ብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስ ወቅዱስ ጳውሎስ

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ሠርታ የሚነበበውን ምንባብ፣ የሚዘመን ዜማ በቀለም ለይታ ሐምሌ ፭ ቀን ከዋዜማው ጀምሮ በታላቅ ድምቀት በዓላቸውን ከምታከብላቸው ሐዋርያት መካከል የሊቀ ሐዋርያት የቅዱስ ጴጥሮስና የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ ዕረፍት አንዱ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን በምድር ላይ ሳሉ እግዚአብሔርን አምነው፣ ራሳቸውን ለእግዚአብሔር ቃል አስገዝተው ታላላቅ ተአምራትን በማድረግ ድውያንን እየፈወሱ፣ በየደረሱበት ቃለ እግዚአብሔርን ለተራቡና ለተጠሙ ምእመናን በመመገብና በማጠጣት በሚታወቁ ስፍር ቁጥር በሌላቸው ቅዱሳን የተከበበች ናት፡፡ ታሪካቸውንም ሰንዳ ለትውልድ በማስተላለፍ ብቸኛዋ ተቋም ናት፡፡ 

የሐዋርያትን ታሪክ ለማወቅ ዋናው ምንጩ የቤተ ክርስቲያን የታሪክ መጻሕፍት ናቸው። በዚህም መሠረት በቤተ ክርስቲያናችን ሐምሌ ፭ ቀን በዓላቸውን ከምታከብርላቸው ሐዋርያት መካከል የሐዋርያው የቅዱስ ጴጥሮስና የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስን ታሪክ እንደሚከተለው አቅርበነዋል።

. ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ የተወለደው በገሊላ ቤተ ሳይዳ ሲሆን እናቱ ባወጣችለት ስም ስምኦን እየተባለ ይጠራ ነበር፡፡ በጐልማሳነቱ ከወንድሙ ከእንድርያስ ጋር በገሊላ ባሕር ዓሣ በማጥመድ ሥራ ላይ ተሠማራ። በ፶፭ ዓመት ዕድሜውም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዝሙርነት ጠርቶታል፡፡ “በገሊላ ባሕር ዳር ሲመላለስም ሁለቱን ወንድማማቾች ጴጥሮስንና እንድርያስን መረባቸውን ወደ ባሕር ሲጥሉ አየ፤ ዓሣ አጥማጆች ነበሩና ጌታችን ኢየሱስም ‘ኑ ተከተሉኝ፤ ሰውን የምታጠምዱ እንድትሆኑ አደርጋችኋለሁ” አላቸው፡፡ (ማቴ. ፬፥፲፰-፳) መረባቸውንም ትተው ተከተሉት፡፡ ቅዱስ ጰጥሮስ በዚህ መንገድ ነው የተጠራውና ቤተሰቡንና ያለውን ሁሉ ትቶ ጌታችንን የተከተለው፡፡

በቂሳርያ ከተማ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያትን “እናንተስማን ትሉኛላችሁ? ብሎ በጠየቃቸው ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ” አለው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ አንተ ብፁዕ ነህ፤ በሰማይ ያለው አባቴ እንጂ ሥጋና ደም ይህን አልገለጠልህምና፡፡ እኔም እልሃለሁ፡- አንተ ዐለት ነህ፤ በዚያች ዐለት ላይም ቤተ ክርስቲያኔን እሠራታለሁ፤ የሲዖል በሮች አይበረቱባትም” አለው፡፡ ጴጥሮስ የሚለው ስም በላቲን ቋንቋ ዐለት ማለት ነው፤ በአርማይክ ደግሞ ኬፋ ይባላል። (ማቴ. ፲፮፥፲፮) በዐለት ላይ የተመሠረተ ቤት ንፋስ በነፈሰ ጊዜ እንደማይፈርስ ሁሉ በክርስቶስ የተመሠረተችው ቤተ ክርስቲያንም በንፋስ የተመሰለው ዲያብሎስ ዙሪዋን ቢዞርም ለያጠፋት እንደማይችል ያመለክታል፡፡ 

ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጥብርያዶስ ባሕር ላይ በእግሩ ሲራመድ ተመልክቶ እርሱም ይሄድ ዘንድ ፈቃድ የጠየቀ፣ መሄድ የጀመረና ማዕበሉን ፈርቶም የተጠራጠረ፣ በዚህም ምክንያት ለመስጠም የደረሰ፣ ጌታችንን ያድነው ዘንድ የተማጸነ፣ ጌታችንም በጥያቄው መሠረት ከመስጠም ያዳነው እንደሆነ ቅዱስ ወንጌል ያስተምረናል፡፡ (ማቴ. ፲፬፥፳፪-፴፫)

በቅፍርናሆም ጉባኤ ጌታን ምሥጢረ ቁርባንን ሲያስተምር አይሁድ ስላልገባቸው ወደ ኋላ አፈገፈጉ። “እናንተ ደግሞ ልትሄዱ ትወዳላችሁ?” ብሎ ጌታችን ሐዋርያትን ጠየቃቸው። “ጌታ ሆይ ወደ ማን እንሄዳለን? አንተ የዘላለም የሕይወት ቃል አለህ። እኛስ አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ እንደሆንክ እናምናለን” በማለት ሐዋርያትን ወክሎ የመለሰ እርሱ ነው። (ዮሐ. ፮፥፷፮-፷፰)

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እረኛው መሞትና ስለ በጎቹ መበተን ሲያስተምር ለደቀ መዛሙርቱ “በዚህች ሌሊት ሁላችሁም ትክኛላችሁ” ብሎ በተናገረ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ፈጥኖ “ሁሉም ቢክዱህ እንኳ እኔ ከቶ አልክድህም” (ማቴ. ፳፮፥፴፬) ብሎ ተናግሯል፡፡ ነገር ግን በዚያው ሌሊት ጌታችን በአይሁድ በምቀኝነት ይሰቅሉት ዘንድ በተያዘ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ አስቀድሞ የተናገረውን ቃል ዘንግቶ ዶሮ ሳይጮህ ሦስት ጊዜ ክዶታል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ የሚታወቅበት ሌላው ትልቁ ነገር ንስሓው ነው። አምላኩን መበደሉን ሲረዳ ተጸጽቶ ምርር ብሎ የንስሓ ዕንባን አንብቷል፡፡ 

በበዓለ ሃምሳ ለደቀ መዛሙርቱ መንፈስ ቅዱስ በወረደላቸው ጊዜ ለተሰበሰቡት አይሁድ ወንጌልን የሰበከ፣ ሦስት ሺህ ምእመናንን አሳምኖ የመጀመሪያዋን አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን በኢየሩሳሌም የመሠረተ እርሱ ነው። (የሐዋ. ፩፥፲፮-፳፫ ፤ ፪፥፲፬-፴) ልዑል እግዚአብሔር ባደለው ጸጋ ጥላው እንኳን ድውያንን ይፈውስ ነበር። (ሐዋ.  ፭፥፲፭)።

ቅዱስ ጴጥሮስ  በፍልስጥኤም፣  በሶርያ፣  በጳንጦን፣  በገላትያ፣  በቀጰዶቅያ፣ በቢታንያ እና በሮሜ ሰብኳል። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በሮሜ አንድ ዓመት ከቅዱስ ጳውሎስ ጋር ካስተማረ በኋላ የሮሜ ክርስቲያኖች እየበዙ ከመምጣታቸውም በላይ የክርስትናው ጉዞ እስከ ሮማ ባለሥልጣናት ደረሰ። የኔሮን የቅርብ ባለሥልጣናት የሆኑት የአልቢኖስና የአግሪጳ ሚስቶች ወደ ክርስትናው ገቡ። በዚህን ጊዜ ኔሮን ንጉሠ ሮማ በቅንዓት ተነሣባቸው።

ኔሮን በሮም የነገሠው በ፶፬ ዓ.ም. ነው። በመንግሥቱ መጀመሪያ ደግ ሰው ነበረ። ነገር ግን በነገሠ በዓመቱ የጨካኝነት ዐመሉ ብቅ ማለት ጀመረ እና የአባቱን ልጅ አስገደለ። በ፶፱ ዓ.ም. ደግሞ እናቱን በመርዝ ገደለ። በ፷፫ ዓ.ም. እያስተማረ ያሰደገውን መምህሩን ፣ በ፷፪ ዓ.ም. የልጅነት ሚስቱን አግታሺያን አስገደለ። ከእርስዋ በኋላ ያገባትን ሚስቱንም ፓፒያን ገደላት። በ፷፬ ዓ.ም ከከተማው ወጣ ብሎ በሚገኘው ቤተ መንግሥቱ ተቀምጦ የሮማን ከተማ እሳት ለቀቀባት። የሮም ሕዝብ በደረሰው አደጋ እጅጉን ተቆጣ። ኔሮንም በክርስቲያኖች አመካኘ። በዚህም የተነሣ በሮማ ከተማ ሁለት ዓይነት ወሬ መናፈስ ጀመረ።

የሮማ አማልክት በክርስቲያኖች ሃይማኖት ስለተቆጡ በከተማዋ እሳት አዘነቡባት የሚለው የመጀመሪያው ሲሆን ክርስቲያኖች ሆን ብለው ከተማዋን አቃጥለዋታል የሚለው ደግሞ ሁለተኛው ወሬ ነበር። የከተማው መጋየት ያበሳጨው የሮማ ሕዝብ፣ ክርስቲያን የሆነውን ሁሉ እያወጣ መግደሉን ተያያዘው። ይህን የሰሙት የአግቢኖስና የአግሪጳ ሚስቶች (የሮም ባለሟሎች ነበሩ) “አንተ ትረፍልን” ብለው በከተማዋ ግንብ በገመድ አሥረው በቅርጫት በማውረድ ቅጥረ ሮማን ለቅቆ እንዲወጣ አደረጉት።

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በኦፒየም ጎዳና ጉዞውን ቀጠለ። ሮማን ለቀቀ። እያዘገመ በሸመገለ ጉልበቱ ሲጓዝ አንድ ቀይ ጐልማሳ ወደ እርሱ ሲመጣ አየ። እየቀረበ ሲመጣ ጌታችን መሆኑን ተረዳ። ወዲያው በፊቱ ተደፋና “ጌታዬ ወዴት እየተጓዝክ ነው?” አለና ጠየቀው። “ዳግም በሮም ልሰቀል” አለው። በዚህ ሰዓት ቅዱስ ጴጥሮስ አዘነና እንደገና ወደ ሮም ተመለሰ። የኔሮን ወታደሮች እየፈለጉት ነበር። “እነሆኝ ስቀሉኝ” አለ ቅዱስ ጴጥሮስ። ያን ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስን ይዘው አሠሩት። ከጥቂት ቀናት በኋላም ሮማውያን የመስቀያውን እንጨት አቀረቡለት። ያን ጊዜ “እኔ እንደ ጌታዬ ልሰቀል አይገባኝም” በማለት ቁልቁል እንዲሰቅሉት ለመነ። እንደለመነውም ሐምሌ ፭ ቀን ፷፯ ዓ.ም ቁልቁል ሰቅለውት በሰማዕትነት ዐረፈ።

. ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ዘሩ ከዕብራዊያን፣ ከብንያም ነገድ ሲሆን የተወለደውም በጠርሴስ ከተማ ነው። ጠርሴስ በንግድዋ የታወቀች የኪልቂያ ዋና ከተማ ናት። በከተማዋ እስከ አምስት መቶ ሺህ የሚገመቱ ከየሀገሩ የተሰባሰቡ ሕዝቦች ነበሩባት። ሮማውያን በሥራቸው ለሚተዳደሩት ሕዝቦች ሮማዊ ዜግነትን ይሰጡ ስለነበር፥ የቅዱስ ጳውሎስ አባት በዜግነት ሮማዊ ነበር። ይህም ለቅዱስ ጳውሎስ ተላልፎለታል።

ቅዱስ ጳውሎስ በኢየሩሳሌም ከታወቀው የገማልያል ትምህርት ቤት ገባ። በዚያም የአይሁድን ሕግና ሥርዓት እየተማረ እስከ ፴ ዓመቱ ቆየ። በ፴ ዓመቱ የአይሁድ ሸንጎ አባል ሆኖ ተቆጠረ።ለኦሪታዊ እምነቱም ቀናተኛ በመሆኑ ክርስቲያኖችን ያሳድድ ነበር። ሊቀ ዲያቆናት ቅዱስ እስጢፋኖስ ተከሶ በአይሁድ ሸንጎ ፊት በቀረበ ጊዜ በድንጋይ ተወግሮ በሰማዕትነት ሲያርፍ የወጋሪዎችን ልብስ በመጠበቅ የተባበረ ነው። “ሰማዕቱ ቅዱስ እስጢፋኖስን በገደሉትም ጊዜ እኔ እዚያ አብረአቸው ነበርሁ፤ የገዳዮችንም ልብስ እጠብቅ ነበር” እንዲል፡፡ (ሐዋ. ፳፪፥፳)

ቅዱስ ጳውሎስ በደማስቆ ከተማ ብዙ ክርስቲያኖች መኖራቸውን ሲሰማ ወደ ሊቀ ካህናቱ ቀርቦ ክርስቲያኖችን ለማጥፋት የሚያስችለውን የፈቃድ ደብዳቤ አገኘ። ከዚህም በኋላ ጭፍሮችን አስከትሎ ወደ ደማስቆ አመራ። ሐዋርያው ጳውሎስ ወደ ከተማዋ ለመድረስ ጥቂት ሲቀረው ነበር ከሰማይ የወረደው ብርሃን አካባቢውን ያለበሰውና “ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ?” የሚለውን ድምፅ የሰማው። ሐዋርያው ጳውሎስም “ጌታ ሆይ ማን ነህ?” ብሎ ጠየቀ። “አንተ የምታሳድደኝ እኔ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ። የመውጊያውን ብረት ብትቃወም ለአንተ ይብስብሃል” ሲል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተናገረው። ያን ጊዜም በወደቀበት ሆኖ እየተንቀጠቀጠ “ጌታ ሆይ ምን አደርግ ዘንድ ትወዳለህ?” ሲል ጠየቀ። ከዚህ በኋላ ተነሥቶ ወደ ደማስቆ እንዲገባ ተነገረው። ነገር ግን ዓይኖቹ ማየት አልቻሉም፤ እየመሩም ወደ ደማስቆ ሐናንያ ወደሚባል ሰው ወሰዱት፡፡ ሐናንያም እጁን ጭኖ ጸለየ፡፡ ከዓይኖቹም እንደ ቅርፊት ያለ ነገር ተገፎ ወደቀለት፣ ዓይኖቹም ተገለጡ፣ ተነሥቶም ተጠመቀ፡፡ ስለ ጌታችንም “የእግዚአብሔር ልጅ ነው” በማለት መስበኩን ቀጠለ፡፡ (የሐዋ. ፱፥፩-፲፰)

አይሁድም ቅዱስ ጳውሎስን ይገድሉት ተነሡ። ሐዋርያት ግን የቅዱስ ጳውሎስን መመለስ ለማመን ቢቸገሩም በርናባስ ወስዶ የጳውሎስን መመለስ በመተረክ እንዲያምኑት አደረጋቸው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በጠርሴስ ከተማ ለዘጠኝ ዓመታት ቆይቷል። ከኢየሩሳሌም ውጭ የአሕዛብ ከተማ በነበረችው በአንጾኪያ የክርስትና ሃይማኖት ተስፋፋ።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመጀመሪያው ጉዞ ያደረገው ከኢየሩሳሌም ወደ አንጾኪያ ከተመለሰ በኋላ በልዑል እግዚአብሔር ጥሪ በአሕዛብ ሀገር ወንጌልን ለመስበክ ከበርናባስ ጋር ወጡ። በዚህ ጉዞአቸው በጠቅላላው ወደ ሁለት ሺህ ኪሎ ሜትር የሚደርስ መንገድ በእግር ተጉዟል። ይህም ጉዞ የተከናወነው በ፵፮ ዓ.ም. አካባቢ ነው። የተሸፈኑትም ሀገሮች ሲሊንውቂያ፣ ቆጵሮስ፣ ስልማን፣ ጳፋ፣ ጰርጌን፣ ገላትያ፣ ጵስድያ፣ ኢቆንዮን፣ ሊቃኦንያ፣ ልስጥራ፣ደርቤን፣ጵንፍልያ፣አታልያና አንጾኪያ ናቸው።

ሁለተኛው ጉዞ የተከናወነው በ፶ ዓ.ም. ገደማ ነው። በመጀመሪያው ጉዞ ማርቆስ አብሮ ተጉዞ ነበር። ነገር ግን ጵንፍልያ ከተማ ሲደርስ እናቱ ስለናፈቀችው መመለስ በመፈለጉ በርናባስ ወደ ኢየሩሳሌም ይዞት መጣ። ስለዚህም በሁለተኛው ጉዞ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲላስን ይዞ ወደ ኪልቂያ ሶርያ ሲጓዝ በርናባስ ደግሞ ማርቆስን አስከትሎ ወደ ቆጵሮስ ሄደ። በዚህ ጉዞው ቅዱስ ጳውሎስ እስከ ግሪክ ደርሶአል። የተጓዘባቸውና ያስተማረባቸው ከተሞችም፦ ደርብያ፣ ልስጥራ፣ፍርግያ፣ ገላትያ፣ ሚስያ፣ጢሮአዳ፣ ሳሞትራቄ፣ ናፑሊ፣ ፊልጵስዩስ፣ ተሰሎንቄ፣ በርያ፣አቴና፣ ቆሮንቶስ፣ አንክራኦስ፣ አፌሶን፣ ቂሳርያ፣ ኢየሩሳሌምና አንጾኪያ ናቸው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመንፈስ ልጁ ጢሞቴዎስን ያገኘው በዚሁ ጉዞው በልስጥራ ከተማ ነው።

ሦስተኛው ጉዞ የተከናወነው በ፶፬ ዓ.ም. ሲሆን የተሸፈኑትም ሀገሮች የሚከተሉት ነበሩ። ገላትያ፣ ፍርግያ፣ ኤፌሶን፣ መቄዶንያ፣ ፊልጵስዩስ፣ ቆሮንቶስ፣ ጢሮአዳ፣ አሶን፣ ሚልጢኒን፣ አንጠቀከስዩ፣ ትሮጊሊዩም፣ መስጡ፣ ቆስ፣ ሩድ፣ ጳጥራ፣ ጢሮስ፣ ጵቶልማይስ፣ ቂሳርያ፣ ኢየሩሳሌም ናቸው።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከልዩ ልዩ ሀገሮች ክርስቲያኖች የሰበሰበውን ዕርዳታ ለኢየሩሳሌም ቤተ ክርስቲያን በመያዝ ሦስተኛውን ጉዞ አጠናቅቆ ኢየሩሳሌም ገባ። ነገር ግን ኢየሩሳሌም የገባበት ጊዜ የፋሲካ በዓል ስለነበር ከልዩ ልዩ ሀገሮች የተሰበሰቡ አይሁድ በከተማዋ ነበሩ። እነዚህ በዝርወት የሚኖሩ አይሁድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን በየሀገራቸው በትምህርቱ የተነሣ ሲቃወሙት የነበሩ ናቸው።

መስበኩን በመቀጠሉ ምክንያት በ፶፰ ዓ.ም በሮም ለቁም እሥር ተዳረገ። የሁለቱን ዓመት የቁም እሥር እንደጨረሰ ወደ ኔሮን ፍርድ ቤት ቀረበ። ይህም በ፷ዎቹ ዓ.ም ነው። በፍርድ ቤቱ በተደረገው ምርመራ የሮሜን ሕግ የሚቃወም ምንም ወንጀል ስላልተገኘበት በነፃ ተለቀቀ፤ ከዚህ በኋላ ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አራተኛውንና የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ያልመዘገበውን ጉዞውን ያደረገው። ይህ ጉዞው በመታሠሩ አዝነው ተክዘው የነበሩ ክርስቲያኖችን ለማጽናናት የጀመራቸውን ሥራዎች ፍጻሜ ለማየት የተደረገ ጉዞ ነው። በዚህም ጉዞው ኢየሩሳሌምን፣ ኤፌሶንን፣ ሎዶቅያን፣ መቄዶንያን፣ ቀርጤስን፣ ጢሮአዳን፣ ድልማጥያን፣ እልዋሪቆን፣ ኒቆጵልዮን፣ ብረንዲስን፣ ጎብኝቷል። በዚህ የመጨረሻ የስብከት ጉዞው ለአራት ዓመታት ያህል ቆይቷል።

በመጨረሻ በ፷፬ ዓ.ም. ኔሮን በጥጋቡ የሮማ ከተማ ስትቃጠል ምን እንደምትመስል ማየት እፈልጋለሁ ብሎ አቃጠላት። የሮም ሕዝብ በከተማው መቃጠል በማዘኑና በማመፁ ነገሩን ሁሉ በክርስቲያኖች ላይ አሳበበ። በዚህም የተነሣ ክርስቲያን የተባለ ሁሉ መሰደድ፣ መሠየፍ፣ መታረድ እጣ ፈንታው ሆነ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም በኒቆጵልዮን ከተማ ሲያስተምር በ፷፭ ዓ.ም. ተይዞ ወደ ወኅኒ ገባ። ለሁለት ዓመት ከስድስት ወር በጨለማ ቤት ታሥሮ ከቆየ በኋላ በ፸፬ ዓመት ዕድሜው በሮም ከተማ በኦስትያ መንገድ አንገቱን ተሰይፎ በ፷፯ ዓ.ም. ሐምሌ ፭ ቀን በሰማዕትነት ዐረፈ።

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ሁለት፣ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ ዐስራ አራት መልእክታትን ጽፈዋል። የቅዱሳኑ ሐዋርያት ረድኤትና በረከታቸው ከሁላችን ጋር ይሁን፤ አሜን።

ምንጭ፦ መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ ሐምሌ ፭፤ መጽሐፍ ቅዱስ ሐዲስ ኪዳን፣

           ቤተ ክርስቲያንህን ዕወቅ ቁጥር ፩፤ በማኅበረ ቅዱሳን

ማኅበረ ቅዱሳን የድጋፍ ማሰባሰቢያ የዕጣ ትኬት ማዘጋጀቱ ተገለጸ

ማኅበረ ቅዱሳን የተቋማዊ ለውጥ ትግበራን ተግባራዊ በማድረግ አገልግሎቱን እያከናወነ የሚገኝ ሲሆን ይህን ተከትሎ በተከለሰው የግቢ ጉባኤያት ሥርዓተ ትምህርት መሠረት በግቢ ጉባኤያት (በዩኒቨርሲቲዎች እና ኮሌጆች) ለሚማሩ ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች በሃይማኖት እና በሥነ ምግባር አንጾ ለማውጣት ለሚተገብራቸው የመምህራን ማፍራት፣ የመመማሪያ መጻሕፍት ዝግጅት፣ እንዲሁም የቨርቹዋል ሥልጠና ማእከል ማቋቋሚያ የሚውል የድጋፍ ማሰባበሰቢያ የዕጣ ትኬት አዘጋጅቷል፡፡ የዕጣ ትኬቱንም ከሐምሌ 01 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ ሥርጭት እና ሽያጭ መጀመሩን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ሥራ አስፈጻሚ የሆኑት አቶ አበበ በዳዳ ገልጸዋል፡፡

የዕጣ ትኬቱም ለግቢ ጉባኤ ተማሪዎችና ቤተሰቦቻቸው፣ ለማኅበሩ አባላት እና ቤተሰቦቻቸው እንዲሁም ለሌሎች ደጋፊ ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን የቀረበ ሲሆን የአንድ ትኬት ዕጣ ዋጋ 100 (አንድ መቶ ብር) ብር መሆኑን አቶ አበበ ገልጸዋል፡፡

የዕጣ ትኬቱም ልዩ ልዩ ሽልማቶችን ያካተተ ሆኖ ተዘጋጅቷል፡፡ ከሽልማቶቹ መካከል፡-

  • ለሰባት ቀናት ወደ ቅድስት ሀገር የኢየሩሳሌም ጉዞ (ጉብኝት)፣
  • ለሰባት ቀናት ወደ ግብጽ ገዳማት ጉዞ (ጉብኝት)፣
  • ለአምስት ቀናት ከአንድ ቤተሰብ ጋር (በአውሮፕላን) ከኢትዮጵያ ገዳማት ወደ አንዱ መንፈሳዊ ጉብኝት እና ሌሎችንም ልዩ ልዩ ዕጣዎችን አካትቷል፡፡

ትኬቱን ከግቢ ጉባኤ ተማሪዎች፣ ከማኅበረ ቅዱሳን አባላት እንዲሁም በማኅበሩ የልማት ተቋማት ሱቆች ማግኘት ትችላላችሁ፡፡

ዕጣው የሚወጣበት ቀን ኅዳር 21 ቀን 2018 ዓ.ም ነው፡፡

ዘገባው፡- የማኅበረ ቅዱሳን ግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ነው፡፡ 

በደረጃ ሁለት ተተኪ አመራርነት ሥልጠና የወሰዱ ሠልጣኞች ተመረቁ

በማኅበረ ቅዱሳን የደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ጽ/ቤት በሥሩ ለሚገኙና ከተለያዩ ግቢ ጉባኤያት ለተወጣጡ ፸፮ አገልጋዮች የደረጃ ሁለት ተተኪ አመራርነት ሥልጠና በመስጠት አስመረቀ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችን በሥራ አስፈጻሚነት የሚመሩትን አባላት አቅም ለመገንባትና የማኅበሩን እንዲሁም የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት በሚገባ የተረዱ፤ መንፈሳዊ ሕይወታቸውም የተስተካከለና አርአያ ሆነው ግቢ ጉባኤን ሊመሩ የሚችሉ የአመራር አባላትን ለማፍራት ታስቦ በክረምት ወቅት በተለያዩ ማስተባበሪያዎች ሥልጠና እየተሰጠ ይገኛል፡፡ በዚህም መሠረት በሐዋሳ እና በወላይታ ሶዶ የሥልጠና ማእከላት የደረጃ ሁለት ተተኪ አመራርነት ሥልጠና ተሰጥቷል፡፡ በሐዋሳ የሥልጠና ማእከል ከሐዋሳ፣ ከባሌ ሮቤ፣ ከሻሸመኔ፣ ከዲላ ማእከላትና ከቡሌ ሆራ ልዩ ወረዳ ማእከል ከሚገኙ ግቢ ጉባኤያት ውስጥ ለተመለመሉ ፳፮ አገልጋዮች የደረጃ ሁለት የተተኪ አመራርነት ሥልጠና ከሰኔ ፩ እስከ ሰኔ ፯ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም. ሲሰጥ ቆይቷል፡፡

ሥልጠናዎቹም፡-  

  • የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመሪነት ሚና ትናንት፣ ዛሬ እና ነገ
  • ኦርቶዶክሳዊነት ሕይወቱና ክህሎቱ
  • የአኀት አብያተ ክርስቲያናት ተሞክሮ
  • ዓለማዊነት (Secularism) ከኦርቶዶክስ እሳቤና ኑሮ አንጻር
  • ማኅበረ ቅዱሳን ማነው?

በሚሉና ሌሎችም ርእሰ ጉዳዮች ላይ ልምድ ባላቸው መምህራን የተሰጠ ሲሆን ከሥልጠናውና ከአሠልጣኖቹ የሕይወት ተሞክሮና ልምድ ዕውቀት እንዳገኙም ሠልጣኞቹ አስረድተዋል፡፡ በሥልጠናውም ሦስት እኅቶችና ፳፫ ወንዶች ተሳትፈው ሰኔ ፯ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም ተጠናቋል፡፡

በተመሳሳይ በወላይታ ሶዶ ማእከል በርእሰ አድባራት ወገዳማት ደብረ መንክራት አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንድነት ገዳም ከአርባ ምንጭ፣ ከወላይታ ሶዶ፣ ከጂንካ፣ ከሆሳዕና እና ከዱራሜ ማእከላት ስር ከሚገኙ ግቢ ጉባኤያት የተመለመሉ ፴፰ ወንዶችና ፲፪ እኅቶች በድምሩ ፶ ሠልጣኞች ከሰኔ ፰ እስከ ፲፬ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም የደረጃ ሁለት አመራርነት ሥልጠና ወስደው ተመርቀዋል፡፡

የደረጃ ሁለት የአመራርነት ሥልጠናው በሐዋሳ ማእከል ከተሰጠው ሥልጠና ጋር ተመሳሳይ ርእሰ ጉዳዮችን ያካተተ ሲሆን በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ የወላይታ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ ተገኝተዋል፡፡ ብፁዕነታቸው ባስተላለፉት መልእክትም የተካሄደው ሥልጠና እጅግ ጠቃሚ የሆነና ሊበረታታ የሚገባ መሆኑን ጠቅሰው ሠልጣኞች በተሰጠው ሥልጠና እግዚአብሔርን በመፍራት ሕይወታችሁን እንድትመሩ፣ የተቀበላችሁትንም መክሊት በማትረፍ፣ በሄዳችሁበት ሁሉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንና ሀገራችሁን ማገልገል ይጠበቅባችኋል” በማለት የአደራ መልእክትና አባታዊ ቡራኬ ሰጥተዋል፡፡

በሁለቱም ማስተባበሪያዎች በሁለት ዙር በተሰጡት ሥልጠናዎች ፷፩ ወንዶችና ፲፭ ሴቶች በድምሩ ፸፮ የደረጃ ሁለት ተተኪ አመራር ሠልጣኞች ተሳትፈውበታል፡፡ በሥልጠና ቆይታቸውም ሠልጠኞቹ ስለ አገልግሎትና ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚገጥሟትን ፈተናዎች ትሻገር ዘንድ የሚጠበቅባቸውን አገልግሎት እንዲያበረክቱ ኀላፊነት እንዲሰማቸው ያደረገና ጥሩ ተሞክሮም ማግኘት እንዲችሉ የረዳቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የተተኪ አመራርና መምህራን ሥልጠና በመካሄድ ላይ እንደሚገኝ ተገለጸ

ማኅበረ ቅዱሳን በስድስት ማስተባበሪያዎችና በዐሥራ አንድ ሥልጠና ማእከላት የደረጃ ሁለት ተተኪ አመራርና መምህራን ሥልጠና በመስጠት ላይ እንደሚገኝ በማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ የተቋማዊ ልማት አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባባሪ ሓጋዚ አብርሃ ገለጹ፡፡

የደረጃ ሁለት ተተኪ አመራርነት ሥልጠናው በመሐል ማእከላት፡- በአዲስ አበባ፣ በአዳማ (በአፋን ኦሮሞ) ፤ በደቡብ ማስተባበሪያ፡- በወላታና ሐዋሳ፤ በምሥራቅ ማስተባበሪያ፡- ድሬዳዋ፤ በሰሜን ምሥራቅ ማስተባበሪያ፡- ደሴ፤ በሰሜን ምዕራብ ማስተባበሪያ ባሕር ዳር፣ ጎንደር፣ ደብረ ማርቆስ ለሰባት ቀናት ሲሰጥ ቆይቶ ተጠናቋል፡፡ በምዕራብ ማስተባበሪያ ጅማ እና በመሐል ማእከላት ማስተባበሪያ ደብረ ብርሃን የሚሰጠው ሥልጠና ደግሞ በሐምሌና ነሐሴ ለማካሄድ ዝግጅት እየተደረገ የሚገኝ ሲሆን ሠልጣኞቹ በየማስተባበሪዎቻቸው በሚገኙ ግቢ ጉባኤያት በልዩ ልዩ የአገልግሎት ዘርፎች ሲያገለግሉ የነበሩ መሆናቸው ታውቋል፡፡

በዚህ ሥልጠናም “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የመሪነት ሚና፣ የምዕራባዊነትና የአረባዊነት መዳረሻ ከኦርቶዶክሳዊ ሉላዊነት አንጻር፣ የኦርቶዶክሳዊነት ሕይወትና ክሂሎት፣ የአኀትና የምሥራቅ ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ተሞክሮ” በሚሉና በሌሎችም ዋና ዋና ርእሰ ጉዳዮች ሥልጠናው የተሰጠ ሲሆን ምሽት ላይ በሚኖረው መርሐ ግብርም የግቢ ጉባኤያት የእርስ በርስ የልምድ ልውውጥና ተሞክሮ በተሳካ ሁኔታ ማካሄድ መቻሉን አስተባባሪው ገልጸዋል፡፡

የደረጃ ሁለት የአዳዲስ ተተኪ መምህራን ሥልጠናም በምሥራቅ ማስተባበሪያ ድሬዳዋ እና በሰሜን ምዕራብ ማስተባበሪያ ባሕር ዳር ሲሰጥ ቆይቶ የተጠናቀቀ ሲሆን፤ በጎንደርና በደብረ ማርቆስ የሚሰጠው ሥልጠና በመካሄድ ላይ ይገኛል፡፡ በሌሎች ሰባት ማእከላት ደግሞ በሐምሌና በነሐሴ ወራት እንደሚሰጥ ይጠበቃል፡፡

የደረጃ ሁለት መምህራን ሥልጠናው ከ፳፭-፴ ቀናት የሚወስድ ሲሆን ዐሥር ርእሰ ጉዳዮችን እንዳካተተ ተገልጿል፡፡ በዚህም መሠረት “የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ሕይወተ ቅዱሳን፣ ክርስትና በሀገራዊ ጉዳዮች፣ የስብከት ዘዴ፣ ሃይማኖትና ሳይንስ፣” እንዲሁም ሌሎች ርእሰ ጉዳዮች ተካተዋል፡፡ በዚህም መሠረት በደረጃ ሁለት ተተኪ አመራርነት ፫፻፷፮፣ በተተኪ መምህርነት ፻፵ ከተለያዩ ማእከላት የተውጣጡ ሠልጣኞች እንደተካተቱ ግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ የተቋማዊ ልማት አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባባሪ ሓጋዚ አብርሃ ገልጸዋል፡፡     

አዲስ አበባ ማእከል የግቢ ጉባኤት ተማሪዎችን አስመረቀ

በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል በልዩ ልዩ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መደበኛ ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የነበሩና በበርካታ ሰንበት ትምህርት ቤቶች መንፈሳዊ ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የቆዩ ከአንድ ሺህ ሁለት መቶ ሠላሳ በላይ የግቢ ጉባኤት ተማሪዎችን በማኅደረ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያምና ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን እንዲሁም በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽርሐ ተዋሕዶ አዳራሽ ሰኔ ፳፪ ቀን ፳፻፲፯ ዓ.ም አስመረቀ።   

በምርቃት መርሐ ግብሩ ላይ የወንጌል ትምህርት፣ በተመራቂዎች ያሬዳዊ ወረብና የበገና ዝማሬ የቀረበ ሲሆን በከፍተኛ ማዕረግ ለተመረቁ ተማሪዎች የምስጋና የምስክር ወረቀት ተሰጥቷቸዋል፡፡

ተመራቂዎች በበኩላቸው በግቢ ጉባኤ ሕይወት ውስጥ ማለፋቸው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከዓለማዊ ፈተናዎች ጠብቃ እንዳቆየቻቸውና ለውጤታማነታቸው ትልቁን ድርሻ እንደነበራት በመመስከር በቀጣይም በተሰማሩበት የሥራ ዘርፍ ሁሉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በማገልገል ኃላፊነታቸውን እንደሚወጡ ገልጸዋል፡፡

በማኅደረ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያምና ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያንና በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ በተከናወኑ መርሐ ግብሮች ላይ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና የተመራቂ ቤተሰቦች የተገኙ ሲሆን ተመራቂዎች የአደራ መስቀል ተበርክቶላቸዋል።

በማኅደረ ስብሐት ቅድስት ልደታ ለማርያምና ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ስድስት መቶ ሃምሳ፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ደግሞ አምስት መቶ ሰማንያ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ማስመረቁን የአዲስ አበባ ማእከል ሚዲያ ክፍል ዘግቧል፡፡

ምንጭ፡-  የአዲስ አበባ ማእከል ሚዲያ ክፍል

ማኅበረ ቅዱሳን በየከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚያስተምራቸውን የግቢ ጉባኤት ተማሪዎችን አሰመረቀ

ማኅበረ ቅዱሳን ላለፉት ዓመታት በየከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መደበኛ ትምህርታቸውን ሲከታተሉና በግቢ ጉባኤያት መንፈሳዊ ትምህርት በመማር ላይ ይገኙ የነበሩ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን ከሰኔ 2017 ዓ.ም ጀምሮ ከየማእከላቱ በማስመረቅ ላይ ይገኛል፡፡

የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ትምህርታቸውን ያጠናቀቁ ተማሪዎችን በልዩ ልዩ መርሐ ግብራት በማስመረቅ ላይ መሆናቸውን ተከትሎ ማኅበረ ቅዱሳንም ባሉት መዋቅሮቹ መሠረት ከየማእከላቱ መረጃዎች እየደረሱን ይገኛሉ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ፡- ጅግጂጋ ዩኒቨርሲቲ፣ አዳማ ሳንስና ቴክሎሎጂ ዩኒቨርሲቲ፣ ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ፣ ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ፣ ወሎ ዩኒቨርሲቲ፣ ወላታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ፣ ጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ፣ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ … ሌሎችም በማስመረቅና ለማስመረቅ ዝግጅት በማድረግ ላይ እንደሚገኙ የደረሱን መረጃዎች ያለመክታሉ፡፡

በ2017 ዓ.ም ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ከተመረቁት መካከል በየትምህርት ክፍሎቻቸውና ከየተቋማቱ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ የሜዳልያና የዋንጫ ተሸላሚዎች ሆነዋል፡፡

ከእነዚህም ውስጥ ጥቂቶቹን በፎቶ ግራፍ አስደግፈን እናቀርባለን፡፡ ዝርዝር መረጃዎችን በቀጣይ ይዘን እንመጣለን፡፡

ሕንጸተ ቤተ ክርስቲያን

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከምታከብራቸው የእመቤታችን ፴፫ በዓላት አንዱ ሰኔ ፳ ቀን በኬልቄዶን አውራጃ በቂሣርያ አገር የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ያለ እንጨት፣ ያለ ጭቃና ያለ ውኃ በሦስት ድንጋዮች በተወደደ ልጇ በጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የታነጸበት ዕለት ነው፡፡  

ቅዱስ ጳውሎስና ቅዱስ በርናባስ ጌታችን በዐረገ በስምንተኛው ዓመት ለፊልጵስዩስ ሰዎች የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ወንጌል ካስተማሩ በኋላ በክርስቶስ ስም አሳምነው በርካታ አሕዛብን በማጥመቅ ቤተ ክርስቲያን ይሠራላቸው ዘንድ ፈለጉ፡፡ ነገር ግን ጌታችን በሊቀ ሐዋርያነት የሾመው ቅዱስ ጴጥሮስ እያለ እንዴት እኛ ይህንን እናደርጋለን? በማለት ቅዱስ ጴጥሮስ ወደ ፊልጵስዩስ ይመጣ ዘንድ መልእክት ላኩበት፡፡ እርሱም ከቅዱስ ዮሐንስ ጋር መጥቶ ከቅዱስ ጳውሎስ እና ቅዱስ በርናባስ ጋር በኢየሩሳሌም ተገናኙ፡፡

በዚያም በአንድነት ሱባኤ ይዘው ከቆዩ በኋላ ጌታችን የሞቱትን አስነሥቶ፣ ያሉትንም ከያሉበት ቅዱሳን ሐዋርያትን ጠርቶ በፊልጵስዩስ አገር ሰብስቦ “በእናቴ በድንግል ማርያም ስም ከጽንፍ እስከ ጽንፍ የሚሠሩትን የአብያተ ክርስቲያናት ሥራ

ላሳያችሁ፤ ሥርዓቱንም ላስተምራችሁ”ብሎ ወደ ምሥራቅ ይዟቸው ወጣ፡፡ በዚያም ሥፍራ ተራርቀው የነበሩ ሦስት ደንጊያዎች ነበሩ፡፡ ጌታችንም ሦስቱን የተራራቁ ድንጋዮችን በተአምራት አቀራርቦ አንሥቶ ጎተታቸው፡፡ ድንጋዮቹም እንደ ሰም ተለጠጡ፣ እንደ ግድግዳም ሆኑ፡፡

ቁመቱን በ፳፬፤ ወርዱን በ፲፪ ክንድ ለክቶ ለቅዱሳን ሐዋርያት ሰጣቸው፡፡ የብርሃን ምሰሶ ከሰማይ ወረደ፣ በሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም አምሳያ አድርጎ አነጻት ሁለንተናዋም ተጠናቀቀ፡፡ ዛሬም በዕለተ ዐርብ በዕፀ መስቀል ላይ ጌታችን የተቆረሰውን ቅዱስ ሥጋ፣ ያፈሰሰውን ቅዱስ ደም ቅዱሳን መላእክት በብርሃን ፅዋ ቀድተው በዓለም ሁሉ ረጭተውታል፡፡ ስለሆነም የጌታችን ደም በነጠበባቸው ቦታዎች ሁሉ ላይ ዛሬም ድረስ ቤተ ክርስቲያን ይሠራባቸዋል፡፡  

ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑ የተሠራውም ጌታችን በዐረገ በ፲፱ኛው፤ እመቤታችን በዐረገች በ፬ኛው ዓመት ሰኔ ፳ ቀን ሲሆን፣ በ፳፩ኛው ቀን (በማግሥቱ) ኅብስት ሰማያዊ፣ ጽዋዕ ሰማያዊ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ወረደ፡፡ ጌታችንም ከእመቤታችን ጋር በቅዱሳን መላእክት ታጅበው ከሰማየ ሰማያት መጥቶ እመቤታችንን ታቦት፤ እርሱ ሠራዒ ካህን፣ ሐዋርያትን ልዑካን አድርጎ ቀድሶ ካቈረባቸው በኋላ “እምይእዜሰ አንትሙኒ ከመዝ ግበሩ፤ ከዛሬ ጀምሮ እናንተም እንደዚህ አድርጉ”ብሎ አዟቸው በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐርጓል፡፡

የሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑ ቁመት በነገሥታት ዘመን የነበሩ የ፳፬ቱ ነቢያት፣ ወይም የ፳፬ቱ ካህናተ ሰማይ፤ ወርዱ ደግሞ የ፲፪ቱ ሐዋርያት ምሳሌ ነው፡፡ ሦስቱ ድንጋዮች የሥላሴ አምሳል ሲሆኑ፣ ከታች አቀማመጣቸው ሦስት፤ ከላይ ሕንፃቸው አንድ መሆኑ የሥላሴን ሦስትነትና አንድነት ያመለክታል፡፡ ሐዋርያት የሠሩትም ሦስት ክፍል አድርገው ሲሆን፡- የመጀመሪያው የታቦተ አዳም፤ ሁለተኛው የታቦተ ሙሴ፤ ሦስተኛው የታቦተ ኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ ዳግመኛም የሦስቱ ዓለማት ማለትም የመጀመሪያው የጽርሐ አርያም፣ ሁለተኛው የኢዮር፣ ሦስተኛው የጠፈር ምሳሌ ነው፡፡

በሌላም በኩል የመጀመሪያው የኤረር፣ ሁለተኛው የራማ፣ ሦስተኛው የኢዮር አምሳል ነው፡፡ በኤረር፡- መላእክት፣ መኳንንት፣ ሊቃናት፤ በራማ፡- ሥልጣናት፣ መናብርት፣ አርባብ፤ በኢዮር፡- ኃይላት፣ ኪሩቤል፣ ሱራፌል ይኖራሉ፡፡ እነዚህ ዘጠኙ ነገደ መላእክት የዘጠኙ መዓርጋተ ቤተ ክርስቲያን (መዓርጋተ ክህነት) አምሳል ሲሆኑ፣ ይኸውም መላእክት – የመዘምራን፤ መኳንንት – የአናጕንስጢሳውያን፤ ሊቃናት – የንፍቀ ዲያቆናት፤ ሥልጣናት – የዲያቆናት፤ መናብርት – የቀሳውስት፤ አርባብ – የቆሞሳት፤ ኃይላት – የኤጲስ ቆጶሳት፤ ሱራፌል – የጳጳሳት፤ ኪሩቤል – የሊቃነ ጳጳሳት አምሳሎች ናቸው፡፡

በዚህችም ዕለት በቂሣርያው በቅዱስ ባስልዮስ ዘመን እንዲህ ሆነ፡- ቅዱስ ባስልዮስ የእመቤታችንን ቤተ ክርስቲያን ከሠራ በኋላ በውስጧ የሚያኖረውን የእመቤታችንን ሥዕል ሊያሠራ መሳያ ሠሌዳ ፈለገ፡፡ ሰዎችም በአንድ ባለጸጋ ቤት ጥሩ ሠሌዳ እንዳለ ነገሩትና ሄዶ ለባለጸጋው ሠሌዳውን እንዲሰጠው ለመነው፡፡ ባለጸጋውም “የልጆቼ ነው አልሰጥም” አለው፡፡ በትዕቢትም ሆኖ በታነጸቸው ቤተ ክርስቲያን ላይ የስድብን ነገር ተናገረ፡፡ ወዲያውም ወድቆ ክፉ አሟሟት ሞተና ልጆቹ ፈርተው ሠሌዳውን አምጥተው ለባስልዮስ ሰጡት፡፡ እርሱም ያንን ሠሌዳ የእመቤታችንን ሥዕል አሳምሮ ይስልበት ዘንድ ለሠዓሊ ወስዶ ሰጠው፡፡

በዚህም ጊዜ እመቤታችን በራእይ ለቅዱስ ባስልዮስ ተገለጠችለትና ከአመፀኛ ሰው የተገኘ ነውና በዚያ ሰው ሠሌዳ ሥዕሏን እንዳያስል ከለከለችው፡፡ የእመቤታችን ሥዕሏ የተሳለበትን ሠሌዳም የት እንደሚገኝ ነገረችውና ባስልዮስ ሄዶ በታላቅ ክብር አምጥቶ በቤተ ክርስቲያኑ አስቀመጠው፡፡ ከሥዕሏም ሥር ድውያንን ሁሉ የሚፈውስ የዘይት ቅባት መፍሰስ ጀመረ፡፡ በዚህም ብዙዎች ድንቅ የሆነ ፈውስን አገኙ፡፡ የከበረች ሥዕሏ ከተቀመጠበት ምሰሶ ሥር ጸበል ፈለቀና ብዙዎች ተፈወሱ፡፡ ይህም የተፈጸመው የእመቤታችን ቤተ ክርስቲያን በከበረችበት ዕለት በሰኔ ፳፩ ቀን ነው፡፡

ምንጭ፡

  • መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሰኔ ፳ ቀን፡፡
  • መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ መ/ር አፈወርቅ ተክሌ፤ አዲስ አበባ፣ ፳፻፭ ዓ.ም፤ ገጽ ፫፻፵፱ – ፫፻፶፩፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“ከሰማይ ከወረደው የሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም፡፡” (ዮሐ. ፫፥፲፫)

በዳዊት

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጆች ድኅነት በራሱ ፈቃድ፣ በአባቱም ፈቃድ፣ በመንፈስ ቅዱስም ፈቃድ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም የነሣውን የሰውን ልጅ ሥጋ ተዋሕዶ(አምላክነቱ ሳይለወጥ ፍጹም ሰው ሆኖ) በምድር ተመላልሷል። በሥጋ ማርያም ተገልጦ በምድር በነበረበት ጊዜ እውነተኛውን መንገድ አስተምሯል፣ መርቷል፤ ድውያነ ሥጋን በተአምራቱ፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርቱ ፈውሷል፤ ዓይነ ሥውራንን አብርቷል፤ ሽባውን ተርትሯል፤ ጎባጣውን አቅንቷል፤ ሥርዓተ ወንጌልን ሠርቷል፤ ከኃጢአት በቀር ፍጹም ሰው ሆኖ ተመላልሷል።

ጌታችን ወደ ምድር የመጣበትና በምድር ላይ ይመላለስ በነበረበት ወቅት የነበሩ መሠረታዊ ዓላማዎች የጠፉትን የአዳምን ልጆች ፈልጎ ወደ እቅፉ ማስገባት፣ በበደል ምክንያት ከእግዚአብሔር ተለይቶ የነበረን የሰውን ማንነት ከእግዚአብሔር(ከራሱ) ጋር ማስታረቅ፣ በበደል ምክንያት ወደ ዓለም የገባውን የዲያብሎስ ማሰሪያ ለዘለዓለሙ ቆርጦ መጣል፣ በሔዋን ምክንያት ተዘግቶ የነበረን የገነት በር መክፈት፣ በሰው ልጆች ሁሉ ተፈርዶ የነበረን ሞት በሞቱ ድል አድርጎ መሻር፣ በሲዖል ተግዘው በጨለማ የነበሩትን በነፍሱ ወደ ሲዖል በመውረድ በርብሮ ማውጣት ዋነኞቹ ነበሩ። እነዚህንም ሁሉ ፍቅር ስቦት በመዋዕለ ሥጋዌው በአምላክነቱ ሥልጣን ሁሉንም ፈጽሟቸዋል።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአምላክነቱ ሞትን ድል አድርጎ በሦስተኛው ቀን ከሙታን መካከል በኵር ሆኖ ከተነሣ በኋላ ለሐዋርያቱና ለሚወዱት ሁሉ እየተገለጠ ትንሣኤውን በገሃድ ሲያስረዳ፣ መጽሐፈ ኪዳንን፣ የመጻሕፍትን ምሥጢር፣ ሕግጋትንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ሲያስተምራቸው ለ፵ ቀናት በምድር ቆይቷል። ከዚህም በኋላ ደቀ መዛሙርቱን “እስከ ቢታንያም ወደ ውጭ አወጣቸው፤ እጁንም አንሥቶ በላያቸውም ጭኖ ባረካቸው። እየባረካቸውም ራቃቸው፤ ወደ ሰማይም ዐረገ።”(ሉቃ. ፳፬፥፶-፶፩)

ዕርገት “ዐርገ፣ ከፍ ከፍ አለ፣ ከታች ወደ ላይ ወጣ፣ ዐረገ” ካለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ሲሆን “ዕርገት፣ መውጣት፣ ከፍ ከፍ ማለት፣ ማረግ” ማለት ነው።(መዝገበ ቃላት ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ገጽ ፯፻፰) ዕርገት ለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲነገር ምሥጢሩ ብዙ ነው፤ በተወዳጅ ሐዋርያው ከሰማይ የወረደው ተብሎ የተነገረለት መድኃኔዓለም ማንም ሳያየው ከሰማይ ወርዶ ብዙዎች እያዩት ከትንሣኤው በኋላ በ፵ኛው ቀን ወደ ቀደመ ክብሩ በርቀት ያይደለ በርኅቀት ዐርጓል። ወደ ሰማይ መውጣቱ ማረጉ የታመነ የሆነው ጌታ አስቀድሞ ስለመውረዱ የተነገረለት፣ የታወቀለት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም “…ወደ ሰማይ የወጣው የወረደው እንደሆነ ዕወቅ…” በማለት በሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ የተነገረውን ያጠነክራል።(ዮሐ አፈ. ክፍ ፳፫፥፳፯)

ጌታችን ከሰማይ የወረደው ንጽሐ ባሕርይው በበደል ምክንያት አድፎበት በግድ ከገነት ወደ ምድር የወረደውን አዳምን ከወደቀበት ሊያነሣው ከወጣበት ሊመልሰው ነው፤ ለዚህም የሰውን ሥጋ ተዋሕዶ ከኃጢአት በቀር ፍጹም ሰው ሆነ፤ ያለመቀላቀል ያለመጠፋት ሥጋና ለመለኮትበመዋሐዳቸው ምክንያት ዐረገ ተብሎ ተነገረለት እንጂ መለኮትስ በሁሉ የሚገኝ በሁሉ የመላ(ምልዑ) ነው። ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “እግዚአብሔር በእልልታ ጌታችንም በመለከት ድምፅ ዐረገ” (መዝ. ፵፮፥፯) በማለት ያረገው መለኮት በሥጋ ተዋሕዶ አንድ ባሕርይ የሆነ እግዚአብሔር ወልድ እንደሆነ ይመሰክራል።

ቅዱስ ሉቃስም በወንጌሉ “እየባረካቸውም ራቃቸው፤ ወደ ሰማይም ዐረገ።” በማለት የገለጠው በኃጢአት ምክንያት ድቀት አጋጥሞት የነበረ ሥጋ በተዋሕዶተ ቃል ማረጉን ሲናገር “ራቃቸው” አለ፤ ራሱ እግዚአብሔር መሆኑን ሲገልጥም እንደ ሌሎቹ መላእክት እንዳሳረገቸው  ሳይሆን ራሱ በሥልጣኑ “ዐረገ” በማለት ያረገው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ የሆነ እንደሆነ ገለጠ፡፡ ክብር ምስጋና ይግባውና የዮሴፍ ልጅ ነው ብለው ለካዱት ለአይሁድም የእግዚአብሔር ልጅ እግዚአብሔር መሆኑን በመመስከር “ከሰማይ ከወረደው የሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም” ካለው ከሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ ጋር ተባበረ።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመጣጡ ወደ ምድር መውረዱ በትሕትና ነበር፤ ሲያርግ ግን በልዕልና ነበርና “ዐርገ በስብሐት፤ በምስጋና ዐረገ” እንላለን። መውረዱን በትሕትና ባደረገባት ገሊላ ዕርገቱንም ከሠላሳ ሦስት ዓመታት በኋላ በዚሁ በገሊላ በልዕልና፣ በስብሐት፣ በዕልልታ አድርጎባታልና።

ስለዚህ እኛም ዕርገቱን መሠረተ ሃይማኖታችን በሆነው ጸሎተ ሃይማኖት ”በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ በአባቱም ቀኝ ተቀመጠ” ብለን ዘወትር እንጸልያለን፤ እንመሰክራለንም። አሁንም ከሊቁ ከአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ጋር “አሁንም ከኛ ጋር በዓልን እንዲያደርጉ አባቶችን እንጥራቸው። ከሁሉ በፊት አዳምን እንጥራው፤ እነሆ እግዚአብሔር ከገነት በወጣህ ጊዜ ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ ያለው ተፈጸመ፤ እግዚአብሔር ሥጋን ከሴት ልጅህ ለበሰ፤ በአባቱም ቀኝ በሰማያት ተቀመጠ፤ ይህን የወደድኸውን አምላክነት ከሴት ልጅህ በተወለደ በመለኮት ሰው መሆን አገኘኸው እንበለው። የሕያዋን እናታቸው ስለሆንሽ ሕይወት የተባልሽ ሔዋን ሆይ በሴትልጅሽ ደስ ትሰኚ ዘንድ ነዪ፤ ሕይወትን አምጥተሻልና፤ በታተመ አፈ ማኅፀኗ የወለደችው እርሱ በረከትን ካገኙደቀ መዛሙርቱ ጋር ቆማ እያየችው ወደ ሰማያዊው አባቱ ዐረገ” (መጽሐፈ ምሥ. ፳፰፥፲፬) እያልን እናክብር እናመስግን! ከበዓለ ዕርገቱ ረድኤት በረከት ያሳትፈን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

ምንጭ፦ መጽሐፍ ቅዱስ፤ መጽሐፈ ምሥጢር፤ ተንከተም (በሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ)

የቅዱስሲኖዶስመግለጫ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ፡፡

በመንፈስ ቅዱስ የሚመራው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በዓመት ሁለት ጊዜ እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው ከጥቅምት 11 እስከ ጥቅምት 20 ቀን 2017 ዓ.ም. ድረስ መደበኛ ስብሰባውን ሲያካሂድ ሰንብቷል፡፡

ምልዓተ ጉባኤው ልዑል እግዚአብሔርን አጋዥና መሪ በማድረግ ስለ ቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት፣ ስለምጣኔ ሀብት እድገት፣ በሀገራችን እየተከሰቱ ስላሉት ውስጣዊና ውጫዊ ፈተናዎች፣ ስለ ሀገር ሰላምና አንድነት፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደርና ሐዋርያዊ ተልእኮ ስለ ሰው ልጅ ሁሉ ደኅንነት በስፋት በመወያየት ለቤተ ክርስቲያንና ለሀገር ጠቃሚ የሆኑ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡

በዚሁ መሠረት፡-

  1. ከጥቅምት 4 ቀን እስከ ጥቅምት 9 ቀን 2017 ዓ.ም. ድረስ የተካሄደው ዓለም አቀፍ ጉባኤ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ 43ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ዓለም አቀፍ ስብሰባ ተሳታፊዎች የቀረበው ቃለ ጉባኤና የአቋም መግለጫ በሁሉም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አህጉረ ስብከት የበጀት ዓመቱ የሥራ መመሪያ እንዲሆን ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ አስተላልፏል፡፡
  • በተለያዩ የሀገራችን አካባቢዎች እየተከሰተ ባለው የሰላም እጦት፣ የእርስ በርስ ግጭት ምክንያት የሰው ሕይወት እየተቀጠፈ፣ አካል እየጎደለ፣ ማኅበራዊ ትሥሥር እየተናደ፣ ሰብአዊ ክብር እየተጎዳ፣ መብት እየተጣሰ፣ በዜጎች ላይ ሥጋትና አለመረጋጋት እየበዛ ሀብትና ንብረት እየወደመ ስለሆነ ጉዳዩ አስቸኳይ መፍትሔ የሚያስፈልገው መሆኑ አጠያያቂ አይደለም፡፡ ስለሆነም በጦርነትና በግጭት የመጣ ሰላም፣ የተገነባ ሀገር የለምና በሀገራችን እያጋጠመ ያለውን ችግር ለመፍታት ካለፈው በመማር በጥበብ፣ በማስተዋልና በሰለጠነ አካሄድ በሰላማዊ መንገድ በመወያየት ችግሩ በእርቅ እንዲፈታ ለሁሉም ወገኖቻችን ቅዱስ ሲኖዶስ የሰላም ጥሪውን በአጽንኦት ያቀርባል፡፡

3. በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትና በሥሩ ባሉ ገዳማትና አድባራት ውስጥ እየቀረቡ ያሉ መጠነ ሰፊ የአስተዳደር ችግሮች እንዲፈቱ ለማድረግ ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ጀምሮ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት፣ በክፍላተ ከተሞችና ችግር አለባቸው ተብለው በጥናት በሚለዩት አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ላይ የማጣራት ሥራ እንዲሠራና ውጤቱ ለውሳኔ እንዲቀርብ በሦስት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የሚመራ ኮሚቴ ቅዱስ ሲኖዶስ ሰይሟል፡፡

4. የኦሲኤን ቴሌቪዥን ስርጭት የተቋረጠ በመሆነ በአዲስ መልክ ሁሉንም የአፋን ኦሮሞ ቋንቋ ተናጋሪዎች ማህበረሰብ ባቀፈ መልኩ አገልግሎት እንዲሰጥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአፋን ኦሮሞ ኔትወርክ በሚል ስያሜ በጠቅላይ ቤተ ክህነት በኩል ውል ተፈርሞ በአዲስ መልክ የሳተላይት ግዥ እንዲፈጸም ሆኖ አስተዳደሩን በተመለከተ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መገናኛ ብዙኃን ድርጅት ጋር በአንድ ሊቀ ጳጳስና ቦርድ ራሱን በቻለ ሥራ አስኪያጅ እየተመራ አገልግሎቱ ከነበረው በተሻለ ሁኔታ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

5. የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ለደቀ መዛሙርት የሚሰጠው የምስክር ወረቀት አድቫንስ ዲፕሎማና ዲግሪ እንዲሆን ሥርዓተ ትምህርቱ ለሚሰጠው የትምህርት ማስረጃ በሚመጥን መልኩ ተሟልቶ፣ ሊኖረው የሚገባው የሰው ኃይል በየዘርፉ ተጠናክሮ ወደ ትግበራ እንዲገባ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፣

6. የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በሥነ ሕንጻና በኪነ ጥበብ በዓለም ደረጃ ከፍተኛ አድናቆትና ክብር የሚሰጠው ከመሆኑ በተጨማሪ በመዐርገ ጵጵስና ፕትርክና የሚሾሙ አባቶች ሥርዓተ ሲመት የሚፈጸምበት፣ ጥንታዊና ታሪካዊ ካቴድራል መሆኑን ታሳቢ በማድረግ ለዕድሳት ሥራው የገንዘብ ድጋፍ እንዲደረግለት ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፤ በተጨማሪም ምእመናን እስከ አሁን እንደሚያደርጉት ሁሉ ለእድሳት ሥራው አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያደርጉ ቅዱስ ሲኖዶስ

ያሳስባል፡፡

7. የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዐቢይ ኮሚቴ ሥራውን አጠናክሮ እንዲቀጥልና በንቃት እንዲሳተፍ ሁሉንም አህጉረ ስብከት ባቀፈ ሁኔታ የአጀንዳ መረጣና ተሳታፊ የመለየት ሥራ እንዲከናወን ሆኖ ዐቢይ ኮሚቴው የሥራ ዕቅዱንና አፈጻጸሙን ለቋሚ ሲኖዶስ እያቀረበ በማስወሰን እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

በአጠቃላይ ቅዱስ ሲኖዶስ በመንፈስ ቅዱስ እየተመራ ላለፉት ተከታታይ ቀናት በመንፈሳዊ፣ በማኀበራዊና ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ተገቢውን ውሳኔ በማስተላለፍ መደበኛ ስብሰባውን በዛሬው ዕለት በጸሎት አጠናቅቋል፡፡ መሐሪና ሁሉን ቻይ የሆነ እግዚአብሔር አምላካችን ለሀገራችን፣ ለሕዝባችን፣ ለዓለሙ ሁሉ ሰላሙን፣ ፍቅሩንና አንድነቱን ይስጥልን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ

ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም

ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ጥቅምት ፳፩ ቀን ፳፻፲፯ ..

ኢትዮጵያ አዲስ አበባ

ነገረ ቅዱሳን

መ/ር መስፍን ምትኬ

ክፍል ሦስት

፫. ቅዱሳን የሚባሉት ምን የፈጸሙ ናቸው?

ቅዱሳን እንደየገድላቸውና ትሩፋታቸው በተለያየ አከፋፈል ሊከፈሉ ቢችሉም በአጠቃላይ ግን ከዚህ በታች የተዘረዘሩትን የፈጸሙ ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡

ሀ. ያላቸውን ሁሉ ትተው አምላካቸውን የተከተሉ ናቸው፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ “እኛ ሁሉን ትተን ተከተልንህ እንግዲህ ምን እናገኛለን?” አለው፡፡  ጌታችን ኢየሱስም እንዲህ አላቸው፡- እውነት እላችኋለሁ የተከተላችሁኝ እናንተ  በዳግም ልደት የሰው ልጅ በክብሩ ዙፋን በተቀመጠ ጊዜ እናንተም በዐሥራ ሁለት ዙፋን ትቀመጣላችሁ፤ በዐሥራ ሁለቱም ነገደ እስራኤል ትፈርዳላችሁ፡፡” (ማቴ. ፲፱፥፳፯-፳፰፤ ማር. ፲፥፳፱-፴፩)

ለ. ሕይወታቸውን በተጋድሎ ያሳለፉ ናቸው

➢ “መከራን የሚታገሥ ሰው ብፁዕ ነው፤ ተፈትኖ እግዚአብሔር ለሚወዱት ተስፋ ያደረገላቸውን የሕይወት አክሊል ይቀበላልና፡፡” መንፈሳዊ ሰው ረቂቅ ጠላት ያለበት ስለሆነ ሁል ጊዜ የተዘጋጀ ሆኖ መኖር አለበት፡፡ ቅዱሳንም ይህን ጦርነት ዐውቀው በፈተና የጸኑና እስከ ሞት ድረስ የታመኑ ናቸው” (ያዕ.  ፩፥፲፪)

“ገና አልጸናችሁምና ደማችሁን ለማፍሰስ እስክትደርሱ ኀጢአትን ተጋደሉአት፤ አሸንፏትም፤ ተስፋችሁን የምታገኙባትን ትምህርትም ውደዱአት” (ዕብ. ፲፪፥፬)

➢ መጋደላቸውም ከውስጣዊ እና ውጫዊ (አፍአዊ) ፈተናዎች ጋር ነው፡፡

  • ውስጣዊ ፈተና፦ ይህ ፈተና አንድ ሰው “ሰው” በመሆኑ የሚፈተነው ፈተና ነው፡፡ ይኸውም ከሰዋዊ ባሕርይ ጋር የተያያዘ በመሆኑ ከዚህ ፈተና የሚሸሹት ሜዳ፣ የሚሸሸጉበት ጓዳ የለም፤ ሰው የነፍሱና ሥጋ ተዋሕዶ ውጤት በመሆኑ በዚህ ዓለም ሕይወት ሲወጣና ሲወርድ ይኖራል፡፡ ሰው በዚህ ዓለም ሕይወቱ ራሱን ለፈጣሪ ለማስገዛት ከራሱ ጋር ብርቱ ተጋድሎ ማድረግ ግድ ይለዋል፡፡

➢ ቅዱስ ጳውሎስ “ሥጋ በመንፈስ ላይ መንፈስ በሥጋ ላይ ይመኛል፡፡ እነዚህም እርስ በእርሳቸው ይቀዋወማሉ፡፡ ስለዚህም የምትወዱትን ልታደርጉ አትችሉም” (ገላ. ፲፥፲፯) ብሎ የገለጸው ይህንን የሰው ሕይወት ያለበትን ብርቱ ጦርነት ለማስገንዘብ ነው፡፡

➢ ስለዚህ “ሰውነቴን እየጎሰምኩ አስገዛዋለሁ” እንዳለ ሐዋርያው ፍቃደ ሥጋችን ለነፍሳችን በጾም በጾሎት በስግደት ልናስገዛ ይገባናል፡፡ (፩ኛ ቆሮ. ፱፥፳፯፤ መዝ. ፷፰፥፲)

  • አፍአዊ (ውጫዊ) ፈተና፡- ሰው የሚፈተነው በውስጣዊ ብቻ ሳይሆን በውጫዊውም ፈተና ጭምር ነው፡፡ ይኸውም በቤተሰብ፣ በጓደኛ፣ በዘመድ፣ በሥራ ቦታ፣ በልማድና ጎጂ ባህል፣ …  ነው፡፡

ሐ. እግዚአብሔርን በራሳቸው (በፍጹም ሰውነታቸው) ያገለገሉ ናቸው፡፡

ጌታችን “እኔን መከተል የሚወድ ቢኖር ራሱን ይካድ መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ” (ማቴ. ፲፮፥፪) በማለት የፍጹምነት መንገድ ተናግሯል፡፡

➢ ሰው በዚህ ዓለም ሲኖር በሕግ ተወስኖ ቤተሰብ መሥርቶ ጌታውን እያገለገለ ይኖራል፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔርን በማገልገልና ይህን ዓለም በማሰብ ልቡ ይከፈልበታል፤ ለዚህ ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ያገባ ግን ሚስቱን ደስ ሊያሰኝ የዚህን ዓለም ኑሮ ያስባል፡፡” (፩ኛቆሮ. ፯፥፴፫) በማለት የልቡን መከፈል ይገልጻል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምሳሌ ሲያስተምርም “አንድ ሰው ታላቅ ምሳን አደረገና ብዙ ሰዎችን ጠራ፡፡” ይለናል፡፡ ነገረ ግን በመልእክተኛው የተጠሩት ሁሉ ምክንያት እየፈጠሩ ቀርተዋል፡፡ ወደ ግብዣ ከተጠሩት ውስጥ ሦስተኛው ሰው እንደ ምክንያት ያቀረበው “ሚስት አግብቼአለሁ ስለዚህም ልመጣ አልችልም በለው” አለው መልእክተኛውን። (ሉቃ. ፲፬፥፳)

➢ ስለዚህ ቅዱሳን ምክንያት ሳያደናቅፋቸው ይህን ዓለምን በመናቅ በምናኔ የኖሩ ናቸው፡፡

መ. ሩጫቸውን በድል የተወጡ ናቸው

➢ መንፈሳዊ ተጋድሎ በሩጫ ይመሰላል፡፡ “በእሽቅድምድም ስፍራ የሚሮጡት፥ ሁሉ እንዲሮጡ ነገር ግን አንዱ ብቻ ዋጋውን እንዲቀበል አታውቁምን? እንዲሁም ታገኙ ዘንድ ሩጡ።” (፩ኛ ቆሮ. ፱፥፳፬) በማለት መንፈሳዊውን ሕይወት በሩጫ መስሎ ተናግሯል፡፡

“በፈተና የሚጸና ሰው የተባረከ ነው፤ ከተፈተነ በኋላ ለሚወዱት ተስፋ ስለ እርሱ የሰጣቸውን የሕይወትን አክሊል ይቀበላልና።” (ያዕ. ፩፥፲፪)

➢ መጋደላችንም ከማን ጋር እንደሆነ ሲገልጽ፦ “መጋደላችን ከደምና ከሥጋ ጋር አይደለምና፥ ከአለቆችና ከሥልጣናት ጋር ከዚህም ከጨለማ ዓለም ገዦች ጋር በሰማያዊም ስፍራ ካለ ከክፋት መንፈሳውያን ሠራዊት ጋር ነው እንጂ።” በማለት እንደተናገረው፡፡ (ኤፌ. ፮፥፲፪)

➢ ይህንን ተጋድሎ በትዕግሥት ያጠናቀቁትም፦

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ስለ ቅዱሳን ተጋድሎና በኋላም የሚያገኙትን ክብር ሲናገር “መልካሙን ገድል ተጋድዬአለሁ፥ ሩጫውን ጨርሼአለሁ፥ ሃይማኖትን ጠብቄአለሁ፤ ወደ ፊት የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል፥ ይህንም ጻድቅ ፈራጅ የሆነው ጌታ ያን ቀን ለእኔ ያስረክባል፥ ደግሞም መገለጡን ለሚወዱት ሁሉ እንጂ ለእኔ ብቻ አይደለም“ ብሏል፡፡ (፪ኛጢሞ. ፬፥፯-፰)

➢ ብዙ ሯጮች ሩጫውን አብረው እንደሚጀምሩ ሁሉ ከሐዋርያት ጋር ጀምረው ሩጫቸውን ያቋረጡም አሉ፡፡ ለምሳሌ ይሁዳ፤ እንዲሁም ዴማስ ከሉቃስና ጢሞቴዎስ ጋር መንፈሳዊ ሕይወቱን መምራት ጀምሮ ሳያጠናቅቁ አቋርጠዋል፡፡ በዚህም ምክንያት የተዘጋጀላቸውን አክሊል አጥተዋል።

ሠ. በፍጹም መንፈሳዊ ጥበብ የኖሩ ናቸው

አምላክችንና ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “እንደ እባብ ልባሞች እንደ ርግብ የዋሆች ሁኑ” በማለት በመንፈሳዊ ጥበብ መኖር እንዲገባ አስታምሯል (ማቴ. ፲፥፮) ምክንያቱም ጠላታችን ረቂቅ አመጣጡም ረቂቅ ነውና ይህንን ረቂቅ ጠላት ለመመከት ጥበብ መንፈሳዊ ያስፈልጋል፡፡

በአጠቃላይ ቅዱሳን፦

ሀ. እስከ ሞት ድረስ የታመኑ ናቸው።

“እስከ ሞት የታመንክ ሁን” (ራእ. ፪፥፲) እንደተባለ እስከ ሕይወታቸው ፍጻሜ ድረስ በጾም በጸሎት ተወስነው በፍጹም ተጋድሎ በአምልኮተ እግዚአብሔር የጸኑ ናቸው።

ለ. በጌታችን በአምላካችንና በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደም ላይ የተመሠረተችውን ቤተ ክርስቲያን እምነትና ሥርዓት ጠብቀው በማስጠበቅ በአገልግሎት የተጉና የተጋደሉ ናቸው።

ሐ. የእግዚአብሔርን ቃል ንባብ፣ ትርጓሜና ምሥጢር ሳያፋልሱ በማስተማር በሃይማኖት የጸኑ እና ምእመናንንም ያበዙ ናቸው።

መ. በሕይወታቸው ነውር በሃይማኖታቸው ነቀፌታ ያልተገኘባቸው ናቸው።

ሠ. ከዓለም ተለይተው በበረሃ ወድቀው፥ ድንጋይ ተንተርሰው፣ ጤዛ ልሰው፣ ዋሻ ዘግተው፣ ጸብአ አጋንንትን ድምፀ አራዊትን እና ግርማ ሌሊትን ሳይሰቀቁ የኖሩ፤ ስለ ሃይማኖታቸው በመመስከር በሰማዕትነት ያረፉ ናቸው።

ረ. ምትሐት ያይደለ እውነተኛ ተአምራትን በማድረግ የሚታወቁ ናቸው።

ሰ. ከፍጹምነት መዓርግ የደረሱ ናቸው።

“እንግዲህ የሰማዩ አባታችሁ ፍጹም እንደ ሆነ እናንተ ፍጹማን ሁኑ” (ማቴ. ፭፥፵፰)

ስለዚህ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፦

➢ ቅዱሳንን እግዚአብሔር እንዳከበራቸው ታከብራቸዋለች

➢ በቅድስና ስም ትጠራቸዋለች፡፡

➢ ከእነርሱ በፊት የቅድስና መዓርግ በተሰጣቸው ሰዎች መዝገብ ስማቸውን በክብር ታኖራለች

➢ ተአምራቸውን ወይም ገድላቸውን ጽፋ በክብር ታስቀምጣለች።

➢ ዐጽማቸው ያለበት ቦታ የሚታወቅ እንደሆነ ሰብስባ በክብር ታስቀምጠዋለች፡፡

➢ በእነርሱ ስም ለጸሎት ለልመናና ለምስጋና የሚሆን መልክእ ትደርሳለች።

➢ ስማቸውንም እየጠራች ትማጸንባቸዋለች፡፡

➢ በእነርሱ ስም ጽላት ትቀርጽላቸዋለች፣ ቤተ ክርስቲያን ታንጽላቸዋለች፡፡

➢ የምእመናንም ስመ ክርስትናቸውን በስማቸው ትሰይማለች።

➢ የሚታሰቡበት ዕለት ትሰጣቸዋለች

➢ የመታሰቢያ ሥዕል ትሥልላቸዋለች፡፡ 

የቅዱሳን መታሰቢያ በቤተ ክርስቲያን

• ቤተ ክርስቲያን የቅዱሳንን ውለታ አትረሳም፡፡ በአፀደ ሥጋ ያሉትን በማገልገል ያረፉትን ቅዱሳንን ደግሞ በማክበር ገድላቸውን በመጻፍ መታሰቢያቸውን ታደርጋለች፡፡ (ዕብ. ፮፥፲)

“እነርሱ በእምነት ተጋደሉ፤ ነገሥታትን ድል ነሡ፤ ጽድቅን አደረጉ፤ ተስፋቸውን አገኙ፤ የአናብስትን አፍ ዘጉ፡፡ የእሳት ኀይልን አጠፉ፤ ከሰይፍ ስለት አመለጡ፤ ከድካማቸው በረቱ” (ዕብ. ፲፩፥፴፪)

• ቅዱሳንን ቤተ ክርስቲያን በማነጽ፣ ጽላት በመቅረጽ ታስባቸዋለች፡፡

“በቤቴና በቅጽሬ ውስጥ ከወንዶችና ከሴቶች ልጆች ይልቅ የሚበልጥ መታሰቢያና ስም እሰጣቸዋልሁ፤ የማይጠፋም የዘለዓለም ስም እሰጣቸዋለሁ፡፡” (ኢሳ. ፶፮፥፭)

• ቤተ ክርስቲያን በቅዱሳን የልደትና የዕረፍት ዕለታት የመታሰቢያ በዓል በማድረግ በቅዳሴና በማኅሌት በማክበር በዓለ ንግሥ ታደርጋለች፡፡ በስማቸው ጠበል ጸዲቅ ታደርጋለች፡፡ (ማቴ. ፮፥፵-፵፪)

• ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳንን የተጋደሉትን ተጋድሎ፣ የደረሰባቸውን ፈተና፣ ከጠላት ዲያብሎስ ጋር ያደረጉትን ጦርነት ድልና አክሊል እስካገኙበት ድረስ ያሉትን ገድላቸውን በመጻፍ ታስባቸዋለች፡፡

“መልካሙን የእምነት ገድል ተጋደል፥ የተጠራህለትንም በብዙም ምስክሮች ፊት በመልካም መታመን የታመንህለትን የዘለዓለምን ሕይወት ያዝ።” (፩ኛጢሞ. ፮፥፲፪)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር