ደብረ ዘይት

በእንዳለ ደምስስ

በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ የዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት ደብረ ዘይት ተብሎ ይጠራል፡፡ ደብረ ዘይት በኢየሩሳሌም የሚገኝና የወይራ ዛፍ በብዛት ያለበት ተራራ ነው። ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀን እያስተማረ፣ ድውያንን እየፈወሰ፣ የተራቡትን እየመገበ፣ ለሚሹት እየተገለጠ ውሎ ማታ ማታ ግን ወደ ደብረ ዘይት ተራራ እየወጣ ይጸልይ ነበር፡፡ “ከዚያም በኋላ ሕዝቡን አሰናብቶ ሊጸልይ ብቻውን ወደ ተራራ ወጣ” እንዲል፡፡ (ማቴ. ፲፬፥፳፫)፤ በሆሣዕና ዕለት ከደብረ ዘይት ተነሥቶ ወደ ኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ገብቷል፤ ከደብረ ዘይት ግርጌ በጌቴ ሴማኒ ጸሎት አድርጓል፤ የአይሁድ ጭፍሮችም መጥተው የያዙት ከዚሁ ደብረ ዘይት ተራራ ነው፡፡ (ማቴ.  ፳፮፥፴፮) በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ሆኖ ስለ ዓለም ፍጻሜና ምልክቱ አስተምሯል፤ (ማር. ፲፫፥፫) በደብረ ዘይት ተራራ ወደ ሰማይ ዐርጓል፤ (ሉቃ. ፳፬፥፶፩-፶፪) በትንቢት እንደተነገረለትም በመጨረሻው ሰዓት በዓለም ፍጻሜ ለፍርድ በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ይገለጣል።

ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “እግዚአብሔር በግልጥ ይመጣል፤ አምላካችን ዝም አይልም፤ እሳት በፊቱ ይነዳል፣ በዙሪያውም ብዙ ዐውሎ አለ” (መዝ. ፵፱፥፫) እንዲል በዚህ የደብረ ዘይት ሳምንት ስለ ዳግም ምጽአት ምልክቶች፣ ስለ ምጽአት እና ተስፋው ይታሰባል። በተለይም በወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ በምዕራፍ ፳፬ በስፋት ተጽፎ እናገኛለን፡፡ ለመሆኑ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህን ዓለም ከመኖር ወደ አለመኖር ለማሳለፍ ከመምጣቱ በፊት የሚታዩ ምልክቶች ምን ምን ናቸው?

የምጽአት ምልክቶች

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከቤተ መቅደስ ወጥቶ በሄደ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ ቀርበው የቤተ መቅደሱን የሕንፃ አሠራር ካሳዩት በኋላ “ይህን ሁሉ ታያላችሁን? ድንጋይ በድንፈጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ አይቀርም” አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ይህን የነገራቸውን ነገር ሰምተው ብቻ ዝም ብለው አላለፉትም፡፡ “ንገረን ይህ መቼ ይሆናል? የመምጣትህና የዓለም ፍጻሜስ ምልክቱ ምንድን ነው?” ብለው ጠይቀውታል፡፡ (ማቴ ፬፥፩-፪)

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ደቀ መዛሙርቱ አብረውት እየዋሉ፣ አብረውት እያደሩ የቃሉን ትምህርት፣ የእጁን ተአምራት እየሰሙ እና እያዩ ምሥጢር ሳይከፈልባቸው ቆይተዋልና በቅድሚያ ከሚመጣው ሁሉ ይጠነቀቁ ዘንድ እንዲህ አላቸው፡፡ “የሚያስታችሁ እንዳይኖር ተጠንቀቁ፤ ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉና ብዙዎችንም ያስታሉ፡፡” ሲል በተማሩት ጸንተው ይኖሩ ዘንድ አሳስቧቸዋል፡፡ ይህ ማስጠንቀቂያ ብዙዎች ክርስቶስን ተቃውመው እንደሚነሡና በጠላትነት እንደሚነሡባቸው፤ ነገረ ግን የሚመጣባቸውን ሁሉ ተቋቁመው በሃይማኖታቸው ጸንተው እንዲኖሩ ያጸናቸው ዘንድ እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የነገረ ምጽአቱን ምልክቶች ሲናገር ከላይ የገለጸውን ብቻ ብሎ አላበቃም፡- “ጦርነትን፣ የጦርነትንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠንቀቁ፤ አትደንግጡ፣ ነገር ግን ፍጻሜው ገና ነው፡፡” ሲል ከሚያስቡት በላይ ከባድ ጊዜ እንደሚመጣ ነግሯቸዋል፡፡ ምልክቶቹንም ሲዘረዝር “ሕዝብ በሕዝብ ላይ፣ መንግሥትም በመንገሥት ላይ ይነሣሉ፤ በየሀገሩም ረኃብ፣ ቸነፈርም የምድር መናወጥም ይሆናል፡፡ እነዚህም የምጥ ጣር መጀመሪያ ናቸው፡፡” ብሏቸዋል፡፡

በደቀ መዛሙርቱም ላይ ስለሚደርሰው መከራ ሲገልጽ፡-”ያን ጊዜም ለመከራ አሳልፈው ይሰጡአችኋልም፣ ይገድሏችኋልም፤ ስለ ስሜም በሰው ሁሉ ዘንድ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ፡፡” በማለት የመከራውን አስከፊነት አስረድቷቸዋል፡፡ በወቅቱ ስለሚሆነውና በሰዎች ዘንድ ፍቅር ጠፍቶ አንዱ አንዱን አሳልፎ እንደሚሰጥ ሲገልጽም “ያን ጊዜም ብዙዎች ሃይማኖታቸውን ይለውጣሉ፤ እርስ በርሳቸውም አሳልፈው ይሰጣጣሉ፤ እርስ በርሳቸውም ይጣላሉ፡፡” ብሏል፡፡ (ማቴ.፳፬፥፱-፲)

ዛሬ በዘመናችን እንደምናየውና እንደምንሰማው ብዙዎች ራሳቸውን “ነቢይ” እያሉ በመጥራት እንክርዳድ የሆነውን የሐሰት ትምህርታቸውን በዓለም ላይ ይዘራሉ፡፡ ይህንንም በተመለከተ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ አድሮ “ብዙዎች ሐሰተኞች ነቢያትም ይመጣሉ፤ ብዙዎችንም ያስታሉ፤ ከዐመፅም የተነሣ ፍቅር ከብዙዎች ዘንድ ትጠፋለች፡፡ እስከ መጨረሻው የሚታገሥ ግን እርሱ ይድናል፡፡ በአሕዛብ ምስክር ሊሆን ይህ የመንግሥት ወንጌል በዓለም ሁሉ ይሰበካል፤ ያን ጊዜም ፍጻሜ ይደርሳል፡፡” ሲል በዘመኑ ስለሚሆነው ነገር በስፋት ገልጾላቸዋል፡፡ ይህም እኛ በዚህ ዘመን ያለን ክርስቲያኖችም ልናስተውለው፣ ዘወትር ከሚመጣው ክፉ ነገር ሁሉ እንጠበቅ ዘንድ በሃይማኖት በመጽናት፣ በጾም፣ በጸሎት፣ በመልካም ምግባራት ዘመኑን ልንዋጅ ይገባል፡፡

ይህ መቼ እንደሚሆን ሲገልጽም “እንግዲህ በነቢዩ በዳንኤል የተባለውን የመፍረሱን የርኵሰት ምልክት በተቀደሰ ቦታ ቆሞ ባያችሁት ጊዜ አንባቢው ያስተውል” ሲል ጊዜውን ይነግረናል፡፡ ይህም በነቢዩ ዳንኤል የተነገረው ትንቢት በቤተ መቅደስ የጥጦስ ጣዖት የታየ እንደሆነ ፍጻሜው እንደ ደረሰ ይጠቁመናል፡፡ (ማቴዎስ አንድምታ)፡፡ የጊዜውን አስከፊነት ሲያመለክትም ያን ጊዜም በይሁዳ ያሉ ወደ ተራሮች እንዲሸሹ፣ በሰገነትም ያሉ በቤት የሚገኘውን እንዳያነሡ፣ በእርሻም ያሉ ያስቀመጡትን ልብስ ለመውሰድ ወደ ኋላ እንዳይመለሱ ይነግረናል፡፡ በዚያ ወራት ለፀነሱና ለሚያጠቡ ወዮላቸው ማለቱ፡- የፀነሡት ከመንገድ ይወልዳሉ፤ የወለዱትም ወተት፣ ፍትፍት አምጡ ብለው ያስቸግሯቸዋልና ይጨነቃሉ፤ እንዲሁም ብዙዎች በዚያ ወራት ኃጢአትን በሐልዮ ፀንሰው ፣ በነቢብ ወልደው፣ በገቢር ለሚያሳድጉ ሰዎች ወዮላቸው መከራ ነፍስ አለባቸው ሲል ነው፡፡ ሽሽታችንም በክረምት ወይም በሰንበት እንዳይሆን ልንጸልይ እንደሚገባ ያስጠነቅቀናል፡፡ በክረምት ላዩ ዝናብ፣ ታቹ ውኃ ነውና መሻገር እንደማይቻል ያሳየናል፡፡ ስለ ተመረጡት ብሎ እግዚአብሔር ቀኖቹን ባያሳጥራቸው ኖሮ እጅግ አስከፊ እንደሆነም ያመለክተናል፡፡

ሐሰተኞች ነቢያት፤ ክርስቶስ በዚህ አለ እያሉ የሚያስቱ እንደሚነሡ፣ የተመረጡትን እስኪያስቱ ድረስ ታላላቅ ተአምራትን እስከማድረስ እንደሚደርሱ ይነግረናል፡፡ ከእነዚህም ምልክቶች በኋላ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መላእክቱን አስከትሎ በምድርና በምድር ያለውን ሁሉ ከመኖር ወደ አለመኖር ያሳልፍ ዘንድ ይመጣል፡፡ ይህንንም ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ ሲገልጽ “ከእነዚያም ቀኖች መከራ በኋላ ወዲያውኑ ፀሐይ ይጨልማል፣ ጨረቃም ብርሃኑን አይሰጥም፤ ከዋክብትም ከሰማይ ይወድቃሉ፤ የሰማያት ኃይል ይናወጣል፡፡ በዚያም ወራት የሰው ልጅ ምልክት በሰማይ ይታያል፡፡ ያን ጊዜም የምድር አሕዛብ ሁሉ ያለቅሳሉ፤ የሰው ልጅንም በኃይልና በብዙ ክብር በሰማይ ደመና ሲመጣ ያዩታል፡፡ መላእክቱንም ከታላቅ የመለከት ድምፅ ጋር ይልካቸዋል፡፡” (ማቴ. ፳፬፥፳፱-፴፩) ይህ ሁሉ የምጥ ጣር መጀመሪያ ነውና ነገረ ምጽአቱ እንደቀረበና በደጃፍ እንዳለ ልናስተውል ይገባል፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም በዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት “ደብረ ዘይት” ብላ ነገረ ምጽአቱን ታስባለች፡፡ ምእመናንም ነገረ ምጽአትን አስበው ከክፋት ተጠብቀውና መልካም ምግባራትን እየፈጸሙ ንስሓ ገብተው የጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙን ተቀብለው ተዘጋጅተው እንዲጠብቁ ታስተምራለች፡፡

የዕለተ ሰንበት መዝሙር (ከጾመ ድጓ)

“እንዘ ይነብር እግዚእነ ውስተ ደብረ ዘይት ወይቤሎሙ ለአርዳኢሁ ዑቁኬ ኢያስሕቱክሙ ወንበሩ ድልዋኒክሙ፤ ብዙኃን ይመጽኡ በስምየ እንዘ ይብሉ አነ ውእቱ ክርስቶስ ወዘአዝለፈ ትዕግሥቶ ውእቱ ይድኅን፤ ወአመ ምጽአቱሰ ለወልደ እጓለ እመሕያው ይትከወስ ኲሉ ኃይለ ሰማያት ወምድር፤ አሜሃ ይበክዩ ኲሎሙ ኃጥአነ ምድር፡ ወይወርድ እግዚእነ እምሰማይ ዲበ ምድር በትእዛዙ ወበቃሉ ወበ አዕላፍ መላእክቲሁ በንፍሐተ ቀርን ዘእም ኀበ እግዚአብሔር ይምሐረነ አብ በይእቲ ሰዓት እሞተ ኃጢአት እስመ ገባሬ ሕይወት ውእቱ እግዚኣ ለሰንበት፡፡”

ትርጉም:- ጌታችን በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ተቀምጦ ሳለ ለደቀ መዛሙርቱ ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ፤ተዘጋጅታችሁም ኑሩ ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉ፤ እስከ መጨረሻው የጸና እርሱ ይድናል፡፡ የሰው ልጅ በሚመጣበት ጊዜ የሰማያትና የምድርኃይላት ሁሉ ይናወጣሉ።ያን ጊዜ በምድር ኃጢአት ያደረጉ ሁሉ ያለቅሳሉ አላቸው፤ ጌታችንም ከባሕርይ አባቱ ከእግዚአብሔር አብ ዘንድ በመለከት ድምፅ ከአእላፍ መላእክት ጋር በክበበ ትስብዕት በግርማ መለኮቱ ከሰማይ ወደ ምድር ይወርደል፡፡ በዚች ዕለትም ከሞተ ኃጢአት አብ  ይማረን የሕይወት ባለቤት የሰንበትም ጌታ ነውና፡፡

ምንባባት መልእክታት

(፩ኛተሰ. ÷፲፫ፍጻ.)

“ወንድሞቻችን ሆይ÷ ስለ ሞቱ ሰዎች÷ ተስፋ እንደሌላቸው ሰዎች እንዳታዝኑ ልታውቁ እንወዳለን፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ሞቶ እንደ ተነሣ ካመንን እንዲሁ እግዚአብሔር ሙታንን በኢየሱስ ያስነሣቸዋል፤ ከእርሱም ጋር ያመጣቸዋል፡፡ …”

  ጴጥ. ÷፯-፲፬

“አሁንም ሰማይና ምድር በዚያ ቃል ለእሳት ተዘጋጅተዋል፤ ኃጥኣን ሰዎች እስከሚጠፉበት  እስከ ፍርድ ቀንም ተጠብቀዋል ነገር ግን ወንድሞቻችን ሆይ÷ ይህን አትርሱ፤ በእግዚአብሔር ዘንድ አንዲት ቀን እንደ አንድ ሺህ ዓመት÷ ሺህ ዓመትም እንደ አንድ ቀን ነውና፡፡ …”

ግብረ ሐዋርያት

(የሐዋ. ፳፬÷፩-፩)

“በአምስተኛውም ቀን ሊቀ ካህናቱ ሐናንያ ከመምህራኑና ጠርጠሉስ ከሚባል አንድ ጠበቃ ጋር ወረደ፤ ጳውሎስንም በአገረ ገዢው ዘንድ ከሰሱት፤ ጳውሎስም በቀረበ ጊዜ ጠርጠሉስ እንዲህ እያለ ይከስሰው ጀመረ፤ “ክቡር ፊልክስ ሆይ÷ በዘመንህ ብዙ ሰላምን አግኝተናል፤ በጥበብህም በየጊዜው በየሀገሩ የሕዝቡ ኑሮ የተሻሻለ ሆኖአል፤ ሥርዓትህንም በሁሉ ዘንድ ስትመሰገን  አግኝተናታል፡፡ …”

ምስባክ

(መዝ. ፵÷)

“እግዚአብሔርሰ ገሃደ ይመጽእ፤ ወአምላክነሂ ኢያረምም፤ እሳት ይነድድ ቅድሜሁ፡፡”

ትርጉም፦ እግዚአብሔር በግልጥ ይመጣል፡ አምላካችንም ዝም አይልም፤ እሳት በፊቱ ይነዳል በዙሪያውም ብዙ ዐውሎ አለ፡፡”

ወንጌል

(ማቴ. ፳፬÷፩-፭) 

“ጌታችን ኢየሱስም ከቤተ መቅደስ ወጥቶ ሄደ፤ ደቀ መዛሙርቱም ወደ እርሱ ቀርበው የቤተ መቅደሱን የሕንፃ አሠራር አሳዩት፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አላቸው÷ ይህን ሁሉ ታያላችሁን? እውነት እላችኋለሁ፤ ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ አይቀርም፡፡” (ተጨማሪውን ያንብቡ)

ቅዳሴ: – ቅዳሴ ዘአትናቴዎስ

 

“ልትድ ትወዳለህን?”

በኢየሩሳሌም በበጎች በር አጠገብ አንዲት መጠመቂያ ነበረች፡፡ ይህች መጠመቂያም በእብራይስጥ ቤተ ሳይዳ ስትባል አምስት አርከኖች ነበሯት፡፡ በዚያም ዕውሮችና አንካሶች፣ ሰውነታቸው የሰለለ በርካታ ድውያን ተጠምቀው ይድኑ ዘንድ የእግዚአብሔር መልአክ ወደ ወንዙ ወርዶ ውኃውን እስኪያነዋውጠው ድረስ ይጠባበቁ ነበር፡፡ ውኃው በሚነዋወጥበት ጊዜም በመጀመሪያ ወርዶ የተጠመቀባት ካለበት ደዌ ሁሉ ይፈወስ ነበር፡፡ (ዮ.፭፥፩-፬)

በዚህ ሥፍራ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት ያህል ድኅነትን ሽቶ ከዛሬ ነገ እድናለሁ እያለ ይጠባበቅ የነበረ በሽተኛ (መጻጉዕ) ነበር፡፡ ሕሙማኑ በቤተ ሳይዳ መጠመቂያ የተሰበሰቡት ድኅነትን ፍለጋ ነው፡፡ ዛሬ ደዌ የጸናበት ከደዌ (ከበሽታ) ለመፈወስ ወደ ጠበል እንደሚሄድ በዘመነ ብሉይ የእግዚአብሔር መልአክ (ቅዱስ ሩፋኤል) በሳምንት አንድ ቀን ወደዚያች መጠመቂያ ገብቶ ውኃውን ሲያናውጥ ቀድሞ ወደ መጠመቂያይቱ የገባ ካለበት ደዌ ሁሉ ይፈወስ ነበር፡፡ ዕለቷም ቀዳሚት ሰንበት (ሰንበተ አይሁድ) ነበረች፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት በበሽታ ሲማቅቅ የነበረውን ሰው በዚያ በቤተ ሳዳ መጠመቂያው አጠገብ ተኝቶ አገኘው፡፡ የጠየቁትን የማይረሣ፣ የለመኑትን የማይነሣ አምላክ ነውና የመጻጉዕን ስቃይ ተመለከተ፡፡ ዝም ብሎም ያልፈው ዘንድ አልወደደም፡፡ ፈቃዱንም ይፈጽምለት ዘንድ “ልትድን ትወዳለህን?” ሲል ጠየቀው፡፡ በሽተኛውም “አዎን ጌታዬ ሆይ፤ ነገር ግን ውኃው በተናወጠ ጊዜ ወደ መጠመቂያው የሚያወርደኝ ሰው የለኝም፤ እኔ በምመጣበት ጊዜ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል” አለው፡፡ (ዮሐ. ፭፥፮-፯) መጻጉዕ አጠገቡ ያለው ቆሞም በሐዘኔታ እየተመለከተ የሚጠይቀው ማን እንደሆነ አላወቀምና ለሠላሳ ስምንት ዘመናት ከአልጋው ጋር ተጣብቆ በሕመም ሲሰቃይ መኖሩን፣ እንደ ሌሎቹም በሽተኞች በፍጥነት ወደ መጠመቂያው መውረድ እንዳልቻለ ለማስረዳት ሞከረ፡፡

ጌታችን መድኃኒታቻን ኢየሱስ ክርስቶስ በቃሉ ብቻ መፈወስ ይችላልና በቅፍርናሆም የመቶ አለቃው ልጅ በታመመ ጊዜ መቶ አለቃው በእምነት ሆኖ “አቤቱ አንተ ከቤቴ ጣራ በታች ልትገባ አይገባኝም፤ ነገር ግን በቃልህ እዘዝ፣ ልጄም ይድናል“ብሎ እንደጠየቀው “እንግዲህ ሂድ እንደ እምነትህ ይሁንልህ” ብሎ በዚያች ስዓት ልጁን እንዳዳነው መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡ (ማቴ.፰፥፰) ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ለመጻጉዕ በቅድሚያ ፈቃዱን ነው የጠየቀው፡፡ መጻጉዕም ከዚያ ሲያሰቃየው ከነበረው ደዌ መፈወስ ሽቷልና ምላሹ “አዎን ጌታዬ ሆይ” ነበር፡፡

መጻጉዕ በመጠመቂያው ዳር አልጋው ላይ ተጣብቆ ሳለ ከእርሱ በኋላ መጥተው ከእርሱ በፊት ድነው የሚሄዱ ሰዎች ሲመለከት ሠላሳ ስምንት ዓመታት አሳልፏል፡፡ ዓመቱ በረዘመ ቁጥር ተስፋ ቆርጦ ቤተ ሳይዳን ቤቴ ብሎ ከመኖር በስተቀር ምንም አማራጭ አልበረውም፡፡ በቤተ ሳይዳ መጠመቂያ ስፍራ አምስት መመላለሻዎች ማለትም፡- በሽተኞች፣ አንካሶች፣ ዕውሮችና እግራቸው የሰለለ ድኅትን ሽተው የአምላካቸው ማዳን ይጠባበቁ ነበር፡፡ በየሳምንቱም መልአኩ ከሰማይ ወርዶ ውኃውን ባናውጠው ጊዜ ቀድሞ የገባው አንድ ሰው ብቻ ይድናል፡፡ ይህንን ዕድል ለማግኘት ደግሞ መጻጉዕ አልታደለም፤ ለምን ቢሉ ሌሎች ቅድመውት ወደ መጠመቂያው ይወርዳሉ፡፡ እርሱም ብቻ አይደለም አንካሶች፣ ዕውሮችና እግራቸው የሰለለ ሰዎችም አቅሙ ስለማይኖራቸው ወደ መጠመቂያው ቢወርዱም በሌላው ስለሚቀደሙ ከውኃው የሚያወጣቸው አያገኙም፡፡ ስለዚህ ከውኃው መልሶ የሚያወጣቸው ሰው ያስፈልጋቸዋል፡፡

መጻጉዕ በዚህ ስፍራ የአንድ ጎልማሳ ዕድሜን ያህል ጊዜ እግዚአብሔርን ደጅ በመጥናት አሳልፏል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዚህን ሰው ችግር ያወቀው ማንም ሳይነግረው ነው፡፡ ይፈውሰውም ዘንድ ወደ እርሱ ቀርቦ “ልትድን ትወዳለህን?” አለው፡፡ ጌታችን የሚፈልገው ይህንን ሰው መፈወስ እንጂ የራሱን ማንነት ማሳየት ስላልነበረ “ላድንህ ትወዳለህን?” አላለውም፡፡ ይህ ሰው የጌታችንን ማንነት አያውቅም፡፡ ነገር ግን ድኅነትን ናፍቋልና “ልትድን ትወዳለህን?” ባለው ጊዜ አላመነታም፡፡ “አዎን ጌታዬ ሆይ” ሲል መለሰ፡፡

ጌታችንምመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በሽተኛውን ይፈውሰው ዘንድ ፈቃዱ ስለሆነ ወደ መጠመቂያው ውረድ አላለውም፡፡ በተቃራኒው ጌታችን በቃል ብቻ መፈወስ ይችላላና “ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሒድ” አለው፡፡ ጌታችን መድኅኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ባላሰበው ባልጠበቀው መንገድ ፈወሰው፡፡ ይህ ሰው ሠላሳ ስምንት ዓመት ሙሉ ሲጠባበቃት የነበረችውን የቤተ ሳይዳ ጠበል ሳያገኝ ፣ በመልአኩ መውረድ ሳይሆን በመላእክት ፈጣሪ ቃል ተፈወሰ፡፡

ከላይ የመቶ አለቃውን ልጅ በቃል ብቻ እንደፈወሰው አይተናል፤ በተጨማሪም በጠበል ተጠምቆ መዳንን በተመለከተ ዕውር ሆኖ የተወለደውን ሰው ታሪክ ማንሣት እንችላለን፡፡ ዕውር ሆኖ በተወለደው ሰው ምክንያት ደቀ መዛሙርቱ “ይህ ሰው ዕውር ሆኖ የተወለደው በማን ኃጢአት ነው? በራሱ ነውን? ወይስ በወላጆቹ?” ብለው በጠየቁት ጊዜ “የእግዚአብሔር ሥራ ሊገለጥበት ነው እንጂ እርሱ አልበደለም፤ ወላጆቹም አልበደሉም፤ …” አላቸው፡፡ በዚህ ብቻ አላበቃም በምድር ላይ ምራቁን እንትፍ አለ፤ ምራቁንም ጭቃ አድርጎ የዕውሩን ዐይኖች ቀባው፡፡ እንዲህም አለው” ሂድና በሰሊሆም መጠመቂያ ታጠብ” አለው፤ ከቶ ለእግዚአብሔር የሚሣነው ነገር የለምና ዕውሩ በታዘዘው መሠረት ሄዶ ታጠበና እያየ ተመለሰ፡፡ (ዮሐ. ፱፥፩-፯) መጻጉዕንም ጠበል ሳያስፈልገው “አልጋህን ተሸክመህ ሂድ” ብሎታልና ተፈውሶ እርሱን ለሠላሳ ስምንት ዓመት ተሸክማው የነበረችውን አልጋ ተሸክሞ ለመሄድ በቃ፡፡

 በእነዚህ ታሪኮች እንደተመለከትነው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እርሱ በወደደው መንገድ ማለትም፡- በጠበል፣ ያለ ጠበልም፤ በቃሉ፣ በዝምታ፣ በሌሎችም መንገዶች ማዳን እንደሚችል እንረዳለን፡፡ መጻጉዕንም ሳይውል ሳያድር፣ ላገግም ሳይል በቅጽበት አፈፍ ብሎ ተነሥቶ የተሸከመችውን አልጋ ተሸክሞ ለመሄድ ችሏል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ይህንን መሠረት አድርጋ የዐቢይ ጾም አራተኛ ሳምንትን “መጻጉዕ” ብላ ሰይማዋለች፡፡

ጌታችን መጻጉዕን ብቻ ፈውሶት ሔደ? ቢባል የፈወሰው እርሱን ብቻ አይደለም፡፡ እርሱን በሥጋ ቢፈውሰውም ተአምራቱን አይተው በማመናቸው በነፍሳቸው የተፈወሱ ይበዛሉ፡፡ “ሕሙማነ ሥጋን በተአምራት፣ ሕሙማነ ነፍስን በትምህርት እየፈወሰ” እንዲሉ አበው በዚያ ሥፍራ በሥጋ ታመው በነፍሳቸው አምነው የዳኑ ብዙዎች ናቸው፡፡

ይህ ሰው ተፈውሶ አልጋውን ተሸክሞ ሲሔድ ሰንበት ለሰው ድኅነት እንደተፈጠረች ያልተረዱ አይሁድ ከአልጋው ተነሥቶ የተሸከመችውን አልጋ ተሸክሞ በአደባባይ ሲያዩት በተሠራው የድኅነት ሥራ አልተደሰቱም፡፡ በዚህም ምክንያት “ዛሬ ሰንበት ነው፤ አልጋህን ልትሸከም አይገባህም” አሉት፡፡ “እንኳን ለዚህ አበቃህ!” ያለው ግን አንድም ሰው አልነበረም፡፡

መጻጉዕም መልሶ “ያዳነኝ እርሱ አልጋህን ተሸክመህ ሂድ አለኝ” አላቸው፡፡ አይሁድም አንድ ጊዜ ጠይቀው ብቻ አላለፉትም ያዳነውን “ሰንበትን ሽሯል” ብለው ለመክሰስ ፈልገዋልና   “አልጋህን ተሸክመህ ሂድ ያለህ ሰውዬው ማነው?” በማለት ጠየቁት፡፡ በወቅቱ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመካከላቸው ተሰውራቸዋልና በቦታው ሊያገኘው አልቻለም፡፡ ነገር ግን መጻጉዕ ያዳነውን ጌታችንን በቤተ መቅደስ አገኘውና ሄዶ ያዳነው ኢየሱስ እንደሆነ ለአይሁድ ነገራቸው፡፡

መጻጉዕ ከዚህ በኋላ ወደ አይሁድ ሄዶ ጌታን መክሰሱና ለጌታ ሞት የመማከራቸው ምክንያት መሆኑ ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “እነሆ ድነሃል፤ ግን ከዚህ የባሰ እንዳያገኝህ ዳግመኛ እንዳትበድል ተጠንቀቅ” ብሎት ነበርና (ዮሐ. ፲፰፥፳፫) ነገር ግን ሊሰማው አልፈቀደም፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተያዘበት በምሴተ ሐሙስ ለሊቀ ካህናቱ አግዞ ጌታችንን በጥፊ መታው፡፡ “ወርቅ ላበደረ ጠጠር” እንዲሉ አበው የሠላሳ ስምንት ዓመት ስቃዩን ረስቶ፣ ከዚያ በላይ መከራ እንደሚያገኘው እየተነገረው ያዳነውን አምላኩን ካደ፡፡

ምንባባትና መልእክታት

የቅዱስ ጳውሎስ መልእክት (ገላ. ፭÷፩-ፍጻሜ)

“እንግዲህ ጸንታችሁ ቁሙ፤ እንደገናም በባርነት ቀንበር አትኑሩ፡፡ እነሆ÷እኔ ጳውሎስ እላችኋለሁ፤ “ብትገዘሩም በክርስቶስ ዘንድ ምንም አይጠቅማችሁም፡፡” ደግሞም ለተገዘረ ሰው ሁሉ የኦሪትን ሕግ መፈጸም እንደሚገባው እመሰክራለሁ፡፡  …” (ገላ. ፭÷፩-ፍጻሜ)

የቅዱስ ያዕቆብ መልእክት (ያዕ.፭÷፲፬- ፍጻሜ)

“ከእናንተ የታመመ ሰው ቢኖር በቤተ ክርስቲያን ያሉ ቀሳውስትን ይጥራና ይጸልዩለት፤ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም የተጸለየበትንም ዘይት ይቅቡት፡፡ የሃይማኖት ጸሎትም ድውዩን ይፈውሰዋል፤ እግዚአብሔርም ያስነሣዋል፤ ኃጢአትንም ሠርቶ እንደሆነ ይሰረይለታል፡፡ …”  (ያዕ. ፭÷፲፬- ፍጻሜ)

ግብረ ሐዋርያት (የሐዋ. ÷፩-፩)

“ጴጥሮስና ዮሐንስም በዘጠኝ ሰዓት ለጸሎት በአንድነት ወደ ቤተ መቅደስ ወጡ፡፡ ከእናቱ ማኅፀንም ጀምሮ እግሩ ሽባ ሆኖ የተወለደ አንድ ሰው ነበር፤ ወደ መቅደስም ከሚገቡት ምጽዋት ይለምን ዘንድ ሁል ጊዜ እየተሸከሙ መልካም በሚሏት በመቅደስ ደጃፍ ያስቀምጡት ነበር፡፡ ጴጥሮስንና ዮሐንስንም ወደ መቅደስ ሲገቡ አይቶ ምጽዋት ይሰጡት ዘንድ ለመናቸው፡፡ ጴጥሮስም ከዮሐንስ ጋር ትኩር ብሎ ተመለከተውና “ወደ እኛ ተመልከት” አለው፡፡ ወደ እነርሱም ተመለከተ፤ ምጽዋት እንደሚሰጡትም ተስፋ አድርጎ ነበር፡፡ ጴጥሮስም “ወርቅና ብር የለኝም ያለኝን ግን እሰጥሃለሁ፤ እነሆ በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሥተህ ሂድ” አለው፡፡ በቀኝ እጁም ይዞ አስነሣው፤ ያን ጊዜም እግሩና ቁርጭምጭሚቱ ጸና፡፡ …” (የሐዋ. ÷፩-፩)

የዕለቱ ምስባክ (መዝ.÷)

“እግዚአብሔር ይረድኦ ውስተ ዓራተ ሕማሙ፤

ወይመይጥ ሎቱ ኩሉ ምስካቤሁ እምደዌሁ

አንሰ እቤ እግዚኦ ተሣሃለኒ፤ እግዚአብሔር በደዌው አልጋ ሳለ ይረዳዋል፤ መኝታውን ሁሉ በበሽታው ጊዜ ያነጥፍለታል፤ እኔስ አቤቱ ማረኝ።” (መዝ. ፵÷፫)

ወንጌል (ዮሐ.፩-፳፬)

“ከዚህ በኋላ የአይሁድ በዓል እንዲህ ሆነ፤ ጌታችን ኢየሱስ ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ። በኢየሩሳሌምም በበጎች በር አጠገብ መጠመቂያ ነበረች፤ ስምዋንም በዕብራይስጥ ቤተ ሳይዳ ይሉአታል፣ አምስት እርከኖችም ነበሩአት፡፡ በዚያም ዕውሮችና አንካሶች፣ ሰውነታቸውም የሰለለ ብዙ ድውያን ተኝተው የውኃውን መናወጥ ይጠባበቁ ነበር፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ ወደ መጠመቂያው ወርዶ ውኃውን በሚያናውጠው ጊዜ ከውኃው መናወጥ በኋላ በመጀመሪያ ወርዶ የሚጠመቅ ካለበት ደዌ ሁሉ ይፈወስ ነበርና፡፡ በዚያም ከታመመ ሠላሳ ስምንት ዓመት የሆነው አንድ ሰው ነበር፡፡ ጌታችን ኢየሱስም በአልጋው ተኝቶ ባየ ጊዜ በደዌ ብዙ ዘመን እንደቆየ ዐውቆ “ልትድን ትወዳለህን?” አለው፡፡ ድውዩም መልሶ “አዎን ጌታዬ ሆይ ነገር ግን ውኃው በተናወጠ ጊዜ ወደ መጠመቂያው የሚያወርደኝ ሰው የለኝም፡፡ እኔ በምመጣበት ጊዜ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል፡ አለው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም “ተነሥና አልጋህን ተሸክመህ ሂድ” አለው፡፡ ወዲያውኑም ያ ሰው ድኖ አልጋውን ተሸክሞ ሄደ፤ ያች ቀንም ሰንበት ነበረች፡፡ …” (ዮሐ. ፭ ፩-፳፬)

ቅዳሴ ቅዳሴ ዘእግዚእነ

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምኵራብ

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የዐቢይ ጾም ሦስተኛ ሳምንትን ምኵራብ ብላ ትጠራዋለች። ምኵራብ ሰቀላ መሰል አዳራሽ፣ የአይሁድ የጸሎት ቤት ማለት ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን አይሁድ በኢየሩሳሌም ሥርዓተ አምልኮ የሚፈጽሙበት ቤተ መቅደስ ነበር፡፡ ናቡከደነፆር ኢየሩሳሌምን    በመውረር ቤተ መቅደሳቸውን አፍርሶ ሕዝቡን ወደ ባቢሎን ካፈለሰ ጊዜ ጀምሮ አይሁድ በሚገኙባቸው ስፍራዎች ሁሉ ለጸሎት ምኵራብ መሥራት እንደ ጀመሩ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላትይገልጻል፡፡

አይሁድ በምኲራቦቻቸው የሕግና የነቢያት መጻሕፍትን (የብራና ጥቅሎች) በአንድ ሣጥን ውስጥ በማስቀመጥ የጸሎት ስፍራዎቻቸውን ለትምህርትና ለአምልኮ ይጠቀሙባቸዋል፡፡ በዓመት አንድ ጊዜ የሚቀርበውን መሥዋዕትና መባዓ ለመስጠትም ወደ ቤተ መቅደስ ይወጡ ነበር፡፡ ይህንን መሠረት አድርጎም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ኦሪትንና ነቢያትን ልሽራቸው የመጣሁ አይምሰላችሁ፤ ልፈጽማቸው እንጂ ልሽራቸው አመልመጣሁም፡፡” እንዲል ሕግ ሊፈጽም ወደ ቤተ መቅደስ ይሄድ ነበር፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተ መቅደስ መሄድ ብቻ ሳይሆን በምኵራብ እየተገኘም ያስተምር ነበር፡፡ “ዕለት ዕለትም በቤተ መቅደስ ያስተምር ነበር፡፡” (ሉቃ. ፲፱፥፵፯)፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምኵራብ ተገኝቶ በሚያስተምርበት ወቅት ነጋዴዎች በመሸጥና በመለወጥ ቤተ መቅደሱን ያውኩ ስለነበር ቤተ መቅደሱን ለማስከበር ሲል በዚያ ያሉትን ሻጮችንና ለዋጮችን እየገረፈ፣ የሚሸጡትንም እየገለበጠ አስወጥቷቸዋል፡፡ “ኢትግበሩ ቤተ አቡየ ቤተ ምሥያጥ፤ ቤትየሰ ቤተ ጸሎት ይሰመይ፤ ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል ተብሎ ተጽፎአል፤ እናንተ ግን የሌባና የቀማኛ ዋሻ አደረጋችሁት” አላቸው፡፡ በዚህ ብቻ አላበቃም “በቤተ መቅደስም በሬዎችና በጎችን፣ ርግቦችን የሚሸጡትን ገንዘብ ለዋጮችንም ተቀምጠው አገኘ። የገመድም ጅራፍ አበጀ፤ በጎችንና በሬዎችን ሁሉንም ከቤተ መቅደስ አስወጣ፤ የለዋጮችንም ገንዘብ በተነ፣ ገበታዎቻቸውንም ገለበጠ። ርግብ ሻጮችንም ‘ይህን ከዚህ አውጡ፤ የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉ፡፡” በማለት አስወጣቸው፡፡ (ዮሐ. ፪፥፲፬-፲፮) በዚህም መሠረት የዐቢይ ጾም ሦስተኛ ሳምንት ምኵራብ ተብሏል፡፡

ዛሬም በዘመናችን የእግዚአብሔርን የቅድስና ስፍራ የሚዳፈሩ፣ ለሙስና እና ለራስ ወዳድነት ያደሩ ከአገልጋዮች እስከ ምእመናን ድረስ እንዳሉ ይታወቃል፡፡ በደሙ የዋጃትን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ‘የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችሁት’ እያለ ዛሬም የእግዚአብሔር ድምፅ ይጣራል፡፡ ቤተ ክርስቲያንን በዘር፣ በጎሳ፣ በቋንቋ፣ በመንደር፣ … በመከፋፈል ለቃለ እግዚአብሔር ባለመታመን ኃጢአት የምንሠራና የግል ፍላጎታችንን ለማሟላት የምንሮጥ ብዙዎች ነን፡፡ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ዶግማ፣ ቀኖና፣ ሥርዓትና ትውፊት በመጠበቅ በንስሓ ሕይወት በመመላለስ ከማገልገል ይልቅ ግላዊ ፍላጎትን ለማሟላት የምንሮጥ ሁሉ ራሳችንን መመርመር፣ ከክፉ ተግባራችንም መመለስ ይጠበቅብናል፡፡ ይህ ካልሆነ እግዚአብሔር ምሕረቱ የበዛ አምላክ እንደ መሆኑ መጠን ክፉ ሥራችን በበዛ ቁጥር የቁጣ በትሩን ማሳረፉ አይቀርምና በዚህ በዐቢይ ጾም በተሰበረ ልብ ሆነን በይቅርታው ይጎበኘን ዘንድ ዘወትር ያለመታከት ልንማጸን፣ ልንጸልይ  ይገባል፡፡

በዕለቱ የሚነበቡ መልእክታት፣ ምስባክ እና ወንጌል

መልእክታት፡-  

የቅዱስ ጳውሎስ መልእክት፡- “እንግዲህ በመብልም ቢሆን በመጠጥም ቢሆን በልዩ ልዩ በዓላትም ቢሆን በመባቻም ቢሆን በሰንበትም ቢሆን የሚነቅፋችሁ እንዳይኖር ተጠንቀቁ፡፡ ይህ ሁሉ ይመጣ ዘንድ ላለው ጥላ ነውና፤ አካሉ ግን የክርስቶስ ነው፡፡ በመታለልና ራስን ዝቅ በማድረግ ለመላእክት አምልኮ ትታዘዙ ዘንድ ወድዶ በአላየውም በከንቱ የሥጋው ምክር እየተመካ የሚያሰንፋችሁ አይኑር፡፡ ሥጋ ሁሉ ጸንቶ በሚኖርበት በሥርና በጅማትም በሚስማማበት በእግዚአብሔርም በሚያድግበትና በሚጸናበት፣ በሚሞላበትም በራስ አይጸናም፡፡

ከዚህ ዓለም ኑሮ ከክርስቶስ ጋር ከሞታችሁ እንደገና በዓለም እንደሚኖሩ ሰዎች እንዴት ትሠራላችሁ? እንዴትስ ይህን አትዳስስ፣ ይህን አትንካ፣ ይህንም አትቅመስ፣ ይሉአችኋል? ይህ ሁሉ እንደ ሰው ትእዛዝና ትምህርት ለጥፋት ነውና፡፡ ይህም ስለ ልብ ትሕትናና እግዚአብሔርንም ስለ መፍራት፣ ለሥጋም ስለ አለማዘን ጥበብን ይመስላል፤ ነገር ግን ከሥጋ በላይ ነው እንጂ ምንም ክብር የለውም፡፡” (ቆላስ. ፪፥፲፮-፳፫)

የቅዱስ ያዕቆብ መልእክት፡- “ወንድሞቼ ሆይ፣ እምነት አለኝ ምግባር ግን የለኝም የሚል ሰው ቢኖር ምን ይጠቅመዋል? በውኑ እምነቱ ልታድነው ትችላለችን? ከወንድሞቻችን ወይም ከእኅቶቻችን የታረዙ ወይም የዕለት ምግብ ያጡ ቢኖሩ ከእናንተም አንዱ ‘በሰላም ሂዱ እሳት ሙቁ ትጠግባላችሁም’ ቢላቸው ለችግራቸውም የሚሹትን ባይሰጣቸው ምን ይጠቅማቸዋል? እንዲሁም ሥራ የሌለው እምነት ቢኖር በራሱ የሞተ ነው፡፡ …”

ነገር ግን አንድ ሰው “አንተ እምነት አለህ እኔም መልካም ሥራ አለኝ፤ እስቲ ሃይማኖትህን ከሥራህ ለይተህ አሳየኝ፤ እኔም እምነቴን በሥራዬ አሳይሃለሁ” ይላል፡፡ አንተም እግዚአብሔር አንድ እንደሆነ ታምናለህ፤ መልካምም ታደርጋለህ፤ እንዲህስ አጋንንትም ያምናሉ፤ ይንቀጠቀጣሉም፡፡ አንተ ሰነፍ ሰው እምነት ያለ ምግባር የሞተች እንደሆነች ልታውቅ ትወዳለህን? አባታችን አብርሃም ልጁን ይስሐቅን ወደ መሠዊያው ባቀረበው ጊዜ በሥራው የጸደቀ አይደለምን? እምነት ለሥራው ትረዳው እንደ ነበር፣ በሥራውም እምነቱ እንደመላችና ፍጽምት እንደሆነችም ታያለህን? መጽሐፍ አብርሃም በእግዚአብሔር አመነ፣ ጽድቅ ሆኖም ተቆጠረለት” የሚለው ተፈጸመ፤ የእግዚአብሔርም ወዳጅ ተባለ፡፡ ሰው በሥራ እንደሚጸድቅ በእምነት ብቻ እንዳይደለ ታያለህን? እንዲሁ ዘማይቱ ረአብ ደግሞ ጉበኞችን ተቀብላ በሌላ መንገድ ባወጣቻቸው ጊዜ በሥራ አልጸደቀችምን? ከነፍስ የተለየ ሥጋ የሞተ እንደሆነ እንዲሁ ደግሞ ከሥራ የተለየ እምነት የሞተ ነው፡፡” (ያዕ. ፪፥፲፰-፳፮)

የሐዋርያት ሥራ፡- “በቂሳርያም ቆርኔሌዎስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፤ ኢጣሊቄ ለሚሉት ጭፍራ የመቶ አለቃ ነበር፡፡ እርሱም ጻድቅና ከቤተሰቡ እግዚአብሔርን የሚፈራ ነበር፤ ለሕዝብም ብዙ ምጽዋት ይሰጥ ነበር፤ ዘወትርም ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ ነበር፡፡ የእግዚአብሔር መልአክም በራእይ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት በግልጥ ታየው፤ ወደ እርሱም ገብቶ፡- “ቆርኔሌዎስ ሆይ” አለው፡፡ ወደ እርሱም ተመልክቶ ፈራና “አቤቱ ምንድነው?” አለ፤ መልአኩም እንዲህ አለው፡- “ጸሎትህም ምጽዋትህም መልካም መታሰቢያ ሆኖ ወደ እግዚአብሔር ዐርጓል፡፡ አሁንም ጴጥሮስ የሚባለውን ስምዖንን ይጠሩልህ ዘንድ ወደ ኢዮጴ ከተማ ሰዎችን ላክ፡፡ እርሱም ቤቱ በባሕር አጠገብ ባለው በቁርበት ፋቂው በስምዖን ቤት በእንግድነት ተቀምጧል፡፡ ልታደርገው የሚገባህን እርሱ ይነግርሃል፡፡” ያነጋገረውም መልአክ ከሄደ በኋላ ከሎሌዎቹ ሁለት፣ ከማይለዩት ጭፍሮቹም አንድ ደግ ወታደር ጠራ፡፡ ነገሩንም ሁሉ ነግሮ ወደ ኢዮጴ ከተማ ላካቸው፡፡” (የሐዋ. ፲፥፩-፱)

ወንጌል

የዮሐንስ ወንጌል፡- “ከዚህም በኋላ እርሱና እናቱ ከወንድሞቹና ደቀ መዛሙርቱም ጋር ወደ ቅፍርናሆም ወረዱ፤ በዚያም ብዙ ያይደለ ጥቂት ቀን ተቀመጡ፡፡ የአይሁድም የፋሲካቸው በዓል ቀርቦ ነበር፤ ጌታችን ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ፡፡ በቤተ መቅደስም በሬዎችንና በጎችን፣ ርግቦችንም የሚሸጡትን ገንዘብ ለዋጮችንም ተቀምጠው አገኘ፡፡ የገመድም ጅራፍ አበጀ፤ በጎችንና በሬዎችን፣ ሁሉንም ከቤተ መቅደስ አስወጣ፣ የለዋጮችንም ገንዘብ በተነ፣ ገበታዎቻቸውንም ገለበጠ፡፡ ርግብ ሻጪዎችንም “ይህን ከዚህ አውጡ፤ የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉ” አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም “የቤትህ ቅናት በላኝ” የሚል ቃል ተጽፎ እንዳለ ዐሰቡ፡፡ …” (ዮሐ. ፪፥፲፪-፳፭)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“ግቢ ጉባኤ ቤተ ክርስቲያን በወጣትነት ዘመናቸው ልጆቿን አቅፋ የያዘችበት ትልቁ ተቋም ነው” (ዐወቀ አበብሽ ከጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ)

ክፍል ሁለት

በእንዳለ ደምስስ

የተከበራችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች በክፍል አንድ ዝግጅታችን በጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ ጤና ሳይንስ በ፳፻፲፮ ዓ.ም ካስመረቃቸው ተማሪዎች ፫.፱ አጠቃላይ ውጤት በማስመዝገብ የዋንጫና ሜዳልያ ተሸላሚ የሆነውን የዐወቀ አበብሽተሞክሮ ማቅረባችን ይታወሳል፡፡ ክፍል ሁለትን እንዲህ አዘጋጅተነዋል- መልካም ቆይታ፡፡

  • ካለህ ውጤት አንጻር የጊዜ አጠቃቀምህን ብታብራራልን?

የጊዜ አጠቃቀምን በተመለከተ እንደ ተማሪው ሥነ ልቡና እና አስተሳሰብ የሚወሰን ነው፡፡ በግቢ ውስጥ ብዙ ዓይነት የተማሪዎችን ባሕርይ ነው የምትመለከተው፡፡ ለጊዜ ግድ የሌለውና በመዝናናት ጊዜውን የሚያባክን፣ ራሱን በጥናት ብቻ የሚጠምድና እወድቃለሁ ብሎ የሚጨነቅ፣ ብቻውን መሆን የሚፈልግ፣ … ብዙ ዓይነት ተማሪ ነው ያለው፡፡

እኔ ግን ከመደበኛ ትምህርቴ ውጪ ጊዜዬን አብቃቅቼ ለቤት ሥራ፣ ለጥናት፣ ለአገልግሎት፣ ለቤተ ክርስቲያን እያልኩ ከፋፍዬ ሳልጨናነቅ ነው ሕይወቴን በዕቅድ የመራሁት፡፡ አንዳንድ ጊዜ የማጥናት ፍላጎት ከሌለኝ ከመተኛት ቀጥታ ወደ ቤተ ክርስቲያን ነው የምሄደው፡፡ ጸሎት አድርጌ፣ ራሴን አረጋግቼና ጥሩ ስሜት ይዤ እመለሳለሁ፡፡ ያኔ ሙሉ ዐቅም ስለሚኖረኝ ለማጥናት አልቸገርም፡፡ በጣም የሚገርምህ ክፍል ውስጥ በደንብ ስለምከታተል፣ እንዲሁም የተማርኩትን ቶሎ ስለምይዝ ለረጅም ሰዓት የማጥናት ልምዱ የለኝም፡፡ ለአላስፈላጊ ሳቅና ጨዋታም ብዙም ትኩረት አልሰጥም፡፡ ይህንን ስል ጓደኞች የሉኝም አልልም፡፡

ለሌሎች የምመክረው ነገር ቢኖር ለጊዜ ያላቸው ትርጉምና አፈጻጸም ላይ ትኩረት ሰጥተው መሥራት እንደሚገባቸው ነው፡፡ “በኋላ እደርሳለሁ” የሚለው አስተሳሰብ ከዓላማ የሚያዘናጋ በመሆኑ ሁሉንም ነገር በጊዜው ማከናወን ተገቢ ነው፡፡ በርካታ ተማሪዎች ስልቹዎች ናቸው፡፡ ይህንን ችግር ለመቅረፍ ቤተ ክርስቲያን ቢሄዱና ጸሎት አድርሰው የጥሞና ጊዜ ወስደው መመለስ ቢችሉ መልካም ነው፡፡ በተለይ ሌሊት ኪዳን አድርሶ መመለስና ማጥናት፣ እንዲሁም ማታ ከራት በኋላ ተመራጭ የጥናት ጊዜያት ስለሆኑ ቢጠቀሙበት እላለሁ፡፡

  • የጓደኛ ተጽእኖን እንዴት ተቋቋምከው?

ጊዜን በአግባቡ እንዳንጠቀም ከሚያደርጉን ነገሮች ውስጥ ጓደኛ ማብዛት ነው፡፡ የጓደኛ ተጽእኖ የሚያሳድረው ተጽእኖ ቀላል አይደለም፡፡ እያንዳንዱ ጓደኛ የራሱ የሆኑ ባሕርያት ስለሚኖሩት ወደአልተፈለገ ድርጊት ሊመራን ስለሚችል ጓደኛን ማወቅ፣ ቁጥራቸውንም መቀነስ ይገባል፡፡

በቅድሚያ የጓደኛ አመራረጥ የሚወሰነው በአንተ አስተሳሰብና ፍላጎት ላይ ተመሥርቶ ነው፡፡ መምረጥ ሲባል እገሌ ይሆነኛል አይሆነኝም ተብሎ ሳይሆን በሂደት ነው፡፡ ጓደኛን ለመምረጥ ሂደትን ይጠይቃልና፤ በቅጽበት በአንድ ጊዜ የሚከናወን ስለማይሆን እዚህ ላይ ጥንቃቄ ይሻል፡፡ ጓደኛን የምታገኘው አንተ በምትውልበት፣ በምታድርበትና በምትሄድበት ስለሆነ በሂደት በአስተሳሰብ፣ ፍላጎትና ዓላማ ላይ ተመሥርቶ ነው መመረጥ ያለበት፡፡

በምትጓዝበት የሕይወት መስመር ላይ በባሕርይ አንተን የሚመስል ሰው ልታገኝ ትችላለህ፡፡ መግባባትና መጠናናት፣ ከዚያም ውሳኔ የሚፈልግ ጉዳይ ነው፡፡ እኔ በጓደኛ አመራረጥ ደረጃ ከታች ክፍል ጀምሮ አብሮኝ የተማረ ጓደኛዬ አንድ ላይ ደርሶን ስለነበር አልተቸገርኩም፡፡ በተረፈ የምቀርባቸው ሁሉ የቤተ ክርስቲያን ወንድሞችና እኅቶች ስለሆኑ ክፉ ጓደኛ አልገጠመኝም፡፡

  • ትምህርትህ ላይ ብቻ ትኩረት አድርግ፤ ወደ ግቢ ጉባኤ እንዳትሄድ የሚል ቤተሰብ ወይም ጓደኛ አልገጠመህም?

ያደግሁት ገጠር ውስጥ ነው፡፡ ቤተሰቦቼም ገበሬዎች ስለሆኑ ስለ ግቢ ጉባኤ የሚያውቁት ነገር የለም፡፡ የእነርሱ ፍላጎትና ምኞት እኔ ተምሬ ጥሩ ደረጃ እንድደርስ የሚችሉትን መርዳት ነው፡፡ ስለዚህ ወደ ግቢ ጉባኤ እንዳልሄድ ያገደኝ ነገር አልነበረም፡፡ በርግጥ አንዳንድ ተማሪዎች ከቤተሰብ ወይም ከጓደኛ በሚደርስባቸው ተጽእኖ ምክንያት “ወደ ግቢ ጉባኤ አትሂዱ” ይላሉ፡፡ ይህ ደግሞ ካለመረዳትና ጥቅሙን ካለመገንዘብ የመነጨ ነው፡፡ እኔ ውጤቴ ያማረ እንዲሆን የግቢ ጉባኤ ሚና ትልቁን ድርሻ ይወስዳል፡፡

  • ግቢ ጉባኤ በመሳተፍህ ምን ጥቅም አገኘህ?

ግቢ ጉባኤ ውስጥ መሳተፍ ትልቅ ጥቅም አለው፡፡ ተማሪ ሃያ አራት ሰዓት ሙሉ ሲያጠና አይቆይም፡፡ ከትምህርት በኋላ ያለው ጊዜ በጣም ብዙ ስለሆነ ካልተጠነቀቅህ ለተለያዩ ችግሮች መጋለጥ አይቀርም፡፡ በግቢም ሆነ በውጪ ተገቢ ያልሆኑ ድርጊቶች ከተማሪዎች የማይጠበቁ ድርጊቶች ስለሚከናወኑ ተጋላጭ ትሆናለህ፡፡ ግቢ ጉባኤ ውስጥ ስትሳተፍ ዓላማ ያለው ሰው ሆነህ ትቀረጻለህ፡፡ ግቢ ጉባኤ ቤተ ክርስቲያን በወጣትነት ዘመናቸው ልጆቿን አቅፋ የያዘችበት ትልቁ ተቋም ነው፡፡ በመንፈሳዊ ትምህርት ታድጋለህ፣ በወንድሞችና እኅቶች ምክር ትታነጻለህ፡፡ ስለዚህ ግቢ ጉባኤ ውስጥ መሳተፍ ለዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ጠቀሜታው እጅግ የጎላ ነው፤ ከክፉ ነገር ትጠበቃለህ፣ በባሕርይ፣ በአስተሳሰብ፣ … አድገህና ተቀርጸህ እንድትወጣ ያደርግሃል፡፡

  • ቤተ ክርስቲያን በእያንዳንዱ የግቢ ጉባኤ ተማሪ ውስጥ ያላት ድርሻ ምንድነው ትላለህ?

ቤተ ክርስቲያንን ማወቅ፣ በቃሏም መመራት፣ ወደ ቅድስናው ስፍራም ዘወትር መገስገስ እንደ አማራጭ የሚቀርብ ሳይሆን ግዴታ ነው፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያን ስትሄድና ስትጸልይ የተበታተነው አእምሮህ ይሰበሰባል፤ በመንፈሳዊ ዕወቀትም ሆነ በመንፈሳዊ ሕይወት እያደግህ ትሄዳለህ፤ ውጤታማም ሆነህ ትወጣለህ፡፡ ስለዚህ ከራስ ጀምሮ ሀገርን ለማገልገል ቤተ ክርስቲያን ያላት ድርሻ ከፍተኛ ነው፡፡

በቀን ውስጥ ትምህርት ላይ የምንሆነው ከስምንት ሰዓት በላይ አይሆንም ስለዚህ ባለን ትርፍ ሰዓት ቤተ ክርስቲያን ሄደን ብንገለገል፣ እንደ ጸጋችንም ብናገለግል በረከት እናገኛለን፡፡

  • በግቢ ጉባኤ አገልግሎት ውስጥ እንደ ችግር የምታነሣው ሐሳብ ካለህ?

እንደ ጅግጅጋ ግቢ ጉባኤ እንደ ችግር የማነሣው ቢኖር ዩኒቨርሲቲው ካለው ርቀት አንጻር ክትትል ያስፈልገዋል፡፡ ማእከሉንም ሆነ ግቢ ጉባኤያቱን መቃኘት፣ የጎደሉ ነገሮችን ማሟላት ላይ የዋናው ማእከል ግቢ ጉባኤት ማስተባበሪያ እገዛ ይፈልጋል፡፡ በተለይ ሦስተኛ እና አራተኛ ዓመት ላይ ለተማሪዎች የሚደረገው ክትትል ዝቅ ያለ ስለሆነ ቢታሰብበት እላለሁ፡፡

ሌላው አንዳንድ ጊዜ የመርሐ ግብር መደራረብ ይታያል፡፡ ግቢዎቹ የተለያዩ እንደመሆናቸው መጠን የፈተና የጊዜ ሰሌዳው ሊለያይ ስለሚችል አንዱ ግቢ ፈተና ሲሆን ሌላው ትምህርት ላይ ወይም ፈተና ጨርሶ ሊሆን ይችላል፡፡ ስለዚህ ይህንን ታሳቢ ያደረገ ቢሆን፣ የመምህራን እጥረትና አቅምም ከግምት ውስጥ በማስገባት በሥልጠና ዕውቀታቸውን ማሳደግ ቢቻል ጥሩ ነው እላለሁ፡፡

  • ከምረቃ በኋላ በርካታ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች መንፈሳዊነትን እዚያው የጨረሱ ስለሚመስላቸው ወደ አገልግሎት ሲመጡ አይታይም፡፡ አንተስ ምን አስበሃል? ለሌሎችስ ምን ትመክራለህ?

የዩኒቨርሲቲው የምረቃ ሥነ ሥርዓት ወዲያው ነው የተፈጸመው፡፡ የግቢ ጉባኤው መርሐ ግብር ግን ልዩ ትኩረት ሰጥቶ በጥሩ ሁኔታ በመንፈሳዊ ምክር፣ በወንጌል ትምህርት፣ በዝማሬና በአባቶች ቡራኬ ነው ያስመረቀንና በጣም ደስተኞች ነን፡፡ እኔ ወዲያው ነው ከግቢ ከወጣሁ በኋላ ማገልግል እንዳለብኝ ራሴን ያሳመንኩት፡፡ እስከ አሁን ከነበረኝ አገልግሎት በይበልጥ አገለግላለሁ ብዬ ነው የማስበው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልዩ ክብር ሰጥታ ነው “ልጆቼ እንኳን ደስ ያላችሁ” ብላ አክብራ በቡራኬ ያስመረቀችን፡፡ ስለዚህ እኛ ደግሞ ውለታዋን ልንመልስ ያስፈልጋል፡፡ ሰፊ አገልግሎት ውስጥ መሳተፍ ባንችል እንኳን ራሳችንን ጥሩ አርቶዶክሳዊ አድርገን ማነጽ በራሱ አገልግሎት ነው፡፡

አገልግሎት ከሥራ ጋር አይመችም የሚሉ ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ከሥራ በኋላ ልናገለግል የምንችልባቸው መንገዶች በርካታ ናቸው፡፡ በሰንበት ት/ቤት፣ በሰበካ ጉባኤ፣ በማኅበራት፣ በማኅበረ ቅዱሳን መዋቅር በማእከላት፣ በወረዳ ማእከላት፣ … መሳተፍ እንችላለን፡፡ ራሳችንን ለስንፍና ከማጋለጥ ልንቆጠብ ያስፈልጋል፡፡

የእያንዳንዳችን ፀጋና የአገልግሎት መንፈስ ስለሚለያይ የሚያስተምረው ቢያስተምር፣ ይበልጥ መማር ያለበት ቢማር፣ የሚያስተባብረውም እንደተሰጠው ኃላፊነት ማገልገል ያስፈልጋል፡፡

  • ተሞክሮህን ስላካፈልከን በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን፡፡

እኔም አመሰግናለሁ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዘወረደ

ትዕግሥት ሳዝነው

ከፍጥረት አልቆ በክብር ቢያበጀው፣

አዳም ክብር ሽቶ ክብሩን አቆሸሸው፣

ምንም ሳያጎድል ሁሉን ለእርሱ ሰጥቶ፣

ይቀመጥባት ዘንድ ገነትን ርስት አድርጎ፣

በውስጧ ያሉትን ፍጥረታትን ገዝቶ፣

አምላኩ ሲሾመው ጌታዋ አድርጎ፡፡

አንድ ሕግ ነበረ ለአምላክ ቃል የገባው፣

ከዛፎቹ ሁሉ አንዷን ዛፍ እንዲተው፣

እንዲህ ሲል አዘዘው፡፡

ክፉ እና ደጉን ከምታሳውቀው፡፣

ሞትን እንዳትሞት ከዚ’ች ዛፍ አትብላ፣

ከእርሷ በበላህ ቀን ትሞታለህና፣

ክብሩን ያላወቀ ማዕረጉን የረሣ፡፡

በተሰጠው ፍጥረት አዳም ተታለለ፣

ትእዛዝ እና ሕጉን የአምላኩን ቃል ጣሰ፡፡

 ዕፀ በለስ በልቶ አምላክ ይሆን ዘንድ፣

 በፍጥረት በእባብ ተታለለ ሳይወድ፣

በበላትም ቅፅበት ቆርጦ እንደወሰዳት፣

ክብርና ማዕረጉን አጥቶ ወረደ ከገነት፣

ሞትንም ሊቀምሳት መጣ ወደ መሬት፣

ትእዛዙን ተላልፎ አዳም ቢበድልም፣

ሕግን በመሻሩ በአዳም በደል ቢያዝንም፡፡

ንስሓን ሊሰጠው ይቅር ሊለው ወ’ዶ፣

ከሰማዩ ክብር ከዙፋኑ ወርዶ፣

ከፈጠረው ፍጥረት ከማርያም ተወልዶ፡፡

እርሱ በመውረዱ አዳም እንዲወጣ፣

አምላክ ሰው ሆነ ከእነክብሩ መጣ፣

አዳም የሻውን የአምላክነት ፀጋ፣

በአምላክ ሰው መሆን ከአምላኩ ተጠጋ፡፡

 የአዳም በደል ሊፍቅ የአዳም ቁስል ሊሽር፣

 አምላክ እንዲወርድ ቢያስገድደው ፍቅር፣

 እሱ ባላጠፋው ባልሠራው ኃጢያት፣

 በጅራፍ ተገርፎ በመስቀል ቢሰቅሉት፣

 አምላክ ነፍሱን ሰጥቶ የእርሱን ነፍስ አዳናት፡፡

 እኛም የአዳም ልጆች  ፍቅሩ ያልገባን፣

 አምላክ ይቅር ሲለን እኛ እየበደልን፣

ንስሓን ቢሰጠን በኃጢአት መኖር መርጠን፣

በዘር በጥላቻ በክፋታችን ደምቀን፣

ከተሰጠን ክብር ጌትነትም ወረድን፡፡

ወንድሙን ሊገድል ወዳጁን ሊከዳ፣

ሰው ከንቱ ሰው መና ይደክማል በጓዳ፡፡

ከተሰጠው ፍቅር ከተሰጠው ሕይወት፣

የክፋት አባቱ ዲያቢሎስ በልጦበት፣

 የዘር ጣዖት ሠርቶ ኖረ ሲሰግድለት፣

 ይህን በደል ዐይቶ ልቡናዬ ቢያዝን፣

 አምላክ ውረድና ቅጣን እንዳልለው፣

 እኔም ሰው ነኝና እንዳልቀጣ ፈራው፣

 ቂም በቀል ትዕቢት መለያየት ስመኝ፣

 በኃጢያት በክፋት በበደል ስጎበኝ፣

 አምላክ ዛሬም ውረድ ከበደሌ እጠበኝ፡፡

 የተሰጠኝ ፍቅር መጻሕፍትን ጥፎ፣

 ሐዋርያትን ሹሞ ሕግና ሥርዓትን፣

 ቀኖናን አትሞ ፃድቃን ሰማዕታትን፣

 መምህራንን ጠርቶ ትእዛዙን ሠራልን፡፡

 በደሙ አትሞ ከሕጉ የወጡት በግራው ሲቆሙ፣

 በሕጉ የፀኑት በቀኙ ሊቆሙ፣

ያኔ ሠርቶልናል ከሰማያት ወርዶ፣

ከፈጠራት ፍጥረት ከድንግል ተወልዶ።

ዘወረደ

ትርጕሙ ከሰማየ ሰማያት የወረደ ማለት ነው፡፡ ከሰማየ ሰማያት የወረደውን፣ ከድንግል ማርያም የተወለደውን አምላክ ለማመስገን ከሰማየ ሰማያት መውረዱን ለመዘከር የሚጾም ጾም ነው፡፡ ጌታችን ጾመ ከማለት አስቀድሞ ከሰማየ ሰማያት መውረዱን ከድንግል ማርያም መወለዱን መናገር አስፈላጊ ነውና የመጀመሪያው ሳምንት “ዘወረደ” ተብሏል፡፡

አምላካችን አምስት ሺህ አምስት መቶው ዘመን ሲፈጸም ከእመቤታችን ከቅድስት ማርያም ከሥጋዋ ሥጋን፣ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ ሰው ከሆነ በኋላ ምልዓቱን ሳይለቅ በሰው አካል ተወስኖ ለሠለሳ ሦስት ዓመታት በዚህ ምድር ላይ ተመላልሶ ወንጌልንም አስተምሯል፡፡ ስለዚህ ወረደ” የሚለው ቃል እግዚአብሔር ሰው ሆኖ ያመለክተናል፡፡

ይህ የዐቢይ ጾም የመጀመሪያው ሳምንት “ጾመ ሕርቃል” እየተባለም ይጠራል፡፡ ሕርቃል (ኤራቅሊዮስ) በ፮፻፲፬ ዓ.ም የነበረ የቤዛንታይን ንጉሥ ነው፡፡ ለክርስቲያኖች ባደረገው ርዳታ ምክንያት አንድ ሳምንት ጾመውለታል፡፡ አባቶቻችንም ይህንን ጾም ወዲህ አምጥተው በየዓመቱ ይጾሙት ነበር፡፡ ዛሬም ድረስ ጾመ ሕርቃል እየተባለ ይጠራል፡፡ (ሙሉ ታሪኩ በፍትሐ ነገሥት ትርጓሜ አንቀጽ ፲፭ ላይ ይገኛል፡፡)

በዚህም መሠረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የዐቢይ ጾም ሳምንታትን ከፋፍላ፣ ስያሜ ሰይማ ልጆቿን ታስተምራለች፡፡ በየሣምንቱም በዕለተ ሰንበት ከሚቀርቡት ምንባባት መካከል ከመልእክታት፣ ከግብረ ሐዋርያት፣ ከመዝሙር፣ ከወንጌል ዕለቱን የተመለከቱትን ትሰብካለች፡፡

 ምንባባት
ከቅዱስ ጳውሎስ መልእክታት፡- (ዕብ.፲፫÷፯-፮)

የእግዚአብሔርን ቃል የነገሩአችሁን መምህሮቻችሁን ዐስቡ፤ መልካም ጠባያቸውን አይታችሁ በእምነት ምሰሉአቸው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትናና ዛሬ እስከ ዘለዓለምም የሚኖር እርሱ ነውና፡፡ ሌላ ልዩ ትምህርት አታምጡ፤ ልባችሁ በመብል ያይደለ በጸጋ ቢጸና ይበልጣልና፤ በዚያ ይሄዱ የነበሩ እነዚያ አልተጠቀሙምና፡፡ ድንኳኒቱን ሲያገለግሉ የነበሩ ካህናት ከእርሱ ሊበሉ የማይቻላቸው መሠዊያ አለን፤ ሊቀ ካህናቱ የሚሠዉትን እንስሳ ደም ስለ ኀጢአት ወደ ቅድስተ ቅዱሳን ያቀርብ ነበርና፤ ሥጋውንም ከሰፈር ውጭ ያቃጥሉት ነበር፡፡ ስለዚህም ኢየሱስ ሕዝቡን በደሙ ይቀድሳቸው ዘንድ ከከተማ ውጭ ተሰቀለ፡፡ አሁንም ተግዳሮቱን ተሸክመን÷ ወደ እርሱ ወደ ከተማው ውጭ እንውጣ፡፡ በዚህ የሚኖር ከተማ ያለን አይደለም የምትመጣውን እንሻለን እንጂ፡፡ በውኑ እንግዲህ በሰሙ አናምን ዘንድ የከንፈሮቻችን ፍሬ የሚሆን የምስጋና መሥዋዕትን በየጊዜው ለእግዚአብሔር ልናቀርብ አይገባንምን? ነገር ግን ለድሆች መራራትን÷ከእነርሱም ጋር መተባበርን አትርሱ፤ እንዲህ ያለው መሥዋዕት እግዚአብሔርን ደስ ያሰኘዋልና፡፡” (ዕብ. ፲፫÷፯-፮)

 (ያዕ. ÷፮-ፍጻ.)

“ነገር ግን ፈጣሪያችን የምትበልጠውን ጸጋ ይሰጣል፤ ስለዚህም “እግዚአብሔር ትዕቢተኞችን ይቃወማል፤ ለትሑታን ግን ጸጋን ይሰጣል” ይላል፡፡ እንግዲህ እግዚአብሔርን እሺ በሉት፤ ሰይጣንን ግን እንቢ በሉት፤ ከእናንተም ይሸሻል፡፡ እግዚአብሔርን ቅረቡት፤ ይቀርባችሁማል፤ እናንተ ኃጥኣን እጆቻችሁን አንጹ፤ ሁለት ዐሳብም ያላችሁ እናንተ ልባችሁን አጥሩ፡፡ እዘኑና አልቅሱ፤ ሳቃችሁን ወደ ልቅሶ÷ ደስታችሁንም ወደ ኀዘን መልሱ፡፡ በእግዚአብሔር ፊት ራሳችሁን ዝቅ አድርጉ፤ እርሱም ከፍ ከፍ ያደርጋችኋል፡፡”

 ግብረ ሐዋርያት፡- (ሐዋ.÷፲፫ፍጻ.)

“ከጥቂት ቀን በኋላም ንጉሥ አግሪጳና በር ኒቄ ወደ ቂሣርያ ወርደው ፊስጦስን ተገናኙት፡፡ተገናኙት፡፡በእርሱ ዘንድ ብዙ ቀን ከቈዩ በኋላ ፊስጦስ የጳውሎስን ነገር ለንጉሡ ነገረው፤ እንዲህም አለው÷ “ፊልክስ በእስር ቤት ትቶት የሄደ አንድ እስረኛ ሰው በእዚህ አለ፡፡ በኢየሩሳሌም ሳለሁም ሊቃነ ካህናትና የአይሁድ ሽማግሌዎች ወደ እኔ መጥተው እንድፈርድበት ማለዱኝ፡፡ አኔም፡- ተከሳሹ በከሳሾቹ ፊት ሳይቆም÷ ለተከሰሰበትም ምላሽ ይሰጥ ዘንድ ፋንታ ሳያገኝ ማንም ቢሆን አሳልፎ መስጠት የሮማውያን ሕግ አይደለም ብየ መለስሁላቸው፡፡ ከዚህም በኋላ፤ በዚሁ በተሰበሰቡ ጊዜ ሳልዘገይ በማለዳ በፍርድ ወንበር ተቀምጬ÷ ያን ሰው እንዲያመጡት አዘዝሁ፡፡ የከሰሱትም በቆሙ ጊዜ÷ እኔ እንደ አሰብሁት በከሰሱት ክስ የሠራው ምንም ነገር የለም፡፡ ስለ ሃይማኖታቸው ከሆነው ክርክርና ስለ ሞተው÷ ጳውሎስ ግን ሕያው ነው ስለሚለው ሰው ስለ ኢየሱስ ከሆነው ክርክር በቀር፤ ስለ ክርክራቸውም የማደርገውን አጥቼ ጳውሎስን ወደ ኢየሩሳሌም ሄደህ በዚያ ልትከራከር ትወዳለህን? አልሁት፡፡” አግሪጳም ፊስጦስን÷ “እኔም ያን ሰው ልሰማው እወደለሁ” አለው፤ ፊስጦስም÷ “እንግደያስ ነገ ትሰማዋለህ …” አለው፡፡

ምስባክ፡- (መዝ. ፪፥፲፩)
“ተቀነዩ ለእግዚአብሔር በፍርሃት ወተሐሠዩ ሎቱ በረዓድ።አጽንዕዋ ለጥበብ ከመ ኢይትመዐፅ እግዚአብሔር፤ ለእግዚአብሔር በፍርሃት ተገዙ፥ በረዓድም ደስ ይበላችሁ። ጥበብን አጽኑአት፤ እግዚአብሔር እንዳይቆጣ።”

ወንጌል፡- (ዮሐ.÷፳፬ )
ጌታችን ኢየሱስም መልሶ÷ “አንተ የእስራኤል መምህራቸው ነህ፤ ነገር ግን አንዴት ይህን አታውቅም?” አለው፡፡ እውነት እውነት እልሃለሁ፤ የምናውቀውን እንናገራለን፤ ያየነውንም እንመሰክራለን፤ ነገር ግን ምስክርነታችንን አትቀበሉንም፡፡ በምድር ያለውን ስነግራችሁ እንዴት ታምኑኛላችሁን? ከሰማይ ከወረደው የሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም፤ እርሱም በሰማይ የሚኖረው ነው፡፡ ሙሴ በምድረ በዳ እባቡን እንደ ሰቀለው የሰው ልጅ እንዲሁ ይሰቀል ዘንድ አለው፡፡ ያመነበት ሁሉ ለዘለዓለም ሕይወትን እንዲያገኝ አንጂ ቤዛ አድርጎ እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲህ ወዶታልና፡፡ ዓለም በእርሱ ይድን ዘንድ ነው እንጂ በዓለም አንዲፈርድ እግዚአአብሔር ልጁን ወደዚህ ዓለም አልላከውምና፡፡ በእርሱ ያመነ አይፈረድበትም፤ በእርሱ ያላመነ ግን ፈጽሞ ተፈርዶበታል፤ በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም አላመነምና፡፡ ፍርዱም ይህ ነው፤ ብርሃን ወደ ዓለም መጥቶአልና፤ ሰውም ሥራው ክፉ ስለሆነ ከብርሃን ይልቅ ጨለማን መርጦአልና፡፡ ሥራው ክፉ የሆነ ሁሉ ብርሃንን ይጠላልና፤ ክፉም ስለሆነ ሥራው እንዳይገለጥበት ወደብርሃን አይመጣም፡፡ አውነትን የሚሠራ ግን ሥራው ይገለጥ ዘንድ ወደ ብርሃን ይመጣል፤ ስለ እግዚአብሔር ብሎ ይሠራልና፡፡ ከዚህም በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ወደ ይሁዳ ምድር ሄደ፤ በዚያም እያጠመቀ አብሮአቸው ተቀመጠ፡፡ ዮሐንስም በዮርዳኖስ ማዶ በሳሌም አቅራቢያ በሄኖን ያጠምቅ ነበር፤ በዚያ ብዙ ውኃ ነበርና፤ ብዙ ሰዎችም ወደ እርሱ እየመጡ ያጠምቃቸው ነበር፡፡ ዮሐንስ ገና ወደ ወኅኒ ቤት አልገባም ነበርና፡፡”
ቅዳሴ
ዘእግዚእነ

ይቆየን፡፡

“ለግቢ ጉባኤ ትምህርቴ የመደበኛው ትምህርቴን ያህል ትኩረት ስሰጠው ነበር፡፡” (ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ አበበ)

ክፍል ሦስት                                           

በእንዳለ ደምስስ

ጉባኤ ቃና፡- በከፍተኛ ትምህርት ተቋም ቆይታዎ ግቢ ጉባኤ ውስጥ በመሳተፍዎ አጋጠሞኛል የሚሉት ችግር ከነበረ ቢገልጹልን?

ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ፡- እኔ በግቢ ጉባኤ ውስጥ በመሳተፌ ገጠመኝ የምለው ችግር የለም፡፡ እንዲያውም ራሴን እንደ ዕድለኛ ነበር የምቆጥረው፡፡ በግቢ ጉባኤ ውስጥ በመሳተፌ በርካታ ጥቅሞችን ነው ያገኘሁት፡፡ ከመምህራኖቼ፣ ከጓደኞቼ፣ እንዲሁም ከማኅበረሰቡ ጋር የነበረኝ ግንኙነት በጣም ጠንካራና ጤናማ ነበር፡፡ በጣም የሚገርምህ ኅብረተሰቡ ራሱ ተማሪውን ይንከባከባል፣ ያቀርብሃል፤ ስለዚህ እንደ ችግር የማነሳው ገጠመኝ የለኝም ማለት እችላለሁ፡፡ ለዚህም በቅርበት ራስን መግለጥና በቅንነት መጓዝ ያስፈልጋል፡፡ እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነታችን ስለሌሎች ሕይወት እንጨነቅ ነበርና ያለንን ለመስጠት ወደ ኋላ አለማለት ያስፈልጋል፡፡

መንፈሳዊ ሕይወታችን መደበኛ ትምህርታችንን በአግባቡ እንድንከታተል፣ ዓላማ እንዲኖረን፣ ጠንቃቃ እንድንሆን ስለሚያደርገን ተጠቃሚዎች ነን፡፡ ይህ አካሄድ ደግሞ ሌሎች ውጫዊ ነገሮች እንዳይረብሹንና መንፈሳዊ ሕይወታችንን ሊያጨናግፉ ከሚችሉ ነገሮች እንድንርቅ አድርጎናል፡፡

በአገልግሎት ላይ ግን አንዳንድ ይገጥሙን የነበሩ ችግሮች ነበሩ፡፡ እንደ ምሳሌ ባነሳ፡- አንዳንድ ተማሪዎች ወደ ቤተ ክርስቲያን መቅረብ ባለመቻላቸው እኛም አጥብቀን ባለመከታተላችን ሃይማኖታቸውን የቀየሩበት ሁኔታ ነበር፡፡ ያሳዝኑኛል፡፡ ከዚህ ውጪ አብረውን ይማሩ የነበሩ ወንድሞቻችን በተለያዩ የጤና እክሎች ምክንያት ያረፉ ልጆች ነበሩ፡፡ ይህ በጣም አሳዛኝ ነገር እንጂ እንደ ችግር የሚነሣ ጉዳይ አይደለም፡፡ ሌላው አንድ ወቅት ሕመም ገጥሞኝ ለሕክምና ወደ አዲስ አበባ መጥቼ ነበር፡፡ ነገር ግን ጠንክሬ እማር ስለነበር ከትምህርት ክፍሉ ከሁሉም ተማሪ የእኔ ውጤት ነበር ከፍተኛው፡፡ ስለዚህ እንደ ችግር ከምቆጥራቸው ይልቅ እንደ መልካም ነገር የምቆጥራቸው ነገሮች ይበዙብኛል፡፡

ጉባኤ ቃና፡- በርካታ ተመራቂዎች ሲመረቁ የሰጡትን ሜዳልያ ምክንያት አድርገው እርስዎን እንደ አርአያ ይቆጥራሉ፡፡ እነርሱም ከፍተኛ ውጤት አመጣለሁ፣ ሜዳልያዬንም እንደ ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ ለማኅበረ ቅዱሳን እሰጣለሁ ብለው ይጀምራሉ፣ ሲፈጽሙም ቃላቸውን ጠብቀው ሲሰጡ እንመለከታለን፡፡ ለመሆኑ ያኔ እንዴት ሊያስቡትና ሜዳልያዎን ሊሰጡ ቻሉ? ምክንያትዎ ምን ነበር?

ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ፡-  ገና ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም ስንገባ ከአቀባበል ጀምሮ የተደረገልን እንክብካቤ፣ ምክራቸው፣ በተለይም ጠንካራ ተማሪዎች እንድንሆን፣ ጊዜያችንን በአግባቡ እንድንጠቀም፣ ጎበዝ ተማሪ እንድንሆን፣ ይህንን ማድረጋችን ለራሳችንም ሆነ ለቤተ ክርስቲያን እንደሚጠቅም፣ በአገልግሎትም እንድንሳተፍ ይመክሩን ነበር፡፡ እኛም ይህንን እንደ መመሪያ ወስደን የምናወጣውን የጊዜ አጠቃቀም ተግባራዊ እያደረግን ውጤታማ ሆነን ለመውጣት ረድቶናል፡፡

የመጀመሪያ ዓመት የመጀመሪያ ሴሚስተር ላይ ፈተና እንደጨረስን በዕለቱ ነበር ከጓደኞቼ ጋር አዲስ አበባ የመጣሁት፡፡ ስለ ውጤት የምጨነቅበት ጊዜ አልነበረም ቤተሰብ ይናፍቅሃል፣ ዕረፍት ትፈልጋለህ፡፡ የዕረፍት ጊዜያችንን ጨርሰን ስንመለስ ቀጥታ ያመራነው ሐመረ ኖኅ ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ነበር፡፡ አንድ በግቢ ጉባኤ ውስጥ ያገለግል የነበረ ወንድማችን የእኔን ውጤት ቀደም ብሎ ሰምቶ ስለነበር በደስታ ነው የተቀበለኝ፡፡ “እንኳን ደስ ያለህ! ከሁሉም ተማሪ የአንተ ውጤት ከፍተኛ ነው፡፡ ጎበዝ! በርታ! እንዲህ ዓይነት ተማሪ ነው የምንፈልገው” ብሎ አበረታታኝ፡፡

ከእኔ ይልቅ እርሱ የነበረው የደስታ ስሜት እስከ ዛሬ አይረሳኝም፡፡ ወዲያውኑ ነው “እኔ ለወንድሞቼ ብዬ የተለየ የሠራሁት ነገር የለም፡፡ በእርግጥ ጠንክሬ ተምሬያለሁ፡፡ የእኔ ውጤት ወንድሞቼን እንዲህ የሚያስደስታቸው ከሆነ በዚሁ ጥረቴ እቀጥላለሁ፤ ስጨርስም ሜዳልያዬን ለእነርሱ ነው የምሰጠው” ብዬ ቃል ገባሁ፡፡ እግዚአብሔርም ረድቶኝ የትምህርት ክፍሌንና የዩኒቨርሲቲው አጠቃላይ አሸናፊ ሆኜ ጨረስኩ፡፡ በገባሁት ቃል መሠረትም በ፲፱፻፺፬ ዓ.ም ማኅበረ ቅዱሳን ጠቅላላ ጉባኤውን ሲያካሂድ በጉባኤው ላይ ተገኝቼ ሜዳልያዬን ሰጠሁ፡፡

ጉባኤ ቃና፡-  እርስዎ የሰጡት ሜዳልያ ለበርካታ ተማሪዎች ውጤታማነት መነሳሳትን ፈጥሯል ማለት ይቻላል፡፡ ሜዳልያቸውንም እያመጡ ለማኅበረ ቅዱሳን በየዓመቱ ያበረክታሉና ይህንን ሲመለከቱ ምን ይሰማዎታል?

ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ፡- እኔ ለማኅበረ ቅዱሳን ሜዳልያውን የሰጠሁት ሌሎችን ለማነሳሳት ብዬ አልነበረም፡፡ ለወንድሞቼ ደስታ ስል ነበር ይህንን ያደረግሁት፡፡ ነገር ግን በሂደት ለሌሎች መነሳሳትና ውጤታማነት አስተዋጽኦ አድርጎ ከሆነ መልካም ነው፡፡ እኔም በዚህ ደስተኛ ነኝ፡፡

ጉባኤ ቃና፡- በርካታ ተማሪዎች የአብነት ትምህርት ተምረው የዲቁና ማዕረግን ተቀብለው ይወጣሉ፡፡ እርስዎ ይህ ዕድል ገጥሞዎት ነበር? 

ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ፡-  አዎ፡፡ ግቢ ጉባኤ ከገባሁ በኋላ ነው የአብነት ትምህርት የተማርኩትና ዲቁና እስከመቀበል የደረስኩት፡፡ በጣም ጠንካራ ጉባኤ ቤት ነበር፡፡ መምህራችንም በጣም ትጉህ ነበሩ፡፡ ወንበር ዘርግተው ከማስተማር በተጨማሪ ተማሪዎቻቸውን ሁሉ ቤተ ክርስቲያን ድረስ ይዘው ገብተው ማኅሌት ያስቆሙናል፣ ከአገልግሎት ጋር እንድንተዋወቅ፣ በሄድንበት ሁሉ ቤተ ክርስቲያንን ከማገልገል ወደ ኋላ እንዳንል ይመክሩናል፡፡ ወርኀዊ በዓላት ይሁን ዓመታዊ በዓላት ከኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን አልፈን አጎራባች አጥቢያዎች ድረስ ይዘውን እየሄዱ ማኅሌት እንድንቆም ያደርጉናል፣ በብዛት መኅሌት ላይ የምገኘው የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች   ነበርን፡፡ በተለይም የሐመረ ኖኅ ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ማኅሌት ከተማው ውስጥ ካሉት ሁሉ ደማቁ ነበር፡፡

ጉባኤ ቃና፡- ቤተሰብ ልጆቻቸውን ወደ ከፍተኛ ትምህርት ሲልኩ ግቢ ጉባኤ ውስጥ እንዲሳተፉ የሚያበረታቱ እንዳሉ ሁሉ ጊዜያችሁን ይሻማባችኋል፤ ወደ ግቢ ጉባኤ እንዳትገቡ እያሉም የሚያስጠነቅቁ ወላጆች አሉና ከተሞክሮዎ ተነስተው ለወላጆች ምን ይመክራሉ?

ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ፡– ግቢ ጉባኤ እንዳይገቡ የሚያደርጉ ወላጆች ግቢ ጉባኤን ካለመረዳት የመነጨ ነው፡፡ ከቤተሰቦቻቸውም ጋር አብረው እየኖሩ ሰንበት ትምህርት ቤት አትሂድ የሚል ወላጅም ያጋጥምሃል፡፡ ግንዛቤ ከማጣት ነው ያልተገባ ፍርድ የሚሰጡት፡፡ ኦርቶዶክሳዊ ሆኖ ልጆቹን ቤተ ክርስቲያን አትሂድ የሚል ወላጅ ስለ እምነቱ ያለውን ግንዛቤ በትክክል ተረድቷል የሚል ግምት የለኝም፡፡ ነገር ግን ወላጆች አንዳንድ ከሚያይዋቸውና ከሚሰሟቸው አሉታዊ መረጃዎች የተነሳ ሰንበት ትምህርት ቤትን ወይም ግቢ ጉባኤያትን የሚስሉበት መንገድ ትክክል ካለመሆን የመነጨ ነው፡፡

በትክክል ግቢ ጉባኤን ወይም ሰንበት ትምህርት ቤትን የሚያውቅ ወላጅ ግን እንዲህ አይልም፡፡ እንዲያውም ዘመኑ ከሚያመጣቸው አንዳንድ ያልተገቡ ድርጊቶችና መረጃዎች የተነሳ ልጆቻቸው እንዳይበላሹባቸው ስለሚሰጉ ወደ ግቢ ጉባኤና ሰንበት ትምህርት ቤት የሚልኩ በርካታ ናቸው፡፡ ወላጆች ልጆቻቸውን ማድመጥ፣ መንገድ መምራት፣ ትክክለኛውን መስመር ይዘው እንዲያድጉ የማድረግ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ ለልጆቻቸው የሚበጃቸውን የማሳየት፣ ከልጆች በተሻለ ስለ ጉዳዩ ከፍ ያለ ግንዛቤው ያላቸው እንዲሆኑ ይጠበቅባቸዋል፡፡

ወደ ሰንበት ትምህርት ቤት የሚሄዱ ልጆች በአብዛኞቹ በተመሳሳይ የዕድሜ ክልልና ተመሳሳይ አስተሳሰብ ያላቸው ናቸው፡፡ ነገር ግን አካባቢያቸውም ሆነ ወላጆቻቸው በተበታተነ ሁኔታ ውስጥ ስለሚገኙ እኩል ግንዛቤ መፍጠር አይቻልም፡፡ ይህንን ችግር ለመፍታት ግን ወላጆችን አሰባስቦ ማስተማር የሚቻልበት ጉባኤ ሊፈጠር ያስፈልጋል፡፡ ይህ ጉባኤ ቤተ ክርስቲያን ቢኖራት ኖሮ አሁን የምናያቸው ችግሮች አይፈጠሩም ነበር፡፡ የሀገር መሠረቱ ወላጆቻችን ናቸው፡፡ ለምሳሌ የእኔ እናት ዘመናዊ ትምህርት የተማረች አይደለችም፣ ነገር ግን ሀገሯን የምትወድ፣ ዘወትር ቤተ ክርስቲያን የምትሳለም፣ እኛንም ወደ ቤተ ክርስቲያን እንድንሄድ ግፊት የምታደርግ እናት ናት፡፡ በእርሷ አቅም ልትነግረን፣ ልታሳየን የፈለገችውን ነገር ነፍጋ አላሳደገችንም፡፡ ቤተ ክርስቲያን እንድንሄድ፣ ጥሩ ዜጎች እንድንሆን የከፈለችው ዋጋ አለና በእኛ እርሷም ደስተኛ ናት፡፡

ትምህርት ቤት ገብቶ የወጣውና ፊደል የቆጠረው፣ ዲግሪ፣ ዶክትሬት አለኝ የሚለው ወላጅ ግን ለልጁ ምንድነው የሚመኝለት? ምን እንዲሆንልት ነው የሚፈልገው? ለዚያ የሚመጥን ሥራ ከወላጆች ይጠበቃል ማለት ነው፡፡ ግቢ ጉባኤ አትሂዱ ሳይሆን ሂዱ ግን ስትሄዱ ይህንን አድርጉ፣ ይህንን ደግሞ አታድርጉ ብሎ ለይቶ ሊመክር፣ ሊከታተል ይገባዋል ወላጅ፡፡ ግቢ ጉባኤ እንዳይሄዱ ቢፈልጉ እንኳን ቤተ ክርስቲያን ሂዱ ብለው ልጆቻቸው ከእግዚአብሔር ጋር ያላቸውን ግንኙነት እንዲያጠናክሩ መርዳት አለባቸው፡፡ ወላጆች በማያውቁት ነገር ላይ የማይገባ ሐሳብ ባይሰጡም መልካም ነው፡፡ አሁን ደግሞ ጊዜው እየከፋ ነው የመጣው፡፡ ሁሉም የማኅበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚ ሆኗል፣ ሁሉም አስተያየት ሰጪ ነው፡፡ ይህ ተገቢ አይደለም፡፡ ያላለፉበትን መንገድ ልምድ ካላቸው ሰዎች ቢጠይቁ፣ ከልጆቻቸው ጋር ቢመካከሩ መልካም ነው፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ብዙ የአገልግሎት መስኮች ላይ ስለተሰማራ እዚህ ላይ እንደሚቸገር ይገባኛል፡፡ እኔም የአገልግሎቱ አካል ስለሆንኩ በቅርብ የምረዳው ነው፡፡ ወላጆች ላይ መሥራት ሀገርና ቤተ ክርስቲያን ላይ መሥራት ማለት ነው፡፡ በተለይ አሁን በእኛ ዕድሜ ላይ ያሉ ወላጆች ላይ ቢሠራ ልጆቻቸውን እንዴት መያዝ እንደሚችሉ ማስተማር ልጆቻችን ኮሌጅ ሲገቡ አይቸገሩም፡፡ ከመጀመሪያው ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተኮትኩተው የማደግ ዕድሉን ስለሚያገኙ ኮሌጅ ሲገቡ ሁሉንም ዐውቀውና ተረድተው ይገባሉ፡፡ በዚህ መልኩ ከሄድን ለውጥ ሊመጣ ችላል ብዬ አስባለሁ፡፡

ጉባኤ ቃና፡- የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ተመርቀው ከወጡ በኋላ ብዙዎቹ ከአገልግሎት ይርቃሉ፡፡ ሕይወት ከምረቃ በኋላ እንዴት መሆን አለበት ይላሉ?

ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ፡- ይህንን በሁለት መንገድ ልንመለከተው እንችላለን፡፡ ግቢ ጉባኤ ውስጥ ያስተማርናቸው ሁሉ አገልጋይ እንዲሆኑ መመኘት መልካም ቢሆንም በቅድሚያ ጥሩ ምእመን ሆኖ መገኘት አለበት፡፡ ስለዚህ ሁሉም አገልጋይ መሆን አይችልም፡፡ ጥሩ ምእመን መሆን ከቻለ ልጆቹን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዲያድጉ የሚያደርግ ከሆነ አላገለገለም ልንለው አንችልም፡፡ ጥሩ ምእመን ጥሩ አገልጋይ ነው፡፡ የሰበካ ጉባኤ፣ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ እኛም ባሉበት አጥቢያ ተሳትፎ እንዲያደርጉ ነው የምንመክራቸው፡፡ ስለዚህ አስተምሯልና ግዴታ ማኅበረ ቅዱሳን ውስጥ መግባት አለባቸው ልንል አንችልም፡፡ ካገኘነው የጣነውን መቁጠር ልማድ ስለሆነብን እንጂ ማኅበረ ቅዱሳን በግቢ ጉባኤ ውስጥ ያስተማራቸው ሁሉ ጠፍተዋል ማለት አይደለም፡፡ ጥሩ ጥሩ ምእመናንን ማፍራታችንም ማሰብ አለብን፡፡ ሌላው ከምረቃ በኋላ የቤተሰብ ኃላፊ መሆን፣ ቤተሰብ የማስተዳደርና የተለያዩ ሥራዎችን መሥራት፣ ልጆችን መንከባከብ፣ ማኅበራዊ ኃላፊነት ሁሉ ስለሚሻሙት ሁሉም በአባልነት ያገልግል ማለት አይቻልም፡፡

ጉባኤ ቃና፡-  ማኅበረ ቅዱሳን በግቢ ጉባኤያት ላይ የሚሰጠውን አገልግሎት ከማጠናከር አንጻር ሊያከናውናቸው ወይም ሊያሻሽላቸው ይገባል የሚሏቸው ጉዳዮችን ቢገልጹልን?

ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ፡- ማኅበረ ቅዱሳን በርካታ የአገልግሎት ዘርፎች ውስጥ ውጤታማ አገልግሎት እያከናወነ እንዳለ ሁላችንም የምንረዳው ጉዳይ ነው፡፡ ነገር ግን የነገዋን ኢትዮጵያንና ቤተ ክርስቲያንን የሚጠቅምና የሚታደግ ትውልድ ለመፍጠር ወላጆች ላይ መሥራት አለበት እላለሁ፡፡ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎቻችን በዕረፍት ጊዜያቸው ከመላው ቤተሰቦቻቸው ጋር እንዲመካከሩ ማድረግ ያለውን ክፍተት እንዲሞላ ያደርገዋል፡፡

አሁን ባለንበት ነባራዊ ሁኔታ የግቢ ጉባኤ አገልግሎት ማስተባበሪያ ውስጥ ብዙ ሥራዎች እየተሠሩ ስለሆነ አጠናክሮ መቀጠል፣ መጻሕፍትን በአግባቡ ለተማሪዎች ተደራሽ ማድረግ፣ ቴክኖሎጂን ተጠቅመን የገጽ ለገጽ ትምህርቶችን ማሠራጨት፣ የተለያዩ መተግበሪያዎችን   ማበልጸግ፣ በሞባይል ስልኮቻቸው ተከታታይ ትምህርቶችን በድምጽ ወይም በጽሑፍ የሚያገኙበት ሁኔታ መፍጠር፣ የግቢ ጉባኤያት ኅብረትን ማጠናከር ያስፈልጋል፡፡ በተጨማሪም ከግቢ ጉባኤ ከወጡ በኋላ በሥነ ምግባር የታነጹና በተመረቁበት ሙያ በብቃት አገልግሎት የሚሰጡ፣ ሁል ጊዜ ራሳቸውን ለማሻሻል የሚተጉ እንዲሆኑ መንገዱን ማመላከት ያስፈልጋል፡፡ ለደረስንበት ደረጃ እግዚአብሔርን ማመስገን፣ ላልደረስንበት ደግሞ በሥራ ላይ የታገዘ ትጋት ሊኖር ይገባል፡፡

አሁን ተመርቀው የሚወጡ ልጆች የሚቀጥለውን የሕይወት ምዕራፍ አንድ ብለው የሚጀምሩበት ነው፡፡ በተሠማሩበት የሥራ መስክ ጠንካራና የሚመሰገኑ ባለሙያዎች እንዲሆኑ እመክራለሁ፡፡   እንደ እከሌ ተብለው እንደ ምሳሌ ሊጠቀሱ የሚችሉ መሆን አለባቸው፡፡ በምንም ነገር ውስጥ ጠንክረው ሳይሠሩ በአቋራጭ የሚገኝ ነገር የለምና እዚህ ላይ ትኩረት ሰጥተው ሊሠሩበት ይገባል፡፡

ጉባኤ ቃና፡- ለነበረን ቆይታ በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን፡፡

ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ፡- እኔም አመሰግናለሁ፡፡

“ለግቢ ጉባኤ ትምህርቴ የመደበኛው ትምህርቴን ያህል ትኩረት ስሰጠው ነበር፡፡” (ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ አበበ)

ክፍል አንድ                                             

በእንዳለ ደምስስ

ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ አበበ በ፲፱፻፹፯ ዓ.ም ከኮልፌ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የ፲፪ኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተናን ፬ ነጥብ በማምጣት በ፲፱፻፹፰-፲፱፻፺፬ ዓ.ም በጅማ ዩኒቨርስቲ የሕክምና ትምህርታቸውን ተከታትለዋል፡፡ በሰባት ዓመታት የሕክምና ትምህርት ቆይታቸው ከትምህርት ክፍሉ እና ከአጠቃላይ የዩኒቨርሲቲው ተመራቂዎች በከፍተኛ ማዕረግ የሜዳልያ ተሸላሚ በመሆን የሕክምና ትምህርታቸውን አጠናቀዋል፡፡ ባስመዘገቡት ውጤት መሠረትም በዩኒቨርሲቲው ለሁለት ዓመታት በመምህርነት ተመድበው አገልግለዋል፡፡

ለሰባት ዓመታት በዩኒቨርሲቲው ትምህርታቸውን ሲከታተሉ በየዓመቱ ዩኒቨርሰቲው የሚያዘጋጃቸውን ሽልማቶች በተደጋጋሚ ለመቀበል ችለዋል፡፡ እንዲሁም በዩኒቨርሲቲው በቆዩባቸው ጊዜያት በግቢ ጉባኤ ውስጥ በንቃት ከሚሳተፉ ወንድሞችና እኅቶች መካከል ነበሩ፡፡

ፕ/ር እንግዳ በሙያቸው በተለያዩ ሆስፒታሎች ውስጥ ያገለገሉና በቅዱስ ጳውሎስ ሚሊኒየም ሆስፒታል ውስጥ በሚገኘው የሕክምና ኮሌጅ ውስጥ በኃላፊነትና በመምህርነት እያገለገሉ ይገኛሉ፡፡ በሙያቸው ባበረከቱት አስተዋጽኦም ከተለያዩ ተቋማት ሽልማቶችን ለማግኘት የቻሉ ባለሙያ ናቸው፡፡

በዚህም መሠረት የካቲት ፲ ቀን ፳፻፲፬ ዓ.ም የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሕክምና ኮሌጅ የማኔጅመንት ቦርድ የዶ/ር እንግዳ አበበን መረጃዎች ከገመገመ በኋላ የሙሉ ፕሮፌሰርነት ማዕረግ ለመጀመሪያ ጊዜ ሰጥቷል፡፡ ፕሮፌሰር እንግዳ አበበ ገላን የሕክምና ዲግሪያቸውን (MD) ከጅማ ዩኒቨርሲቲ ፣ የቀዶ ሕክምና ስፔሻሊቲ ዲግሪያቸውን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በቀዶ ሕክምና እንዲሁም የሰብ-ስፔሻሊቲ ዲግሪያቸውን በኩላሊት ንቅለ ተከላ ከቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም የሕክምና ኮሌጅ ያገኙ ሲሆን፤ የተለያዩ አጫጭር የሞያ ሥልጠናዎችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር መከታተላቸውን የሕክምና ኮሌጁ አስታውቋል፡፡

ፕሮፌሰር እንግዳ አበበ ገላን በግላቸውና ከሙያ አጋሮቻቸው ጋር ከ፵ በላይ በምርምር የተደገፉ ጥናታዊ ፅሁፎችን በታወቁ አገራዊና ዓለም አቀፋዊ መጽሔቶች ላይ ለኅትመት አብቅተዋል፡፡ በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሕክምና ኮሌጅ በሚገኘው የሕክምና ትምህርት ቤት ውስጥ የቀዶ ሕክምና ትምህርት ክፍል ኃላፊ ሆነው በማገልገል ላይ ይገኛሉ።

ወደ ቃለ ምልልሳችን ከመግባታችን በፊት አብረዋቸው የሚሠሩ ባለሙያዎች ስለ ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ አበበ የሰጡትን የምስክርነት ቃል በጥቂቱ እነሆ፡-

“እጅግ በጣም ታታሪ እና ትሁት ስለሆነው ፕ/ር እንግዳ አበበ ሳወራ በኩራት ነው፡፡ ወደ ቀዶ ጥገና ክፍል የሚሄድ ሁሉ ያውቀዋል፡፡ ጠዋት ታካሚዎችን ስንጎበኝ ለአንድ ቀን የተኛ ታካሚ እንኳን በእርሱ መታየት ይፈልጋል፡፡ በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል የሚማሩ ተማሪዎች ሁሉ እንደ እርሱ መሆን ይፈልጋሉ፡፡ በሆስፒታል ውስጥ በሚሠሩ ሰዎች ሁሉ የተከበረ ነው፡፡ የቀዶ ጥገና ፕሮፌሰርና የኩላሊት ንቅለ ተከላ ሐኪም የሆነው ፕ/ር እንግዳ አበበ ለእኛ ልዩ አርአያችን ነው፡፡” (ዶ/ር ፍራኦል)

“በእርሱ መማር መቻሌ ታላቅ ዕድል ነው፡፡ ሰው አክባሪ፣ ትሁት፣ እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው ነው፡፡”(ምሕረት ተዘራ)

“የተባረኩ እጆች፣ የሚደንቅ ዕውቀት ያለው ሰው ነው፡፡ ከእርሱ ጋር ቀዶ ጥገና ከገባህ የሚያሳስብህ አይኖርም፡፡”(ቶሌ ካን ያደቴ)

“በሀገራችን ካሉ ምርጥ የቀዶ ጥገና ሐኪሞች አንዱ ነው፡፡ ትህትናው፣ ዕውቀቱ እና ታማኝነቱ ሁሉም ተስማምተው ስለ እርሱ መልካምነት እንዲያወሩ አድርጎታል፡፡”(አዲስ ዓለም ገንታ)

“ፕ/ር እንግዳ እጅግ የምትደነቅ ትሁት እና ሥራ ወዳድ ሰው ነህ፡፡ አብሬህ በመሥራቴ ዕድለኛ እንደሆንኩ ይሰማኛል፡፡” (ቤላ ሮማን)

“እርሱ በጣም የሚደንቅና ታላቅ ሰብእና ያለው ሰርጀን ነው፤ በጣም ትሁት፣ ታታሪና ጠንካራ ሠራተኛ እንዲሁም ለታካሚዎች አክብሮት የሚሰጥ ሰው ነው፡፡ እርሱን በቃላት መግለጽ አይቻልም፡፡ በእርሱ በመማሬ በጣም ደስተኛ ነኝ፡፡” (አያንቱ ተስፋዬ)

ከላይ የቀረበው ምሥክርነት “Hakim 2011 Nominee” በተሰኝ ድረ ገጽ ላይ ያገኘነው መረጃ ሲሆን ከዲ/ን ፕ/ር እንግዳ አበበ ጋር በሕክምናው ዘርፍ የሠሩ እና የተማሩ ባለሙያዎች ናቸው፡፡ ለመሆኑ ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ አበበ ማን ናቸው? በየጊዜው የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን ታሳቢ በማድረግ በምናሳትማቸው የጉባኤ ቃና መጽሔት እትሞቻችን በግቢ ጉባኤያት ውስጥ ያለፉና የሕይወት ተሞክሯቸው ሌሎችን ያስተምራል ያልናቸውን ወንድሞችና እኅቶችን በቃና እንግዳ ዓምዳችን እናቀርባለን፡ እኛም በዚህ ዝግጅታችንም የግቢ ጉባኤ ቆይታቸውን መሠረት አድርገን ከሕይወት ተሞክሯቸው ያካፍሉን ዘንድ ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ አበበን እንግዳችን አድርገናቸዋል፡፡ መልካም ቆይታ ይሁንላችሁ፡፡

ጉባኤ ቃና፡- ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም ከመግባትዎ በፊት ለቤተ ክርስቲያን የነበረዎትን ቅርበት ቢገልጹልን?

ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ፡- ተወልጄ ያደግሁት አዲስ አበባ ነው፡፡ ልጅ ሆኜ እንደማንኛውም ሕፃን እናቴ ወደ ቤተ ክርስቲያን ትወስደኝና ታስቆርበኝ ነበር፡፡ በዕድሜ ከፍ ስል ከሌላ ጊዜ በተለየ ሁኔታ የፍልሰታ ለማርያም ጾምን በጉጉት እጠብቀው ስለነበር ከሰፈር ጓደኞቼ ጋር ወደ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ እቆርብ ነበር፡፡ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን ስከታተልም ቅዱስ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን የረቡዕ ሠርክ እና እሑድ ከቅዳሴ በኋላ ልዩ ጉባኤ በየዐሥራ አምስት ቀኑ ይካሄድ ስለነበር ያለማቋረጥ እሳተፍ ነበር፡፡ በሠርክ ጉባኤም እየተገኘሁ በመማር ስለ እምነቴና ስለ ቤተ ክርስቲያን ለማወቅ ጥረት ከማድረግ ወደ ኋላ አላልኩም፡፡ በተለይም በወቅቱ ያስተምሩን የነበሩት መምህራን በዘመኑ ላለነው ወጣቶችና ኦርቶዶክሳውያን አርአያ ነበሩ ማለት ይቻላል፡፡ ስለዚህ ከልጅነቴ ጀምሮ ቤተ ክርስቲያንን ለማወቅና ስለ እምነቴ ለመረዳት የቻልኩትን አድርጌያለሁ ማለት እችላለሁ፡፡ ይህም በወጣትነት ዘመኔ ራሴን እንድገዛና በፈሪሃ እግዚአብሔር እንድታነጽ አድርጎኛል፡፡

ጉባኤ ቃና፡- የከፍተኛ ትምህርትን ለመከታተል ከቤተሰብ ርቆ መሄድ እንዴት ይገልጹታል?

ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ፡- ከቤተሰብ መራቅ በራሱ አስፈሪ ያደርገዋል፡፡ ለአንዲት ቀን ከቤተሰብ ተለይቶ የማያውቅ ተማሪ በአንድ ጊዜ ወደተመደበበት ለመሄድ ሲታሰብ ከራስ አልፎ ቤተሰብ ውስጥ የሚፈጥረው ስጋት ቀላል አይደለም፡፡ በቤተሰብ በኩል ምክሮችና መመሪያዎች ይበዙብሃል፤ “እንዲህ አድርግ፣ እንዲህ ደግሞ አታደርግ” ትባላለህ፡፡ በዚህ ላይ ወጣትነት በራሱ አዲስ ነገር ለማየትና ለመሞከር ፍጥነት የሚታይበት ጊዜ ነው፡፡ ለተወሰኑ ቀናት አካባቢውን ለማጥናትና ለመልመድ ሲባል ቁጥብነት በተማሪው ዘንድ ይታያል፡፡

እኔ የተመደብኩት ጅማ ዩኒቨርሲቲ ነበር፡፡ እንደማንኛውም ተማሪ ፍርሃት ይኖራል፡፡ ነገር ግን ብዙ አልተቸገርኩም፡፡ ከእኛ ቀድመው ወደ ዩኒቨርሲቲው የገቡና የግቢ ጉባኤ ተሳታፊ የነበሩ ወንድሞችና እኅቶች አውቶቡስ ተራ ሄደው ነው የተቀበሉን፡፡ ቦርሳችንን ተሸክመው እየተንከባከቡ እግራችንን በሽሚያ አጥበው፣ አስመዘግበውን፣ ማደሪያ ክፍላችን ድረስ ወስደው ነው ያስገቡን፡፡ በዚህ እንክብካቤ ውስጥ ፍርሃት ይጠፋል፡፡ በጣም ደስ የሚል አቀባበል ነበር፡፡ አንዳንዶች ቶሎ ለመልመድ ቢቸገሩም በአብዛኛው ግን ቶሎ ይለምዳል፡፡ ስለዚህ እኔ አልተቸገርኩም ማለት እችላለሁ፡፡

ጉባኤ ቃና፡- ግቢ ጉባኤ ውስጥ መሳተፍ እንዴት ጀመሩ?

ዲ/ን ፕ/ር እንግዳ፡- ቀድሞ መርካቶ ቅዱስ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን ሠርክ ላይ ይሰጥ የነበረው የወንጌል ትምህርትና አገልግሎት በጣም ረድቶኛል፡፡ በተለይ በወቅቱ ያገለግሉ የነበሩ መምህራን እግር ሥር ቁጭ ብለን እንማር ስለነበር እኔም አንድ ቀን ወደ አገልግሎት እንደምገባና እንደ እነርሱ ባይሆንም የአቅሜን አበረክታለሁ የሚል ሕልም ነበረኝ፡፡ በወቅቱ በሚያገለግሉ ወንድሞቻችን ላይ በጣም መንፈሳዊ ቅናት እቀና ነበር፡፡ ጅማ ዩኒቨርሲቲ ስገባ የነበረው ግቢ ጉባኤ በጣም ጠንካራና የተደራጀ ነበር፡፡ አስተባባሪዎቹም የሚመጣውን ተማሪ የሚንከባከቡበት መንገድ አስደሳች ስለነበር ገብተን መንፈሳዊውን ማዕድ ለመካፈል አልተቸገርንም፡፡ ቤተ ክርስቲያን መሄድ የምትፈልጉ ኑ እናሳያችሁ እያሉም ይወስዱን ስለነበር እኔም ከፍተኛ ፍላጎት ስለነበረኝ ለመግባት ችያለሁ፡፡  እኛን ለማቅረብና ግቢ ጉባኤ ውስጥ እንድንማር የሚያደርጉት ጥረት፣ በዚያውም እንደ አቅማችን በአገልግሎት እንድንሳተፍ ያበረታቱን ነበር:: የመጀመሪያ ዓመት ላይ በግቢ ጉባኤው አማካይነት ይሰጥ የነበረውን መንፈሳዊ ትምህርት በመማር ነው ያሳለፍኩት፡፡ መምህራኖቻችንም ቤተ ክርስቲያንን እንድንወድ፣ የጸሎት ሕይወት እንዲኖረን፣ ጊዜያችንን አጣጥመን ውጤታማ ሆነን እንድንወጣ ዘወትር ይመክሩን ነበር፡፡

ይቆየን

“ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ፣ ሞታ ለማርያም የዐጽብ ለኵሉ” (ድጓ ዘአስተርእዮ ማርያም)

በእንዳለ ደምስስ

አስተርእዮ ቃሉ አስተርአየ፤ ታየ፣ ተገለጠ ከሚለው የግዕዝ ግሥ የተገኘ ቃል ሲሆን መታየት፣ መገለጥ ማለት ነው። ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ፣ ከነፍሷ ነፍስን ነሥቶ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በማሕፀኗ አድሮ የተወለደበት (በሥጋ የተገለጠበት)፣ አንድነት፣ ሦስትነቱም የተገለጠበት ወቅት በመሆኑ ከልደት በዓል እስከ ጥር መጨረሻ ዘመነ አስተርእዮ በመባል ይታወቃል። የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በዓለ ዕረፍትም በዘመነ አስተርእዮ ውስጥ ስለሚውልና ስለሚከበር “አስተርእዮ ማርያም” ተብሏል።

ታላቁ የቤተ ክርስቲያናችን አባት ቅዱስ ያሬድም በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሞት እጅግ ተደንቆ “ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ፣ ሞታ ለማርያም የዐጽብ ለኲሉ፤ ሞት ለማንኛውም ሰው ሁሉ የተገባና የማይቀር ነው፣ የማርያም ሞት ግን ሁሉን ያስደንቃል” በማለት ገልጾታል።(ድጓ ዘአስተርእዮ ማርያም)፡፡

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሞትና ትንሣኤ እንዴት ነው ቢሉ፤ ቅዱሳን አባቶቻችን ነገረ ማርያም በተሰኘው የምስጋና መጽሐፍ በስፋት ይተርኩታል፡-

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በስልሣ አራት ዓመቷ ከዚህ ዓለም ዐርፋለች፡፡ እንደምን ነው ቢሉ ሦስት ዓመት ከወላጆቿ ከሐና እና ከኢያቄም፣ ዐሥራ ሁለት ዓመት በቤተ መቅደስ ሐርና ወርቅ አስማምታ ስትፈትል ኑራለች፡፡ በዐሥራ አምስት ዓመቷ ከቤተ መቅደስ ወጥታም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በግብረ መንፈስ ቅዱስ ፀንሳ፣ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በማኅፀኗ አድሮ ተወልዷል፡፡ ሠላሳ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ከልጇ ከወዳጇ ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ከሀገር ሀገር፣ ረሃቡንና ጥሙን ታግሳ እስከ ዕለተ ስቅለቱ አብራው ኑራለች፡፡ በስቅለቱ ጊዜም እጅግ ይወደው ከነበረው ከወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ጋር በመስቀሉ ሥር ተገኝታለችና እናቱን ለቅዱስ ዮሐንስ አደራ ሰጥቷታል፡፡ ለቅዱስ ዮሐንስ ብቻ ሳይሆን በእርሱ በኩል ለክርስቲያኖች ሁሉ ተሰጥታናለች፡፡ በቅዱስ ዮሐንስ ቤትም ዐሥራ አምስት ዓመታትን ኖራለች፡፡ እነዚህን ስንደምር ለስልሣ አራት ዓመታት በዚህ ምድር ላይ እንደኖረች እንረዳለን፡፡

ስልሣ አራት ዓመት በዚህ ዓለም ኖራም ጥር ፳፩ ቀን በዕለተ እሑድ ጌታ እልፍ አዕላፋት መላእክቱን አስከትሎ መጥቶ “እናቴ ሆይ ከዚህ ዓለም ድካም ላሳርፍሽ መጣሁ” አላት።  እርሷም “ልጄ ሰማይና ምድር የማይወስኑህ፣ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በማኅፀኔ ተሸክሜ፣ በድንግልና ወልጄህ እሞታለሁን?” አለችው። ወደ ሲኦል ወስዶም በሲኦል የሚሠቃዩ ነፍሳትን አሳይቶ “እናቴ ሆይ ሞትሽ ለእነዚህ ሁሉ ነፍሳት ቤዛ ይሆንላቸዋል” አላት። እርሷም በሲኦል ያሉትን ነፍሳት ሥቃይ ከተመለከተች በኋላ አዝና “ይሁን” አለችው። ቅዱስ ሥጋዋን ከቅዱስ ነፍሷ ለይቶ ነፍሷን በመላእክት ዝማሬ በይባቤ ወደ ሰማይ አሳረጋት። ደቀ መዛሙርቱንም ከያሉበት በደመና ጠቅሶ ካለችበት አድርሶ “የእመቤታችሁን ሥጋዋን በክብር አሳርፉ” አላቸው። (ተአምረ ማርያም)፡፡

ሐዋርያት በአጎበር አድርገው ወደ ጌቴ ሰማኒ ይዘው ሲሄዱ አይሁድ በምቀኝነት ተነሣስተው ቀድሞ ልጇ ተነሣ፣ ዐረገ እያሉ ሲያውኩን ይኖራሉ አሁን ደግሞ እርሷን ተነሣች፣ ዐረገች እያሉ ሊያውኩን አይደለምን? በእሳት እናቃጥላታለን ብለው ተነሡ። ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ በትዕቢት ተራምዶ አጎበሩን ጨበጠው። ጌታችንም መልአኩን ልኮ በሰይፍ እጁን ቆረጠው፣ ከአጎበሩም ተንጠልጥሎ ቀረ። ታውፋንያ የደረሰበትን ተመልከቶ በድያለሁ ማሪኝ ብሎ ቢማጸናት እጁ ተመልሶለታል። ከዚህም በኋላ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከደቀ መዛሙርቱ ቅዱስ ዮሐንስን አስከትሎ በደመና ነጥቆ፣ ከገነት ወስዶ ከዕፀ ሕይወት ሥር አኖራት።

ቅዱስ ዮሐንስ ሲመለስም ደቀ መዛሙርቱ በአንድነት ሆነው “እንደምን ሆነች?” አሉት፡፡ እርሱም “ከገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አለች” አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ቅዱስ ዮሐንስ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ዕርገት አይቶ እኛ ሳናይ ብለው በነሐሴ መባቻ ጾም ጀመሩ፡፡ ሁለት ሱባኤ ሲፈጸምም እሑድ አምጥቶ ሰጥቷቸው ቀብረዋታል፡፡ በሶስተኛው ቀን ማክሰኞ ከመ ትንሣኤ ወልዳ፣ እንደ ልጇ ተነሥታለች።

በዚህ ጊዜ ቅዱስ ቶማስ አልነበረምና ደመና ጠቅሶ ከሀገረ ስብከቱ ሲመጣ ስታርግ አገኛት “ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ፣ ዛሬ ደግሞ የአንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁን?” ብሎ ከሐዘኑ የተነሣ ከደመናው ላይ ወደ መሬት ሊወድቅ ወደደ፡፡ እመቤታችንም “አይዞህ አትዘን እነርሱ ትንሣኤዬንና ዕርገቴን አላዩም አንተ ግን አይተሃልና ተነሣች፣ ዐረገች ብለህ ንገራቸው” ብላ የያዘችውን ሰበን ሰጥታ ሰደደችው። ከዚህ በኋላ ሄዶ ሐዋርያት በተሰበሰቡበት “የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ?” አላቸው፡፡ “አግኝተን ቀበርናት” አሉት፡፡ “ሞት በጥር፣ በነሐሴ መቃብር? ተዉ ይህ ነገር አይመስለኝም” አላቸው። ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ ሁል ጊዜ ልማድህ ነው፣ አንተ ብቻ ተጠራጥረህ አትቀርም ሰውን ሁሉ ስታጠራጥር ትኖራልህ” ብሎ ተቆጥቶ ወደ መቃብሯ ሄደው ቢከፍቱት የእመቤታችንን ሥጋ አጡት፡፡ ሁሉም ደንግጠው በቆሙበት ሐዋርያው ቶማስም አታምኑኝም ብዬ እንጂ “እመቤታችንስ ተነሣች፣ ዐረገች” አላቸው፡፡ የያዘውንም ሰበን ሰጥቷቸው ለበረከት ተካፍለውታል። በዓመቱ ሐዋርያት “ቅዱስ ቶማስ ትንሣኤሽንና ዕርገትሽን አይቶ እኛ ሳናይ” ብለው ነሐሴ አንድ ቀን ጾም ጀመሩ፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በ፲፮ኛው ቀን እመቤታችንን መንበር አድርጎ፣ ቅዱስ ጴጥሮስን ካህን፣ ሊቀ ዲያቆናት ቅዱስ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ በዚያው ላይ ቀድሶ አቁርቧቸዋል። ቤተ ክርስቲያንም ይህንን መታሰቢያ አድርጋ በየዓመቱ ታከብረዋለች። ቅዱስ ያሬድ በዚህ ተደንቆም “ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ፣ ሞታ ለማርያም የዐጽብ ለኵሉ፤ ሞት ለማንኛውም ሰው ሁሉ የተገባና የማይቀር ነው፣ የማርያም ሞት ግን ሁሉን ያስደንቃል” በማለት ተናገረ፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሞታ እንደማትቀር፣ እንደምትነሣና እንደምታርግ ጠቢቡ ሰሎሞንም ምሥጢር ተገልጦለት ሲናገር “ወዳጄ ሆይ ተነሺ፣ መልካምዋ ርግቤ ሆይ ነዪ” በማለት ተናግሯል፡፡(መኃ.፪. ፲)፡፡ ምንም እንኳን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ንጽሐ ሥጋ፣ ንጽሐ ነፍስ፣ ንጽሐ ልቡናን አስተባብራ የያዘች ብትሆንም የሥጋ ሞት ለማንም እንደማይቀር ሲያስረዳም “ርግብየ ተንሥኢ ወንዒ፣ ርግቤ ሆይ ተነሺ፣ ነዪ” አለ፡፡

በተአምረ ማርያም መግቢያ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ክብርና ቅድስና የተጠቀሰውን በማስከተል ጽሑፋችንን እናጠቃልል፡- “እንደ እመቤታችን እንደ ማርያም የአብ ማረፊያ የሆነ ማነው? እንደ እመቤታችን እንደ ማርያም የወልድስ ማደሪያ የሆነ ማነው? እንደ እመቤታችን ማርያም የመንፈስ ቅዱስ ቤት የሆነ ማነው? ለሰው ኃጢአት ሳይሠራ መኖር ይቻለዋልን? ከአራቱ ባሕሪያት ከተፈጠረ ሰው ከእመቤታችን በቀር እሳትን የተሸከመ፣ ኃጢአትንም ያልሠራ የለም፤ እመቤታችን ማርያም ከመላእክት ይልቅ ንጽሕት ናት፣ እመቤታችን ማርያም ከሴቶች ሁሉ ትበልጣለች፡፡ የእመቤታችን ማርያም ሐሳብ እንደ አምላክ ሐሳብ ነው፡፡ የእመቤታችን ማርያም መልኳ እንደ አምላክ መልክ ነው፣ የአምላክን መልክ ይመስላል፡፡ እመቤታችን ማርያም ንጽሕት በመሆንዋ አምላክን እንዲያድርባት አደረገችው፡፡ እመቤታችን ማርያም ለአምላክ የደስታ ማደሪያ ሆነችው፡፡ እመቤታችን ማርያም አምላክን በድንግልና ወለደችው፡፡ እመቤታችን ማርያም በነቢያት ትነገር ነበር፡፡ እመቤታችን ማርያም በሐዋርያትም ትነገር ነበር፡፡ እመቤታችን ማርያም በፍጥረት አንደበት ትመሰገናለች፣ የቤተ ክርስቲያን ልጆች አክብሯት ለእኛ ለኃጥኣን መድኃኒታችን ስለሆነች፡፡ በጎ አገልግሎትም ለሚያገለግሉት ዋጋውን ትሰጠዋለች፣ ሳትጠራጠሩ በፍጹም ልቡናችሁ እመኑባት እሷ መድኃኒታችን ናትና፡፡ በሥዕሏ ፊት ስገዱ ለሥዕሏም ያልሰገደ ግን ከቆመበት ቦታ ይጥፋ፣ ስም አጠራሩም አይታወቅ፡፡ (ተአምረ ማርያም መግቢያ)፡፡

ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በረከት ረድኤት ያሳትፈን፡፡ አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ቃና ዘገሊላ

እንደ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ በጥምቀት በዓል ማግስት ጥር ፲፪ ቀን የቃና ዘገሊላ በዓል ይከበራል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቃና ዘገሊላ በተደረገ ሠርግ ቤት ያደረገውን ተአምር በማሰብ በዓልን ታደርጋለች፡፡ በዓሉ ቃና ዘገሊላ የሚል ስያሜ ያገኘው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከገሊላ ክፍል ቃና በተባለችው ቦታ በፈፀመው ተአምር መነሻነት ነው፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቃና በዶኪማስ ቤተ በተደረገ ሠርግ እመቤታችን ለሠርገኞቹ ዘመድ ነበረችና ከእናቱ ከድንግል ማርያም እንዲሁም መምህርን ጠርቶ ደቀ መዛሙርቱን መተው ሥርዓት ስላልሆነ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ተገኝቷል፡፡ በሠርጉ ቤትም ሥርዓቱ እየተከናወነ ሳለ የተዘጋጀው የወይን ጠጅ አለቀባቸው፡፡ ይህን የተገነዘቡት ዶኪማስና አስተናባሪዎቹ ተደናግጠው ሳለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የወይን ጠጁ ማለቁን ተረድታ ጭንቀታቸውን ወደሚያቀልለው ልጇ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ዘንድ ቀርባ “ልጄ የወይን ጠጅ አልቆባቸዋል” አለችው፡፡ እርሱም መልሶ አንቺ ሴት ከአንቺ ጋር ምን አለኝ? ጊዜዬ ገና አልደረሰም አላት፡፡ ይህም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ የሚውልበትና ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለሰው ልጆች ሁሉ ለዘለዓለም ድኅነት ያድል ዘንድ ጊዜው አለመድረሱን ሲያመለክት ነው፡፡ እመቤታችንም ለአገልጋዮቹ የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ አለቻቸው፡፡ በቦታው የነበሩትን ስድስት ጋኖች ውኃ ሞልተው እንዲያመጡ አዘዘቻቸው፡፡ እያንዳንዱም ጋን ሁለት ወይም ሦስት እንስራ ይይዙ ነበር፡፡ አስተናባሪዎቹም ውኃውን በጋኖቹ ሞልተው አቀረቡለት፣ ውኃውንም ወደ ወይን ለወጠው፡፡  እነርሱም እየቀዱ ለታዳሚዎች አቀረቡ፡፡

ታዳሚዎቹም በወይን ጠጁ ልዩ ጣዕም ተደንቀው ሙሽራውን ጠርተው ሰው ሁሉ መልካሙን የወይን ጠጅ አስቀድሞ ያጠጣል፤ ከጠገቡ በኋላም ተርታውንም ያመጣል፤ አንተ ግን መልካሙን የወይን ጠጅ እስከአሁን አቆየህ አሉት፡፡ ጌታችን ኢየሱስም በቃና ዘገሊላ ያደረገው የተአምራት መጀመሪያ ይህ ነው፤ ክብሩንም ገለጠ፤ ደቀ መዛሙርትም አመኑበት፡፡ (ዮሐ.፪፥፩፲፩)

የቃና ዘገሊላ ጥንተ ነገሩ ወይም ታሪኩ የተፈፀመው በሌላ ጊዜ ቢሆንም አባቶቻችን የውኃን በዓል ከውኃ በዓል ጋር ለማክበር ብለው ወደ ጥር ፲፪ አምጥተውታል፡፡ ይህም ውኃ ወደ ወይን የተለወጠበትን በዓል ከጌታ ጥምቀት በዓል ጋር ለማስተሣሠር በማሰብ ነው፡፡ በመሆኑም የቃና ዘገሊላ በዓል ጥር ፲፪ ቀን ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ታከብረዋለች፡፡

እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሣይነግሯት በልብ ያለውን የምታውቅ እናት ናትና የሠርጉ አስተናባሪዎች ይህ ጎደለ ሳይሏት የልቡናቸውን ሐዘን ተመልክታ ከልጇ ከወዳጇ አማልዳ የጎደላቸውን ሞልታለች፤ ያስጨነቃቸውንም አርቃለች፤ ለችግራቸውም ደርሳላቸዋለች፡፡ ሳይነግሯት የልቡናን አይታ ካማለደች ስሟን ጠርተው ለሚለምኗት ሁሉ እመቤታችን ትደርሳለችና ዘወትር ወደ እርሷ እንጸልይ ዘንድ ይገባል፡፡   

ከእናታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ረድኤት በረከት ያሳትፈን፡፡ አሜን!