በዓለ ግዝረት

እግዚአብሔር የግዝረት ሥርዓትን ለአበ ብዙኀን አብርሃም የሰጠው የቃል ኪዳን ምልክት ነው። እግዚአብሔርም አብርሃምን አለው፡- “አንተ ደግሞ ቃል ኪዳኔን ትጠብቃለህ፤ አንተ፣ ከአንተም በኋላ ዘርህ በትውልዳቸው፡፡ በእኔና በአንተ መካከል፣ ከአንተም በኋላ በዘርህ መካከል የምትጠብቋት ቃል ኪዳኔ ይህች ናት፤ ከእናንተ ወንድ ሁሉ ይገረዝ፡፡ የሰውነታችሁን ቊልፈት ትገረዛላችሁ፤ በእኔና በእናንተ መካከል ላለውም ቃል ኪዳን ምልክት ይሆናል” በማለት ቃል ኪዳንን አኖረ፡፡ (ዘፍ.፲፯፥፯-፲፬) በሊቀ ነቢያት ሙሴ ዘመንም ግዝረት የእስራኤል ሕዝብ ምልክት ነበር። እግዚአብሔርም ሙሴንና አሮንን አላቸው፡- ”ይህ የፋሲካ ሕግ ነው፤ ከእርሱ ባዕድ ሰው አይብላ፡፡ አገልጋይ ወይም በብር የተገዛ ቢኖር ከተገረዘ በኋላ ያን ጊዜ ከእርሱ ይብላ” (ዘፀ. ፲፪፥፵፫)

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ግዝረትን በተመለከተ “ኦሪትንም ብትፈጽም ግዝረት ትጠቅምሃለች፤ ኦሪትን ባትፈጽም ግን ግዝረትህ አለመገዘርህ ትሆንብሃለች፡፡ አንተ ሳትገዘር ብትኖር ኦሪትንም ብትጠብቅ አለመገዘርህ መገረዝ ትሆንልሃለች፡፡” (ሮሜ. ፪፥፳፭) በማለት ለሮሜ ክርስቲያኖች በላከው መልእክቱ ጽፎላቸዋል፡፡ ይህም የሥጋን ሸለፈት መገረዝ ሳይሆን የልብ መለወጥና በእግዚአብሔር ማመን፣ ሕጉንም መፈጸም እንደሆነ ያመለክተናል፡፡ ይህንንም ሲያጸና “የእግዚአብሔርን ትእዛዝ መጠበቅ ነው እንጂ መገዘርም አይጠቅምም፤ አለመገረዝም አይጎዳም፡፡” (ቆሮ.፪፥፲፱) እንዲል፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ኦሪትና ነቢያትን ልሽራቸው የመጣሁ አይምሰላችሁ፤ ልፈጽማቸው እንጂ ልሽራቸው አልመጣሁም፡፡” እንዳለ (ማቴ.፭፥፲፯) እርሱ ራሱ ይገረዝ ዘንድ ሥርዓቱንም ለመፈጸም ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደ በስምንተኛው ቀን ወደ ቤተ መቅደስ በወሰደችው ጊዜ ተገርዞ ተገኝቷል እንጂ በፍጡራን እጅ አልተገረዘም። የገራዡ ምላጭም በገራዡ እጅ እንዳለ ውኃ ሆኖ ተገኝቷል (መጽሐፈ ስንክሳር ጥር ስድስት)። ይህም በመለኮታዊ ኃይሉ ነው።

በዚህም ምክንያት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን የግዝረት በዓል በየዓመቱ ጥር ፮ ቀን ታከብራለች (መጽሐፈ ስንክሳር ጥር ስድስት)። ስሙም ገና በሥጋ ሳይፀነስ የእግዚአብሔር መልአክ ባወጣለት ስም “ኢየሱስ” ተብሎ ተጠራ፡፡ (ሉቃ. ፪፥፳፩-፳፬)

ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በኅቱም ድንግልና ተጸንሶ በኅቱም ድንግል መወለዱ እንደማይመረመር ሁሉ ግዝረቱም አይመረመርም፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተዘጋ ቤት ሐዋርያት ተሰብስበው ባሉበት ገብቶ እንደወጣ ሁሉ እርሱ በሚያውቀው ረቂቅ ጥበብ ከሥጋው ምንም ምን ሳይቈረጥ፣ ምንም ደም ሳይፈሰው ተገርዞ ተገኝቷል፡፡

ኢየሱስ ማለት መድኃኒት ማለት ሲሆን ይህ ስም የወጣለት በተወለደ በስምንተኛው ቀን ነው፡፡ ይህም በኦሪቱ ሥርዓት መሠረት ወንድ ልጅ በተወለደ በስምንት ቀን ከተገረዘ በኋላ ስም የማውጣት ልማድ አለና የኦሪትን ሕግ ለመፈጽም ይገረዝ ዘንድ ሄደ፡፡ ““ኦሪትና ነቢያትን ልሽራቸው የመጣሁ አይምሰላችሁ፤ ልፈጽማቸው እንጂ ልሽራቸው አልመጣሁም፡፡” እንዲል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *