ብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስ ወቅዱስ ጳውሎስ
ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ሠርታ የሚነበበውን ምንባብ፣ የሚዘመን ዜማ በቀለም ለይታ ሐምሌ ፭ ቀን ከዋዜማው ጀምሮ በታላቅ ድምቀት በዓላቸውን ከምታከብላቸው ሐዋርያት መካከል የሊቀ ሐዋርያት የቅዱስ ጴጥሮስና የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ ዕረፍት አንዱ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን በምድር ላይ ሳሉ እግዚአብሔርን አምነው፣ ራሳቸውን ለእግዚአብሔር ቃል አስገዝተው ታላላቅ ተአምራትን በማድረግ ድውያንን እየፈወሱ፣ በየደረሱበት ቃለ እግዚአብሔርን ለተራቡና ለተጠሙ ምእመናን በመመገብና በማጠጣት በሚታወቁ ስፍር ቁጥር በሌላቸው ቅዱሳን የተከበበች ናት፡፡ ታሪካቸውንም ሰንዳ ለትውልድ በማስተላለፍ ብቸኛዋ ተቋም ናት፡፡

የሐዋርያትን ታሪክ ለማወቅ ዋናው ምንጩ የቤተ ክርስቲያን የታሪክ መጻሕፍት ናቸው። በዚህም መሠረት በቤተ ክርስቲያናችን ሐምሌ ፭ ቀን በዓላቸውን ከምታከብርላቸው ሐዋርያት መካከል የሐዋርያው የቅዱስ ጴጥሮስና የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስን ታሪክ እንደሚከተለው አቅርበነዋል።
፩. ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ
ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ የተወለደው በገሊላ ቤተ ሳይዳ ሲሆን እናቱ ባወጣችለት ስም ስምኦን እየተባለ ይጠራ ነበር፡፡ በጐልማሳነቱ ከወንድሙ ከእንድርያስ ጋር በገሊላ ባሕር ዓሣ በማጥመድ ሥራ ላይ ተሠማራ። በ፶፭ ዓመት ዕድሜውም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዝሙርነት ጠርቶታል፡፡ “በገሊላ ባሕር ዳር ሲመላለስም ሁለቱን ወንድማማቾች ጴጥሮስንና እንድርያስን መረባቸውን ወደ ባሕር ሲጥሉ አየ፤ ዓሣ አጥማጆች ነበሩና ጌታችን ኢየሱስም ‘ኑ ተከተሉኝ፤ ሰውን የምታጠምዱ እንድትሆኑ አደርጋችኋለሁ” አላቸው፡፡ (ማቴ. ፬፥፲፰-፳) መረባቸውንም ትተው ተከተሉት፡፡ ቅዱስ ጰጥሮስ በዚህ መንገድ ነው የተጠራውና ቤተሰቡንና ያለውን ሁሉ ትቶ ጌታችንን የተከተለው፡፡
በቂሳርያ ከተማ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያትን “እናንተስማን ትሉኛላችሁ?” ብሎ በጠየቃቸው ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ” አለው፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ አንተ ብፁዕ ነህ፤ በሰማይ ያለው አባቴ እንጂ ሥጋና ደም ይህን አልገለጠልህምና፡፡ እኔም እልሃለሁ፡- አንተ ዐለት ነህ፤ በዚያች ዐለት ላይም ቤተ ክርስቲያኔን እሠራታለሁ፤ የሲዖል በሮች አይበረቱባትም” አለው፡፡ ጴጥሮስ የሚለው ስም በላቲን ቋንቋ ዐለት ማለት ነው፤ በአርማይክ ደግሞ ኬፋ ይባላል። (ማቴ. ፲፮፥፲፮) በዐለት ላይ የተመሠረተ ቤት ንፋስ በነፈሰ ጊዜ እንደማይፈርስ ሁሉ በክርስቶስ የተመሠረተችው ቤተ ክርስቲያንም በንፋስ የተመሰለው ዲያብሎስ ዙሪዋን ቢዞርም ለያጠፋት እንደማይችል ያመለክታል፡፡
ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጥብርያዶስ ባሕር ላይ በእግሩ ሲራመድ ተመልክቶ እርሱም ይሄድ ዘንድ ፈቃድ የጠየቀ፣ መሄድ የጀመረና ማዕበሉን ፈርቶም የተጠራጠረ፣ በዚህም ምክንያት ለመስጠም የደረሰ፣ ጌታችንን ያድነው ዘንድ የተማጸነ፣ ጌታችንም በጥያቄው መሠረት ከመስጠም ያዳነው እንደሆነ ቅዱስ ወንጌል ያስተምረናል፡፡ (ማቴ. ፲፬፥፳፪-፴፫)
በቅፍርናሆም ጉባኤ ጌታን ምሥጢረ ቁርባንን ሲያስተምር አይሁድ ስላልገባቸው ወደ ኋላ አፈገፈጉ። “እናንተ ደግሞ ልትሄዱ ትወዳላችሁ?” ብሎ ጌታችን ሐዋርያትን ጠየቃቸው። “ጌታ ሆይ ወደ ማን እንሄዳለን? አንተ የዘላለም የሕይወት ቃል አለህ። እኛስ አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ እንደሆንክ እናምናለን” በማለት ሐዋርያትን ወክሎ የመለሰ እርሱ ነው። (ዮሐ. ፮፥፷፮-፷፰)
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እረኛው መሞትና ስለ በጎቹ መበተን ሲያስተምር ለደቀ መዛሙርቱ “በዚህች ሌሊት ሁላችሁም ትክኛላችሁ” ብሎ በተናገረ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ፈጥኖ “ሁሉም ቢክዱህ እንኳ እኔ ከቶ አልክድህም” (ማቴ. ፳፮፥፴፬) ብሎ ተናግሯል፡፡ ነገር ግን በዚያው ሌሊት ጌታችን በአይሁድ በምቀኝነት ይሰቅሉት ዘንድ በተያዘ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ አስቀድሞ የተናገረውን ቃል ዘንግቶ ዶሮ ሳይጮህ ሦስት ጊዜ ክዶታል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ የሚታወቅበት ሌላው ትልቁ ነገር ንስሓው ነው። አምላኩን መበደሉን ሲረዳ ተጸጽቶ ምርር ብሎ የንስሓ ዕንባን አንብቷል፡፡
በበዓለ ሃምሳ ለደቀ መዛሙርቱ መንፈስ ቅዱስ በወረደላቸው ጊዜ ለተሰበሰቡት አይሁድ ወንጌልን የሰበከ፣ ሦስት ሺህ ምእመናንን አሳምኖ የመጀመሪያዋን አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን በኢየሩሳሌም የመሠረተ እርሱ ነው። (የሐዋ. ፩፥፲፮-፳፫ ፤ ፪፥፲፬-፴) ልዑል እግዚአብሔር ባደለው ጸጋ ጥላው እንኳን ድውያንን ይፈውስ ነበር። (ሐዋ. ፭፥፲፭)።
ቅዱስ ጴጥሮስ በፍልስጥኤም፣ በሶርያ፣ በጳንጦን፣ በገላትያ፣ በቀጰዶቅያ፣ በቢታንያ እና በሮሜ ሰብኳል። ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በሮሜ አንድ ዓመት ከቅዱስ ጳውሎስ ጋር ካስተማረ በኋላ የሮሜ ክርስቲያኖች እየበዙ ከመምጣታቸውም በላይ የክርስትናው ጉዞ እስከ ሮማ ባለሥልጣናት ደረሰ። የኔሮን የቅርብ ባለሥልጣናት የሆኑት የአልቢኖስና የአግሪጳ ሚስቶች ወደ ክርስትናው ገቡ። በዚህን ጊዜ ኔሮን ንጉሠ ሮማ በቅንዓት ተነሣባቸው።
ኔሮን በሮም የነገሠው በ፶፬ ዓ.ም. ነው። በመንግሥቱ መጀመሪያ ደግ ሰው ነበረ። ነገር ግን በነገሠ በዓመቱ የጨካኝነት ዐመሉ ብቅ ማለት ጀመረ እና የአባቱን ልጅ አስገደለ። በ፶፱ ዓ.ም. ደግሞ እናቱን በመርዝ ገደለ። በ፷፫ ዓ.ም. እያስተማረ ያሰደገውን መምህሩን ፣ በ፷፪ ዓ.ም. የልጅነት ሚስቱን አግታሺያን አስገደለ። ከእርስዋ በኋላ ያገባትን ሚስቱንም ፓፒያን ገደላት። በ፷፬ ዓ.ም ከከተማው ወጣ ብሎ በሚገኘው ቤተ መንግሥቱ ተቀምጦ የሮማን ከተማ እሳት ለቀቀባት። የሮም ሕዝብ በደረሰው አደጋ እጅጉን ተቆጣ። ኔሮንም በክርስቲያኖች አመካኘ። በዚህም የተነሣ በሮማ ከተማ ሁለት ዓይነት ወሬ መናፈስ ጀመረ።
የሮማ አማልክት በክርስቲያኖች ሃይማኖት ስለተቆጡ በከተማዋ እሳት አዘነቡባት የሚለው የመጀመሪያው ሲሆን ክርስቲያኖች ሆን ብለው ከተማዋን አቃጥለዋታል የሚለው ደግሞ ሁለተኛው ወሬ ነበር። የከተማው መጋየት ያበሳጨው የሮማ ሕዝብ፣ ክርስቲያን የሆነውን ሁሉ እያወጣ መግደሉን ተያያዘው። ይህን የሰሙት የአግቢኖስና የአግሪጳ ሚስቶች (የሮም ባለሟሎች ነበሩ) “አንተ ትረፍልን” ብለው በከተማዋ ግንብ በገመድ አሥረው በቅርጫት በማውረድ ቅጥረ ሮማን ለቅቆ እንዲወጣ አደረጉት።
ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በኦፒየም ጎዳና ጉዞውን ቀጠለ። ሮማን ለቀቀ። እያዘገመ በሸመገለ ጉልበቱ ሲጓዝ አንድ ቀይ ጐልማሳ ወደ እርሱ ሲመጣ አየ። እየቀረበ ሲመጣ ጌታችን መሆኑን ተረዳ። ወዲያው በፊቱ ተደፋና “ጌታዬ ወዴት እየተጓዝክ ነው?” አለና ጠየቀው። “ዳግም በሮም ልሰቀል” አለው። በዚህ ሰዓት ቅዱስ ጴጥሮስ አዘነና እንደገና ወደ ሮም ተመለሰ። የኔሮን ወታደሮች እየፈለጉት ነበር። “እነሆኝ ስቀሉኝ” አለ ቅዱስ ጴጥሮስ። ያን ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስን ይዘው አሠሩት። ከጥቂት ቀናት በኋላም ሮማውያን የመስቀያውን እንጨት አቀረቡለት። ያን ጊዜ “እኔ እንደ ጌታዬ ልሰቀል አይገባኝም” በማለት ቁልቁል እንዲሰቅሉት ለመነ። እንደለመነውም ሐምሌ ፭ ቀን ፷፯ ዓ.ም ቁልቁል ሰቅለውት በሰማዕትነት ዐረፈ።
፪. ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ዘሩ ከዕብራዊያን፣ ከብንያም ነገድ ሲሆን የተወለደውም በጠርሴስ ከተማ ነው። ጠርሴስ በንግድዋ የታወቀች የኪልቂያ ዋና ከተማ ናት። በከተማዋ እስከ አምስት መቶ ሺህ የሚገመቱ ከየሀገሩ የተሰባሰቡ ሕዝቦች ነበሩባት። ሮማውያን በሥራቸው ለሚተዳደሩት ሕዝቦች ሮማዊ ዜግነትን ይሰጡ ስለነበር፥ የቅዱስ ጳውሎስ አባት በዜግነት ሮማዊ ነበር። ይህም ለቅዱስ ጳውሎስ ተላልፎለታል።
ቅዱስ ጳውሎስ በኢየሩሳሌም ከታወቀው የገማልያል ትምህርት ቤት ገባ። በዚያም የአይሁድን ሕግና ሥርዓት እየተማረ እስከ ፴ ዓመቱ ቆየ። በ፴ ዓመቱ የአይሁድ ሸንጎ አባል ሆኖ ተቆጠረ።ለኦሪታዊ እምነቱም ቀናተኛ በመሆኑ ክርስቲያኖችን ያሳድድ ነበር። ሊቀ ዲያቆናት ቅዱስ እስጢፋኖስ ተከሶ በአይሁድ ሸንጎ ፊት በቀረበ ጊዜ በድንጋይ ተወግሮ በሰማዕትነት ሲያርፍ የወጋሪዎችን ልብስ በመጠበቅ የተባበረ ነው። “ሰማዕቱ ቅዱስ እስጢፋኖስን በገደሉትም ጊዜ እኔ እዚያ አብረአቸው ነበርሁ፤ የገዳዮችንም ልብስ እጠብቅ ነበር” እንዲል፡፡ (ሐዋ. ፳፪፥፳)
ቅዱስ ጳውሎስ በደማስቆ ከተማ ብዙ ክርስቲያኖች መኖራቸውን ሲሰማ ወደ ሊቀ ካህናቱ ቀርቦ ክርስቲያኖችን ለማጥፋት የሚያስችለውን የፈቃድ ደብዳቤ አገኘ። ከዚህም በኋላ ጭፍሮችን አስከትሎ ወደ ደማስቆ አመራ። ሐዋርያው ጳውሎስ ወደ ከተማዋ ለመድረስ ጥቂት ሲቀረው ነበር ከሰማይ የወረደው ብርሃን አካባቢውን ያለበሰውና “ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ?” የሚለውን ድምፅ የሰማው። ሐዋርያው ጳውሎስም “ጌታ ሆይ ማን ነህ?” ብሎ ጠየቀ። “አንተ የምታሳድደኝ እኔ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ። የመውጊያውን ብረት ብትቃወም ለአንተ ይብስብሃል” ሲል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተናገረው። ያን ጊዜም በወደቀበት ሆኖ እየተንቀጠቀጠ “ጌታ ሆይ ምን አደርግ ዘንድ ትወዳለህ?” ሲል ጠየቀ። ከዚህ በኋላ ተነሥቶ ወደ ደማስቆ እንዲገባ ተነገረው። ነገር ግን ዓይኖቹ ማየት አልቻሉም፤ እየመሩም ወደ ደማስቆ ሐናንያ ወደሚባል ሰው ወሰዱት፡፡ ሐናንያም እጁን ጭኖ ጸለየ፡፡ ከዓይኖቹም እንደ ቅርፊት ያለ ነገር ተገፎ ወደቀለት፣ ዓይኖቹም ተገለጡ፣ ተነሥቶም ተጠመቀ፡፡ ስለ ጌታችንም “የእግዚአብሔር ልጅ ነው” በማለት መስበኩን ቀጠለ፡፡ (የሐዋ. ፱፥፩-፲፰)
አይሁድም ቅዱስ ጳውሎስን ይገድሉት ተነሡ። ሐዋርያት ግን የቅዱስ ጳውሎስን መመለስ ለማመን ቢቸገሩም በርናባስ ወስዶ የጳውሎስን መመለስ በመተረክ እንዲያምኑት አደረጋቸው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በጠርሴስ ከተማ ለዘጠኝ ዓመታት ቆይቷል። ከኢየሩሳሌም ውጭ የአሕዛብ ከተማ በነበረችው በአንጾኪያ የክርስትና ሃይማኖት ተስፋፋ።
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመጀመሪያው ጉዞ ያደረገው ከኢየሩሳሌም ወደ አንጾኪያ ከተመለሰ በኋላ በልዑል እግዚአብሔር ጥሪ በአሕዛብ ሀገር ወንጌልን ለመስበክ ከበርናባስ ጋር ወጡ። በዚህ ጉዞአቸው በጠቅላላው ወደ ሁለት ሺህ ኪሎ ሜትር የሚደርስ መንገድ በእግር ተጉዟል። ይህም ጉዞ የተከናወነው በ፵፮ ዓ.ም. አካባቢ ነው። የተሸፈኑትም ሀገሮች ሲሊንውቂያ፣ ቆጵሮስ፣ ስልማን፣ ጳፋ፣ ጰርጌን፣ ገላትያ፣ ጵስድያ፣ ኢቆንዮን፣ ሊቃኦንያ፣ ልስጥራ፣ደርቤን፣ጵንፍልያ፣አታልያና አንጾኪያ ናቸው።
ሁለተኛው ጉዞ የተከናወነው በ፶ ዓ.ም. ገደማ ነው። በመጀመሪያው ጉዞ ማርቆስ አብሮ ተጉዞ ነበር። ነገር ግን ጵንፍልያ ከተማ ሲደርስ እናቱ ስለናፈቀችው መመለስ በመፈለጉ በርናባስ ወደ ኢየሩሳሌም ይዞት መጣ። ስለዚህም በሁለተኛው ጉዞ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሲላስን ይዞ ወደ ኪልቂያ ሶርያ ሲጓዝ በርናባስ ደግሞ ማርቆስን አስከትሎ ወደ ቆጵሮስ ሄደ። በዚህ ጉዞው ቅዱስ ጳውሎስ እስከ ግሪክ ደርሶአል። የተጓዘባቸውና ያስተማረባቸው ከተሞችም፦ ደርብያ፣ ልስጥራ፣ፍርግያ፣ ገላትያ፣ ሚስያ፣ጢሮአዳ፣ ሳሞትራቄ፣ ናፑሊ፣ ፊልጵስዩስ፣ ተሰሎንቄ፣ በርያ፣አቴና፣ ቆሮንቶስ፣ አንክራኦስ፣ አፌሶን፣ ቂሳርያ፣ ኢየሩሳሌምና አንጾኪያ ናቸው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመንፈስ ልጁ ጢሞቴዎስን ያገኘው በዚሁ ጉዞው በልስጥራ ከተማ ነው።
ሦስተኛው ጉዞ የተከናወነው በ፶፬ ዓ.ም. ሲሆን የተሸፈኑትም ሀገሮች የሚከተሉት ነበሩ። ገላትያ፣ ፍርግያ፣ ኤፌሶን፣ መቄዶንያ፣ ፊልጵስዩስ፣ ቆሮንቶስ፣ ጢሮአዳ፣ አሶን፣ ሚልጢኒን፣ አንጠቀከስዩ፣ ትሮጊሊዩም፣ መስጡ፣ ቆስ፣ ሩድ፣ ጳጥራ፣ ጢሮስ፣ ጵቶልማይስ፣ ቂሳርያ፣ ኢየሩሳሌም ናቸው።
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከልዩ ልዩ ሀገሮች ክርስቲያኖች የሰበሰበውን ዕርዳታ ለኢየሩሳሌም ቤተ ክርስቲያን በመያዝ ሦስተኛውን ጉዞ አጠናቅቆ ኢየሩሳሌም ገባ። ነገር ግን ኢየሩሳሌም የገባበት ጊዜ የፋሲካ በዓል ስለነበር ከልዩ ልዩ ሀገሮች የተሰበሰቡ አይሁድ በከተማዋ ነበሩ። እነዚህ በዝርወት የሚኖሩ አይሁድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስን በየሀገራቸው በትምህርቱ የተነሣ ሲቃወሙት የነበሩ ናቸው።
መስበኩን በመቀጠሉ ምክንያት በ፶፰ ዓ.ም በሮም ለቁም እሥር ተዳረገ። የሁለቱን ዓመት የቁም እሥር እንደጨረሰ ወደ ኔሮን ፍርድ ቤት ቀረበ። ይህም በ፷ዎቹ ዓ.ም ነው። በፍርድ ቤቱ በተደረገው ምርመራ የሮሜን ሕግ የሚቃወም ምንም ወንጀል ስላልተገኘበት በነፃ ተለቀቀ፤ ከዚህ በኋላ ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አራተኛውንና የሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ ያልመዘገበውን ጉዞውን ያደረገው። ይህ ጉዞው በመታሠሩ አዝነው ተክዘው የነበሩ ክርስቲያኖችን ለማጽናናት የጀመራቸውን ሥራዎች ፍጻሜ ለማየት የተደረገ ጉዞ ነው። በዚህም ጉዞው ኢየሩሳሌምን፣ ኤፌሶንን፣ ሎዶቅያን፣ መቄዶንያን፣ ቀርጤስን፣ ጢሮአዳን፣ ድልማጥያን፣ እልዋሪቆን፣ ኒቆጵልዮን፣ ብረንዲስን፣ ጎብኝቷል። በዚህ የመጨረሻ የስብከት ጉዞው ለአራት ዓመታት ያህል ቆይቷል።
በመጨረሻ በ፷፬ ዓ.ም. ኔሮን በጥጋቡ የሮማ ከተማ ስትቃጠል ምን እንደምትመስል ማየት እፈልጋለሁ ብሎ አቃጠላት። የሮም ሕዝብ በከተማው መቃጠል በማዘኑና በማመፁ ነገሩን ሁሉ በክርስቲያኖች ላይ አሳበበ። በዚህም የተነሣ ክርስቲያን የተባለ ሁሉ መሰደድ፣ መሠየፍ፣ መታረድ እጣ ፈንታው ሆነ። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም በኒቆጵልዮን ከተማ ሲያስተምር በ፷፭ ዓ.ም. ተይዞ ወደ ወኅኒ ገባ። ለሁለት ዓመት ከስድስት ወር በጨለማ ቤት ታሥሮ ከቆየ በኋላ በ፸፬ ዓመት ዕድሜው በሮም ከተማ በኦስትያ መንገድ አንገቱን ተሰይፎ በ፷፯ ዓ.ም. ሐምሌ ፭ ቀን በሰማዕትነት ዐረፈ።
ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ሁለት፣ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ ዐስራ አራት መልእክታትን ጽፈዋል። የቅዱሳኑ ሐዋርያት ረድኤትና በረከታቸው ከሁላችን ጋር ይሁን፤ አሜን።
ምንጭ፦ መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኃ ሐምሌ ፭፤ መጽሐፍ ቅዱስ ሐዲስ ኪዳን፣
ቤተ ክርስቲያንህን ዕወቅ ቁጥር ፩፤ በማኅበረ ቅዱሳን