ፈተና በክርስቲያናዊ የአገልግሎት ሕይወት

ለሜሳ ጉተታ

ክርስትና የተግባር ሕይወት ነዉ ፡፡ የክርስትና ሕይወት ተራ ኑሮ ብቻም ሳይሆን ዘለዓለማዊ ዓላማ ያለው ሕይወትም ጭምር ነዉ፡፡ በተጨማሪም የክርስትና ሕይወት እግዚአብሔርን እና ቅዱሳንን የምንመስልበት ሕይወት እንዲሁም ቅዱስ የምንሆንበት ሕይወት ነዉ፡፡ ቅዱሳንን እንድንመሰል የሚያደርገን የክርስትና ሕይወትን በሕይወት፣ በፍቅር፣ በቅድስና፣ በትዕግስት፣ በታማኝነት፣ በንጽህና መኖር እና መግለጥ ሲቻል ብቻ  ነዉ፡፡  ለዚህ ነዉ ሐዋርያው ቅዱስ ጰዉሎስ እኔ ክርስቶስን እንደምመስል እናንተም እኔን  ምሰሉ ያለን፡፡

የክርስትና ሕይወት  በመንፈሳዊነት ይገለጣል፡፡ ቃሉን በመማር፣ በመስማት፣ በሕይወትም በመግለጥ (በመኖር) ይገለጣል፡፡ “የክርስትና ሕይወት የቅድስና ሕይወት ነዉ”  ስንል ቅድስናዉ የሚገለጠዉ በአገልግሎት ሕይወት፣ ትጋት እና ፍቅር ነዉ፡፡ ክርሰትና አገልጋይነት ነዉ፤ ያዉም በታማኝነት እና በመንፈሳዊነት የምናከናውነው፡፡

አገልግሎት ለቅድስና ሕይወት ያበቃል፡፡ ከኃጢአት፣ ከክፋት፣ ከበደል፣ ከክፉ ምኞት ሐሳብ እና ተግባርም ይሠዉራል፡፡ ለፀጋ እግዚአብሔር፣ ለመንግሥቱና ለርሰቱም ያበቃል፡፡ ለበለጠ ፀጋ እና ክብርም ያደርሳል፡፡ ሰማያዊና ምድራዊ፣ መንፈሳዊ ሀብትን እና ክብርንም ያሰጣል፡፡ ማቴ ፡25፡ 14-30. መንፈሳዊ አገልግሎት፣ መንፈሳዊነት እና ክርሰትና ራስን መካድን፣ ራስን ማሸነፍን፣ ዓለምን መጥላትን/መተዉን፣ ለእግዚአብሔር ራስን አሳልፎ ማስገዛትን/መስጠትን ይፈልጋል፡፡ ‹‹ኑሮዬ ይበቃኛል›› ማለትን ይፈልጋል፡፡ ምክንያትን ማሸነፍን፣ ትዕግሰትን እና ማስተዋል ይጠይቃል ፡፡

የክርስትና ሕይወት በአገልግሎት ይገለጣል ስንል አገልግሎት ፈተና እንዳለዉም ደግሞ መርሳት የለብንም፡፡  መንፈሳዊ አገልግሎት መከራ ይበዛበታል፣ መዉጣት እና መዉረድ መዉደቅ እና መነሳትም አለው፡፡ ያለ ክርስትና ሕይወት መንፈሳዊነት የለም፤ የእግዚአብሔር ሰውም መሆን አይቻልም፡፡

እዉነተኛ አገልገሎት፣ የክርስትና ሕይወት እና  መንፈሳዊነት  ባለበት ቦታ ሁሉ መከራ እና ፈተና አለ፤ ያለ ፈተናም ጸጋን መቀበል አይቻልም፡፡ ለዚህም ነዉ ሐዋርያት በራሳቸው የተፈተነ ሕይወት ተግባራዊ ማሳያነት “ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በብዙ መከራ እንገባ ዘንድ ያስፈልገናል” እያሉ ያስተማሩት (የሐዋ.14፡21-22)፡፡ ይህም መከራ የደረሰባቸው በደስታ የሚቀበሉትና በመንፈስ የሚበለጽጉበት ሆኖላቸዋል፤ “… ቃሉን በብዙ መከራ ከመንፈስ ቅዱስ  ደስታ ጋር ተቀብላችሁ እኛና ጌታን የምትመስሉ ሆናችሁ፡” (1ተሰ. 1፡6) እንዲል፡፡

ቅዱስ ጳዉሎስ ለቆሮንቶስ ሰዎች በጻፈዉ መልእክቱ በመከራ ስለሚገኝ በረከት እንዲህ ያስተምረናል። “በብዙ መከራ ተፈትነው ሳሉ የደስታቸዉ ብዛትና የድኅነታቸው ጥልቀት የልግስናቸው ባለጠግንት አብዝቶአል።” (2ኛ ቆሮ.8፡2)፡፡ ፈተና በተለያዩ መንገዶች በተለያዩ ምክንያቶችም ሊመጣብን ይችላል፡፡  ለመባረክና  ለመዳንም በፈተና መጽናት ያስፈልጋል፡፡  ለዚህ ነዉ መጽሐፍ ቅዱሰ በተደጋጋሚ ‹‹እሰከ መጨረሻዉ የሚጸና እርሱ ግን ይድናል›› በማለት አጽንቶ የሚመክረን (ማቴ 10፡ ማቴ 24፡ ማር 13)፡፡

ፈተና የክርሰትያናዊ ሕይወት አንዱ መገላጫ ነዉ ፡፡ ያለፈተና በአገልግሎት እና በመንፈሳዊ ሕይወት ያለፉ ቅዱሳን የሉም፡፡ ይህን ሲያስረዳ ቅዱስ ጰዉሎስ 2ኛቆሮ. 11፡22-29 ላይ፡- “—–በድካም አብዝቼ፣ በመገረፍ አብዝቼ፣ በመታሰር አትርፌ፣ በመሞት ብዙ ጊዜ ሆንሁ፡፡ አይሁድ አንድ ሲጎድል አርባ ግርፋት አምስት ጊዜ ገረፉኝ፡፡ ሦስት ጊዜ  በበትር ተመታሁ፤  አንድ  ጊዜ  በድንጋይ  ተወገርሁ፤  መርከቤ ሦስት  ጊዜ  ተሰበረ፤  ሌሊትና ቀን በባሕር ውስጥ  ኖርሁ። ብዙ ጊዜ  በመንገድ ሄድሁ፤ በወንዝ  ፍርሃት፣ በወንበዴዎች  ፍርሃት፣  በወገኔ በኩል ፍርሃት፣  በአሕዛብ  በኩል  ፍርሃት፣  በከተማ ፍርሃት፣  በምድረ በዳ ፍርሃት፣  በባሕር ፍርሃት፣  በውሸተኞች  ወንድሞች በኩል ፍርሃት  ነበረብኝ፡፡ በድካምና በጥረት፣  ብዙ ጊዜም  እንቅልፍ  በማጣት፣  በረሀብና  በራቁትነት ነበርሁ። የቀረዉንም  ነገር ሳልቆጥር ዕለት ዕለት  የሚከብድብኝ የአብያተ ክርስቲያናት ሁሉ አሳብ ነው”  በማለት ስለ ክርሰቲያናዊ የአገልግት ሕይወት እና የመከራን ጥብቅ ቁርኝት ያስረዳናል ፡፡

የክርስቲያን  መንፈሳዊ የሕይወት ጉዞ  በድሎት እና በምቾት የተሞላ አይደለም፡፡ ይልቁንም በማያቋርጡ ተጋድሎዎች የተሞሸረ ነዉ እንጂ፡፡ ክርሰቲያናዊ ሕይወት ቅዱሳንን የምንመሰልበት እና ቅዱስ የምንሆንበት ሕይወት ነዉ፡፡ መከራ እና ፈተና የክርሰትና  የሕይወት ቅመም ነዉ፡፡ ከጸጋ ወደ ጸጋ ያሳድጋል፣ ያተጋል፣ ያበረታል፣ ለንሰሐ ሕይወት ያበቃል፣ ወደ ጾም እና ጸሎት ይመራል፡፡ ሁል ጊዜ ወደ ቤተ እግዚአብሔርም እንድንሄድ ሕይወታችንን በእርሱ ፍቃድ፣ ትእዛዝ እና ሀሳብም እንድንመራ ያደርጋል፡፡  ያለ ፈተናና  መከራ የክርስትና ሕይወት፣ ድኅነት እና ጽድቅ አይገኝም፡፡ መከራ ሲባል ደግሞ ልንችለዉና ልናሸንፈዉ ከምንችለዉ በላይ እንደማንፈተን መጽሐፍ እንዲህ ይነግረናል፡- ‹‹ከሚቻላችሁ መጠን ይልቅ ትፈተኑ ዘንድ የማይፈቅድ እግዚአብሔር የታመነ ነዉ፤ ትታገሡም ዘንድ እንድትችሉ ከፈተናዉ ጋር መዉጫዉን ደግሞ ያደርግላችኋል፡፡” (1ኛ ቆሮ 10፡13)

