ጾመ ጋድ(ገሃድ)

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ካሏት ሰባቱ የአዋጅ አጽዋማት መካከል አንዱ ጾመ ጋድ(ገሃድ) ነው፡፡ ገሃድ ማለት ለውጥ(ምትክ) ወይም ልዋጭ፤ እንዲሁም ግልጥ፣ ተገላጭ በማለት ይተረጎማል፡፡ ይህንንም ደስታ ተክለ ወልድ በመዝገበ ቃላት መጽሐፋቸው ጋድ(ገሃድ) እንዲህ ይተረጉሙታል፡- “ገና፣ የጥምቀት ከተራ (የልደትና የጥምቀት ዋዜማ) እንደ ዐርብ ረቡዕ እና ፍልሰታ፣ እንደ ሑዳዴ የሚጾም፡፡ ትርጓሜው የሚገለጥ፣ ተገላጭ፣ ግልጥ ማለት ነው፡፡ ጌታችን እንደ ሰውነቱ በአጭር ቁመት፣ በጠባብ ደረት ተወስኖ መታየቱን ያስረዳል” (ደስታ ተክለ ወልድ መዝገበ ቃላት፤ ገጽ ፪፻፴፪)፡፡

ጥር ፲ የሚነበበው ስንክሳር በጥምቀት ዋዜማ መጾም እንደሚገባ ሲገልጽ፡- “በዚች ዕለት ምንም መብልን ሳይቀምሱ ምእመናን ሁሉ እስከ ምሽት ይጾሙ ዘንድ ከእኛ አስቀድመው የነበሩ ታላላቅ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን መምህራን ሥርዓትን ሠሩ፤ በምሽትም ቢሆን በታላቁ ጾም ከሚበላው በቀር ጥሉላትን አይቅመሱ፡፡ በዚህች ዕለት ምእመናን እስከ ምሽት እንዲጾሙት ያዘዙበት ምክንያት ይህ ነው፡- የልደትና የጥምቀት በዓል በረቡዕ ወይም በዐርብ ቀን ቢውል በበዓለ ሃምሳ የሚበላውን የጥሉላት መብል በጥዋት በመብላት ምእመናን ሁሉ በዓሉን እንዲያከብሩ አባቶቻችን ሐዋርያት አዝዘዋል፡፡ እሊህ ሁለቱ የእግዚአብሔር ታላላቅ በዓሎቹ ናቸውና፡፡”

ይህም ማለት ልደት እና ጥምቀት ረቡዕና ዐርብ ከዋሉ በዋዜማው ማክሰኞና ሐሙስ ይጾማሉ። ረቡዕና ዐርብ ምንም እንኳን የጾም ቀናት ቢሆኑም የፍስክ ቀን ሆነው ይከበራሉ። የልደት እና የጥምቀት በዓል እሑድ ቢውሉ በዋዜማው ቅዳሜ የጥሉላት ምግብ አይበላም። እንዲሁም ልደት እና ጥምቀት ሰኞ ቢውሉ እሑድ ጥሉላት አይበላም። እንደ ሌሎች የአጽማዋት ቀናት እህልና ውኃ ግን አይጾሙም።

ፍትሐ ነገሥት ስለ ጾም ሲገልጽ፡- “ጾምስ በሕግ ውስጥ በታወቀው ጊዜ የሰው ከምግብ መከልከል ነው፤ በደሉን ለማስተሥረይ ዋጋውንም ለማብዛት እርሱን ወዶ ሕግን ለሠራለት እየታዘዘ የፈቲውን ኃይል ያደክም ዘንድ ለነባቢት ነፍሱም ትታዘዝ ዘንድ” በማለት ይተረጉመዋል፡፡ በዚህ ጊዜ መጾም እንደሚገባም ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት ሠርታለች፡፡ (ፍትሐ ነገሥት ንባቡና ትርጓሜው፣ አንቀጽ ፲፭፥፭፻፷፬)

ጾም ወደ እግዚአብሔር የምታደርስ የነፍስ ምግብ ናትና ሥጋችንን ለነፍሳችን አስገዝተን ጾምን በመቀደስ የበረከቱ ተሳታፊዎች ያደርገን ዘንድ የአምላካችን እግዚአብሔር ፈቃድ ይሁን አሜን፡፡

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *