ታቦተ እግዚአብሔርን ከጣዖት ጋር አንድ የሚያደርግ ማን ነው? (፪ኛ ቆሮ. ፮፥፲፮)

በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርተ ወንጌልና ሐዋርያዊ አገልግሎት ማስተባበሪያ

በስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ዋና ክፍል የተዘጋጀ

የካቲት ፳ ቀን ፳፻፲ .

‹ታቦት› ማለት ‹የእግዚአብሔር ክብር መገለጫ፣ የእግዚአብሔር የክብሩ ዙፋን› ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ሙሴን በታቦት ላይ ኾኖ ያነጋግረው ነበር (ዘፀ. ፳፭፥፳፪፤ ዘኍ. ፯፥፹፱)፡፡ ሕገ እግዚአብሔር በወረቀት ላይ መጻፍ ሲጀምር ብዙ ምሥጢራት በእግዚአብሔር አንደበት ለሊቀ ነቢያት ሙሴ ተነግረዋል፡፡ ነቢዩ ሙሴ ከእግዚአብሔር ጋር ቃል በቃል ከተነጋገረባቸው አንዱ ምሥጢር ደግሞ ‹‹እንደ ቀደመው የድንጋይ ጽላት ቅረፅ›› የሚለው ትእዛዝ ነው፡፡ ኃይለ ቃሉም ‹‹እግዚአብሔር ሙሴን አለው፤ ሁለት የድንጋይ ጽላት እንደ ፊተኛው አድርገህ ቅረፅ፤ ወደ እኔም ወደ ተራራው ውጣ፡፡ በሰበርሃቸው በፊተኞቹ ጽላቶች የነበሩትን ቃላት እጽፍባቸዋለሁ፤›› የሚል ነው (ዘፀ. ፴፬፥፩-፪)፡፡ ከመጽሐፍ ቅዱሱ ንባብ ውስጥ በማያሻማ መልኩ እንደ ተመለከትነው ሙሴ በቀደሙት ጽላቶች ፈንታ ሌላ ጽላት እንዲቀርፅ ትእዛዝ ተሰጥቶታል፡፡ ዝቅ ብሎም ‹‹ሙሴም ሁለት ጽላት እንደ ቀደመው አድርጎ ቀረፀ›› በማለት ይደመድማል (ዘፀ.፴፬፥፬)፡፡

እንግዲህ ይህን ቃል እንዲሁ በዓይነ ሥጋም ኾነ በዓይነ ልቡና (ነፍስ) ለተመለከተው እግዚአብሔር በአንደበቱ ‹‹ታቦት ቅረፅ›› ብሎ ለሙሴ ሲናገር፣ ሙሴም ‹‹አሜን›› ብሎ ትእዛዙን ሲፈጽም ያሳያል፡፡ ይህም ብዙ ምሥጢር እንዳለው ግልፅ ነው፡፡ ለምን ቢሉ? አንደኛ ታቦት እንዲቀርፅ ሙሴ መታዘዙ ታቦት ለጊዜው ለእስራኤል ዘሥጋ የሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያና መማጸኛ እንዲኾን ነው፡፡ ሁለተኛ የፊተኛው ታቦት ከተሰበረ በኋላ ሁለተኛ ታቦት እንዲቀርፅ ሙሴ መታዘዙ ታቦት በቅዱሳን ስም እየተቀረፀ ለትውልደ ትውልድ እንደሚተላለፍ ለመግለጽ ነው፡፡ በሌላ አነጋገር የቀደሙት ጽላቶች በጣዖት ምክንያት ከተሰበሩ በኋላ ዳግመኛ እንዲቀረፁ ማዘዙ ታቦት አንድ ጊዜ ብቻ ለአምልኮት የሚፈለግ ከዚያ በኋላ የሚጣል እንዳልኾነ ለማስተማር ነው፡፡ የዚህ ዂሉ የምሥጢር መሠረት ግን ታቦቱ በብሉይም ኾነ በሐዲስ ኪዳን እስከ ወዲያኛው ሊኖር ከእግዚአብሔር መሰጠቱን እንድናውቅ ይረዳናል፡፡ ይህም ‹‹እንደ ቀደሙት ዂሉ ዐሠርቱ ቃላትን በዚህ ላይ እጽፋለሁ›› ማለቱ ነው፡፡

ስለዚህ በብሉይም ኾነ በሐዲስ ኪዳን ታቦቱ ላይ ዐሥሩ ቃላት መኖራቸው ነው፡፡ ከዐሥሩ ቃላት አንዱ ደግሞ ‹‹ከእኔ በቀር ሌሎች አማልክት አይኑሩህ›› የሚለው ትእዛዝ አንደኛው ነው (ዘፀ. ፳፥፫)፡፡ ከታቦቱ ላይ የእግዚአብሔር እንጂ የጣዖት ስም አልተጻፈበትምና፡፡ ለታቦት መስገዳችንም ይህን ሥርዓተ ምሥጢር በማወቅ እንጂ ባለማወቅ ለቅርፃ ቅርፅ ወይም ለጣዖት እየሰገድን አምልኮ ባዕድ እየፈጸምን አይደለም፡፡ እንግዲህ ስሙ ስመ አምላክ ከኾነ፣ ትእዛዙም ጣዖታዊ ሳይኾን አምላካዊ ከኾነ፣ በእግዚአብሔር ቃል አንደበት ታቦት እንዲቀርፅ ለሙሴ መለኮታዊ ትእዛዝ ከታዘዘ፣ ታቦት የስሙ ማረፊያ ኾኖ ሊኖር እንጂ በዘመን ሊሻር የሚችል አይደለም፡፡ ለምን ቢሉ በሊቀ ነቢያት ሙሴ ጊዜም ኾነ ዛሬ ከታቦቱ ላይ የታተመው ስመ አምላክ (የአምላክ ስም) ነውና፡፡

ሊቀ ነቢያት ሙሴ በተሰጠው ታቦት አምልኮተ እግዚአብሔርን ሲፈጽምበት ኑሮ ዐረፈ፡፡ ከእርሱ ቀጥሎ ኢያሱም እንደ ሙሴ ካህናቱን ታቦት አሸክሞ ወደ ምድረ ርስት ገባ፡፡ በኋላም ዳዊት ከአቢዳራ ቤት ወደ ኢያቡስ አስመጥቶ በቃል ኪዳኑ ታቦት ፊት ዘመረ፡፡ (ኢያ. ፫፥፩-፲፯፤ ፪ኛ ሳሙ. ፮፥፲-፲፪)፡፡ ቤተ አቢዳራ (የአቢዳራ ቤት) በታቦቱ እንደ ከበረ ዳዊትም በታቦቱ ሊከብር መፈለጉ የታቦቱን ክብር በመንፈሰ ትንቢት በማወቁ ነው፡፡ ስለዚህ ከሙሴ እስከ ዳዊት፣ ከዳዊት እስከ ልደተ ክርስቶስ ታቦት የእግዚአብሔር የክብሩ መገለጫ ኾኖ ሲሰገድለት ኑሯል፡፡ ወደፊትም በዚህ ሥርዓት ይቀጥላል፡፡

በሐዲስ ኪዳን ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰውን ሥጋ ተዋሕዶ፣ በመስቀል ተሰቅሎ፣ በከርሠ መቃብር ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት አድሮ፣ ከሙታን ተነሥቶ ወደ ዙፋኑ ሲያርግ ዐረገ፡፡ ከዚህ በኋላ አበው ሐዋርያት ወንጌልን አስተማሩ፡፡ በአንድ ቀን ትምህርት በእልፍ የሚቈጠሩ ምእመናን አመኑ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ የቆሮንቶስ ምእመናን በቀዳሚነት ይጠቀሳሉ፡፡ እነዚህ የቆሮንቶስ ምእመናንም አምነው ከተጠመቁ፣ ከጨለማ ከወጡ በኋላ የለመዱት ልማድ እንዲህ ቶሎ ሊለወጥ አይችልምና በቅዱስ ጳውሎስ መዋዕለ ስብከት እየሾለኩ ወደ ቤተ ጣዖት መሔዳቸው አልቀረም፡፡

ይህን የተረዳው ቅዱስ ጳውሎስ የታቦትን ቅዱስነት የጣዖትን ርኩስነት ሲገልጽ ታቦቱን ‹‹ታቦተ እግዚአብሔር›› ብሎ ጣዖቱን ‹‹ርኩስ›› በማለት ገለጸው፡፡ ይኸውም ‹‹የእግዚአብሔርን ታቦት በጣዖት ቤት ውስጥ የሚጨምር ማን ነው?›› (፪ኛ ቆሮ. ፮፥፲፮) ብሎ ካነጻጸረ በኋላ ወደ ጣዖት የሚገሰግሱ ባዕዳንን ሲመክር ደግሞ ‹‹ወደ ረከሱት አትቅረቡ›› ሲል መክሯቸዋል፤ አስተምሯቸዋል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ርኩስ›› ብሎ  የነቀፈው ጣዖቱን ሲኾን፣ ‹‹ታቦተ እግዚአብሔር›› ብሎ የገለጸው ደግሞ ታቦቱን ነው፡፡ እንግዲህ ታቦትና ጣዖት በቅዱስ ጳውሎስ አንደበት እንዲህ የሰማይና የምድርን ያህል ርቀት አላቸው፡፡

በሐዲስ ኪዳን ታቦት አያስፈልግም ለሚሉ ዂሉ ይህ ‹‹ታቦተ እግዚአብሔር›› ተብሎ በቅዱስ ጳውሎስ አንደበት የተመሰከረለት ታቦት ለመኖሩ በቂ ምስክር ነው፡፡ በሌላ አገላለጽ በቅዱስ ጳውሎስ ዘመን ጣዖት እንደ ነበረ ታቦትም ነበረ፡፡ ነገር ግን አለፈ ብሎ በማስተማር ፈንታ ታቦቱን ከጣዖት ክርስቶስን ከቤልሆር ለይቶ አያስተምርም ነበር፡፡ እርሱ ግን ‹‹ክርስቶስና ቤልሆር በማንኛውም ነገር ኅብረት እንደሌላቸው ታቦትና ጣዖትም እንዲሁ ናቸው›› ብሎ ታቦቱን ‹‹ታቦተ እግዚአብሔር››፣ ጣዖቱን ‹‹ርኩስ›› ብሎ ለይቶ አስተማረ፡፡ እንግዲህ ይህ ቃል አማናዊ እንጂ የምሳሌ ትምህርት ስላልኾነ በብሉይም ኾነ በሐዲስ ኪዳን  ታቦት መኖሩን በሚገባ ያስረዳል፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታቦቱ መኖሩ በዚህ ቃል መሠረት ነው እንጂ አላዋቂዎች እንደሚሉት በስሕተት አይደለም፡፡

ታቦቱ ላይ ስመ አምላክ ታትሞበታል፡፡ ስመ አምላክ የታተመበት እንዴት ‹‹ቅርፅ ቅርፅ›› ተብሎ ሊጠራ ይችላል? እርግጥ ነው ራሱ እግዚአብሔር ታቦት እንዲቀርፅ ‹‹እንደ ቀደመው አድርገህ ቅረፅ›› በማለት ሙሴን አዝዞታል (ዘፀ. ፴፬፥፩-፪)፡፡ ታቦቱ ስመ አምላክ ከተጻፈበት በኋላ ታቦት እንጂ ‹‹ቅርጻ ቅርፅ›› ተብሎ በመጽሐፍ ቅዱስ አልተመዘገበም፡፡ ቅርፃ ቅርፅ የሚባለው ስመ አምላክ ያልተጻፈበት ተራ ነገር ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም አክብሮ ‹‹ታቦተ እግዚአብሔር›› ብሎ ጠራው እንጂ ‹‹ቅርፃ ቅርፅ›› ብሎ አላሳነሰውም፡፡ ለምን ቢሉ ስሙ ታትሞበታልና ነው፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ ስሙን በወደደው ላይ ጽፎ ማስተማር ይችላልና፡፡ እግዚአብሔር ለሙሴ ሲነግረው ‹‹በመንገድህ ይጠብቅህ ዘንድ ወዳዘጋጀሁትም ሥፍራ ያገባህ ዘንድ እነሆ እኔ መልአኬን በፊትህ እሰዳለሁ፤ በፊቱም ተጠንቀቁ፡፡ ቃሉንም አድምጡ፡፡ ስሜም በእርሱ ስለ ኾነ ኀጢአት ብትሠሩ ይቅር አይልምና አታስመርሩት›› ብሎታል (ዘፀ. ፳፫፥፳-፳፪)፡፡

በዚህ ኹኔታ ስንመለከተው ደግሞ ታቦቱ ላይ ስሙ ታትሞበታል፡፡ ስሙ የታተመው ደግሞ የምናመልከው እግዚአብሔር ለመኾኑና የምንሰግደውም ለስመ እግዚአብሔር እንጂ ለሌላ እንዳልኾነ ምስክር ሊኾነን ነው፡፡ እናም አምላካችን እግዚአብሔር የቃል ኪዳኑን ታቦት ለሙሴ ሲሰጠው ታቦቱ ላይ ስሙ ተጽፎ ነበር፡፡ ይህም የክብሩ መገለጫ ሊኾን  እስራኤል ዘሥጋ ስሙን እየጠሩ እንዲያመልኩት ነው፡፡ ዛሬም በሐዲስ ኪዳን ለታቦት እንሰግዳለን፤ ስሙ ተጽፎበታልና፡፡ አምልኮ ባዕድ አልፈጸምንም፡፡ ‹‹ወንሰግድ ውስተ መካን ኀበ ቆመ እግረ እግዚእነ፤ የጌታችን እግር በቆመበት ዂሉ እንሰግዳለን›› ብሎ ቅዱስ ዳዊት እንዳስተማረን (መዝ. ፻፴፩፥፯)፡፡ ምክንያቱም ታቦት እግዚአብሔር በጸጋ፣ በረድኤት የሚያድረበትና የሚገለጽበት ነውና (ዘፀ. ፳፭፥፳፪፤ ዘኍ. ፯፥፹፱)፡፡

በዘመነ ኦሪት የእግዚአብሔር ታቦት የሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያ ኾኖ አግልግሎት ሰጥቷል፡፡ ይኸውም ስመ እግዚአብሔር ስለ ተጻፈበት ነው፡፡ በሐዲስ ኪዳንም ታቦተ እግዚአብሔር የሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያ ነው፡፡ ለምን ቢሉ ስመ እግዚአብሔር ተጽፎበታልና ነው፡፡ ዛሬም በሕገ ወንጌል ክብሩ ሊገለጽ የሚችለው ስመ እግዚአብሔር ስለ ተጻፈበት ነው፡፡ ስመ እግዚአብሔር ደግሞ ትናንት በብሉይ ኪዳን ዛሬም በሐዲስ ኪዳን አንድ ነው፡፡ አንድ ነው ማለትም ያው ስሙ ሌላ እርሱ ሌላ አይደለም ማለት ነው፡፡ እናም ዛሬም ኾነ ነገ ስመ እግዚአብሔር መጥራት ለስሙ መስገድ ሃይማኖታዊ ምሥጢራችን ነው፡፡ ‹‹በሰማይም ኾነ በምድር ለስሙ ጕልበት ዂሉ ይንበረከካል፤ ይሰግዳል›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ፊል. ፪፥፲)፡፡ እስራኤልም በታቦቱ ፊት ስግደት ያቀርቡ ነበር (ኢያ. ፯፥፮)፡፡

ሕዝበ እስራኤል ታቦቱን ለማክበር ሲሉ ካህናቱ ታቦቱን ተሸክመው ሲሔዱ ሕዝቡ ከታቦቱ ሁለት ሺ ክንድ ያህል ይርቁ ነበር (ኢያ. ፫፥፬) ዛሬ በቤተ ክርስቲያናችን ምእመናን ለእግዚአብሔር ክብር ሲሉ ከታቦቱ ራቅ ይበሉ የሚባለው ከዚህ የተነሣ ነው፡፡ ሰሎሞን ታላቁን ቤተመቅደስ ከሰራ በኋላ ታቦቱን በታላቁ ቤተመቅደስ ውስጥ በክብር አስቀምጦታል (፩ኛ ነገ. ፰፥፮)፡፡ ከዚያም አገልግሎቱ ቀጥሏል፡፡ የዚህ ታቦት ክብር በሐዲስ ኪዳን በሰማይ ታይቷል (ራእ. ፲፩፥፲፱)፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድ በተለይ በሐዲስ ኪዳን የታቦት ክብር በምድር ብቻ ሳይኾን ሰማያዊ ኾኗል፤ ‹‹የእግዚአብሔር ታቦት በሰማይ ታየ›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ራእ. ፲፩፥፲፱)፡፡ ይኸውም ከብሉይ ኪዳን ዘመን ይልቅ በሐዲስ ኪዳን ዘመን የታቦት ክብር እጅግ የበለጠ መኾኑንና በሐዲስ ኪዳን ልንገለገልበት እግዚአብሔር የፈቀደ መኾኑን ያመለክታል፡፡ እግዚአብሔር ባይፈቅድ ኖሮ ክብሩን በሰማይ አይገልጽም ነበርና፡፡

በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ታቦት ማለት ለዓለም ራሱን መሥዋዕት አድርጎ የሰጠ ለአምላካችንና ለመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋ እና ክቡር ደም የክብር ዙፋን (መሠዊያ) ነው፡፡ በታቦቱ ላይ የሚጻፈውም ቃልም ‹‹አልፋ ዖሜጋ›› (ፊተኛውና ኋለኛው፤ መጀመሪያውና መጨረሻው የዘላለም አምላክ) የሚለው ቅዱስ ስሙ ነው (ራእ. ፳፪፥፲፫)፡፡ በታቦቱ ፊትም የሚሰገደው ለዚህ ቅዱስ ስም ነው፡፡ ‹‹በላይ በሰማይ፣ በታች በምድር የማናቸውንም ምሳሌ እና ቅርፅ በፊትህ አታድርግ፤ አትስገድላቸውም፤›› (ዘፀ. ፳፥፬-፭) የመሳሰሉትን ኃይለ ቃላት በመጥቀስ ታቦት፣ ሥዕል፣ መስቀል አያስፈልግም የሚሉ ሰዎች አሉ፡፡ ኾኖም ይህ ኃይለ ቃል በእግዚአብሔር ፈንታ ለሚመለክ ጣዖት እንጂ የክብሩ መገለጫ ለኾነው ታቦትና እርሱ ፈቅዶ ለሰጠን የቅዱሳን ሥዕልና መስቀል የሚጠቀስ አይደለም፡፡

በተመሳሳይ መልኩ በትንቢተ ኤርምያስ ፫፥፲፮ ላይ ‹‹ከእንግዲህ የእግዚአብሔርን ታቦት ብላችሁ የማትጠሩበት ጊዜ ይመጣል›› ተብሎ ስለ ተጻፈ በሐዲስ ኪዳን የእግዚአብሔር ታቦት ብለን መጥራት የለብንም የሚሉ ሰዎችም አሉ፡፡ ነቢዩ ኤርምያስ ይህን ቃል የተናገረው ለእስራኤል ነው፡፡ እስራኤል ከእግዚአብሔር ጋር የሚገናኙበትን፣ ጠላትን ድል የሚያደርጉበትን፣ ከእግዚአብሔር በረከት የሚያገኙበትን የቃል ኪዳን ታቦቱን እየተዉ ወደ አምልኮ ጣዖት ተመለሱ፡፡ በዚህ ጊዜ ግልጥ አድርጎ ከባቢሎን ናቡከደነፆር ይመጣል፤ ኢየሩሳሌምን ይወራል፡፡ ቤተ መቅደሱን ያፈርሳል፡፡ እናንተንም ማርኮ ወስዶ ሰባ አመት ይቀጠቅጣችኋል ብሎ ትንቢት ተናገረባቸው፡፡ የተናገረው አልቀረም፤ ናቡከደነፆር መጣ፤ ኢየሩሳሌምም ተወረረች፤ ቤተ መቅደሱም ፈረሰ፤ ንዋያተ ቅድሳቱም ተዘረፉ፤ እስራኤልም ተማረኩ፡፡ አሁን በሰው አገር ጠላትን ድል የሚያደርጉበት፣ ከእግዚአብሔር የሚገናኙበት የእግዚአብሔር ታቦት አልተገኘም፡፡ ያን ጊዜ የነቢዩ ቃል ተፈጸመ፡፡ የእግዚአብሔር ታቦት አልተገኘምና የታቦቱን ስም መጥራት አልቻሉም፡፡ ይህን ትንቢት ለምን ተናገረ ብለው ኤርምያስን የገዛ ወገኖቹ ከመጸዳጃ ቤት ከተውታል፡፡ የተናገረው ግን አንዱም አልቀረም፤ ተፈጸመ፡፡

እኛ የሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች ግን ታቦታችን አልጠፋብንም፤ ምናልባት የጠፋባቸው ለማያምኑ ነው እንጂ፤ ታቦተ ጽዮን በኢትዮጵያ አሁንም ትገኛለች፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የክህነት አገልግሎት

በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርተ ወንጌልና ሐዋርያዊ አገልግሎት ማስተባበሪያ

በስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ዋና ክፍል የተዘጋጀ

የካቲት ፲፫ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

‹ክህነት›፣ ‹‹ተክህነ – አገለገለ›› ከሚል የግእዝ ቃል የወጣ ሲኾን ትርጕሙም ‹‹አገልግሎት፣ መላላክ፣ ለሌሎች መኖር፣ መጥዎተ ርእስ (ራስን መስጠት) መላ ሕይወትን ለእግዚአብሔር ማስረከብ›› ማለት ነው፡፡ ክህነት ካለ ካህናት ይኖራሉ፤ ክህነት አገልግሎቱ፣ ሹመቱ፤ ካህናት ደግሞ አገልጋዮቹ፣ ተሿሚዎቹ ናቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ ካህናት መላእክት ናቸው፡፡ የመጀመሪያ የእግዚአብሔር እና የሰው ልጆች አገልጋዮች፡፡ ‹‹በዙፋኑ ዙሪያ ሃያ አራት ወንበሮች ነበሩ፡፡ በእነዚያ ወንበሮችም ሃያ አራት አለቆች (ካህናተ ሰማይ) ተቀምጠዋል፡፡ ነጭ ልብስም ለብሰዋል፡፡ በራሶቻቸው ላይ የወርቅ አክሊሎች ደፍተው ነበር … በዂለንተናቸው ዓይኖችን የተመሉ ናቸው፡፡ ‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ የነበረውና ያለው፣ የሚመጣውም፤ ዂሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክ› እያሉ›› ቀንና ሌሊት አያርፉም፡፡  እነዚህ በዙፋን ላይ ለተቀመጠው ከዘለዓለም እስከዘለዓለም በሕይወት ለሚኖረው ለእርሱ አክሊላቸውን በዙፋኑ ፊት አውርደው ይሰግዳሉ፡፡ እንዲህም ይላሉ፤ ‹ጌታችን እና አምላካችን ሆይ፣ አንተ ዂሉን ፈጥረሃልና በፈቃድህም ኾነዋልና ተፈጥረውማልና ክብርና ውዳሴ ኀይልም ለአንተ ይገባል፤››› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ራእ. ፬፥፬)፡፡

ይህ ከላይ የተመለከትነው ኃይለ ቃል ለክህነት እና ለካህናት አገልግሎት መሠረቱ ነው፡፡ ‹‹በመዓልትም በሌሊትም አያርፉም›› ያለው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ካህናትን የዘወትር አገልግሎት በግልጽ ያሳያል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን፣ ‹‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ምስጋናው በሰማይና በምድር የሞላ ነው›› በማለት የምታሰመግነው በክህነት እና በካህናት አማካይነት ነው፡፡ ካህናት፣ ምድራውያን መላእክት ናቸው፡፡ መላእክት እንደሚያመሰግኑ ያመሰግናሉ፤ በእግዚአብሔር ፊት እንዲቆሙ ይቆማሉ፡፡ የክህነት አግልግሎት ከመላእክት ቀጥሎ የተሰጠው ለሰው ልጅ ነው፡፡ ለሰው የተሰጠው ክህነት ፈጣሪውን እንዲያመሰግንበት ብቻ አይደለም፡፡ መሥዋዕት ሊሠዋበት፣ ዕጣን ሊያሳርግበት፣ ሰውን ሊረዳበት የተሰጠ ነው፡፡ ለሰው ክህነት ተሰጠው ስንል ሰው ዂሉ ካህን ነው ማለት አይደለም፡፡ ከሰው ልጆች ወገን ለክህነት የተመረጡ አሉ፡፡ ዂሉም ሰው ተነስቶ ካህን ነኝ ሊል አይችልም፡፡ ይህ ማለት የአካል ክፍል እንደማጥፋት ማለት ነው፡፡ በአካል ውስጥ ዓይን፣ እጅ፣ እግር፣ አፍ፣ አፍንጫ … አሉ፡፡ ዂሉም የአካል ክፍሎች ዓይን መኾን አይችሉም፡፡ እጅ መዳሰስ፣ እግር መሔድ፣ ዓይን ማየት፣ አፍንጫ ማሽተት፣ አፍ መጉረስ ነው የሥራ ድርሻቸው፡፡ እጅ፣ እግር፣ አፍ፣ አፍንጫ፣ ጆሮ ካላየን ቢሉ፣ ዓይን እንኹን ብለው ቢያስቡ ወይም ነን ቢሉ ዓይን መኾን (ማየት) አይችሉም፡፡ ማየት የዓይን ተግባር እንደ ኾነ ዂሉ ሰዎችም ካህን ሳይኾኑ ነን በማለት መዓርገ ክህት አይገኝም፡፡ እግዚአብሔር የመረጣቸው ካህናት ይኾናሉ እንጂ፡፡

ክህነት በብሉይ ኪዳን

እግዚአብሔር ሙሴን ለምስፍና (ለመስፍንነት)፣ አሮንን ለክህነት መርጧቸዋል፡፡ የመረጠበት ግብርም ረቂቅ ነው፡፡ ዂሉም እስራኤል ግን መሳፍንት፣ ገዢዎች፣ መሪዎች አልነበሩም፡፡ የሌዊ ወገን ለክህነት፣ የይሁዳ ወገን ለመንግሥት የተመረጠ ነበር (ዘኍ. ፫፥፮)፡፡ የሌዊ ነገድ ተለይተው የክህነቱን አገልግሎት፣ መሥዋዕት መሠዋት የመሳሰሉትን ይሠሩ ነበር (ዘዳ. ፲፥፰፤ ፳፰፥፩-፵፫)፡፡ ሌሎች ነገደ ፳ኤል ድንኳን በመሸከም ልዩ ልዩ አገልግሎት ይሠጡ ነበር፡፡ ይህን የተላለፈ ፳ኤላዊ መቀሠፍቱ ከባድ ነበር፡፡ ከላይ እንደ ተመለከትነው ለክህነት መመረጥ፣ መለየት፣ መቀባት፣ መሾም፣ መቀደስ የግድ ያስፈልጋል፡፡ ማንም ዝም ብሎ ካህን ነኝ፤ ነቢይ ነኝ ማለት አይችልም፡፡ መሥዋዕቱን ምእመናነ እስራኤል ያመጣሉ፤ አሮንና ልጆቹ ደግሞ መሥዋዕቱን ያቀርባሉ፡፡ ሕዝቡ በጉን፣ ርግቡን፣ ዋኖሱን፣ በሬውን ያመጣሉ፤ ካህናቱ እጃቸውን ጭነው ይጸልያሉ፤ ኀጢአትን ያስተሰርያሉ፡፡ ሕዝቡን ያስተምራሉ፤ ይመክራሉ፡፡ ሕዝቡም ይመከራል፤ ይገሠፃል፡፡

በእግዚአብሔር ሳይመረጡና ሳይሾሙ ካህን ነን ቢሉ የሚመጣው ቅጣት ከባድ ነው፡፡ ከሌዊ ወገን የተወለዱ ዳታንና አቤሮን የደረሰባቸው ቅጣት በመጽሐፍ ቅዱስ ተመዝግቧል (ዘኍ. ፲፮፥፩-፶፩)፡፡ ያልተሰጣቸውን ሽተው፣ ከህነት ሳይኖራቸው ለማጠን ገብተው የእሳት ራት ሆነዋል፡፡ መሬት ተከፍቶ ውጧቸዋል፡፡ በሕይወት ሳሉ ተቀብረዋል፡፡ ለክህነት የተመረጠው አሮንና ልጆቹ ግን አልጠፉም፡፡ ከዚህ እንዳየነው ለክህነት መመረጥ፣ መቀደስ፣ መለየት፣ መሰጠት ያስፈልጋል፡፡ ይህ ሳይኾን ማንም ተነሥቶ ካህን ነኝ፣ ነቢይ ነኝ ቢል ይህ ዕጣ ፋንታ ይገጥመዋል፡፡ እግዚአብሔር አልመረጠውምና፡፡ የእነዚህ ሰዎች ዕጣን ማሳረግ (ማጠን) ለመቅሠፍት፤ የሳኦል መሥዋዕትም መንግሥትን ለማጣት ዳርጓቸዋል፡፡ ሳኦል፣ ሳሙኤል እስኪመጣ መታገሥ አቅቶት መሥዋዕት በመሠዋቱ ነው መንግሥቱን የተነጠቀው (፩ኛ ሳሙ. ፲፭፥፳፪፤ ፳፰፥፲፯)፡፡

ክህነት በሐዲስ ኪዳን

ክህነት በዓለመ መላእክት፣ በብሉይ ኪዳን ምን እንደሚመስል ተመልክተናል፡፡ በዓለመ መላእክት መሥዋዕቱ ምስጋና፣ ውዳሴ፣ ተልእኮ ነው፡፡ ካህናቱ መላእክት ናቸው፡፡ ቤተ መቅደሱ ዓለመ መላእክት ነው፡፡ በብሉይ ካህናቱ ከሌዋውያን የአሮን ልጆች፣ ቤተ መቅደሱ የመገናኛው ድንኳን፣ መሥዋዕቱ ላም፣ በግ፣ ፍየል፣ ርግብ፣ ዋኖስ የእኽል አይነቶች ናቸው፡፡ የሐዲስ ኪዳን ክህነቱም፣ መሥዋዕቱም፣ ካህናቱም ከተመለከትነው የተለየ ነው፡፡ ክህነቱና ካህናቱ ልዩ የሚኾንበት ምክንያት መሥዋዕቱ ልዩ በመኾኑ ነው፡፡ መሥዋዕቱ በቀራንዮ ዐደባባይ ዓለም ለማዳን ሥጋውን ቈርሶ፣ ደሙን አፍስሶ የሰጠን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ቀደም ሲል ያየነው የመላእክት መሥዋዕት ዓለምን ማዳን አልተቻለውም፡፡ የሌዋውያንን መሥዋዕትም አንድ ኀጢአተኛ ሰው ያመጣዋል፡፡ ከመርገም ያልተለየ ካህን ይሠዋዋል፡፡ መሥዋዕቱም ሥጋዊ ይቅርታን ብቻ ያሰጥ ነበር፡፡ መሥዋዕቱ፣ በአቀራረቡም ጉድለት ነበረበት፡፡ ስርየቱ የሚያስገኘውም ላመጣው ሰው ብቻ ነበር፡፡

የሐዲስ ኪዳን መሥዋዕት ግን መሥዋዕቱ ፍጹም ጉድለት የሌለበት ነው፡፡ መሥዋዕቱም፣ አቅራቢውም፣ ተቀባዩም ኢየሱስ ክርስቶስ በመኾኑ ክህነቱም ፍጹም ነው፡፡ ይህን ፍጹም ክህነት ፍጹም የሆነውን መሥዋዕት ለሚያቀርቡ ካህናት ሰጠ፡፡ ክህነቱን አገልግሎቱን በትህትና አሳያቸው አስተማራቸው፡፡ ክህነቱንም መሥዋዕቱንም ሰጣቸው፡፡ በዚህ የተነሳ የሐዲስ ኪዳን ካህናት መላእክት ያልሰዉትን የብሉይ ኪዳን ካህናት ያላቀረቡትን መሥዋዕት የማቅረብ የማገልገል ሥልጣነ ክህነት የተሰጣቸው በመሆኑ ክህነቱ ምጡቅ ምስጢሩ ጥልቅ አገልግሎታቸውም ረቂቅ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ፣ ‹‹ኢተአምሩኑ ከመ መላእክተ ጥቀ ንኴንን ኅድጉሰ ዘዝ ዓለም፤ የዚህን ዓለም ዳኝነት ተዉትና በመላእክት ስንኳን እንድንፈርድ አታውቁምን?›› ሲል እንደ ጠቀሰው፤ መምህራነ ቤተ ክርስቲያንም ‹‹ዘኢተገብረ ለመላእክት ተገብረ ለካህናት፤ ለመላእክት ያልተደረገ ለካህናት ተደረገ›› በማለት እንደሚያስተምሩን (፩ኛ ቆሮ. ፮፥፲፫)፡፡

የብሉይ ኪዳን ካህናት ሰዉን ከእግዚአብሔር ጋር ለማስታረቅ አልተቻላቸውም፡፡ የሐዲስ ኪዳን ካህናት ግን የጠብ ግድግዳ ከፈረሰ፣ ልጅነት ከተመለሰ፣ ጸጋ ከተገኘ፣ ሰውና እግዚአብሔር ከተገናኘ በኋላ ስለ ተሾሙ ክህነታቸው ልዩ፣ መሥዋዕታቸው ልዩ፣ ክብራቸው ልዩ ነው፡፡ ምድራውያን ናቸው፤ ነገር ግን ሰማያዊ ሥልጣን አላቸው፡፡ የተሾሙትም ሰማያዊውን ርስት ለመስበክ፣ ሰውን ከምድራዊ ግብር ለይተው ሰማያዊ ጸጋ አሰጥተው መንግሥተ ሰማያትን ለማውረስ ነው፡፡ አምላክ ይህን ያደረገው በመልእክት አይደለም፤ ሰው ኾኖ መጥቶ ሥርዓቱን ሠርቶ አሳይቶ ሥልጣኑን ሰጥቶ አገልግሎቱን መሥርቶ ነው፡፡ ‹‹ወአልቦ ዘይነስእ ክብረ ለርዕሱ ዳዕሙ ዘጸውዖ እግዚአብሔር በከመ አሮን፤ በቃሁ ነቃሁ ብሎ ክብረ ክህነትን ለራሱ የሚያደርግ የለም፡፡ እግዚአብሔር እንደ አሮን ነው እንጂ (እንደ አሮን በእግዚአብሔር ከተጠራ በቀር ማንም ክብርን ለራሱ የሚወስድ የለም፤››) እንዳለ (ዕብ. ፭፥፬)፡፡

ማጠቃለያ

በአጠቃላይ ሥልጣነ ክህነት በጳጳሳት እጅ የሚሰጥ ሥልጣን ነውና ማቃለል አይገባም፡፡ ካህናት የእግዚአብሔር ዓይኖች ናቸውና፡፡ እግዚአብሔር ኀጢአተኛውን የሚያየው፣ የሚጐበኘውና ኀጢአቱን ይቅር የሚለው በእነርሱ በኩል ነው፡፡ ‹‹ሒድ ራስህን ለካህን አሳይ›› (ማቴ. ፰፥፬) ተብሎ እንደ ተጻፈ ካህን አየን ማለት እግዚአብሔር አየን ማለት ነው፡፡ ካህን የእግዚአብሔር ዓይን ነውና፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ የምንኾነውም በካህናት ተጠምቀን ነውና (ማቴ. ፳፰፥፲፱)፡፡ በዚህ መሠረት ያለ ካህን እና ያለ መሥዋዕት የሚፈጸም አገልግሎት የለም፡፡ ቢኖርም አገልግሎቱ የውሸት ነው፡፡ ሕሙማን በክህነት አገልግሎት ይድናሉ፡፡ ‹‹ከእናንተ የታመመ ሰው ቢኖር በቤተ ክርስቲያን ያሉ ቀሳውስትን ወደ እርሱ ይጥራና ይጸልዩለት፡፡ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም የተጸለየበትንም ዘይት ይቅቡት የሃይማኖት ጸሎት ድውዩን ይፈውሰዋል፡፡ እግዚአብሔርም ያስነሣዋል፤ ኀጢአትንም ሠርቶ እንደ ኾነ ይሰረይለታል፤›› እንዲል (ያዕ. ፭፥፲፫-፲፮)፡፡

ካህናት ይህን ዂሉ የማድረግ ሥልጣን የተሰጣቸው የቤተ ክርስቲያን አባቶች ናቸው፡፡ በትረ ክህነት የጨበጡ፣ በእግዚአብሔር የተመረጡ፣ አጋንንትን የሚቀጡ፣ ኀጢአትን እንደ ሰም አቅልጠው የሚያጠፉ ናቸው፡፡ ሰውን ወደ እግዚአብሔር ያቀርባሉ፤ የእግዚአብሔርን መንጋ ምእመናንን ይጠብቃሉ፡፡ በለመለመ መስክ በጠራ ውኃ ያሠማራሉ፡፡ ማለት ያልተበረዘ ያልተከለሰ ከሐዋርያት የተገኘ ንጹሕ ወንጌልን ያስተምራሉ፡፡ ‹‹ነዋ በግዑ ለእግዚአብሔር ዘየአትት ወያሴስል ኃጢአተ ዓለም፤ እነሆ የዓለምን ኀጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ›› እያሉ ሰውን ዂሉ ወደ እግዚአብሔር መንግሥትና ወደ ዘለዓለማዊ ሕይወት የሚያቀርቡ የድኅነት በር ናቸው (ዮሐ. ፩፥፳፱)፡፡

የኤልያስ መንፈስ በኤልሳዕ፤ የሙሴ መንፈስ በኢያሱ እንዳደረ የሐዋርያት መንፈስ ያደረበት እግዚአብሔር የመረጠው የገለጠው ክህነት በአበው ጳጳሳት ቅባትና ጸሎት አማካይነት ይታደላል፡፡ አባቶች ጳጳሳት በአንብሮተ እድ ባርከው በንፍሐት እፍ ብለው በእግዚአብሔር ስም ክህነቱን ካላሳደሩበት በቀር ማንም ካህን መኾን አይችልም፡፡ እግዚአበሔር የሾመው ሐዋርያትን ብቻ አይደለም፤ ጳጳሳትንም የሾመው እርሱ ነውና፡፡ ‹‹በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ዂሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሐዋ. ፳፥፳፰)፡፡ ጌታችን ‹‹እውነት እላችኋለሁ፤ በምድር የምታስሩት ዂሉ በሰማይ የታሰረ ይኾናል፡፡ በምድርም የምትፈቱት ዂሉ በሰማይ የተፈታ ይኾናል›› በማለት ለቅዱሳን ሐዋርያት የማሰር የመፍታት ሥልጣን እንደ ሰጣቸው በማያሻማ ኹኔታ በቅዱስ ወንጌል ተቀምጧል (ማቴ. ፲፰፥፲፰፤ ሉቃ. ፳፬፥፶፤ ዮሐ. ፳፥፳፪-፳፬፤ ሐዋ. ፱፥፲፯፤ ፩ኛ ጢሞ. ፬፥፲፭)፡፡

ስለዚህ ክህነት በእግዚአብሔር ጥሪ የሚፈጸም በእግዚአብሔር ሰጭነት የሚከናወን መኾኑን ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ ሥልጣን እግዚአብሔር መጀመሪያ የመረጠው ቅዱሳን ሐዋርያትን ነው፡፡ የመጀመሪያዎቹ የሐዲስ ኪዳን ካህናት ሐዋርያት ናቸው፡፡ የመረጣቸው፣ የጠራቸው፣ የሾማቸውም እርሱ ራሱ ነው (ማቴ. ፲፥፩)፡፡ ሥልጣኑን ያገኙት ከባለቤቱ ከኢየሱስ ክርስቶስ መኾኑን ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡ ሥልጣነ ክህነት ሐዋርያት ተቀብለውት የሚቀር ሳይኾን ለተመረጡ ሰዎች ሊሰጡት እንደሚችሉ መጽሐፍ ቅዱስ ምስክር ነው (ሐዋ. ፩፥፳፬)፡፡ በዚህ መልኩ የሚሾሙ ካህናት የእግዚአብሔር አገልጋዮች የሐዋርያት ተከታዮች ሐዋርያት ናቸው፡፡ ለእነርሱ የተሰጠውን ሥልጣን ማመን፣ መቀበልና መጠቀም ይገባል፡፡ ከዚህ ውጪ በየፌርማታው ነቢይ ነኝ ካህን ነኝ ከሚሉት መጠንቀቅ ያሻል፡፡ ክህነት ዝም ብሎ በየመንገዱ የሚታፈስ አይደለም፡፡ ማንም እየተነሣ የሚዘግነው የእድር ቆሎም አይደለምና፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምልጃ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን

በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርተ ወንጌልና ሐዋርያዊ አገልግሎት ማስተባበሪያ 

በስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ዋና ክፍል የተዘጋጀ

 የካቲት ፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም 

፩. ምልጃ ምንድን ነው?

ምልጃ በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከሚደረጉ የጸሎት ክፍሎች አንዱ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን የምስጋና ጸሎት፣ የልመና ጸሎት፣ የምልጃ ጸሎት አላት፤ እነዚህንም በንባብ፣ በቃልና በዜማ ታደርሳቸዋለች፡፡ ‹‹ጌታ ቅርብ ነው፡፡ በነገር ዂሉ በጸሎትና በምልጃ ከምስጋና ጋር በእግዚአብሔር ዘንድ ልመናችሁን አስታውቁ እንጂ በአንዳች አትጨነቁ›› እንዲል (ፊልጵ. ፬፥፮)፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አማላጅ ናት፡፡ በመኾኑም ጸሎተ አስተብቊዖ (የምልጃ ጸሎት) አላት፡፡ ለምሳሌ ያህልም ‹‹ዕውቀትን እርሱን መፍራትንም እግዚአብሔር ይሰጣቸው ዘንድ ስለ መኳንንት እና ሥልጣን ስላላቸው እንማልዳለን›› (ሥርዓተ ቅዳሴ) የሚለው የጸሎት ዓይነት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምስክርነትና መነሻ ያለው ኃይለ ቃል ነው፡፡ ይኸውም ‹‹እንግዲህ እግዚአብሔርን በመምሰልና በጭምትነት ዂሉ ጸጥና ዝግ ብለን እንድንኖር ልመናና ጸሎት ምልጃም ምስጋናም ስለ ሰዎች ዂሉ ስለ ነገሥታትና ስለ መኳንንትም ዂሉ እንዲደረጉ ከዂሉ በፊት እንመክራለን›› በማለት ቅዱስ ጳውሎስ ካስተማረው ትምህርት የተወሰደ ነው (፩ኛ ጢሞ. ፪፥፩)፡፡

አንድ ክርስቲያን ስለ ራሱ ይለምናል፤ ያመሰግናልም፡፡ ከዚህ ባለፈ ደግሞ ስለ ሌላው ይማልዳል፤ ያመሰግናልም፡፡ በዚህ መልኩ ነው ምልጃና የራስ ልመና ተለያይተው የሚቀመጡት፡፡ ይኹን እንጂ ሁለቱም ያው የጸሎት ዘርፎች ናቸው፡፡ ሁለቱም የጸሎት ክፍሎች የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ሲኾኑ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ምልጃንና ልመናን ሳትቀላቅል ነው የምታከናውናቸው፡፡ ስለዚህ ምልጃ ማለት ማስታረቅ፣ ማቅረብ፣ ማስማማት፣ ማስማር ማለት ነው፡፡

ምልጃን አስመልክቶ በዓለም ላይ ሦስት ዓይነት አመለካከቶች ይንጸባረቃሉ፤

  • አንዳንዶች ‹‹ምልጃ የሚባል የለም፤ ማንም ስለ ማንም አይማልድም፤ በቀጥታ ወደ እግዚአብሔር መቅረብ ይቻላል›› ይላሉ፡፡
  • አንዳንዶቹ ደግም ‹‹ምልጃ አለ፤ ያስፈልጋል›› ይሉና አማላጁ ግን (ሎቱ ስብሐት፤ ክብር ይግባውና) ክርስቶስ ነው ይሉናል፡፡
  • ሌሎቹ ደግሞ ‹‹ምልጃ አለ፤ ምልጃ የፍጡር ሥራ ነው እንጂ የፈጣሪ ሥራ አይደለም›› ይላሉ፡፡ የእኛ አስተምህሮም መደቡ ከዚህ ነው፡፡

የፕሮቴስታንት እምነት ስለ ቅዱሳን ምልጃ እንደሚከተለው ያስተምራል፤

  • ቅዱስ ብሎ ነገር የለም፤ ዂላችንም (ምእመናን በሙሉ) ቅዱሳን ነን፡፡
  • በሕይወተ ሥጋ እያለን አንዳችን ለአንዳችን ስንጸልይ ብቻ ነው ምልጃ ተፈጸመ የሚባለው፡፡

ይህ አባባል ብቻውን ካየነው ከላይኛው አባባል ጋር ይጣረሳል፡፡ ሁላችንም ቅዱሳን ከሆን አንዳችን ስለአንዳችን የምንጸልይበት ፋይዳ ምንድን ነው? የሚል ጥያቄም ያስነሣል፡፡

  • በዐፀደ ሥጋ እንጂ በዐፀደ ነፍስ ማንም ስለ ማንም መጸለይ አይችልም የሚል ነው፡፡

፪. ምልጃ የማን ሥራ ነው?

ምልጃ የፍጡራን ሥራ ብቻ ነው፡፡ በምንም ዓይነት የፈጣሪ ሥራ ሊኾን አይችልም፡፡ ከፍጡራንም ቢኾን የሚፈጽሙት ሁለት አካላት ሲኾኑ አንደኛ እግዚአብሔር አከብሮ የፈጠራቸው ቅዱሳን መላእክት፤ በተጋድሎና በቸርነቱ ባለሟልነት፣ ክብርና ጸጋን የሰጣቸው ቅዱሳን ሰዎች ናቸው፡፡ ከዚህ ውስጥ ቅድስተ ቅዱሳን የኾነችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በተለየ ቅድስናዋና ክብሯ ሰፊውን የምልጃ አገልግሎት ትይዛለች፡፡ ምልጃ የኀጢአተኞች ሥራ አይደለም፡፡ ኀጥእ ሰው የራሱን ኀጢአት ለማስተስረይ መትጋት ይጠበቅበታል፡፡ ከኀጢአተኞች ኀጢአት እንጂ በረከት ሊወጣ አይችልምና (፩ኛ ሳሙ. ፳፬፥፲፫)፡፡

፫. የምልጃ ዓይነቶችና አፈጻጸማቸው

የምልጃ ዓይነቱ ወይም መደቡ ሁለት ነው፤ አንደኛው በዚህ ዓለም ማለትም በዐፀደ ሥጋ የሚከናወን ሲኾን፣ ሁለተኛው ደግሞ በዐፀደ ነፍስ ማለትም በነፍስ ዓለም የሚከናወን ነው፡፡ በአፈጻጸማቸውም መጽሐፍ ቅዱስን መሠረት በማድረግ እንደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ በሦስት ዋና ዋና መስመሮች ይከናወናሉ፤

አንደኛ በቅዱሳን ክብርና ባለሟልነት (የማማለድ ጸጋ)፤ በአምላከ ቅዱሳን በልዑል እግዚአብሔር ችሮታ ያመነው በደለኛ ወይም ምልጃ ፈላጊ ምእመን ወዶና ፈቅዶ ወደ አማላጁ ቀርቦ የአማላጁን ስም በክብር እየጠራ ምልጃ ሲጠይቅ የሚፈጸም የምልጃ ዓይነት ነው፡፡ ለዚህም ማሳያ የሚኾነን የነቢዩ ኤልሳዕ ታሪክ ነው፡፡ ‹‹… ከኤልያስም የተቀበለውን መጎናጸፊያ አነሣ፤ ተመልሶ በዮርዳኖስ ዳር ቆመ፡፡ ከኤልያስም በተቀበለው መጎናጸፊያ ውሃውን መታና የኤልያስ አምላክ እግዚአብሔር ወዴት ነው? አለ፡፡ ውሃውንም በመታ ጊዜ ወዲህና ወዲያ ተከፈለ፤ ኤልሳዕም ተሻገረ›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (፪ኛ ነገ. ፪፥፩-፲፮)፡፡

በዚህ መሠረት እኛ ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን፡-

  • በአምላከ ቅዱሳን በእግዚአብሔር ስም እንማጸናለን
  • ወደ አምላካችን አማልዱን ስንል ቅዱሳንን እናስቀድማቸዋለን
  • የቅዱሳንን ስማቸውን ጠርተን ፈጣሪያችንን ስንማጸን እንደ ውኃ ሙላትና እንደ ተራራ የተጋረጠብንን መከራና ችግር ፈተና ዂሉ ይወገድልናል፡፡

‹‹ኢዮሳፍጥም ‹በእርሱ እግዚአብሔርን የምንጠይቅበት የእግዚአብሔር ነቢይ በዚህ አይገኝምን?› አለ፡፡ ከባሪያዎቹ አንዱ ‹በኤልያስ እጅ ላይ ውኃ ያፈስ የነበረው የሳፋጥ ልጅ ኤልሳዕ ከዚህ አለ› አለ፤›› (፪ኛ ነገ. ፫፥፲፩)፡፡ በዚህ ኃይለ ቃል ንጉሡ ራሱ እግዚአብሔርን መጠየቅ ይችል ነበር፤ ይህንን ያደረገው ስለ ትሕትናው፣ ቅዱሳንን ስለ ማክበሩ ነው፡፡ ኤልሳዕም በቀጥታ እግዚአብሔርን ጠርቶ ይህን ውኃ ክፈለው ማለት ይችል ነበር፤ ግን የአባቱን የመምህሩን የኤልያስን ክብር ጠንቅቆ ስለሚያውቅ ራሱን በትሕትና አሳንሶ መምህሩን አስበልጦና አክብሮ በመገኘቱ ነው፡፡

ሁለተኛ የማማለድ ጸጋ ከእግዚአብሔር የተሰጣቸው ቅዱሳኑ ያለ ምልጃ ጠያቂው አቤቱታ ‹‹ማርልኝ›› እያሉ ወደ ፈጣሪያው የሚያቀርቡት የምልጃ አፈጻጸም ነው፡፡  ይህንን ሁለተኛውን የምልጃ መስመር የሚያብራራልን ምሳሌ በኦሪት ዘፀአት ፴፪፥፩-፴፪ ተመዝግቦ የምናገኘው የሙሴ ታሪክ ነው፡፡ እስራኤል የጥጃ ምስል አቁመው ጣዖት በማምለካቸው እግዚአብሔር እንዳያጠፋቸው በቀጥታ ስለ ሕዝቡ በእግዚአብሔር ፊት ቆመ፡፡ አስራኤል ለምንልን እስከሚሉትም አልጠበቀም፡፡

እንዲህ እያለም ጸለየ፤ ‹‹አቤቱ ቍጣህ፣ በታላቅ ኃይልና በጽኑ እጅ ከግብጽ ምድር ባወጣኸው በሕዝብህ ላይ ስለምን ተቃጠለ? … ከመዓትህ ተመለስ፤ ለሕዝብህም በክፋታቸው ላይ ራራ፡፡ ‹ዘራችሁን እንደ ሰማይ ከዋክብት አበዛለሁ፤ ይችንም የተናገርኋትን ምድር ዂሉ ለዘራችሁ እሰጣታለሁ፤ ለዘለዓለምም ይወርሷታል› ብለህ በራስህ የማልህላቸውን ባሪያዎችህን አብርሃምንና ይስሐቅን እስራኤልንም አስብ፡፡›› ሙሴ ይህን ጸሎት አቅርቦ ሲያበቃ ምን ኾነ ብለን ብንጠይቅ ‹‹እግዚአብሔርም በሕዝቡ ላይ ሊያደርግ ስላሰበው መዓት ራራ›› ይለናል መጽሐፍ ቅዱስ፡፡

ልጇ ታሞባት ምሕረት ለመለመን ወደ ክርስቶስ መጥታ የነበረችው ከነዓናዊት ሴትም ልመናዋን እያቀረበች በነበረችበት ወቅት ሐዋርያት ወደ ክርስቶስ ተጠግተው ‹‹… በኋላችን ትጮኻለችና አሰናብታት›› ሲሉ ያሳሰቡት (የማለዱት) እርሷ ለምኑልኝ ስላለቻቸው ሳይኾን ባለሟልነታቸው ባሰጣቸው ጸጋና ክብር ተጠቅመው ነው (ማቴ. ፲፭፥፳፩-፳፰)፡፡ እኛም ከቅዱሳን ኋላ ኾነን ብንጮኽ ይህንኑ ነው የሚያደርጉልን፡፡

ሦስተኛ እግዚአብሔር በአማላጁና በሚማለድለት መሃል ገብቶ ሲያዝ የሚፈጸም የምልጃ ዓይነት ነው፡፡ እግዚአብሔር ራሱ በቀጥታ ምሕረት መስጠት እየቻለ ‹‹እገሌ ይጸልይልህ›› ብሎ ኀጥኡን መላኩ ስለ ምን ነው ቢሉ የቅዱሳንን ክብርና ባለሟልነት ለመግለጽ ስለ ወደደ ነው፡፡ አንድም እንዲህ ያለውን የመዳኛ መንገድ ማብዛቱ የቸርነቱ ውጤት ነው፡፡ ይህን ለማየት ምሳሌ የሚኾነን ደግሞ የአብርሃም ታሪክ ነው፡፡ የጌራራው ንጉሥ አቤሜሌክ የአብርሃምን ሚስት ከክብር ሊያሳንሳት በወሰዳት ጊዜ የኀጥኡን መጥፋት ሳይኾን ከጥፋቱ ተመልሶ በሕይወት መኖሩን የሚወድ አምላክ ‹‹የሰውየውን (የአብርሃምን) ሚስት መልስ፤ ነቢይ ነውና ስለ አንተም ይጸልያል ትድናለህም፤›› ብሎ ሲራራና ኀጥኡን ወደ ጻድቁ ሲመራው እንመለከታለን (ዘፍ. ፳፥፩-፲፰)፡፡

፬. ምልጃ በዐፀደ ነፍስ

‹‹በዐፀደ ሥጋ ያለውን ምልጃ እንቀበላለን፤ በዐፀደ ነፍስ ግን አይደረግም›› ለሚሉ መጽሐፍ ቅዱስ በዐፀደ ነፍስ ስላለው ምልጃ እንደሚከተለው ያስተምረናል፤ ነፍስ ከእግዚአብሔር የተሰጠች ተመልሳም ወደ እግዚአብሔር የምትሔድ፤ እንድናስብ እንድንናገርና ሕያው ኾነን እንድንኖር ያስቻለችን ረቂቅ ፍጥረት ነች (ዘፍ. ፪፥፯፤ መክ. ፲፪፥፯)፡፡ ስለዚህ ቅዱሳን ዂሉን የሚያውቁት፣ ከሞት (የሥጋ ሞት) በኋላ ሕያው የሚኾኑት፣ የምናናግራቸውና የሚያናግሩን በዚህች ነፍስ ነው፡፡ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም የሙታን ሳይኾን የሕያዋን አምላክ መኾኑን የነገረን ለዚሁ ነው (ማቴ. ፳፪፥፴፪)፡፡ ወደ እግዚአብሔር የሔዱ ቅዱሳን ከዚህ ዓለም ዕረፍታቸው በኋላ በዚህ ዓለም ስለሚኾነው ነገር እግዚአብሔር በገለጠላቸው መጠን እንደሚያውቁ እና እንደሚያማልዱ መጽሐፍ ቅዱስ ይነግረናል፡፡

ለአብነት ያህል የሚከተሉትን የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርቶች እንመልከት፤

ሀ. ከዚህ ዓለም ከተለየ (ከክርስቶስ ልደት በፊት) አንድ ሺሕ አምስት መቶ ዓመታት ገደማ የሚኾነው ነቢዩ ሙሴ እና ነፍሱና ሥጋው ሳይለያዩ በብሔረ ሕያዋን የሚኖረው ነቢዩ ኤልያስ ሁለቱም በዘመነ ሥጋዌ ከጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር በደብረ ታቦር ተገልጠዋል፡፡ ‹‹ሲጸልይም የፊቱ መልክ ተለወጠ፤ ልብሱም ተብለጭልጮ ነጭ ኾነ። እነሆም፥ ሁለት ሰዎች እነርሱም ሙሴና ኤልያስ ከእርሱ ጋር ይነጋገሩ ነበር፤ በክብርም ታይተው በኢየሩሳሌም ሊፈጽም ስላለው ስለ መውጣቱ ይናገሩ ነበር፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሉቃ. ፱፥፳፱-፴፪)፡፡

ለ. ቅዱሳን ሰማዕታት ካረፉ በኋላ በዐፀደ ነፍስ ኾነው በዚህ ዓለም ስላለው ኹኔታ እንደሚያውቁና እንደሚጸልዩ በራእየ ዮሐንስ እንደሚከተለው ተገልጧል፤ ‹‹አምስተኛውንም ማኅተም በፈታ ጊዜ፥ ስለ እግዚአብሔር ቃልና ስለ ጠበቁት ምስክር የታረዱትን የሰዎች ነፍሳት ከመሠዊያ በታች አየሁ። በታላቅ ድምፅም እየጮኹ ‹ቅዱስና እውነተኛ ጌታ ሆይ፥ እስከ መቼ ድረስ አትፈርድም? ደማችንንስ በምድር በሚኖሩት ላይ እስከ መቼ አትበቀልም?› አሉ። ለእያንዳንዳቸውም ነጭ ልብስ ተሰጣቸው፡፡ እንደ እነርሱም ደግሞ ይገደሉ ዘንድ ያላቸው የባሪያዎች ባልንጀራዎቻቸውና የወንድሞቻቸው ቍጥር እስኪፈጸም ድረስ ገና ጥቂት ዘመን እንዲያርፉ ተባለላቸው፤›› (ራእ. ፮፥፱-፲፩)፡፡

ሐ. ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረው የአብርሃም የባለጸጋው እና የአልዓዛር ታሪክ በአካለ ነፍስ ምልጃና ልመና መኖሩን የሚያስረዳ ነው (ሉቃ. ፲፮፥፲፱)፡፡

መ. ቅዱስ ጴጥሮስ ከሞቱ በኋላ ለምእመናን እንደሚጸልይላቸው የገለጠው ሌላው ምስክር ነው፡፡ ‹‹ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳመለከተኝ ከዚህ ማደሪያዬ መለየቴ ፈጥኖ እንዲኾን አውቃለሁና። ከመውጣቴም በኋላ እነዚህን ነገሮች እንድታስቡ በየጊዜው ትችሉ ዘንድ እተጋለሁ፤›› በማለት ቅዱስ ጴጥሮስ እንደ ተናገረው (፪ኛ ጴጥ. ፩፥፲፫-፲፭)፡፡

ማጠቃለያ

በሥጋ የተለዩ፣ በነፍስ ግን ሕያዋን የኾኑ ቅዱሳን በሥጋ ለሞቱት ሰዎች ያማልዳሉ፤ በሥጋ ያልሞቱት ደግሞ በሥጋ ለሞቱት ‹‹አማልዱን›› እያሉ ይጸልያሉ፡፡ ‹‹በዚያ ወራት የወዳጆቼ የጻድቃን ልመናቸው ወደ ሰማይ ወጣች፤ ከዚህ ዓለም በግፍ የፈሰሰ የጻድቁም ደም በመላእክት ጌታ ፊት ተወደደ፡፡ በእነዚህ ወራቶች በሰማይ የሚኖሩ ጻድቃን በአንድ ቃል ኾነው ተባብረው ያመሰግናሉ፤ ለሰው ፈጽመው ይለምናሉ፡፡ ፈጣሪያቸውን ያመሰግናሉ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሄኖክ ፲፪፥፴፫)፡፡ ሙታን ለሕያዋን፣ ሕያዋን ለሙታን ይጸልያሉ ማለትም ይኸው ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን በቅዱሳን ጸሎትና ምልጃ ይጠብቀን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ነገረ ድኅነት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን

በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርተ ወንጌልና ሐዋርያዊ አገልግሎት ማስተባበሪያ 

በስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ዋና ክፍል የተዘጋጀ

የካቲት ፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የዚህ ጽሑፍ መዘጋጀት መሠረታዊ ዓላማ፡-

  • ስለ ሰው መዳን ግልጽ ያልኾነላቸው አካላት ስለ ድኅነት የሚናገሩት ከቅዱሳት መጻሕፍት ውጪ መኾኑን ማሳየት፤
  • በእምነት (በማመን) ብቻ እንድናለን የሚሉ አካላት አስተምህሮ ስሕተት እንዳለበት መግለጽ፤
  • በመስቀል ላይ በተደረገው ድኅነት አዳምና ልጆቹ የዳኑት ከምን እንደ ኾነ ማብራራት፤
  • እንዴትና ከምን እንደ ዳንን ለመግለጽ፤
  • ድኅነታችን እንዴት እንደምንፈጽም በማስረዳት ስለ ሰው መዳን ግልጽ ላልኾነላቸው (የተሳሳተ ትምህርት ለሚሰጡ) አካላት ምላሽ ለመስጠት ነው፡፡

መግቢያ

የሰው ልጅ ትእዛዘ እግዚአብሔርን በማፍረሱ ከእግዚአብሔር ተለየ፤ በዲያብሎስ ቁራኝነት ተይዞ በዲያብሎስ ክፋት ተመርዞ አምስት ሺ ከአምስት መቶ ዘመናትን ኖረ፡፡ ከሰው ልጅ ውድቀት ጀምሮ የሰው ልጅ ፍላጎት ድኅነትን ማግኘት ነበር፡፡ የሰው ልጅ የመዳን ተስፋውን ከፈጣሪው ተቀብሎ በተስፋ ኖረ፡፡ የሰው መዳን የእግዚአብሔር ማዳን በሰጠው ተስፋ መሠረት በነቢያት ትንቢት ተነገረ፤ ሱባዔ ተቈጠረ፡፡ ከዚህ ከደረሰበት መከራ ፍጡር ሊያድነው አይችልምና በእሩቅ ብእሲ (በሰው) ደም ነጻ ሊወጣ አልተቻለውም፡፡ የሰው ልጅ ባቀረበው መሥዋዕት፣ ባደረሰው ጸሎት የነበረበትን ዕዳ መሠረዝ ተሳነው፡፡ ነቢያት፣ ካህናት ለዘመናት የበሬ፣ የላም፣ የበግ መሥዋዕት የፍየል፤ የእኽል፤ የዋኖስ እና የርግብ መሥዋዕት አቀረቡ፤ ስብ አጤሱ፤ የእንስሳትን ደም አፈሰሱ፤ ሰውን ግን ማዳን አልተቻላቸውም፡፡ ‹‹ጽድቃችን እንደ መርገም ጨርቅ ኾነ›› እንዳለ ነቢዩ ኢሳይያስ (ኢሳ. ፷፬፥፮)፡፡

ለአዳም በገባው ቃል ኪዳን መሠረት ድኅነት የናፈቀውን፤ መከራ ያስጨነቀውን የሰውን ልጅ ያድነው ዘንድ ነቢያት በተናገሩት ትንቢት፣ በቈጠሩት ሱባዔ፣ እግዚአብሔር አምላክ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ፣ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደ፡፡ ድኅነት ርቆት፣ መከራ በዝቶበት መዳን ሲፈልግ ከነበረው ሥጋ ጋር ወሀቤ ሕይወት (ሕይወት ሰጭ) አዳኝ ይኾነው ዘንድ መለኮት ተዋሐደ፡፡ ድኅነትን አጥቶ ሲሰቃይ ለነበረው የሰው ልጅ ፈጣሪ የተዘጋ ርስቱን (ገነትን)፣ የተቀማ ልጅነቱን፣ ያጣውን አንድነቱን መለሰለት፡፡ ስለዚህም የምሥራች ተነገረ፤ ድኅነት ተበሠረ፡፡ በዚህም የሰው ልጅ ተጠቀመ፤ የነቢያት ትንቢትም ተፈጸመ፡፡

ሰው የዳነው ከምንድን ነው?

፩. ከበደለው በደል (ጥንተ አብሶ)

የሰው ልጅ በአምላክ ሰው መኾን የበደሉትንም ያልበደሉትንም ያስቀጣ ከነበረው በደል ነጻ ኾኗል፡፡ አሁን ማንም ሰው በአዳም በደል አይጠየቅም፡፡ በራሱ ፈቃድ ሕግ ጥሶ፣ ትእዛዝ አፍርሶ የተከፈለለትን ዋጋ መጠቀም ባለ መቻሉ ይቀጣል እንጂ፡፡ “ከባላጋራችን የተነሣ በትእዛዝ የተጻፈዉን የዕዳችንን ደብዳቤ ደመሰሰልን፤ ከመካከላችንም አራቀው፤ በመስቀሉም ቸነከረው፤” (ቈላ. ፪፥፲፬፤ ራእ. ፩፥፭)፡፡ ለነበረብን በደል ይቅርታ አድርጎ ደሙን አፍስሶ ሥጋውን ቈርሶ ይቅርታ ሰጠን፡፡ ባሮች ነበርን፤ ልጆቹ አደረገን፡፡ የነቢያት ጩኸት ይህን የተመለከተ ነበር፤ “… የቀደመ በደላችንን አታስብብን፤ አቤቱ፥ ምሕረትህ በቶሎ ታግኘን፤ እጅግ ተቸግረናልና፤” የሚል (መዝ. ፸፰፥፰)፡፡ እግዚአብሔር አምላክ የሰውን ጩኸቱን አይቶ ልመናውን ሰምቶ በደሉን አስወግዶለታል፡፡

፪. ከዘለዓለም ሞት (ፈርሶ በስብሶ ከመቅረት፣ ከሞተ ነፍስ)

ሞት ማለት አንደኛ የነፍስና የሥጋ መለያየት ነው፤ የነፍስና የሥጋ መለያየት በትንሣኤ አንድ ኾነው እንደሚነሡ ክርስቶስ በሥጋ ወደ መቃብር፣ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ በሲኦል የነበሩትን ከሞተ ነፍስ ከመከራ ነጻ አወጣ፤ ሙስና መቃብርን አጠፋ፡፡ ለሰው ልጅ፣ ከሞት በኋላ ሕይወት፣ ከመቃብር ባሻገር ትንሣኤ መኖሩን አሳየ፡፡ “ሞት ሆይ፥ እንግዲህ መውጊያህ ወዴት አለ? መቃብር ሆይ፥ አሸናፊነትህ ወዴት አለ?” እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ (፩ኛ ቆሮ. ፲፭፥፶፭)፡፡ “ከሲኦል እጅ እታደጋቸዋለሁ፤ ከሞትም እቤዣቸዋለሁ፤” (ሆሴ. ፲፫፥፲፬) ተብሎ የተነገረው የነቢዩ ቃል ይፈጽም ዘንድ የሰው ልጅ ከሞት (ከዲያብሎስ) ባርነት ከሲኦል ግዛት ድኗል፡፡ “ከጨለማ አገዛዝ አዳነን፤ ወደ ተወደደው ልጁ መንግሥትም መለሰን፤” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ቈላ. ፩፥፲፫)፡፡

የሰው ልጅ በተከፈለለት ዋጋ ከሞተ ነፍስ የሚድንበትን መንገድ አገኘ፤ ፈጣሪው ሰው ኾኖ ከሞት የሚያመልጥበትን መንገድ አስተማረው፡፡ ሞተ ሥጋን በትንሣኤው ድል ነሣለት፤ የተዘጋውን ገነት ከፍቶ ለዘለዓለም በሕይወት መንገድ መራው፡፡ ስለዚህም ነው ጌታችን “እውነት እውነት እላችኋለሁ፤ ቃሌን የሚሰማ በላከኝም የሚያምን የዘለዓለም ሕይወትን ያገኛል፡፡ ከሞትም ወደ ሕይወት ተሻገረ እንጂ ወደ ፍርድ አይሔድም፤” በማለት ያስተማረን (ዮሐ. ፭፥፳፬)፡፡ ይህም በእኛ ሥራ ሳይኾን በእግዚአብሔር ቸርነት የተደረገልን የማዳን ሥራ ነው፡፡ ራሱ ባለቤቱ በይቅርታው ብዛት ያደረገልን ነው፡፡ አምላካችን ፈርሶ በስብሶ መቅረትን አስወገደልን፤ ከሞተ ነፍስም አዳነን፡፡ ሞተ ነፍስ ከእግዚአብሔር መለየት ነበር፤ እግዚአብሔር ሰው ሲኾን ይህ ሞት ተወገደ፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ኾኗልና (ሮሜ. ፰፥፴፩)፡፡

በዚህ መንገድ ከእግዚአብሔር መለየት ቀረልን፤ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ሆኗልና፤ ማለት ከሥጋችን ሥጋ ከነፍሳችን ነፍስ ነሥቶ በተዋሕዶ ከእኛ ጋር ተዛምዷል፤ ስለዚህ የእኛን ሞት እርሱ ሞተልን መከራችንንም ተቀበለልን፡፡ “በእውነት ደዌያችንን ተቀበለ፤ ሕመማችንንም ተሸከመ፤ ስለ እኛም ታመመ፤” እንዳለ ኢሳይያስ (ኢሳ. ፶፫፥፬)፡፡ ደዌያችንን ተቀብሎ ሕመማችንን ተሸክሞ ሞታችንን ሞቶ ሕይወትን ሰጠን፤ ከሞት አዳነን “ዘዚአነ ሞተ ነሥአ ወእንቲአሁ ሕይወተ ወሀበነ፤ የእኛን ሞት ሞቶ የእርሱን ሕይወት ሰጠን፤” እንዳለ ቅዱስ ኤፍሬም፡፡

ክርስቶስ ሞቶ ከተነሣ በኋላ ሞት ኃይሉን አጥቷል፤ ከዚያ በፊት ሞት ሰውን ዂሉ ወደ ሲኦል ወደ ሁለተኛ ሞት የሚያጓጉዝ ነበር፤ አሁን ግን ሰውን ወደ  ሕይወት የሚያደርስ ነው፡፡ ሞት ወደ ገነት ወደ መንግሥተ ሰማያት የምንጓዝበት መንገድ ኾኗል፡፡ ሰዎች የሚፈሩት ሳይኾን የሚፈልጉት ኾኗል፤ ወደ እግዚአብሔር የምንሔድበት ስለ ኾነ፡፡ ከአዳም ጀምሮ እስከ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መምጣት ድረስ የበደሉትም ያልበደሉትም በመስቀል ላይ በተከፈለው ዋጋ ድነዋል፡፡ ጌታችን ይህን ድኅነት የሚናገሩ፣ የምሥራቹን የሚያወሩ፣ ላለፈው ይቅርታ መደረጉን፣ ለሚመጣው ሕግ መሠራቱን የሚመሰክሩ ሐዋርያትን መርጦ ሾመ፡፡ ለወደፊቱ ለሚመጣው ትውልድ ድኅነት እንደሚገኝ ለማስተማር በዓለም ዂሉ ላካቸው፤ በቃላቸውም የሚድኑትን ዕለት ዕለት በእነርሱ ላይ ይጨምር ነበር (ሐዋ. ፪፥፵፯)፡፡

አሁን እንዴት እንድናለን?

የታመሙት ድነዋል፤ ሲኦል የነበሩት ወጥተዋል፡፡ እኛስ ድነናል ወይስ እንድናለን? እኛማ እንድናለን፡፡ ካሣው ለዂሉም ተከፍሏል፤ አምላካችን የሞቱትን አድኗልና፡፡ በሕይወተ ሥጋ ያለን እኛ ግን ድኅነቱን ተቀብለን በሃይማኖት (በእምነት)፣ በጥምቀት፣ ቅዱስ ሥጋውን በመብላት፣ ክቡር ደሙን በመጠጣት የተሠራውን ሕግ በመጠበቅ ድኅነትን እናገኛለን፡፡ ድነናል ብለን የምናወራ ከኾነ ሕግ ለምን አስፈለገን? በገነት ለሚኖሩት ከሲኦል ለወጡት ሕግ አያስፈልጋቸውም፡፡ በተጻፈ ሕግ አይመሩም፤ እኛ ግን በተጻፈ ሕግ ከኦሪት ወደ ወንጌል የተሸጋገርነው የምንጠብቀው እና የሚጠብቀን የሚያድነን ሕግ ተሠርቶልናል፡፡

በዚህ እንድናለን፤  በሕጉ ካልኖርን ደግሞ እንቀጣለን፡፡ ከዚህ ላይ ‹‹የሚድኑትን›› የሚለውን ቃል ልብ ማለት ያሻል፡፡ ‹‹የዳኑትን›› አይደለም ያለው፤ ‹‹የሚድኑትን›› አለ እንጂ፡፡ ስለዚህ ክርስትና ወይም ሕገ ወንጌል የዳኑትን ለማዳን የተሰጠ ሕግ ሳይኾን ያልዳኑት እንዲድኑ የተሰጠ ሕግ ነው፡፡ የኦሪት ሕግ (የኦሪት መሥዋዕት) ማዳን የሚችል አልነበረም፤ ወንጌል ግን ለዓለም ድኅነት የተሰጠ ሕግ ነው፡፡ ሐዋርያት ዓለም እንዲድን የሕይወትን ወንጌል ይዘው ዞሩ፤ አስተማሩ፡፡ ወንጌል የተሰበከው ለዳኑት ሳይኾን ለሚድኑት ነው፡፡ ስለዚህ ለመዳን ምን ያስፈልጋል? የሰው ልጅ ለመዳን የሚስፈልጉት ነገሮች የሚከተሉት ናቸው፤

፩ኛ ማመን

የሰው ልጅ፣ ከዂሉ አስቀድሞ የዓለም መደኀኒት ክርስቶስ ሕግን እንደ ሠራለት አምኖ መመለስ ያስፈልገዋል፡፡ “ለሰው ዂሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃን ወደ ዓለም (ወደ ሰው) የመጣው ነው፡፡ በዓለም ነበረ፤ ዓለሙም በእርሱ ኾነ፤ ዓለሙ ግን አላወቀውም፡፡ ወደ ወገኖቹ መጣ፤ ወገኖቹ ግን አልተቀበሉትም፡፡ ለተቀበሉት ዂሉ ግን በስሙ ለሚያምኑ የእግዚአብሔር ልጆች እንዲኾኑ ሥልጣንን ሰጣቸው፡፡ እነርሱም ከእግዚእሔር ተወለዱ …፤” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ዮሐ. ፩፥፱)፡፡ ቀደም ሲል የነበረው ድኅነት ለተቀበሉትም ላልተቀበሉትም የተደረገ፤ ላመኑትም ላላመኑት የተፈጸመ ድኅነት ነው፡፡ አሁን ግን ላመኑ እንጂ ላላመኑ የሚሰጥ ድኅነት የለም፡፡

፪. መጠመቅ

“ያመነ የተጠመቀ ይድናል” (ማር. ፲፮፥፲፮) ተብሎ በቅዱስ ወንጌል እንደ ተነገረው ለመዳን እምነት ያስፈልጋል፤ ከእምነት ቀጥሎ መጠመቅ ያሻል፤ ይህን ካሣ ተፈጽሞ የተሠራውን ሕግ መፈጸም ግዴታ ነው፡፡ ለመዳን ማመን ብቻ አይበቃም፡፡ እምነትማ አጋንንትም አላቸው፡፡ ዕለት ዕለት የሚድኑበት፣ የሚጨመሩበት መንገዱ እምነትና ጥምቀት ነው፡፡ የቅዱሳን ሐዋርያት ተግባርም ይህ ነበር፡፡ ሕይወትን ድኅነትን መስበክ፤ ያመነውን ማጥመቅ፤ የድኅነቱ ተሳታፊ ማድረግ ወደ ድኅነቱ ማስገባት፤ የሕይወትን ቃል ለዂሉ መመስከር ነው፡፡ ዓላማው ለማሳመን፣ ለማጥመቅ፣ ለማዳን ነው፡፡ ለመዳን አምኖ መጠመቅ የግድ አስፈላጊ መኾኑን በሐዋርያት ሥራ የተመዘገበው የጃንደረባው ታሪክ ያስረዳናል (ሐዋ. ፰፥፴፭-፴፯)፡፡

ማመን ብቻውን ስለማያድን ጃንደረባው ‹‹አምናለሁ›› ብሎ ከማመን አልፎ ሃይማኖቱን መስክሯል፤ ፊልጶስም ‹‹ድነሃል፤ ሒድ›› አላለውም፤ አጠመቀው እንጂ፡፡ ስለዚህ ከእምነት ቀጥሎ መጠመቅ ለድኅነት ወሳኝ ጉዳይ ነው፡፡ ስለዚህ ነው ዓለምን ለማዳን የመጣው አምላካችን ሐዋርያትን ወደ ዓለም ዂሉ የላከው (ማቴ. ፳፰፥፲፱)፡፡ ተልዕኮውም በቃ ‹‹አድኛቸዋለሁ›› አይደለም፤ እንዲያምኑ፣ እንዲጠመቁ፣ ትእዛዙን እንዲጠብቁ፣ ደቀ መዛሙርት እንዲኾኑ ነው፡፡ ድኅነት የሚገኘው በዚህ መንገድ ነው፡፡ በማውራት ብቻ ‹‹ድኛለሁ›› ብሎ ተዘልሎ በመቀመጥ አይደለም፡፡ “… እነዚህ ሰዎች የልዑል እግዚአብሔር አገልጋዮች ናቸው፤ የሕይወትንም መንገድ ያስተምሯችኋል …” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሐዋ. ፮፥፲፯)፡፡

ቅዱሳት መጻሕፍት የመዳንን መንገድ የሚነግሩን እንድናየው አይደለም፤ እንድንጓዝበት ነው እንጂ፡፡ “… ‹ጌቶቼ፥ እድን ዘንድ ምን ላድርግ?› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እመን፤ አንተ እና ቤተሰቦችህ ትድናላችሁ› አሉት፡፡ የእግዚአብሔርንም ቃል ለእርሱና በቤቱ ላሉት ዂሉ ነገሩአቸው … በዚያው ጊዜ ከቤተ ሰቡ ዂሉ ጋር ተጠመቀ፤” (ሐዋ. ፲፮፥፴-፴፬)፡፡ ከዚህ ላይ ‹‹ድናችኋል›› ሳይኾን ‹‹ትድናላችሁ›› የሚለውን ቃል ልብ ይሏል፡፡ “ዳግመኛ ከውኃ እና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ሰው ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም” እንዳለ (ዮሐ. ፫፥፭)፡፡ ስለዚህ ሰው አምኖ ይጠመቃል፤ ከእግዚአብሔርም ይወለዳል፤ በዚህ ድኅነትን ገንዘብ ያደርጋል፡፡ ከእግዚአብሔር ካልተወለደ በፍጹም ሊድን አይችልም፡፡ መዳን ማለት የእግዚአብሔርን መንግሥት ወርሶ ስሙን ቀድሶ መኖር ነው፡፡ ስለዚህ የሕይወት እና የድኅነት ወንጌል ለዓለሙ ዂሉ ይሰበካል፤ ዂሉም ይድን ዘንድ (ማር. ፲፮፥፰)፡፡

፫. ሥጋውን መብላት ደሙን መጠጣት

ሰው ካመነ ከተጠመቀ በኋላ ማድረግ ያለበት ቅዱስ ሥጋውን መብላት፣ ክቡር ደሙን መጠጣት ነው፡፡ ሥጋ ወደሙ ሕይወት የሚገኝበት የእምነት እና የጥምቀት ማተሚያ መደምደሚያ ነው፡፡ እምነት መሠረት፤ ጥምቀት መሰረት የሚጸናበት ከእግዚአብሔር የምንወለድበት፤ ሥጋው እና ደሙ ማረጋገጫ ነው፡፡ ያመነ በጥምቀት ይወለዳል፤ የተወለደ ደግሞ የሚያድግበት ምግብ ያስፈልገዋል፡፡ ምግቡም ሥጋውና ደሙ ነው፡፡ ይህን በልቶ ጠጥቶ የሚኖር የእግዚአብሔር ልጅ፣ የእግዚአብሔር የመንግሥቱ ወራሽ፣ የስሙ ቀዳሽ ይኾናል፡፡

“የሰው ልጅ ለሚሰጣችሁ ለዘለዓለም ሕይወት ለሚኖር መብል ሥሩ እንጂ ለሚጠፋው መብል አይደለም፤ ይህን እግዚአብሔር አብ አትሞታልና … የእግዚአብሔር እንጀራ ከሰማይ የሚወርድ፤ ለዓለም ሕይወትን የሚሰጥ ነውና …” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ዮሐ. ፮፥፳፯-፶፬፤ ሮሜ. ፭፥፱፤ ኤፌ. ፩፥፯፤ ፩ኛ ዮሐ. ፩፥፯)፡፡ ስለዚህ አምነን ተጠምቀን ሥርየት የተገኘበትን እና የሚገኝበትን ሥጋውን መብላት ያፈልጋል፡፡ በሃይማኖት ከብረን፣ በጥምቀት ተወልደን፣ በሥጋው በደሙ ታትመን ድኅነትን ገንዘብ እናደርጋለን፡፡

፬. መልካም መሥራት (ዐቂበ ሕግ)

