማዳን ሥራውን ሁሉ ፈጽሞ በሥጋው በመቃብር ሲያርፍ፣ በነፍሱ ሲዖልን በርብሮ ባዶዋን አስቀርቷታል፡፡ በዚያ ለነበሩት ነፍሳትም የዘለዓለም ዕረፍትን ያወረሰበት ዕለት ስለሆነ ከሌሎቹ ዕለታት የተለየ ዕለት ለማለት ቅዱስ ቅዳሜ ተብሏል፡፡

ሰባቱ የመስቀል ላይ ጩኸቶች

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአይሁድ በይሁዳ አማካይነት ተላልፎ ከተሰጠበት ሐሙስ ምሽት ጀምሮ ስቃይ ሲያጸኑበት ቆይተዋል፡፡ በዕለተ ዐርብም ይሰቅሉት ዘንድ አስከ ቀራንዮ መስቀል አሸክመው የተለያዩ ጸዋትወ መከራ እያጸኑበት ወስደውታል፡፡ በመሰቀል ላይ በሁለቱ ወንበዴዎች መካከል ከተሰቀለበት ሰዓት ጀምሮም የተናገራቸው ቃላት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን “ሰባቱ የመስቀል ላይ ጩኸቶች ወይም “ሰባቱ አጽርሐ መስቀል” በማለት ሰይማ ታስባቸዋለች፡፡ እነርሱም በመጽሐፍ ቅዱስ የተጠቀሱ ሲሆን ቀጥለንም በዝርዝር እንመለከታቸዋለን፡-

፩ኛ. “ኤሎሄ ኤሎሄ ላማሰበቅታኒ፤ አምላኬ አምላኬ ለምን ተውኸኝ

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሳለ በዘጠኝ ሰዓት የተናገረው ቃል እንደሆነ በወንጌል ተጽፎ እናገኘዋለን፡፡ “በዘጠኝ ሰዓትም ጌታችን ኢየሱስ ኤሎሄ ኤሌሄ ላማሰበቅታኒ ብሎ በታላቅ ቃል ጮኸ፡፡ይኸውም አምላኬ አምላኬ ለምን ተውኸኝ? ማለት ነው፡፡ በዚያም ቆመው የነበሩት በሰሙ ጊዜ ይህስ ኤልያስን ይጠራል አሉ” (ማቴ.፳፯፥፵፭) እንዲል፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምላኬ አምላኬ ለምን ተውኸኝ ብሎ የተናገረበት መሠረታዊ ሐሳብ፡- ያችን የድኅነት ቀን ከአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን በኋላ ያለችውን ዕለተ ዓርብ በተስፋ ይጠባበቅ የነበረውን አዳምን ወክሎ እንደሆነ አበው ያስረዳሉ፡፡ (ማቴ.፳፯፥፵፭ አንድምታ ትርጓሜ)፡፡ በመሆኑም አምላኬ አምላኬ ያለው በአዳም ተገብቶ እንደሆነ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ እንዲሁም አምላኬ አምላኬ ያለው ሰውነቱን ሲገልጥ ነው፡፡ ይህም ፍጹም አምላክነቱንና ፍጹም ሰውነቱን ማለት ነው፡፡

፪ኛ. “ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትሆናለህ

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደል ሳይኖርበት እንደ በደለኛ ተቆጥሮ በሁለት ወንበዴዎች መካከል ነበር የተሰቀለው፡፡ “ከእርሱ ጋርም ሁለት ወንበዴዎችን አንዱን በቀኙ አንዱን በግራው ሰቀሉ፡፡ መጽሐፍ ከዐመፀኞች ጋር ተቈጠረ ያለው ተፈጸመ” (ማር.፲፭፥፳፯) ይላልና፡፡

በቀኝ በኩል የተሰቀለው ወንበዴ ጌታችንን “አቤቱ በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ›” አለው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም መልሶ እንዲህ አለው “እውነት እልሃለሁ ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትሆናለህ፡፡” (ሉቃ.፳፫፥፵፫)፡፡

፫ኛ. “አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ

“ያን ጊዜም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ድምጹን ከፍ አድርጎ አባት ሆይ ነፍሴን በአንተ እጅ አደራ እሰጣለሁ ብሎ ጮኸ፤ ይህንም ብሎ ነፍሱን ሰጠ” (ሉቃ.፳፫፥፵፮)፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ “አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ” በማለት የተናገረው ቃል የተሰቀለው እርሱ እግዚአብሔር ወልድ እንደሆነና የአብ የባሕርይ ልጁ እንደሆነ ያሳያል፡፡

፬ኛ. “አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው

ምንም በደል ሳይኖርበት አይሁድ በክፋት ተነሳስተው መከራ አጸኑበት፤ ያን ሁሉ የግፍ ግፍ በጭካኔ የተሞላ መከራ ሲያደርሱበት ልባቸውን ዲያብሎስ ስላደነዘዘው የሚራራ ልብ አጡ፡፡በዚያንም ጊዜ መምህረ ይቅርታ ቸሩ አምላካችን ለሠቃዮቹ “አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው አለ” (ሉቃ.፳፫፥፴፬)፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደለኞች ይቅርታን ያገኙ ዘንድ ይቅር በላቸው አለ፡፡ ልመናውንም ያቀረበው ወደ ባሕርይ አባቱ ነው፡፡ ከባሕርይ አባቱ ጋር ደግሞ በባሕርይ፣ በሕልውና፣ በአገዛዝ፣ በፈቃድ አንድ ናቸው፡፡ እንዲሁም የሰውን ባሕርይ ባሕርይ አድርጎ ፍጹም ሰው እንደሆነ ሲያስረዳ ነው፡፡ይህም በደለኞችን ከራሱ ጋር ያስታረቀበት የፍቅር ድምጽ ነው፡፡

አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅርበላቸው ማለቱ አባት ሆይ ብሎ የባሕርይ ልጅነቱን ከመግለጹ በተጨማሪ ይቅር በላቸው ማለቱ ጠላትን ይቅር ማለት የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ የመሆኑ አንዱ ማሳያ ነው፡፡ ምክንያቱም ጠላቶቻችሁን ውደዱ ብሎ ያስተማረ እርሱ ብቻ ነውና፡፡

፭ኛ. “እነሆ ልጅሽ፤ እናትህ እነኋት

“ጌታችን መድኀኒታችንን ኢየሱስም እናቱንና የሚወደውን ደቀ መዝሙሩን ቆመው ባያቸው ጊዜ እናቱን ‘አንቺ ሆይ እነሆ ልጅሽ’ አላት፡፡ ከዚህም በኋላ ደቀ መዝሙሩን ‘እናትህ እነኋት’ አለው፡፡ ከዚያችም ሰዓት ጀምሮ ደቀ መዝሙሩ ተቀብሎ ወደ ቤቱ ወሰዳት” (ዮሐ.፲፱፥፳፮)፡፡ ደቀ መዝሙሩ ተብሎ የተጠቀሰው ጌታችን ይወደው የነበረ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊው ነው፡፡ ይህንንም የጻፈው እርሱ ነው (ዮሐ.፳፩፥፳፬)፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ከዐሥራ ሁለቱ ደቀ መዛሙርት አንዱ ቢሆንም ሐሙስ ማታ እረኛው ሲያዝ ከተበተኑት በጎች ጋር አብሮ አልሸሸም፡፡ በዚያች በአስጨናቂዋ ሰዓት ከጌታችን ጋር እስከ እግረ መስቀሉ ተጓዘ፡፡የክርስቶስ ፍቅር ፍርሃቱን ሁሉ አርቆለት የአይሁድን ቁጣና ዛቻ ሳይፈራ ጸንቶ በመቆሙ እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለእኛ ሁሉ እርሱ በኩል ተሰጠችን፡፡ እናታችን ድንግል ቅድስት ማርያም ሁል ጊዜም ቢሆን ከእግረ መስቀሉ ሥር ለሚገኙ፣ ልባቸው ቀራንዮን ለሚያስብ ሁሉ እናት እንድትሆን እነርሱም ልጆቿ እንዲሆኑ በቅዱስ ዮሐንስ በኩል ተሰጥታናለች፡፡

በመሆኑም “እነሆ ልጅሽ፤ እናትህ እነኋት” የሚለው የመስቀሉ ቃል በመስቀል ላይ የተከፈለልንን ዋጋ አስበን በእርሱ አምነን በምግባር ታንጸን እንደ ፈቃዱ በምንኖር ክርስቲያኖችና ለድኅነታችን ምክንያት በሆነች በእመ አምላክ በቅድስት ድንግል ማርያም መካከል የእርሷ እናትነት፣ የእኛ ልጅነት የተመሠረተበት የፍቅር ቃል ነው፡፡

፮ኛ. “ተጠማሁ

“ከዚህም በኋላ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ሁሉ እንደ ተፈጸመ ባየ ጊዜ የመጽሐፍ ቃል ይፈጸም ዘንድ ‘ተጠማሁ’ አለ” (ዮሐ.፲፱፥፳፰)፡፡

ውኆችን በእፍኙ የሰፈረ፣ የባሕር አሸዋን የቆጠረ፣ ውኆችንም ጠርቶ በምድር ፊት ላይ የሚያፈሳቸው፣ የባሕር ጥልቀትንና ዳርቻን የወሰነ፣ የኤርትራን ባሕር እንደ ግድግዳ ያቆመ አምላክ “ተጠማሁ” ብሎጮኸ፡፡ (ኢሳ.፵፥፲፪፣አሞ.፱፥፮)፡፡

“የተጠማ ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ በእኔም የሚያምን መጽሐፍ እንደ ተናገረ የሕይወት ውኃ ምንጭ ከሆዱ ይፈልቃል” (ዮሐ.፯፥፴፯) በማለት እርሱ የሕይወት ውኃ እንደሆነ ተናገረ፡፡ አምላክ ሲሆን “ተጠማሁ” ብሎ መጮኹ ስለ ምንድንነው ብለን ቅዱሳት መጻሕፍትን ስንመረምር፡- አንደኛ የመከራውን ጽናት፣ ከሚነገረው በላይ መከራውን እንዳጸኑበት የሚያሳይ ሲሆን፤ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ እርሱ የተጠማው የሰውን መዳን ነው፡፡ ሌላው ደግሞ በዚያን ወቅት እንኳ ከክፉ ሥራው ተመልሶ የሚጸጸት፣ የሚራራ፣ ንስሓ የሚገባ ሰው በማጣቱ መድኃኒት እርሱ ቀርቦ ሳለ የሰው ልጅ ባለማስተዋሉ ወደ እርሱም በፍቅር ባለመቅረቡና ባለመመለሱ ተጠማሁ አለ፡፡

፯ኛ. “ሁሉ ተፈጸመ

”ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስም ሆምጣጤውን ቀምሶ ሁሉ ተፈጸመ አለ፡፡ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን ሰጠ” (ዮሐ.፲፱፥፴)፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕተ ዐርብ በመስቀል ላይ ሳለ ‘ተፈጸመ’ ብሎ መናገሩ ብዙ ትርጉም ያለው ቃል ነው፡፡ እነርሱም፡-

 በነቢያት ስለ እኔ የተነገረው ትንቢት፣ የተመሰለው ምሳሌ፣ በቅዱሳን አበው የተቆጠረው ሱባኤ፣ ጊዜው ደርሶ የአዳም ተስፋ ተፈጸመ፡፡

 የሰው ልጅ በዲያብሎስ አገዛዝ በሞትና በጨለማው ሥልጣን፣ በአጋንንት ወጥመድ ታስሮ የሚኖርበት የፍዳ ዘመን አለቀ ተፈጸመ፡፡

 በእግዚአብሔርና በሰው፣ በመላእክትና በሰው፣ በሰማይና በምድር መካከል ቆሞ የነበረው የጥል ግድግዳ ፈረሰ፣ የተጻፈው የዕዳ ጽሕፈት ተደመሰሰ፣ የሰው ልጅ ዕዳ በደል ተከፈለ በአምላክ የቤዛነት ሥራ ሁሉ ተፈጸመ ማለት ነው፡፡

እነዚህ ከአንድ እስከ ሰባት የጠቀስናቸው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ መራራውን መከራ እየተቀበለ የተናገራቸው የመጨረሻ ቃላቶቹ ናቸው፡፡ ወደዚህ ዓለም ሰው ሆኖ የመጣበትን ዓላማ አከናውኖ ሲጨርስ በመጨረሻ “ተፈጸመ ኵሉ” በማለት ነፍሱን ከሥጋው ለየ፡፡ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶም በሲኦል ባርነት ለነበሩት አዳምና ልጆቹ ነጻነትን ሰበከላቸው፡፡ በአካለ ሥጋ ደግሞ ወደ መቃብር ወርዶ ሙስና መቃብርን አጠፋልን፡፡

የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን አሜን፡፡

ጸሎተሐሙስ

ጸሎተ ሐሙስ

ጸሎተ ሐሙስን ሕፅበተ ሐሙስ፣ የምስጢር ቀን፣ የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ፣ የነፃነት ሐሙስ እየተባለ ይጠራል፡፡

ሕጽበተ ሐሙስ

ጌታችን በዚህ ዕለት የደቀ መዛሙርቱን እግር በፍጹም ትሕትና ዝቅ ብሎ አጥቧል፡፡ ይህም ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለምን ሁሉ ኃጢአት ለማጠብ የመጣ የንጽሕና፣ የቅድስና አምላክ መሆኑን ያጠይቃል፡፡ ስለዚህም ዕለቱ “ሕጽበተ ሐሙስ” ይባላል፡፡ ይህን ለማስታወስ ዛሬም ሊቃነ ጳጳሳትና ቀሳውስት በመካከላችን ተገኝተህ የእኛንና የሕዝብህን ኃጢአት እጠብ፤ እኛም የአንተን አርአያነት ተከትለን የልጆቻችንን እግር እናጥባለን ሲሉ በቤተ ክርስቲያን የተገኙ ምእመናንን እግር በወይንና በወይራ ቅጠል ያጥባሉ፡፡

የምሥጢር ቀን

ከሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን አንዱ ምሥጢረ ቍርባን በዚህ ቀን ተመሥርቷልና ዕለቱ “የምሥጢር ቀን” ይባላል፡፡ ይኸውም ጌታችን ኅብስቱንና ጽዋውን አንሥቶ ይህ ስለ እናንተ በመስቀል ላይ የሚቈረሰው ሥጋዬ ነው፡፡ እንካችሁ፤ ብሉ፡፡ ይህ ስለ እናንተ ነገ በመስቀል ላይ የሚፈስ ደሜ ነው፤ ከእርሱም ጠጡ በማለት እርሱ ከእኛ፤ እኛም ከእርሱ ጋር አንድ የምንሆንበትን ምሥጢር ከጠላት ዲያብሎስ ሰውሮ፣ ለደቀ መዛሙርቱ የገለጠበት ቀን በመሆኑ የተሰጠ ስያሜ ነው፡፡ በዚህ ዕለት ክርስቲያን የሆነ ሁሉ በንስሐ ታጥቦ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለመቀበል ይዘጋጃል፡፡

የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ

መድኃኒታችን ክርስቶስ መሥዋዕተ ኦሪት ማለትም በእንስሳት ደም የሚቀርበው መሥዋዕት ማብቃቱን ገልጦ፣ ለድኅነተ ዓለም ራሱን የተወደደ መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበበት ዕለት በመሆኑ ይህ ዕለት “የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ” ይባላል (ሉቃ. ፳፪፥፳)፡፡ “ኪዳን” ማለት በሁለት ወገን መካከል የሚደረግ ውል፣ ስምምነት፣ መሐላ ማለት ነው፡፡ በዚህ መሠረት ጌታችን ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ዘለዓለማዊውን ቃል ኪዳን በራሱ ደም የፈጸመበት ዕለት ስለ ሆነ ሐሙስ “የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ” ተባለ፡፡

የነጻነት ሐሙስ

ይህ ዕለት ለኃጢአትና ለዲያብሎስ ባሪያ ሆኖ መኖር ማብቃቱ የተገለጠበት፤ የሰው ልጅ ያጣውን ክብር መልሶ ማግኘቱ የተረጋገጠበት ቀን ስለ ሆነ “የነጻነት ሐሙስ” ይባላል፡፡ ጌታችን ስለ ሰው ልጅ ነጻነት ሲናገር ከእንግዲህ ወዲህ ባሮች አልላችሁም፤ ባርያ ጌታው የሚያደርገውን አያውቅምና፡፡ ወዳጆች ግን ብያችኋለሁ በማለት ከባርነት የወጣንበትን፤ ልጆች የተባልንበትን ቀን የምናስብበት በመኾኑ “የነጻነት ሐሙስ” ይባላል (ዮሐ. ፲፭፥፲፭)፡፡ እያንዳንዱ ክርስቲያንም ከኃጢአት ባርነት ርቆ፣ ከእግዚአብሔር ጋር የሚያወዳጀውን መልካም ሥራ በመሥራት ሕይወቱን መምራት ይኖርበታል፡፡ ባሮች ሳይሆን ወዳጆች ተብለን በክርስቶስ ተጠርተናልና፡፡

በዚህ ዕለት እንደ ማክሰኞ ሆሉ ጌታችን በዮሐንስ ወንጌል ፲፬፥፲፮ የሚገኘውን ሰፊ ትምህርት ለደቀ መዛሙርቱ አስተምሯል፡፡ የትምህርቱም ዋና ዋና ክፍሎችም ምሥጢረ ሥላሴን፣ ምሥጢረ ሥጋዌንና ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን ያካትታሉ፡፡ ጌታችን እነዚህን ትምህርቶች በስፋትና በጥልቀት መማር እንደሚገባ ሲያስረዳ፣ ለደቀ መዛርቱ ምሥጢሩን በተአምራት ሊገልጥላቸው ሲቻለው በሰፊ ማብራርያ እንዲረዱት አድርጓል፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ያልገባቸውንም እየጠየቁ ተረድተዋል፡፡ ምእመናንም በቤተ ክርስቲያን ተገኝተን መማርና ያልገባንን ጠይቀን መረዳት እንደሚገባን ከዚህ እንማራለን፡፡ መድኃኒታችን ክርስቶስ ራሱን ለአይሁድ አሳልፎ የሰጠውም በዚሁ ዕለት ከምሽቱ በሦስት ሰዓት ነው (ማቴ. ፳፮፥፵፯-፶፰)፡፡

በጸሎተ ሐሙስ በቤተ ክርስቲያን የሚፈጸም ሥርዓት

በዚህ ዕለት ስግደቱ፣ ጸሎቱ፣ ምንባባቱ እንደ ተለመደው ይከናወናሉ፡፡ መንበሩ (ታቦቱ) ጥቁር ልብስ ይለብሳል፡፡ ጸሎተ ዕጣን ይጸለያል፤ ቤተ ክርስቲያኑም በማዕጠንት ይታጠናል፡፡ ሕጽበተ እግር ይደረጋል፡፡ ቅዳሴ ይቀደሳል፡፡ በየቤቱ ደግሞ ጉልባን ይዘጋጃል፡፡

ሕጽበተ እግር

ከቀኑ በዘጠኝ ሰዓት ዲያቆኑ ሁለት ኵስኵስቶችን ውኃ ሞልቶ ያቀርባል፤ አንዱ ለእግር፣ አንዱ ለእጅ መታጠቢያ፡፡ ‹ጸሎተ አኰቴት› በመባል የሚታወቀው የጸሎት ዓይነት ይጸለያል፡፡ ወንጌል ተነቦ ውኃው በካህኑ (በሊቀ ጳጳሱ) ይባረክና የሕጽበተ እግር ሥርዓት ይከናወናል፡፡ ይኸውም ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር በማጠብ ያሳየውን የተግባር ትምህርት ለማሳየት ነው (ዮሐ. ፲፫፥፲፬)፡፡ ከውኃው በተጨማሪ የወይራና የወይን ቅጠልንም ለሥርዓተ ሕጽበቱ ማስፈጸሚያነት እንጠቀምባቸዋለን፡፡ ምሥጢሩም የሚከተለው ነው፡-

ወይራ ጸኑዕ ነው፡፡ ወይራ ክርስቶስም ጽኑዕ መከራ መቀበሉን ከማስረዳቱ በተጨማሪ እኛም (እግራችንን የሚያጥቡን አባቶች እና የምንታጠበው ምእመናን) መከራ ለመቀበል ዝግጁ ነን ለማለት ሥርዓተ ሕጽበቱን በወይራ እንፈጽማለን፡፡ የወይኑ ቅጠልም መድኃኒታችን ክርስቶስ በወይን የተመሰለ ደሙን አፍስሶ ለምእመናን የሕይወት መጠጥ አድርጎ መስጠቱን ለማዘከር በወይን ሥርዓተ ሕጽበትን እናከናውናለን (ማቴ. ፳፮፥፳፮)፡፡ በቀኝና በግራ የቆሙ ሊቃውንትም ‹‹ሐዋርያቲሁ ከበበ እግረ አርዳኢሁ ሐጸበ›› እያሉ ይዘምራሉ፡፡ ይህ ሥርዓት ከተጠናቀቀ በኋላ ሥርዓተ ቅዳሴው ተከናውኖ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ምእመናን ይቀበላሉ፡፡

 ቅዳሴ

የጸሎተ ሐሙስ ቅዳሴ የሚከናወነው በተመጠነ ድምፅ ሲሆን፣ እንደ ደወል (ቃጭል) የምንጠቀመውም ጸናጽልን ነው፡፡ ልኡካኑ የድምፅ ማጉያ ሳይጠቀሙ በለኆሣሥ (በቀስታ) ይቀድሳሉ፡፡ ምክንያቱም ይሁዳ በምሥጢር ጌታችንን ማስያዙን ለመጠቆም ሲሆን፣ በሌላ በኩል ደግሞ የዘመነ ብሉይ ጸሎት ዋጋው ምድራዊ እንደ ነበር ለማስታወስ ነው፡፡ በመቀጠል ክብር ይእቲ፣ ዕጣነ ሞገር፣ ዝማሬ የተባሉ የድጓ ክፍሎች ተዘምረው አገልግሎቱ ይጠናቀቃል፡፡ ሕዝቡም ያለ ኑዛዜና ቡራኬ ይሰናበታሉ፡፡

ጉልባን

ጉልባን ከባቄላ ክክ፣ ከስንዴ ወይንም ከተፈተገ ገብስ ጋር አንድ ላይ ተቀቅሎ የሚዘጋጅና የጸሎተ ሐሙስ ዕለት የሚበላ ንፍሮ ነው፡፡ በጸሎተ ሐሙስ በቤት ውስጥ ከሚፈጸሙ ተግባራት አንዱ ጉልባን ማዘጋጀት ነው፡፡ ጉልባን እስራኤላውያን ከግብጽ ባርነት ሲወጡ በችኮላ መጓዛቸውን የምናስታውስበት ከእስራኤላውያን የመጣ ትውፊታዊ ሥርዓት ነው፡፡ በአገራችን ኢትዮጵያ አብዛኞቹ የትውፊት ክንዋኔዎች የብሉይ ኪዳን መነሻ ስላላቸው ይህ ሥርዓት ዛሬም በኢትዮጵያውያን ምእመናን ዘንድ ይከበራል፡፡

ጉልባን እስራኤላውያን ከባርነት በወጡ ጊዜ አቡክተው፣ ጋግረው መብላት አለመቻላቸውን ያስታውሰናል፡፡ በወቅቱ ያልቦካውን ሊጥ እየጋገሩ ቂጣ መመገብ፤ ንፍሮ ቀቅለው ስንቅ መያዝ የመንገድ ተግባራቸው ነበርና፡፡ ይህን ታሪክ ለማሰብም በሰሙነ ሕማማት በተለይም በጸሎተ ሐሙስ ቂጣና ጉልባን ይዘጋጃል፡፡ በጸሎተ ሐሙስ የሚዘጋጀው ጉልባንና ቂጣ ጨው በዛ ተደርጎ ይጨመርበታል፡፡ ይኸውም ጨው ውኃ እንደሚያስጠማ ሁሉ፣ ጌታችንም በመከራው ወቅት ውኃ መጠማቱን ለማስታወስ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ሆሳዕና በአርያም

ሆሣዕና ማለት መድኃኒት ወይም አቤቱ አሁን አድን ማለት ነው፡፡ በዐቢይ ጾም ስምንተኛ ሳምንት የሚከበር በዓል ሲሆን ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘጠኙ ዓበይት በዓላት አንዱ ነው። ከስምንቱ የዐቢይ ጾም እሑዶች አንዱና የመጨረሻው ሳምንት ከትንሣኤ ቀድሞ የሚገኝ የሕማማት መግቢያ ዋዜማ ነው።

“አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ እጅግ ደስ ይበልሽ፤ አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ እልል በዪ፤ እነሆ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው፤ ትሑትም ሆኖ በአህያም በአህያይቱም ግልገል በውርንጫይቱ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል፡፡” (ዘካ. ፱÷፱) በማለት በነቢያት የተነገረው ይፈጸም ዘንድ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከደብረ ዘይት ቤተ ፋጌ በአህያ ውርንጫ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም መግባቱን በማሰብ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዓሉን በድምቀት ታከብረዋለች፡፡

በወንጌሉም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ወደ ኢየሩሳሌም ደብረ ዘይት ቤተ ፋጌ በደረሰ ጊዜ ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ ሁለቱን ደቀ መዛሙርት ጠርቶ “በፊታችሁ ወደአለችው መንደር ሂዱ ያን ጊዜም የታሰረች አህያ ከውርንጫዋ ጋር ታገኛለችሁ፤ ፍቱና አምጡልኝ” አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም የሰው ንብረት ዘርፈን እንዴት እናመጣለን? ብለው መፍራታቸውን የተረዳው ጌታችንም “ምን ታደርጋላችሁ? የሚላችሁ ቢኖር ጌታቸው ይሻቸዋል በሉ፤ ያን ጊዜ ይሰዱአችኋል” አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ሄደው ጌታችን ኢየሱስ እንዳዘዛቸው አደረጉ፡፡

ልብሳቸውንም በአህያውና በውርንጫይቱ ላይ አድርገው ጌታችንም በእነርሱ ላይ ተቀመጠ፡፡ ሕዝቡም ልብሳቸውን በመንገድ ላይ አነጠፉለት፤ ዘንባባ እና የዛፎችንም ጫፍ ጫፍ እየቆረጡ “ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩክ ነው፤ ሆሣዕና በአርያም” እያሉ ይጮሁ ነበር፡፡ (ማቴ. ፳፩÷፩-፲፩) ልብሳቸውን ማንጠፋቸውም ለክብሩ መግለጫ ነው፡፡ እንዲህ ባለ ክብርና ምስጋና ወደ ኢየሩሳሌም ሲገባ ከተማዋ በዝማሬና በአመስጋኞች ጩኸት ተናወጠች፡፡

የሕዝቡ ጩኸትና ደስታ ያበሳጫቸው ፈሪሳዊያንና አይሁድ የሚያመሰግኑትን ዝም እንዲያሰኝ ጌታችንን ቢጠይቁትም “እነዚህ ዝም ቢሉ ድንጋዮች ያመሰግኑኛል” ብሎ መልሶላቸዋል፡፡ በነቢዩ ዳዊት “ከሚጠቡ ሕፃናትና ከልጆች ምሥጋናን አዘጋጀህ” (መዝ. ፰÷፪) ተብሎ የተነገረው ትንቢት እንዲፈጸም የአርባ የሰማንያ ቀን የዓመት የሁለት ዓመት ሕፃናትም አመስግነውታል፡፡ አዋቂዎችም ሕፃናትም “ሆሣዕና በአርያም” እያሉ ማመስገናቸው “መድኃኒት መባል ለአንተ ነነይገባሃል” ማለታቸው ነው።

በበዓለ ሆሣዕና ከሚነሳው ታሪክ ውስጥ የአህያዋና የውርንጫዋ ጉዳይ ነው፡፡ ጌታችን ኪሩቤል በሚሸከሙት ዙፋን የሚቀመጥ አምላክ ሲሆን ትሁት ሆኖ በአህያ ላይ ተቀመጠ፡፡ አህያዋን ከነውርንጫዋ “ፈታችሁ አምጡልኝ” ማለቱ የሰውን ልጅ ከኃጢአት እሥራት ለመፍታት የመጣ አምላክ መሆኑን ያመለክተናል፡፡ ደቀ መዛሙርቱም አህዮቹን ፈተው ማምጣታቸው ሥልጣነ ክህነታቸውን ያመለክታል፡፡ “በምድር የፈታችሁት በሰማይ የተፈታ ይሁን” እንዲል፡፡

በአህያ ላይ ልብሳቸውን ማንጠፋቸው የምትመች የማትቆረቁር የወንጌልን ሕግ ሰጠኸን ሲሉ ነው፡፡ በአህያ የተቀመጠ ሰው በፈረስ እንደተቀመጠ ሰው ፈጥኖ አያመልጥም። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከፈለጉኝ አያጡኝም ሲል በአህያ ተቀምጧል፡፡

ከኢየሩሳሌም እስከ ቤተ መቅደስ ፲፮ ምዕራፍ ነው፡፡ ፲፬ቱን በእግሩ ሄዶ ሁለቱን በአህያዋ፣ በውርንጫይቱ ደግሞ ሦስት ጊዜ ቤተ መቅደሱን ዞሯል፡፡ ይህም የሦስትነቱ ምሳሌ፣ አሥራ አራቱን በእግሩ መሄዱ አሥርቱ ትእዛዛትን፣ አራቱ ደግሞ የአራቱ ኪዳናት ማለትም ኪዳነ ኖኅ፣ ክህነተ መልከ ጼዴቅ፣ ግዝረተ አብርሐም እና ጥምቀተ ዮሐንስን ያመለክተናል፡፡

ከግለሰብ ደጅ የተፈታችን አህያ “ጌታዋ ይፈልጋታል” ብሎ ያስፈታት በፈጣሪነቱ ወይም ስለፈጠራት ገንዘቡ ስለሆነች ነው፡፡ አህያን ያልናቀ አምላክ እኛም ከኃጢአት ርቀን ብንፈልገው ማደሪያዎቹ ሊያደርገን ፈቃዱ ነው፡፡ የአህያዋን መፈታት የፈለገ ጌታ እኛም ወደ ካህናት ቀርበን ኃጢአታችንን ተናዘን ከበደል እሥራት እንድንፈታ ይፈልጋልና፡፡

ሆሣዕና ከረቡዕ ጀምሮ የሚታሰብ ታላቅ የቤተ ክርስቲያን የበዓል ቀን እንደሆነ ይታወቃል። በዋዜማዎቹ ዕለታት ከቅዱስ ያሬድ ድርሰት ከሆነው ከጾመ ድጓ “ሆሣዕና በአርያም፣ ሆሣዕና ለወልደ ዳዊት …’’ በማለት ይዘመራል፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተ መቅደስ ሲገባ ሕዝቡ ዘንባባ ይዘው “ቡርክ ዘይመጽእ በስመ እግዚአብሔር፤ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ የተባረክ ነው።’’ (መዝ. ፻፲፯፥፣፳፮) በማለት ስለተቀበሉት ይህን በማሰብ ቤተ ክርስቲያናችን ዘንባባ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ታድላለች፤ በቤተ ክርስቲያን በአራቱም ማዕዘናት ከአራቱም ወንጌል ዕለቱን የሚመለከቱ ምንባባት ይነበባሉ፡፡ ከቅዱስ ማቴዎስ (ማቴ. ፳፩፥፩-፲፯)፤ ከቅዱስ ማርቆስ (ማር. ፲፩፥፩-፲)፤ ከቅዱስ ሉቃስ (ሉቃ.፲፱፥፳፱-፴፰)፤ ከቅዱስ ዮሐንስ (ዮሐ. ፲፪፥፲፪-፳)።

በሰሙነ ሕማማት ጸሎተ ፍትሐት ስለማይፈጸም ጸሎተ ፍትሐት የሚደረገው በዚሁ ዕለት ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብ

ደብረ ዘይት

በእንዳለ ደምስስ

በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ የዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት ደብረ ዘይት ተብሎ ይጠራል፡፡ ደብረ ዘይት በኢየሩሳሌም የሚገኝና የወይራ ዛፍ በብዛት ያለበት ተራራ ነው። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀን እያስተማረ፣ ድውያንን እየፈወሰ፣ የተራቡትን እየመገበ፣ ለሚሹት እየተገለጠ ውሎ ማታ ማታ ግን ወደ ደብረ ዘይት ተራራ እየወጣ ይጸልይ ነበር፡፡ “ከዚያም በኋላ ሕዝቡን አሰናብቶ ሊጸልይ ብቻውን ወደ ተራራ ወጣ” እንዲል፡፡ (ማቴ. ፲፬፥፳፫)፤ በሆሣዕና ዕለት ከደብረ ዘይት ተነሥቶ ወደ ኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ገብቷል፤ ከደብረ ዘይት ግርጌ በጌቴ ሴማኒ ጸሎት አድርጓል፤ የአይሁድ ጭፍሮችም መጥተው የያዙት ከዚሁ ደብረ ዘይት ተራራ ነው፡፡ (ማቴ.  ፳፮፥፴፮) በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ሆኖ ስለ ዓለም ፍጻሜና ምልክቱ አስተምሯል፤ (ማር. ፲፫፥፫) በደብረ ዘይት ተራራ ወደ ሰማይ ዐርጓል፤ (ሉቃ. ፳፬፥፶፩-፶፪) በትንቢት እንደተነገረለትም በመጨረሻው ሰዓት በዓለም ፍጻሜ ለፍርድ በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ይገለጣል።

ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “እግዚአብሔር በግልጥ ይመጣል፤ አምላካችን ዝም አይልም፤ እሳት በፊቱ ይነዳል፣ በዙሪያውም ብዙ ዐውሎ አለ” (መዝ. ፵፱፥፫) እንዲል በዚህ የደብረ ዘይት ሳምንት ስለ ዳግም ምጽአት ምልክቶች፣ ስለ ምጽአት እና ተስፋው ይታሰባል። በተለይም በወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ በምዕራፍ ፳፬ በስፋት ተጽፎ እናገኛለን፡፡ ለመሆኑ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህን ዓለም ከመኖር ወደ አለመኖር ለማሳለፍ ከመምጣቱ በፊት የሚታዩ ምልክቶች ምን ምን ናቸው?

የምጽአት ምልክቶች

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከቤተ መቅደስ ወጥቶ በሄደ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ ቀርበው የቤተ መቅደሱን የሕንፃ አሠራር ካሳዩት በኋላ “ይህን ሁሉ ታያላችሁን? ድንጋይ በድንፈጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ አይቀርም” አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ይህን የነገራቸውን ነገር ሰምተው ብቻ ዝም ብለው አላለፉትም፡፡ “ንገረን ይህ መቼ ይሆናል? የመምጣትህና የዓለም ፍጻሜስ ምልክቱ ምንድን ነው?” ብለው ጠይቀውታል፡፡ (ማቴ ፬፥፩-፪)

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ደቀ መዛሙርቱ አብረውት እየዋሉ፣ አብረውት እያደሩ የቃሉን ትምህርት፣ የእጁን ተአምራት እየሰሙ እና እያዩ ምሥጢር ሳይከፈልባቸው ቆይተዋልና በቅድሚያ ከሚመጣው ሁሉ ይጠነቀቁ ዘንድ እንዲህ አላቸው፡፡ “የሚያስታችሁ እንዳይኖር ተጠንቀቁ፤ ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉና ብዙዎችንም ያስታሉ፡፡” ሲል በተማሩት ጸንተው ይኖሩ ዘንድ አሳስቧቸዋል፡፡ ይህ ማስጠንቀቂያ ብዙዎች ክርስቶስን ተቃውመው እንደሚነሡና በጠላትነት እንደሚነሡባቸው፤ ነገረ ግን የሚመጣባቸውን ሁሉ ተቋቁመው በሃይማኖታቸው ጸንተው እንዲኖሩ ያጸናቸው ዘንድ እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የነገረ ምጽአቱን ምልክቶች ሲናገር ከላይ የገለጸውን ብቻ ብሎ አላበቃም፡- “ጦርነትን፣ የጦርነትንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠንቀቁ፤ አትደንግጡ፣ ነገር ግን ፍጻሜው ገና ነው፡፡” ሲል ከሚያስቡት በላይ ከባድ ጊዜ እንደሚመጣ ነግሯቸዋል፡፡ ምልክቶቹንም ሲዘረዝር “ሕዝብ በሕዝብ ላይ፣ መንግሥትም በመንገሥት ላይ ይነሣሉ፤ በየሀገሩም ረኃብ፣ ቸነፈርም የምድር መናወጥም ይሆናል፡፡ እነዚህም የምጥ ጣር መጀመሪያ ናቸው፡፡” ብሏቸዋል፡፡

በደቀ መዛሙርቱም ላይ ስለሚደርሰው መከራ ሲገልጽ፡-”ያን ጊዜም ለመከራ አሳልፈው ይሰጡአችኋልም፣ ይገድሏችኋልም፤ ስለ ስሜም በሰው ሁሉ ዘንድ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ፡፡” በማለት የመከራውን አስከፊነት አስረድቷቸዋል፡፡ በወቅቱ ስለሚሆነውና በሰዎች ዘንድ ፍቅር ጠፍቶ አንዱ አንዱን አሳልፎ እንደሚሰጥ ሲገልጽም “ያን ጊዜም ብዙዎች ሃይማኖታቸውን ይለውጣሉ፤ እርስ በርሳቸውም አሳልፈው ይሰጣጣሉ፤ እርስ በርሳቸውም ይጣላሉ፡፡” ብሏል፡፡ (ማቴ.፳፬፥፱-፲)

ዛሬ በዘመናችን እንደምናየውና እንደምንሰማው ብዙዎች ራሳቸውን “ነቢይ” እያሉ በመጥራት እንክርዳድ የሆነውን የሐሰት ትምህርታቸውን በዓለም ላይ ይዘራሉ፡፡ ይህንንም በተመለከተ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ አድሮ “ብዙዎች ሐሰተኞች ነቢያትም ይመጣሉ፤ ብዙዎችንም ያስታሉ፤ ከዐመፅም የተነሣ ፍቅር ከብዙዎች ዘንድ ትጠፋለች፡፡ እስከ መጨረሻው የሚታገሥ ግን እርሱ ይድናል፡፡ በአሕዛብ ምስክር ሊሆን ይህ የመንግሥት ወንጌል በዓለም ሁሉ ይሰበካል፤ ያን ጊዜም ፍጻሜ ይደርሳል፡፡” ሲል በዘመኑ ስለሚሆነው ነገር በስፋት ገልጾላቸዋል፡፡ ይህም እኛ በዚህ ዘመን ያለን ክርስቲያኖችም ልናስተውለው፣ ዘወትር ከሚመጣው ክፉ ነገር ሁሉ እንጠበቅ ዘንድ በሃይማኖት በመጽናት፣ በጾም፣ በጸሎት፣ በመልካም ምግባራት ዘመኑን ልንዋጅ ይገባል፡፡

ይህ መቼ እንደሚሆን ሲገልጽም “እንግዲህ በነቢዩ በዳንኤል የተባለውን የመፍረሱን የርኵሰት ምልክት በተቀደሰ ቦታ ቆሞ ባያችሁት ጊዜ አንባቢው ያስተውል” ሲል ጊዜውን ይነግረናል፡፡ ይህም በነቢዩ ዳንኤል የተነገረው ትንቢት በቤተ መቅደስ የጥጦስ ጣዖት የታየ እንደሆነ ፍጻሜው እንደ ደረሰ ይጠቁመናል፡፡ (ማቴዎስ አንድምታ)፡፡ የጊዜውን አስከፊነት ሲያመለክትም ያን ጊዜም በይሁዳ ያሉ ወደ ተራሮች እንዲሸሹ፣ በሰገነትም ያሉ በቤት የሚገኘውን እንዳያነሡ፣ በእርሻም ያሉ ያስቀመጡትን ልብስ ለመውሰድ ወደ ኋላ እንዳይመለሱ ይነግረናል፡፡ በዚያ ወራት ለፀነሱና ለሚያጠቡ ወዮላቸው ማለቱ፡- የፀነሡት ከመንገድ ይወልዳሉ፤ የወለዱትም ወተት፣ ፍትፍት አምጡ ብለው ያስቸግሯቸዋልና ይጨነቃሉ፤ እንዲሁም ብዙዎች በዚያ ወራት ኃጢአትን በሐልዮ ፀንሰው ፣ በነቢብ ወልደው፣ በገቢር ለሚያሳድጉ ሰዎች ወዮላቸው መከራ ነፍስ አለባቸው ሲል ነው፡፡ ሽሽታችንም በክረምት ወይም በሰንበት እንዳይሆን ልንጸልይ እንደሚገባ ያስጠነቅቀናል፡፡ በክረምት ላዩ ዝናብ፣ ታቹ ውኃ ነውና መሻገር እንደማይቻል ያሳየናል፡፡ ስለ ተመረጡት ብሎ እግዚአብሔር ቀኖቹን ባያሳጥራቸው ኖሮ እጅግ አስከፊ እንደሆነም ያመለክተናል፡፡

ሐሰተኞች ነቢያት፤ ክርስቶስ በዚህ አለ እያሉ የሚያስቱ እንደሚነሡ፣ የተመረጡትን እስኪያስቱ ድረስ ታላላቅ ተአምራትን እስከማድረስ እንደሚደርሱ ይነግረናል፡፡ ከእነዚህም ምልክቶች በኋላ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መላእክቱን አስከትሎ በምድርና በምድር ያለውን ሁሉ ከመኖር ወደ አለመኖር ያሳልፍ ዘንድ ይመጣል፡፡ ይህንንም ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ ሲገልጽ “ከእነዚያም ቀኖች መከራ በኋላ ወዲያውኑ ፀሐይ ይጨልማል፣ ጨረቃም ብርሃኑን አይሰጥም፤ ከዋክብትም ከሰማይ ይወድቃሉ፤ የሰማያት ኃይል ይናወጣል፡፡ በዚያም ወራት የሰው ልጅ ምልክት በሰማይ ይታያል፡፡ ያን ጊዜም የምድር አሕዛብ ሁሉ ያለቅሳሉ፤ የሰው ልጅንም በኃይልና በብዙ ክብር በሰማይ ደመና ሲመጣ ያዩታል፡፡ መላእክቱንም ከታላቅ የመለከት ድምፅ ጋር ይልካቸዋል፡፡” (ማቴ. ፳፬፥፳፱-፴፩) ይህ ሁሉ የምጥ ጣር መጀመሪያ ነውና ነገረ ምጽአቱ እንደቀረበና በደጃፍ እንዳለ ልናስተውል ይገባል፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም በዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት “ደብረ ዘይት” ብላ ነገረ ምጽአቱን ታስባለች፡፡ ምእመናንም ነገረ ምጽአትን አስበው ከክፋት ተጠብቀውና መልካም ምግባራትን እየፈጸሙ ንስሓ ገብተው የጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙን ተቀብለው ተዘጋጅተው እንዲጠብቁ ታስተምራለች፡፡

የዕለተ ሰንበት መዝሙር (ከጾመ ድጓ)

“እንዘ ይነብር እግዚእነ ውስተ ደብረ ዘይት ወይቤሎሙ ለአርዳኢሁ ዑቁኬ ኢያስሕቱክሙ ወንበሩ ድልዋኒክሙ፤ ብዙኃን ይመጽኡ በስምየ እንዘ ይብሉ አነ ውእቱ ክርስቶስ ወዘአዝለፈ ትዕግሥቶ ውእቱ ይድኅን፤ ወአመ ምጽአቱሰ ለወልደ እጓለ እመሕያው ይትከወስ ኲሉ ኃይለ ሰማያት ወምድር፤ አሜሃ ይበክዩ ኲሎሙ ኃጥአነ ምድር፡ ወይወርድ እግዚእነ እምሰማይ ዲበ ምድር በትእዛዙ ወበቃሉ ወበ አዕላፍ መላእክቲሁ በንፍሐተ ቀርን ዘእም ኀበ እግዚአብሔር ይምሐረነ አብ በይእቲ ሰዓት እሞተ ኃጢአት እስመ ገባሬ ሕይወት ውእቱ እግዚኣ ለሰንበት፡፡”

ትርጉም:- ጌታችን በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ተቀምጦ ሳለ ለደቀ መዛሙርቱ ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ፤ተዘጋጅታችሁም ኑሩ ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉ፤ እስከ መጨረሻው የጸና እርሱ ይድናል፡፡ የሰው ልጅ በሚመጣበት ጊዜ የሰማያትና የምድርኃይላት ሁሉ ይናወጣሉ።ያን ጊዜ በምድር ኃጢአት ያደረጉ ሁሉ ያለቅሳሉ አላቸው፤ ጌታችንም ከባሕርይ አባቱ ከእግዚአብሔር አብ ዘንድ በመለከት ድምፅ ከአእላፍ መላእክት ጋር በክበበ ትስብዕት በግርማ መለኮቱ ከሰማይ ወደ ምድር ይወርደል፡፡ በዚች ዕለትም ከሞተ ኃጢአት አብ  ይማረን የሕይወት ባለቤት የሰንበትም ጌታ ነውና፡፡

ምንባባት መልእክታት

(፩ኛተሰ. ÷፲፫ፍጻ.)

“ወንድሞቻችን ሆይ÷ ስለ ሞቱ ሰዎች÷ ተስፋ እንደሌላቸው ሰዎች እንዳታዝኑ ልታውቁ እንወዳለን፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ሞቶ እንደ ተነሣ ካመንን እንዲሁ እግዚአብሔር ሙታንን በኢየሱስ ያስነሣቸዋል፤ ከእርሱም ጋር ያመጣቸዋል፡፡ …”

  ጴጥ. ÷፯-፲፬

“አሁንም ሰማይና ምድር በዚያ ቃል ለእሳት ተዘጋጅተዋል፤ ኃጥኣን ሰዎች እስከሚጠፉበት  እስከ ፍርድ ቀንም ተጠብቀዋል ነገር ግን ወንድሞቻችን ሆይ÷ ይህን አትርሱ፤ በእግዚአብሔር ዘንድ አንዲት ቀን እንደ አንድ ሺህ ዓመት÷ ሺህ ዓመትም እንደ አንድ ቀን ነውና፡፡ …”

ግብረ ሐዋርያት

(የሐዋ. ፳፬÷፩-፩)

“በአምስተኛውም ቀን ሊቀ ካህናቱ ሐናንያ ከመምህራኑና ጠርጠሉስ ከሚባል አንድ ጠበቃ ጋር ወረደ፤ ጳውሎስንም በአገረ ገዢው ዘንድ ከሰሱት፤ ጳውሎስም በቀረበ ጊዜ ጠርጠሉስ እንዲህ እያለ ይከስሰው ጀመረ፤ “ክቡር ፊልክስ ሆይ÷ በዘመንህ ብዙ ሰላምን አግኝተናል፤ በጥበብህም በየጊዜው በየሀገሩ የሕዝቡ ኑሮ የተሻሻለ ሆኖአል፤ ሥርዓትህንም በሁሉ ዘንድ ስትመሰገን  አግኝተናታል፡፡ …”

ምስባክ

(መዝ. ፵÷)

“እግዚአብሔርሰ ገሃደ ይመጽእ፤ ወአምላክነሂ ኢያረምም፤ እሳት ይነድድ ቅድሜሁ፡፡”

ትርጉም፦ እግዚአብሔር በግልጥ ይመጣል፡ አምላካችንም ዝም አይልም፤ እሳት በፊቱ ይነዳል በዙሪያውም ብዙ ዐውሎ አለ፡፡”

ወንጌል

(ማቴ. ፳፬÷፩-፭) 

“ጌታችን ኢየሱስም ከቤተ መቅደስ ወጥቶ ሄደ፤ ደቀ መዛሙርቱም ወደ እርሱ ቀርበው የቤተ መቅደሱን የሕንፃ አሠራር አሳዩት፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አላቸው÷ ይህን ሁሉ ታያላችሁን? እውነት እላችኋለሁ፤ ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ አይቀርም፡፡” (ተጨማሪውን ያንብቡ)

ቅዳሴ: – ቅዳሴ ዘአትናቴዎስ

 

“ልትድ ትወዳለህን?”

በኢየሩሳሌም በበጎች በር አጠገብ አንዲት መጠመቂያ ነበረች፡፡ ይህች መጠመቂያም በእብራይስጥ ቤተ ሳይዳ ስትባል አምስት አርከኖች ነበሯት፡፡ በዚያም ዕውሮችና አንካሶች፣ ሰውነታቸው የሰለለ በርካታ ድውያን ተጠምቀው ይድኑ ዘንድ የእግዚአብሔር መልአክ ወደ ወንዙ ወርዶ ውኃውን እስኪያነዋውጠው ድረስ ይጠባበቁ ነበር፡፡ ውኃው በሚነዋወጥበት ጊዜም በመጀመሪያ ወርዶ የተጠመቀባት ካለበት ደዌ ሁሉ ይፈወስ ነበር፡፡ (ዮ.፭፥፩-፬)

በዚህ ሥፍራ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት ያህል ድኅነትን ሽቶ ከዛሬ ነገ እድናለሁ እያለ ይጠባበቅ የነበረ በሽተኛ (መጻጉዕ) ነበር፡፡ ሕሙማኑ በቤተ ሳይዳ መጠመቂያ የተሰበሰቡት ድኅነትን ፍለጋ ነው፡፡ ዛሬ ደዌ የጸናበት ከደዌ (ከበሽታ) ለመፈወስ ወደ ጠበል እንደሚሄድ በዘመነ ብሉይ የእግዚአብሔር መልአክ (ቅዱስ ሩፋኤል) በሳምንት አንድ ቀን ወደዚያች መጠመቂያ ገብቶ ውኃውን ሲያናውጥ ቀድሞ ወደ መጠመቂያይቱ የገባ ካለበት ደዌ ሁሉ ይፈወስ ነበር፡፡ ዕለቷም ቀዳሚት ሰንበት (ሰንበተ አይሁድ) ነበረች፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት በበሽታ ሲማቅቅ የነበረውን ሰው በዚያ በቤተ ሳዳ መጠመቂያው አጠገብ ተኝቶ አገኘው፡፡ የጠየቁትን የማይረሣ፣ የለመኑትን የማይነሣ አምላክ ነውና የመጻጉዕን ስቃይ ተመለከተ፡፡ ዝም ብሎም ያልፈው ዘንድ አልወደደም፡፡ ፈቃዱንም ይፈጽምለት ዘንድ “ልትድን ትወዳለህን?” ሲል ጠየቀው፡፡ በሽተኛውም “አዎን ጌታዬ ሆይ፤ ነገር ግን ውኃው በተናወጠ ጊዜ ወደ መጠመቂያው የሚያወርደኝ ሰው የለኝም፤ እኔ በምመጣበት ጊዜ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል” አለው፡፡ (ዮሐ. ፭፥፮-፯) መጻጉዕ አጠገቡ ያለው ቆሞም በሐዘኔታ እየተመለከተ የሚጠይቀው ማን እንደሆነ አላወቀምና ለሠላሳ ስምንት ዘመናት ከአልጋው ጋር ተጣብቆ በሕመም ሲሰቃይ መኖሩን፣ እንደ ሌሎቹም በሽተኞች በፍጥነት ወደ መጠመቂያው መውረድ እንዳልቻለ ለማስረዳት ሞከረ፡፡

ጌታችን መድኃኒታቻን ኢየሱስ ክርስቶስ በቃሉ ብቻ መፈወስ ይችላልና በቅፍርናሆም የመቶ አለቃው ልጅ በታመመ ጊዜ መቶ አለቃው በእምነት ሆኖ “አቤቱ አንተ ከቤቴ ጣራ በታች ልትገባ አይገባኝም፤ ነገር ግን በቃልህ እዘዝ፣ ልጄም ይድናል“ብሎ እንደጠየቀው “እንግዲህ ሂድ እንደ እምነትህ ይሁንልህ” ብሎ በዚያች ስዓት ልጁን እንዳዳነው መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡ (ማቴ.፰፥፰) ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ለመጻጉዕ በቅድሚያ ፈቃዱን ነው የጠየቀው፡፡ መጻጉዕም ከዚያ ሲያሰቃየው ከነበረው ደዌ መፈወስ ሽቷልና ምላሹ “አዎን ጌታዬ ሆይ” ነበር፡፡

መጻጉዕ በመጠመቂያው ዳር አልጋው ላይ ተጣብቆ ሳለ ከእርሱ በኋላ መጥተው ከእርሱ በፊት ድነው የሚሄዱ ሰዎች ሲመለከት ሠላሳ ስምንት ዓመታት አሳልፏል፡፡ ዓመቱ በረዘመ ቁጥር ተስፋ ቆርጦ ቤተ ሳይዳን ቤቴ ብሎ ከመኖር በስተቀር ምንም አማራጭ አልበረውም፡፡ በቤተ ሳይዳ መጠመቂያ ስፍራ አምስት መመላለሻዎች ማለትም፡- በሽተኞች፣ አንካሶች፣ ዕውሮችና እግራቸው የሰለለ ድኅትን ሽተው የአምላካቸው ማዳን ይጠባበቁ ነበር፡፡ በየሳምንቱም መልአኩ ከሰማይ ወርዶ ውኃውን ባናውጠው ጊዜ ቀድሞ የገባው አንድ ሰው ብቻ ይድናል፡፡ ይህንን ዕድል ለማግኘት ደግሞ መጻጉዕ አልታደለም፤ ለምን ቢሉ ሌሎች ቅድመውት ወደ መጠመቂያው ይወርዳሉ፡፡ እርሱም ብቻ አይደለም አንካሶች፣ ዕውሮችና እግራቸው የሰለለ ሰዎችም አቅሙ ስለማይኖራቸው ወደ መጠመቂያው ቢወርዱም በሌላው ስለሚቀደሙ ከውኃው የሚያወጣቸው አያገኙም፡፡ ስለዚህ ከውኃው መልሶ የሚያወጣቸው ሰው ያስፈልጋቸዋል፡፡

መጻጉዕ በዚህ ስፍራ የአንድ ጎልማሳ ዕድሜን ያህል ጊዜ እግዚአብሔርን ደጅ በመጥናት አሳልፏል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዚህን ሰው ችግር ያወቀው ማንም ሳይነግረው ነው፡፡ ይፈውሰውም ዘንድ ወደ እርሱ ቀርቦ “ልትድን ትወዳለህን?” አለው፡፡ ጌታችን የሚፈልገው ይህንን ሰው መፈወስ እንጂ የራሱን ማንነት ማሳየት ስላልነበረ “ላድንህ ትወዳለህን?” አላለውም፡፡ ይህ ሰው የጌታችንን ማንነት አያውቅም፡፡ ነገር ግን ድኅነትን ናፍቋልና “ልትድን ትወዳለህን?” ባለው ጊዜ አላመነታም፡፡ “አዎን ጌታዬ ሆይ” ሲል መለሰ፡፡

ጌታችንምመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በሽተኛውን ይፈውሰው ዘንድ ፈቃዱ ስለሆነ ወደ መጠመቂያው ውረድ አላለውም፡፡ በተቃራኒው ጌታችን በቃል ብቻ መፈወስ ይችላላና “ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሒድ” አለው፡፡ ጌታችን መድኅኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ባላሰበው ባልጠበቀው መንገድ ፈወሰው፡፡ ይህ ሰው ሠላሳ ስምንት ዓመት ሙሉ ሲጠባበቃት የነበረችውን የቤተ ሳይዳ ጠበል ሳያገኝ ፣ በመልአኩ መውረድ ሳይሆን በመላእክት ፈጣሪ ቃል ተፈወሰ፡፡

ከላይ የመቶ አለቃውን ልጅ በቃል ብቻ እንደፈወሰው አይተናል፤ በተጨማሪም በጠበል ተጠምቆ መዳንን በተመለከተ ዕውር ሆኖ የተወለደውን ሰው ታሪክ ማንሣት እንችላለን፡፡ ዕውር ሆኖ በተወለደው ሰው ምክንያት ደቀ መዛሙርቱ “ይህ ሰው ዕውር ሆኖ የተወለደው በማን ኃጢአት ነው? በራሱ ነውን? ወይስ በወላጆቹ?” ብለው በጠየቁት ጊዜ “የእግዚአብሔር ሥራ ሊገለጥበት ነው እንጂ እርሱ አልበደለም፤ ወላጆቹም አልበደሉም፤ …” አላቸው፡፡ በዚህ ብቻ አላበቃም በምድር ላይ ምራቁን እንትፍ አለ፤ ምራቁንም ጭቃ አድርጎ የዕውሩን ዐይኖች ቀባው፡፡ እንዲህም አለው” ሂድና በሰሊሆም መጠመቂያ ታጠብ” አለው፤ ከቶ ለእግዚአብሔር የሚሣነው ነገር የለምና ዕውሩ በታዘዘው መሠረት ሄዶ ታጠበና እያየ ተመለሰ፡፡ (ዮሐ. ፱፥፩-፯) መጻጉዕንም ጠበል ሳያስፈልገው “አልጋህን ተሸክመህ ሂድ” ብሎታልና ተፈውሶ እርሱን ለሠላሳ ስምንት ዓመት ተሸክማው የነበረችውን አልጋ ተሸክሞ ለመሄድ በቃ፡፡

 በእነዚህ ታሪኮች እንደተመለከትነው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እርሱ በወደደው መንገድ ማለትም፡- በጠበል፣ ያለ ጠበልም፤ በቃሉ፣ በዝምታ፣ በሌሎችም መንገዶች ማዳን እንደሚችል እንረዳለን፡፡ መጻጉዕንም ሳይውል ሳያድር፣ ላገግም ሳይል በቅጽበት አፈፍ ብሎ ተነሥቶ የተሸከመችውን አልጋ ተሸክሞ ለመሄድ ችሏል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ይህንን መሠረት አድርጋ የዐቢይ ጾም አራተኛ ሳምንትን “መጻጉዕ” ብላ ሰይማዋለች፡፡

ጌታችን መጻጉዕን ብቻ ፈውሶት ሔደ? ቢባል የፈወሰው እርሱን ብቻ አይደለም፡፡ እርሱን በሥጋ ቢፈውሰውም ተአምራቱን አይተው በማመናቸው በነፍሳቸው የተፈወሱ ይበዛሉ፡፡ “ሕሙማነ ሥጋን በተአምራት፣ ሕሙማነ ነፍስን በትምህርት እየፈወሰ” እንዲሉ አበው በዚያ ሥፍራ በሥጋ ታመው በነፍሳቸው አምነው የዳኑ ብዙዎች ናቸው፡፡

ይህ ሰው ተፈውሶ አልጋውን ተሸክሞ ሲሔድ ሰንበት ለሰው ድኅነት እንደተፈጠረች ያልተረዱ አይሁድ ከአልጋው ተነሥቶ የተሸከመችውን አልጋ ተሸክሞ በአደባባይ ሲያዩት በተሠራው የድኅነት ሥራ አልተደሰቱም፡፡ በዚህም ምክንያት “ዛሬ ሰንበት ነው፤ አልጋህን ልትሸከም አይገባህም” አሉት፡፡ “እንኳን ለዚህ አበቃህ!” ያለው ግን አንድም ሰው አልነበረም፡፡

መጻጉዕም መልሶ “ያዳነኝ እርሱ አልጋህን ተሸክመህ ሂድ አለኝ” አላቸው፡፡ አይሁድም አንድ ጊዜ ጠይቀው ብቻ አላለፉትም ያዳነውን “ሰንበትን ሽሯል” ብለው ለመክሰስ ፈልገዋልና   “አልጋህን ተሸክመህ ሂድ ያለህ ሰውዬው ማነው?” በማለት ጠየቁት፡፡ በወቅቱ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመካከላቸው ተሰውራቸዋልና በቦታው ሊያገኘው አልቻለም፡፡ ነገር ግን መጻጉዕ ያዳነውን ጌታችንን በቤተ መቅደስ አገኘውና ሄዶ ያዳነው ኢየሱስ እንደሆነ ለአይሁድ ነገራቸው፡፡

መጻጉዕ ከዚህ በኋላ ወደ አይሁድ ሄዶ ጌታን መክሰሱና ለጌታ ሞት የመማከራቸው ምክንያት መሆኑ ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “እነሆ ድነሃል፤ ግን ከዚህ የባሰ እንዳያገኝህ ዳግመኛ እንዳትበድል ተጠንቀቅ” ብሎት ነበርና (ዮሐ. ፲፰፥፳፫) ነገር ግን ሊሰማው አልፈቀደም፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተያዘበት በምሴተ ሐሙስ ለሊቀ ካህናቱ አግዞ ጌታችንን በጥፊ መታው፡፡ “ወርቅ ላበደረ ጠጠር” እንዲሉ አበው የሠላሳ ስምንት ዓመት ስቃዩን ረስቶ፣ ከዚያ በላይ መከራ እንደሚያገኘው እየተነገረው ያዳነውን አምላኩን ካደ፡፡

ምንባባትና መልእክታት

የቅዱስ ጳውሎስ መልእክት (ገላ. ፭÷፩-ፍጻሜ)

“እንግዲህ ጸንታችሁ ቁሙ፤ እንደገናም በባርነት ቀንበር አትኑሩ፡፡ እነሆ÷እኔ ጳውሎስ እላችኋለሁ፤ “ብትገዘሩም በክርስቶስ ዘንድ ምንም አይጠቅማችሁም፡፡” ደግሞም ለተገዘረ ሰው ሁሉ የኦሪትን ሕግ መፈጸም እንደሚገባው እመሰክራለሁ፡፡  …” (ገላ. ፭÷፩-ፍጻሜ)

የቅዱስ ያዕቆብ መልእክት (ያዕ.፭÷፲፬- ፍጻሜ)

“ከእናንተ የታመመ ሰው ቢኖር በቤተ ክርስቲያን ያሉ ቀሳውስትን ይጥራና ይጸልዩለት፤ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም የተጸለየበትንም ዘይት ይቅቡት፡፡ የሃይማኖት ጸሎትም ድውዩን ይፈውሰዋል፤ እግዚአብሔርም ያስነሣዋል፤ ኃጢአትንም ሠርቶ እንደሆነ ይሰረይለታል፡፡ …”  (ያዕ. ፭÷፲፬- ፍጻሜ)

ግብረ ሐዋርያት (የሐዋ. ÷፩-፩)

“ጴጥሮስና ዮሐንስም በዘጠኝ ሰዓት ለጸሎት በአንድነት ወደ ቤተ መቅደስ ወጡ፡፡ ከእናቱ ማኅፀንም ጀምሮ እግሩ ሽባ ሆኖ የተወለደ አንድ ሰው ነበር፤ ወደ መቅደስም ከሚገቡት ምጽዋት ይለምን ዘንድ ሁል ጊዜ እየተሸከሙ መልካም በሚሏት በመቅደስ ደጃፍ ያስቀምጡት ነበር፡፡ ጴጥሮስንና ዮሐንስንም ወደ መቅደስ ሲገቡ አይቶ ምጽዋት ይሰጡት ዘንድ ለመናቸው፡፡ ጴጥሮስም ከዮሐንስ ጋር ትኩር ብሎ ተመለከተውና “ወደ እኛ ተመልከት” አለው፡፡ ወደ እነርሱም ተመለከተ፤ ምጽዋት እንደሚሰጡትም ተስፋ አድርጎ ነበር፡፡ ጴጥሮስም “ወርቅና ብር የለኝም ያለኝን ግን እሰጥሃለሁ፤ እነሆ በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሥተህ ሂድ” አለው፡፡ በቀኝ እጁም ይዞ አስነሣው፤ ያን ጊዜም እግሩና ቁርጭምጭሚቱ ጸና፡፡ …” (የሐዋ. ÷፩-፩)

የዕለቱ ምስባክ (መዝ.÷)

“እግዚአብሔር ይረድኦ ውስተ ዓራተ ሕማሙ፤

ወይመይጥ ሎቱ ኩሉ ምስካቤሁ እምደዌሁ

አንሰ እቤ እግዚኦ ተሣሃለኒ፤ እግዚአብሔር በደዌው አልጋ ሳለ ይረዳዋል፤ መኝታውን ሁሉ በበሽታው ጊዜ ያነጥፍለታል፤ እኔስ አቤቱ ማረኝ።” (መዝ. ፵÷፫)

ወንጌል (ዮሐ.፩-፳፬)

“ከዚህ በኋላ የአይሁድ በዓል እንዲህ ሆነ፤ ጌታችን ኢየሱስ ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ። በኢየሩሳሌምም በበጎች በር አጠገብ መጠመቂያ ነበረች፤ ስምዋንም በዕብራይስጥ ቤተ ሳይዳ ይሉአታል፣ አምስት እርከኖችም ነበሩአት፡፡ በዚያም ዕውሮችና አንካሶች፣ ሰውነታቸውም የሰለለ ብዙ ድውያን ተኝተው የውኃውን መናወጥ ይጠባበቁ ነበር፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ ወደ መጠመቂያው ወርዶ ውኃውን በሚያናውጠው ጊዜ ከውኃው መናወጥ በኋላ በመጀመሪያ ወርዶ የሚጠመቅ ካለበት ደዌ ሁሉ ይፈወስ ነበርና፡፡ በዚያም ከታመመ ሠላሳ ስምንት ዓመት የሆነው አንድ ሰው ነበር፡፡ ጌታችን ኢየሱስም በአልጋው ተኝቶ ባየ ጊዜ በደዌ ብዙ ዘመን እንደቆየ ዐውቆ “ልትድን ትወዳለህን?” አለው፡፡ ድውዩም መልሶ “አዎን ጌታዬ ሆይ ነገር ግን ውኃው በተናወጠ ጊዜ ወደ መጠመቂያው የሚያወርደኝ ሰው የለኝም፡፡ እኔ በምመጣበት ጊዜ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል፡ አለው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም “ተነሥና አልጋህን ተሸክመህ ሂድ” አለው፡፡ ወዲያውኑም ያ ሰው ድኖ አልጋውን ተሸክሞ ሄደ፤ ያች ቀንም ሰንበት ነበረች፡፡ …” (ዮሐ. ፭ ፩-፳፬)

ቅዳሴ ቅዳሴ ዘእግዚእነ

ወስብሐት ለእግዚአብሔር