የእግዚአብሔር ፈቃድ

ክፍል ሁለት

በመ/ር ተርቢኖስ ቶሎሳ

ሰው ወደ ክርስትናው ዓለም ሲገባ የራሱን ፈቃድ ያወርድና የጌታውን ፈቃድ ተሸክሞ ወደ ቀራንዮ ሲጓዝ ይኖራል።  እንደ ሰውኛ የግል ስሜትና የግል ፈቃድ ቀራንዮ አያደርስም። መድኅነ ዓለም ክርስቶስ ያን ወጣት “ወደ ሕይወት መግባት ብትወድ ትእዛዛትን ጠብቅ … ያለህን ሸጠህ ለድሆች ስጥ” ማለቱ ለምን ይመስላችኋል? ሰው በእግዚአብሔር ፈቃድ እንጂ በሰውነቱ ፈቃድ መንግሥቱን እንደማይወርስ ለማጠየቅ ነው።

ቀሬናዊው ስምዖን የጌታውን መስቀል ተሸክሞ ያንን አስቸጋሪ ጎዳና የተጓዘው ቤተ ክርስቲያኒቱ በጌታዋ ፈቃድ ትኖር ዘንድ እንዳላት ለማሳየት እንጂ ጌታውን ደክሞት ሊያሳርፍ አልነበረም። ስለዚህ የክርስትና ጉዟችን እንደ ሰው ፈቃድ ሰውን እናስደስት ዘንድ ሳይሆን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ መንግሥቱን እንወረስ ዘንድ ነው።  ለዚህም ነው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ብሎ የሚመክረን፦ “የእግዚአብሔርን ፈቃድ እንደሚያደርጉ እንደ ክርስቶስ ባሪያዎች እንጂ ለሰው ደስ እንደምታሰኙ ለታይታ የምትገዙ አትሁኑ!” በማለት። (ኤፌ. ፮፥፮)

ባሪያ ለራሱ ፈቃድ የለውም፤ ፈቃዱ ሁሉ ለጌታው ነው። የቆመን ቁረጥ፣ የወደቀን ፍለጥ ቢል ለጌታ ይገባዋል፤ ባሪያ በጌታው ሥር ይኖራልና። ሐዋርያውም “እንደ ክርስቶስ ባሪያዎች” ማለቱ በፈቃዱ ጥላ ሥር የሚኖሩትን ለመጠቆም ነበር። ስለዚህ በበጎ ፈቃዱ ውስጥ የሰው ልጅ ታላቅ ድርሻ አለው። ድርሻውም የጌታውን ፈቃድ በጸሎት መጠየቅ ነው። በክርስትና አስተምህሮ ፈቃደ እግዚአብሔርን ጸሎት አብዝቶ ይገልጠዋል። “ለምኑ ይሰጣችኋል” እንደተባለ። ስለዚህ ጸሎት የፈቃዱ መገለጫ እንደሆነ በዚህ እናውቃለን።

የሰውን ጉድለትና ምልዓት ይነግሩት ዘንድ የማይሻ ጌታ ሆኖ ሳለ ነገር ግን በጸሎት እንጠይቀው ዘንድ ይወዳል። ምክንያቱ ደግሞ ጸሎት የፈቃዱ መገለጫ ስለሆነ ነው። ለመከሩ ሠራተኛ እንደሚያስፈልገው ያወቀው ፍጥረት አመልክቶት አይደለም። በባሕርይው ዕውቀት እንጂ። “እንግዲህ የመከሩን ጌታ ወደ መከሩ ሠራተኞችን እንዲልክ ለምኑት” ብሎ የሚናገር ራሱ የመከሩ ጌታ ነው። (ዮሐ. ፪፥፳፭) ለገዛ መከሩ ግን በጸሎት እንዲጠየቅ ሐዋርያትን ያነሣሣል።  ይህም የሆነው በፈቃዱ ውስጥ የሰው ልጅ ድርሻ እንዳለው ለማስረዳት ነው።

ስለ ደቀ መዝሙሩ ኤጳፍራ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በተናገረበት ክፍል “በእግዚአብሔር ፈቃድ ሁሉ ተረድታችሁና ፍጹማን ሆናችሁ እንድትቆሙ ስለ እናንተ በጸሎቱ ይጋደላል።” ይላል። (ቆላ. ፬፥፳፪) የእግዚአብሔር ፈቃድ በረድኤትነት የሚገለጠው ኤጳፍራ በጸሎት ሲጋደል እንደሆነ መመዝገቡ በፈቃደ እግዚአብሔር ዘንድ ያለውን የሰውን ልጅ ድርሻ ጠንቅቆ የሚያስረዳ ዐውድ ነው። ድርሻ አለው ማለት ግን ፈቃድን ይወስናል፣ ፈቃድን ይሰጣል፣ ያስረዝማል፣ ያሳጥራል ማለት ሳይሆን ይህ ፈቃዱ እንዲሰጠው በጸሎት ለእግዚአብሔር ምሕረት ምክንያት ይሆናል ማለት ነው። “ስለዚህ እኛ ደግሞ ይህን ከሰማንበት ቀን ጀምረን የፈቃዱ ዕውቀት መንፈሳዊ ጥበብንና አእምሮን ሁሉ እንዲሞላባችሁ እየለመንን ስለ እናንተ ጸሎትን አልተውንም።”  እንዲል (ቆላ. ፩፥፱) ፈቃዱ የነገሮች ሁሉ በር ነውና ለዚህ ነው ጸሎት ያስፈለገው።

በክርስትና ሕይወት መኖር ማለት እንደ ፈቃዱ እንኖር ዘንድ ተጠርተናልና በተፈጸመው ፈቃድ እርሱን እያመሰገንን ባልተፈጸመው ፈቃድ የቀረንን እየጠየቅን መኖር ማለት ነው።  ይህ ሲሆን የእግዚአብሔርን ፈቃድ እንዴት እናውቃለን? ቢሉ እግዚአብሔር የቀደመ ፈቃዱን በነቢያት፣ በካህናት፣ በራእይ፣ በትንቢት፣ በምሳሌ፣ በሱባኤ ገልጧል።

በአዲስ ኪዳን ደግሞ የማይፈጸም ፈቃዱን በአንድ ልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ገልጦልናል። እርሱም እንዲህ ብሎ ነገረን። “ዓለምን ላድን እንጂ በዓለም ልፈርድ አልመጣሁም…” ። (ዮሐ. ፲፪፥፵፯) ክርስቶስ አስቀድሞ መጾሙ መጾማችን ፈቃዱ እንደሆነ ሊያስረዳን ነበር።  ወደ ገዳም መግባቱም ገዳማውያኑ በግብር ይመስሉት ዘንድ ፈቃዱን እየሰጣቸው ነበር። ወደ ዶኪማስ ቤት መሄዱም በትዳር ተወስነው፣ ልጅ ወልደው፣ ጎጆ ቀልሰው ለሚኖሩ ሰዎች ኑሯቸውን ባርኮ ለመስጠት ነበር። ሥጋውና ደሙ፣ እናቱና መስቀሉ ፈቃዱን ያወቅንባቸው መገለጫዎቹ ናቸው።  ይበልጥ ደግሞ ፈቃዱን ለማወቅም ሆነ ለመጠየቅ እግዚአብሔርን በጾምና በጸሎት አብዝቶ መቅረብ፣ በበጎ ምግባር መጽናት፣ ሰውነትን ከኃጢአት አንጽቶ በፊቱ ለምሕረት መቆም፣ ወደ ቤተ ክርስቲያን በተሰበረ ልቡና፣ በቀና ሕሊና መመላለስ ፈቃዱን የምናውቅባቸውና ፈቃዱን የምንፈጽምባቸው መንገዶች ናቸው፡፡

ስለ ፈቃደ እግዚአብሔር ስናጠና ልናድርጋቸው የሚገቡን ጥንቃቄዎች

ፈቃደ እግዚአብሔርን ስንጠይቅ ኃጢአታችንን ተናዝዘን ከኃጢአት ነጻ ልንሆን ይገባል። ከዚያም ቀጥሎ ስሜቶቻችን ሁሉ ሊያሳስቱን ስለሚችሉ ጥንቃቄ ልናድርግ ይገባል። የምንፈጽመው ድርጊት ሁሉ “እግዚአብሔርን ያስደስተዋልን?” ብለን ልንጠይቅ ይገባል። መልካምና ክፉ ነገሮችም ወደ እግዚአብሔር ፈቃድ ሊመሩን ስለሚችሉ ቶሎ ከመማረርና ቶሎ ከመደሰት ልንቆጠብ ይገባል። “ወያመጽእ እግዚአብሔር ደዌ በእንተ ጥኢናሃ ለነፍስ፤ ስለ ነፍስ ድኅነት እግዚአብሔር በሥጋ ላይ ደዌን ያመጣል” እንደተባለ (ማር ይስ. ፪) ሁኔታዎችም ሁሉ ከእግዚአብሔር ፈቃድ ሊያወጡን ይችላሉ። “በእስያ ስለ ደረሰብን መከራ ወንድሞቻችን ሆይ ታውቁ ዘንድ እንዳለንና ስለ ሕይወታችን እንኳ ተስፋ እስክንቆርጥ ድረስ ከዐቅማችን በላይ ያለ ልክ ከብዶን ነበር። ”፪ኛ ቆሮ. ፩፥፰-፱)።

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በዚህ ብቻ ሳያበቃ “አይሁድ አንድ ሲጓድል አርባ ግርፋት አምስት ጊዜ ገረፉኝ፣ ሦስት ጊዜ በበትር ተመታሁ፣ አንድ ጊዜ በድንጋይ ተወገርኩ፣ መርከቤ ሦስት ጊዜ ተሰበረ፤ ሌሊትና ቀን በባሕር ውስጥ ኖርኩ፣ ብዙ ጊዜ በመንገድ ሄድኩ፡፡ በወንዝ ፍርሃት፣ በወንበዴዎች ፍርሃት፣ በወገኔ በኩል ፍርሃት፣ በአሕዛብ በኩል ፍርሃት፣ በከተማ ፍርሃት፣ በምድረ በዳ ፍርሃት፣ በውሸተኞች ወንድሞች በኩል ፍርሃት ነበረብኝ። በድካምና በጥረት ብዙ ጊዜም እንቅልፍ በማጣት በረሃብና በጥም በብርድና በራቁትነት ነበርኩ።” ይላል። (፪ኛቆሮ. ፲፩፥፳፬)

ስለዚህ ቅዱስ ጳውሎስ ይህ ሁሉ መከራና እንግልት በፈቃደ እግዚአብሔር መሆኑን ስለ ዐወቀና ስለተረዳ መከራውን ሳይሰቀቅ ጸንቷል። መከራም ሆነ ደስታ በፈቃደ እግዚአብሔር ሊሆን ስለሚችል በሁሉ ልንታገሥ እና በጸሎት ልንጸና ይገባል። በጥቅሉ የእግዚአብሔር ፈቃዱ በምልዐት ባይታወቅም ባወቅነውና በተረዳነው መጠን የሰው ልጅ ስሙን ጠርቶ ክብሩን ወርሶ እንዲኖር ነው።

የእግዚአብሔርን ፈቃድ ዐውቀን፣ በፈቃዱም ኖረን፣ ስሙን ጠርተን፣ ክብሩን ወርሰን እንድንኖር መልካም ፈቃዱ ይሁንልን። አሜን።

ስብሐት ለእግዚአብሔር ለዘገብረ ሰማየ ወምድረ!

የእግዚአብሔር ፈቃድ

ክፍል አንድ

በመ/ር ተርቢኖስ ቶሎሳ

የሰው ልጅ በአንድ ጸጋ ብቻ አይወሰንም። አንድ ጸጋ ብቻውን የእግዚአብሔርን ሰጭነት የሰውን ልጅ ተቀባይነት ቢገልጥ እንጂ ወደ መንግሥተ ሰማያት ለሚደረገው ጉዞ ዋና አይሆንም።

ይህን ለማየት በብሉይ ኪዳን ዘመን እስራኤላውያን ወደ ተስፋይቱ ምድር ያደረጉትን ጉዞ በቀላሉ መመልከት በቂ ነው። እግዚአብሔር አምላካችን “ባርነት ይብቃ” ብሎ ሙሴን በመሪነት ወደ ግብፅ ላከ።  ሙሴም ብቻውን በቂ አይደለምና “አሮን እኁከ ይኩንከ አፈ፤ አሮን ወንድምህ አፍ ይሁንህ” ብሎ ሰጠው። ከሚገጥመውም ፈተና ይታደገውና ይጠብቀው ዘንድም መልአኩን ላከለት።

ለዚህ መንገደኛ ሕዝብ ከደመና ላይ የሚወርደው መና፣ ከዐለት የሚፈልቀው ውኃ፣ ከላይ፣ ግራና ቀኝ የሚጋርደው ደመና፣ ሕዝቡን የሚያጽናኑ ሌዋውያን፣ የሚያስታርቁ ካህናት፣ ምስጋናው የማይታጣባት ደብተራ ኦሪት፣ ለኃጢአት ስርየት የሚሆነው መሥዋዕቱና የመሳሰሉት ሁሉ ከላይ የተሰጡት ጸጋዎቹ ናቸው።

በፍጻሜው ምድረ ርስትን ብቻ በሚያስገኝ በዚህ አስጨናቂ ጉዞ ውስጥ እግዚአብሔር ሙሴን ብቻ ጸጋ አድርጎ አለመስጠቱ በብዙ ሀብታት ተውባና ደምቃ ወደ ዘለዓለማዊት መንግሥቱ የምትጓዘዋ ቤተ ክርስቲያን በብዙ ጸጋ የምታገኘውን ሀብት ለማሳየት ነው።  “ያመነ የተጠመቀ ይድናል” ስለተባለች በጥምቀት ጸጋነት ብቻ ለጽድቁ እበቃለሁ አትልም። (ማር. ፲፮÷፲፮) እንዲሁም “ሥዬን የበላ፣ ደሜንም የጠጣ፣ የዘለዓለም ሕይወት አለው” ስለተባለም በሥጋውና በደሙ ብቻ እጸድቃለሁ አትልም። “በእምነት ጽደቁ” ስለተባለ ምግባር ለምኔ አትልም። ለጽድቋ እምነት፣ ክህነት(የሚናዝዝ፣ የሚያጠምቅ፣ የሚያቆርብ)፣ ጥምቀት፣ ሜሮን፣ ቁርባንና ምግባር ጸጋዎቿ እንደሆኑ ታምናለች።

በጉዞዋ ፈርዖን ይነሣባታል፤ ከኋላዋ አእላፍ ፈታኞች ይከተሏታል። ነገር ግን አይቀድሟትም። መከተላቸውም እስከ ኤርትራ ባሕር ድረስ ነውና ለተሻገረ ሕዝብ ጭንቅ አይሆኑም። በእርግጥ ከግብፅ እስከ ኤርትራ ድረስ ያለው ጉዞ ከኤርትራ እስከ ምድረ ርስት ድረስ ካለው ጉዞ ጋር ሲነጻጸር እጅጉን አስጨናቂ ነው። በዚህ ጉዞ የሙሴ ፍጹም መሪነት ጎልቶ አልተገለጠም፤ የምድሪቱም ዓቅም ገና አልተስተዋለም፣ የግብፃውያን ፉከራና ግርግርታም እስከ ባሕረ ኤርትራ ድረስ ፈጽሞ አልታጣም። የጠላት ኮቴም በቅርብ ይከተል ነበር። የፈርዖንም ተስፋ ገና አልተቋጨም፣ ከኤርትራ በኋላ ግን አዲስ ታሪክ ይጀመራል። ፈርዖንም አይጨብጥም፣ ኤርትራም፤ አታሰጥምም።

በዚህ ዐውድ ፈርዖን ዲያብሎስ ነው፡፡ ኤርትራም ሲኦል ናት።  ከኤርትራ ማዶ ማርያም እኅተ ሙሴ ለምስጋና ተሰልፋለች። እውነትም አመስጋኟ ማርያም የምትገኘው ከኤርትራ በኋላ ነውና እንደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም “ተዐብዮ ነፍስየ ለእግዚአብሔር፤ ነፍሴ እግዚአብሔርን ታከብረዋለች” አለች። ከግብፅ እስከ ኤርትራ የተደረገው ጉዞም ከጓዳ በተዘጋጀ ስንቅ ነበር።  ከኤርትራ በኋላ ግን ውኃው ከዐለት ይፈልቃል፤ መናውም ከደመና ይወርዳል።

ነገር ግን ቤተ ክርስቲያኒቱን ክርስቶስ በቤዛነቱ ከተቤዣት በኋላ ለመንገዷ ስንቅ ይሆኗት ዘንድ ቤት ያፈራቸውን ኮርማውንና ጠቦቱን መሥዋዕት አድርጋ አታቀርብም።  ከሰማይ የወረደላትን መና (ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ የቆረሰላትን ሥጋውንና ያፈሰሰላትን ደሙን) መሥዋዕት አድርጋ ታቀርባለች አንጂ።

ተናዳፊውን እባብ አልፈው፣ የበለዓምን ርግማን ተራምደው፣ ዮርዳኖስን ተሻግረው፣ ግንቡን አፈራርሰው፣ ጠላት ደምስሰው ርስታቸውን ገንዘብ ማድረግ እንደ ሥጋ ሲታይ ለአእላፈ እስራኤል አይወጡት ተራራ ነው። በብሉይ ኪዳኑ ለነበረው ምድረ ርስት መውረስ ምክንያቱ የእግዚአብሔር ፈቃድ ነው። ሆኖም ቤተ ክርስቲያኒቱ ይህን ሁሉ ውጣ ውረድ የምታልፍ ናትና የእስራኤል ጉዞ ምድረ ርስትን በመውረስ ይደማደማል።

እግዚአብሔር አምላካችን ገዥ እና መጋቢ አምላክ ስለሆነ በባሕርይ ለሚገዛው ፍጥረት ፈቃዱን ያለ ወሰን ሰጥቷል። የምድር ወሰን ስፋት፣ የሰማይ ምጡቅ ጽናት ያለ መናወጽ የሚኖረው በፈቃዱ ተራዳኢነት ነው። የኦሪት ዘፍጥረት ጸሐፊው ሙሴ “በቀዳሚ ገብረ እግዚአብሔር ሰማየ ወምድረ፤ በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይና ምድርን ፈጠረ” ሲል የሰማይና የምድር መፈጠር የእግዚአብሔር ፈቃዱም እንደሆነ ለማጠየቅ ነው። (ዘፍ. ፩፥፩) ለዚህም ነው በፈቃዱ በስድስት ቀን የፈጠረውን ፍጥረት እስከ ዓለም ፍጻሜ በፈቃዱ ሲመግብ የሚኖረው።

የእግዚአብሔር ፈቃድ የሰው ልጅ በአዳም የሕይወት ጉዞ በኩል በገነት ይኖርለት ዘንድ ነው። “… ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህ” ብሎ አዳምን ማስጠንቀቁ በሕይወት ይኖርለት ዘንድ እንጂ አስጨናቂ ስለሆነ አይደለም። (ዘፍ. ፪÷፲፯)

ቃኤልን “ለምንት ቀተልኮ ለአቤል እኍከ፤ አቤል ወንድምህን ለምን ገደልኸው” ብሎ እግዚአብሔር መጠየቁ አቤል ይሞትበት ዘንድ ስለማይሻ ነው። አቤል በአባቱ በኩል የሞት ሞትን ትሞታለህ የሚል የሞት ዕዳ ቢተላለፍበትም ይህ ፍርድ ግን ቃኤልን ከባለ ዕዳነት አልታደገውም። በአጠቃላይ የሰው ልጅ እንደጠፋ ይቀር ዘንድ የእግዚአብሔር ፈቃድ አልነበረም። (ዘፍ. ፬፧፱)

ፈቃዱ ወደ ቀደመ ርስቱ ገነት ወደ ነበረበት ሕይወት ይመለስለት ዘንድ ነውና፣ ብዙ ምሳሌያትን አስመሰለ፤ ቁጥራቸው የበዙ ነቢያትን በኢየሩሳሌምና በሰማርያ አሰማራ፤ ሱባኤ አስቆጠረ፤ ተስፋውን አስነገረ፤ ለኦሪታውያኑ ምልክት አድርጎ ግዝረትን ሰጠ፣ አድርግ አታድርግ ብሎ ትእዛዙን አጸና፤ ኦሪትን በሕግነት፣ ካህናትን በአባትነት ሰጠ።

ይህ ሁሉ በአዲስ ኪዳን፣ ለሚፈጸመው ድኅነት ጥላ ይሆን ዘንድ እና የማዳኑን ተስፋ በልቡና ለማጽናት ነበር። የዘመኑ ፍጻሜም ሲደርስ የአዳም መዳን ፈቃዱ ነውና መጥቶ አዳነን። ” እስመ በፈቃዱ ወበሥምረተ አቡሁ መጽአ ወአድኃነነ” እንዲል ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴ ማርያም ድርሰቱ።  አስቀድሞም “ኃጢአታችሁ እንደ አለላ ብትሆን እንደ አመዳይ ትነጻለች፤ እንደ ደምም ብትቀላ እንደ ባዘቶ ትጠራለች” እያለ በተስፋ ማጽናናቱ ይመጣ ዘንድ ያለውን ድኅነት ከደጅ እንዳለ ለማጠየቅ ነበር። (ኢሳ. ፩፧፲፰)

የሰው ልጅ መዳን አቻ የለሽ ፈቃዱ ነውና አዳምን የመሰለ ሌላ ልፍጠር ሳይል በደለኛውን አዳም የንስሓ ጊዜ ሰጥቶ ወደ ራሱ መለሰው። አድንሃለሁ እንዳለውም ሰው በመሆን ፈቃዱን ፈጸመ።  የእግዚአብሔር ፈቃድ እንደ ንጉሥ ትእዛዝ ነው፤ ረዘመ ብለው አያሳጥሩትም፤ አጠረ ብለውም አያስረዝሙትም። ፈቃዱም “ድንገት የወለደው፣ ዘመን ያወረደው” አይደለም። መታመን የእግዚአብሔር ፈቃድ ነውና።

እርሱን እኛ ባናምነውም፣ ብናምነውም መታመኑ አይለወጥም፤ አይናወጥም። “ባናምነውም እርሱ የታመነ ሆኖ ይኖራል” መባሉ ለዚህ ነው። (፪ኛጢሞ. ፪÷፲፫) ስለዚህ ፈቃዱ የጸና ነው የሚባለው ከዚህ የተነሣ ነው። የጸና ነው ማለትም ምክንያት ሳይከለክለው ይፈጽማል ማለት ነው። “እኔ አምላክ ነኝና፣ ሌላም የለምና የቀድሞውንና የጥንቱን ነገር አስቡ፡፡ እኔ እግዚአብሔር ነኝ እንደ እኔም ያለ ማንም የለም፡፡ በመጀመሪያ መጨረሻውን፣ ከጥንትም ያልተደረገውን እናገራለሁ፤ ምክሬ ትጸናለች፣ የመከርሁትንም ሁሉ አደርጋለሁ።” እንዲል (ኢሳ.  ፵፮፥፱-፲)

ከመጀመሪያ መጨረሻውን የሚናገር እርሱና ከእርሱ የሆነ ብቻ ነው። የፈቃዱ ጥንቱ መጀመሪያ ቢሆንም ፈጻሜ ፈቃድነቱ ግን የሚታወቀው መጨረሻ ነው። ስለዚህ የእግዚአብሔር ፈቃድ በፍጥረት ፈቃድና ዓላማ አይለካምና ከመጀመሪያ የመጨረሻውን የሚናገር እርሱ ነው። አንዳች ሕጸጽ የሌለበትና ምክንያት የሚከለክለው ፈቃድ የለውምና “ፈቃዴን ሁሉ እፈጽማለሁ” አለ። በፈታሒነቱ ቀዳማዊ አዳም የሞት ሞትን ጽዋዕ ይጎነጭ ዘንድ ፈቃዱ ነበርና ከአዳም ጀምሮ እስከ ሙሴ ድረስ ሞት ነገሠ።  (ሮሜ. ፭፥፲፬) አዳም ይድንም ዘንድ ፈቃዱ ነውና አንድያ ልጁን አብ ለሞት አሳልፎ ሰጠ። (ዮሐ. ፫፥፲፮)

በሰብአ ትካት ዘመን እግዚአብሔር ያን አመጸኛ ትውልድ ማጥፋት፣ ኖኅንም እስከ ልጆቹ ማዳን   ፈቃዱ ነበርና ኖኅንና ቤተሰቡን በምሕረቱ አተረፈ፤ ሰብአ ትካትን በመዓቱ ቀሰፈ። (ዘፍ. ፯፥፳፩) አብርሃምን እንደ ሰማይ ከዋክብት፣ እንደ ባሕር አሸዋ ማብዛት የማይለወጥ ፈቃዱ ነውና ይህንንም አደረገለት። ስለዚህ የእግዚአብሔር ፈቃድ ተከፍሎ የሚፈጸም፣ ተከፍሎም የማይፈጸም ነው ልንለው አንችልም።

የሰው ልጅ ፈቃድ አለው። ይህን ፈቃዱን “ነጻ ፈቃድ” ልንለው እንችላለን። ባለፈቃዱ ሰውም ፈቃዱን ይፈጽምበት ዘንድ ጊዜና ሁኔታ ያጣል።  በዚህም ተከፍሎ ያለበት ፈቃድ ሕልም ብቻ ሆኖ ይመክናል። ምክንያቱም ተፈጥሮው የምክንያት ጥገኛ ስለሆነ። ለመገለጡ እንጂ ለመኖሩ ምክንያት የሌለው እግዚአብሔር ግን የወደደውን ያደርግ ዘንድ ይቻለዋል።

“በከመ ፈቀደ ይገብር ወበከመ ሐለየ ይፌጽም፤ እንደ አሰበው ያደርጋል፣ እንደ ፈቃዱም ይፈጽማል” እንደተባለ። በሌላም ስፍራ “በምድርም የሚኖሩ ሁሉ እንደ ኢምንት ይቆጠራሉ፤ በሰማይም ሠራዊት በምድርም ላይ በሚኖሩ መካከል እንደ ፈቃዱ ያደርጋል፤ እጁንም የሚቃወማት ወይም ‘ምን ታደርጋለህ?’ የሚለው የለም” ተብሏል።  (ዳን. ፬፥፴፭) ይህን ወሰን የለሽና እንዲህ ነው ተብሎ የማይደረስበትን በጎ ፈቃዱን ነው “አባታችን ሆይ በሰማያት የምትኖር ስምህ ይቀደስ መንግሥትህ ትምጣ፣ ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች እንዲሁም በምድር ትሁን!”  እያልን በጸሎታችን የምንጠይቀው። (ማቴ. ፮፥፱-፲፩)

እንጀራችንን በማዕድ አቅርበን የዕለት እንጀራችንን ዛሬ ስጠን ብለን መጠየቃችን የእንጀራችን ቁልፉ በበጎ ፈቃዱ በኩል ስለሆነ ነው። እናም ያለ እርሱ ፈቃድ እንኖር ዘንድ አይቻለንምና ይህንን በጎ ፈቃዱን መነኮሳት በምናኔ ይማጸኑታል፡ ባህታውያን በበረሃ ደጅ ይጠኑታ፤ ካህናቱ በመቅደስ ይጠይቁታል፤ ምእመናንም ይናፍቁታል።  ምክንያቱም “ያለ እኔ ምንም ማድረግ አትችሉም” ተብሎ ተነግሯልና ነው። (ዮሐ. ፲፭፥፭) ስለዚህ ያለ እርሱ ፈቃድ የምንፈጽመው ጉዳይ የለንምና ሁል ጊዜ እንደ ፈቃዱ ልንኖር ተገባን። ክርስቲያን ማለት የበጎ ፈቃዱ ባለሟል ነውና፡፡

ይቆየን

ስደትና ምሥጢሩ

በመ/ር ተመስገን ዘገየ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፮ ቀን ያለውን ወቅት ዘመነ ጸጌ በማለት ሰይማ ወቅቱ ላይ ያተኮረ አገልግሎት ትፈጽማለች፡፡ ጽጌ ማለት አበባ ማለት ነው። ጠቢቡ ሰሎሞን “እስመ ናሁ ክረምት ኀለፈ ወዝናም ገብአ ድኀሬሁ ጽጌ አስተርአየ በውስተ ምድርነ፤ እነሆ ክረምት አለፈ፣ ዝናቡም አልፎ ሄደ፣ አበቦችም በምድር ላይ ተገለጡ፣ የዜማም ጊዜ ደረሰ፣ የቁርዬም ቃል በምድራችን ተሰማ” እንዲል (መኃ. ፪÷፲፩-፲፪)

“እነሆ ክረምት አለፈ” በማለት ጠቢቡ ሰሎሞን የተናገረው የእስራኤል የመከራ ዘመን ማለፉን ለማመልክት ሲሆን መከራን በክረምት መስሎ ተናግሮታል፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንም በምሥጢር ሲተረጉሙት የአዳም የመከራ ዘመን አለፈ ማለት እንደሆነ ያብራራሉ፡፡

ይህንን ወቅት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ወደ ምድረ ግብፅ የተሰደደችበትን ጊዜ ታስባለች፡፡ በጌታችን ልደት ሰብአ ሰገል የሕፃኑን መወለድ ተረድተው ሊሰግዱለትና ግብር ሊያገቡለት በኮከብ እየተመሩ ወደ ቤተ ልሔም ለመድረስ ፍለጋቸውን ባጠናከሩበት ወቅት “ኮከቡን በምሥራቅ አይተን እንሰግድለት ዘንድ መጥተናልና የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው?” ብለው ጠየቁ፡፡ ሄሮድስም በሰማ ጊዜ ደነገጠ፤ የካህናት አለቆችንና የሕዝቡን ጻፎች ሁሉ ሰብስቦ ክርስቶስ በየት እንደሚወለድ ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም በይሁዳ ክፍል በቤተ ልሔም እንደሆነ ነገሩት፡፡ ሰብአ ሰገልን በምሥጢር አስጠርቶም በቤተ ልሔም መሆኑን ነግሮ ሲመለሱ በእርሱ በኩል እንዲመጡ ዜናውንም እንዲያበስሩት አሰናበታቸው፡፡ (ማቴ. ፪፥፩-፰)

ሰብአ ሰገል በኮከቡ ተመርተው ቤተ ልሔም ደርሰው ለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰግደው የሚገባውን ወርቅ፣ ከርቤ እና ዕጣን አቅርበው፣ ወደ ሀገራቸው ሊመለሱ በተነሡ ጊዜም የጌታ መልአክ ወደ ሄሮድስ እንዳይገቡ ስለ ነገራቸው በሌላ መንገድ ወደ ሀገራቸው ሄዱ፡፡ ይህን የተረዳው ሄሮድስ በሰብአ ሰገል ማታለል ተበሳጨ “…ወአዘዘ ሐራሁ ወፈነወ ይቅትሎ ኩሉ ሕጻናተ ዘቤተ ልሔም ወዘኩሉ አድያሚሃ፤ ወታደሮቹን በቤተ ልሔምና በአውራጃዋ ያሉ ሕፃናትን ሁሉ ግደሉ ብሎ አዝዞ ሰደደ፡፡” (ማቴ.፪÷፲፮)

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ይህንን የቤተ ልሔም ሕፃናትን እልቂት በተመለከተ “… አየሁም እነሆም በጉ በጽዮን ተራራ ቆሞ ነበር፡፡ ከእርሱም ጋር ስሙና የአባቱ ስም በግምባራቸው የተጻፈላቸው መቶ አርባ አራት ሺህ ነበሩ” በማለት ገልጾታል፡፡ (ራዕ. ፲፬÷፩-፫) በዚህም ምክንያት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከልጇ ጋር ተሰደደች፤ ዲያብሎም አሳደዳት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ የእመቤታችን ስደት በተመለከተ ሲገልጽ “…ታላቅ ምልክትም በሰማይ ታየ፤ ፀሐይን ተጎናጽፋ ጨረቃ ከእግሮችዋ በታች ያላት በራስዋም ላይ የ፲፪ ከዋክብት አክሊል የሆነላት አንዲት ሴት ነበረች፡፡ እርሰዋም ጸንሳ ነበር፤ ምጥም ተይዛ ልትወልድ ተጨንቃ ጮኸች። ሌላም ምልክት በሰማይ ታየ፤ እነሆም ታላቅ ቀይ ዘንዶ ሰባት ራሶችና አሥር ቀንዶችም ነበሩት፣ በራሶቹም ላይ ሰባት ዘውዶች ነበሩት …” (ራዕ. ፩፥፩-፬)

ሴት የተባለች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ቤተ ክርስቲያን ረቂቅ ናት፣ የክርስቶስም አካል ናት፡፡ የምትታየው ቤተ ክርስቲያን በተጋድሎ ላይ ያለች ስትሆን የማትታየው ቤተ ክርስቲያን ደግሞ ድል ያደረገችው ናት፡፡ ፀሐይ የተባለው ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሆን በቀንም በሌሊትም የሚያበራ እውነተኛ ብርሃን ነው፡፡ ጨረቃ የተባሉ ቅዱሳን፣ ፲፪ ከዋክብት የተባሉት ፲፪ቱ ቅዱሳን ሐዋርያት ናቸው፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ “ምጥ” ስንል በተለያየ ዘይቤ እንደ አገባቡ ይተረጎማል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ “ምጥ” ያለው የድንግል ማርያምን መንገላታት፣ የግብፅ በረሃ ስደትና ጭንቀትን ለማመልከት ነው፡፡ ለምሳሌ፦ ቅዱስ ጳውሎስ፣ ኢሳይያስ እና ሙሴ ምጥን እንደሚከተለው ገልጸውታል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ “ልጆች ሆይ ክርስቶስ በእናንተ እስኪሣል ድረስ ዳግመኛ ስለ እናንተ ምጥ ይዞኛል” ይላል (ገላ. ፬፥÷፲፱) ሙሴ “አሕዛብ ሰሙ፣ ተንቀጠቀጡም፤ በፍልስጥኤም የሚኖሩትን ምጥ ያዛቸው” ይላል፡፡ (ዘጸ. ፲፭፥÷፲፬) እንዲሁም ነቢዩ ኢሳይያስ “ስለዚህ ወገቤ ሕመም ተሞላ፣ እንደምትወልድ ሴት ምጥ ያዘኝ፣ ከሕመሜ የተነሣ አልሰማም ከድንጋጤም የተነሣ አላይም” ብሏል፡፡ በተጨማሪም ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ “ወሬዋ ወደ ግብጽ በደረሰ ጊዜ በጢሮስ ወሬ ምጥ ይይዛቸዋል” እንዲል፡፡ (ኢሳ. ፳፫፥÷፭)

የስደት ምክንያቶች  

ስደት በተለያዩ ምክንያቶች ሊከሰት ይችላል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ በጦርነት፣ በወረርሽኝ፣ እና በሌሎችም ሰው ሠራሽና ተፈጥሯዊ ክስተቶች መነሻነት ሰዎች ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ ሊሰደዱ ይችላሉ፡፡ አድካሚ ጉዞ፣ መራብ፣ መጠማት እና ሌሎች ችግሮችም ያጋጥማሉ፡፡

በሕግ የተከለከሉ ሥራዎችን በመሥራት ለስደት የሚዳረጉም ብዙዎች ናቸው፡፡ እንደ አዳም   “…እነርሱም ቀኑ በመሸ ጊዜ የእግዚአብሔር አምላክን ድምጽ ከገነት ውስጥ ሲመላለስ ሰሙ አዳምና ሚስቱ ከእግዚአብሔር ከአምላክ ፊት በገነት ዛፎች መካከል ተሸሸጉ” በማለት እንደተገለጸው፡፡ (ዘፍ.፫÷፰) እንደ እስራኤል ሀገራቸው በጠላት በተወረረ ጊዜ ተማርከው ለስደት የሚዳረጉ “… በውኑ ይህ  ሰው ኢኮንያን የተናቀና የተሰበረ የሸክላ ዕቃ  ነውና?  እርሱና ዘሩስ   በማያውቁት ምድር ስለምን ተጥለው ወደቁ?” እንደተባለ (ኤር. ፳፪÷፳፰) የሰው ሕይወት ጠፍቶባቸው የሚሰደዱም አሉ፡፡ “… ፈርዖንም ይህን ነገር በሰማ ጊዜ ሙሴን ሊገድለው ፈለገ፡፡ ሙሴ ግን ከፈርዖን ፊት ኮበለለ፤ በምድያም ምድርም ተቀመጠ፡፡ (ዘፍ. ፪÷፲፩-፲፮) እንደ ሄሮድስ በሥጋዊ ቅንዓት ተነሳሥቶም አንዱ መንግሥት ሌላውን መንግሥት ሊያጠፋው ሲነሣ ሕዝብ ለስደት ይዳረጋል፡፡

እግዚአብሔር ለምን ወደ ግብፅ መሰደድን መረጠ?

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከልጇ ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ጋር ወደ ግብፅ መሰደድ ምክንያት አንዱ ቀደምት አበው ወደ ግብፅ ተሰደው ስለነበር ነው፡፡ ለምሳሌ፡-

፩. አብርሃም ከሚስቱ ከሣራ ጋር በምድር ሁሉ ላይ ረሃብ በሆነ ጊዜ ወደ ግብፅ ተሰዶ ነበር፡፡ ግብፅም በደረሱ ጊዜ አብርሃም እንዳይገድሉት ስለፈራ ሣራን ስለ አንቺ ነፍሴ ትድን ዘንድ ወንድሜ ነው በዪ ብሏት ነበር፡፡ (ዘፍ. ፲፪÷፲-፳)

፪. ዮሴፍ በወንድሞቹ ተሽጦ ወደ ግብፅ ተሰዷል፡፡ ፲፯ ዓመት በሆነው ጊዜ ከአባቱ ልጆች ከባላና ከዘለፋ ልጆች ጋር በግ ይጠብቅ ነበር፡፡ ያየውንም ሕልም ለወንድሞቹ ነገራቸው፡፡ እነርሱም በቅንዓት ተነሣስተው ወንድማቸውን ከሚገድሉት ለእስማኤላውያን ሊሸጡት ተስማሙ፡፡ “እነዚያ እስማኤላውያን ነጋዴዎችም ሲያልፉ ወንድሞቹ የሴፍን ጎትተው አወጡት፤ ለእስማኤላውያንም በሃያ ብር ሸጡት፡፡ እነርሱም ዮሴፍን ወደ ግብጽ ወሰዱት” እንዲል፡፡ (ዘፍ. ፴፯፥፳፰)

ጌታችን ለምን ተሰደደ?

፩. ስደትን ለቅዱሳን ባርኮ ለመስጠት፣

፪. ትንቢተ ነቢያትን ለመፈጸም፣ (ኢሳ.19÷1፤ (ሆሴ. ፲፩÷፩))

፫. ገዳማተ ግብጽን እና ገዳማተ ኢትዮጵያን ለመባረክ፣

፬. ሰይጣንን ከሰው ልቡና አስወጥቶ ለመስደድ፡፡

የስደት ቆይታቸውን በተመለከተ

ቅዱስ ዮሐንስ የስደት ቆይታ ጊዜያቸውን በዕለት በወርና በዓመት ገልጾታል፡፡ “ከመ ትትዐቀብ   በህየ በኩሉ መዋዕል ዐሠርተ ወክልዔተ ምዕተ ወተሰዓ ዕለተ፤ ሴቲቱም በዘመኑ ሁሉ አንድ ሺህ ሁለት መቶ ስሳ ቀን በዚያ ትጠበቅ ዘንድ እግዚአብሔር ወደ አዘጋጀላት ቦታ ወደ በረሃ ሸሸች (ራዕ. ፲፪÷፮)፤ አርባዓ ወክልዔተ አውራኀ፤ ለአርባ ሁለት ወር ሥልጣን ተሰጠው (ራዕ.፲፫÷፭)፤ ዘመን፣ ወአዝማን፣ ወመንፈቀ ዘመን፤ ዘመን ያለው ፩ ዓመት፣ ወአዝማን ሲል ፪ ዓመት፣ ወመንፈቅ ሲል ስድስት ወርን ለማመልከት ነው፡፡ ስንደምረው ሦስት ዓመት ከስድስት ወር ይሆናል፡፡(ራዕ.፲፪÷፲፬)

ልዩ ልዩ መከራን በመቀበል ለሦስት ዓመት ከስድስት ወር በግብፅ ከቆዩ በኋላ ሄሮድስ መሞቱን የእግዚአብሔር መልአክ ለአረጋዊው ዮሴፍ ተገልጦ “የሕፃኑን ነፍስ የሚሹ ሞተዋልና ተነሥተህ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ” በማለት ተናገረው፡፡ አረጋዊው የሴፍም ሕፃኑንና እናቱን ይዞ ወደ እስራኤል ምድር ገባ፡፡ (ማቴ. ፪፥፳፩) ይህም የሚያመለክተን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስደትን ባርኮና ቀድሶ ለሰው ልጆች መስጠቱንና ስለ ስሙ የሚሰደዱ ብፁዓን እንደሚሰኙ ሲያስተምረን ነው፡፡ “ስለ ጽድቅ የሚሰደዱ ብፁዓን ናቸው” በማለት እንደገለጸው፡፡ (ማቴ. ፭፥፲)

ስደትን ከላይ እንደተመለከትነው እጅግ አስከፊ ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደተሰደደ ሁሉ በየዘመናቱ በተለያዩ ምክንያቶች ልንሰደድ እንችላለን፤ በርካታ ጸዋትወ መከራንም ልንቀበል እንችላለን፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔርን ተስፋ አድርጎ በጽናት መከራውን ተቋቁሞ ማለፍ ከሰው ልጆች ይጠበቃል፡፡

አበ ብዙኀን አብርሃም ከዘመዶቹ ተለይቶ ወደማያውቀው ምድር ሲሰደድ እግዚአብሔርን ተስፋ አድርጎ ነው፡፡ “እግዚአብሔርም አብርሃምን አለው፤ ከሀገርህ፣ ከዘመዶችህም፣ ከአባትህም ቤት ተለይተህ ውጣ፤ እኔ ወደማሳይህ ምድር ሂድ” በመባሉ በእምነት፣ በተስፋ ወጥቷልና ዘሩን እንደ ሰማይ ከዋክብትና እንደ ምድር አሸዋ እንዳበዛለት ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክራሉ፡፡ (ዘፍ. ፲፪፥፩) እኛም በተለያዩ ምክንያቶች ስደት በገጠመን ጊዜ እግዚአብሔርን ተስፋ አድርገን ከመከራው ሁሉ ሸሽጎ የበረከቱ ተሳታፊዎች እንዲያደረገን አምላከችን ይርዳን፡፡ አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“እንድታገኙ ፈጽማችሁ ሩጡ” (፩ኛቆሮ. ፱÷፳፬)

በዲ/ን ግርማ ተከተለው

ቃሉን የተናገረው ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሁለት የሕይወት ገጽታ እንደ ነበረው ይታወቃል። የመጀመሪያው በክርስቶስ ከማመኑ በፊት ምሁረ ኦሪት፣ ኋላ ደግሞ የሐዲስ ኪዳን ሐዋርያነትን የተጎናጸፈ ቅዱስና ታማኝ አገልጋይ ነው። ከአሳዳጅነት ተጠርቶ ሰዎችን ለመንግሥተ ሰማይ ይበቁ ዘንድ በጽናት ያስተማረ፣ ለክርስቶስ ፍቅር ሲል ልዩ ልዩ ፀዋትወ መከራዎችን በመቀበል በሰማዕትነት ያረፈ ታላቅ የቤተ ክርስቲያናችን ሐዋርያ ነው።

ቅዱስ ጳውሎስ በጻፋቸው ፲፬ መልእክታት በሁለት ሥፍራዎች ስለ ሩጫ አስተምሯል። የመጀመሪያው፡- “መልካሙን ገድል ተጋድዬአለሁ፥ ሩጫዬን ጨርሼአለሁ፥ ሃይማኖቴን ጠብቄአለሁ…” በማለት ለመንፈስ ልጁ ለጢሞቴዎስ ጽፎለታል። (፪ኛጢሞ. ፬÷፯) በዚህ አንቀጽ ከእርሱ የሚለይበት ጊዜ መድረሱን፣ የሚያስጨንቅ ጊዜ /ዘመን/ መምጣቱንና በዚህ ጊዜም ልጁ ጢሞቴዎስ እንዴት መኖርና እንዴት ማገልገል እንዳለበት ያስረዳበት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሁሉን ታግሦ አገልግሎቱን በታማኝነት፣ በትጋት እንዲሁም የተጠራበትን ዓላማ ተረድቶ በማገልገሉም ምን ዓይነት ሽልማት እንደሚጠብቀው ነግሮታል።

ሁለተኛው፡- “በእሽቅድምድም ሥፍራ የሚሽቀዳደሙ ሁሉ እንደሚፋጠኑ አታውቁምን? ለቀደመው የሚደረግለት ዋጋ አለ፤ እንዲሁ እናንተም እንድታገኙ ፈጽማችሁ ሩጡ።” በማለት በሩጫ መስሎ መንፈሳዊ ቁም ነገርን አስተምሯል። (፩ኛቆሮ. ፱÷፳፬) ሩጫ በጥንቷ ግሪክ በስፋት ይታወቅና ይዘወተር የነበረ፤ ታላላቅ ሽልማቶችንም ያስገኝ የነበረ የስፖርት ዓይነት ነው። ከዚህ መረዳት እንደሚቻለው ሩጫ በዚህ ዘመን የተጀመረ ሳይሆን በጥንት ዘመንም የነበረ ስፖርት መሆኑንና የቆሮንቶስ ክርስቲያኖችንም በሚያውቁትና በሚገባቸው መልኩ እንዳስተማራቸው እንረዳለን። ጌታችንም በመዋዕለ ሥጋዌው የተለያዩ ምሳሌዎችን በመጠቀም በሰሚዎቹ የአኗኗር ዘይቤ አንጻር ሲያስተምር እንደነበር ይታወቃል። ለምሳሌ በዘር በመንገድ በእርሾ፤ በበግና በፍየል እየመሰለ አስተምሯል። (ማቴ. ፲፫፥፲፮፤ ፳፭፥፴፩-፴፬፤ሉቃ. ፲፪፥፲፫)

በሩጫ ውድድር እናሸንፋለን ብለው የሚሮጡ ብዙዎች ቢሆኑም የሮጠ ሁሉ ግን ሽልማት (ሜዳልያ) አያገኝም። ለምሳሌ በአንድ ጊዜ የሚሮጡ መቶ ሰዎች ቢሆኑ፣ ሦስቱ ሰዎች የሜዳልያ ተሸላሚዎች ሲሆኑ፣ ሌሎቹ ደግሞ ተሸናፊ ይሆናሉ። ሁሉም ይሮጣሉ፣ ሁሉ ግን ተሸላሚ አይሆኑም ማለት ነው። እንደዚሁ ሁሉ የክርስትናን ሕይወት ለመኖር መንፈሳዊ ሩጫን የሚጀምር ብዙ ነው፤ ነገር ግን በአግባቡና በትጋት እየወደቁና እየተነሡ ሩጠው የሚጨርሱ ጥቂቶች ናቸው፡፡ “የተጠሩ ብዙዎች፥ የተመረጡ ግን ጥቂቶች ናቸውና” እንዲል። (ማቴ. ፳÷፲፮)

በክርስትና ሕይወት መንፈሳዊውን ፍሬ ለማፍራትና ለሽልማት ለመብቃት ያሉትን ውጣ ውረዶች ሁሉ ታግሦና በዓላማ ሩጦ መጨረስን ይጠይቃል። በሩጫ ውጤት የሚያስመዘግቡ አትሌቶችን ስንመለከት፣ ለዚህ ስኬት የሚበቁት በብዙ ትዕግሥትና ድካም አሰልቺውን ልምምድ አልፈው ነው። ያሰኛቸውን ሁሉ አይበሉም፣ አይጠጡም። መርጠው ይበላሉ፣ መርጠው ይጠጣሉ ማለት ነው። መተኛት ቢያስፈልጋቸውም የሞቀ አልጋቸውን ትተው በጠዋት ማልደው በመነሣት ልምምድ ያደርጋሉ። ከዚህ የምንረዳው ለመሮጥ የሚያስፈልጉ ነገሮች መኖራቸውን ነው። ምግብና መጠጥ አመራረጥ፣ እንቅልፍ መተው፣ ተግቶ ልምምድ ማድረግ፣ ለሩጫ ሕግ መገዛት አስፈላጊ ከሆኑ ነገሮች ጥቂቶቹ ናቸው። በክርስትና ሕይወትም እንዲሁ ነው። የተገኘውን ሁሉ ከመብላት ይልቅ ንቆ ትቶ በመጾም፤ እንቅልፍን በመተው ተግቶ በመጸለይ፤ ከራስ ቀንሶ ለሌላ በመስጠት፤ ዓለማዊውን ሽልማት ንቆ ለእውነት በመቆም እንዲሁም ለሥጋችን ዕረፍት የሚሆኑ ጊዜን፣ ገንዘብን፣ ጉልበትን ለመንፈሳዊ አገልግሎት በማዋል ለሽልማት መብቃት ያስፈልጋል።

ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ይህንን የቅዱስ ጳውሎስን ትምህርት አብራርቶ ባስተማረበት ድርሳኑ፤ ለሩጫ ሦስት ነገሮች ያስፈልጋሉ ይላል። አንደኛው፡- በሩጫ ጊዜ ብዙ ተመልካቾች ከመኖራቸው የተነሣ በተለይ ዙሩን በመምራት ላይ ላሉት በማጨብጨብና በመጮህ ድጋፍ ይሰጣሉ። በዚህ ጊዜ ይላል ሊቁ፣ ሯጮቹ ዘወር ብለው አጨብጫቢዎቹን መመልከት የለባቸውም። ሁለተኛ፡- ሯጮቹ መመልከትና መከተል ያለባቸው ከፊታቸው ያሉትን የቀደሟቸውን እንጂ ከኋላቸው ያሉትን መሆን የለበትም። በሦስተኛ ደረጃ፡- በዚያን ዘመን እንደ አሁኑ የሩጫ ሜዳ ኖሮ ሳይሆን ሩጫ የሚከናወነው በአትክልት ሥፍራ ነው። በዚህ ሥፍራ ደግሞ የተለያዩ ለመብላት የሚያስጎመጁ ፍራፍሬዎች አሉ። ስለዚህ ሯጩ ፍራፍሬውን ለመብላት ሩጫውን ማቆም የለበትም። ምንም እንኳ ፍራፍሬዎቹ ለመብላት የሚያስጎመጁ ቢሆኑም ለዓላማው ሲል ሽልማቱን ላለማጣት ታግሦ መሮጥ ያስፈልጋል። ሊቁ በክርስትና ሕይወትም እንዲህ ነው ይላል።

አንድ ክርስቲያን በመንፈሳዊ ሕይወቱ ብዙ ሩጫዎች አሉበት። ጾም፣ ጸሎት፣ ስግደት፣ ቅዳሴ፣ ምጽዋት፣ ዘወትር ቃለ እግዚአብሔርን መስማት፣ በአጠቃላይ ክርስቲያናዊ ሕይወትና ሥነ ምግባር በክርስቲያኖች ሕይወት ውስጥ ሊኖሩ የሚገቡ ሩጫዎች ናቸው። እነዚህን ተግባራት ለመፈጸም ደግሞ የምንተዋቸው ብዙ ሥጋዊ ፍላጎቶች አሉን፡፡ ነገር ግን በዚህ ሕይወት ውስጥ ያለፉ፣ ሩጫቸውን በድል ያጠናቀቁትን አብነት አድርገን የምንከተላቸው ቅዱሳን አባቶቻችንና እናቶቻችን አሉ። ለምሳሌ ጾምን ለመጾም ርኀብን መታስ ያስፈልጋል፣ በተለያዩ የሥራ ቦታዎች የሚቀርቡልንን ሥጋዊ ፍላጎቶቻችንን የሚቀሰቅሱና ለሥጋ ድሎት ብቻ የሚሆኑ ጥቅማ ጥቅሞችን መናቅ፣ መተው ያስፈልጋል። ጸሎትን ለማቅረብ ጊዜን መሥዋዕት ማድረግን፣ እንቅልፍን መተውን፣ ዘወትር ደጅ መጥናትን ይጠይቃል። ሌሎችንም መንፈሳዊ ተግባራት ለመፈጸም ብዙ ንቀን የምንተዋቸው ነገሮች መኖር አለባቸው። ካልሆነ ከጀመርነው ሩጫ ያሰናክሉንና ሽልማትን ለማግኘት፣ ገነት መንግሥተ ሰማያትየመግትን ዕድል ያሳጡናል።

በሩጫ ጊዜ ደጋፊዎችም ነቃፊዎችም እንዳሉ ሁሉ፣ የክርስትናውን ሕይወት ጉዞ ስንጀምርም እንዲሁ የሚነቅፉንና በውዳሴ ከንቱ ሊጥሉን የሚፈልጉ አያሌ አካላት ሊኖሩ ይችላሉ። በዚህ ጊዜም ጊዜያችንን በአግባቡ ለመጠቀምና ላለመውደቅ /ላለመሸነፍ/ ትኩረታችንን ማድረግ ያለብን በሩጫችን (በመንፈሳዊ ሕይወታችን) ላይ መሆን አለበት። በሐዋርያት ሕይወትም ይህ ዓይነቱ ፈተና አጋጥሞ እንደ ነበር መረዳት ይቻላል። ቅዱስ ጳውሎስና በርናባስ መንፈሳዊውን አገልግሎት (ያመኑትን ላላመኑት በሚያስተምሩበት ጊዜ) ካላመኑት አይሁዳውያን ተቃውሞ ደርሶባቸው ነበር። በሌላ ቦታ ደግሞ የሚያደርጉትን ተአምራት በመመልከት ሊያወድሷቸው /ሊያመልኳቸው/ ፈልገውም ነበር። ሁለቱም ሐዋርያት ለሁለቱም ሁኔታዎች ቦታ አልሰጡም። ምክንያቱም በደረሰባቸው ተቃውሞው ተስፋ ቢቆርጡ፤ የቀረበላቸውን ከንቱ ውዳሴና የተሰጣቸውን የማይገባቸውን ቦታ ተቀብለው ቢሆን ኖሮ ከጀመሩት ሩጫ ይሰናከሉ ነበር፤ የቀረበላቸውንም አክሊል ያሳጣቸው ነበር። ስለዚህ ሩጫችንን /መንፈሳዊ ሕይወታችንን/ ከሚያደናቅፉ ነገሮች ራሳችን መቆጠብ እና በመንፈሳዊ ሩጫችን መትጋት ያስፈልጋል፡፡

ሐዋርያው “እንድታገኙ ፈጽማችሁ ሩጡ” እንዳለን፤ ክርስቲያን ሁል ጊዜም በዓላማ የሚጓዝ፣ የጀመረውን ሩጫም /መንፈሳዊ ሕይወት/ ምንነትና የሚያስገኘውን ዋጋ በሚገባ መረዳት ይጠበቅበታል። ምንም እንኳን በዚህ ምድር መንፈሳዊ በመሆናችንና በእግዚአብሔር በመታመናችን የምናገኛቸው ብዙ ነገሮች ቢኖሩም፤ ለእኛ ለክርቲያኖች የመጨረሻ ሽልማት ዓለም ሳይፈጠር የተዘጋጀልንን መንግሥቱን መውረስ ነውና ለዚህ የሚያበቃንን ሩጫችንን በአግባቡና በትጋት መሮጥ ይገባል።

የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ሁሉ ተራዳኢነት አይለየን፤ አሜን!

ክርስቲያናዊ ሕይወት ከግቢ ጉባኤያት በኋላ

በመ/ር ተመስገን ዘገዬ

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከብዙ ውጣ ውረድ ማለትም ዓለማዊና መንፈሳዊ ትምህርታቸውን በአግባቡ ከተማሩ በኋላ ተመርቀው ሲወጡ እንዴት መኖር እንደለባቸውና ምን ማድረግ እንደሚገባቸው በዚህ ጽሑፍ ለማሳየት እንሞክራለን፦

፩. ከወንድሞች ጋር በኅብረት መኖር 

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ በተሰማሩበት ሁሉ ከማኅበረሰቡ ጋር በኅብረት መኖሩ መልካም ነው፡፡ ክርስትና የኅብረት እንጂ የብቸኝነት ሩጫ አይደለችም፡፡ መጽሐፍም «ወንድሞች በሕብረት ቢቀመጡ እነሆ መልካም ነው፤ እነሆም ያማረ ነው» ሲል መናገሩም ይህንን ያስረዳል፡፡ (መዝ.፻፴፫፥፩)

ጠቢቡ ሰሎሞንም «ድካማቸው መልካም ዋጋ አለውና አንድ ብቻ ከመሆን ሁለት መሆን ይሻላል፡፡ አንዱ ቢወድቅ ሁለተኛው ያነሣዋልና፤ አንድ ብቻውን ሆኖ በወደቀ ጊዜ ግን የሚያነሣው ሁለተኛ የለውምና ወዮለት፡፡» ብሎ እንደተናገረው የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ በዚህ ዓለም ሲኖሩ በብዙ መንገድ መደጋገፍ ያሻቸዋል፡፡ (መክ.፬፦፱) አንዱ ለሌላው መሥዋዕት  እስከ መሆን ድረስ  አብሮ በፍቅር  መኖር ይገባል፤  የክርስትና ትርጉሙ ይህን  ነውና፡፡ የሞላለትና በሁሉ  ምሉዕ  የሆነ ሰው በዚህ ዓለም ማግኘቱ አስቸጋሪ ሊሆን ስለሚችል መደጋገፍ፣ መረጃ መለዋወጥ  ያስፈልጋል፡፡

በአንድነት መኖር በኢኮኖሚም ለመደጋገፍ፣ እንዲሁም ከተለያዩ የውስጥና የውጭ ፈተናዎች ለመከላከል፣ እንዲሁም ለመጠበቅ ይረዳል፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን «ብረት ብረትን ያስለዋል፤ ሰው ባልንጀራውን ይስለዋል፡፡» በማለት መልካም ጓደኛ ሌላውን ጥሩና የተስተካከለ ሰው እንዲሆን እንደሚረዳው ተናግሯል፡፡ (ምሳ.፳፯፥፲፮) መተራረም የሚቻለው በመከባበርና መልካሙን መንገድ በመከተል፤ አንተ ከእኔ ትሻላለህ በመባባል የተሰጠውን አስተያየት በመጠቀም የሕይወት ለውጥ ማምጣት ሲቻል ብቻ ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት «ከቸር ሰው ጋር ቸር ሆነህ ትገኛለህ፤   ከቅን ሰው ጋር ቅን ሆነህ ትገኛለህ፤ ከንጹሕ  ጋር ንጹሕ  ሆነህ ትገኛለህ» እንዲል፡፡ (መዝ.፲፯፥፳፭)

፪. በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ተካፋይ መሆን፡-

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለልጆቿ የምታድላቸው ሰባት ሀብታት (ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን) አሏት፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን «ጥበብ ቤትዋን ሠራች፥ ሰባቱንም ምሰሶችዋን አቆመች። ፍሪዳዋን አረደች፥ የወይን ጠጅዋን ደባለቀች፥ ማዕድዋን አዘጋጀች። ባሪያዎችዋን ልካ በከተማዪቱ ከፍተኛ ሥፍራ ላይ ጠራች። አላዋቂ የሆነ ወደዚህ ፈቀቅ ይበል፤ አእምሮ የጐደላቸውንም እንዲህ አለች። ኑ፥ እንጀራዬን ብሉ፥ የደባለቅሁትንም የወይን ጠጅ ጠጡ። አላዋቂነትን ትታችሁ በሕይወት ኑሩ፥ በማስተዋልም መንገድ ሂዱ።» በማለት ይገልጻል፡፡ (ምሳ.፱÷፩-፭) በዚህ ቃለ ትንቢት መሠረት ጥበብ የተባለው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ ቤት የተባለችውም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፣ እንዲሁም የክርስቲያኖች ሰውነት ናት፤ ሰባቱ ምሰሶዎች የሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናቸው። የታረደው ፍሪዳ ቅዱስ ሥጋው፣ የተደባለቀው ወይን የክቡር ደሙ ምሳሌ ነው።

በቅዱስ ወንጌል «ኢየሱስም፡- ‘ኑ፥ ምሳ ብሉ’ አላቸው። ከደቀ መዛሙርቱ አንተ ማን ነህ? ብሎ ሊጠይቀወ የደፈረ የለም፤ ጌታችን እንደሆነ አውቀዋልና፡፡ ጌታችን ኢየሱስም መጣና ኅብስቱን   አንሥቶ ሰጣቸው፥ ከዓሣወም እንዲሁ።» ተብሎ እንደተጻፈ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ በምንችውለውና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን በሚፈቅድልን መሠረት በአገልግሎት መሳተፍ ይጠበቅብናል፡፡ ገና በሥራ ቦታ ተመድበን እንደሄድንም የንስሓ አባት መያዝ፣ በየጊዜው ንስሓ መግባትና እየተገናኘን ቀኖና ተቀብለን ሥጋ ወደሙን መቀበል ያስፈልገናል፡፡ (ዮሐ.፳፩፥፲፪)

በሕይወታችን «የበይ ተመልካች» መሆን አያስፈልግም፡፡ «እውነት እውነት እላችኋለሁ የሰውን ልጅን ሥጋ ካልበላችሁ ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም፤ … ሥጋዬን   የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ በእኔ ይኖራል፤ እኔም በእርሱ እኖራለሁ» እንደተባለ ክርስቲያን  የሆነ ሁሉ  ከዚህ ምሥጢር  በየጊዜው  መሳተፍ  እንዳለበት መረዳት ይገባል፡፡ (ዮሐ.፮፥፶፫-፶፮)

የምንሠራቸው ሥራዎች የሚባረኩት በመንፈሳዊ ሕይወታችን የምናድገው፣ መንግሥቱንም መውረስ የምንችለው ቅዱስ ሥጋውን ስንበላ፣ ክቡር ደሙንም ስንጠጣ ብቻ ነው፡፡ የምሥጢራት ተካፋይ በመሆን ሌሎችም እንዲካፈሉ ማድረግ ይኖርብናል፡፡

፫. ኑሮን በዕቅድ መምራት፡-

ዕቅድ የሌለው ሁሉ መንገዱ ውጣ ውረድ የበዛበት ነው፡፡ ኑሮዬ ይበቃኛል ብለን መኖር የምንችለው በዕቅድ ስንመራ ብቻ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ «ስለ ጉድለት አልልም የምኖርበት ኑሮዬ ይበቃኛል ማለትን ተምሬለሁ» ያለው ክርስቲያን ሕይወቱን እንደዚሁ በዘፈቀደ እንደመጣለት መምራት እንደማይገባው ሲያስገነዝበን ነው፡፡ (ፊል.፬፥፲) ዕድሜያችን በዕቅድ ላይ ተመሥርተን በመምራት ካልተጠቀምንበት ምንም ሳንሠራበት ያልቃል፡፡ እግዚአብሔር ፍጥረቱን ሲፈጥር በአንድ ጊዜ ማከናውን የሚችለውን ስድስት ቀናት የፈጀበት እያንዳንዱን ነገር በዕቅድና በሥርዓት ማከናወን እንደሚገባ ሲያስተምረን ነው፡፡ ሥራ የምንሠራበት፣የምንጸልይበት፣ ትምህርተ ሃይማኖት የምንማርበት፤ ንስሓ ገብተን ቅዱስ ቊርባኑን የምንቀበልበት የራሳችን  ዕቅድ ያስፈልገናል፡፡

የምናገኘው ገንዘብ ያለ ዕቅድና ዓላማ የምናወጣ ከሆነ ከወር ወር መድረስ አንችልም፡፡ ደመወዛችን የተቀበልን ሰሞን ሆቴል የምናማርጥ ከሆነ በወሩ አጋማሽ ጾማችንን ማደራችን የማይቀር ጉዳይ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ «ነገር ግን ሁሉ በአገባብና በሥርዓት ይሁን» ይላል (፩ኛቆሮ.፲፬፥፵) የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር የቄሣርን ለቄሣር እንደተባለ በእግዚአብሔር ድርሻ ላይ ታማኞች መሆን አለብን፡፡ ስለሆነም በበረከት እንዲያትረፈርፈን ዐሥራት የማውጣት ልምድ  ከመጀመሪያው ደመወዛችን መጀመርና በየወሩ ዐሥራታችንን ማውጣት ይኖርብናል፡፡

፬. በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የአገልግሎት መዋቅር ውስጥ በአገልግሎት መሳተፍ

ልዑል እግዚአብሔርን ማገልገል የምንችለው በቤተ ክርስቲያን ሲሆን በዕውቀታችን፤ በጉልበታችን፤ በገንዘባችንና በጊዜያችን ሁሉ እግዚአብሔርን ማገልገል ይጠበቅብናል፡፡አንዳንዶች ለምን አታገለግሉም ሲባሉ የማይረባ ምክንያት እየደረደሩ ከቤተ ክርስቲያን ይርቃሉ፡፡ ሌሎች ደግሞ እንዲለመኑ፣ «እባካችሁ» እንዲባሉ ይፈልጋሉ፡፡ በማገልገላችን ከኃጢአት እንጠበቃለን፣ ሰላምና ተስፋ የተሞላበት ኑሮ እንኖራለን፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም «ስለዚህ ወንድሞቼ ሆይ መጠራታችሁንና መመረጣችሁን ታፀኑ ዘንድ ከፊት ይልቅ ትጉ፤ እነዚህን ብታደርጉ ከቶ አትሰናከሉም» በማለት በአገልግሎት መትጋት እንደሚገባን ይመክረናል፡፡ (፩ኛጴጥ.፩፥፲)

ብዙዎች ከተመረቅን በኋላ አገልግሎት ያለ አይመሰለንም፡፡ አገልግሎታችንም ግቢ ጉባኤ ላይ ብቻ ይቀራል፡፡ ይህ ደግሞ የክርስትናውን ምሥጢር በአግባቡ አለማወቅ ነው፡፡ ጌታችንም ስለ ለቅዱሳን ሐዋርያት ስለ ነገረ ምጽአቱ ሲያስተምራቸው «እስከ መጨረሻው የሚጸና ግን እርሱ ይድናል» እንዳላቸው ግቢ ጉባኤ ብቻ በማገልገላችን የምንድን አይደለንም፤ እስከ መጨረሻው የሕይወት ፍጻሜ ድረስ ቃሉን በመጠበቅና በማገልገል መጓዝ እንጂ፡፡ (ማቴ.፳፬፥፲፫) የሕይወት አክሊልንም ለመቀበል እስከ መጨረሻው መትጋት ያስፈልጋል፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስም  «ትቀበለው ዘንድ  ስላለህን መከራ ምንም አትፍራ፤ እነሆ እንድትፈተኑ ሰይጣን ከእናንተ አንዳንዶችን ወደ እሥር ቤት እንዲገቡ ያደርጋል፡፡  ዐሥር ቀንም መከራ ትቀበላላችሁ፤ እስከ ሞት ድረስም የታመንህ ሁን የሕይወት አክሊልንም እሰጥሃለሁ» ይላል፡፡ (ራዕ.፪፥፲)

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በሚገኙ መዋቅሮች ማለትም በሰ/ት/ቤት፣ በሰበካ ጉባኤ በመታቀፍ ማገልገል ይገባል፡፡ በተለይም ለአገልግሎት   የሚመች ሰበካ ጉባኤ እንዲመሠረትና በዚያም ውስጥ የራስን አሻራ በማሳረፍ ቤተ ክርስቲያንን መደገፍ፣ የተሻለና ቀልጣፋ አሠራርን መከተል የሚያስችሉ መንገዶችን በመቀየስ የድርሻን መወጣት ያስፈልጋል፡፡

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ በተመረቁበት የሙያ መስክ ገብተው አስፈላጊውን ሥራ መሥራት ብቻ በቂ አይደለም፡፡ በታማኝነትና በቅንነት መሥራትንም ይጠይቃል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ሁኔታ በአሁኑ ጊዜ የልጆቿችን ሙያ እንደምትሻ ግልጥ ነው፡፡ በተለይም የልማት ተቋማትን በማደራጅት (ለምሳሌ ፕሮጀክት በመቅረጽ) በኩል ያለባትን የመዋዕለ ንዋይ  ችግር ለመቅረፍ የምትወስዳቸው ርምጃዎች ማንነቷን የሚያሳውቁ እንጂ የሚያደበዝዙ እንዳይሆኑ  በውስጧ ሆነው ምሥጢሯንና  ቋንቋዋን የሚያውቁ የራሷ ልጆች ቢያጠኑላት ዛሬ የሚታዩት አስተዳደራዊ ችግሮች ባልተከሠቱ  ነበር፡፡

ተመርቀን ከየግቢ ጉባኤያት ተለይተን ወደ ሥራ ዓለም ስንሠማራ እንደ የአካባቢው ነባራዊ ሁኔታ በተለያዩ ደረጃዎች ላይ ያሉ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ያጋጥሙናል፡፡ ተጠናክረው በጥሩ አገልግሎት የሚገኙ፣ ተቋቁመው በአገልጋይ እጥረት ምክንያት አገልግሎት ያቆሙ፣ እንዲሁም ያልተቋቋሙባቸው አካባቢዎች ሊያጋጥሙን ይችላል፡፡ ከጠንካሮቹ ሰ/ት/ቤቶች ልምድ በመውሰድ የሚጠናከሩበትን መንገድ ማሰብ፣ መቀየስና ተግባራዊ እንዲሆን የተቻለውን ጥረት ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ በግቢ ጉባኤያት ካገኘናቸው ልምዶችም በመነሣት ስልት መቀየስ ከግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ የሚጠበቅ ተግባር ነው፡፡

በየሄድንባቸው አካባቢዎች ሰ/ት/ ቤት ከማቋቋማችን በፊት አስቀድመን አካባቢውን ሕዝብ ጠባዩን ፍላጎቱን ባህሉንና የኗኗር ዘይቤውን ማጥናት ያስፈልጋል፡፡ ማጥናት፣ ከዚያም በቃለ ዓዋዲው መሠረት ማደራጀት እንዳለብን ማሰብ ተገቢ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ብዙ ከመናገር ብዙ መስማትና ከማገልገልም በፊት ብዙ መገልገልን መምረጥ አስፈላጊ ነው፡፡ ያለውን ሁኔታ ሳናጠና በድፍረት መግባት መውጫችንን ያከብደዋልና፡፡ «እንደ እባብ ብልህ እንደ ርግብ የዋህ» መሆን ያስፈልጋል፡፡(ማቴ.፲፥፲፮) በተቻለ መጠን እኛ እንደ ወንድምና እኅት ቀርበን የሥጋዊ ሕይወታችን አለመሟላት መንፈሳዊና ሕይወታችንን እንደሚያጎድለው ብዙዎችም ወደ መጥፎ ሕይወት እንዳይገቡ ማሰገንዘብ አለብን፡፡

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ከምረቃ በኋላ የሚያጋጥሟቸው ፈተናዎች

በመ/ር ተመስገን ዘገየ

ክፍል ፩

ፈተና በቤተ ክርስቲያናችን እምነት፣ ሥርዓት፣ ቀኖናና ትውፊት መሠረት በምናደርገው መንፈሳዊ ጉዞ ውስጥ ዓላማችንን ለማደናቀፍ ከተለያዩ አካላትና አቅጣጫ የሚገጥመን መሰናክል ወይም እንቅፋት ነው፡፡

ፈተና ከየትም አቅጣጫና አካባቢ ወይም ምክንያት ይምጣ በውስጡ ግን ዓላማ ይኖረዋል።ቅዱስ ያዕቆብ “በፈተና የሚጸና ሰው የተባረከ ነው፡፡ ከተፈተነ በኋላ ለሚወዱት ተስፋ ስለ እርሱ የሰጣቸውን የሕይወት አክሊል ይቀበላልና፡፡ ማንም ሲፈተን በእግዚአብሔር እፈተናለሁ አይበል፤ እግዚአብሔር በክፉ አይፈትንምና እርሱ ራሱስ ማንንም አይፈትንም፤ ነገር ግን እያንዳንዱ በራሱ ምኞት ሲሳብና ሲታለል ይፈተናል“ ብሏል (ያዕ. ፩፥፲፪-፲፬)፡፡ ትልቁ ነገር የፈተናው መምጣት ሳይሆን ፈተናውን ለማለፍ መንፈሳዊ ትጥቅን በመታጠቅ ድል መንሣትን እናገኝ ዘንድ ዝግጁና ብቁ ሆኖ መገኘቱ ላይ ነው።

ይህም በቅዱሳት መጻሕፍት “ለሰው ሁሉ ከሚሆነው በቀር ምንም ፈተና አልደረሰባችሁም፤ ነገር ግን ከሚቻላችሁ መጠን ይልቅ ትፈተኑ ዘንድ የማይፈቅድ እግዚአብሔር የታመነ ነው፥ ትታገሡም ዘንድ እንድትችሉ ከፈተናው ጋር መውጫውን ደግሞ ያደርግላችኋል” ተብሎ ተጽፏል፡፡ (፩ኛ ቆሮ. ፲፥፲፫)

በትምህርት ዓለም ሳለን ከሚያጋጥሙን ፈተናዎች ለየት የሚሉ ፈተናዎች የሚያጋጥሙን ገና ከተመረቅን ማግሥት ጀምሮ ነው፡፡ እኛ የሕይወት ለውጥ ባደረግን ቁጥር ፈተናውም እንዲሁ   ይለዋወጣልና ለዚህም ደግሞ ራስን ማዘጋጀት ያስፈልጋል፡፡ ከምረቃ በኋላ ከሚያጋጥሙ ችግሮችና ፈተናዎች መካከል

፩. እንደ ተመረቁ ሥራ አለመያዝ

በዚህ ዘመን አንዱ መሠረታዊ ችግር ከብዙ ድካም የትምህርት ጊዜና ውጣ ውረድ ቀጥሎ ያለው ፈተና ሥራ አለማግኘት ነው፡፡ ሥራ ቶሎ ባለማግኘቱም የተመረቁበትን የትምህርት መስክ ማጥላላትና የሌላውን ማድነቅ ይጀመራል፡፡ ወደ ተስፋ መቁረጥና አልባሌ ተግባራት  የሚሄዱም ብዙዎች  ናቸው፡፡ ሥራ  የፈታ አእምሮ ምን ጊዜም “የሰይጣን  ቤተ ሙከራ“ ነው፡፡]

ብዙዎቻችን ደግሞ ለሥራ ያለን አመለካከት የተሳሳተ ነው፡፡ የተሳሳተ አመለካካት የሚመነጨው ደግሞ ከመንግሥት ተቋማት ተቀጥረን ቢሮ ይዘን ካልሠራን ሥራ የሠራን ስለማይመስለንና ሥራ ፈጥረን ስለማንሠራ ነው፡፡ አንዳንዶችም የአካባቢው ወሬና አሉባልታ በመፍራት ያልሆነ ምርጫ ሲመርጡ ይታያሉ፡፡ “እስከ አሁን ሥራ እንዴት አልያዝክም?” የሚል ጥያቄን ይሸሹታል፡

ጠቢቡ ሰሎሞን “ለሁሉም ዘመን ከሰማይ በታችም ለሆነ ነገር ሁሉ ጊዜ አለው፡፡ ለመወለድ   ጊዜ አለው፣ ለሞሞትም ጊዜ አለው፣ ለመትከል ጊዜ አለው፣ የተተከለውንም ለመንቀል ጊዜ አለው፡፡ … ለሠራተኛ የድካሙ ትርፉ ምንድር ነው?” (መክ. ፫፥፩-፰) ብለን እግዚአብሔርን ተስፋ ማድረግ አለብን፡፡ ሁሉም ነገር ያልፋል ነገር ግን የሚያልፈው ጊዜና ችግር በሕይወታችን ላይ ጥቁር ጠባሳ ጥሎ እንዳይሄድ ልንጠነቀቅ ይገባል፡፡ በዚህም የወጣትነት ጊዜ ለነፍሳችን የሚጠቅም ሥራን ለመሥራት መሽቀዳደም (መሯሯጥ) ብልህነት ነው፡፡

፪. አለመረጋጋት፦

አለመረጋጋት ብዙ ተመራቂዎች ከከፍተኛ የትምህርት ተቋማት እንደተመረቁ የሚያጋጥማቸው ፈተና ነው፡፡ ብዙዎች ከመመረቃቸው በፊት ያስቡት የነበረውን ሁሉ ለማሟላት አቅም ሲያንሳቸው መረጋጋት ይጎድላቸዋል፡፡ እንደ ተመረቁ ሁሉም ነገር በአንድ   ጊዜ እንደማይሟላ ዐውቆ ፍላጎትን መግታት የግድ ነው፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ”… ኑሮዬ ይበቃኛል፤ ለሚለው ግን እግዚአብሔርን መምሰል እጅግ ማትረፊያ ነው፤ ወደ ዓለም ምንም እንኳ አላመጣንምና አንዳችንም ልንወስድ አይቻለንም፡፡   ምግብና ልብስ ከኖረን ግን እርሱ ይበቃናል፤ ዳሩ ግን ባለ ጠጎች ሊሆኑ የሚፈልጉ በጥፋትና በመፍረስ ሰዎችንም በሚያሰጥምና በሚያሰንፍ በሚጎዳም በብዙ ምኞትና በፈተና በወጥመድም ይወድቃሉ፤ ገንዘብን መውድድ የክፋት ሁሉ ሥር ነውና” ይላል (፩ኛ ጢሞ. ፮፥፮-፲) ባገኘነው ነገር ሁሉ እግዚአብሔርን ማመስገን ይኖርብናል፡፡ ኑሮአችንም በመጠን አድርገን መኖር መቻል አለብን፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ “… በመጠን ኑሩ፣ ንቁም፤ ባላጋራችሁ ዲያብሎስ የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሣ አንበሳ ይዞራልና በዓለም ያሉት ወንድሞቻችሁ ያን መከራ በሙሉ እንዲቀበሉ እያወቃችሁ በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት፤ በክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ዘላለም ክብሩ የጠራችሁ የጸጋ ሁሉ አምላክ ለጥቂት ጊዜ መከራን ከተቀበላችሁ በኋላ ራሱን ፍጹማን ያደርጋችኋል፣ ያጸናችሁማል፣ ያበረታችሁማል …” (፩ኛ ጴጥ. ፮፥፰-፲፩) ሕይወት የሚጣፍጠው ታግለው በብዙ ፈተና ውስጥ አልፈው ሲያገኙት ነው፡፡ ስለዚህ በመጠን ፍላጎትን ቀንሶ መኖር መለማመድ ያስፈልገናል፡፡

የአንድ የከፍተኛ ትምህርት ተቋም ተመራቂ መቼና የትም ቢሆን እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር እንደሆነ ካላመነ በሕይወቱ መረጋጋትና ማስተዋል ሊኖረው አይችልም፡፡ የከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ተመራቂዎች መሠረታዊ ችግር ይህ ነው፡፡ ሥራ የት ቦታ እንደሚመደቡ እያሰቡ ይጨነቃሉ፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “… እንግዲህ ምን እንበላለን? ምንስ እንጠጣለን?  ምንስ እንለብሳለን? ብላችሁ አትጨነቁ ይህንስ ሁሉ አሕዛብ ይፈልጋሉ፡፡ ይህ ሁሉ እንዲያስፈልጋችሁ የሰማዩ አባታችሁ ያውቃልና፡፡ ነገር ግን አስቀድማችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ጽድቁንም ፈልጉ ይህ ሁሉ ይጨመርላችኋል፡፡ ነገ ለራሱ ይጨነቃልና ለነገ አትጨነቁ ለቀኑ ክፋቱ ይበቃዋል” ብሎናል፡፡ (ማቴ. ፮፥፴፩-፴፬)

፫. መወሰን፦

ለከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ተመራቂዎች ከሚያስፈልጉት ነገሮች ትልቁና ዋነኛው መወሰን መቻል ነው፡፡ በራስ ላይ መወሰን ካልተቻለ ሌሎች (ቤተሰብ፣ ዘመድ) እንዲወስኑ ፈቀድንላቸው ማለት ነው፡፡ ዕቅድ፣ ሂደትና ግብ ሊኖር ይገባናል፡፡ የዕቅድ ዐቀበት የለውም ፈተናው ክንውኑ ስለሆነ የከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ተመራቂዎች ውሳኔዎቻቸውን በተረጋጋ ሁኔታ ሊወስኑ ይገባል፡፡

ይቆየን፡፡

መንፈሳዊ ወጣት

በእንዳለ ደምስስ

የሰው ልጅ ሕይወት በዐራቱ የዕድሜ ክልል ይከፋፈላል፡፡ ይኸውም የሕፃንነት፣ የወጣትነት፣ የጎልማሳነትና የእርግና ዘመናት ተብለው ይታወቃሉ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ የወጣትነት የዕድሜ ክልል በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አስተምሮ መሠረት ከሃያ እስከ ዐርባ ዓመት ያለውን ዕድሜ የያዘ ነው፡፡

ቅዱሳት መጻሕፍት እነዚህን የሰው ልጅ የተፈጥሮ ባሕርያት በአራቱ ባሕርያተ ሥጋ ማለትም በነፋስ፤ በእሳት፤ በውኃና በመሬት ሲመስሏቸው አምስተኛ ነፍስን ጨምሮ በአንድ ሰው የሕይወት ዘመን ላይ ሲንጸባረቁ ይኖራሉ፡፡ የመሬት መሠረቷ ጽናቷ ነፋስ ነው፡፡ የእኛም ከላይ ሥጋችን መሬት ነው፡፡ መሬትም በውኃ ላይ ናት ይህም ውኃው ደማችን ነው፡፡ የእኛም ሥጋችን በደማችን ነውና የሚጸናው፤ የውኃ ሕይወት ነፋስ ነው፡፡

ከሃያ እስከ ዐርባ ያለው የዕድሜ ክልል የእሳትነት ባሕርይ ጎልቶ የሚታይበት በመሆኑ ዘመነ እሳት ወይም ምግበ እሳት ይባላል፡፡ እሳት ያገኘውን እንደሚያቃጥል እና እንደሚፈጅ ሁሉ ወጣትነትም በመንፈሳዊ ሕይወት ካልተገራ ሁሉን ልጨብጥ፣ ሁሉን ላድርግ የሚል ስሜታዊነት ጎልቶ የሚታይበት ወቅት ነው፡፡ ይህ ደግሞ ለጥፋትና ለርኵሰት አሳልፎ ይሰጣል፡፡

ይህንን የእሳትነት ዘመን በሰከነና ማስተዋል በተሞላበት ሁኔታ ለማለፍ ሕይወትን በመንፈሳዊነት መምራት ይገባል፡፡ ፈቃደ ነፍስን በፈቃደ ሥጋ ላይ ማሠልጠን፣ በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደት እንዲሁም በልዩ ልዩ ኦርቶዶክሳዊ ምግባራት በማነጽ ዓለምን ማሸነፍ ከወጣቶች ይጠበቃል፡፡

በቅድሚያ ወጣቶችን ከመንፈሳዊ ሕይወት ሊያስወጡ ይችላሉ የምንላቸውን ነጥቦች ቅዱሳት መጻሕፍትን መነሻ በማድረግ ጥቂቶቹን እንመልከት፡-

ስሜታዊነት፡-

ከላይ ለመጠቆም እንደሞከርነው ከሌሎቹ የዕድሜ ዘመናት በተለየ ሁኔታ በወጣቶች ላይ ቅጽበታዊ ውሳኔዎችና ድርጊቶችን ለመፈጸም የሚሽቀዳደሙበት ጊዜ ነው፡፡ “ሁሉን ነገር አሁን ካላደረግሁ” የሚል ስሜት ሲነዳቸው እናስተውላለን፡፡ ለዚህም እንደ ምሳሌ ቃየልን መመልክት እንችላለን፡፡

ቃየል በወንድሙ በአቤል ላይ በቅናት መንፈስ በመነሣሣት ስሜቱን መቆጣጠር ተስኖት ወንድሙን እስከ መግደል አድርሶታል፡፡ ቃየል ምድርን የሚያርስ አራሽ ሆነ፤ አቤልም በግ ጠባቂ ሆነ፡፡ ነገር ግን ሁለቱም ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አቀረቡ፡፡ አቤል ከሚጠብቃቸው በጎች ጥፍሩ ያልዘረዘረውን፣ ቀንዱ ያልከረከረውን፣ ጸጉሩ ያላረረውን የአንድ ዓመት ጠቦት ሲያቀርብ፣ ቃየል ግን አርሶ ካከማቸው ስንዴ እግዚአብሔር አይበላው፣ ምን ያደርግለታል በሚል በንዝህላልነት እንክርዳዱን አቀረበ፡፡ እግዚአብሔርም ወደ አቤል መሥዋዕት ተመለከተ፤ ከሰማይም እሳት ወርዶ በላው፤ ቃየልም ተበሳጨ በወንድሙም ላይ በጠላትነት ተነሣ፡፡ ይገድለውም ዘንድ ወደ ሜዳ ይዞት ወጣ፡፡ “ና ወደ ሜዳ እንሂድ አለው፤ በሜዳም ሳሉ ቃየል በወንድሙ በአቤል ላይ ተነሣበት፣ ገደለውም” (ዘፍ.፬፥፰) በምድርም ላይ ተቅበዝባዥ ሆኖ ኖረ፡፡ ይህንን ስንመለከት ቃየል በቅናት መንፈስ መነሣቱንና ስሜታዊነት አይሎበት ነገሮችን ለማመዛዘን ጊዜ ሳይወስድ የከፋውን ኃጢአት እስከ መሥራት አደረሰው፡፡

የዝሙት ጾር፡-

በወጣትነት የዕድሜ ክልል ያሉ ወጣቶች ከሚፈተኑበት አንዱ ጉዳይ ራሳቸውን ለዝሙት መንፈስ አሳልፈው መስጠታቸው ነው፡፡ በወጣትነት ዘመን ለተቃራኒ ጾታ ያላቸው ስሜት እጅግ የሚያይልበት እና በመንፈሳዊ ሕይወት ባለመቃኘቱ ምክንያት ከሐሳብ አልፎ ወደ ድርጊት መጣደፍ ጎልቶ የሚታይበት ነው፡፡

ወጣቱ የዳዊት ልጅ አምኖን በእኅቱ ትዕማር ፍቅር ተነደፈ፡፡ የታመመ መስሎም ተኝቶ እኅቱ ትዕማር እንድትንከባከበው በጓደኛው በተንኮል አመንጪነት ተነሣስቶ አባቱን አስፈቀደ፡፡ ነገር ግን ትዕማር ወንድሟን ልትንከባከበው በመጣች ጊዜ “እኅቴ ሆይ ነዪ ከእኔ ጋር ተኚ፤ አላት፡፡ እርስዋም አለችው፡- ወንድሜ ሆይ አታዋርደኝ፤ እንዲህ ያለ ነገር በእስራኤል ዘንድ አይገባምና ይህን ነውረኛ ሥራ አታድርግ” ብላ ለመነችው፡፡ እርሱ ግን ምክሯን አልሰማም፡፡ ለስሜታዊነት ራሱን አሳልፎ ሰጥቷልና እኅቱን አስነወራት፡፡ በእግዚአብሔርም ፊት ኃጢአትን ሠራ፡፡ (፪ኛ ሳሙ. ፲፫፥፩-፲፱)፡፡

ዓለምን መውደድ፡-

ሌላው ከሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ደቀ መዛሙርት መካከል ወጣቱ ዴማስ ነው፡፡ ዴማስ ከሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እግር ሥር ቁጭ ብሎ የተማረ፣ በሄደበት የሚሄድ፣ ባደረበት የሚያድር ሆኖ ሳለ ብልጭልጩ የተሎንቄ ከተማ (ዓለም) አታለለው፡፡ ከመንፈሳዊው ዓለም ይልቅ ሥጋዊው ሕይወቱን ለማስደሰት ሲል ወደ ከተማው ኮበለለ፡፡ ዓለምም ውጣው ቀረች፡፡ በዚህም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በሐዘን “ዴማስ ይህን የዛሬውን ዓለም ወድዶ እኔንም ተወኝ፤ ወደ ተሰሎንቄም ሄደ” በማለት ገልጿል፡፡

በወጣትነት ዘመን ከመንፈሳዊ ሕይወት የሚለዩ ጉዳዮች መካከል እንደ ምሳሌ ከላይ ጥቂቶቹን ተመለከትን እንጂ ዘርዝረን ልንጨርሳቸው አንችልም፡፡

ወጣቶች በመንፈሳዊ ሕይወታቸው እንዲጸኑ የሚያደርጓቸውን ጉዳዮችን በጥቂቱ ስንመለከት ደግሞ፡-

ራስን መግዛት፡-

በእሳት በተመሰለው ወጣትነት ዘመን ራስን መግዛት መቻል ትልቅ ሰማዕትነት ነው፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን “የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጉብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ” (መክ. ፲፪፥፩) እንዲል በወጣትነት ዘመን በመንፈሳዊ ሕይወት መትጋት፣ እንደ እግዚአብሔርም ፈቃድ መጓዝ በመጨረሻ በእግዚአብር ፊት ለክብር የሚያበቃ ነው፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ “ሰው ራሱ በገዛ ምኞቱ ሲሳብና ሲታለል ይፈተናል” (፩ኛ ያዕ. ፩፥፲፬) ላይ በማለት እንዳስተማረን፤ በወጣትነት ዘመን የሚገኝ ምኞት ከመጠን በላይ ወደ ጥፋት የሚስብና የሚያታልል ነው፡፡ በተለይም ሰው በገዛ ምኞቱ ሲሳብ በወጣትነት ዘመን ምንም አእምሮው የበሰለ ቢሆንም እንኳ ራሱን መግዛት ካልቻለ በብዙ ነገር ይፈተናል፡፡

ራስን ከመግዛት ጋር እንደ ምሳሌ ከምናነሣቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች መካከል አንዱ የዮሴፍ ወልደ ያዕቆብ ታሪክ ነው፡፡ በወንድሞቹ ተንኮልና ምቀኝነት ከተጣለበት ጉድጓድ አውጥተው ወደ ባዕድ ሀገር (ግብጽ) ሸጡት፡፡ ዮሴፍ የፈርዖን ጃንደረባ የመጋቢዎቹም አለቃ የሚሆን የግብጽ ሰው ጲጢፋራ ወደ ግብጽ ካወረዱት ከይስማኤላውያን እጅ ገዛው፡፡ “እግዚአብሔር ከዮሴፍ ጋር ነበር፤ ሥራውም የተከናወነለት ሰው ሆነ፤ በግብፃዊው ጌታው ቤትም ተሾመ፡፡” እንዲል ለባርነት የተሸጠው ዮሴፍ እግዚአብሔር በግብጽ ምድር ከፍ ከፍ አደረገው፡፡ (ዘፍ. ፴፱፥፩-፲፰)፡፡

ነገር ግን የጌታው ሚስት በዮሴፍ ላይ ዐይኗን በመጣሏ ከእርሷም ጋር እንዲተኛ ጠየቀችው፡፡ ዮሴፍ ግን “በእግዚአብሔር ፊት እንዴት ኃጢአትን እሠራለሁ?” (ዘፍ. ፴፱፥፱) በማለት የቀረበለትን ጥሪ እምቢ አለ፡፡ ታገለችውም፤ ልብሱንም በእጇ ትቶላት ሸሸ፡፡ በዚህም ምክንያት ለእሥር በመዳረግ፣ መከራም እስከ መቀበል ድረስ ጸና፡፡ ይህም በቀላሉ የተገኘ ድል አልነበረም፤ ራሱንም በመግዛት ከክፉ ጋር ባለመተባበር ሰውነቱንም ከርኩሰት ጠበቀ፡፡ ዮሴፍ ወጣት ነው፤ ነገር ግን የእግዚአብሔርን ክብር፣ ጠባቂነቱም እንደማይለየው በማመን እምቢ ማለትን መረጠ፡፡ በዘመኑም እንደነበሩት ወጣቶች ከኃጢአት ጋር አልተባበረም፡፡ እግዚአብሔርም በግብጽ ምድር አዛዥ አደረገው፤ በክብርም ላይ ክብርን አጎናጸፈው፡፡

እግዚአብሔርን መፍራት፡-

“ልጆቼ ኑ ስሙኝ፤ እግዚአብሔርን መፍራት አስተምራችሁ ዘንድ” (መዝ. ፴፫፥፲፩) በማለት ነቢየ እግዚአብሔር እንደተናገረው ወጣቶች እግዚአብሔርን በመፍራት፣ በፊቱም መልካምን በማድረግ እንደ ቃሉ መመላለስ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ወጣት ነኝና በዚህ ዕድዬ ማየት ያለብኝን ሁሉ ማየት አለብኝ በማለት ተፈትቶ እንደተለቀቀ እምቦሳ ፈቃደ ሥጋቸውን ለማስደሰት መሮጥ አይገባቸውም፡፡ እግዚአብሔርን በመፍራት ቢኖሩ ከላይ እንዳየነው እንደ ዮሴፍ “በእግዚአብሔር ፊት ኃጢአትን አልሥራም” በማለት ክፉን በመጠየፍ የወጣትነት ዘመናቸውን በመንፈሳዊ ሕይወት ማነጽ አስፈላጊ ነው፡፡ ለክብር የሚያበቃው እርሱ ነውና፡፡

ጻድቁ ኢዮብ በዲያብሎስ በተፈተነና በተለያዩ መንገዶች እግዚአብሔርን ይክድ ዘንድ ሲፈትነው ሦስቱ ጓደኞቹ በማይገባ ምክር እግዚአብሔርን ይክድ ዘንድ ተከራክረውታል፡፡ እርሱ ግን በእግዚአብሔር ላይ ያለው እምነት ጽኑ ነውና “ሰውንም፡- እነሆ እግዚአብሔርን መፍራት ጥበብ ነው፤ ከክፉ መራቅም ማስተዋል ነው” ሲል መልሶላቸዋል፡፡ (ኢዮ. ፳፰፥፳፰) እግዚአብሔርን በመፍራት መኖርም ለበለጠ ክብር እንደሚያበቃ ከጻድቁ ኢዮብ መማር ተገቢ ነው፡፡

ዕውቀትን መፈለግ፡-

ዕውቀት ሁሉ ወደ መልካም መንገድ ይመራል ማለት አይቻልም፡፡ መልካሙንና ክፉውን መመርመርና ወደ ቀናውም መንገድ ለመጓዝ ፈቃደ እግዚአብሔርን መጠየቅ፣ በመምህራንም መታገዝ ይገባል፡፡ በቃል የተነገረ፣ በመጽሐፍ የሰፈረ ሁሉ ዕውቀት ልንለው አንችልም፤ ወደ ጠማማው መንገድ የሚመሩ፣ እግዚአብሔርንም ከማወቅ የሚለዩ አሉና ጥንቃቄን ይሻል፡፡ “እነሆ ከእኔ አስቀድመው በኢየሩሳሌም ላይ ከነበሩት ሁሉ ይልቅ ጥበብን አበዛሁ፤ ልቤንም ለጥበብና ለዕውቀት ሰጠሁ፡፡” በማለት ጠቢቡ ሰሎሞን እንደተናገረው በወጣትነት ዘመን በኦርቶዶክሳዊ ትምህርት የተቃኘ ጥበብንና ዕውቀትን መፈለግ ተገቢ ነው፡፡ (መክ. ፩፥፲፮)

