መለያየት- ከክርስቶስ የመለየት ምልክት ነው!

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከእውነተኛ መምህራቸው እና አምላካቸው ክርስቶስ ይልቅ የእርሱን ቃል ባስተማሯቸው ሰዎች ማንነት በመመካት እርስ በርስ ሲከፋፈሉ ለነበሩት የገላትያ ምእመናን፡- “በእምነት በኩል ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁና፤ ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና። አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁ። “ ብሎ ነግሯቸዋል፡፡ (ገላ. 3:27 -28)

ከዚህ መልእክት የምንረዳው እውነት የአንድነታችን መሠረቱ በጥምቀት አማካይነት፣ በእምነት በኩል  የክርስቶስ አካል መሆናችን ነው፡፡  ይህም ሲባል ክርስቲያኖችን ሁሉ አንድ ያደረጋቸው በክርስቶስ ማመናቸውና በእምነት አንድ መሆናቸው እንጂ እንደማንኛውም ሰው በመልክ፣ በባህል፣ ተወልደው ባደጉበት ቦታና በትምህርት ደረጃቸው አንድ ሊሆኑ እንደማይችሉ ይታወቃል፡፡ ይልቁንም ኦርቶዶክሳውያን የሆንን ሁላችን እንደማንኛውም ሰው አስቀድመው በተጠቀሱት በእነዚህ ነገሮች ሁሉ ልንለያይ ብንችልም እንኳን አንድ አምላክ ብለን ስለምናምን፣ ከአንዲት ማኅጸነ ዮርዳኖስ እና ከአንዱ አብራከ መንፈስ ቅዱስ በአንዲት ጥምቀት አማካይነት ተወልደን የአንዱ የእግዚአብሔር ልጆች ስለሆንን፣ የክርስትና ሃይማኖትን በአንድነት ስለምንቀበል፣  በአንዲት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ስለምንኖር አንድ ነን፡፡

እናም በአንዲት ጥምቀት አንዱን ክርስቶስን የለበሱ ክርስቲያኖች በሚለብሷቸው ባህላዊ አልባሳት ምክንያት ሊለያዩ አይችሉም፤ ምድራዊው መገለጫ ከሰማያዊው ሊበልጥባቸው አይችልምና፡፡ በአንድ የፍቅር ገመድ የተሳሰሩ ምእመናን በቋንቋቸው መለያየት ምክንያት አንድነታቸው ሊፈተን አይገባውም፤ የክርስቲያኖች ዋነኛው መግባቢያ ፍቅር እንጂ ቋንቋ አይደለምና፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ በገላትያ ምእመናን አማካይነት ‹‹አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም›› ብሎ ሲመክረን የትውልድ ዜግነታችንን ለማስካድ አይደለም፤ ከተወለድንበት ቦታ ይልቅ ክርስቲያን ሆነን፣ የክርስትናን ምግባራት ሁሉ ፈጽመን ከምንወርሳት ሰማያዊት አገር በእጅጉ እንደሚያንስ ለማጠየቅ እንጂ፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ‹‹ባሪያ ወይም ጨዋ የለም›› ሲልም በወቅቱ ሰዎች እርስ በርሳቸው የተከፋፈሉባቸውን ኩነቶች ከመግለጡም ባሻገር ‹‹በክርስትና ሰው ሁሉ ሰው በመሆኑ ብቻ እኩል ነው እንጂ መበላለጥ አለመኖሩን›› ለማስረዳት ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ በክርስትና የሚገኘው አንድነት ‹‹ወንድ›› ወይም ‹‹ሴት›› የሚባል የጾታ ልዩነትን እንኳን የሚያስረሳ፣ ፍጹም አንድ አካል መሆንን እንደሚያረጋግጥ ሐዋርያው አስረግጦ የተናገረው ተፈጥሮን ለመካድ አይደለም፤ በክርስቶስ አንድ የሆነ ክርስቲያን እንኳንስ በሰው ሰራሽ ነገሮች መለያየት ቀርቶ የተፈጥሮ ድንበር እንኳን ረቂቁን መንፈሳዊ አንድነት ሊያፈርሰው እንደማይቻለው ለማሳየት እንጂ፡፡

በዚሁ መሠረት ‹‹አንድ›› መንጋ የሆነው መንፈሳዊ ቤተሰብ ደግሞ እንደ አንድ ልብ መካሪ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆኖ በፍጹም የአንድነት መንፈስ ጸንቶ ይኖራል እንጂ ዘመን በተቀየረ፣ ወሬ በተወራ ቁጥር በሆነው ባልሆነው ሁሉ አይለያይም፡፡ ሐዋርያው በክርስቲያኖች መካከል አንድነት እንጂ መለያየት ፈጽሞ መኖር እንደሌለበት በተማጽኖ ቃል ‹‹ነገር ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ሁላችሁ አንድ ንግግር እንድትናገሩ በአንድ ልብና በአንድ አሳብም የተባበራችሁ እንድትሆኑ እንጂ መለያየት በመካከላችሁ እንዳይሆን በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እለምናችኋለሁ።›› ሲል የሚናገረውም ለዚሁ ነው (1ቆሮ.1:10)፡፡

ከምንም በላይ ደግሞ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ለክርስቲያኖች የሚሰጠው በአንድነት ሕይወት ውስጥ መሆኑ በሐዋርያት ኑሮ ተረጋግጧል፡- በጽርሐ ጽዮን ‹‹…ሁሉም በአንድ ልብ ሆነው፣ አብረው ሳሉ…›› መንፈስ ቅዱስ እንደወረደላቸውም ቅዱስ መጽሐፋችን ይመሰክራልና (ሥራ. 2፡1)፡፡ ደግሞም፡- «በሰላም ተሳስራችሁ ከመንፈስ ቅዱስ የሚገኘውን ለመጠበቅ ትጉ። በተጠራችሁ ጊዜ ለአንድ ተስፋ እንደተጠራችሁ ሁሉ አንድ አካልና አንድ መንፈስ አለ። እንዲሁም አንድ ጌታ አንድ እምነት እና አንድ ጥምቀት አለ። ደግሞም  ከሁሉ በላይ የሆነ በሁሉም የሚሠራ፤ በሁሉም የሚኖር የሁሉም አባት የሆነ አንድ አምላክ አለ።»  ተብለን እንደተመከርን (ኤፌ4፤3-7) ለአፍታም ቢሆን መዘንጋት የለብንም፡፡

በጋራ በምንጸልየው ጸሎተ ሃይማኖታችንም ውስጥ፡- «ሐዋርያት በሰሯት በአንዲት ቅደስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን» እንላለን፤ የቤተ ክርስቲያን ልዩ መገለጫዋ አንድነቷ ነውና፡፡ ቤተ ክርስቲያን ደግሞ በዋናነት በምድር ያሉት ምእመናንና ተጋድሏቸውን የፈጸሙ ቅዱሳን ኅብረት ወይም አንድነት ናት፡፡ “እንተ በምድር ሥረዊሃ ወበሰማይ አእጹቂሃ..፤ ሥሮቿ በምድር፣ ቅርንጫፎቿም በሰማይ ያሉ” የሚለው የቅዱስ ያሬድ ትምህርትም ለዚህ ትልቅ አስረጂ ነው፡፡

ከምንም በላይ ደግሞ አማናዊውን የክርስቶስን ሥጋና ደም የተቀበሉ ሁሉ የአንዱ ክርስቶስ አካል ብልቶች ሆነዋልና አንድ ናቸው፡፡ “…ይዌልጦሙ በቅጽበት አባላተ ክርስቶስ ይኩኑ፤ በኃይለ ጥበቡ መንክር ወዕጹብ ኪኑ፤ ድንቅና ዕፁብ በሆነ በጥበቡ ኀይል የክርስቶስ አካላት ይሆኑ ዘንድ በቅጽበት ይለውጣቸዋል፡፡” እንዲል መልክአ ቁርባን፡፡ በዚህ መልኩ አንድ የሆኑ ክርስቲያኖች የአንዱ ወይን ግንድ (የክርስቶስ) ልዩ ልዩ ቅርንጫፎች ናቸው እንጂ የተለያዩ ተክሎች አይደሉም (ዮሐ.15፡5)፡፡ እናም በክርስቶስ ክርስቲያኖች የተሰኙ ሁሉ በአንድ አማናዊ እረኛ የሚመሩ አንድ መንጋ ናቸው እንጂ የሚለያዩ አይደሉም (ዮሐ.10፡16)፡፡

እንዲህ ዓይነቱ የአንድነት መንፈስ ደግሞ የሚገኘው ሥጋዊና ደማዊ እውቀት አይደለም፤ ይልቁንም በእምነት እንጂ፡፡ ለዚሁም ነው ‹‹ሁላችን የእግዚአብሔርን ልጅ በማመንና በማወቅ ወደሚገኝ አንድነት፣ ሙሉ ሰውም ወደ መሆን….እስክንደርስ ድረስ…›› ተብሎ የተገለጸው (ኤፌ.4፡12-13)፡፡ ምንጊዜም ክርስቲያን ሆኖ ከምእመናን አንድነት በመነጠል ‹‹ሙሉ›› ሊሆን የሚችል እንደማይኖር በዚህ ተገልጧል፡፡

እኛ ክርስቲያኖች ‹‹አንዲት ቤተ ክርስቲያን›› ብለን የምናምነው በሰማይ ካሉት መላእክትና በአጸደ ነፍስ ካሉ ደቂቀ አዳም ጋር ጭምር አንድነት ያገኘንባትን መንፈሳዊ ኅብረት ነው፡፡ በምድር ካሉና ዕለት ዕለት ከምናያቸው ወንድሞቻችና እኅቶቻችን ጋር ያለንን ኅብረት በማቋረጥ ፈጽሞ ከማናያቸው ከእግዚአብሔር እና ቅዱሳኑ ጋር ኅብረት አለን ብንል ዘበት ይሆናል፤ ‹‹…ያየውን ወንድሙን የማይወድ ያላየውን እግዚአብሔርን ሊወደው እንዴት ይችላል?›› እንዲል (1ዮሐ.4፡20)፡፡

በምንም ሒሳብ አብረውን ከሚያገለግሉና መንግሥተ እግዚአብሔርን ለመውረስ አብረውን ከሚደክሙ ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ኅብረት መነጠል ጤነኛነት ሊሆን አይችልም፡፡ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ በአንድነት ውስጥ የሚሰጥ መሆኑን አስቀድመን ተመልክተናል፤ በተቃራኒው ደግሞ መለያየትን የሚዘራውና አንድነትን በመፈታተን ደስ የሚለው ቢኖር ጠላታችን ሰይጣን ብቻ ነው፡፡ ስለዚህም አንዴ በቋንቋ፣ ሌላ ጊዜ በዘውግ፣ ከዚያ ሲያልፍም በትውልድ መንደር እየተከፋፈሉ መናቆሩ ማንን እንደሚያስደስት ማስተዋል ያስፈልጋል፡፡ ከምንም በላይ ኦርቶዶክሳዊ ቤተሰብ መሆን መቼም ሊበጠስ በማይችል መንፈሳዊ የፍቅር ገመድ እርስ በርስ ሊያስተሳስረን ይገባል፤ ከዚህ የወጣ ክርስትና የለምና፡፡

ምንጭ፡- የጉባኤ ቃና መጽሔት መልእክት (መጋቢት 2010 ዓ.ም)

ቤተ ክርስቲያን ማን ናት? (ክፍል ሁለት)

በመ/ር ኃ/ሚካኤል ብርሃኑ

ቤተ ክርስቲያን ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ እግዚአብሔርን በማመን የጸኑ በሥራቸው የተመሠከረላቸው የእውነተኛ አማኞች ማኅበር ናት፡፡ በምድር ላይ ከተመሠረቱ ማኅበራት ሁሉ ይልቅ አምሳያ የሌላት በእግዚአብሔር ፈቃድ ለእግዚአብሔር ዓላማ በእግዚአብሔር የተመረጡና የተጠሩ ሰዎች ጉባኤ በመሆኗ ከሁሉ የተለየች ተብላለች፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም እንደጻፈው ”እግዚአብሔር አስቀድሞ የወሰናቸውን እነዚህን ደግሞ ጠራቸው፤ የጠራቸውንም እነዚህንም ደግሞ አጸደቃቸው፤ ያጸደቃቸውንም እነዚህን ደግሞ አከበራቸው” (ሮሜ 8÷30) ይላልና፡፡

Read more

ቤተ ክርስቲያን ማን ናት? (ክፍል አንድ)

በመ/ር ኃይለሚካኤል ብርሃኑ

«ቤተ ክርስቲያን» የሚለው ቃል የግእዝ ቃል ሲሆን መጽሐፍ ቅዱስ በመጀመሪያ በተጻፈበት በዕብራይስጥ ቋንቋ «ካሃል» (Qahal) እና «ኤዳህ» (Edah) ተብሎ ይተረጐማል፡፡ ሐዲስ ኪዳን በተጻፈበትና ሰብአ ሊቃናት (Septuagint) ብሉይ ኪዳንን ከዕብራይስጥ ወደ ግሪክኛ በተረጐሙበት ትርጒም አቅሌሲያ (akklesia) በሚል ቃል ተጽፏል፤ ወደ ግእዝ ሲተረጐምም ቤተ ክርስቲያን ተብሎ ተተርጉሟል፡፡

Read more

‹‹ሁሉ በአግባቡ እና በሥርዓቱ ይሁን›› ፩ኛ ቆሮ.፲፬፥፵ (የመጨረሻ ክፍል)

በዲ/ን ታደለ ሲሳይ

ማኅበራዊ የመገናኛ ብዙኀንን ስንጠቀም መልካሙን ከክፉ መለየት፣ ከአስተምህሮአችን ጋር ከሚቃረነው መራቅ ይኖርብናል፡፡ ስለዚህ መንፈሳዊ እና ሃይማኖታዊ መልእክቶችን በማኅበራዊ የመረጃ መረቦች በምናስተላልፍበት ወቅት የሚከተሉትን ሥርዓታዊ አካሄዶች መከተል አለብን፡፡

Read more

‹‹ሁሉ በአግባቡ እና በሥርዓቱ ይሁን›› ፩ኛ ቆሮ.፲፬፥፵ (ክፍል ሁለት)

በዲ/ን ታደለ ሲሳይ

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከጻፋቸው መልእክታት መካከል ለቆሮንቶስ ሰዎች በጻፈው መልእክቱ ላይ እንዳስቀመጠው፡ ‹‹ነገር ግን ሁሉ በአግባብ እና በሥርዓት ይሁን›› 1ኛ ቆሮ. ፲፬፤፵ ብሏል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህንን መልእክት መሠረት አድርጋ  ልጆቿን ታስተምራለች፡፡ በሁሉም የአምልኮ ዘርፍ ሥርዓት መሥርታ ሕግጋተ እግዚአብሔርን እያጣቀሰች ምእመናን በቀና መንገድ እንዲመሩ ታሳስባለች፡፡ ያላመኑትን ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር በማምጣት፤ ያመኑትን በእምነት በማጽናት፤ የጸኑትን ደግሞ በመባረክ እና በመቀደስ ለማያልፈው ዘለዓለማዊ መንግሥት እንዲበቁ የንስሓ ትምህርትን በማስተማር ለንስሓ ሕይወት ታዘጋጃለች፡፡ ከሕግ እና ከሥርዓት ብሎም ከትክክለኛ አስተምህሮዎቿ የሚርቁ፤ የሚሸሹ እና የሚቃወሙትን ደግሞ በምክረ ካህን ታስተምራለች፤ እምቢ አሻፈረኝ ያሉትን ደግሞ  ታወግዛለች፡፡

Read more

‹‹ሁሉ በአግባቡ እና በሥርዓቱ ይሁን›› ፩ኛ ቆሮ.፲፬፥፵ (ክፍል አንድ)

በዲ/ን ታደለ ሲሳይ

ጊዜ ገቢር ለእግዚአብሔር እንዲል እግዚአብሔር ሁሉንም ነገር የሚሠራበት ጊዜ አለው፡፡ ዓለምን ሲፈጥር፣ ሙታንን ሲያስነሣ፣ ድዉያንን ሲፈውስ፣ የተሰደዱትን ሲመልስ፣ ያዘኑትን ሲያረጋጋ እርሱ ጊዜ አለው፡፡ ሁሉንም በጊዜው ውብ አድርጎ ሠራው እንዲል ለሥራው ሁሉ ጊዜ አለው፡፡ የሰው ልጅም በእግዚአብሔር የተፈጠረ፣ እርሱ የሠራለትን ሥርዓት ተከትሎ የሚኖር እንደመሆኑ ለእንቅስቃሴው ሁሉ ጊዜ አለው፡፡ የሰው ልጅ በጨለማ የኖረበት ጊዜ አለው፤ በብርሃን ውስጥ ያለፈበትም ጊዜ አለው፡፡ የሰው ልጅ በድንቁርና የኖረበት ጊዜ አለ፤ በዕውቀት ብርሃን የተመላለሰበት ጊዜ አለ፡፡ የሰው ልጅ በጥበብ ሰክኖ ፈጣሪውን ያመሰገነበት ጊዜም አለው፡፡ የሰው ልጅ ባልተጻፈ ሕግ የተመራበት ጊዜ አለው፤ በተጻፈ ሕግም የተመራበት ጊዜ አለው፡፡

Read more

መናፍቃን የሚስቱባቸውና የሚያስቱባቸው መንገዶች (የመጨረሻ ክፍል)

…በዳዊት አብርሃም…

የግል ሐሳብ በመጽሐፍ ቅዱስ ድጋፍ እንዲያገኝ መጣር

ትክክለኛ የክርስቲያን ነገረ መለኮት ምንጩ መጽሐፍ ቅዱስ ነው፡፡ አንዳንዶች ግን የሚፈልጉትን ነገረ መለኮት በራሳቸው ፈልስፈው ሲያበቁ የግል አሳባቸው በመጽሐፍ ቅዱስ ተደጋፊ እንዲሆን ጥቅሶችን ማፈላለግ ይጀምራሉ፡፡ የእነርሱን ሐሳብ  የሚደግም ወይም የሚደግፍ የሚመስል ቃል ሲያገኙ ደስ ተሰኝተው ያንን ያገኙትን አንድ ጥቅስ ደጋግመው ይጠቅሳሉ፡፡ የነርሱን ሐሳብ የሚቃወም ጥቅስ ሲያጋጥማቸው ደግሞ ጥቅሱን እነርሱ ወደሚፈ ልጉት ሐሳብ  ለማምጣት ይጥራሉ፡፡ ማርቲን ሉተር አሳቡን የተቃወመበትን የያዕቆብ መልእክት ‹‹ገለባ›› ብሎ በግልጽ ከማጣጣል ውጪ ብዙ አልተቸገረም፡፡ የእርሱ ተከታዮች የሆኑት ግን እንደ መምህራቸው ቅዱስ ቃሉን ሰድቦ ማለፍ እንደማያዋጣ ገብቷቸዋል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ሐሳባቸውን ለመቀየርና ከመጽሐፍ ቅዱስ የተገኘውን ነገረ መለኮት ለመቀበልም አልፈለጉም፡፡ ለዚህ አጣብቂኝ እንደ መፍትሔ የተጠቀሙት የሐዋርያው ያዕቆብን መልእክት እንዴት ቢተረጐም የነርሱን ሐሳብ ሊደግፍ እንደሚችል በማሰብ ቃሉን ወደራሳቸው ግላዊ ሐሳብ  ማምጣት ነው፡፡ ይህንንም ስልት ተጠቅመው እንደሚከተለው ደመደሙ፡፡

Read more

መናፍቃን የሚስቱባቸውና የሚያስቱባቸው መንገዶች (አራተኛ ክፍል)

በዳዊት አብርሃም

ጥቅሱን ካጠቃላዩ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ነገረ መለኮት (Biblical Theology) አንጻር ለማየት አለመቻል

 ትክክለኛ ትምህርተ መለኮት ጥቅሶችን በዘፈቀደ መደርደር አይደለም፡፡ የተደረደሩት ጥቅሶች ከጥንት ከሐዋርያት ጀምሮ በመጣ አመክንዮ ተያይዘው ትርጉም የሚያስገኙበት ዘዴ አለ፡፡ ይህም ትውፊት ይባላል፡፡ ትውፊት የሌላቸው አብያተ ክርስቲያናት የሉም፡፡ ትውፊትን የሚያጥላሉት ፕሮቴስታንቶች እንኳ ከአውሮፓ የተሐድሶ አባቶች ከነማርቲን ሉተር የሚነሣ የአስትምህሮ ቅብብሎሽ አላቸው፡፡ ምንም አስተምህሯቸውን በጣም የሚለውጡ ክስተቶች እየተፈጠሩ ከነርሱ መካከል ወግ አጥባቂዎች የሆኑት እስኪደነግጡ ቢደርሱም መለዋወጥን የሚፈቅድ ሥርዓት ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ የራሳቸው ትውፊት ነው፡፡

Read more

መናፍቃን የሚስቱባቸውና የሚያስቱባቸው መንገዶች (ሦስተኛ ክፍል)

…በዳዊት አብርሃም…

ጥቅሱን ከዳራው መነጠል

መጽሐፍ ቅዱስ ምንም በመንፈስ ቅዱስ አነሳሽነት የተጻፈ ቢሆንም የተጻፈው ግን በሰዎች ነው፡፡ የተጻፈውም ለሰዎች ነው፤ የተጻፈበት ቋንቋ፣ ቦታና የተወሰነ ጊዜ አለ፡፡ ስለዚህ የአጻጻፉን ባህል፣ በዘመኑ የነበረውን ኹኔታ፣ መጽሐፉ የተጻፈበትን ዓላማ በማወቅና በዚያም ውስጥ የጥቅሱን ትክክለኛ መልእክት በመረዳት መጥቀስ እንጂ እንደመሰለ አንሥቶ መጥቀስ ስሕተት ላይ ይጥላል፡፡

Read more

መናፍቃን የሚስቱባቸውና የሚያስቱባቸው መንገዶች (ክፍል ሁለት)

በዳዊት አብርሃም

  1. ጥቅሱን ከዓውዱ ነጥሎ መጥቀስ

አንድን ጥቅስ በተሟላ መልኩ በትክክል ጠቅሶ ድምዳሜ ላይ መድረስ ትክክል ባይሆን እንኳ የተሻለ ነገር አያጣውም፡፡ ስሕተቱን የከፋ፣ የስሕተት ስሕተት የሚያደርገው አንዲቷን ጥቅስ ቆንጽለው ሲጠቅሷት ነው፡፡ ብዙዎች መናፍቃን አንድን ጥቅስ አሟልተው ለመረዳት ጥቂት መስመሮችን ከፍ ብለው እንዲሁም ከጠቀሱት ጥቅስ ቀጥሎ ያሉትን ጥቂት ዐረፍተ ነገሮች ጨምረው ለመመልከት ቢሞክሩ ድምዳሜያቸውን ርግፍ አድርገው መተው ወይም የሚያሰሙትን ተቃውሞ ባልደገሙት ነበር፡፡

ይህንም በሚቀጥሉት ስለ ነገረ ድኅነት ከተጻፉት ጥቅሶች አንጻር እንመልከት፡፡ “ጸጋው በእምነት አድኖአችኋልና፤ ይህም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው እንጂ ከእናንተ አይደለም፡፡” (ኤፌ2፡8-9) የዚህ ጥቅስ መልእክት በጣም ግልጽ ይመስላል፤ ጥቅሱ ‹ሥራ አያስፈልግም፣ እምነትና ጸጋ ብቻቸውን ለመዳን በቂ ናቸው› የሚል መልእክት የያዘ መስሎ ይታያል፡፡ ግን ሳንቸኩል አንድ ቁጥር ወረድ ብለን ንባባችንን ብንቀጥል እንዲህ የሚል እገኛለን፡፡ “እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን።” (ኤፌ2፡10)

Read more