ያመነ፣ የተጠመቀ፣ ሥጋውን የበላ፣ ደሙን የጠጣ ዂሉ በመልካም ሥራ መኖር አለበት፡፡ መልካም ሥራ የሌለው እምነት፣ ጥምቀት፣ ቊርባን ብቻውን አያድንም፤ ያመነ የተጠመቀ ሰው ፈጣሪውን በሃይማኖት መከተል በግብር መምሰል አለበት፡፡ “መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ፤” (ማቴ. ፭፥፲፮)፡፡ የሰው ልጅ ከላይ የተዘረዘሩ ተግባራትን ከፈጸመ እንንደየሥራው መጠን ዋጋውን እንደሚቀበል ቅዱሳት መጽሐፍት ምስክሮች ናቸው፡፡ “እነሆ በቶሎ እመጣለሁ፤ ለእያንዳንዱ እንደየሥራው መጠን እከፍለው ዘንድ ዋጋዬ ከእኔ ጋር ነው፤” (ራእ. ፳፪፥፲፪፤ ያዕ. ፪፥፳፮)፡፡

አምላካችን ለፍርድ ሲመጣ የሚጠይቀው ሃይማኖት ብቻ ሳይኾን ሥራ መኾኑን መዘንጋት ሞኝነት ነው፡፡ “… ብራብ አላበላችሁኝም፤ ብጠማ አላጠጣችሁኝም፤ ብታረዝ አላለበሳችሁኝም …” እንዳለ ጌታችን (ማቴ. ፳፭፥፴፭-፵፭)፡፡ ስለዚህ ለድኅነቱ ተግባር አስፈላጊ ነው፡፡ ከተግባር ጋር ዐቂበ ሕግ (ሕግ መጠበቅ) ተገቢ ነው፡፡ “የዘለዓለም ሕይወትን አገኝ ዘንድ ምን ላድርግ?” ብሎ ለጠየቀው ጐልማሳ ጌታችን የሰጠው ምላሽም “… ትእዛዛትን ጠብቅ” የሚል ነው (ማቴ. ፲፱፥፲፮-፲፯)፡፡ የዘለዓለም ሕይወትን ለመውረስ እግዚአብሔር በቸርነቱ የሚቀበለው መልካም ሥራ ወሳኝ ጉዳይ ነውና፡፡

፭. መጽናት

ለመዳን ከማመን፣ ከመጠመቅ፣ ሥጋውን ከመብላት፣ ደሙን ከመጠጣት በተጨማሪ በዚሁ ጸንቶ መኖር ያስፈልጋል፡፡ ገብተው የወጡ፤ አምነው የካዱ ዂሉ ድኅነት የላቸውም፡፡ “በዂሉም ዘንድ ስለ ስሜ የተጠላችሁ ትኾናላችሁ፤ እስከ መጨረሻ የሚጸና ግን እርሱ ይድናል፤” (ማቴ. ፲፥፳፪፤ ፳፬፥፲፫፤ ማር. ፲፫፥፲፫)፡፡ “እኛም የምንደፍርበትን የምንመካበትን ተስፋ እስከ መጨረሻው አጽንተን ብንጠብቅ ቤቱ ነን … የመጀመሪያ እምነታችንን እስከ መጨረሻው አጽንተን ብንጠብቅ የክርስቶስ ተካፋዮች ኾነናል …” (ዕብ. ፫፥፮-፲፬)፡፡ “እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ኹን፤ የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለሁ፤” (ራእ. ፪፥፲)፡፡

“ድል ለነሣውና እስከ መጨረሻ ሥራዬን ለጠበቀው እኔ ደግሞ ከአባቴ እንደ ተቀበልኩ በአሕዛብ ላይ ሥልጣን እሰጠዋለሁ፡፡ በብረት በትር ይገዛቸዋል፤ እንደ ሸክላ ይቀጠቅጣቸዋል፤” (ራእ. ፪፥፳፮)፡፡ የሰው ልጅ የሚድነው በእምነት፣ በጥምቀት፣ በሥጋው በደሙ፣ በመልካም ሥራ ጸንቶ ሲኖር ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ጸንተን እንድኖር እና መንግሥቱን እድንወርስ፤ ስሙን እንድንቀድስ አምላካችን በቸርነቱ ይርዳን፡፡ እንግዲህ ዂላችሁም ወደ ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በመመለስ (በመምጣት) ድኅነታችሁን በመፈጸም የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ የተዘጋጃችሁ ኹኑ መልእክታችን ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

አውጣኪ፣ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ እና የኬልቄዶን ጉባኤ – ካለፈው የቀጠለ

በቀሲስ ዶ/ምክረ ሥላሴ ገ/አማኑኤል

ጥር ፳፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.

… ቀጥሎ በ2ኛው የኤፌሶን ጉባኤ የተወገዘው የዶሪሌኡም ኤጲስቀጶስ አውሳብዮስ ተነሥቶ ዲዮስቆሮስ እሱንና የቊስጥንጥንያውን ፍላብያኖስን ‹‹ምንም የሃይማኖት ጕድለት ሳይገኝብን ያለ አግባብ አውግዞናል ጥቃትም አድርሶብናል፡፡ በተጨማሪም አውጣኪን ከግዝቱ በመፍታት የኦርቶዶክስ እምነትን አበላሽቷል፤›› በማለት ክስ አቀረበ፡፡ ይህ ተመሳሳይ ክስ በሮሙ ፖፕ ተወካዮችም ቀርቧል፡፡ በመሠረቱ ይህ ክስ እውነት እንኳ ቢሆን የሚመለከተው ሲኖዶሱን እንጂ የሲኖዶሱን ሊቀ መንበር ዲዮስቆሮስን አልነበረም፡፡ ከዚህ ላይ ልንገነዘበው የሚገባው የሮሙ ፖፕ ተወካዮችም ሆኑ ከሳሹ አውሳብዮስ በአጠቃላይ የኬልቄዶን ጉባኤም ቢሆን ዲዮስቆሮስን በእምነት ክህደት አልከሰሱትም፡፡ ሆኖም መናፍቅ ነው ተብሎ የታሰበውን አውጣኪን የ449 ዓ.ም. ሲኖዶስ ነጻ አድርጎ ከውግዘቱ ስለፈታው ብቻ ዲዮስቆሮስን የአውጣኪን የኑፋቄ ትምህርት ተቀብሏል ብለው በጭፍኑ ደምድመዋል፡፡ አውጣኪ ግን በፊት ያስተምር የነበረውን የኑፋቄ ትምህርት ትቶ በቃልም በጽሑፍም ኦርቶዶክሳዊ የእምነት መግለጫ በማቅረቡ በዚህ መሠረት ነው 2ኛው የኤፌሶን (የ449) ሲኖዶስ ነጻ ያደረገው፡፡ ስለዚህ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ አውጣኪ ያቀረበው የእምነት መግለጫ የሚገኝበት የ449 ሲኖዶስ ቃለ ጉባኤ እንዲነበብ ጠየቀ፡፡

የ449 ሲኖዶስ ቃለ ጉባኤ የመጀመሪያው ክፍል ከተነበበ በኋላ ጉባኤውን የጠራው ንጉሡ ዳግማዊ ቴዎዶስዮስ መሆኑና አውጣኪንም ነጻ ያደረጉት በጉባኤው የነበሩት ጳጳሳት በሙሉ ተስማምተው በፊርማቸው ያጸደቁት መሆኑ ተነበበ፡፡ በ449 ዓ.ም. በ2ኛው የኤፌሶን ሲኖዶስ ላይ የነበሩት ጳጳሳት ግን የ449 ሲኖዶስን ውሳኔ ፈጽሞ እንደማያውቁት የፈረሙትም በወታደሮች ተገደው በባዶ ወረቀት ላይ መሆኑን አጥብቀው ተናገሩ:: የግብጽ ጳጳሳት ግን ይህን በሰሙ ጊዜ ‹‹የክርስቶስ ወታደር የዚህን ዓለም ባለሥልጣን ፈጽሞ አይፈራም፡፡ እሳት አንድዱ አንድ ሰማዕት እንዴት እንደሚሞት እናሳያችሁ!›› ብለው በጉባኤው ፊት ተናገሩ፡፡ ባዶ ወረቀት ላይ ነው የፈረምነው ካሉት አንዱ የኤፌሶኑ ኤጲስ ቆጶስ እስጢፋኖስ ነበር፡፡ ይህ ሰው አውጣኪ ነጻ እንዲደረግ ተነሥተው ከተናገሩት ሰዎች ሁለተኛው ነበር፡፡ አውሳብዮስና ፍላብያኖስም እንዲወገዙ ከተናገሩት 5ኛው ተናጋሪ እሱ ነበር፡፡  የሲኖዶሱ ጸሓፊ በ449 ሲኖዶስ ቃለ ጉባኤ ላይ የአውጣኪን የሃይማኖት መግለጫ ሲያነብ አንዳንድ አባቶች ይህን መግለጫ እንዳላዩትና ፊርማቸውም አስመስሎ የተፈረመ ነው በማለት ካዱ፡፡

ከዚህ በኋላ በጉባኤው ፓትርያርክ ዲዮስቆሮስ እምነቱን እንዲገልጽ ተጠይቆ ሁለቱ ባሕርያት (የመለኮትና የሥጋ) ያለ መቀላቀልና ያለ ትድምርት፣ ያለ መለወጥና ያለ መለያየት በአንድ አካል እንደተዋሐዱ በሚገባ አስረዳ፡፡ እንዲሁም በቅዱስ ቄርሎስ ትምህርት መሠረት ‹‹አአምን በአሐዱ ባሕርይ (ህላዌ) ዘቃለ እግዚአብሔር ሥግው፤›› ብሎ አስረዳ፡፡ ጉባኤውም በዚህ በዲዮስቆሮስ እምነት ላይ ምንም እንከን፣ ምንም ስሕተት አላገኘም፡፡ ጉባኤው በሌላ መንገድ ‹‹አውጣኪ በጽሑፍ ካቀረበው የተለየ በቃል ቢናገር ምን ትፈርድ ነበር?›› ብለው በጠየቁት ጊዜ፣ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ‹‹አውጣኪ የጻፈውን ትቶ ሌላ የክህደት ነገር ቢናገር፣ እሱን ማውገዝ ብቻ ሳይሆን በእሳትም እንዲቃጠል እፈርድበት ነበር፤›› ብሎ መለሰ፡፡ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ በእንደዚህ ያለ ነጐድጓዳዊ አነጋገር ሁሉን ግልጥልጥ አድርጎ በተናገረ ጊዜ፣ ኬልቄዶናውያን ጸጥ አሉ፡፡ ዲዮስቆሮስን በመቃወም የተናገሩ የምሥራቅ አህጉር ጳጳሳት ግን ንግግሩ ልባቸውን ነክቶት ‹‹በድለናል፤ ይቅርታ እንጠይቃለን!›› በማለት ጮኹ፡፡

የመንግሥቱ ዳኞች በባዶ ወረቀት ላይ ነው የፈረምነው ስላሉት እንደገና ሲጠይቋቸው ‹‹በድለናል፤ ይቅርታ እንጠይቃለን፤›› ሲሉ መለሱ፡፡ እንደገና ፍላብያኖስን ዲዮስቆሮስ ነው ያስገደለው ስላሉት ቢጠየቁ አሁንም ‹‹በድለናል፤ ይቅርታ እንጠይቃለን፤›› ሲሉ መለሱ፡፡ በዚህ ሁኔታ እነዚህ ጳጳሳት 1ኛ/ በሐሰት በባዶ ወረቀት ላይ ፈርመናል በማለታቸውና፣ 2ኛ/ ፍላብያኖስንና አውሳብዮስን ያለ አግባብ በማውገዛቸው ይቅርታ ጠየቁ፡፡ የመንግሥቱ ዳኞች ፍላብያኖስ ኦርቶዶክስ መሆኑን አጥብቀው በጠየቁ ጊዜ፣ የሮሙ ተወካዮችና አብዛኞቹ አባላት በ449 ሲኖዶስ ጊዜ የነበሩትም ጭምር ፍላብያኖስ ኦርቶዶክስ እንደነበረ ተናገሩ፤ ‹‹ታዲያ ለምን ተወገዘ?›› ሲሉ ዳኞቹ ጠየቁ፡፡ በዚህ ጊዜ ዲዮስቆሮስ ፍላብያኖስ ‹‹ክርስቶስ ከሥጋዌ በኋላ ሁለት ባሕርያት እንዳለው አጥብቆ ይናገር ነበር፤›› ብሎ ተናገረ፡፡ የዚህም እውነት እንዲወጣ ብሎ የ449 ሲኖዶስ ቃለ ጉባኤ ቀርቦ እንዲነበብ አበክሮ ጠየቀ፡፡ ለዚህ ምንም መልስ አልተሰጠውም፡፡

ሁሉም ዳኞቹም ጭምር ቃለ ጉባኤው እንዳይነበብ ስለፈለጉ ጸጥ አሉ፡፡ ሁሉም ዝም ቢሉም ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ንግግሩን በመቀጠል ፍላብያኖስ ‹‹ክርስቶስ ከሥጋዌ በኋላ ሁለት ባሕርያት አለው፤›› እያለ እንደሚናገር መልሶ መላልሶ አስረዳ፡፡ የቀድሞ አባቶች ግን ለምሳሌ አትናቴዎስ፣ ጎርጎርዮስና ቄርሎስ ‹‹አሐዱ ባሕርይ ዘእግዚአብሔር ቃል ሥግው›› እንጂ ከተዋሕዶ በኋላ ‹‹ሁለት ባሕርያት›› ፈጽሞ እንደማይሉ በመጻሕፍቶቻቸው ሁሉ ለማንበብ እንደሚቻል አስረዳ፡፡ የቀረቡትን ማስረጃዎች ሁሉ ከቁም ነገር ሳያስገቡ ጉባኤውም በሚገባ ሳይወያይበት ዳኞቹ በጭፍን ፍላብያኖስና አውሳብዮስ ያላግባብ ነው የተወገዙት በማለት ውሳኔ አሳለፉ፡፡ በተጨማሪም አውጣኪ ቀርቦ ሳይጠየቅ ለ449 ጉባኤ ያቀረበውንም የሃይማኖት መግለጫ ሳይመለከቱ፣ በጭፍን በ449 ሲኖዶስ ላይ ያለ አግባብ ነው ነጻ ሆኖ ከግዝቱ የተፈታው ብለው ዳኞቹ፣ የፖፑ ተወካዮችና ሌሎቹ የጉባኤው አባላት ወሰኑ፡፡ ይህ በግልጥ የሚያመለክተው የኬልቄዶን ጉባኤ የተጠራው ዲዮስቆሮስንና አውጣኪን ለማውገዝና ፍላብያኖስንና አውሳብዮስን ነጻ ለማድረግ መሆኑን ነው፡፡

ከላይ ለቀረቡት ጥብቅ ማስረጃዎች ምንም መልስ ሳይሰጡ የመንግሥቱ ዳኞችና የሮሙ ፖፕ እንደራሴዎች የፖፑን የዶግማ ደብዳቤ (Tomos) አስተያየቱን እንዲገልጥ ለፓትርያርክ ዲዮስቆሮስ ሰጡት፡፡ ዲዮስቆሮስም ለጥቂት ጊዜ ከአነበበው በኋላ፣ ደብዳቤው ኦርቶዶክሳዊ ሳይሆን ንስጥሮሳዊ መሆኑን ገልጦ ደብዳቤውንና ደራሲውን ያለ አንዳች ማመንታት አወገዘ፡፡ ከተሰበሰቡት ጳጳሳት ብዙዎቹ ስለ ልዮን ደብዳቤ (Tomos) የዲዮስቆሮስን አስተያየትና ስሜት ተጋርተዋል፡፡ ነገር ግን አስተያታቸውን በይፋ ለመግለጥ ድፍረት አልነበራቸውም፡፡ ሌሎች ደግሞ ስለዚሁ ደብዳቤ ታላቅ ጥርጣሬና መደናበር እንዳደረባቸው በፊታቸው ላይ ይነበብ ነበር፡፡ ይህን የአባላቱን ሁኔታ የተመለ ከቱት ዳኞች በደብዳቤው ውስጥ የሚያውክና የሚያስቸግር ነገር እንዳለ ጥያቄ አቀረቡ፡፡ አንዳንድ ጳጳሳት ምንም ችግር አለመኖሩን ገልጠው፣ ሆኖም አንዳንድ የላቲን ቃላትንና አባባሎችን በደንብ ለመመርመር ጊዜ ለማግኘት ስብሰባው ለአምስት ቀናት እንዲበተን ጠየቁ፡፡ ጥያቄአቸውም ወዲያውኑ ተቀባይነት አግኝቶ ስብሰባው ተበተነ፡፡

ነገር ግን ከሦስት ቀናት በኋላ ጳጳሳቱ የመንግሥቱ ዳኞች በሌሉበት ለነሱም ሳይነግሩ ይፋዊ ስብሰባቸውን በፖፑ እንደራሴ ፓስካሲኑስ (Paschasinus) ሊቀ መንበርነት ቀጠሉ፡፡ በዚህ ስብሰባ ላይ የግብጽ ጳጳሳትና ሌሎች ብዙ ጳጳሳት አልተገኙም፡፡ ስብሰባውን እንደጀመሩ የፖፑ እንደራሴና የስብሰባው ሊቀ መንበር ‹‹የፖፑ ደብዳቤ መከበር አለበት፡፡ ሁሉም ደብዳቤውን መቀበል አለባቸው፡፡ ይህን ደብዳቤ የሚቃወም ተከሶ በጉባኤው ፊት መቅረብ አለበት፤›› ሲል አወጀ፡፡ ወዲያውኑ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወደ ስብሰባው እንዲመጣ ወደ ማረፊያ ቦታው ሦስት ጳጳሳትና አንድ ዲያቆን ተላኩ፡፡ በዚያን ጊዜ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ከቤት እንዳይወጣ ንግሥት ብርክልያ ባዘዘቻቸው ወታደሮች ይጠበቅ ነበር፡፡ መልእክተኞቹም ዲዮስቆሮስን ወደ ጉባኤው እንዲመጣ በጠየቁት ጊዜ፣ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ‹‹ጉባኤው የተበተነው ለአምስት ቀናት ሲሆን አሁን ገና ሦስት ቀናት ነው ያለፉት፡፡  አሁን እንዴት ለመሰብሰብ እንችላለን? ለመሆኑ የመንግሥቱ ተወካዮች ዳኞች ተነግሯቸዋል?›› ብሎ ጠየቀ፡፡ ለመጀመሪያው ጥያቄ መልስ አልተሰጠውም፡፡ ለሁለተኛው ጥያቄ ግን ‹‹ለቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ምእመናን አያስፈልጉም፤›› ሲሉ መለሱለት፡፡

ቀጥሎ ከቤት ወጥቶ ወደ ስብሰባው ለመሄድ ይፈቅዱለት እንደሆነ ወታደሮቹን ማስፈቀዳቸውን መልእክተኞቹን ጠየቀ፡፡ እነርሱም በበኩላቸው ‹‹እኛ የተላክነው አንተን እንድንጠራ ነው እንጂ ወታደሮችን እንድንጠይቅ እይደለም፤›› ሲሉ መለሱና ተመልሰው ሄዱ፡፡ ለሁለተኛ ጊዜ ሌሎች መልእክተኞች ለዲዮስቆሮስ ሌላ ጥሪ አቀረቡ፡፡ እሱም የመንግሥት ተወካዮች ዳኞች ከሌሉ እንደማይ መጣ ነግሯቸው ተመለሱ፡፡ ይህ ሁሉ የተደረገው በሲኖዶስ ሕግ መሠረት አንድ ሰው ሦስት ጊዜ ተጠርቶ ካልመጣ እንደሚወገዝ ስለሚያውቁ በዚሁ መሠረት ዲዮስቆሮስን በሌለበት ለማውገዝና የፖፕ ልዮንን የዶግማ ደብዳቤ (Tome of Leo) ሁሉም እንዲቀበሉት ለማድረግ ነበር፡፡ ይህም የታቀደው በፖፑ ወኪሎች ነበር፡፡ በዚህ መካከል ሌሎች ከሳሾች ቀርበው በፓትርያርክ ዲዮስቆሮስ ላይ የተለያዩ እምነትን የማይመለከቱ የሐሰት ክሶችን እንዲያቀርቡ ተደረገ፡፡ በመጨረሻም ዲዮስቆሮስ ወደ ጉባኤው እንዲመጣ ለሦስተኛ ጊዜ መልእክተኞች ላኩበት፡፡ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ የኬልቄዶን ጉባኤ ሤራ በደንብ ስለገባው የሃይማኖት መልእክቱን ቀደም አድርጎ ያስተላለፈ መሆኑን ገልጾ በሕመም ምክንያት ወደ ጉባኤው ለመሄድ አለመቻሉን ስለገለጠላቸው መልእክተኞቹ ተመልሰው ሄዱ፡፡ የፖፑ ተወካዮችና አንዳንድ የእነርሱ ደጋፊዎች ዲዮስቆሮስን ለማውገዝ ይህንኑ ነበር የፈለጉት፡፡

የቅዱስ ዲዮስቆሮስ በኬልቄዶናውያን መወገዝ

የሮሙ ፖፕ ልዮን፣ የሮም የምሥራቁ ክፍል ንጉሠ ነገሥት የመርቅያንና የንግሥቲቱ የብርክልያ ታላቅ ተጽእኖ የነበረበት ይህ የኬልቄዶን ጉባኤ መጀመ ሪያም የተሰበሰበው ዲዮስቆሮስን ለማው ገዝና ከሥልጣኑ ለማውረድ ስለነበረ፣ እሱን ለማውገዝ ብዙ ምክንያቶች ይፈልጉ ነበር፡፡ በሃይማኖት በኩል ምንም ስሕተት ስላላገኙበት የቤተ ክርስቲያንን ቀኖና አፍርሷል በማለት እሱን ወንጀለኛ ለማድረግ አስበው ሕጉን የሚያስከብሩት የመንግሥት ዳኞች ለአምስት ቀናት ጉባኤውን በበተኑበት ጊዜ ከግማሽ ያነሱ አባላት ተሰብስበው ቅዱስ ዲዮስቆሮስ በጉባኤው ላይ እንዲገኝ ሦስት ጊዜ ደጋግመው ጥሪ እንዲደርሰው አደረጉ፡፡ ዲዮስቆሮስም ከላይ እንደተገለጸው ሕግ አስከባሪዎቹ ዳኞችና ሌሎች ከእርሱ ጋር የተከሰሱት በሌሉበት ለመገኘት ስላልፈለገ በጉባኤው ላይ አልተገኘም፡፡ ይህን ምክንያት አድርገው ‹ሲያሻኝ ጭስ ወጋኝ› እንደሚሉት ቀኖና አፍርሷል በማለት የተሰበሰቡት በአንድ ድምፅ አወገዙት፡፡

ሲያወግዙትም ሦስት ምክንያቶች ዘርዝረዋል፤ 1ኛ/ በመናፍቅነት የተከሰሰውንና የተወገዘውን አውጣኪን ነጻ አድርጎ ወደ ቤተ ክርስቲያን አንድነት መልሶታል፡፡ ከዚህ ላይ አውጣኪ በጽሑፍ ያቀረ በውንና በቃልም ያረጋገጠውን ኦርቶዶክሳዊ የሃይማኖት መግለጫ ሊመለከ ቱት አልፈለጉም፡፡ 2ኛ/ የሮሙ ፖፕ ልዮን የላከውን የሃይማኖት መግለጫ ደብዳቤ (The Tome of Leo) ባለመ ቀበል ደብዳቤውንም ፖፕ ልዮንንም አውግዟል የሚል ነው፡፡ 3ኛ/ በጉባኤው ላይ እንዲገኝ ሦስት ጊዜ ተጠርቶ አልተገኘም የሚል ነበር፡፡

ፓትርያርክ ዲዮስቆሮስ ከተወገዘና ከሥልጣን እንዲወርድ ከተወሰነበት በኋላ ንግሥት ብርክልያ በግል አስጠርታ ሐሳቡን ለውጦ በልዮን ጦማር (Tome of Leo) ላይ እንዲስማማና እንዲፈርም ትእዛዝ አዘል ምክር ሰጥታው ነበር ይባላል፡፡ እሱ ግን መንፈሰ ጠንካራ ስለነበር የንግሥቲቱን ትእዛዝና ምክር አልተቀበለም፡፡ በዚህ ተናዳ ንግሥቲቱ ቅዱስ ዲዮስቆሮስን በወታደሮች በሚያሰቅቅ ሁኔታ አስደበደበችው፡፡ በዚህም ድብደባ ጥርሶቹ ወላልቀው ጽሕሙም ተነጫጭቶ ነበር፡፡ እሱም የተነጨ ጽሕሙንና የወለቁትን ጥርሶች በአንድ ላይ ቋጥሮ ‹‹ይህ የሃይማኖት ፍሬ ነው፤›› የሚል ጽፎበት ለግብጽ ምእመናን ልኮላቸዋል ይባላል፡፡

የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወደ ግዞት መላክ

እጅግ የሚገርመው የኬልቄዶን ጉባኤ ስብሰባውን ሳይፈጽም የጉባኤውም ዘገባ ገና ሳይደርሰው የቊስጥ ንጥንያ ንጉሠ ነገሥት መርቅያን የጉባኤውን ውሳኔዎች ሁሉ የሚያጸድቅ ጽሑፍ ለጉባኤው ላከ፡፡ እንዲሁም ንጉሡ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ጋግራ (ጋንግራ) ወደሚባል ደሴት እንዲጋዝ ትእዛዝ አስተላለፈ፡፡ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወደተጋዘበት ወደ ደሴተ ጋግራ በሄደ ጊዜ በፈቃዳቸው ሁለት ጳጳሳትና ሁለት ዲያቆናት ተከትለዉት ሄደው ነበር፡፡ ሦስተኛው ጻድቅ የነበረ መቃርዮስ የተባለ የኤድኮ ጳጳስ አብሮት ለመሄድ በመንገድ ላይ ሳለ ‹‹ቅዱስ ማርቆስ ደሙን ባፈሰሰበት ከተማ የሰማዕትነት አክሊል ስለሚጠብቅህ ቶሎ ብለህ ሂድ እንዳያመልጥህ፤›› ብሎ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ስለነገረው ወዲያውኑ ወደ ግብጽ ሄደ፡፡ ንጉሠ ነገሥት መርቅያን ፓትርያርክ ዲዮስቆሮስን ወደ ግዞት እንዲላክ ከአደረገ በኋላ የጉባኤው ውሳኔ በመንግሥት መጽደ ቁን በመግለጽ ለእስክንድርያና ለመላዋ የግብጽ ሕዝብና ለግብጽ ቤተ ክርስቲያን መልእክት ላከ፡፡ ወዲያውኑም በዲዮስቆሮስ ምትክ ፕሮቴሪዮስ የሚባል ኤጲስ ቆጶስ በቊስጥ ንጥንያ ሹሞ ወደ እስክንድርያ በብዙ ወታደሮች ታጅቦ እንዲሄድ አደረገ፡፡ ወታደሮቹም ለአዲሱ ፓትርያርክ የማይታዘዙትንና የማይገዙትን ከባድ ቅጣት እንዲቀጡ በጥብቅ ታዝዘው ነበር፡፡

የግብጽ ክርስቲያኖች ግን ለዲዮስቆሮስ ታማኝነታቸውን በመግለጥ ንጉሡ ለላከው ፓትርያርክ አንገዛም አሉ፡፡ የግብጽ ጳጳሳትም አስቸኳይ ስብሰባ አድርገው ለፓትርያርክ ዲዮስቆሮስ ታማኝነታቸውን በአንድ ድምፅ ገልጠው፣ ፖፕ ልዮንንና የልዮንን ጦማር (The Tome of Leo I) እንዲሁም የኬልቄዶንን ጉባኤን ጉባዔ ከለባት ብለው በመጥራት አወገዙት፡፡ ፓትርያርክ አንዲሆን የተላከባቸውንም ፕሮቴሪዮስን አወገዙ፡፡ ንጉሠ ነገሥቱ መርቅያንም ይህን እንደሰማ አጸፋውን ለመመለስ ጳጳሳቱ በሙሉ በኬልቄዶን ጉባኤ ውሳኔና በልዮን ጦማር ላይ እንዲ ፈርሙ በግብጽ ለነበሩት የጦር ሹማም ንቱና መኰንኖቹ ትእዛዝ አስተላለፈ፡፡ መኰንኖቹም በትእዛዙ መሠረት ጽሑፎቹን ለማስፈረም ወደየጳጳሳቱ ሲሄዱ መጀመሪያ የተገኘው ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወደ ግዞት ሊከተለው ሲል ‹‹ወደ እስክን ድርያ ሂድ፤ በዚያ የሰማዕትነት አክሊል ይጠብቅሃል፤›› ያለው የኤድኮ ጳጳስ አባ መቃርዮስ ነበር፡፡ ወታደሮቹ ጽሑፎቹን አልፈርምም በማለቱ ከዚያው ደብድበው ገድለውታል፡፡ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነታቸው በመጽናታቸውና የኬልቄዶንን ጉባኤ ባለመቀበላቸው ሠላሳ ሺሕ (30,000) የሚሆኑ ካህናትና ምእመናን ተገድለዋል፡፡ ከጥቂት የሰበካ አብያተ ክርስቲያናት በስተቀር አብዛኞቹ የአብያተ ክርስቲያናት ሕንጻዎች የኬልቄዶንን ጉባኤ ለሚደግፉ ጥቂት ክርስቲያኖች በንጉሠ ነገሥቱ ትእዛዝ እንዲሰጣቸው ተደረገ፡፡

ፓትርያርክ ዲዮስቆሮስ አምስት ዓመት በግዞት ግፍና ሥቃይ እየተቀበለ ከቆየ በኋላ በ456 ዓ.ም. ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ፡፡ መላው የግብጽ ካህናትና ምእመናን የአባታቸውን ማረፍ በሰሙ ጊዜ ታላቅ ሐዘን ተሰማቸው፡፡ ወዲያውኑ ካህናቱና ሕዝበ ክርስቲያኑ ተሰብስበው የዲዮስቆሮስ ዋና ጸሓፊ የነበረውን ጢሞቴዎስ የተባለውን አባት በአንድ ድምፅ መርጠው በዲዮስቆሮስ ፋንታ ዳግማዊ ጢሞቴዎስ ተብሎ የእስክን ድርያ 26ኛው ፓትርያርክ ሆኖ እንዲሾም አደረጉ፡፡ ይህ ምርጫ በሚካሄድበት ጊዜ የንጉሠ ነገሥቱ የመርቅያን ዋና እንደራሴ አገረ ገዥው በእስክንድርያ አልነበረም፡፡ ገዥው ሲመለስ የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ካህናትና ምእመናን አዲስ ፓትርያርክ መርጠው መሾማቸውን በሰማ ጊዜ እጅግ ተናደደ፡፡ አገረገ ዥውም ግብጻውያን ፓትርያርክ የመምረጥ መብት እንዳልነ በራቸው ነገራቸው፡፡ ለማናቸውም እርሱ እስከሚመለስ ድረስ መጠበቅ ነበረባቸው በማለት ምርጫውን እንደማይቀበለው በግልጥ ነገራቸው፡፡ ለእነሱ የተሾመላቸ ውንና መንግሥትም የሚቀበለውን ፕሮቴሪዮስን የግድ መቀበልና ለእርሱ መታዘዝ እንዳለባቸው ነግሮአቸው ሌላ ፓትርያርክ መምረጥ በመንግሥት ላይ እንደማመፅ የሚያስቆጥርና ከባድ ቅጣት የሚያስከትል ነው በማለት አስጠነቀቃቸው፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ አዲሱ የእስክንድርያ ፓትርያርክ ዳግማዊ ጢሞቴዎስ ጳጳሳቱን በሙሉ ጠርተው ሲኖዶስ አደረጉና የኬልቄዶንን ጉባኤና የጉባኤውን ደጋፊዎች እንደገና አወገዟ ቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ዲዮኒስዮስ የሚባል አንድ የመንግሥት ወታደራዊ ከፍተኛ ባለሥልጣን ከቊስጥንጥንያ ተልኮ መጣ፡፡ የመጣውም የግብጽ ክርስቲያኖች በሙሉ መንግሥት የሾመውን ፕሮቴሪ ዮስን እንዲቀበሉ ለማድረግ ነበር፡፡ ለእርሱም የማይታዘዙትን ከባድ ቅጣት እንዲቀጣቸው ሥልጣን ተሰጥቶት ነበር የመጣው፡፡ ይህ ባለሥልጣን በመጣ ጊዜ ፓትርያርክ ዳግማዊ ጢሞቴዎስ ከእስክንድርያ ወጥተው የተለያዩ ሀገረ ስብከቶችን በመጐብኘት ላይ ነበሩ፡፡ ፓትርያርኩ በተመለሱ ጊዜ መንበረ ሊቀ ጵጵስናቸው ውጭውም ውስጡም በመንግሥት ቊልፍ ተቈልፎ አገኙት፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑ በዚህ እጅግ ተናደው መንግሥት ወደሾመው ፓትርያርክ ወደ ፕሮቴሪዮስ ሄደው በንጉሡ የተሾመውን ፓትርያርክ ከተደበቀበት አውጥተው ገደሉት፡፡ ይህ ዓመፅ መንግሥትን ስላሳሰበ በሕዝብ ላይ አጸፋዊ እርምጃ ለመውሰድ አልተፈለገም፡፡ ሆኖም ንጉሥ መርቅያን ግብጻውያን የመረጡት ፓትርያርክ ጢሞቴዎስና ወንድሙ ተይዘው ዲዮስቆሮስ ታስሮበት በነበረበት በደሴተ ጋግራ እንዲጋዙ አደረገ፡፡ ይህንም ያደረገው የሕዝቡን መንፈስ ለመስበርና ተስፋ ለማስቈረጥ ነበር፡፡ የሕዝቡ መንፈስ ግን ፈጽሞ አልተለወጠም፡፡

የቊስጥንጥንያ መንግሥት ደጋግሞ ፓትርያርክ ቢልክም ግብጻውያን ግን መንግሥት የሚልካቸውን ፈጽሞ አይቀበሉም ነበር፡፡ እስከ ኬልቄዶን ጉባኤ ድረስ በግብጽ የነበሩ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ በቅዳሴና በሌሎች የጸሎት አገልግሎት ጊዜ በግሪክኛ ቋንቋ ነበር የሚጠቀሙት፡፡ ከዚህ በኋላ ግን በቅብጥ ቋንቋ መጠቀም ጀመሩ፡፡ ከ451 ዓ.ም. ጀምሮ ማለት ከኬልቄዶን ጉባዔ በኋላ አንዲት ቤተ ክርስቲያን ለሁለት ተከፈለች፡፡ በአንድ በኩል የሮም ንጉሠ ነገሥት መንግሥት ሙሉ ድጋፍ የነበራቸው እኛ መለካውያን ብለን የምንጠራቸው የምዕራቡ አብያተ ክርስቲያናት የሮም ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያንና የግሪክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ተከታዮች የሆኑ ሁሉ ሲሆኑ፣ በሌላ በኩል ደግሞ የምሥራቅ ወይም የኦርየንታል ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ማለት የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ የሶርያ፣ የአርመንና የሕንድ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ናቸው፡፡

የፖፕ ልዮን ቀዳማዊ የሃይማኖት መግለጫ ጦማር

የልዮን የሃይማኖት መግለጫ ጦማር (ደብዳቤ) (The Tome of Leo) የሚከተሉት ነጥቦች ነበሩት፡-

1ኛ/በክርስቶስ ውስጥ የመለኮት ባሕርይና የትስብእት ባሕርይ በአንድ አካል አንድ ሆኑ፤ ያለ መቀላቀል፣ ያለ መለያየትና ያለ መለወጥ፡፡

2ኛ/ እያንዳንዱ ባሕርይ የግብር ክልሉን ጠብቆ ይኖራል፡፡ ይህም ማለት መለኮት የመለኮትን ሥራ ይሠራል፤ ትስብእትም የትስብእትን ሥራ ይሠራል፡፡ 

3ኛ/ ‹‹ከመዋሐድ በፊት ሁለት ነበሩ፤ ከተዋሐዱ በኋላ ግን አንድ ባሕርይ ነው ማለት ሞኝነት ነው፤›› የሚል ኃይለ ቃል ይገኝበታል፡፡

ከልዮን ጦማር ውስጥ ከዚህ በላይ የገለጥናቸው አንድ አካል ከማለቱ በስተቀር የንስጥሮስን ትምህርት ነው የሚገልጡት፡፡ ሁለቱ ባሕርያት አንድ ሆኑ ሲሉ እንደ ኀዳሪና ማኅደር፣ ጽምረትን እንጂ ተዋሕዶን አይገልጡም፡፡ ተዋሕዶ ግን እንደ ነፍስና ሥጋ ነው፡፡ ‹‹እያንዳንዱ ባሕርይ የግብር ክልሉን ጠብቆ ይኖራል›› የሚለው በተዋሕዶ የቃል ገንዘብ ለሥጋ፣ የሥጋ ገንዘብ ለቃል መሆኑንና መገናዘቡን መወራረሱንም የሚጻረር ነው፤ ቅዱስ ቄርሎስ እንዲህ ይላል ‹‹እንቲአሁ ለቃል ኮነ ለሥጋ ወእንቲአሁ ለሥጋ ኮነ ለቃል፡፡›› ይህም ማለት ‹‹የቃል ገንዘብ ለሥጋ ሆነ፤ የሥጋም ገንዘብ ለቃል ሆነ፤›› ማለት ነው፡፡  ይህ ፍጹም ተዋሕዶን የሚያመለክት ነው፡፡  ስለዚህ ነው ሥግው ቃል በተዋሕዶ አንድ አካል አንድ ባሕርይ ነው የምንለው፡፡

የልዮንን ጦማርና የኬልቄዶንን ጉባኤ ውሳኔ በመከተል የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያንና የግሪክ ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት በሙሉ ‹‹ክርስቶስ ሁለት ባሕርያት አንድ አካል አለው›› ይላሉ፡፡ በአገላለጽም ሁለቱ ባሕርያት የተዋሐዱት ያለ መቀላቀል፣ ያለ መለያየትና ያለ መለወጥ ነው ይላሉ፡፡ አንድ ባሕርይ ለማለት የፈሩት ወደ አውጣኪ ትምህርት ይወስደናል ብለው በመፍራት ነው፡፡ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ሁለቱ ባሕርያት (የሥጋና የመለኮት) ተዋሐዱ ስንል ‹‹ወረሰዮ አሐደ ምስለ መለኮቱ ዘእንበለ ቱስሕት ወኢትድምርት፣ ዘእንበለ ፍልጠት ወኢውላጤ›› (ያለ መቀላቀልና ያለ መጨመር፣ ያለ መለየትና ያለ መለወጥ ከመለኮቱ ጋር አንድ አደረገው፤) እንላለን፡፡  አባቶቻችን ያስተማሯት ርትዕት ሃይማኖታችንም ይህች ናት፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ማስገንዘቢያ

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች፣ ይህ ጥናታዊ ጽሑፍ ለማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል መቅረቡንና በታኅሣሥ ወር ፳፻፱ ዓ.ም በታተመው ፳፬ኛ ዓመት ቍጥር ፰ ሐመር መጽሔት፣ ከገጽ ፰ – ፲፭ ለንባብ መብቃቱን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

አውጣኪ፣ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ እና የኬልቄዶን ጉባኤ – የመጀመሪያ ክፍል

በቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገ/አማኑኤል

ጥር ፳፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

መግቢያ

ከክርስቶስ ልደት በኋላ በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ በመካከለኛው ምሥራቅ በተለይ በአንጾኪያና በግብጽ የቤተ ክርስቲያንን አንድነት ያወከና ታላቅ ብጥብጥ የፈጠረ በምሥጢረ ሥላሴ እምነት ላይ የተነሣ የተሳሳተ ትምህርት ነበር፡፡ ይኸውም አርዮስ ከእስክንድርያዊው መምህሩ ከአርጌኒስ በቀሰመው ትምህርት በዘዴ ‹‹ክብር ምስጋና ይግባውና እግዚአብሔር ወልድን ፍጡር ነው፤ አምላክም አይደለም፤›› ለማለት ‹‹ሀሎ አመ ኢሃሎ ወልድ›› (ወልድ ያልነበረበት ጊዜ ነበር) በግሪክኛ፡- ‹‹ኢን ፖቴ ኦቴ ኡክ ኢን›› ብሎ የክሕደት ትምህርት በማስተማሩ መላው የክርስትናው ዓለም ታውኮ ነበር፡፡ ይህ በ325 ዓ.ም. በኒቂያ ጉባኤ አርዮስና ኑፋቄው በመወገዙ ችግሩ መፍትሔ አግኝቶ ነበር፡፡ ከ106 ዓመታት በኋላ ደግሞ ንስጥሮስ ከአንጾኪያ በአገኘው ትምህርት በቊስጥንጥንያ ቤተ ክርስቲያን በምሥጢረ ሥጋዌ እምነት ላይ ስለ ክርስቶስ የተሳሳተ ትምህርት ያስተምር ጀመር፡፡

ይኸውም ንስጥሮስ 1ኛ ክርስቶስ ሁለት አካል ሁለት ባሕርይ አለው፤ 2ኛ/ ክርስቶስ ፍጹም ሰው እንጂ ፍጹም አምላክ አይደለም፤ እንዲሁም  3ኛ/ እመቤታችን ሰውን እንጂ አምላክን አልወለደችም፤ ስለዚህ እመቤታችን ወላዲተ ሰብእ እንጂ ወላዲተ አምላክ ልትባል አይገባትም (ሕስወኬ ትሰመይ ወላዲተ አምላክ፣ በአማን ትሰመይ ወላዲተ ሰብእ) ብሎ በማስተማሩ ይህ ኑፋቄ በ431 ዓ.ም. ላይ በታላቁ መምህር በእስክንድርያው ፓትርያርክ በቅዱስ ቄርሎስ አማካኝነት በኤፌሶን ጉባኤ ተወግዞ ችግሩ ተወግዶ ነበር፡፡ ሆኖም የንስጥሮስ የክህደት እምነት ጨርሶ ሳይጠፋ በዚያው በመካከ ለኛው ምሥራቅ በተለይ በፋርስና በባቢሎን እንዲሁም በኤዴሳ  ሲስፋፋ ቆይቷል፡፡ እንዲሁም ንስጥሮሳውያን በኤፌሶንና በቊስጥንጥንያ በብዛት ይገኙ ነበር፡፡

አውጣኪና ትምህርቱ

የንስጥሮስን ትምህርት በጥብቅ ይቃወሙ የነበሩት የግብጽ መነኰሳትና ካህናት ነበሩ፡፡ በቊስጥንጥንያም ቢሆን አያሌ የንስጥሮስ ተቃዋሚዎች ነበሩ፡፡ የንስጥሮስን ትምህርት አጥብቆ ይቃወም የነበረና ለኦርቶዶክስ ሃይማኖት እጅግ ቀናኢ የነበረ አውጣኪ የተባለ በቊስጥንጥንያ የአንድ ትልቅ ገዳም አበምኔት (መምህር) ነበር፡፡ አውጣኪ ‹‹ክርስቶስ ሁለት አካል ሁለት ባሕርይ አለው›› የሚለውን የንስጥሮሳውያንን ትምህርት አጥብቆ በመቃወም እሱ ወደ ተቃራኒው የባሰ ክህደት ውስጥ ገባ፡፡ አውጣኪ በቊስጥንጥንያ ‹‹ክርስቶስ አንድ አካል አንድ ባሕርይ ብቻ አለው፤›› እያለ ያስተምር ጀመር፡፡ አባባሉ የቅዱስ ቄርሎስን ኦርቶዶክሳዊ ትምህርት ይመስላል፡፡ አውጣኪ ግን ‹‹አንድ ባሕርይ›› ሲል የክርስቶስን መለኮታዊ ባሕርይ ብቻ ማለቱ ነበር፡፡

በአውጣኪ አባባል ‹‹ሁለቱ ባሕርያት ማለት የሥጋና የመለኮት ባሕርያት በተዋሐዱ ጊዜ የመለኮት ባሕርይ የሥጋን ባሕርይ ውጦታል፤ አጥፍቶታል፡፡ ሥጋና መለኮት ከተዋሐዱ በኋላ በክርስቶስ ላይ የሚታየው የመለኮት ባሕርይ ብቻ ነው፡፡ በክርስቶስ የሥጋ ባሕርይ ተውጦ የመለኮት ባሕርይ ብቻ ነው የሚታየው፤›› ይል ነበር፡፡ ይህ አባባል በእኛም ቤተ ክርስቲያን ማለት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የተወገዘ ነው፡፡ አውጣኪ በተጨማሪ ከሥጋዌ በኋላ ክርስቶስ ፍጹም ሰው ነው ለማለት ‹‹ክርስቶስ ዘዕሩይ ምስሌነ በትስብእቱ›› ማለት ‹‹ክርስቶስ በትስብእቱ (በሥጋው) ከእኛ ጋር አንድ ነው›› የሚለውን ኦርቶዶክሳዊ አነጋገር አይቀበልም ነበር፡፡ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እምነት መሠረት ‹‹ክርስቶስ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው ነው፡፡›› ነገር ግን ፍጹም ሰው ካልሆነና እኛን ወክሎ በመስቀል ላይ በሥጋው መከራን ካልተቀበለ፣ የእኛ የሰዎች ድኅነት አስተማማኝ አይሆንም፡፡ በክርስቶስ የሥጋና የመለኮት ባሕርያት ተዋሕደው በመስቀል ላይ በአንድነት ባሕርዩ በተቀበለው መከራ ድኅነትን አግኝተናል፡፡

‹‹በክርስቶስ የሥጋ ባሕርይ ተውጦ ወይም ጠፍቶ የመለኮት ባሕርይ ብቻ ነው የሚታየው›› የሚለውን የአውጣኪን የኑፋቄ (የክህደት) ትምህርት የሰማው የቊስጥንጥንያ ፓትርያርክ ፍላብያኖስ ወዲያውኑ ደብዳቤ ጽፎ ስሕተቱን በማስረዳት አውጣኪ ከስሕተቱ እንዲታረምና ይህን ትምህርት እንዳያሰራጭ አስጠነ ቀቀው፡፡ አውጣኪ ግን የኑፋቄ ትምህርቱን አላቆመም፡፡ ከዚህ ላይ አንድ ነገር ማስታወስ አለብን፤ ይኸውም አውጣኪ ክሪሳፍዮስ ለተባለው ለንጉሠ ነገሥቱ ለዳግማዊ ቴዎዶስዮስ ኃይለኛ ጠቅላይ ሚኒስትር የንስሓ አባት ስለነበር የልብ-ልብ የተሰማው ይመስላል፡፡ ፓትርያርክ ፍላብያኖስም ይህንን ስለሚያውቅ ይመስላል አውጣኪን በጣም ሊጫነው አልፈለገም፡፡

ሆኖም ኃይለኛ የነበረ የዶሪሊያም ሊቀ ጳጳስ የነበረው አውሳብዮስ አውጣኪን አጥብቆ ስለ ተቃወመውና ስለ ከሰሰው፣ የቊስጥንጥንያው ፓትርያርክ ፍላብያኖስ እንደተለመደው የመላው አብያተ ክርስቲያናት ጳጳሳት ተጠርተው ጉባኤ በማድረግ ፈንታ፣ በእርሱ ስር የሚተዳደሩትን ሃያ ዘጠኝ ጳጳሳትንና ሠላሳ ሦስት የገዳማት አበምኔቶችን ብቻ ሰብስቦ በእርሱ ሰብሳቢነት በ448 ዓ.ም. በቊስጥንጥንያ አህጉራዊ ሲኖዶስ አድርጎ የአውጣኪን የክሕደት ትምህርት መመርመር ጀመረ፡፡ አውጣኪ በጉባኤው ላይ እንዲቀርብ ሁለት ጊዜ ተጠርቶ ለመቅረብ አልፈለገም፡፡ ለሦስተኛ ጊዜ ሲጠራ ብቻ ቀርቦ ስለ ኑፋቄ ትምህርቱ ሲጠየቅ ግልጽ ያልሆነ የሃይማኖት መግለጫ በጽሑፍ አቀረበ፡፡

መግለጫው ግን ስለተከሰሰበት የክህደት ትምህርት ምንም አይገልጥም፡፡ ሆኖም የዶሪሊያም ጳጳስ አውሳብዮስ ግልጥ አድርጎ ‹‹ክርስቶስ በትስብእቱ ከእኛ ጋር አንድ ነው?›› ብሎ በጠየቀው ጊዜ አውጣኪ አንድ አይደለም በማለት ካደ፡፡ ከክህደቱም እንዲመለስ ቢጠየቅ አሻፈረኝ አለ፡፡ ስለዚህ ጉባኤው አውጣኪን አወገዘው፡፡ ከአበምኔት ሹመቱና ከክህነት ሥልጣኑም ሽሮ ተራ ሰው አደረገው፡፡ የሮሙ ፖፕ ለቊስጥንጥንያው ፓትርያርክ ፍላብያኖስ ‹‹ክርስቶስ ሁለት ባሕርያት አንድ አካል አለው›› የሚል የሃይማኖት ፎርሙላ የያዘ ደብዳቤ ልኮለት ስለነበረ፤ አውጣኪ ይህንንም ነበር እንዲቀበል የተጠየቀው፡፡ ይህ ደግሞ ከንስጥሮስ ኑፋቄ ጋር የተዛመደ ስለነበረ (ይህ አባባል መንፈቀ ንስጥሮሳዊ ይባላል) አውጣኪ አልቀበልም አለ፡፡

ስለዚህ አውጣኪ ‹‹የቅዱስ ቄርሎስን ሃይማኖት ስለመሰ ከርኩ እንጂ አንዳች የሃይማኖት ስሕተት ሳይኖርብኝ ያለ አግባብ ተወገዝኩ፤›› ብሎ ለንጉሠ ነገሥቱ ለዳግማዊ ቴዎዶስዮስ አመለከተ፡፡ እንዲሁም ለሮም ፖፕ ለልዮን ቀዳማዊና ለእስክን ድርያው መንበረ ፓትርያርክ ለዲዮስቆሮስ ለሌሎችም ጳጳሳት ደብዳቤ ላከ፡፡ የቊስጥንጥንያው ፓትርያርክ ፍላብያኖስም በበኩሉ የአውጣኪን ኑፋቄና ጉባኤው ስለ እርሱ የወሰነውን ውሳኔ ለፖፕ ልዮን ላከለት፡፡ ፖፑም የጉባኤውን ውሳኔ በማጽደቅ ምሥጢረ ሥጋዌን የያዘ ደብዳቤ ለፍላብያኖስ በድጋሚ ላከለት፡፡ በደብዳቤውም ውስጥ ክርስቶስ ሁለት ባሕርያትና አንድ አካል እንዳለው በግልጽ አስፍሯል፡፡ ይህም አባባል ከላይ እንደተገለጸው መንፈቀ ንስጥሮሳዊ ነው፡፡

ሁለተኛው የኤፌሶን ሲኖዶስ (449)

አውጣኪ በቊስጥንጥንያ እጅግ የተከበረ ሰው ስለነበረና ብዙም ደጋፊዎች ስለነበሩት የእርሱ በ448 ዓ.ም. ጉባኤ መወገዝ ብዙዎችን አስቆጥቶ ነበር፡፡ እንደውም ያወገዘው ፓትርያርክ ፍላብያኖስ ንስጥሮሳዊ ነው እየተባለ ይወራና ይወቀስ ጀመር፡፡ ንጉሠ ነገሥቱም የነገሩን ክብደት ተመልክቶ ምናልባትም በአውጣኪ ንስሓ-ልጅ በጠቅላይ ምኒስትሩ ተጽእኖ ይሆናል ዓለም-አቀፍ የአብያተ ክርስቲያናት ጳጳሳት ሲኖዶስ በኤፌሶን እንዲደረግ ለጳጳሳቱ ሁሉ ጥሪ አስተላለፈ፡፡ ስብሰባውም በነሐሴ ወር 449 ዓ.ም. በኤፌሶን እንዲሆን ተወሰነ፡፡ ባለፉት ሲኖዶሶች እንደተደረገው ሁሉ የእስክንድርያው ፓትርያርክ ዲዮስቆሮስ ሰብሳቢ እንዲሆን ንጉሠ ነገሥቱ ወሰነ፡፡ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ሰብሳቢ በመሆኑ ሃያ ሦስት ከሚሆኑ ከግብጽ ጳጳሳት ጋር ቀደም ብሎ ኤፌሶን ደረሰ፡፡

ፖፕ ልዮን ግን ይህ ስብሰባ እንዲደረግ አልፈለገም ነበር፡፡ እንደውም ለንጉሠ ነገሥቱ ታላቅ እኅት ለብርክልያ ንጉሡ ጉባኤውን እንዳይጠራ እንድታግባባው ጠይቋት ነበር፡፡ ሆኖም ንጉሠ ነገሥቱ በሐሳቡ ጸንቶ ጉባኤውን ስለጠራ ፖፑም ሦስት መልእክተኞች ላከ፡፡ በጉባኤው ላይ አንድ መቶ ሠላሳ አምስት ጳጳሳት ተሰብስበው ነበር፡፡ ምንም እንኳ ጉባኤው ስብሰባውን የጀመረው አንድ ሳምንት ዘግይቶ ቢሆንም የሮሙ ፖፕ እንደራሴዎች በዚህ ጊዜ ሊገኙ አልቻሉም፡፡ የቊስጥንጥንያው ፓትርያርክ ፍላብያኖስም በጉባኤው ላይ እንዲገኝ ተጠርቶ አልመጣም፡፡ የቀረበትንም ምክንያት አልገለጠም፡፡ ምናልባትም በእሱ ሰብሳቢነት የተሰበሰበው አህጉራዊ ሲኖዶስ ያወገዘው የአውጣኪ ጉዳይ እንደገና እንዲታይ በመደረጉ ቅር ብሎት ሳይሆን አይቀርም፡፡ ይህ ደግሞ አዲስ ነገር አልነበረም፡፡ ከዚህ በፊትም ብዙ መናፍቃን አርዮስም ጭምር መጀመሪያ በአህጉራዊ ሲኖዶሶች ከተወገዙ በኋላ ነበር ጉዳያቸው እንደገና በዓለም-አቀፍ ሲኖዶሶች እንዲታዩ የተደረገው፡፡

