መናፍቃን የሚስቱባቸውና የሚያስቱባቸው መንገዶች (አራተኛ ክፍል)
በዳዊት አብርሃም
ጥቅሱን ካጠቃላዩ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ነገረ መለኮት (Biblical Theology) አንጻር ለማየት አለመቻል
ትክክለኛ ትምህርተ መለኮት ጥቅሶችን በዘፈቀደ መደርደር አይደለም፡፡ የተደረደሩት ጥቅሶች ከጥንት ከሐዋርያት ጀምሮ በመጣ አመክንዮ ተያይዘው ትርጉም የሚያስገኙበት ዘዴ አለ፡፡ ይህም ትውፊት ይባላል፡፡ ትውፊት የሌላቸው አብያተ ክርስቲያናት የሉም፡፡ ትውፊትን የሚያጥላሉት ፕሮቴስታንቶች እንኳ ከአውሮፓ የተሐድሶ አባቶች ከነማርቲን ሉተር የሚነሣ የአስትምህሮ ቅብብሎሽ አላቸው፡፡ ምንም አስተምህሯቸውን በጣም የሚለውጡ ክስተቶች እየተፈጠሩ ከነርሱ መካከል ወግ አጥባቂዎች የሆኑት እስኪደነግጡ ቢደርሱም መለዋወጥን የሚፈቅድ ሥርዓት ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ የራሳቸው ትውፊት ነው፡፡