ክርስቲያን ለማመን ብቻ አልተጠራም፡፡ ለማገልገል፣ የቅድስና ሕይወትንም ለመኖር፣ ለመልካም ሥራ እና የእግዚአብሔርንም መንግሥት ለመዉረስ ጭምር ነዉ እንጂ፡፡ ለዚህ ነዉ መጽሐፍ ‹‹እግዚአብሔር ለቅድስና ጠርቶናል›› የሚለን (1ኛ ተሰ.4፡7)፡፡

ዳግመኛም የተጠራነው በስሙም መከራን ለመቀበል እና ለመፈተንም ጭምር ነው፡- ቅዱስ ጰዉሎስ ‹‹ስለ እርሱ መከራን ደግሞ ልትቀበሉ እንጅ በእርሱ ልታምኑ ብቻ አልተጠራችሁም››  በማለት ያሰተማረንም ይህንን ያስረዳል፡፡ ፊልጵ.(1፡29)

ሁሉም የሚደርስብን ፈተና ግን  በእግዚአብሔር ሰለአመንን በመልካም ሥራችን ነዉ ብሎ መዉሰድ ደግሞ አግባብነት የለውም፡፡ ከእግዚአብሔር የሚመጣብን ፈተና ከእምነታችን ጽናት፣ ከፍቅሩ  ጥልቀት እና ስፋት፣ ለበለጠ ፀጋ  እና ክብር እንበቃ ዘንድ በመንፈሳዊ ሕይወታችን  ጥንካሬ  ደረጃ የሚመጣብን ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ የአባታችን የአብርሃም  ፈተና እና የትዕግስተኛዉ አባታቸን ኢዮብ ዓይነት ፈተና ማለት ነዉ ፡፡

ግን በእኛ ስህተት፣ በኃጢአታችን ብዛት፣ ለትምህርት እና ለቅጣትም ጭምር  የሚመጣም ፈተና አለ፡፡  በዚህ ጊዜ ከኃጢአት መመለስ፣ ማዘንና ማልቀስ፣ ንሰሐም መግባት፣ መጾም እና መጸለይም  ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ ቅዱስ ያዕቆብ፡- ‹‹ማንም ሲፈተን በእግዚዚአብሔር እፈተናለሁ አይበል፤ እግዚአብሔር በክፉ አይፈትንምና፡፡ እርሱ ራሱስ ማንንም አይፈትንም፤ ነገር ግን እያንዳንዱ በራሱ ምኞት ሲሳብ እና ሲታለል ይፈተናል ፡፡ ከዚህ በኋላ ምኞት ፀንሳ ኃጢአትን ትወልዳለች፣ ኃጢአትም ካደገች በኋላ ሞትን ትወለዳለች›› በማለት ይመክረናል፡፡ ያዕ. 1፡13.

ስለዚህ ክርስቲያን ሲኖር እንዴት መኖር አለበት? ስንል፡- ‹‹ስለዚህም ምክንያት ትጋትን ሁሉ እያሳያችሁ በእምነታችሁ በጎነትን ጨምሩ፡፡ በበጎነትም እዉቀትን፣ በእዉቀትም ራስን መግዛትን፣ ራስንም በመግዛት መጽናትን፣ በመጽናትም እግዚአብሔርን መምሰልን፣ እግዚአብሔርንም በመምሰል የወንድማማች መዋደድ፣ በወንድማማችም መዋደድ ፍቅርን ጨምሩ›› የሚለንን ቃሉን መሠረት እና የሕይወታችን መመርያ በማድረግ መኖር አለብን፡፡ (2ኛ ጴጥ ፡ 1፡5-8)

የክርስትና ሕይወት  ማስተዋል፣ እምነት እና ትእግስትን ይጠይቃል፡፡ ዝም ብሎ በሰዉ ከመነዳት መጠበቅ አለብን፡፡ የዓላማ ሰዉ መሆን ይኖርብናል ፡፡ የተፈጠርንበትን ዓላማ እና ክብርንም መርሳት የለብንም፡፡ የስም ሳይሆን የተግባር እና የሕይወት ክርሰቲያን ሆነን  ክርስትናንም በሕይወት ገልጠን  ለመንግሥቱ እና ለክብሩ እንዲያበቃን የእርሱ የአምላካችን መልካም ፍቃድ ይሁንልን፤ አሜን ፡፡

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *