ማቴዎስ ወንጌል
ሐምሌ 28 ቀን 2006 ዓ.ም.
ምዕራፍ 7 ካለፈው የቀጠለ
ሠ. ሰፊ ደጅ የተባለች ባለጸጋን መጽውት ድኃን ጹም ማለት ነው፡፡
ሰፊ ደጅ የተባለች ፈቃደ ሥጋ ናት ወደ ሰፊው ደጅ የሚገቡ ብዙዎች ወደ ጠባቧ ደጅ የሚገቡ ደግሞ ጥቂቶች መሆናቸው ጌታን አያስቀናውም፡፡ ምክንያቱም ጥቂት ዕንቁ ያለው ደግሞ ብዙ ወርቅ ባለው፤ ጥቂት ወርቅ ያለው ብዙ ብር ባለው፤ ጥቂት ብር ያለው ብዙ ብረት ባለው፤ ጥቂት ብረት ያለው ብዙ ሸክላ ባለው አይቀናም፡፡
6. ስለ ሐሰተኞች ነቢያት
የበግ ለምድ ለብሰው ይመጣሉ የተባሉት ነጣቂ ተኩላዎች መንፈሳውያን መስለው የሚመጡ ሥጋውያን፤ ሃይማኖታውያን መስለው የሚመጡ መናፍቃን ናቸው፡፡ ጌታችን “በውስጣቸው ግን ነጣቂዎች ተኩላዎች ናቸው፡፡” ማለቱ ቢመረምሯቸው ሰውን ከመንጋው/ ከማኅበረ ምእመናን/ መካከል እየነጠቁ ወደ ገሃነም የሚያወርዱ መሆናቸውን ሲያጠይቅ ነው፡፡ እነዚህም ወይንና በለስ የማይገኝባቸው እሾሆችና ኩርንችቶች በመሆናቸው ከፍሬያቸው እንደሚታወቁ ተናግሯል፡፡ ይህም “ሥራቸውን አንሠራም ትምህርታቸውን ግን ብንማር ምን ዕዳ ይሆናል? ትሉኝ እንደሆነ ከመናፍቅ መምህር ሃይማኖት፣ ከሐሰተኛ መምህር እውነተኛ ትምህርት ቃል አይገኝም ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ወይን ወይንን ኮሶ ደግሞ ኮሶን ያፈራል እንጂ ወይን ኮሶን፣ ኮሶ ደግሞ ወይንን አያፈራም፡፡ መልካም ፍሬ የማያደርግ ዛፍ ተቆርጦ ወደ እሳት እንዲጣል መናፍቃንንም ሥላሴ በገሃነም እሳት ፍዳ ያጸኑባቸዋል፡፡
ጌታችን ከዚህ አያይዞ “ሁሉ ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ ይሉሃል፤ ታዲያ ወደ መንግሥትህ የሚገባውንና የማይገባውን በምን እናውቃለን? ትሉኝ እንደሆነ የሰማይ አባቴን ፈቃድ የሠራ ይገባል እንጂ ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ የሚለኝ ሁሉ ወደ መንግሥተ ሰማያት አይገባም፡፡ በዚያን ጊዜም ከቶ አላውቃችሁም፤ እናንተ ዓመፀኞች ከእኔ ራቁ ብዬ እመሰክርባቸዋለሁ” ብሏል፡፡ ትንቢት መናገርማ በለዓምም ትንቢት ተናግሯል፡፡ ዘኁ.20፡4፣17፡፡ አጋንንትን ለማውጣት ደቂቀ አስቄዋ አጋንንትን አውጥተዋል የሐዋ.19፡14፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ስለእነዚህ ሰዎች ሲናገር “እንደ እነዚህ ያሉ ሰዎች የክርስቶስን ሐዋርያት እንዲመስሉ ራሳቸውን እየለወጡ ውሸተኞች ሐዋርያትና ተንኰለኞች ሠራተኞች ናቸውና፡፡
ይህም ድንቅ አይደለም፤ ሰይጣን ራሱ የብርሃንን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣልና፡፡ እንግዲህ አገልጋዮቹ ደግሞ የጸድቅን አገልጋዮች እንዲመስሉ ራሳቸውን ቢለውጡ ታላቅ ነገር አይደለም፤ ፍጻሜአቸውም እንደ ሥራቸው ይሆናል፡፡” ሲል አስጠንቅቋል 2ኛ ቆሮ.11፡13-15፡፡ በኦሪቱም “በመካከልህም ነቢይ ወይም ሕልም አላሚ ቢነሣ ምልክትም ተአምራትም ቢሰጥህ እንደነገረህም ምልክቱ ተአምራቱም ቢፈጸም እርሱም ሄደን የማታውቃቸውን ሌሎች አማልክት እንከተል እናምልካቸውም ቢልህ፣ አምላካችሁን እግዚአብሔርን በፍጹም ልባችሁ በፍቡጸምም ነፍሳችሁ ትወድዱት እንደሆነ አምላካችሁ እግዚአብሔር ሊፈትናችሁ ነውና የዚያን ነቢይ ቃል ወይም ያን ሕልም አላሚ አትስሙ” ተብሏል ዘዳ.13፡1-3፡፡
7. በዓለት ላይ ስለተመሠረተውና በአሸዋ ላይ ስለተሠራው ቤት፡፡
ጌታችን በዚህ በመጨረሻው አንቀጽ ላይ ቃሉን ሰምቶ እንደ ቃሉ የሚኖረውን ልባም ሰው በዓለት ላይ በተመሠረተ ቤት መስሎታል፡፡ በዓለት ላይ የተመሠረተውም ቤት ዝናብ ወርዶ በጐርፍ፣ ነፋስ ነፍሶ በነፋስ ተገፈቶ አልወደቀም ብሏል፡-
ዓለት ለኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወልድ ዋሕድ ብለው ለሚታመንበት ሁሉ መንፈሳዊ መጠን የሚገኝበትና መንፈሳዊ መሠረት የሚቆምበት ዓለት ነው 1ኛ.ቆሮ.10፡4፡፡ ለማያምኑት ግን የማሰናከያ ዓለት ተብሎአል ኢሳ.8፡14፣ 1ኛ.ጴጥ.2፡8፡፡ ጌታችን ቅዱስ ጴጥሮስንም ዓለት ነህ ብሎታል ማቴ.16፡16-18፡፡ ዝናም ነፋስ የባለ መከራ ነው፡፡
ከምሳሌው የምንረዳው ዋነኛው ምሥጢር እንደሚከተለው ነው፡፡
-
ሃይማኖትን በበጎ ልቡና ይዘው እንደ ቃሉ የሚኖሩ ሰዎች ዓላውያን መኳንንት መከራ ቢያጸኑባቸው፣ ቤተሰቦቻቸውም ንጉሥ የወደደውን ዘመን የወለደውን ይዛችሁ ኑሩ ብለው ቢገፋፏቸው ምንም ይሁን ምን በክህደት አይወድቁም፡፡ እነዚህ ሃይማኖታቸውንና ምግባራቸውን እንደ ኢዮብ ባለ ሰውነት ይዘው የሚኖሩ ሰዎች የልጅ ሞት፣ የሀብት ውድመት እና የአልጋ ቁራኛ የሚያደርግ ደዌ ቢያጋጥማቸውም በምስጋና ይኖራሉ እንጂ ሃይማኖታቸውን አይለውጡም፡፡
-
ሃይማኖትን በበጎ ልቡና ይዘው እንደቃሉ የሚኖሩ ሰዎች በምክረ ካህን በፈቃደ ካህን ስለሚኖሩ አጋንንት በጎ አስመስለው ገፋፍተው ከክፉ ወጥመድ አይጥሏቸውም፡፡ እንዲህ ዓይነቶቹን ሰዎች አጋንንት በአሳብ ይዋጓቸዋል፡፡ እነዚህ ሰዎች እንደ እንጦንስ እንደ መቃርስ ንጽሕ ጠብቀን ከሴት ርቀን እንኖራለን የሚል አሳብ ሲመጣባቸው ቸኩለው አይወስኑም፡፡ ፈጥነው ለመምህረ ንስሐቸው ይነግራሉ፡፡ እነርሱም ቆዩ ይሏቸዋል፡፡ ደግሞም እንደ እንጦንስ እንደ መቃርስ ንጽሕ ጠብቀን ከሴት ርቀን መኖር አይቻለንም፤ እንደ ኢዮብ እንደ አብርሃም በሕግ ጸንተን እንኖራለን የሚል አሳብም ሲመጣባቸው ለመምህረ ንስሐቸው ይነግሩታል፡፡ እርሱም የሰይጣን ፆር እንደሆነ ዐውቆ ቆዩ ይላቸዋል፡፡ በመጨረሻም አጋንንት ሁሉም አይሆንልንም አሰኝተው ሃይማኖቱን ለማስለቀቅ ይገፋፏቸዋል፡፡ ይሁን እንጂ እነዚህ ሰዎች በምክረ ካህን በፈቃደ ካህን በእግዚአብሔር ቃል ላይ ተመሥርተው ስለሚኖሩ አይወድቁም፡፡
ጌታችን ቃሉን ሰምቶ እንደቃሉ የማይኖረውን ሰው ደግሞ በአሸዋ ላይ በተሠራ ቤት መስሎታል፡፡ ይህንንም ቤት ጐርፍ ነፋስ በገፉት ጊዜ አወዳደቁ የከፋ ሆኗል፡፡ እነዚህም ሃይማኖታቸውን በበጎ ልቡና ያልያዙ ሰዎች ናቸው፡፡ እንደ ቃሉ ይኖሩ መከራውን ተሰቅቀውና በወሬ ተፈትነው በክህደት ይወድቃሉ፡፡ ለጊዜው በጌታ ዐፀደ ወይን በቤተ ክርስቲያን ቢበቅሉም ፀሐይ ሲወጣ ግን ይጠወልጋሉ ማቴ.13፡5-6፣20፡፡
ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህን አስተምህሮ ከፈጸመ በኋላ ሕዝቡ ትምህርቱን አደነቁ፡፡ ምክንያቱም እንደ ጻፎቻቸው ሳይሆን እንደ ባለሥልጣን ያስተምራቸው ነበረ፡፡ ይህም ማለት ንጉሥ እንዲህ ይላችኋል እንደሚሉ ሹማምንት ያይደለ እኔስ እላችኋለሁ እያለ አስተምሯቸዋልና ነው፡፡
“ከመዝ ይቤ እግዚአብሔር” እንደሚሉ ዐበይት ነቢያት ያይደለ ሠራዔ ሕግ እንደ መሆኑ እኔስ አላችኋለሁ እያለ አስተምሯቸዋል፡፡ “ከመዝ ይቤ ሙሴ፤ ከመዝ ይቤ ሳሙኤል፣” እንደሚሉ ደቂቀ ነቢያት ያይደለ ፈጻሜ ሕግ እንደመሆኑ አስተምሯቸዋል፡፡
“ከባድና አስቸጋሪ ሸክም ተብትበው በሰው ትከሻ ይጭናሉ እነርሱ ግን በጣታቸው ስንኳ ሊነኩት አይወዱም፡፡” እንዳላቸው ጸሐፍት ፈሪሳውያን ያይደለ እንደ ጌትነቱ በርኅራኄ አስተምሯቸዋል፡፡ ከወርቁ የጠራውን፣ ከግምጃ ያማረውን፣ ከላሙ የሰባውን እንደሚሉ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ያይደለ የቸርነቱን ሥራ እየሠራ አስተምሯቸዋል፡፡
የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን አሜን፡፡
ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 4ኛ ዓመት ሰኔ 1989 ዓ.ም.


ማኅበረ ቅዱሳን በ2006 ዓ.ም. ከዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ግቢ ጉባኤያት በርካታ ተማሪዎችን አስመርቋል፡፡ በዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ቆይታቸው ያስመዘገቡት ውጤት ከፍተኛ በመሆኑም በርካቶች የተሸለሙትን ዋንጫና ሜዳልያ በሥጦታ ለማኅበሩ በማበርከት ላይ ይገኛሉ፡፡
ደስታ ሲገልጹ “ይህ ውጤት በሀገራችን በሚገኙ ዩኒቨርስቲዎች ታሪክ በጥቂቶች ብቻ ሊመዘገብ የሚችል ከፍተኛ ውጤት ነው፡፡ ካስመዘገበው ውጤት ይልቅ ደግሞ ታማኝ አገልጋይ ሆኖ በሕይወቱ አንድ ጊዜ ብቻ ሊገጥመው የሚችለውን እድል ውድ ሥጦታ ለማኅበሩ መሥጠቱ አስደንቆኛል፡፡ ብዙዎቻችንንም ያስተማረ ነው፡፡ ወደፊትም በሕይወቱ የተሳካ ጊዜ አሳልፎ ለሌሎች አርአያ እንዲሆን እመኛለሁ” ብለዋል፡፡
ማእከል የፈቃደ እግዚእ ኮሌጅ ተመራቂዎቹ ዘውዴ ደሴና ከፍያለው ስመኝ ለማኅበሩ ማእከላት ሜዳልያቸውን አስረክበዋል፡፡ እንዲሁም ከሐረር የሜንሽን አግሮ ቴክኒካል ኮሌጅ ግቢ ጉባኤ ሰብሳቢ የሆነው ቃል ኪዳን ዓለሙ ሜዳልያውን በማእከሉ በኩል ለኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን እንዲሰጥለት አበርክቷል፡፡
የማኅበረ ቅዱሳን 11ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ ነሐሴ 24 እና 25 ቀን 2006 ዓ.ም. በማኅበሩ ሕንፃ መሰብሰቢያ አዳራሽ የሀገር ውስጥና የውጭ ማእከላት፤ የወረዳ ማእከላትና ግንኙነት ጣቢያዎች፤ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያት ተወካዮች፤ የማኅበሩ ሥራ አመራርና ሥራ አሥፈፃሚ አባላት፤ የማኅበሩ ልዩ ልዩ ክፍል ተጠሪዎች፤ ጥሪ የተደረገላቸው ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት አካሄደ፡፡
የጠቅላላ ጉባኤው ተሳታፈዎች ከነሐሴ 23 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ የእንኳን ደህና መጣችሁ አቀባበል የተደረገላቸው ሲሆን፤ የጸሎት፤ የመርሐ ግብር ትውውቅና ማስገንዘቢያ በጠቅላላ ጉባኤው አዘጋጅ አብይ ኮሚቴ ሰብሳቢ በዶክተር ዳኝነት ይመኑ ቀርቧል፡፡ የእጽበተ እግር መርሐ ግብርም ተከናውኗል፡፡
አገልግሎት ፤ የአብነት ትምህርት ቤቶችና ገዳማትን በማጠናከር ረገድ፤ የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ አገልግሎት ለማጠናከር ከአህጉረ ስብከቶች ጋር እየተሠሩ ስለሚገኙ በርካታ ተግባራት ፤ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያትን በማጠናከር ረገድ፤ የማኅበሩን ተቋማዊ አቅም ለማሳደግ እየተሠሩና በመሠራት ላይ የሚገኙ ሥራዎች፤ ያጋጠሙ ችግሮችና የተወሰዱ መፍትሔዎችን በዝርዝር አቅርበዋል፡፡
ጠቅላላ ጉባኤው በሁለተኛ ቀን ውሎው ብፁዕ አቡነ ሰላማ የምሥራቅ ሐረርጌ ሊቀ ጳጳስ የተገኙ ሲሆን፤ በሰጡት ቃለ ምእዳን “ያሰባሰባችሁ እግዚአብሔር ነው፤ በእናንተ ኃይል አልተሰባሰባችሁም፡፡ ፈቃደ እግዚአብሔር አስነስቷችኋልና በጉዟችሁ ፈተና ሊገጥማችሁ ይችላል፡፡ ፈተና ደግሞ ያለ ነው፤ ይጠቅማል እንጂ አይጎዳም፡፡ ከሚወድህ ይልቅ የሚጠላህ ይጠቅምሃል እንዲሉ አባቶቻችን ካልተፈተኑ ክብር አይገኝም፡፡ በአገልግሎታችሁ እንደጸናችሁ ሳትበሳጩ ልትጓዙ ያስፈልጋል፡፡ እግዚአብሔር ማኅበሩን ይባርክ” ብለዋል፡፡
የማኅበረ ቅዱሳን ስልታዊ እቅድ አጋማሽ ዘመን ግምገማ በማስመልከት ከጥር 2005 ዓ.ም. እስከ ግንቦት 2006 ዓ.ም. የተከናወኑትን ሥራዎች ተገምግመው ሓላፊነት በወሰደው አጥኒ ቡድን ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርበዋል፡፡ ጠቅላላ ጉባኤውም ውይይት በማድረግ አቅጣጫ ሰጥቷል፡፡ በዚህም መሠረት ቀጣይ አፈጻጸማችን ምን መምሰል እንደሚገባው ለማሳየት ቢሞከር፤ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ከስትራቴጂክ እቅዱ አንጻር አስታርቆ ማስኬድ፤ የክብደት አሥራር ሥርዓቱን ግልጽ ማድረግ፤ ግምገማው ከስልታዊ እቅዱ ጋር በደንብ ቢታይ የሚሉና ሌሎችም ጠቃሚ ነጥቦች ከተካተቱት ውስጥ ይገኙበታል፡፡ የጥናት ቡድኑ ከጠቅላላ ጉባኤው በተሰጡት ሃሳቦች መሠረት የግምገማውን ውጤት በአጭር ጊዜ ውስጥ ለመደበኛ ሥራ አመራር ጉባኤ እንዲያቀርብ፤ ሥራ አመራር ጉባኤውም አጽድቆ በሚመለከታቸው አካላት ተግባራዊ እንዲደረግ እንዲያስተላልፍ ውሳኔ ላይ ተደርሷል፡፡




በማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል ሐምሌ 26 እና 27 2006 ዓ.ም በጀርመን ካስል ደብረ ቀራንዮ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ያሉበትን ሁኔታ፣ የማኅበረ ቅዱሳንን ታሪክ፣ አገልግሎትና በየጊዜው ያጋጠሙትን ችግሮች እንዲሁም የቤተክርስቲያን አገልግሎት በአውሮፓ በተለይም በጀርመን ያለበትን ሁኔታ፣ የአመሠራረት ታሪከ እና መንፈሳዊ እንቅስቃሴ የሚያስቃኝ ዐውደ ርእይ ተካሔደ።
ዐውደ ርእዩ ነሐሴ 3 እና 4 ቀን 2006 ዓ.ም በኮሎኝ ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ላይ በአጥቢያው ሰበካ ጉባኤና በሊቀ ካህናት ዶ/ር መርዓዊ ተበጀ በጀርመን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሓላፊ ፈቃድ ለምእመናን ለመታየት በቅቷል። ዐውደ ርእዩን የከፈቱት ሊቀ ካህናት ዶ/ር መርዓዊ ተበጀ ሲሆኑ በዕለቱ የቀረበው ዐውደ ርእይ ጥንታዊ ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ያሉበትን ሁኔታ ምእመናን እንዲረዱት የሚያደርግ በመሆኑ ማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእዩን በዚህ ቤተክርስቲያን ማካሔዱ ያስደሰታቸው መሆኑን ተናግረዋል። በመቀጠልም የድጓ እና የአቋቋም መምህር የሆኑት እና ከካርል ስሩህ አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተክርስቲያን የመጡት ሊቀ ጠበብት ተክሌ ሲራክ ስለአብነት ትምህርት ቤቶች ሥርዓተ ትምህርት እና በአሁኑ ወቀት ተማሪዎች ስላሉባቸው ቸግሮች ሰፊ ገለጻ አድርገዋል፡፡ ችግሮቹን ለመፍታት አባቶች፣ ምእመናንና ማኅበራት ሊያደርጓቸው ይገባል ያሏቸውን የመፍትሔ ሐሳቦች ጠቁመዋል::
በማኅበረ ቅዳሳን ሐዋሳ ማዕከል በተለያዩ አምስት ቋንቋዎች የሚያስተምሩ 33 ሰባኪያነ ወንጌል በሐዋሳ ካህናት ማሠልጠኛ ለአንድ ወር በቀንና በማታ ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ትምህርቶችን እና ሥልጠናዎችን ሲከታተሉ ቆይተው ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የሲዳማ፣ የጌዲኦ፣ የአማሮና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በተገኙበት ሐምሌ 27 ቀን 2006 ዓ.ም በሐዋሳ ደብረ ምጥማቅ መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን በድምቀት አስመረቀ፡፡
ተመራቂ ሰልጣኞቹ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ባልተስፋፋባቸው የገጠር አብያተ ክርስቲያናት መካከል ከሲዳማ፣ ከጌዲኦ፣ ከአማሮና ከቡርጂ ሀገረ ስብከት የተውጣጡ ሲሆን፤ በሲዳምኛ፤ በጌዲኦኛ፤በኩየርኛ፤በቡርጂኛና በኦሮምኛ ቋንቋዎች የሚያገለግሉ ናቸው፡፡ በአንድ ወር ቆይታቸውም ከሚሰጣቸው መንፈሳዊ ትምህርት በተጨማሪ በስብከት ዘዴ ላይ ያተኮረ የልምምድ ልውውጥ አድርገዋል፡፡
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን የአዳማ ማእከል ለሚያስገነባው የአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የአጸደ ሕፃናትና የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሣልሳይ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የበላይ ሓላፊ ሐምሌ 27 ቀን 2006 ዓ.ም. የመሠረት ድንጋይ አኖሩ፡፡
በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሣልሳይ መሪነት፤ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች፤ የናዝሬት ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ካህናትና አገልጋዮች፤ የማእከሉ አባላትና ጥሪ የተደረገላቸው ምእመናን በተገኙበት ጸሎተ ወንጌል በማድረስ ብፁዕነታቸው የመሠረት ድንጋይ ባኖሩበት ወቅት በሰጡት ቃለ ምእዳን “ከሁሉም ነገር በፊት የሰው ሀብት ዕውቀት ነው፡፡ ዕውቀት ደግሞ የማይሠረቅ ሀብት በመሆኑ የማይሠረቀውን፤ የማይዘረፈውን ሀብተ እግዚአብሔርን መያዝ መልካም ነው፤ የመሠረት ድንጋይ የምናኖረውም ድንቁርናን ለማጥፋት ነው” ብለዋል፡፡
ቀሲስ እሸቱ ታደሰ የማኅበሩን መልእክት ሲያስተላልፉ “ማኅበረ ቅዱሳን የተማረ ትውልድን ለመቅረጽ፤ ትምህርት ለማስፋፋት እንደ አንድ ዓላማ አድርጎ በመያዝ በየአኅጉረ ስብከቱ ዐሥር ትምህርት ቤቶችን በመክፈት ቤተ ክርስቲያንን የሚያውቅና በዕውቀት የበለጸገ ትውልድ ለማፍራት በመሥራት ላይ ነው፡፡ የአዳማ ማእከል ከ2004 ዓ.ም. ጀምሮ ቤት ተከራይቶ የዐፀደ ሕፃናትና የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በመክፈት አገልግሎት እየሠጠ ቢሆንም፤ የተማሪዎቹ ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተበራከተ በመምጣቱ ሰፋ ያለ ቦታ ማግኘት አማራጭ የሌለው ጉዳይ ሆነ፡፡ በዚህም መሠረት የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስን በማስፈቀድ በአንድ ሚሊዮን ብር ከአባላት በማሰባሰብ በአዳማ ከተማ መሬት በመግዛት በዛሬው እለት በብፁዕነታቸው የመሠረት ድንጋይ ለማኖር በቅተናል” ብለዋል፡፡

በዚህም መሠረት በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት /ለሐይቅ እስጠፋኖስ አቡነ ኢየሱስ ሞዓ አንድነት ገዳም፤ ለቦሩ ደብረ ብርሃን ሥላሴ፤ ለከሚሴ ደብረ ገነት ቅዱስ ገብርኤል አብያተ ክርስቲያናት/፤ በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት /ለመርሳ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን፤ ለራማ ደብረ ሲና ኪዳነ ምሕረት አንድነት ገዳም/፤ በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት /ለደብረ ብርሃን ሥላሴ፤ ለአቡን ቤት ቅዱስ ገብርኤል፤ ለአበራ ቅዱስ ጊዮርጊስ፤ ለመንበረ መንግስት መድኃኔዓለም፤ ለግምጃ ቤት ቅድስት ማርያም አብያተ ክርስቲያናት/ ውስጥ ለሚገኙ የአብነት ትምህርት ተማሪዎች የአልባሳትና የሳሙና ድጋፍ ተደርጎላቸዋል፡፡
አንድነት ገዳም ከሚገኙ የቅዳሴ ተማሪዎች አንዱ ይገልጻል፡፡