‹‹ሁሉ በአግባቡ እና በሥርዓቱ ይሁን›› ፩ኛ ቆሮ.፲፬፥፵ (ክፍል ሁለት)
በዲ/ን ታደለ ሲሳይ
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ከጻፋቸው መልእክታት መካከል ለቆሮንቶስ ሰዎች በጻፈው መልእክቱ ላይ እንዳስቀመጠው፡ ‹‹ነገር ግን ሁሉ በአግባብ እና በሥርዓት ይሁን›› 1ኛ ቆሮ. ፲፬፤፵ ብሏል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህንን መልእክት መሠረት አድርጋ ልጆቿን ታስተምራለች፡፡ በሁሉም የአምልኮ ዘርፍ ሥርዓት መሥርታ ሕግጋተ እግዚአብሔርን እያጣቀሰች ምእመናን በቀና መንገድ እንዲመሩ ታሳስባለች፡፡ ያላመኑትን ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር በማምጣት፤ ያመኑትን በእምነት በማጽናት፤ የጸኑትን ደግሞ በመባረክ እና በመቀደስ ለማያልፈው ዘለዓለማዊ መንግሥት እንዲበቁ የንስሓ ትምህርትን በማስተማር ለንስሓ ሕይወት ታዘጋጃለች፡፡ ከሕግ እና ከሥርዓት ብሎም ከትክክለኛ አስተምህሮዎቿ የሚርቁ፤ የሚሸሹ እና የሚቃወሙትን ደግሞ በምክረ ካህን ታስተምራለች፤ እምቢ አሻፈረኝ ያሉትን ደግሞ ታወግዛለች፡፡