ከላይ የተጠቀሱት ጳጳሳት ተጠብቀው ባይመጡም ፓትርያርክ ዲዮስቆሮስ የተገኙትን አንድ መቶ ሠላሳ አምስት ጳጳሳት ይዞ በነሐሴ ወር 449 ዓ.ም. ስብሰባውን ጀመረ፡፡ ጉባኤው የተደረገው እንደበፊቱ በኤፌሶን በቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ነበር፡፡ ጉባኤውም እንደተጀመረ አውጣኪ ተጠርቶ ስለተከሰሰበት ጉዳይ መልስ እንዲሰጥ ተጠየቀ፡፡ አውጣኪ በቊስጥንጥንያ ሕዝብ እጅግ የተወደደና የተደነቀ ከመሆኑም በላይ በቃላት የሚጫወት ቅንነት የጐደለው ሰው ነበር፡፡ አውጣኪ በጉባኤው ፊት ቀርቦ በራሱ እጅ የተጻፈና የፈረመበት የእምነት መግለጫ አቀረበ፡፡ መግለጫውም ከመነበቡ በፊት ራሱ እንዲህ ሲል ጮኾ ተናገረ፡- ‹‹ከልጅነቴ ጀምሮ በግልጥ በምነና (በብሕትውና) ለመኖር ነበር የምፈልገው፡፡ ዛሬ በሕዝብ መካከል በመገኘቴ ታላቅ ሐዘን ይሰማኛል፡፡ ሆኖም እምነቴን ለመመስከር ስለሆነ ደስታ ይሰማኛል፡፡ በኒቅያ ጉባኤ የተወሰነውንና አባታችን የእስክንድርያው ፓትርያርክ ቅዱስ ቄርሎስ ያስተማረውን እምነት በትክክል እቀበላለሁ፤›› አለ፡፡ ከዚህ በኋላ የጉባኤው ጸሓፊ የሚከተለውን የአውጣኪ የእምነት መግለጫ ማንበብ ጀመረ፤ መግለጫውም እንዲህ ይላል፡-

‹‹ሁሉን በያዘ፣ የሚታየውንና የማይታየውን በፈጠረ በአንድ አምላክ አምናለሁ፡፡ በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ በሚሆን በአንድ ልጁ በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ አምናለሁ፤ ለእኛ ለሰዎች ሲል ለድኅነታችን ከሰማይ ወረደ፡፡ ሥጋ ለበሰ፤ ሰውም ሆነ፡፡ ታመመ፤ ሞተ፤ በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡ ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ ዳግመኛም በሕያዋንና በሙታን ላይ ለመፍረድ ይመጣል፡፡ እርሱ ያልነበረበት ጊዜ ነበረ የሚሉ፣ ከመወለዱም በፊት አልነበረም፤ ካለምንም ተፈጠረ የሚሉት፣ ከአብ ጋር በባሕርዩ የተለየ ነው የሚሉት፣ የእርሱ ሁለቱ ባሕርያት ተቀላቅለዋል ወይም ተዋውጠዋል የሚሉት፣ እነዚህ ሁሉ በአንዲት ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን የተወገዙ ናቸው፡፡ እኔም የምከተለው እምነት ይህ ነው፡፡ በዚህ እምነት እስካሁን ኖሬአለሁ፤ ወደፊትም እስክሞት ድረስ በዚሁ እኖራለሁ፡፡›› የሚል ነበር፡፡

አውጣኪ ይህንን ለጉባኤው ሲያስረዳ ተከትለዉት የመጡትም መነኰሳት አውጣኪ ያቀረበውና የተናገረው ትክክል መሆኑን ከዚያው በጉባኤው ፊት አረጋገጡ፡፡ ስለዚህ ይህን የሃይማኖት መግለጫ ከአዩና ከሰሙ በኋላ አራት ሊቃነ ጳጳሳት ማለት የኢየሩሳሌሙ፣ የአንጾኪያው፣ የኤፌሶኑና የቂሣርው ዘቀጰዶቅያ አውጣኪ በእምነቱ ኦርቶዶክስ ነው በማለት ለጉባኤው አጽንተው ሲናገሩ ሁሉም አውጣኪ ከተከሰሰበት ኑፋቄ ንጹሕ መሆኑን በአንድ ድምፅ ወሰኑ፡፡ ከተላለፈበትም ውግዘት ፈቱት፡፡ ሥልጣነ ክህነቱንም መልሰውለት ወደ ቀድሞው የሓላፊነት ሥራው እንዲመለስ ውሳኔ አስተላለፉ፡፡ የሁለት ባሕርይን ሐሳብ ይቀበል የነበረው የዶሪሊያም ጳጳስ አውሳብዮስ አውጣኪን በመወንጀል መግለጫ ሲያቀርብ በዚያ የተሰበሰቡት መነኰሳትና ምእመናን በታላቅ ድምፅ ‹‹አውሳብዮስ ይቃጠል! አውሳብዮስ በሕይወቱ ይውደም! ክርስቶስን ለሁለት እንደ ከፈለ እሱም ለሁለት ይከፈል!›› እያሉ ይጮኹ ጀመር፡፡

የቊስጥንጥንያን ፓትርያርክ ፍላብያኖስንና አውጣኪን ያወገዙትን ጳጳሳት የሮሙን ፖፕ ልዮን 1ኛን ጭምር አውጣኪን ያለ አግባብ በማውገዛቸውና ሥልጣናቸውን ያለ አግባብ በመጠቀማቸው ጉባኤው ካወገዛቸው በኋላ፣ የሚከተለውን አጭር መግለጫ አወጣ፡- ‹‹ከኒቅያ እስከ ኤፌሶን አባቶቻችን በጉባኤ ተሰብስበው ከወሰኑት ሃይማኖት ሌላ የሚጨምር፣ የሚቀንስ ወይም የሚያሻሽል ቢኖር የተወገዘ ይሁን፡፡›› ዘግይተው የደረሱት የፖፑ መልእከተኞች ዩልዮስና ሬናቱስ የተባሉት ጳጳሳትና ዲያቆን ሂላሩስ ከፖፑ የተላከውን የሃይማኖት መግለጫ ደብዳቤ እንዲነበብ ጠይቀው ነበር፡፡ ነገር ግን ደብዳቤው ‹‹ክርስቶስ ሁለት ባሕርያት አንድ አካል አለው›› ስለሚልና ይህም ከንስጥሮስ ኑፋቄ ጋር ስለሚመሳሰል ጉባኤው እንዲነበብ አልፈቀደም፡፡ በዚህም ምክንያት የፖፑ መልእከተኞች ተቀይመው ወዲያውኑ በድብቅ ከጉባኤው ወጥተው ወደመጡበት ተመለሱ፡፡ የጉባኤውም ውሳኔ በንጉሠ ነገሥቱ በዳግማዊ ቴዎዶስዮስ ጸደቀ፡፡ የቊስጥንጥንያ ፓትርያርክ ፍላብያኖስ በኤፌሶን 2ኛ ጉባኤ እንደተወገዘ ወዲያውኑ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል፡፡

የዚህን ጉባኤ ውሳኔ ሲሰማ የሮሙ ፖፕ ልዮን ቀዳማዊ እጅግ ተናዶ ጉባኤውን ‹‹ጉባኤ ፈያት (የወንበዴዎች ጉባኤ)›› ብሎ ጠራው፡፡ የጉባኤውንም ሊቀ መንበር ቅዱስ ዲዮስቆሮስን አወገዘው፡፡  ከእስክንድርያ ጋር የነበረውንም ግንኙነት ጨርሶ አቋረጠ፡፡ ፖፑ ይህን ሁሉ ያደረገው እሱ የላከው የሃይማኖት ነክ ደብዳቤ በጉባኤው ላይ ስላልተነበበና የእርሱም መልእክተኞች በጉባኤው ላይ በሙሉ ባለመካፈላቸው ነበር፡፡ በተጨማሪም ፖፑ ለንጉሠ ነገሥቱ ለዳግማዊ ቴዎዶስዮስ የኤፌሶኑን ጉባኤ የዲዮስቆሮስ ጉባኤ ብሎ በመጥራት በጉባኤው ላይ ያለውን ቅሬታ ከገለጸ በኋላ፣ ሌላ ዓለም አቀፍ ሲኖዶስ (ጉባኤ) እንዲጠራ ጥብቅ ሐሳብ አቀረበ፡፡ እንዲረዳውም የምዕራቡን ክፍል ገዥ (ንጉሥ) የነበረውን ሣልሳዊ ዋሌንቲኒያኖስን (Valentinianus III) እና ሚስቱን ንግሥት አውዶቅሲያን አጥብቆ ለምኖ ነበር፡፡

እነዚህም ባለሥልጣኖች እያንዳንዳቸው ሐሳቡን በመደገፍ ለንጉሠ ነገሥቱ ለዳግማዊ ቴዎዶስዮስ ደብዳቤ ጽፈው ነበር፡፡ ዳግማዊ ቴዎዶስዮስ ግን ሁለተኛው የኤፌሶን ጉባኤ ፈሪሃ እግዚአብሔር ያላቸው የቅዱሳን አባቶች ጉባኤ መሆኑን ገልጦ በመጻፍ ስለ ኦርቶዶክስ ሃይማኖት ምንም የሚያሳስብ ነገር አለመኖሩን ገልጦ አሳስቧቸዋል፡፡ በተጨማሪም የምዕራቡን ንጉሥና ንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ እንዳይገቡ መክሯቸው ነበር፡፡ ፖፕ ልዮን ግን ሌላ ዓለም-አቀፍ ሲኖዶስ እንዲደረግ ዳግማዊ ቴዎዶስዮስን አጥብቆ መጠየቁን ቀጠለ፡፡ ሆኖም የፖፑ ጥረት ሁሉ ውጤት አላስገኘም፡፡ ምክንያቱም ዳግማዊ ቴዎዶስዮስ ለ2ኛው የኤፌሶን ጉባኤ ታላቅ አክብሮት ስለነበረውና ውሳኔውንም በሚገባ ስላጸደቀው ነበር፡፡

የኬልቄዶን ጉባኤ

ሁለተኛው የኤፌሶን ጉባኤ ከአለፈ ከአንድ ዓመት በኋላ በሐምሌ ወር 450 ዓ.ም. ዳግማዊ ቴዎዶስዮስ በድንገት ከፈረስ ላይ ወድቆ ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ፡፡ ቴዎዶስዮስ ወራሽ ስላልነበረው ለአልጋው ቅርብ የነበረች ታላቅ እኅቱ ብርክልያ (Pulcheria) ነበረች፡፡ ብርክልያ ግን በድንግልና መንኵሳ ነበር የምትኖረው፡፡ ሆኖም ብርክልያ ለሥልጣን ስለጓጓች ምንኵስናዋን አፍርሳ የሮም መንግሥት የጦር አዛዥ ጄኔራል የነበረውን መርቅያን (Marcianus) አግብታ በነሐሴ ወር 450 ዓ.ም. እሱ ንጉሠ ነገሥት እሷ ንግሥት ሆነው የሮምን ንጉሠ ነገሥት መንግሥት ማስተዳደር ጀመሩ፡፡ ይህ የብርክልያ ምንኵስናን ማፍረስ በኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ በተለይም በግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ዘንድ ተቀባይነትን አላገኘም ነበር፡፡ የሮሙ ፖፕ ግን ከአዲሶቹ የሮም መንግሥት ንግሥትና ንጉሠ ነገሥት ዘንድ ተወዳጅነትን ለማግኘት ሲል ጋብቻቸውን በማወደስ አጸደቀላቸው፤ ቡራኬውንም ላከላቸው፡፡ በዚህም ምክንያት ፖፕ ልዮን ከቊስጥንጥንያ ንጉሣዊ ቤተሰብ ጋር ወዳጅነትን መሠረተ፡፡ እንኳን ደስ አላችሁ ብሎም በጻፈው ደብዳቤ መጨረሻ ላይ እሱ የፈለገው ዓለም አቀፍ ሲኖዶስ እንዲሰበሰብ አሳሰበ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በንጉሠ ነገሥቱ በመርቅያንና በፖፕ ልዮን መካከል ብዙ የወዳጅነት ደብዳቤዎች ተጻጽፈዋል፡፡

ንጉሠ ነገሥቱ መርቅያን በሥልጣኑ በ2ኛው በኤፌሶን ጉባኤ የተወገዘው የፍላብያኖስ አስከሬን ፈልሶ በቊስጥንጥንያ በሐዋርያት ቤተ ክርስቲያን በታላቅ ክብር እንዲቀበር አደረገ፡፡ የተጋዙት ጳጳሳትም ከግዞት ወጥተው ወደየሥራቸው እንዲመለሱ አደረገ፡፡ በመሠረቱ በሲኖዶስ የተወገዙት ወደ ቀድሞ ሥራቸው መመለስ የሚችሉት በንጉሥ ትእዛዝ ሳይሆን በጳጳሳት ሲኖዶስ መሆን ስለነበረበት ንጉሡ ያደረገው ሕገ-ወጥ ሥራ ነበር:: ፖፑም የሱ ፍላጎት ስለነበረ ይህንን አልተቃወመም፡፡ በተቃራኒው ንጉሡ የተወገዙት ጳጳሳት ወደየሀገረ ስብከታቸው እንዲመለሱ የፍላብያኖስም አስከሬን ወደ ቊስጥንጥንያ ፈልሶ በክብር እንዲቀበር በማድረጉ ፖፕ ልዮን ለንጉሠ ነገሥቱ ልባዊ ምስጋና አቅርቧል፡፡ ንጉሠ ነገሥቱ መርቅ ያንና ንግሥቲቱ ብርክልያ 2ኛው የኤፌሶን ሲኖዶስ ባቀረበው የሃይማኖት መግለጫ መሠረት ነፃ ያደረገውን አውጣኪንም ያለ ሲኖዶስ ውሳኔ ወደ ሰሜን ሶርያ እንዲጋዝ አደረጉ፡፡

ፖፕ ልዮን በአሳሰበው መሠረት ንጉሥ መርቅያን ጥቅምት 8 ቀን 451 ዓ.ም. ዓለም-አቀፍ ሲኖዶስ እንዲደረግ ለጳጳሳት ሁሉ ጥሪ አስተላለፈ፡፡ ጉባኤውም እንዲደረግ የታሰበው ከቊስጥንጥንያ 96 ኪሎ ሜትር ያህል ርቃ በምትገኝ በኒቅያ ነበር፡፡ ነገር ግን በጸጥታ ምክንያት ከቊስጥንጥንያ 3 ኪሎ ሜትር ብቻ ርቃ በምትገኘው በኬልቄዶን እንዲሆን ንጉሡ ስለ ወሰነ ጉባኤው በኬልቄዶን ሆነ፡፡ ንጉሥ መርቅያንና ንግሥት ብርክልያ በጉባኤው መክፈቻ ላይ ተገኝተዋል፡፡ ጉባኤው በሥነ ሥርዓት መካሄዱን የሚቆጣጠሩ 18 ዳኞች በንጉሡ ተሠይመው ነበር፡፡ እነዚህ ሁሉ ዳኞች መሠየማቸው መንግሥት ሲኖዶሱን ምን ያህል እንደተቈጣጠረው ያመለክታል፡፡ የጉባኤው አባላት አቀማመጥ እንደሚከተለው ነበር፤

ዳኞቹ በመኻል ከዳኞቹ በስተግራ የፖፑ መልእክተኞች፣ ቀጥሎ የቊስጥንጥንያው አናቶልያስ፣ የአንጾኪያው ማክሲሙስ፣ የቂሣርያውና የኤፌሶኑ ጳጳሳትና ሌሎች የምሥራቅና የመካከለኛው ምሥራቅ አህጉር ጳጳሳት ሲሆኑ፣ በቀኝ በኩል ቅዱስ ዲዮስቆሮስ፣ የኢየሩሳሌም፣ የተሰሎንቄ፣ የቆሮንቶስ፣ የግብጽ፣ የኢሊሪኩም፣ የፍልስጥኤም ጳጳሳትና ሌሎች ጳጳሳት ተቀምጠዋል፡፡ በኤፌሶን ጉባኤ የተወገ ዙትን ንስጥሮሳውያን መናፍቃንን የቂሮስ ኤጲስቆጶስ ቴዎዶሪጦስንና የኤዴሳን ኤጲስቆጶስ ኢባንን የዚህ ጉባኤ አባላት አድርገው ተቀበሏቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ብዙ ብጥብጥ ተነሣ፤ የግብጽ ጳጳሳት በኤፌሶን ጉባኤ የተወገዙትን ንስጥሮሳውያን ቴዎዶሪጦስንና ኢባንን ጉባኤው በአባልነት በመቀበሉ ‹‹አይሁዶችን፣ የክርስቶስን ጠላቶች ከዚህ አስወጡ!›› እያሉ በመጮኽ ተቃውሟቸውን አሰሙ፡፡ ጉባኤው ግን የእነሱን ጩኸት ከቁም ነገር አልቈጠረውም፡፡

ጉባኤውን በሊቀ መንበርነት በተራ የመሩት ከመንግሥት የተሠየሙት ዳኞችና የሮሙ ፖፕ መልእከተኞች ነበሩ፡፡ የሮሙ ተወካዮች ጉባኤውን ሲመሩ ይህ የመጀመሪያ ጊዜ ነበር፡፡ ከአሁኑ በስተቀር ባለፉት ዓለም-አቀፍ ሲኖዶሶች ሁሉ የእስክንድርያው ፓትርያርክ ከሊቃነ መናብርቱ ዋናው ነበር፡፡ አሁን ግን የእስክን ድርያውን ፓትርያርክ ዲዮስቆሮስን ለመኰነን የተሰበሰበ ሲኖዶስ ስለሆነ ዲዮስቆሮስ ከሊቃነ መናብርቱ አንዱ አልሆነም፡፡ የጉባኤው አባላት ቦታቸውን ይዘው እንደተቀመጡ የሮሙ ፖፕ ተወካይ ፓስካሲኑስ (Paschasinus) ተነሥቶ ለዳኞቹ ፓትርያርክ ዲዮስቆሮስ ከተቀመጠበት ቦታ ማለት ከጉባኤው እንዲነሣና ሌላ ቦታ እንዲቀመጥ አመለከተ፡፡ የመንግሥቱ ዳኞች ለምን ይነሣል ብለው በጠየቁ ጊዜ፣ ሌላው የፖፑ መልእክተኛ ሊሴንቲያስ (Licentius) የተባለው ዲዮስቆሮስ ከዚህ በፊት የሮሙ ፖፕ ሳይፈቅድ በሥልጣኑ ሲኖዶስ (የ449 ሲኖዶስን ማለቱ ነው) እንዲካሄድ አድርጓል በማለት ክስ አቀረበ፡፡

ይህ ግን መሠረት የሌለው ክስ ነበር፡፡ ምክንያቱም ከዚህ በፊት የተደረጉት ሲኖዶሶች ሁሉ የተጠሩትና የተካሄዱት በሮም ንጉሠ ነገሥት ፈቃድና ትእዛዝ እንጂ በሮሙ ፖፕ ፈቃድ አልነበረም፡፡ ያለፈውም የሁለተኛው የኤፌሶን ሲኖዶስ የተጠራው በዳግማዊ ቴዎዶስዮስ ትእዛዝ እንጂ በፓትርያርክ ዲዮስቆሮስ ሥልጣን አልነበረም፡፡ ስለዚህ የቀረበው ክስ ዳኞቹን አላረካ ቸውም፡፡ በዚህ ጉዳይ ብዙ ጭቅጭቅ ስለተፈጠረ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ በፈቃዱ ቦታውን ለቆ ተከሳሾች በሚቀመጡበት ቦታ ሄዶ ተቀመጠ፡፡ የሮሙ ፖፕ ተወካዮች በሁለተኛው የኤፌሶን ጉባኤ ፓትር ያርክ ዲዮስቆሮስ የቤተ ክርስቲያንን ቀኖና አፍርሷል ሲሉ ከሰሱ፡፡ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ሲመልስ እሱ በንጉሠ ነገሥቱ በቴዎ ዶስዮስ ትእዛዝና ጥያቄ መሠረት ነው ጉባኤውን የመራው፡፡ እሱ ቀኖናን አፈረሰ? ወይስ በኤፌሶን ጉባኤ የተወገዙትን ንስጥሮሳውያን መናፍቃንን የቂሮስ ኤጲስ ቆጶስ ቴዎዶሪጦስንና የኤዴሳን ኤጲስቆጶስ ኢባንን የዚህ ጉባኤ አባላት አድርገው የተቀበሉት እነሱ ናቸው ቀኖና አፍራሾች? ብሎ ጥያቄ አቀረበ፡፡ ሆኖም ይህ የፓትርያርክ ዲዮስቆሮስ ጥያቄ ምንም መልስ ሳይሰጠው በዝምታ ታለፈ፡፡

ይቆየን

አርዮስ እና መንፈቀ አርዮሳውያን በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሱት ችግር – የመጨረሻ ክፍል

በቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል

ኅዳር ፲፪ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

፫. ከኒቅያ ጉባኤ በኋላ አርዮሳውያን እና መንፈቀ አርዮሳውያን

የኒቅያ ጉባኤ ከተፈጸመ ከሦስት ዓመት በኋላ ማለት በ፫፻፳፰ ዓ.ም የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ እለእስክንድሮስ ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፡፡ ሊቀ ጳጳስ እለእስክንድሮስ ከመሞታቸው አስቀድሞ በተናዘዙት ቃል መሠረት፣ በኒቅያው ጉባኤ የተዋሕዶ ጠበቃ የነበሩትና በኒቅያው ጉባኤ ትምህርተ ሃይማኖትን (ጸሎተ ሃይማኖትን) ያረቀቁት ታላቁ አትናቴዎስ በምትካቸው በጳጳሳት፣ በካህናትና በሕዝብ ሙሉ ድምፅ ተመርጠው የእስክንድርያ ፓትርያርክ ሆነው ተሾሙ፡፡ ፓትርያርክ አትናቴዎስ በኒቅያ ጉባኤ ጊዜ የአርዮስና የተከታዮቹን የክሕደት ትምህርት በመቃወም ባቀረቡት ክርክርና ለኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት መጠበቅ ባበረከቱት ተጋድሎ በምዕራብም ሆነ በምሥራቅ ባሉ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ ‹‹ታላቁ አትናቴዎስ›› እየተባሉ ይጠራሉ፡፡ አርዮሳውያን እና መንፈቀ አርዮሳውያን በኒቅያ ጉባኤ ከተወገዙ በኋላም በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ ዘመቻቸውን ከበፊቱ አብልጠው ስለ ቀጠሉ፣ ታላቁ አትናቴዎስ በጽሑፍና በቃል ትምህርት ለእነዚህ መናፍቃን ምላሽ መስጠታቸውን እስከ ዕለተ ሞታቸው ድረስ አላቋረጡም ነበር፡፡

የኒቅያ ጉባኤ እንደ ተፈጸመ አርዮስ እና የአርዮስ ተከታዮች ሁሉ በንጉሡ በቈስጠንጢኖስ ትእዛዝ ወደ ግዞት ተልከው ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ አርዮሳውያን የንጉሡንና የፖለቲካ ባለ ሥልጣኖችን ለመወዳጀትና የእነርሱን ድጋፍ ለማግኘት ይሯሯጡ ጀመር፡፡ ስለዚህም ከሁለት ዓመት በኋላ ቆስጣንዲያ በተባለችው በንጉሡ እኅት እና የንጉሡ ወዳጅ በነበረው በኒቆምዲያው ኤጲስ ቆጶስ አውሳብዮስ አማካይነት ብዙዎቹ አርዮሳውያን ከግዞት እንዲመለሱ ታላቅ ሙከራ ተደረገ፡፡ በዚህም ምክንያት አርዮስና አያሌ አርዮሳውያን ከግዞት ተመለሱ፡፡ ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ቤተ ክርስቲያንን ያወካት የነገሥታቱ በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባት ነበር፡፡ በጉባኤ ሲኖዶስ የተወገዘው አርዮስ ከውግዘት እንዲፈታና ወደ እስክንድርያ ተመልሶ በቤተ ክርስቲያን በየነበረው ሥልጣን አገልግሎቱን እንዲቀጥል ንጉሡ ለሊቀ ጳጳሱ ለአትናቴዎስ ትእዛዝ አስተላለፈላቸው፡፡ ንጉሡ ይህን ትእዛዝ ያስተላለፈው ‹‹አርዮስ ከክሕደቱ ተመልሷል›› ብለው ወዳጆቹ ያስወሩትን ወሬ በመስማትና ‹‹የአርዮስ የእምነት መግለጫ ነው›› ተብሎ የቀረበለትን ግልጽ ያልሆነ መረጃ በመመልከት ነበር፡፡ ነገር ግን ይህን መግለጫ አርዮስን ያወገዘው ሲኖዶስ መርምሮ ሲያጸድቀው ነበር – ከክሕደቱ መመለሱ የሚታወቀው፡፡

በ፫፻፳፱ ዓ.ም የአርዮስ ደጋፊ በነበረው በኒቆምዲያው ኤጲስቆጶስ አውሳብዮስ የተመራውና አርዮሳውያን በብዛት የነበሩበት ጉባኤ ተሰብስቦ ‹‹አርዮስ ከውግዘቱ ተፈቷል›› በማለት ወሰኑ፡፡ የውሳኔአቸውን ግልባጭ በማያያዝም አትናቴዎስ አርዮስን እንዲቀበለው ንጉሠ ነገሥቱ መልእክት አስተላለፈ፡፡ አትናቴዎስ ግን የንጉሡን ትእዛዝና የአርዮሳውያንን ጉባኤ ውሳኔ አልቀበልም አሉ፡፡ ያልተቀበሉበትንም ምክንያት በዝርዝር ለንጉሡ ጻፉ፡፡ አርዮሳውያንና መንፈቀ አርዮሳውያንም የአትናቴዎስን እምቢታ (የንጉሡን ትእዛዝ አለመቀበል) መነሻ በማድረግ አትናቴዎስን እና ሌሎች ኦርቶዶክሳውያን መሪዎችን ከንጉሠ ነገሥቱ ጋር ለማጣላት የተቻላቸውን ሁሉ ጥረት አደረጉ፡፡ አርዮስ ወደ እስክንድርያ ተመልሶ ወደ ቀድሞው የክህነት ሥልጣኑ እንዲመለስ ንጉሠ ነገሥቱ ቈስጠንጢኖስ ያዘዘውን ትእዛዝ አትናቴዎስ ባለመቀበላቸውና መንግሥት በአርዮስ ጉዳይ ጣልቃ መግባቱን በመቃወማቸው የተነሣም ንጉሠ ነገሥቱ እጅግ ተቈጥቶ ነበር፡፡

ፓትርያርክ አትናቴዎስ የአርዮስ መወገዝም ሆነ መፈታት የሚመለከተው ቤተ ክርስቲያንን እንጂ ቤተ መንግሥትን አለመሆኑን ገልጠው ከመጻፋቸውም በላይ፣ ‹‹በሲኖዶስ የተወገዘ በመንግሥት ሳይሆን በሲኖዶስ ነው መፈታት ያለበት›› እያሉ ይናገሩ ስለ ነበር ንጉሡ በዚህ እጅግ አልተደሰተም ነበር፡፡ ንጉሡ በአትናቴዎስ ላይ መቆጣቱን የሚያውቁ አርዮሳውያንም አትናቴዎስን በልዩ ልዩ የሐሰት ክሶች ይከሷቸው ጀመር፡፡ ከሐሰት ክሶቹም አንዱ ‹‹ከግብጽ ወደ ቊስጥንጥንያ ስንዴ እንዳይላክ አትናቴዎስ ከልክለዋል›› የሚል ሲሆን፣ ሌላው ደግሞ ‹‹በንጉሡ ላይ ለሸፈቱ ሽፍቶች አትናቴዎስ ስንቅና መሣሪያ ያቀብሉ ነበር›› የሚል ነበር፡፡ ሌሎችም ሞራልንና ወንጀልን የሚመለከቱ የሐሰት ክሶችም ቀርበውባቸዋል፡፡

ሆኖም ግን ንጉሠ ነገሥቱ ቈስጠንጢኖስ አትናቴዎስን ለመበቀል ጥሩ አጋጣሚ ስላገኘ በአትናቴዎስ ላይ የቀረቡት ክሶች በጉባኤ እንዲታዩ ትእዛዝ አስተላለፈ፡፡ ጉባኤውም በ፫፻፴፭ ዓ.ም በጢሮስ ከተማ ተካሔደ፡፡ አትናቴዎስም ማንንም ሳይፈሩ ወደ ጉባኤው ሔዱ፡፡ ጉባኤው እንደ ተጀመረም በአትናቴዎስ ላይ የቀረቡትን ክሶች መስማት ጀመረ፡፡ በዚህ ጉባኤ አብዛኞቹ አርዮሳውያን ስለነበሩ፣ አትናቴዎስ በተከሰሱባቸው ክሶች ሁሉ ነጻ ቢሆኑም በግፍ ወደ ግዞት ቦታ እንዲሔዱ ተፈርዶባቸው ትሬቭ (ፈረንሳይ ውስጥ የምትገኝ) ወደምትባል ቦታ ተጋዙ፡፡

፬. የአርዮስ ድንገተኛ ሞት

ፓትርያርክ አትናቴዎስን በግፍ ወደ ግዞት ቦታ እንዲሔዱ የፈረደባቸው የቂሣርያው ጉባኤ፣ ‹‹አርዮስ ተጸጽቶ ከክሕደቱ መመለሱን የሚያመለክት መጣጥፍ አቅርቧል›› በሚል ሰበብ አርዮስን ከግዝቱ ፈቶ ነጻ አወጣው፡፡ አትናቴዎስ ወደ ግዞት በመላካቸው አርዮሳውያን እና መንፈቀ አርዮሳውያን ምቹ ጊዜ አግኝተው ስለ ነበር አርዮስን ወደ ሀገሩ ወደ እስክንድርያ ለመመለስ ይሯሯጡ ጀመር፡፡ የአርዮስ ነጻ መውጣትም ንጉሡ በሚኖርበት በቊስጥንጥንያ በይፋ እንዲከበር በማሰብ አርዮስ በወዳጆቹና በደጋፊዎቹ ታጅቦ ወደ ቊስጥንጥንያ እንዲሔድ አደረጉ፡፡ በዚያም በሐዋርያት ቤተ ክርስቲያን ከቊስጥንጥንያው ሊቀ ጳጳስ ጋር እንዲቀድስና ወደ ክርስቲያን አንድነት መግባቱ በይፋ እንዲታወጅ ዝግጅት ተደርጎ ሳለ ሆዱን ሕመም ተሰምቶት ወደ መጸዳጃ ቤት ሔዶ በዚያው ቀረ፡፡ አርዮስ ስለ ዘገየባቸው ደጋፊዎቹ ሔደው ቢያዩት ሆድ ዕቃው ተዘርግፎ ሞቶ አገኙት፡፡ በዚህም ‹‹የእግዚአብሔር ቊጣና መቅሠፍት በአርዮስ ላይ ተገለጠ›› ተብሎ በብዙ ሰዎች ዘንድ ታመነ፡፡ ሆኖም በአርዮስ ሞት የተበሳጩ አንዳንድ የአርዮስ ደጋፊዎች የእግዚአብሔርን ፍርድ አይተው ከክሕደታቸው በመመለስ ፈንታ ‹‹አርዮስ የሞተው በመድኃኒት ተመርዞ ነው›› ብለው ማውራትና ማስወራት ጀመሩ፡፡

፭. አርዮሳውያን እና መንፈቀ አርዮሳውያን የኒቅያን ውሳኔ ለመቀልበስ ያደረጉት ዘመቻ

የእስክንድርያው ፓትርያርክ ታላቁ አትናቴዎስ የክርስቶስን አምላክነት የካደውን የአርዮስን ሞት የሰሙት ያለ ፍትሕ በግፍ በተጋዙበት ሀገር ሳሉ ነው፡፡ ታላቁ ቈስጠንጢኖስም ብዙ ጊዜ በሕይወት አልቆየም፡፡ ንጉሡ ታሞ ግንቦት ፳፩ ቀን ፫፻፴፯ ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ፡፡ ሦስቱ ልጆቹ ማለት ዳግማዊ ቈስጠንጢኖስ፣ ቆንስጣንዲያስ እና ቁንስጣ መንግሥቱን ለሦስት ተከፋፈሉት፡፡ ከሦስቱ ልጆቹ መካከል የምዕራቡን ክፍል ይገዙ የነበሩት ሁለቱ ማለት ኦርቶዶክሳውያኑ ዳግማዊ ቈስጠንጢኖስ እና ቁንስጣ ሲሆኑ፣ መናገሻ ከተማውን ቊስጥንጥንያ ላይ አድርጎ የምሥራቁን ክፍል ይገዛ የነበረው ደግሞ አርዮሳዊው ቆንስጣንዲያስ ነበር፡፡ ትልቁ ቈስጠንጢኖስ ከሞተ ከአንድ ዓመት በኋላ ኅዳር ፳፫ ቀን ፫፻፴፰ ዓ.ም አትናቴዎስ ተግዘውበት የነበረበትን ሀገር ይገዛ የነበረው ዳግማዊ ቈስጠንጢኖስ አትናቴዎስን ከተጋዙበት እንዲመለሱ አደረገ፡፡ አትናቴዎስ ከግዞት ወደ እስክንድርያ ሲመለሱም ሕዝቡ እጅግ ተደስቶ በዕልልታና በሆታ ተቀበላቸው፡፡ አቀባበሉም ለአንድ ተወዳጅ ንጉሠ ነገሥት የሚደረግ አቀባበል ዓይነት ነበር፡፡

ፓትርያርክ አቡነ አትናቴዎስ በአርዮሳውያንና በመንፈቀ አርዮሳውያን ነገሥታት ያለ ፍትሕ በግፍ ለአምስት ጊዜያት ያህል ሕይወታቸውን በግዞት ነው ያሳለፉት፡፡ በእስክንድርያ መንበረ ጵጵስና በፓትርያርክነት የቆዩት ለ፵፮ ዓመታት ቢሆንም፣ ፲፭ቱን ዓመታት ያሳለፉት በግዞትና በስደት ነበር፡፡ ፓትርያርክ አትናቴዎስ ከዕድሜያቸው አብዛኛውን ዘመን ያሳለፉት ከአርዮሳውያን ጋር በመታገልና በመዋጋት ነበር፡፡ አንድ ታሪክ ጸሓፊም ‹‹ሙሴ ለእስራኤል ሕዝብ ምድረ ርስትን ለማውረስ የጀመረውን ተግባር ከግቡ ሳያደርስ እንደ ተጠራ፣ አትናቴዎስም ከአርዮሳውያን ጋር ያደርጉ የነበረውን ትግል ሳይጨርሱ ነው ለሞት የተጠሩት፤›› በማለት የፓትርያርክ አትናቴዎስን ተጋድሎና የአገልግሎት ፍጻሜ ያስረዳሉ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ማስገንዘቢያ

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች! ‹‹አርዮስ እና መንፈቀ አርዮሳውያን በጥንት ቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሱት ችግር›› በሚል ርእስ በቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል የተዘጋጀው ይህ ጥናታዊ ጽሑፍ፣ በግንቦት ወር ፳፻፰ ዓ.ም ለማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል መቅረቡን፤ እንደዚሁም በኅዳር ወር ፳፻፱ ዓ.ም በታተመው ፳፬ኛ ዓመት ቍጥር ፯ ሐመር መጽሔት፣ ከገጽ ፰ – ፲፬ ለንባብ መብቃቱን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

አርዮስ እና መንፈቀ አርዮሳውያን በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሱት ችግር – ክፍል ሦስት

በቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል

ኅዳር ፲፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በስብሰባው ላይ አርዮሳውያን በኒቆምዲያው ኤጲስቆጶስ አውሳብዮስ አማካይነት የሃይማኖት መግለጫ (confession of faith) አቀረቡ፡፡ የተሰበሰቡት አባቶች አብዛኛዎቹ በጩኸትና በቁጣ ድምፅ የእምነት መግለጫውን ተቃወሙት፡፡ ጽሑፉንም በእሳት አቃጠሉት፡፡ ከዚህ በኋላ የቂሣርያው አውሳብዮስ በሀገረ ስብከቱ በጥምቀት ጊዜ የሚጠመቁ ሁሉ የሚያነቡት የሃይማኖት ጸሎት (መግለጫ) አቀረበ፡፡ ይህ መግለጫ ከኒቅያው የሃይማኖት ጸሎት ጋር ተመሳሳይነት ስለነበረው ለጊዜው ተቀባይነትን አግኝቶ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን ‹‹ዋሕደ ባሕርይ ምስለ አብ›› ወይም ‹‹ዘዋሕድ ምስለ አብ በመለኮቱ›› (omoousios) የሚለውን አገላለጽ ባለማካተቱ ጠንከር ባሉ ኦርቶዶክሳውያን ዘንድ ተቀባይነት አላገኘም፡፡ በስብሰባው ወቅት አርዮስ ትክክለኛ የእምነት አቋሙን እንዲገልጽ ተጠይቆ ‹‹ሀሎ አመ ኢሀሎ ወልድወልድ ያልነበረበት ጊዜ ነበረ፡፡ አብ ወልድን ከምንም (እምኀበ አልቦ) ፈጠረውና የእግዚአብሔር ልጅ አደረገው፡፡ አብም ወልድን ከፈጠረው በኋላ ሥልጣንን ሰጥቶት ዓለሙን ሁሉ እንዲፈጥር አደረገው፤›› ብሎ ሲናገር አብዛኞቹ የጉባኤው አባላት በጌታችን ላይ የተናገረውን የጽርፈት (የስድብ) ቃል ላለመስማት ጆሯቸውን ሸፈኑ ይባላል፡፡

በክርክሩ ጊዜ ‹‹ወልደ አብ ኢየሱስ ክርስቶስ መድኃኒት ነው፤ አዳኛችን ነው፡፡ አዳኝ መሆኑን ካመንን የባሕርይ አምላክነቱን ማመን አለብን፡፡ የሚያድን እግዚአብሔር ብቻ መሆኑን ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክራሉ፡፡ በቅዱሳት መጻሕፍት ምስክርነት የወልድ አምላክነት ከሰው ልጆች የመዳን ምሥጢር ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ወልድ የባሕርይ አምላክ ካልሆነ ግን እኛም አልዳንም ማለት ነው፡፡ በእርሱ መዳናችንን ካመንን ግን ያዳነን እሱ አምላክ መሆኑን ማወቅና ማመን አለብን፡፡ ፍጡር ፍጡራንን ማዳን አይችልምና፤›› ብሎ አትናቴዎስ አርዮስን ሲጠይቀውና ሲከራከረው የሰሙት አብዛኞቹ የጉባኤው አባላት በደስታ ተዋጡ፡፡ አርዮስ ‹‹ወልድ በምድር ሕይወቱ ታላቅ ትሕትናንና ተጋድሎን በማሳየቱ በባሕርይ ሳይሆን በጸጋ የአምላክነትን ክብር ስላገኘ ስግደት ይገባዋል፤›› ይላል፡፡ አትናቴዎስም ‹‹ክርስቶስ ከባሕርይ አባቱ ከአብ ጋር አንድ ነው፡፡ ነገር ግን ወልድ ፍጡር ነውካልን ለእርሱ የአምልኮ ስግደት ማቅረብ አማልኮ ባዕድ ነዋ!›› ሲለው አርዮስ መልስ አላገኘም፡፡

ከአርዮሳውያን ጋር የከረረ ክርክር የተደረገው በሁለት ጉዳዮች ነበር፤ እነዚህም ፩ኛ አርዮስ ወልድን ‹‹ፍጡር ነው›› ለማለት ‹‹ሀሎ አመ ኢሀሎ ወልድወልድ ያልነበረበት ጊዜ ነበር›› ሲል ኦርቶዶክሳውያን ወልድን ዘለዓለማዊ ነው ለማለት ‹‹አልቦ አመ ኢሀሎ ወልድወልድ ያልኖረበት ጊዜ የለም›› ብለው የአርዮሳውያንን ክሕደት አጥላልተው አወገዙት፡፡ ፪ኛ አርዮስና ደጋፊዎቹ ‹‹ወልድ በባሕርዩ (በመለኮ) ከአብ ጋር አንድ አይደለም፤›› የሚሉትን ጉባኤው ካወገዘ በኋላ፣ ኦርቶዶክሳውያን ወልድን “Omo-ousios” (ዋሕደ ባሕርይ ምስለ አብ ወይም ዘዋሕድ ምስለ አብ በመለኮቱወልድ ከአብ ጋር በባሕርዩ በመለኮቱ አንድ ነው)›› አሉ፡፡ የአርዮስ ደጋፊዎች የነበሩትም የአርዮስን የክሕደት ትምህርት ያልተቀበሉ በማስመሰልና ኦርቶዶክሳውያን በመምሰል “Omoi-ousios” (የወልድ ባሕርይ ከአብ ባሕርይ ጋር ተመሳሳይ ነው) ብለው ሐሳብ አቀረቡ፡፡ የእነዚህንም ሐሳብ ጉባኤው ፈጽሞ አልተቀበለውም ነበር፡፡ እነዚህም መንፈቀ አርዮሳውያን (Semi-Arians) ተብለው ተወግዙ፡፡

“Omo-ousios” (ዋሕደ ባሕርይ ምስለ አብ በመለኮቱ ወይም ዘዋሕድ ምስለ አብ በመለኮቱ) የሚለውን ሐረግ አርዮሳውያንና መንፈቀ አርዮሳውያን አጥብቀው ተቃውመውት ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ የኮርዶቫው ኤጲስቆጶስ ኦስዮስና የእስክንድርያው ሊቀ ዲያቆን አትናቴዎስ ባቀረቡት ሐሳብ መሠረት “Omo-ousios” (ዋሕደ ባሕርይ ምስለ አብ በመለኮቱ ወይም ዘዋሕድ ምስለ አብ በመለኮቱ ወይም ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ) የሚለው ሐረግ ተጨምሮበት፣ የወልደ አብ ኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት የሚያረጋግጥ ፯ አናቅጽ ያሉት ቃለ ሃይማኖት (ጸሎተ ሃይማኖት) ተዘጋጅቶ ቀረበና የጉባኤው አባቶች ሁሉ ፈረሙበት፡፡ ከጸሎተ ሃይማኖት ፯ አንቀጾች መካከል የመጀመሪያው አንቀጽ የሚከተለው ነው፤

‹‹ሁሉን በያዘ፣ ሰማይንና ምድርን፣ የሚታየውንና የማይታየውን በፈጠረ በአንድ አምላክ በእግዚአብሔር አብ እናምናለን፡፡ ዓለም ሳይፈጠር ከእርሱ በተወለደ፣ የአብ አንድ ልጁ በሚሆን በአንድ ጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ እናምናለን፡፡ ከብርሃን የተገኘ ብርሃን፣ ከእውነተኛ አምላክ የተገኘ አምላክ፣ የተወለደ እንጂ ያልተፈጠረ፣ በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ የሚሆን፣ ሁሉ በእርሱ የሆነ (የተፈጠረ) በሰማይም  በምድርም፡፡ ስለ እኛ ስለ ሰዎች እኛን ለማዳን ከሰማይ የወረደ፤ ሥጋ የሆነ፡፡ ሰው ሆኖም ስለ እኛ የታመመ፡፡ በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ የተነሣ፡፡ ወደ ሰማይ የዐረገ፡፡ በሕያዋንና በሙታን ይፈርድ ዘንድ ዳግመኛ የሚመጣ፡፡ በመንፈስ ቅዱስም እናምናለን፡፡››

በመጨረሻም ከዚህ በላይ እንደተገለጠው ጉባኤው የወልድን አምላክነትና በባሕርይ (በመለኮት) ከአብ ጋር አንድ መሆኑን በውል አረጋግጦና ወስኖ አርዮስንና መንፈቀ አርዮሳውያንን አውግዞ ከማኅበረ ክርስቲያን ለይቷቸዋል፡፡ አርዮስና የተወገዙት አርዮሳውያን ሁሉ በንጉሠ ነገሥቱ እንዲጋዙ ተደርገዋል፡፡

፪. በኢትዮጵያ ጸሎተ ሃይማኖት በተለይ የ‹‹Omoousios tw patri›› ትርጕም

‹‹Omoousios tw patri›› የሚለው የግሪኩ ሐረግ በግእዝ የተተረጐመው ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ›› ተብሎ ሲሆን፣ በአማርኛው ነጠላ ትርጕም ግን ‹‹በመለኮቱ ከአብ ጋር የሚተካከል›› ተብሎ ነው የተተረጐመው፡፡ የግሪኩ ቃል የሚገልጠው ‹‹በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ የሚሆን›› ማለትን ነው፡፡ ‹‹የሚተካከል›› የሚለው ቃል ግን የግሪኩንም ሆነ የግእዙን ሐረግ አይወክልም፡፡ እንዳውም ‹‹መተካከል›› የሚለው ቃል መመሳሰልን ወይም ምንታዌን (ሁለትዮሽን) ነው እንጂ አንድነትን አይገልጥም፡፡ ይህ ደግሞ የመንፈቀ አርዮሳውያንን ሐሳብ ስለሚመስል የኢትዮጵያ ሊቃውንት የአማርኛውን ትርጕም እንደገና ሊያስቡበት ይገባል፡፡ በእርግጥ ‹‹ዐረየ›› ማለት ‹‹ተካከለ ማለት ነው፡፡ አለቃ ኪዳነ ወልድ እንደሚሉት በሌላ መንገድ ግን ‹‹ዐረየ›› የሚለው ግስ ‹አንድ ሆነ የሚል ትርጕም አለው፡፡ ለምሳሌ ‹‹ወምስለ ብሉይ ኢይዔሪ›› የሚለው ኃይለ ቃል ‹‹ከአሮጌው ጋር አንድ አይሆንም›› ተብሎ ይተረጐማል፡፡ እንደዚሁም በመዝሙረ ዳዊት ‹‹እስመ ተማከሩ ኅቡረ ወዐረዩ›› የሚለው ኃይለ ቃል ‹‹አንድ ሆነው በአንድነት ተማክረዋልና›› የሚል ትርጕም አለው፡፡

ስለዚህ ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ›› የሚለው ሐረግ ‹‹በመለኮቱ ከአብ ጋር አንድ የሚሆን›› ተብሎ መተርጐም አለበት፡፡ ‹‹በመለኮቱ ከአብ ጋር የሚተካከል›› ከተባለ ግን ይህ መንፈቀ አርዮሳዊ አነጋገር ይሆናል፡፡ ምክንያቱም መንፈቀ አርዮሳውያን ‹‹ወልድ ከአብ ጋር በመለኮት ይመሳሰላል እንጂ አንድ አይደለም›ነው የሚሉት፡፡ ሃይማኖተ አበውን የተረጐሙ አባቶችም ‹‹ዐረየ›› ወይም ‹‹ዕሩይ›› የሚለውን ቃል ‹አንድ የሆነ› ብለው ነው የተረጐሙት፡፡ ለምሳሌ ‹‹ወውእቱ ዕሩይ ምስሌሁ በመለኮት›› የሚለውን ሲተረጕሙ ‹‹እርሱም በመለኮት ከአብ ጋር አንድ ነው›› ብለውታል፡፡ እንደዚሁም ‹‹ነአምን በሥላሴ ዕሩይ በመለኮት›ሲተረጐም ‹‹በመለኮት አንድ በሚሆኑ በሥላሴ እናምናለን›› ተብሎ ነው፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ‹‹ወበከመ ወልድ ዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ›› የሚለው ኃይለ ቃል ትርጕም ‹‹ወልድ በባሕርዩ ከአብ ጋር አንድ እንደ ሆነ›› ማለት ነው፡፡ እንደዚሁም የቅዳሴው የአንድምታ ትርጕም ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ›› የሚለውን ኃይለ ቃል የተረጐሙት ሊቅ ‹‹ከአብ ጋር በመለኮቱ አንድ የሚሆን›› በማለት ነው፡፡

እንግዲህ ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ›› የሚለው ኃይለ ቃል ‹‹ከአብ ጋር በመለኮቱ አንድ የሚሆን›› ተብሎ ከተተረጐመ ምንም የእምነት ጕድለት ወይም ስሕተት አይኖረውም፡፡ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስም ይህን ኃይለ ቃል ‹‹ዘዕሩይየሚተካከል›› ተብሎ እንዳይተረጐም ብለው ‹‹ዘዋሕድ ምስለ አብ በመለኮቱ›› በማለት አርመዉታል፡፡ ትርጕሙ ጥሩ ነው፤ ነገር ግን ‹‹ዘዕሩይ›› የሚለው ቃል የወጣበት ‹‹ዐረየ›› የሚለው ግስ ከላይ እንደተገለጸው ‹‹አንድ ሆነ›› የሚል ትርጕም ስላለው ‹‹ዘዕሩይ›› የሚለው ግእዙ ባይለወጥ ጥሩ ይመስለኛል፡፡ መስተካከል ያለበት ግእዙ ሳይሆን የአማርኛው ትርጕም ነው፡፡ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስም በዋናው ጸሎተ ሃይማኖት ላይ ‹‹ዘዕሩይ›› የሚለውን ቃል ሳያርሙ እንዳለ አስቀምጠውታል፡፡

ይቆየን

አርዮስ እና መንፈቀ አርዮሳውያን በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሱት ችግር – ክፍል ሁለት

በቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል

ኅዳር ፲ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ በሰማዕትነት ከሞተ በኋላ በ፫፻፲፪ ዓ.ም አርኬላዎስ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ (ፓትርያርክ) ሆኖ በምትኩ ተሾመ፡፡ በዚህ ጊዜ አርዮስ ከክሕደቱ የተጸጸተ መስሎ ወደ ፓትርያርክ አርኬላዎስ ቀረበ፡፡ የአርዮስ ደጋፊዎችም ፓትርያርኩ ከውግዘቱ እንዲፈታው በአማላጅነት በመቅረባቸው፣ አዲሱ ፓትርያርክ የቀድሞውን ፓትርያርክ የተፍጻሜተ ሰማዕት ጴጥሮስን ትእዛዝና አደራ በመዘንጋት አርዮስን ከውግዘቱ ፈታው፡፡ ይባስ ብሎም የቅስና ማዕረግ ሰጥቶ ሾመው፡፡ ሆኖም አርኬላዎስ አንድ ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በሞት ተለየ፡፡ የሰማዕቱን የቅዱስ ጴጥሮስን ቃል ባለመጠበቁ የመቅሠፍት ሞት ነው የሞተው ይባላል፡፡

በአርኬላዎስም ምትክ ስመ ጥሩውና በዘመኑ ሁሉ ለቤተ ክርስቲያን እጅግ የተጋደለ አባት እለእስክንድሮስ (፫፻፲፪ – ፫፻፳፰ ዓ.ም) በካህናትና ምእመናን ተመርጦ ተሾመ፡፡ እለእስክንድሮስ ወዲያውኑ የአርዮስን የክሕደት ትምህርት በይፋ እየተቃወመ አርዮስን በጥብቅ አወገዘ፡፡ የአርዮስ ደጋፊዎች አርዮስን ከፓትርያርኩ ጋር ለማስማማት አጥብቀው ቢሞክሩም ፓትርያርክ እለእስክንድሮስ አልበገርም አለ፡፡ አርዮስ ተጸጽቶ፣ ስሕተቱን ለጌታ ለኢየሱስ ክርስቶስ ተናዝዞ ከተመለሰ ጌታ ምልክት ስለሚሰጠው ያንጊዜ እርሱ እንደሚቀበለው ነግሮ አሰናበታቸው፡፡ አርዮስ በበኩሉ በድፍረት የክሕደት ትምህርቱን ማሠራጨት ቀጠለ፡፡ ሕዝቡም ትምህርቱን በቀላሉ እንዲቀበለው የክሕደት ትምህርቱን በግጥምና በስድ ንባብ እያዘጋጀ ያሠራጭ ጀመር፡፡ ያም የግጥም መጣጥፍ ‹ታሊያ› ይባል ነበር፡፡ ትርጕሙም ማዕድ ማለት ነው፡፡ ሕዝብ ደግሞ ግጥም ማንበብ ስለሚወድና በግጥም መልክ ያነበበውን ስለማይዘነጋው የአርዮስን ትምህርት ለመቀበል ደርሶ ነበር፡፡

ሊቀ ጳጳሱ እለእስክንድሮስም ምእመናን ከአርዮስ የክሕደት ትምህርት እንዲጠበቁ እየዞረ በማስጠንቀቅ ያስተምር ጀመር፡፡ ፓትርያርኩም በ፫፻፲፰ ዓ.ም በእስክንድርያና በአካባቢዋ የሚገኙትን ጳጳሳትና ካህናት ሰብስቦ አርዮስንና ተከታዮቹን በጉባኤ አወገዛቸው፡፡ አርዮስ ግን ከስሕተቱ ባለመመለሱ ፓትርያርክ እለእስክንድሮስ በ፫፻፳፩ ዓ.ም አንድ መቶ የሚሆኑ የእስክንድርያንና የሊብያን ኤጲስቆጶሳት ሰብስቦ ጉባኤ በማድረግ የአርዮስን ክሕደት በዝርዝር አስረዳቸው፡፡ ሲኖዶሱም ጉዳዩን በሚገባ ከመረመረ በኋላ አርዮስን በአንድ ድምፅ አወገዘው፡፡ አርዮስም በበኩሉ እየዞረ ‹‹እለእስክንድሮስ ሰባልዮሳዊ ነውየሰባልዮስን የክሕደት ትምህርት ያስተምራል›› እያለ የሊቀ ጳጳሱን የእለእስክንድሮስን ስም ማጥፋት ጀመረ፡፡ በመሠረቱ ከሰባልዮስ ትምህርት ጋር የሚቀራረበው ‹‹ወልድ ፍጡር ነው›› (ሎቱ ስብሐት) የሚለው የአርዮስ ትምህርት ነው እንጂ ‹‹ወልድ የባሕርይ አምላክ ነውከአብም ጋር በባሕርይ አንድ ነው (ዘዋሕድ ምስለ አብ በመለኮቱ)›› የሚለው ትምህርት አይደለም፡፡

የአርዮስ ትምህርት በእስክንድርያና በመላዋ ግብጽ ብዙም ተቀባይነት ባለማግኘቱ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ወደ ሦርያና አንጾኪያ እየዞረ ቀድሞ ጓደኞቹ ለነበሩትና የእርሱን የክሕደት ትምህርት ለሚደግፉ ጳጳሳት ሁሉ ፓትርያርክ እለእስክንድሮስ ያለ አግባብ እንዳወገዘውና እንዳባረረው ከመንገሩም በላይ ‹‹እለእስክንድሮስ የሰባልዮስን ትምህርት ያስተምራል›› እያለ ስሙን ያጠፋ ጀመር፡፡ በዚያ የነበሩት የአርዮስ የትምህርት ቤት ጓደኞች ጳጳሳት ለምሳሌ የኒቆምዲያው ኤጲስቆጶስ አውሳብዮስና የቂሣርያው ኤጲስቆጶስ አውሳብዮስ የአርዮስን ሐሳብ ይደግፉ ስለነበር አርዮስ የክሕደት ትምህርቱን እየዞረ እንዲያስተምር ፈቀዱለት፡፡ ከዚህም በላይ ደፍረው ፓትርያርክ እለእስክንድሮስ አርዮስን እንዲቀበለው ጠየቁለት፡፡ ፓትርያርክ እለእስክንድሮስ ግን ይህንን ጥያቄ አልተቀበለውም ነበር፡፡ እንደውም እለእስክንድሮስ በበኩሉ የአርዮስን የክሕደት ትምህርት በመቃወምና በማውገዝ ብዙ ደብዳቤዎችን በመላዋ ግብጽና በመካከለኛው ምሥራቅ ለሚገኙ ሊቃነ ጳጳሳትና ኤጲስ ቆጶሳት ያስተላልፍ ጀመር፡፡

በአርዮስ ደጋፊ በኒቆምዲያ ኤጲስቆጶስ አውሳብዮስ አሳሳቢነትና ሰብሳቢነት በ፫፻፳፪ እና ፫፻፳፫ ዓ.ም በተከታታይ ሁለት ጉባኤያትን አድርገው የአርዮስ ትምህርት ትክክለኛ መሆኑን በማብራራትና ‹‹የአርዮስ ሃይማኖት ትክክል ስለሆነ መወገዝ አይገባውም›› በማለት የእለእስክንድሮስን ውግዘት በመሻር ለአርዮስ ፈረዱለት፡፡ አርዮስም ወደ እስክንድርያ ተመልሶ ያንኑ የክሕደት ትምህርቱን በስፋት ያስተምር ጀመር፡፡ በአርዮስ ክሕደት ምክንያት የተነሣው ውዝግብ በመላው የክርስትና አህጉር ሁሉ በተለይም በምሥራቁ የሮም ግዛት በመሠራጨቱ ቤተ ክርስቲያንና የሮም ግዛት በሙሉ እጅግ ታወኩ፡፡ ጳጳሳትና መምህራን እርስበርሳቸው ይነታረኩ ጀመር፡፡ በዚህም ሰላም ጠፍቶ በዚያው ወቅት የመላ የሮም ንጉሠ ነገሥት መንግ ሥት ብቸኛ ቄሣር የሆነውን ታላቁን ቈስጠንጢኖስ እጅግ አሳሰበው፡፡ ንጉሠ ነገሥት ቈስጠንጢኖስ በመላ ግዛቱ ሰላም እንዲሰፍን በመሻቱ ውዝግቡን በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ለማብረድ መልእክተኞችን ደብዳቤ አስይዞ ወደየጳጳሳቱ ይልክ ጀመር፡፡ በደብዳቤውም የቃላት ጦርነት እንዲያቆሙና በሰላም እንዲኖሩ ይጠይቅ ነበር፡፡

ለዚህም መልእክት ጉዳይ ሽማግሌ የነበረውን በስፔን የኮርዶቫ ጳጳስ ኦስዮስን ወደ እስክንድርያ ደብዳቤ አስይዞ ላከው፡፡ ኦስዮስም በአንድ በኩል ከእለእስክንድሮስና ከግብጽ ኤጲስቆጶሳት ጋር፣ በሌላ በኩል ደግሞ ከአርዮስና ከእርሱ ደጋፊዎች ጋር ተወያይቶ በሁለቱ መካከል የነበረውን ልዩነት በሚገባ ከመረመረ በኋላ ወደ ንጉሠ ነገሥቱ ወደ ቈስጠንጢኖስ ተመልሶ ነገሩ ከባድ የሃይማኖት ጉዳይ ስለሆነ የመላው ሕዝበ ክርስቲያን ጳጳሳት የሚገኙበት ታላቅ ጉባኤ ተጠርቶ ውዝግቡ በጉባኤ ታይቶ ቢወሰን እንደሚሻል ለንጉሠ ነገሥቱ ምክር ሰጠ፡፡ ታላቁ ቈስጠንጢኖስም ምክሩን ተቀብሎ የመላው አብያተ ክርስቲያናት መሪዎች የሚሳተፉበት ዓለም አቀፋዊ ሲኖዶስ እንዲደረግ አዋጅ ነገረ፡፡ ጉባኤውም የቢታንያ አውራጃ ከተማ በሆነችው በኒቅያ እንዲሆን ተወሰነ፡፡ ለጉዞና ለኑሮ የሚያስፈልገው ወጪ ሁሉ ከመንግሥት ካዝና እንዲሆን ንጉሠ ነገሥቱ ትእዛዝ አስተላለፈ፡፡

ስለዚህም ቈስጠንጢኖስ በነገሠ በሃያ ዓመቱ በ፫፻፳፭ ዓ.ም በሮም ግዛት ውስጥ የነበሩት ሊቃነ ጳጳሳት፣ ኤጲስቆጶሳትና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንዲሰበሰቡ ጥሪ አስተላለፈ፡፡ እያንዳንዱ ኤጲስቆጶስ ሁለት ቀሳውስትንና ሦስት ምእመናንን (ሊቃውንትን) ይዞ እንዲመጣ ንጉሡ በፈቀደው መሠረት ብዙ ቀሳውስትና ምእመናን (ሊቃውንት) በጉባኤው ላይ ተገኝተው ነበር፡፡ ለጉባኤው የተሰበሰቡት አባቶችም ፫፻፲፰ ያህሉ ነበር፡፡ በጉባኤው የተሰበሰቡትን አባቶች ቍጥር የቤተ ክርስቲያን ጸሐፊዎች ከፊሎቹ ከፍ፣ ሌሎቹ ደግሞ ዝቅ አድርገው ይጽፋሉ:: ለምሳሌ የቂሣርያው አውሳብዮስ ፪፻፶ ነበሩ ሲል፣ ቴዎዶሬት ደግሞ ፪፻፸ ነበሩ ይላል፡፡ እንደዚሁም ሶቅራጥስ ፫፻፤ ሶዞሜን ደግሞ ፫፻፳ ነበሩ ይላሉ፡፡

በጉባኤው የተሰበሰቡት አባቶች በሕይወታቸው ንጽሕናና ቅድስና መሰል የሌላቸው፣ በሃይማኖታቸውም የሐዋርያትን ፈለግ የተከተሉ ነበሩ፡፡ ከዚህም ሁሉ ጋር በገቢረ ተአምራት ከፍ ያለ ዝና ያላቸው ነበሩ፡፡ በስብሰባውም ላይ ሃያ አርዮሳውያን ኤጲስቆጶሶች፣ የተወሰኑ አርጌንሳውያንና የፍልስፍና ምሁራን ተጠርተው መጥተው ነበር፡፡ የጉባኤው የክብር ፕሬዝዳንት ንጉሠ ነገሥቱ ታላቁ ቈስጠንጢኖስ ሲሆን፣ ጉባኤውን በሊቀ መንበርነት እንዲመሩ የተመረጡት ሦስት ሊቃነ ጳጳሳት ነበሩ፡፡ እነዚህም፡- የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ አቡነ እለእስክንድሮስ፣ የአንጾኪያው ሊቀ ጳጳስ ኤዎስጣቴዎስ እና የኮርዶቫው (የእስፔኑ) ጳጳስ ኦስዮስ ነበሩ፡፡ ከጉባኤው ተካፋዮች መካከል እጅግ የታወቁ ምሁራን ነበሩ፡፡

ከእነዚህም ጥቂቶቹ እጅግ የተማረ፣ ንግግር ዐዋቂና ለኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ቀናተኛ የነበረው፣ የእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ዲያቆን ሆኖ ለሊቀ ጳጳሱ ለእለእስክንድሮስ እንደ አፈ ጉባኤ የነበረው አትናቴዎስና ስመ ጥር የነበረው የቂሣርያው አውሳብዮስ ነበሩ፡፡ እንደዚሁም በዘመነ ስደት ጊዜ ለሃይማኖታቸው ብዙ ሥቃይ የተቀበሉ፣ ዓይናቸው የጠፋ፣ እጅ ወይም እግራቸው የተቆረጠ በቅድስናቸው የታወቁ አባቶችም ነበሩ፡፡ ከዚህም ሌላ በምንኵስና እና በብሕትውና ኑሯቸው እጅግ የታወቁ፣ የዛፍ ሥርና ቅጠል ብቻ በመብላት ይኖሩ የነበሩ፣ ተአምራትን በማድረግ በክርስቲያኖች ዘንድ እጅግ የተከበሩ አባቶች ነበሩ፡፡

ጉባኤው በአብዛኛው የተካሔደው በኒቅያ ከተማ በምትገኘው በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሲሆን፣ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ እዚያው ኒቅያ በሚገኘው በንጉሠ ነገሥቱ ቤተ መንግሥት አዳራሽ ይካሔድ እንደነበር ይነገራል፡፡ ጉባኤውም በሦስት ቡድን የተከፈለ ነበር፤ ይኸውም የመጀመሪያው የኦርቶዶክሳውያን፣ ሁለተኛው የአርዮሳውያን፣ ሦስተኛው ደግሞ የመንፈቀ አርዮሳውያን ቡድን ሲሆን፣ በመጀመሪያው ቡድን የነበሩት ኦርቶዶክሳውያን መሪዎችም የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ እለእስክንድሮስ፣ ሊቀ ዲያቆኑ አትናቴዎስ፣ የአንጾኪያው ሊቀ ጳጳስ ኤዎስጣቴዎስ፣ የኮርዶቫው (የእስፔኑ) ኤጲስቆጶስ ኦስዮስ፣ የአንኪራው (ዕንቆራው) ኤጲስቆጶስ ማርሴሎስ ወዘተ. ነበሩ፡፡

ከእነዚህም ሁሉ በክርክሩ ወቅት ጠንካራና ከባድ ክርክር ይከራከር የነበረውና፣ ለተቃዋሚዎቹ አፍ የሚያስይዝ ምላሽ ይሰጥ የነበረው የእስክንድርያው ሊቀ ዲያቆን አትናቴዎስ ነበር፡፡ በሁለተኛው ቡድን የነበሩትም አርዮስና የንጉሡ ወዳጅ የነበረው የኒቆምዲያው ኤጲስቆጶስ አውሳብዮስ፣ የኒቅያው ኤጲስቆጶስ ቴኦግኒስ፣ የኬልቄዶን ኤጲስቆጰስ ማሪስና የኤፌሶን ኤጲስቆጶስ ሜኖፋንቱስ ነበሩ፡፡ አርዮስ ግን ተከሳሽ ስለነበረ በየጊዜው በጉባኤው እየተጠራ መልስ ይሰጥ ነበር እንጂ የሲኖዶሱ ተካፋይ አልነበረም፡፡ ሦስተኛው ቡድን የመንፈቀ አርዮሳውያን (የመሀል ሰፋሪዎች) ቡድን ሲሆን፣ የእነርሱ ወኪልም የታወቀው የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊ የቂሣርያው ኤጲስቆጶስ አውሳብዮስ ነበር፡፡ ይህ ሰው መንፈቀ አርዮሳዊ ሆኖ ከቆየ በኋላ በመጨረሻ ወደ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተመልሷል፡፡

ይቆየን

አርዮስ እና መንፈቀ አርዮሳውያን በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሱት ችግር – ክፍል አንድ

በቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል

ኅዳር ፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በመጀመሪያው አራት መቶ ዓመታት ውስጥ ቤተ ክርስቲያን በብዙ አቅጣጫ የተለያዩ ችግሮች ደርሰውባት እጅግ ስትሠቃይ ቆይታለች፡፡ በቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሱት ችግሮችም ከሁለት አቅጣጫዎች የመጡ ነበሩ፤ አንደኛው ከቤተ ክርስቲያን ውጭ ሲሆን ሁለተኛው ከዚያው ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተነሡ ችግሮች ነበሩ፡፡ በመጀመሪያው አብዛኛውን ጊዜ ችግር የተነሣው ከአሕዛብ ነገሥታት ሲሆን፣

፩ኛ/ የሮም መንግሥት ገዢዎችና በክፍላተ ሀገሩ የነበሩት የእነርሱ ወኪሎች እነሱ ያመልኩአቸው የነበሩትን ጣዖታት ክርስቲያኖች ስለማይቀበሉና ጨርሰውም ስለሚያወግዙ፤

፪ኛ/ አሕዛብ ያደርጉት እንደነበረው ክርስቲያኖች ለሮም ነገሥታት የአምልኮ ክብር ስለማይሰጡ፣ በቤተ ክርስቲያን ላይና በክርስቲያኖች ላይ በየጊዜው ስደት ታውጆ ክርስቲያኖች ሲሠቃዩ ኖረዋል፡፡

፫ኛ/ የጣዖታት ካህናትና የጣዖታት ምስል ሠራተኞች በክርስትና ሃይማኖት መስፋፋት ምክንያት የጣዖት አምልኮ እጅግ ስለቀነሰና በአንዳንድ ቦታዎችም አምልኮ ጣዖት ጨርሶ ስለቀረ ኑሮአቸው በመቃወሱ፣ ከአሕዛብ ነገሥታት ጋር በመወገን በክርስቲያኖች ላይ ልዩ ልዩ ችግሮች ይፈጥሩ ነበር፡፡

በቤተ ክርስቲያን ላይ ከውስጥ የተነሡ ችግሮችም እጅግ የበዙና የከፉም ነበሩ፡፡ ከመጀመሪያ ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ብዙ መለያየትና መከፋፈል ስለታየ አንዲት ቤተ ክርስቲያን ለብዙ ክፍሎች ትከፋፈል ይሆናል ተብሎ ተፈርቶ ነበር፡፡ በግብረ ሐዋርያት ላይ እንደተጠቀሰው ከአይሁድ ወገን ወደ ክርስትና በገቡትና ከአሕዛብ ወገን ወደ ክርስትና በገቡት ክርስቲያኖች መካከል የታዩት ብዙ ልዩነ ቶች ነበሩ፡፡ ይህ ችግር በ፶፩ ዓ.ም በተደረገው በሐዋርያት ጉባኤ በተሰጠው ውሳኔ መፍትሔ አግኝቶ በመጠኑም ቢሆን ችግሩ ተወግዶ ነበር፡፡ በኋላ ደግሞ በሁለተኛውና በሦስተኛው መቶ ዓመት ላይ ተነሥተው የነበሩት ዶኬቲኮች፣ ግኖስቲኮችና የሰባልዮስና የጳውሎስ ሳምሳጢ ተከታዮች የነበሩ መናፍቃን ተነሥተው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ብዙ የከፋ ብጥብጥ ተነሥቶ ነበር፡፡

ይህም ችግር በየክፍላተ ሀገሩ በተጠሩ ሲኖዶሶች (ጉባኤዎች) የቤተ በክርስቲያን አንድነት ተጠብቆ ቆይቷል፡፡ እንደዚሁም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ስለምሥጢረ ሥላሴ ዶግማ (ትምህርት) በቤተ ክርስቲያን መምህራን መካከል ብዙ ልዩነቶች ተፈጥረው ነበር፡፡ የእነጳውሎስ ሳምሳጢና የእነሰባልዮስ የኑፋቄ ትምህርቶች በቤተ ክርስቲያን አህጉራዊ ጉባኤያት (ሲኖዶሶች) ተወግዘው በዚህ ምክንያት የተነሣው ውዝግብ ጥቂት ረገብ ብሎ ነበር፡፡ ነገር ግን ከግማሽ ምእት ዓመት በኋላ በአርዮስ የምሥጢረ ሥላሴ ትምህርት ምክንያት ማለት አርዮስ ‹‹ወልድ ፍጡር ነው›› (ሎቱ ስብሐት) ብሎ በመነሣቱ ቤተ ክርስቲያን ለብዙ ዓመታት ስትታወክና ስትበጠበጥ ቆይታለች፡፡

፩. የአርዮስ የክሕደት (የኑፋቄ) ትምህርት

አርዮስ ከሦስተኛው ምእት ዓመት አጋማሽ በኋላ በ፪፻፷ ዓ.ም አካባቢ በሰሜን አፍሪካ በሊብያ ነው የተወለደው፡፡ ስሙ እንደሚያመለክተው የትውልድ ዘሩ (የዘር ሐረጉ) የሚዘዘው ከግሪክ ሲሆን፣ የተገኘውም ከክርስቲያን ቤተሰብ ነበር፡፡ በትውልድ ሀገሩ መሠረታዊ ትምህርቱን ከአጠናቀቀ በኋላ እስክንድርያ በሚገኘው ከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ገብቶ ከፍተኛ ትምህርት ተምሯል፡፡ አርዮስ በእስክንድርያ ከፍተኛ ትምህርት ቤት ትምህርቱን ካጠናቀቀ በኋላ ወደመካከለኛው ምሥራቅ ሔዶ በአንጾኪያ ከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ገብቶ ከፍተኛ የትርጓሜ መጻሕፍት ትምህርትና የነገረ መለኮት ትምህርት ተምሯል፡፡ መምህሩም የታወቀው ሉቅያኖስ ነበር፡፡ ከእስክንድርያ ትምህርት ቤት ይልቅ የአንጾኪያ ትምህርት ቤት ለአርዮስ የክህደት ትምህርት ቅርበት እንደነበረው ብዙ ሊቃውንት ይናገራሉ፡፡

አርዮስ አብዛኛውን የኑፋቄ ትምህርቱን ያገኘው ከሉቅያኖስና ከአንጾኪያ ትምህርት ቤት ነው፡፡ በአንጾኪያ የሚፈልገውን ትምህርት ከጨረሰ በኋላ ወደ እስክንድርያ ተመልሶ ኑሮውን በዚያው አደረገ፡፡ አርዮስ እጅግ ብልህና ዐዋቂ ሰው በመሆኑ ብዙ ሰዎች ያደንቁት ነበር፡፡ አንደበተ ርቱዕም ስለነበረ ተናግሮ ሕዝብን በቀላሉ ማሳመን እንደሚችል ይነገርለታል፡፡ በዚያ በነበረው ዕውቀትና ታላቅ የንግግር ችሎታ የእስክንድርያ ፓትርያርክ የነበረው ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ ዲቁና ሾመው፡፡ የእስክንድርያ ከፍተኛ ትምህርት ቤት ከከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህርት ሌላ የግሪክ ፍልስፍናን በተለይም የፕላቶንን ፍልስፍና ያስተምሩ ስለነበር፣ አርዮስም ፍልስፍናን በተለይም ሐዲስ ፕላቶኒዝም (Neo-Platonism) የተባለውን ፍልስፍና በሚገባ ተምሯል፡፡

በዚህም የእስክንድርያውን ከፍተኛ ትምህርት ቤት ታላቅ መምህር የነበረውን የአርጌንስን (Origen) የተዘበራረቀ የምሥጢረ ሥላሴን ትምህርት ተከትሎ መጓዝ ጀመረ፡፡ አርጌንስ በምሥጢረ ሥላሴ ትምህርቱ አብን ከወልድ፣ ወልድን ደግሞ ከመንፈስ ቅዱስ በማዕረግና በዕድሜ ያበላልጥ ነበር፡፡ አርጌኒስ አብን፣ ወልድንና መንፈስ ቅዱስን በማበላለጥ አብ ከወልድ እንደሚበልጥ፣ መንፈስ ቅዱስ ደግሞ ከወልድ እንደሚያንስ ያስተምር ነበር፡፡ ስለዚህ የአርዮስ የክህደት ትምህርቱ ዋናው መሠረት አርጌኒስ እንደሆነ አያጠራጥርም፡፡ ምንም እንኳን አርጌኒስ ስለቅድስት ሥላሴ ቢያስተምርም፣ አርዮስ አጥብቆ የተናገረውና የኑፋቄ ትምህርቱን ያስተማረው ስለአብ እና ስለወልድ ነበር፡፡ በአጠቃላይ የአርዮስ የክሕደት ትምህርት የሚከተለው ነው፤

፩. አብ ብቻ ዘለዓለማዊ (ዘአልቦ ጥንት ወኢተፍጻሜት) ነው፡፡ ወልድ ግን ዘለዓለማዊ አይደለም፡፡ ነገር ግን እርሱ ያልነበረበት ጊዜ ነበር ለማለት ‹‹ሀሎ አመ ኢሀሎ›› (እርሱ ያልነበረበት ጊዜ ነበር) እያለ ያስተምር ጀመር፡፡ ስለዚህ አብ አባት ተብሎ የተጠራውና እንደ አባት የታወቀው ከዘመናት በኋላ እንጂ ከዘመናት በፊት አብ ተብሎ አይጠራም አለ፡፡ ይህንን ያለው ‹‹ወልድ ፍጡር ነው›› (ሎቱ ስብሐት) ብሎ ያልነበረበት ጊዜ ነበረ ለማለት ነበር፡፡

፪. የአርዮስ ዋናው የክሕደት ትምህርቱ ‹‹ወልድ ፍጡር ነው›› (ሎቱ ስብሐት) ማለትም ‹‹ወልድ ከመፈጠሩ በፊት አልነበረም፤›› የሚል ነው፡፡ ‹‹አብወልድን ከምንም ፈጠረና የእግዚአብሔር ልጅ እንዲሆን አደረገውለወልድ ጥበብ፣ ቃል የሚባሉ የኃይላት ስሞች አሉት›› እያለ ያስተምር ነበር፡፡ ለክሕደቱ መሠረት የሆነውና ሁልጊዜ ይጠቅሰው የነበረውም፡- ‹‹ትቤ ጥበብ ፈጠረኒ መቅድመ ሉ ተግባሩጥበብ ከፍጥረቱ ሁሉ አስቀድሞ እኔን ፈጠረኝ አለች፤›› ተብሎ በመጽሐፈ ምሳሌ ፰፥፳፪ ላይ የተጠቀሰው ኃይለ ቃል ነበር፡፡ በአርዮስ አስተሳሰብ ጥበብ የተባለ ወልድ ነው፤ ስለዚህ እግዚአብሔር አብ መጀመሪያ ወልድን ፈጠረ፡፡  ከዚያ በኋላ ወልድ ዓለምንና በውስጡ ያሉትን ሁሉ ፈጠረ ብሎ ያምን ነበር፡፡ ያለ ወልድ ምንም የተፈጠረ ፍጥረት የለም ብሎ ያስተምርም ነበር፡፡

፫. ከዚህም ሌላ አርዮስ ወልድን ከአብ ሲያሳንስ ‹‹ወልድ በባሕርዩ ከአብ ጋር አንድ አይደለም›› ይል ነበር፡፡ በሌላ በኩል ግን ወልድን ከሌሎች ከፍጡራን እጅግ ያስበልጠዋል፡፡ ወልድም በጸጋ የአብ ልጅ እንደሆነ ይናገራል፡፡ እንደዚሁም ወልድ በምድር ሕይወቱ ታላቅ ትሕትናንና ተጋድሎን በማሳየቱ በባሕርይ ሳይሆን በጸጋ የአምላክነትን ክብር እንዳገኘ አርዮስ በአጽንዖት ይናገር ነበር፡፡

፬. በአርዮስ አመለካከት ወልድ በባሕርዩ ፍጹም ስላልሆነ የአብን መለኮታዊ ባሕርይ ለማየትም ለማወቅም አይችልም ይል ነበር፡፡

፭. አርዮስ ስለ መንፈስ ቅዱስ ሲናገር ‹‹ወልድ ለአብ የመጀመሪያ ፍጥረቱ እንደሆነ፣ መንፈስ ቅዱስ ደግሞ ለወልድ የመጀመሪያ ፍጥረቱ ነው›› ይል ነበር፡፡

ይህን የአርዮስን ክሕደት የሰማው የእስክንድርያ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ (ፓትርያርክ) ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ አርዮስን አስጠርቶ የሚያስተምረው ትምህርት ሁሉ የተሳሳተ መሆኑን ገልጾለት ከስሕተቱ ተመልሶና ተጸጽቶ ከቅዱሳን አበው ሲተላለፍ በመጣው በኦርቶዶክስ እምነት እንዲጸና መከረው፡፡ አርዮስ ግን ከአባቱ ከተፍጻሜተ ሰማዕት ጴጥሮስ የተሰጠውን ምክር ወደ ጎን በመተው የክሕደት ትምህርቱን በሰፊው ማስተማር ቀጠለ፡፡ ይህንን የተመለከተ ያ ደግ አባት አርዮስን አውግዞ ከዲቁና ማዕረጉ ሻረው፡፡ የግብጽ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት እንደሚለው፣ ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ አርዮስን ያወገዘው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በራእይ ተገልጦለት በሰጠው ትእዛዝ መሠረት ነው፡፡

በአንድ ሌሊት በራእይ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በአንድ ወጣት አምሳል እንደ ፀሓይ የሚያበራ ረጅም ነጭ ልብስ (ቀሚስ) ለብሶ ለቅዱስ ጴጥሮስ ይታየዋል፡፡ ልብሱ ለሁለት የተቀደደ ሆኖ ቢያየው ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ደንግጦ ጌታን ‹‹መኑ ሰጠጣ ለልብስከልብስህን ማን ቀደደብህ?›› ብሎ ይጠይቀዋል፡፡ ጌታም ‹‹አርዮስ ልብሴን ቀደደብኝ›› ብሎ መለሰለት፡፡ ይኸውም በአባቶች ትርጕም ‹‹አርዮስ ከባሕርይ አባቴ ከአብ ለየኝ (አሳነሰኝ)›› ማለት ነው፡፡ ጌታም አርዮስን ከእንግዲህ ወዲያ ወደ ቤተ ክርስቲያን አንድነት እንዳይቀበለው አዝዞት ተሰወረ፡፡ ተፍጻሜተ ሰማዕት ጴጥሮስ ራእዩን ያየው በዲዮቅልጥያኖስ ስደት ጊዜ ተይዞ ለመገደል በእስር ቤት በነበረበት ወቅት ነበር፡፡ አርዮስም ቅዱስ ጴጥሮስ እንደሚገደል አውቆ ከውግዘቱ ሳይፈታው እንዳይሞት ከውግዘቱ እንዲፈታው አማላጆች ይልክበታል፡፡ ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ ግን አርዮስን ‹‹በሰማይና በምድር የተወገዘ ይሁን!›› በማለት ውግዘቱን አጸናበት፡፡ በዚያኑ ቀን ተማሪዎቹን አርኬላዎስን እና እለእስክንድሮስን አስጠርቶ ያየውን ራእይ በመግለጥ አርዮስን እንዳይቀበሉትና ከእርሱም ጋር ኅብረት እንዳይኖራቸው አዘዛቸው፡፡

ይቆየን