በተለይም ወጣቶች አባቶቻችን እግዚአብሔር ገልጾላቸው በእምነት ጸንተው የመረመሩትና ለትውልድ ያስተላለፉትን መንፈሳዊ ዕውቀት መገብየት፣ መጻሕፍትን መመርመር በሁለት ወገን የተሳለ ሰይፍ ሆነው እንዲወጡ ያስችላቸዋል፡፡ “ስለዚህ የቀደመውን ትውልድ ጠይቅ፣ አባቶችንም በየወገናቸው በትጋት መርመምር” ሲል ጻድቁ ኢዮብ እንደተናገረው ለሕይወት ጠቃሚና መንፈሳዊነትን የሚጨምረውን ዕውቀትና ጥበብ መፈለግ፣ እርሱንም አጥብቆ መያዝና እንደ ቃሉም መጓዝ ከወጣቶች ይጠበቃል፡፡ (ኢዮ. ፰፥፰)

መንፈሳዊ ምግባራትን መፈጸም፡-

ጾም ጸሎት፣ ስግደት፣ ምጽዋት እና ሌሎችንም መንፈሳዊ ምግባራት ከወጣቶች ሕይወት ጋር የተቆራኘ ሊሆን ይገባዋል፡፡ መንፈሳዊ ምግባራትን ይዞ የተገኘ ወጣት የኑፋቄ ትምህርቶች እንደ ወጀብ ቢወርዱ እንኳን አይደናገጥም፡፡ ዲያብሎስ መንፈሳውያን ወጣቶችን ለማሰናከል በዙሪያቸው ይዞራልና እነዚህን ምግባራት በመፈጸም ድል መንሣት ያስፈልጋል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ የጴጥሮስ በመልእክቱ “እንግዲህ አዋቆች ሁኑ፤ ትጉም፤ ጠላታችሁ ጋኔን የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሣ አንበሳ ይዞራልና፡፡ እርሱንም በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት” (፩ኛጴጥ. ፭፥፰) በማለት እንደነገረን መንፈሳዊ ትጥቅ የሆኑትን በጎ   ምግባራት በመፈጸም ማሸነፍ ያስፈልጋል፡፡

በንስሓ ሕይወት መመላለስ፣ ቅዱስ ሥጋውን እና ክቡር ደሙን በመቀበል መንፈሳዊ ሕይወትን ማጽናት ከአንድ ኦርቶዶክሳዊ ወጣት ይጠበቃል፡፡ በየጊዜው ዲያብሎስ አቅጣጫውንና ዓይነቱን እየለዋወጠ ለሚያመጣቸው ፈተናዎችና ውጣ ውረዶች ባለመደናገጥ መንፈሳዊውን ጋሻ መያዝ ተገቢ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለኤፌሶን ሰዎች በላከው መልእክቱ “ስለዚህም በክፉ ቀን መቃወም እንድትችሉ የእግዚአብሔርን ጋሻ ያዙ፤ እንድትጸኑም በሁሉ የተዘጋጃችሁ ሁኑ” እንዲል ወጣቶች ለመንፈሳዊ ምግባራት ልዩ ትኩረት ሰጥተው ዲያብሎስ የሚያመጣውን ፈተና ድል መንሣት ይጠበቅባቸዋል፡፡ (ኤፌ. ፮፥፲፫)

በአጠቃላይ መንፈሳዊ ወጣቶች በኦርቶዶክሳዊ አኗኗር የተቃኙ፣ ራሳቸውንም የሚያንጹ እና የሚመጡባቸውን ፈተናዎች ሁሉ በመንፈሳዊ መንጽር በመቃኘት እንዳይወድቁም እየተጠነቀቁ መንፈሳዊውን ጎዳና መጓዝ ይገባቸዋል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ “እንግዲህ ወገባችሁን በእውነት ታጥቃችሁ ቁሙ፤ የጽድቅንም ጥሩር ልበሱ፡፡ ከዚህም ሁሉ የሚንበለበሉ የክፉ ፍላጻዎች ሁሉ ማጥፋት እንድትችሉ የእምነትን ጋሻ አንሡ፡፡ … ይኸውም የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡” በማለት ለኤፌሶን ሰዎች እንዳስተማረው ወጣቶች ቃለ እግዚአብሔርን እውነተኛ ጋሻቸው ማድረግ፣ በዲያብሎስም ላይ በመሠልጠን ድል መንሣት ያስፈልጋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ሕንጸተ ቤተ ክርስቲያን

በኬልቄዶን አውራጃ በቂሣርያ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ያለ እንጨት፣ ያለ ጭቃና ያለ ውኃ በሰኔ ፳ ቀን ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሦስት ድንጋዮች ቤተ ክርስቲያን ያነጸበት ዕለት የከበረ በዓል ነው፡፡

ይህም የሆነው ቅዱስ ጳውሎስና ቅዱስ በርናባስ ወደ ፊልጵስዩስ ገብተው በክርስቶስ ስም አሳምነው ብዙ አሕዛብን ካጠመቁ በኋላ ቤተ ክርስቲያን ሊሠሩላቸው ፈልገው በተነሡበት ጊዜ ነበር፡፡ ቤተ ክርስቲያኗንም ለመሥራትም ለርእሰ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ መልእክት ላኩበት፡፡ ከቅዱስ ጳውሎስ እና ቅዱስ በርናባስ ጋር በኢየሩሳሌም ተገናኙ፤ ቅዱስ ዮሐንስም ከቅዱስ ጴጥሮስ ጋር አብሮ መጥቶ ነበር፡፡

በዚያም በአንድነት ሱባዔ ይዘው በለመኑት ጊዜ ጌታችን የሞቱትን አስነሥቶ፣ ያሉትንም ጠርቶና ቅዱሳን ሐዋርያትን በፊልጵስዩስ ሀገር ሰብስቦ “በእናቴ በድንግል ማርያም ስም ከጽንፍ እስከ ጽንፍ የሚሠራውን የአብያተ ክርስቲያናት ሥራ ላሳያችሁ፤ ሥርዓቱንም ላስተምራችሁ ሰብስቢያችኋለሁ” ብሎ ወደ ምሥራቅ ይዟቸው ወጣ፡፡ (መጽሐፈ ሥንክሳር ሰኔ ፳ ቀን)

በዚያ ሥፍራ የነበሩትን ሦስት ድንጋዮችንም የተራራቁትን አቀራርቦ፣ ጥቃቅኑን ታላላቅ አድርጎ ቁመቱን በ፳፬ ወርዱን በ፲፪ ክንድ ለክቶ ለቅዱሳን ሐዋርያት ሰጣቸው፡፡ ከዚህ በኋላ ቅዱሳን ሐዋርያት ድንጋዩ በእጃቸው ላይ እየተሳለ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑን ሠርተው ፈጽመውታል፡፡ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑም የተሠራው ጌታችን በዐረገ በ፲፱ኛው፣ እመቤታችን በዐረገች በ፬ኛው ዓመት ሰኔ ፳ ቀን ሲሆን በማግሥቱ በ፳፩ኛው ቀን ኅብስት ሰማያዊ፣ ጽዋዕ ሰማያዊ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ወረደ፡፡ ጌታችንም ከእመቤታችን ጋር ከሰማየ ሰማያት መጥቶ እመቤታችንን ታቦት፣ ሐዋርያትን ልዑካን አድርጎ፣ እርሱ ሠራዒ ካህን ሆኖ ቀድሶ አቆረባቸው፡፡

ከዚያም በኋላ “ከዛሬ ጀምሮ እናንተም እንደዚህ አድርጉ” ብሎ አዟቸው በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐርጓል፡፡ የሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ቁመት የ፳፬ቱ ካህናተ ሰማይ አምሳል ነው፤ ወርዱ ደግሞ የ፲፪ቱ ሐዋርያት ምሳሌ ነው፡፡ አንድም ሦስቱ ድንጋዮች የሥላሴ አምሳል ምሳሌ ናቸው፤ ከታች አቀማመጣቸው ሦስት፣ ከላይ ሕንጻቸው አንድ መሆኑ የሥላሴን ሦስትነትና አንድነት ያስረዳል፡፡ የሠሩት ሦስት ክፍልም የመጀመሪያው ክፍል የታቦተ አዳም፣ ሁለተኛው የታቦተ ሙሴ፣ ሦስተኛው የታቦተ ኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ አንድም የሦስቱ ዓለማት ማለትም የጽርሐ አርያም፣ የኢዮር፣ የጠፈር ምሳሌ ነው፡፡ አንድም አንደኛው የኤረር፣ ሁለተኛው የራማ፣ ሦስተኛው የኢዮር አምሳል ነው፡፡ በኤረር፡- መላእክት፣ መኳንንት፣ ሊቃናት፤ በራማ፡- ሥልጣናት፣ መናብርት፣ አርባብ፤ በኢዮር፡- ኃይላት፣ ኪሩቤል፣ ሱራፌል ይኖራሉ፡፡ እነዚህ ዘጠኙ ነገደ መላእክት የዘጠኙ መዓርጋተ ቤተ ክርስቲያን (መዓርጋተ ክህነት) አምሳል ሲሆኑ ይኸውም መላእክት የመዘምራን፣ የመኳንንት የአናጕንስጢሳውያን፣ ሊቃናት የንፍቀ ዲያቆናት፣ ሥልጣናት የዲያቆናት፣ መናብርት የቀሳውስት፣ አርባብ፣ የቆሞሳት፣ ኃይላት፣ የኤጲስ ቆጶሳት፣ የሱራፌል፣ የጳጳሳት፣ የኪሩቤል እንዲሁም የሊቃነ ጳጳሳት ምሳሌዎች ናቸው፡፡

ይህም በምድር የሚኖሩ ደቂቀ አዳም ከቅዱሳን በቀር ወደ ሰማይ መውጣት እንደማይቻላቸውና ከመዘምራን እስከ ጳጳሳት ድረስ ያሉ ካህናትም ከእነርሱ በላይ ያሉትን መዓርግ መሥራት እንደማይቻላቸው ያስረዳል፡፡ እንደዚሁም መላእክት ወደ ምድር መውረድ እንደሚቻላቸውና ሊቃነ ጳጳሳትም ከእነርሱ በታች ያሉ ካህናትን ተልእኮ መፈጸም እንደሚቻላቸው ያስረዳል፡፡ በጽርሐ አርያም መንበረ ብርሃን፣ ታቦተ ብርሃን፣ መንጦላዕተ ብርሃን እንደዚሁም ፬ ፀወርተ መንበር፣ ፳፬ አጠንተ መንበር (መንበሩን የሚያጥኑ) መላእክት አሉ፡፡ ጽርሐ አርያም የመቅደስ፣ መንበረ ብርሃን የመንበር፣ መንጦላዕተ ብርሃን የቤተ መቅደሱ መጋረጃ፣ ፬ቱ ፀወርተ መንበር የ፬ቱ ሊቃነ ጳጳሳት ወይም የመንበሩ እግሮች፣ ፳፬ቱ አጠንተ መንበር የጳጳሳት (የኤጲስ ቆጶሳት) ምሳሌዎች ናቸው፡፡

ምንጭ፡-መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሰኔ ፳ ቀን እንዲሀም መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ ገጽ ፫፻፵፱-፫፻፶፩

“ዳግመኛ ልትወለዱ ይገባችኋል” (ዮሐ. ፫፥፯)

ይህንን ቃል የተናገረው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአይሁድ መምህር ለሆነው ኒቆዲሞስ በጥምቀት ዳግመኛ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊወርስ እንደማይችል ባስረዳበት ትምህርቱ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ ምንም እንኳን የአይሁድ መምህር ቢሆንም ምሥጢሩን እያመሠጠረ የኦሪትን ትምህርት ቢያስተምርም ስለ ዳግም መወለድ ምሥጢር ተሠውሮበት ጌታችንን ተደጋጋሚ ጥያቄዎችን ሲጠይቅ እንመለከታለን፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ላይ ለሠላሳ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ሲመላለስ ኢአማንያንን በትምህርቱ ፣ የታመሙትን በተአምራት እየፈወሰ፣ አምስት እንጀራና ሁለት አሣን አበርክቶ የተራቡትን አጥግቦ፣ የተጠሙትን አጠጥቶ እንደመሻታቸው ፈጽሞላቸዋል፡፡ ነገር ግን አምላክ ሲሆን የአዳምን ሥጋ ለብሷልና ራሱን “የእግዚአብሔር ልጅ” እያለ ይጠራል በማለት አይሁድ በምቀኝነት ተነሥተው በየጊዜው ይፈትኑት ነበር፡፡ በአንድ በኩል ከሮማውያን ቅኝ ግዛት ነጻ የሚያወጣቸው መሲሕ ይፈልጋሉ፤ በሌላ በኩል ደግሞ ለብዙ ዘመናት በሮማውያን በባርነት ቀንበር ስለ ተሰቃዩ ተስፋ ቆርጠው ነበር፡፡ መሲሕ ቢመጣ እንኳ ይመጣል ብለው የሚጠብቁት ጦር ይዞ፣ ሠራዊት አስከትሎ እንደሆነ ነበር የሚያምኑት፡፡ ለዚህም ነው የክርስቶስን መሲሕነት ያልተቀበሉት፡፡

ለዚህም ትልቅ ማሳያ የሚሆነን ከፈሪሳውያን ወገን የሆነው የኦሪት መምህሩ ኒቆዲሞስ ነው፡፡ በዚህም መሠረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህንን ሰው ለማሰብ የዐቢይን ጾም ሰባተኛ ሳምንት እሑድ በስሙ ሰይማ ታከብረዋለች፡፡ ተከታዮቿ ምእመናንም የእርሱን አሠረ ፍኖት እንዲከተሉ ትመክራለች፤ ታስተምራለችም፡፡

ኒቆዲሞስ ማነው?

ከአይሁድ መካከል ፈሪሳውያን ሕግን የሚያጠብቁ ቀሚሳቸውንም የሚያስረዝሙ፣   የማይፈጽሙትን ሕግ በሕዝብ ላይ የሚጭኑና ራሳቸውን ከሌሎች በላይ ከፍ የሚያደርጉ፣ የአብርሃምን ሥራ ሳይሠሩ አባታችን አብርሃም ነው እያሉ የሚመጻደቁ ናቸው፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ምንም እንኳ ፈሪሳዊ ቢሆንም አለቃ እንዲሆን በሮማውያን የተሾመ ባለ ሥልጣን ነው፡፡

ኒቆዲሞስ ለአይሁድ መምህራቸው ሲሆን የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርቱን ሰምቶ፣ ተአምራቱን አይቶ በፍጹም ልቡ ከእግሩ ሥር ቁጭ ብሎ የተሠወረውን ይገልጥለት ዘንድ ለመማር ራሱን ከዚህ ሕዝብ ለይቶ በፍጹም ልቡ ክርስቶስን ፍለጋ የመጣ ፈሪሳዊ ነው፡፡ በቀን በብርሃን ወደ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀርቦ ለመማር የአይሁድን ክፋትና ተንኮልን ያውቃልና ይህንን ፍራቻ በጨለማ አምላኩን ፍለጋ መጥቷል፡፡ “መምህር ሆይ ልታስተምር ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን” በማለትም መስክሯል፡፡ (ዮሐ. ፫፥፪)

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የኒቆዲሞስን ምስክርነት ሲሰማም “እውነት እውነት እልሃለሁ ዳግመኛ ያልተወለደ ሰው የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየት አይችልም” በማለት መልሶለታል፡፡ ኒቆዲሞስ ምሥጢሩ ቢረቅበትና መረዳት ቢሣነው “ሰው ከሸመገለ በኋላ ዳግመኛ መወለድ እንደምን ይችላል? ዳግመኛ ይወለድ ዘንድ ወደ እናቱ ማኅፀን ተመልሶ መግባት ይችላልን?” ሲል ጠይቋል፡፡ ጌታችንም የኒቆዲሞስን ጥያቄ “እውነት እውነት እልሃለሁ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ሰው ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፤ ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነውና ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነውና፡፡ ስለዚህ ዳግመኛ ልትወለዱ ይገባችኋል ስላልሁህ አታድንቅ” በማለት ለእግዚአብሔር ምንም የሚሣነው ነገር እንደሌለና የኒቆዲሞስ አመጣጥ ከልብ መሆኑን አውቆ ምሥጢረ ጥምቀትን (ዳግም ልደትን) ገለጸለት፡፡ (ዮሐ.፫፥፭-፯)

ኒቆዲሞስ ከጌታችን ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እግር ሥር ጭ ብሎ ተምሯልና በቀራንዮ አደባባይ ራሱን ለዓለሙ ቤዛ አድርጎ ሲሰጥ “እስከ ሞት ከአንተ አንለይህም” ያሉት ደቀ መዛሙርቱ ከዮሐንስ በቀር ሲበታተኑ፣ ቀራንዮ ላይ የተገኘው ኒቆዲሞስ ነበር፡፡ ጌታችን “ሁሉ ተፈጸመ” ብሎ ነፍሱን ከሥጋው ሲለይ ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ሆነው የክርስቶስን  ሥጋ ከአለቆች ለምነው በመገነዝ በአዲስ መቃብር ለመቅበር በቃ፡፡ በዚህ ምክንያት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የዐቢይ ጾም ሰባተኛው ሳምንት “ኒቆዲሞስ” በማለት ታከብራለች፡፡(ማቴ.፳፮፥፴፩-፴፭፤ ዮሐ. ፲፱፥፴)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

“የእግዚአብሔር ቀን እንደ ሌባ ድንገት ትመጣለች” (፪ጴጥ ፫፡፲)

መ/ር ቢትወደድ ወርቁ

በቤተ ክርስቲያን የሚከበሩ በዓላት በሙሉ ኃላፍያትን የሚያስታውሱና እነርሱንም በማሰብና በማክበር በረከት የሚገኝባቸው ሲሆኑ የደብረ ዘይት በዓል ግን ገና ያልተፈጸመውና ወደፊት ሊፈጸም ያለው ምጽአተ ክርስቶስ የሚታሰብበት በዓል ነው፡፡

ምጽአተ ክርስቶስ ማስተዋል የተሰጣቸው የሰው ልጆች የመጨረሻውን ፍርድ ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚቀበሉበት፣ ሰማይና ምድር የሚያልፉበት፣ መንግሥተ ሰማያት የምትገለጥበት ነው፡፡ ፃድቃን “እናንተ የአባቴ ቡሩካን ዓለም ሳይፈጠር የተዘጋጀላችሁን መንግሥት ትወርሱ ዘንድ ኑ፡፡” የሚለውን የሕይወት ቃል የሚሰሙበት፤ ኃጥአን ደግሞ “እናንተ የተረገማችሁ ለሰይጣንና ለመልእክተኞቹ ወደተዘጋጀው ወደ ዘለዓለም እሳት ሂዱ” የሚለውን ይግባኝ የሌለውን የእግዚአብሔርን የመጨረሻ ፍርድ የሚቀበሉበት ቀን ነው፡፡ (ማቴ ፳፭፡፴፬-፵፩)

ስለዚያች ቀን ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ሲያስተምር “ሰማያት የሚነዋወጡባትና የሚያልፉባት ቀድሞ የነበረው ፍጥረት ሁሉ በእሳት ነበልባል የሚቃጠልባት የእግዚአብሔር ቀን ግን እንደ ሌባ ድንገት ትመጣለች” (፪ጴጥ ፫፡፲) በማለት ተናግሯል፡፡ የክርስቶስን የምጽአት ቀን፤ ማሰብ ሲባል በቀኑ ሊሆኑ ያላቸው እነዚህን እያሰቡ መጨነቅ አይደለም ሊሆንም አይገባውም፤ ቀኑን እያሰባችሁ ተጨነቁ አልተባለምና፡፡ ወይም ደግሞ ለቀኑ አንዳች የሕይወት ዝግጅት ሳያደርጉ ንስሓ ሳይገቡ ከክፋት ሳይመለሱ “ጌታ ሆይ ና” በማለት ቀኑን መናፈቅም አይደለም፡፡ ይህንን በተመለከተ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለተሰሎንቄ ምእመናን ሲያስተምራቸው “ነገር ግን ወንድሞች ሆይ ስለ ጌታችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ መምጣትና ወደ እርሱ ስለ መሰብሰባችን በመንፈስ ወይም በቃል ወይም ከእኛ እንደሚመጣ በመልእክት የጌታ ቀን ደርሶአል ብላችሁ ከአእምሮአችሁ ቶሎ እንዳትናወጡ እንዳትደነግጡም እንለምናችኋለን፡፡” ብሏቸዋል (፪.ተሰ ፪፡፩-፪)

ስለ ቀኑ በማሰብ በመጨነቅና ቀኑን በመናፈቅ የተጎዱ ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ፡- ቢቢሲ የተባለው የዜና አውታር መጋቢት ፲፯ ቀን ፳፻ (እ.ኤ.አ.) ዘገባው በኡጋንዳ ውስጥ በምትገኝ ካኑንጉ በምትባል መንደር በፈረንጆቹ ሚሊኒየም ላይ የዓለም ፍፃሜ ይሆናል ብለው ያመኑና ራሳቸውን “የእግዚአብሔርን ዐሥርቱን ትእዛዛት የማስጠበቅና ዳግም የማደስ ንቅናቄ ቡድን” በማለት የጠሩ ሰባት መቶ አባላት ቤት ተዘግቶባቸው በእሳት እንዲቃጠሉ ሆነው ተጨፍጭፈዋል፡፡  (Uganda’s Kanungu cult massacre that killed 700 followers – BBC News)

በተመሳሳይ መንገድ “ጌታ ሊመጣ ነውና ይህን አድርጉ፤ ይህን ስጡ እንዲህ ዓይነት ስፍራ ሄዳችሁ ራሳችሁን ደብቁ ወዘተ” በሚሉ መልእክቶች ትዳራቸውን የበተኑ ሥራቸውን ትተው ለጉስቁልና፤ ትምህርታቸውን አቋርጠው ለማኅበራዊ ቀውስ የተዳረጉ ሰዎች አያሌ ናቸው፡፡ ሠርተው ኑሯቸውን ለውጠው ሀገራቸውን፣ ወገናቸውንና ቤተሰቦቻቸውንም መርዳት ሲገባቸው ውድና መተኪያ የሌለውን ጊዜያቸውን ሰውተው ለነዚህ የሐሰት ነቢያት አገልጋይ ሆነው የቀሩ ሰዎችም ብዙ ናቸው፡፡

ይህ ሊሆን ሰለሚችልም ጌታችን አስቀድሞ በደብረ ዘይት ለደቀ መዛሙርቱ ባስተማረው የምጽአት ትምህርቱ “በዚያን ጊዜ ማንም፡- እነሆ ክርስቶስ ከዚህ አለ፤ ወይም ከዚያ አለ ቢሏችሁ አትመኑ፤ ሐሰተኞች ክርስቶሶችና ሐሰተኞች ነቢያት ይነሣሉና ቢቻላቸውስ የተመረጡትን እንኳ እስኪያስቱ ድረስ ታላላቅ ምልክትና ድንቅ ያሳያሉ” በማለት አስጠንቅቆናል፡፡ (ማቴ. ፳፬፡፳፫-፳፭)

ሰዎችን ወደ ንስሓና እግዚአብሔርን ወደ ማመን ከማቅረብ ይልቅ በዚህ መንገድ የምጽአትን ቀን ምክንያት ሕዝብን በማስደንገጥና በማስደንበር ጥቃቅንና ዐበይት ምልክቶችን በማሳየት ወደ ራሳቸው በመምራት ገንዘቡን በመበዝበዝ ኑሮውን በማጎሳቆልና ከዚያም ሲያልፍ ሕይወቱንም በመንጠቅ ልቡን ከፍቶ የሰጣቸውን ሕዝብ መጫወቻ የሚያደርጉ ነቢያተ ሐሰት አሉ፡፡

በኢትዮጵያ ታሪክም በተመሳሳይ መንገድ ራሳቸውን “ክርስቶስ” አድርገው በመሾም ያሳቱ ለማሳትም የሞከሩ ሰዎች ነበሩ፡፡ እንደ ምሳሌም በዐሥራ ስድስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን በዐፄ ዘድንግል ዘመነ መንግሥት በአማራ ሳይንት በኩል “እኔ ክርስቶስ ነኝ” የሚል ሰው ተነሥቶ ነበር፡፡ ጌታ ያደረገውን በማስመሰል ዐሥራ ሁለት የሐሰት ሐዋርያት፣ ሰባ ሁለት የሐሰት አርድእት፣ ሠላሳ ስድስት የሐሰት ቅዱሳት አንስት አስከትሎ ትምህርቱን እስከ ማሠራጨት ደርሶ ነበር፡፡ንጉሡ ይህን ሰምተው በወታደር አስያዙት፤ ጭፍሮቹም ተበታተኑ፡፡ እርሱም ወደ ንጉሡ ቀርቦ ቢጠየቅ “አዎ እኔ ክርስቶስ ነኝ ከድንግል ማርያም ተወልጄ ሞቼ ተነሥቼ ወደ ሰማይም ዐርጌ ነበር፡፡ ከቤተ እሥራኤል በመወለዴ እሥራኤል ያልሆኑት ሁሉ ባዕድ አደረገን እንዳይሉኝ አሁን ደግሞ ከቤተ አሕዛብ ከምትሆን ከመርዐተ ወንጌል ተወለድኩ፡፡” አላቸው፡፡ (ወላጅ እናቱ መርዐተ ወንጌል ትባላለች) ንጉሡም “ሰይጣን በሰው እያደረ እንዴት ይጫወትብናል፡፡” ብለው በመገረም በሰይፍ እንዲቀጣ እንዳደረጉት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ይመሰክራል፡፡(ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ፡- የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ገጽ ፺፮)

በቅርቡ እንኳን በሀገረ ኬንያ ኤልዩድ ሲሚዩ የተባለ የ፰ ልጆች አባት “እኔ ኢየሱስ ክርስቶስ ነኝ!” በማለት ዐውጆ አያሌ ተከታዮችን አፍርቷል፡፡ ሚስቱም ኤን ቲቪ ከተባለ የቴሌቪዥን ጣቢያ ጋር ባደረገችው ቃለ ምልልስ የባሏን “ኢየሱስነት” በማስረጃ ለማረጋገጥ ስትሞክር “ባሌ ተራውን ውኃ ጥዑም ወደ ሆነ ሻይ ለውጦ አብዝቶአል፡፡ ብዙዎችም ከሻይው ቀምሰው በጣዕሙ ተገርመዋል፣ ወደ ቤታቸውም ወስደዋል” በማለት ተናግራለች፡፡

በተግባሩ የተበሳጩ ሰዎችም “ክርስቶስ ሕማምን ተቀብሎ እንደተሰቀለ፤ ኤልዩድ ሲማዩም ከስቅለት በዓል በፊት ተሰቃይቶ በመስቀል መሰቀል አለበት፤ ሞትንም አሸንፎ ይነሣ እንደሆነ እናያለን” በማለታቸው ይህ ሰው ፈርቶ ጥበቃ እንዲደረግለት ለፖሊስ እንዳመለከተ ኦፕላንዲያ የተባለው ድረ ገጽ በየካቲት ፳፱ ቀን ፳፻፲፭ ዓ ም (March 08,2023) ዘገባው አስነብቧል፡፡ (https://www.opindia.com/author/opindia/amp/)

ምን እናድርግ?

ዕለተ ምጽአት ሲታሰብ ክርስቲያኖች ሊጠይቁት የሚገባቸው ጥያቄ ምን እናድርግ? የሚለውን ጥያቄ ነው፡፡ ምን እናድርግ? ለሚለው ጥያቄም ቅዱሳት መጻሕፍት በስፋትና በጥልቀት መልስ የሰጡን ቢሆንም ጥቂቶቹን ጠቅለል አድርገን እንመልከት፡-

፩. እንጠንቀቅ

ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱሳን ደቀ መዛሙርቱ የመምጣትህና የዓለም መጨረሻ ምልክቱ ምንድነው? በማለት በጠየቁት ጊዜ ምልክቶችን ከነገራቸው በኋላ በመደጋገም “ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ” በማለት እስከ ዓለም ፍፃሜ የሚነሣው ትውልድ ሊያደርግ የሚገባውን ነገር አስተምሯል፡፡ (ማቴ. ፳፬፡፬) ዘመናችን እውነት በሚመስሉ ግን በሐሰት በተሞሉ ትምህርቶችና አስተሳሰቦች፤ እውነተኛ በሚመስሉ ነገር ግን ደግሞ እውነትን በየቀኑ እየገደሉ ለመቅበር በሚሞክሩ ሐሰተኞች የተሞላ ጊዜ ነው፡፡ አደገኛ የሚመስለውም ሐሰትና ሐሰተኞቹ ከእውነት ጋር እጅግ መመሳሰላቸው ነው፡፡ “የአምልኮት መልክ አላቸው ኃይሉን ግን ክደውታል፡፡” እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ (፪.ጢሞ. ፫፡፭)

. እንጠበቅ

ጌታችን በሁለተኛ ደረጃ ልናደርግ የሚገባን ነገር መጠበቅ እንደሆነ አስተምሮናል፡፡ “ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠበቁ፡፡” እንዲል (ማቴ ፳፬፡፮) መጠበቅ (ጠ) ፊደልን አላልተን ስናነብ ለካህናት ሥራቸው ሲሆን፤(ጠ) ፊደልን አጥብቀን ስናነብ ለምእመናን በአንድ ቦታ መወሰንን የእግዚአብሔርን ሕጉን ትእዛዙን መጠበቅን በሥርዓት መመላለስን ገንዘብ እንዲያደርጉ ያስገነዝባል፡፡ “ተጠበቁ!” ሲልም ከቤተ እግዚአብሔር አትውጡ፤ በሕገ እግዚአብሔር ጸንታችሁ ቁሙ፤ በሥርዓተ እግዚአብሔር ተመላለሡ በእምነት ጽኑ ማለቱ ነው፡፡

. እንዘጋጅ

ጌታችን በወንጌል “ስለዚህ እናንተ ደግሞ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ የሰው ልጅ በማታስቡበት ሰዓት ይመጣልና” በማለት እንዳስተማረን፡፡ (ማቴ ፳፬፡፵፬) መዘጋጀት በኃጢአት የተበላሸን አኗኗርና ሕይወት በንስሓ ማደስ በቅዱስ ሥጋውና በክቡር ደሙ ማተም ነው፡፡ (ራእ. ፯፡፲፬) መዘጋጀት ከተጣሉት ጋር መታረቅ፤ የሰረቁትን መመለስ፤ የበደሉትን መካስ፤ ከወደቁበት መነሣት ከርኩሰት መቀደስ ነው፡፡ መዘጋጀት የራስን ኃጢአት ብቻ እያሰቡ በሰው ከመፍረድ መቆጠብ ነው፡፡ መዘጋጀት አሁን እንደሚሞቱ ሆኖ ማሰብ ዘለዓለም እንደሚኖሩ ሆነው እግዚአብሔርን ማስደሰት ድርሻን መወጣትና እግዚአብሔርን መፍራትን፣ እምነትን፣ ራስን መግዛትን፤ ንስሓን፣ ትዕግሥትን፣ ሕሊናን መጠበቅን ገንዘብ አድርጎ መገኘት ነው፡፡

በቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ዕለተ ምጽአትን አስመልክቶ ከዋዜማው ጀምሮ የሚነበቡ ምንባባት፣ የሚዘመሩ መዝሙራት፣ የሚሰበከው ምስባክ ሁሉ ነገረ ምጽአትን የሚያስታውሱ ናቸው፡፡ ቀኑ ግን መቼ እንደሚሆን አናውቅም፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ “ክርስቶስ በሚመጣበት ጊዜስ ከወዴት እንደሆነ ማንም አያውቅም” እንዲል (ዮሐ. ፯፥፳፯)፡፡ ድንገት ባልታሰበ ጊዜ እንደሚመጣም “የእግዚአብሔር ቀን እንደ ሌባ ድንገት ትመጣለች” (፪ጴጥ ፫፡፲) በማለት ቅዱስ ጼጥሮስ በመልእክቱ እንደተናገረው በዘመናችን ሁሉ እንደ እግዚአብሔር ቃል መመላለስ፣ በንስሓ ራስን አዲስ አድርጎ ተዘጋጅቶ መጠበቅ ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር