“በእኔ ውስጥ ያሉ ተኩላዎች”

ብፁዕ አቡነ ሙሳ የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን

የወጣቶች ጉዳይ ሊቀ ጳጳስ

   ዲ/ን በረከት አዝመራው እንደተረጎመው

ክፍል አንድ

እየተነጋገርንበት ያለው ርእስ በመንፈሳዊ ሕይወታችን በውጭና በውስጥ ያሉብንን ተግዳሮቶች እንዴት መዋጋት እንዳለብን የሚያመልክት ነው፡፡ እነዚህ ተግዳሮቶች በእኛ ውስጥ እና ከእኛ ውጭ ያሉ “ተኩላዎች” ናቸው፡፡ እኛ እንደ በጎች ነን፤ ውስጣዊውንና ውጫዊውን ሕይወታችንን እየተፈታተኑ ሊናጠቁ የሚሞክሩት ደግሞ ተኩላዎች ናቸው።

የዛሬው ትምህርት ስለ ውስጣዊ ተኩላዎች ነው፡፡ እነዚህም በሕይወታችን የሚታዩ ውስጣዊ ተቃርኖዎችና ጠላቶች ናቸው፡፡ በመንፈሳዊ፣ በማኅበራዊና ዘለዓለማዊ የሕይወት ጉዟችን በትክክለኛው አቅጣጫ እንጓዝ ዘንድ ይህንን ርእስ ልንነጋገርበት ይገባል፡፡ ሁሉን ብናገኝ ዘለዓለማዊነታችንን ግን ብናጣ ምን ይጠቅመናል? ስለዚህ ዘለዓለማዊነትን እንድናገኝ አጥብቀን መሥራትና በሕይወታችን ትልቅ ቦታ ልንሰጠው የሚገባ ውሳኔን ይጠይቃል፡፡ እንደምታዩት ዓለም ትለዋወጣለች፤ ስለዚህ እውነታ ሊሆን የሚችለው የማይለወጠው ዘለዓለማዊነት ነው፡፡ ዓለምና ክብሯም ያልፋል፡፡ ስለዚህ ከዚህ ዓለም ሕይወት አሻግረን ፊታችን ያለውን ልንመለከት ግድ ይለናል፡፡፡ ቁሳዊውን ዓለም ብቻ የሚያስቡ ሰዎች ግን ታላቅ ስህተት ፈጽመዋል፡፡ ወሰንና መጨረሻ ከሌለው ከዘለዓለማዊው ዓለም ከእግዚአብሔር መንግሥት ይልቅ በውስኑ ዓለም ባክነው ይቀራሉና፡፡

የተፈጠርነው በእኛ ውስጥና ውጪ ካሉ ተኩላዎች ጋር አይደለም፡፡ እነዚህ በኃጢአት የሚመጡ ናቸው፡፡ እግዚአብሔር በመጀመሪያ አዳምንና ሐዋንን ሲፈጥር ያለ እነዚህ ተኩላዎች ነው፡፡ እነርሱ በኤደን ገነት የእግዚአብሔር ከእነርሱ ጋር መኖር እየተሰማቸው ከእርሱ ጋር ይኖሩ ነበር፤ በእግዚአብሔር ትእዛዝ መሠረት ከዕፀ በለስ በስተቀር በገነት ውስጥ ካለው ዛፍ ሁሉ ይበሉም ነበር፡፡ የተፈቀደውም ጉዞ ሲደርሱ ከዕፀ ሕይወትም መብላቸው አይቀርም ነበር፡፡ እነርሱ ግን የተለየ ምርጫ መረጡ፡፡ በእርግጥ በዚህ ውሳኔአቸው ብዙም አንጸጸትበትም፡፡ ለድኅነት ታሪክ እኛ በእርሱ እርሱም በእኛ የሚኖርበትን ነገር ፈጥሯልና እግዚአብሔር ወልድ በተለየ አካሉ ሰው በመሆኑ የመንግሥቱ ወራሾች እንድንሆን ጠርቶናል፡፡ እነሆ አሁን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እስክንደርስ ድረስም ሁሉ ከፍ ከፍ የምንል ሆነናል፡፡

ስንፈጠር የተፈጠርነው በእግዚአብሔር አምሳል ነው፡፡ በጥበብና በአእምሮ ቅድስና በምንላቸው በፍቅር፤ በመንፈስና በምግባራት፣ በነፃነትና ነፃ ፈቃድ እንዲሁም በዘለዓለም ሕይወታችን እግዚአብሔርን የምንመስል ሆነናል፡፡ ሆኖም አዳምና ሔዋን ነፃነታቸውን ያለ አግባብ በተጠቀሙበት ጊዜ ከዕውቀት ዛፍ በሉ፤ ኃጢአትን በሠሩ ጊዜ ብሩህ አእምሯቸውን ማጣት ጀመሩ፡፡ ነፃነት ወደ አዳምና ሔዋን ውድቀት አመራ፤ ፈተና ከዲያብሎስ መጣ፤ ከኤደን ገነትም መውጣትም በእግዚአብሔር ተደረገ፡፡

በወደቀው ሰብእናቸው ለዘለዓለም እንዳይኖሩ በማሰብ ከሕይወት ዛፍ እንዳይበሉ በፍርዱ ከኤደን አስወጣቸው፡፡ ለዘለዓለም እንዲኖሩ ቢፈልግም ከድኅነት በኋላ መሆን ነበረበት፡፡ ስለዚህም ከመንግሥቱ ተለይተን እንዳንቀር ገነት ከእርሱ ጋር እንኖር ዘንድ ድኅነትን ማዘጋጀት ጀመረ፡፡

ስለዚህ የተኩላዎቹ ፈጣሪዎች እኛ እንጂ እግዚአብሔር አይደለም፡፡ ሁሉን ከፈጠረ በኋላ ሁሉም መልካም ነበርና ሰውንም ከፈጠረ በኋላ “በጣም መልካም” ብሏልና፡፡ ተኩላዎቹ ማደግ የጀመሩት በእኛ ውስጥ ነው፡፡ እነዚህ የውስጥ ተኩላዎች ምንድን ናቸው?

የመጀመሪያው ክፉ እኔነት ነው፡፡ ሁለተኛው የኃጢአት ሕግ የተጠናወተው አእምሮ ነው፡፡ ይህ አእምሮ እንደዚህ እንዲሆን ባይፈጠርም በኃጢአት ከጨለመ በኋላ እንደዚህ ሆነ፡፡ ሦስተኛው ሥጋችን ነው፡፡ ነገር ግን ሥጋ በራሱ ችግር እንዳልሆነ ማወቅ ይገባናል፡፡ ተኩላ የሚያደርገው በውስጣችን የሚኖረው ኃጢአት ነው፡፡ ለምሳሌ አንድ ዐይን መልካምም ክፉም ነገር ሊያይ ይችላል፡፡ መንፈሳዊ እድገታችንና አኗኗራችንን የሚያሰናክሉት ሦስት የውስጥ ተኩላዎች እንዚህ ናቸው፡፡

የክፉ እኔነት ተኩላ /Ego/

እኔነት እንዴት ተኩላ ሊሆን ይችላል? እኔነት/Ego/ ከእግዚአብሔር እና ከሌሎች ተለይተን በራሳችን ውስጥ ታጥረን በትዕቢት፤ በከንቱ ውዳሴና በራስ ወዳድነት እንድንያዝ ምክንያት ይሆናል፡፡ ከቅዱስ ጳውሎስ “ኃይልን በሚሰጠኝ በክርስቶስ ሁሉን እችላለሁ” ከሚለው መልእክት በተቃራኒ በራሳችን ብቁ እንደሆንን እና አግዚአብሔር ሳያስፈልገን ሁሉን ማድረግ እንደምንችል እንድናምን ያደርገናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ግን “ሁሉን እችላለሁ” ብሎ አላቆመም፤ እነዚህን ማድረግ የሚችል በእግዚአብሔር መሆኑን ዐውቋል፡፡ እኔነት የተጠናወተው ሰው በሕይወቱ ያሉትን መልካም ነገሮች ከእግዚአብሔር ጋር ማዛመድ አይፈልግም፡፡ ክፉ እኔነት/Ego/ በኤደን ገነት የኃጢአቶች ምንጭ ነበር፡፡ ዲያብሎስ የወደቀው እንደ እግዚአብሔር  ሊሆን በመፈለጉ ነውና፡፡ አዳምና ሔዋንም በእባቡ የተታለሉት እንደ እግዚአብሔር መሆን ፈልገው ነው፡፡

እግዚአብሔር በሕይወትህ ሲኖር መንፈስህ ከፍ ከፍ ይላል፤ እኔነትህ ግን ዝቅ ዝቅ ይላል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ “እርሱ ሊበዛ እኔ ግን ላንስ ይገባል” እንዳለ በሕይወትህ የእግዚአብሔር ቦታ ከጨመረ እኔነትህ /Ego/ እየቀነሰ ነው ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔርን በሕይወታችን የምንፈልገውም ለዚህ ነው፡፡ በንስሓ፣ በቍርባን፣ በጸሎት፣ በመንፈሳዊ አገልግሎት፣ በቅዱሳት መጻሕፍት ጥናት፣ በጾም፣ በስግደት እና በምሥጋና እግዚአብሔር በውስጣችን ያድራል፡፡ ከእግዚአብሔር ጋር በምናደርገው በማንኛውም ግንኙነት ወደ ላይ የተዘረጋ መስመር እንመሠርታለን፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ጊዜ ወደ ውስጥ እንዘረጋለን እርሱም እኔነት /Ego/ ነው፡፡

ምድራዊው ገጽታ ደግሞ ሥጋዊነት ነው፡፡ ወደ ላይ እንመለከት ዘንድ ካህኑ በቅዳሴ ጊዜ “ልባችሁን ከፍ ከፍ አድርጉ” የሚለን እኛም “ከመንፈስህ ጋር ነው” ብለን የምንመልሰው ይህንን ነው፡፡ መፍትሔአችን እግዚአብሔር ነው፡፡ እርሱን በውስጣችን ልንይዝ ይገባል፡፡ ይህንን ምሳሌ ተመልከቱ፡፡ ልብን በጎነ ሦስት/Triangle/ ብንመስለው /በእርግጥም ልብ ሦስት ጎን ቅርጽ አለው፤ ዓለምን በጎነ ሦስቱ /Triangle/ ዙሪያ በተሳለ ክብ ቅርጽ ብንወክላት፣ ውስጥ ያሉት ማዕዘናት በምንም ተአምር በክቡ ሊሞሉ አይችሉም፡፡ ጎነ ሦስት የሆነውን ልብ ለመሙላት በሦስትነት የሚኖረው እግዚአብሔር ያስፈልጋል፡፡ የቅድስት ሥላሴ ፍቅር ግን ልቡናህን በደስታ፣ በቅድስና፣ በጥበብ እና በዘለዓለማዊነት ይመላዋል፡፡ እንድትኖር ወደተፈጠርክለት የእግዚአብሔር አምሳልነት ይመልስሃል፡፡

የክፉ እኔነትን /Ego/ ውጥንቅጥ ለመፍታት እግዚአብሔር ፍቅር፣ አምልኮቱ በልቡናህ ውስጥ ማደግ አለበት፣ በዚህ ጊዜ ክፉ እኔነትህ ይቀንሳልና፡፡

ምንጭ፡- ጉባኤ ቃና ጥቅምት ፳፻፬ ዓ.ም

ይቆየን፡፡

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *