በእኔ ውስጥ ያሉ ተኩላዎች

ብፁዕ አቡነ ሙሳ የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን

የወጣቶች ጉዳይ ሊቀ ጳጳስ

   ዲ/ን በረከት አዝመራው እንደተረጎመው

ክፍል ሁለት

በኃጢአት የጎሰቆለ አእምሮ እንደ ተኩላ

አእምሮ /Mind/ በኃጢአት ጨልሟል፡፡ በዚህ ጨለማነት ምክንያት ብሩህ ካልሆነውና ከጨለመው አእምሮ የወጡ ብዙ ፍልስፍናዎችና የእምነት መጣመሞች /deviation/ አሉ፡፡ ከእነዚህ መካከል እግዚአብሔርን መካድ መርሑ የሆነው አቴይዝም /atheison/፤ እግዚአብሔር መኖሩን የሚያምነው ነገር ግን ከእርሱ ጋር መገናኘትን የማይፈልገው በዚህ መርሑም “በሰማይ ያለህ አባታችን ሆይ፣ አንፈልግህምና በዚያው ቆይ” የሚለው ኤግዚሰተንሻሊዝም /Existentialism/፤ ሁሉም ነገር /ወንበሩም ድንጋዩም/ የእግዚአብሔር የአካል  ክፍል እንደሆነ የሚናገረው ፓንትይዝም /pantheism/ ተጠቃሽ ናቸው፡፡

አእምሮ የጨለመው በኃጢአት ነው፡፡ አእምሮ ብሩህ ሲሆን ግን እግዚአብሔርን እናውቀዋለን፤ በመኖሩም በሁሉም እየሠራ እንደሆነ እንረዳለን፤ ወደ ዘለዓለማዊው መንግሥት የሚመራን እውነተኛው አምላክ እርሱ እንደሆነ እናውቃለን፡፡

በቅርቡ አንድ ታሪክ በኢንተርኔት አንብቤአለሁ፡፡ የተወሰኑ ልጃገረዶችን በክፍሏ የምታስተምር መምህርት ወደ አትክልት ቦታ ወሰደቻቸው፡፡ ከእነዚህ ወጣት ልጃገረዶች አንዷን ”ከጓደኞችሽ ፊት ሆነሽ መልሽልኝ፤ ይህ ዛፍ ይታይሻል?” አለቻት፡፡

“አዎ” አለች

“ያ ሕንፃስ ይታይሻል?” አለቻት፡፡

“አዎ” አለች፡፡

“እግዚአብሔርንስ ታይዋለሽ?”

“አላየውም” ልጅቷ መለሰች፡፡

መምህሯም “ስለዚህ እግዚአብሔር የሚባል ነገር የለም” አለች፡፡

ሌሎች ልጆች በመደናገጥ ላይ ሳሉ አንዷ ልጅ ተነሥታ “መምህር ዛፉ ይታይሻል?” አለቻት፡፡

“አዎ” አለች፡፡

“ወፎችስ ይታዩሻል?”

መምህሯም “አዎ” አለች፡፡

“ሰማዩስ ይታይሻል?” አለች ተማሪዋ ወደ ሰማይ እያየች፡፡

“አዎ” አለች መምህሯ፡፡

ተማሪዋ ጥያቄዋን ቀጠለች፡፡ “አእምሮሽን ታይዋለሽ?” ስትል ጠየቀች

“አላየውም” ብላ መለሰች መምህሯ፡፡

ተማሪዋም መምህሯን እየተመለከተች “ስለዚህ መምህር አእምሮ የለሽም” አለቻት፡፡

በብሩህና በጨለምተኛ አእምሮ መካከል ያለው ልዩነት ይህ ነው፡፡ እግዚአብሔርን ማየትና መንካት ምን ልዩነት ይፈጥር ይሆን? የቴሌቪዥን ሞገድን ማየት እንችላለን? ኤሌክትሪክንስን መንካት እንችላለን? ስለዚህ የሉም ማለት ነውን?

ብሩሃን ልንሆን ይገባል፣ ብሩህነትም ሊገኝ የሚችለው መጽሐፍ ቅዱስን በማንበብና በቤተ ክርስቲያን አስተምህሮዎች በመታነጽ ነው፡፡

ዲያብሎስ በተለያየ መንገድ ዕውቀትና ጥበብ ያለን በማስመሰል ያታልለናል፤ እውነተኛው አብርሆት /Enlightmet/ ያለው ግን በቅዱሳት መጻሕፍት ነው፡፡ በዳዊት መዝሙር “ሕግህ ለእግሬ መብራት ለመንገዴም ብርሃን ነው” ብሏል፡፡ አንተ ብሩህ ነህ /Enlightened/ ከሆንክ ሌሎችን ብሩሃን ማድረግ ለመንገዳቸው ብርሃን መስጠት ይቻልሃል፡፡ ይህም በሥራህ፣ በዘመዶችህ እና በጓደኞችህ ሁሉ ይሆናል፡፡

የሥጋ ምኞት እንደ ተኩላ

ሥጋ ተኩላ ሊሆን ይችላል፡፡ ሥጋ ነፍስን፣ ነፍስም ሥጋን እንደሚዋጉ እና እርስ በእርሳቸው እንደሚቀዋወሙ በመጽሐፍ ቅዱስ ተጽፏል፡፡ ይህ ከክርስቶስ መምጣት በፊት ጀምሮ የነበረ ነው፡፡ ክርስቶስ ግን ይህን የሥጋ ኃጢአት ዝንባሌ በእኛ ውስጥ ያሸንፈዋል፤ እንቆጣጠረውም ዘንድ ኃይል ይሰጠናል፡፡ በእርግጥ ኃጢአት እንደተመረዘ ማር ይጣፍጣል፡፡ ከክርስቶስ ጋር ያለች ነፍስ ግን ኃጢአትን መከላከልና መተው ይቻላታል፡፡ በመጽሐፈ ምሳሌ እንደተጻፈ በክርስቶስ “የጠገበች ነፍስ የማር ወለላ /ኃጢአትን/ ትረግጣለች” እንደተባለ፡፡

በኢንተርኔት የሙሰራጭ የዝሙት /pornographic/ ፊልሞችን ጨምሮ ወደ ኃጢአት የሚገፋፉ ብዙ ፈተናዎች እንዳሉባችሁ አውቃለሁ፡፡ እንዲህ ዓይነቱ እንደ ተርታ ነገር እየተለመደ ሲሄድ ዝሙት በሁሉም ቦታ የሚገኝ ተገቢ /normal/ እና ቅቡል /accepted/ እየሆነ ነው፡፡

ነገር ግን ይህ ወደ በለጠ ጥማት ነው የሚመራው፡፡ ስለዚህ በሥጋ ፍላጎት እየተመሩ በዝሙት ከመውደቅ መታቀብ ሕገ እግዚአብሔርን ማክበር ያስፈልጋል፡፡ ሥጋህን ጨዋማ ውሃ ከሰጠኸው ሁሌም ሳይረካ ሲጠማ ይኖራል፡፡ በክርስትና ግን እስከ ጋብቻ ድረስ በንጽሕና መቆየት ይገባል፡፡ እግዚአብሔር ያለበትን ቅዱስ ጋብቻ በእግዚአብሔር ቅድስና ሆነን ራሳችን በንጹሕ የጋብቻና የግንኙነት ቅዱስ ሕይወት እንመራ ዘንድ ይገባናል፡፡

በሥጋ የምትኖሩ ከሆነ በሥጋችሁም ትሞታላችሁ፡፡ ድል አድራጊ ሊያደርግህ የሚችል ብቸኛው አማራጭ ግን መንፈሳዊነት ነው፡፡ በመንፈስ ስትኖር በእርካታና በደስታ ትኖራለህ፡፡ በጭንቀትና በጾታዊ ፍላጎት /sexual desire/ መካከል ጥብቅ ግንኙነት አለ፡፡ በእግዚአብሔር ታምነህና ደስ ተሰኝተህ የምትኖር ከሆ ግን ከዚህ ጭንቀትና በዚህም ከሚመጣው ተገቢ ያልሆነ የሥጋ ፈቃድና ምኞት ነጻ ትሆናለህ፡፡ በጭንቀትና በስህተት፣ በአስቸጋሪ ነገሮች በተከበበ ሕይወት የምትኖር ከሆነ ምንም ይሁን ምን ደስታን የምታገኝበት መንገድ መፈልገህ አይቀርም፡፡ ከኃጢአት የሚመጣው ደስታ ጊዜአዊና ወዲያው ደግሞ የበደለኝነት እና ጸጸት ስሜት የሚያስከትል በመሆኑ እግዚአብሔርን እናመሰግናለን፡፡ ከእግዚአብሔር የሚገኘው ደስታ ግን ዘለዓለማዊ ነው፡፡ በእኛ ያደረገው የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ ነውና፡፡ ይህ ደስታ በሕይወታችን የምንረካበት፣ የኃጢአትና የምኞት መንገዶችን እንዳንፈልግ በማድረግ ሁል ጊዜ በርካታ ያኖረናል፡፡ ለዘለዓለማዊ ሕይወትም እንድንበቃ ያደርገናል፡፡

ለማጠቃለል እነዚህን ተኩላዎች ለመከላከል በዚህ መንገድ እንዝመት

  • እኔነት /Ego/፡- በሕይወታችን እግዚአብሔርን ከፍ ከፍ እናድርግ እኛነታችን ግን ዝቅ ይበል፡፡
  • አእምሮ /Mind/፡- በእግዚአብሔር ቃል አእምሯችንን ብሩህ እናድርግ
  • ሥጋ /Flesh/፡- የክፉ ምኞት ደስታዎችን ከመፈለግ ተቆጥበን “የወይን ወለላን እስክንረግጥ” ድረስ የደስታ እርካታን የምናገኝበትን መንፈሳዊነትን ለማግኘት እንታገል፡፡

ምንጭ፡- ጉባኤ ቃና ጥቅምት ፳፻፬ ዓ.ም

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *