“የጻድቅ መታሰቢያ ለዘለዓለም ይኖራል”(መዝ.፻፳፮፥፮)

ሐምሌ አምስት ቀን በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከሚከበሩ በዓላት ውስጥ የክቡራን የዐበይት አባቶቻችን የቅዱስ ጴጥሮስና የቅዱስ ጳውሎስ የሰማዕትነታቸው መታሰቢያ ዕለት ነው፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ አሣ አጥማጅ ነበር፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን አኢየሱስ ክርስቶስ ከመረጣቸው ፲፪ቱ ሐዋርያት መካከል አንዱ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከቅዱስ ጴጥሮስ በፊት ወንድሙ እንዲርያስን የጠራው ሲሆን ለሐዋርያነት ከተመረጠበት ጊዜ አንስቶ ከጌታችን እግር ሥር እየተከተለ በዋለበት እየዋለ፣ ባደረበት እያደረ የቃሉን ትምህርት፣ የእጁን ተአምራት እየሰማና እያየ የኖረ፤ አስከ ሕይወቱ ፍፃሜም የተጠራበትን የሐዋርያነት አገልግሎት በተጋድሎ የፈጸመ፣ ጌታችንም በሐዋርያት ሁሉ ላይ አለቃ አድርጎ የሾመው፣ በኋላም በመስቀል ላይ ቁልቁል ተሰቅሎ በሰማዕትነት ያረፈበት ዕለት ነው፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ “የሰውን ልጅ ሰዎች ማን ይሉታል?” ብሎ በጠየቀ ጊዜ ቅዱስ ጳጥሮስ ከሐዋርያት መካከል “አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ” ሲል መስክሯል፡፡ በዚህም ምክንያት “አንተ ዐለት ነህ በዚህችም ዐለት ላይም በቤተ ክርስቲያኔን እሠራታለሁ፤ የሲዖል በሮችም አይበረቱባትም፤ የመንግሥተ ሰማያትንምመክፈቻዎች እሰጥሃለሁ” ብሎ ጌታችን የመሠከረለትና የሐዋርያት ሁሉ አለቃ አድርጎ የሾመው ሐዋርያ ነው፡፡(ማቴ.፲፮፥፲፫-፲፱)፡፡

፲፪ቱ ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ በወረደላቸው ዕለትም ሦስት ሺህ ሰዎችን በስብከቱ ያሳመነ ታላቅ ሐዋርያ ነው፡፡ በጥላውና በለበሰው ልብሱ ታላላቅ ተአምራትንም በማድረግ፣ ወንጌልንም በልዩ ልዩ ቦታዎች እየተዘዋወረ ያለ ፍርሃት አስተምሯል፡፡ ነገር ግን በቅዱስ ጴጥሮስ የወንጌል ትምህርት ብዙዎችን ወደ ክርስትና እየመለሰ፣ ጣዖታትን እያጠፋ ስላስቸገራቸው የሮሜ መኳንንት ሊገድሉት ተስማሙ፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም እንዲገድሉት መስማማታቸውን በሰማ ጊዜም ልብሱን ቀይሮ ከሮሜ ከተማ ሲወጣ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ተሸክሞ ወደ ከተማ ሲገባ አገኘው፡፡ “አቤቱ ጌታዬ ወዴት ትሄዳለህ?” አለው፡፡ ጌታችንም “ልሰቀል ወደ ሮሜ ከተማ እሄዳለሁ” ብሎ መለሰለት፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም “አቤቱ ዳግመኛ ትሰቀላለህን?”አለው፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ “ጎልማሳ ሳለህ ወገብህን በገዛ እጅህ ታጥቀህ ወደ ወደድከው ትሄዳለህ፤ በሸመገልክ ጊዜ ግን እጅህን ታነሣና ሌላ ያስታጥቅሃል” ያለውን የጌታችንን ቃል አሰበ፤ አስተዋለውም፡፡ ተጸጽቶም ወደ ሮሜ ተመለሰ፡፡ ንጉሡ ኔሮንም እንዲሰቅሉት አዘዘ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ግን “እንደ ጌታዬ ልሰቀል አይገባኝምና ቁልቁል ስቀሉኝ” በማለቱ ቁልቁሊት ተሠቅሎ ሰማዕትነት ተቀብሏል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ሐምሌ ፭ ቀኑን ታስበዋለች፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ ሁለት መልእክታትንም ጽፏል፡፡

በዚህም ቀን የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስ መታሰቢያው ነው፡፡ ሳውል ቀድሞ ሕገ ኦሪትን ጠንቅቆ የሚያውቅና ክርስቲያኖችን የሚያሳድድ ሰው ነበር፡፡ ክርስቲያኖችንም ለማሰቃየትና ለመግደል ደብዳቤ ለምኖ ወደ ደማስቆ አቅራቢያ ሄደ፡፡ ደማስቅ በደረሰ ጊዜም ከሰማይ መብረቅ ብልጭ ብሎበት በምድር ላይ ወደቀ፡፡ ወዲያውም “ሳውል፣ ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ?” የሚል ድምጽ ሰማ፡፡(ሐዋ.፱፥፬)፡፡

ሳውልም “አቤቱ አንተ ማነህ?” አለ፡፡ ጌታችንም “አንተ የምታሳድደኝ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ፤ በሾለ ብረት ላይ ብትረግጥ ለአንተ ይብስብሃል” ሲል ተናገረው፡፡ “አቤቱ ምን እንዳደርግ ትሻለህ?” ሲል ጠየቀ፡(ሐዋ.ሐዋ.፱፥፭-፮)፡፡ ጌታችንም ከደቀ መዛሙርት አንዱ ወደሆነው ሐናንያ እንዲሄድ ነገረው፡፡ ዐይኖቹም ታውረው ነበር፡፡ ሳይበላና ሳይጠጣም በደማስቆ ለሦስት ቀናት ቆየ፡፡ ሐናንያም ባገኘው ጊዜ “ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ታይ ዘንድ፣ የመንፈስ ቅዱስንም ጸጋ ይሞላብህ ዘንድ ወደ አንተ ልኮኛል” አለው፡፡ ከሳውል ዐይኖች ላይም ቅርፊት መሰል ነገር እየተቀረፈ ወደቀ፡፡ ለማየትም ቻለ፤ ወዲያውም ተጠመቀ፤ ምግብም በልቶ በረታ፡፡ ክርስቶስ የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅነትንም መሰከረ፡፡ ስሙም ጳውሎስ ተባለ፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ የተጠራበትን ተልእኮ ለመፈጸም እየተዘዋወረ የክርስቶስን ወንጌል እየሰበከ ታላላቅ ተአምራትንም ማድረጉን ቀጠለ፤ ወደ ሮሜ ከተማም ገብቶ በስብከቱ ብዙዎች ሰዎች አምነው አጠመቃቸው፡፡ ነገር ግን ንጉሡ ኔሮን ቅዱስ ጳውሎስን ይዞ ከፍተኛ ሥቃይ አደረሰበት፡፡ በመጨረሻም አንገቱ ተሰይፎ እንዲሞት ተፈርዶበት ሐምሌ ፭ ቀን ሰማዕትነትን ተቀበለ፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ አሥራ አራት መልእክታትን ጽፏል፡፡

ምንጭ፡- ስንክሳር

ገድለ ሐዋርያት

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

2 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *