ቅዱስ ፓትርያርኩ የአዲስ ዓመት የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት አስተላለፉ
ጳጉሜን 4 ቀን 2006 ዓ.ም.
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ለ2007 ዓ.ም. አዲስ ዓመት እንኳን አደረሳችሁ መልእክት አስተላለፉ፡፡
የመግለጫውን ሙሉ ቃል አቅርበነዋል፡፡
ጳጉሜን 4 ቀን 2006 ዓ.ም.
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ለ2007 ዓ.ም. አዲስ ዓመት እንኳን አደረሳችሁ መልእክት አስተላለፉ፡፡
የመግለጫውን ሙሉ ቃል አቅርበነዋል፡፡
ጳጉሜን 3 ቀን 2006 ዓ.ም.
እንዳለ ደምስስ
በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል የተዘጋጀው 6ኛው ሀገር ዓቀፍ ዐውደ ጥናት ጳጉሜን 1 ቀን 2006 ዓ.ም. በማኅበሩ ሕንፃ መሰብሰቢያ አዳራሽ ተካሔደ፡፡
ለአንድ ቀን በተዘጋጀው ዐውደ ጥናት 6 በምርምር ማእከሉ የተመረጡ ጥናቶች ቀርበዋል፡፡ በዚህም መሠረት በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት በመቄት ወረዳ የደብረ ገነት ናዙኝ ማርያምና የአቡነ አሮን መንክራዊ ፍልፍል አብያተ ክርስቲያናት ታሪክ፤ ኪነ ሕንፃ፤ ተንቀሳቃሽ ቅርስና ያሉበት ሁኔታ በሚል ርዕስ በዲያቆን ፀጋዬ እባበይ በዲላ ዩኒቨርስቲ የአርኪዮሎጂ መምህር የመጀመሪያውን ጥናት አቅርበዋል፡፡
የደብረ ገነት ናዙኝ ማርያምና የአቡነ አሮን መንክራዊ ገዳማት የተረሱ ፍልፍል አብያተ ክርስቲያናት መሆናቸውን የገለጹት ጥናት አቅራቢው፤ ፍልፍል አብያተ ክርስቲያናቱ በከፍተኛ ጉዳት በአደጋ ውስጥ እንደሚገኙና በጥናት ላይ የተደገፈ ጥገና እንደሚያስፈልጋቸው ተናግረዋል፡፡
ናዙኝ ማርያም ሁለተኛው የኢትዮጵያ ጳጳስ የነበሩት አቡነ ሙሴ በ4ኛው መቶ ክፍለ ዘመን እንዳነጿት አብራርተው፤ ቤተ ክርስቲያኗ ለአክሱማውያን ውቅር አብያተ ክርስቲያናት መሠረት፤ አለበለዚያም ለኋለኞቹ ድልድይ እንደሆነች በጥናታቸው ዳስሰዋል፡፡በመቄት ወረዳ ብቻ ከ19 በላይ ፍልፍል አብያተ ክርስቲያናት ሲገኙ 13ቱ በአቡነ ሙሴ፤ ሁለቱ ደግሞ በአቡነ አሮን እንደታነጹ ገልጸዋል፡፡
ሁለተኛው ጥናት ሥነ ምኅዳርን ያማከለ የአካባቢ ጥበቃ እቅድ የደብረ ሊባኖስ ገዳም ደን የሥነ ምኅዳር አገልግሎት ለማሳደግ በሚል ርዕስ በመስፍን ሳህሉ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የአካባቢ ጥናት ተማሪ የቀረበ ሲሆን፤ የደብረ ሊባኖስን ገዳም ደን የሥነ ምኅዳር አገልግሎት ለማሳደግ በርካታ ሥራዎች መሠራት እንደሚገባቸው በጥናት አቅራቢው ተገልጿል፡፡ ቀድሞ የነበረው ተፈጥሯዊ ደን መመናመን፣ በተለያዩ ምክንያቶች መሬቱ እየተራቆተ መምጣቱ፤ የአፈሩ መሸርሸር፣ ለጐርፍ አደጋ ገዳሙ መጋለጡንና የአካባቢው የአየር ጸባይ መለዋወጥ ገዳሙን ለከፍተኛ አደጋ እንዳጋለጠው ጠቅሰዋል፡፡
በዲያቆን ሔኖክ ሐይሉ /MA/ ከማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል የቀረበው 3ኛው ጥናት የተቀናጀ ሃይማኖታዊ እና የምክክር /counseling/ መርህ የካህናትን የማማከር ክሂል በማሳደግ ረገድ ያለው ውጤታማነት ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አንጻር በሚል ርዕስ ላይ ትኩረት ያደረገ የምክክር ባለሙያዎች ማሰልጠኛ ቢጋር አዘጋጅተው አቅርበዋል፡፡
የንስሐ አባቶች ከንስሐ ልጆቻቸው ጋር ያላቸውን ግንኙነት ለማጠናከር ዘመኑን የዋጀ ዘመናዊ የሥነ ልቦና የማማከር አገልግሎት ሥልጠና ቢወስዱ ውጤታማ የቤተ ክርስቢተያንን አገልግሎት ለመተግበር እንደሚረዳቸው ጠቁመዋል፡፡ የንስሃ ልጆቻቸው ኃጢአታቸውን ተናዝዘው፤ ንስሃ ገብተው፣ ቀኖናቸውን ተቀብለው ወደ ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ የመቅረብ ሂደት እንደተጠበቀ ሆኖ፤ በጓደኝነት፤ በትዳር፣ እንዲሁም በማኅበራዊ ሕይወት ውስጥ ለሚገጥማቸው መሰናክል የንስሐ አባቶች የሥነ ልቦና የማማከር አገልግሎት ላይ እውቀት ኖሯቸው ከልጆቻቸው ምክክር ቢያደርጉ አገልግሎቱን የተሟላ ሊያደርገው እንደሚችል በጥናቱ ተጠቁሟል፡፡
በሦስቱም ጥናቶች ላይ ከተጋባዥ የቤተ ክርስቲያን አባቶች፣ ምሁራንና ከተሳታፊዎች ጥያቄና አስተያየት ቀርቦ ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡
ከሰዓት በኋላ በቀጠለው ዐውደ ጥናት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የብራና መጻሕፍት ይዞታቸው፤ ያካተቷቸው ምሥጢራትና ከባሕር ማዶ ስለሚገኙት መጻሕፍት በሚል ርእስ መጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የሐዲስ ኪዳን ትርጓሜ መምህር ጥናታቻውን አቅርበዋል፡፡
ቤተ ክርስቲያናችን ካሏት በብዙ ሺህ ከሚቆጠሩ አስደናቂ የብራና መጻሕፍት መካከል ቀዳሚዎቹ የዓለም የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ሊቃውንት ለምስክርነት የሚጠቀሙባቸው ረጅም ዘመናትን ያስቆጠሩ የብሉይ፤ የሐዲስ ኪዳን፣ የጸዋትወ ዜማ፣ የጸሎትና የምስጋና መጻሕፍት፣ መጻሕፍተ ሊቃውንት እና የሃይማኖት መጻሕፍት፣ መጻሕፍተ መነኮሳትና ሌሎችም መጻሕፍት በተለያዩ ምክንያቶች ከሀገር ወጥተው በውጭ ሀገራት እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡
በተለያዩ ዓለማት ያሉ ተመራማሪዎች እነዚህ ሁሉ ጥበባት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንዳሉ በማወቃቸው መጻሕፍቱን በተለያዩ አጋጣሚዎች ከሀገራችን እንዲወጡ አድርገዋል፡፡ እንደ ምሳሌም ጀምስ ብሩስ /ከ1768-1773/ መጽሐፈ ሔኖክን እና በርካታ መጻሕፍትን ይዘው እንደወጡ በጥናቱ ተጠቅሷል፡፡
በዚህም መሠረት በቫቲካን ቤተ መጻሕፍት 1082፣ በእንግሊዝ 850፣ በጀርመን 734፣ በጣሊያን 550 ወዘተ የብራና መጻሕፍት እንደሚገኙ በጥናታቸው አካትተዋል፡፡
በዶ/ር አምሳሉ ተፈራ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፊሎሎጂ ትምህርት ክፍል ሓላፊ የቀረበው ጥናት የአማርኛ ሥርዓተ ጽሕፈት በቤተ ክህነት ሊቃውንት እይታ በሚል ርዕስ ሲሆን፤ እንደ ኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት የፊደላት ምንጫቸው ከፈጣሪ የተገኘ፣ ለሄኖስ በሰማይ ሰሌዳ ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ የተገለጸና፤ የግዕዝ ፊደላት ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በሥራ ላይ መዋላቸውን ገልጸዋል፡፡ አማርኛን በተመለከተም ከግዕዙ የወሰዳቸው 26 አናባቢዎች እንዳሉ ሆነው፤ በኋላ 7 ከዚያም /ቨ/ን በመጨመር 34 እናት ፊደላት /consonants/፤ እንዲሁም 4 ደቃልው /labioverals/ /ኰ፣ጐ፣ቈ፣ኈ/ ፊደሎች አሉት:: 20 ፍንድቅ ፊደላትን /ሏ፣ ሟ፣ ሷ፣ ሯ…./ በመጨመር የአገልግሎት አድማሱን ማስፋቱን በጥናታቸው ጠቅሰዋል፡፡ በዚህም መሠረት 278 ድምጽ ወካይ ፊደላት /characters/ አሉት፡፡
ከፊደላት ጋር የሚከሰቱ ችግሮችን አስመልክቶም በአማርኛ ፊደል ገበታ ላይ ተመሳሳይ ድምጽ ያላቸው ስለሚገኙ፤ በአጻጻፍ ረገድ በርካታ ልዩነቶች መኖራቸው፤ ራብዕ ድምጸት ያላቸው ከግእዙ ጋር ተመሳሳይነት ያላቸው ፊደላት መኖራቸው፤ ሳድስና ሳልስን እያቀያየሩ መጠቀም፣ ደቃልውና ፍንድቅ ፈደላትን በዝርዝር የመጠቀም ዝንባሌ፣ በመሠረታዊ ቃሉ ላይ የሌለውን ቃል መጨመር፣ የአናባቢዎች ቅጥል አለመለየት ችግሩን ይበልጥ እንዳሰፋው ጠቁመዋል፡፡
ይህ ችግር በምሁራን ዘንድ ሞክሼ ቃላት ይቀነሱ፤ አይቀነሱ የሚለው ሐሳብ ዛሬም ድረስ እያከራከረ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡ አማራጮችንም በተመለከተ የኢትዮጵያ ቋንቋዎች አካዳሚ በ1973 ዓ.ም. ተመሳሳይ ድምጽ ያላቸው ፊደሎች ከገበታው ላይ ተቀንሰው በአንድ ፊደል ብቻ ይወከሉ የሚል ሲሆን፣ የቤተ ክህነት ሊቃውንት አቋም ደግሞ ፊደላት የፈጣሪን ቸርነት የሚገልጹ እና ከእሱ የተገኙ ስለሆኑ ሁሉም ጠንቅቆ ሊጽፋቸው ይገባል እንጂ በፍጹም ሊቀነሱ አይገባም፡፡ ፊደላቱ በሙሉ መንፈሳዊ፣ ተፈጥሯዊና ሙያዊ ትርጓሜ ስላላቸው ያንን ያጣሉ በማለት ይገልጻሉ፡፡
አማርኛ እንዴት ሥርዓተ ጽሕፈቱን ይጠብቅ የሚለውን እንደመፍትሔ ሲያቀርቡም የአማርኛ ሥርዓተ ጽሕፈት መጠበቅ ይገባዋል፡፡ ይህ ሊሆን የሚችለው ግን እየተጠቀምንበት የሚገኘውን የግዕዙን ሥርዓተ ሰዋሰውና የትውስት ቃላት እንዳሉ መጠበቅ ሲቻል ነው ብለዋል፡፡
የአማርኛ ፊደል የሚጽፍ ሁሉ ፊደላቱን እንዲጠነቀቅ ማስተማር፣ በባለሙያ የተሠናዱ የሥርወ ቃላት መዝገበ ቃላት እና የሰዋሰው መጻሕፍትን ማዘጋጀት፣ ያሉት ፊደላት እስካሁን ድረስ ሲጻፉ ኖረዋል በዚህም እጅግ በርካታ መጻሕፍትና የሥነ ጽሑፍ ውጤቶች ተመርተዋል፣ አገልግሎትም እየሰጡ ስለሚገኙ የፊደላቱ መብዛትና መመሳሰል አሳሳቢ እንዳልሆነና ሥርዓተ ጽሕፈቱን ከቅድመ ትምህርት ቤት ጀምሮ በየደረጃው ወጥነት ባለው መንገድ ማስተማር ወዘተ.. እንደመፍትሔ አቅርበዋል፡፡
የመጨረሻው ጥናት ክርስቲያናዊ ጾም በሰው ልጅ ጤና ላይ የሚያሳድረው ተጽእኖ ጾም ከተለያዩ ሃይማኖቶች አንጻር በሚል በዲያቆን ታደሰ አለሙ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ FDS እና የሥነ ምግብ የዶክትሬት ተማሪ ቀርቧል፡፡ በቀረቡ ጥናቶች ላይ በርካታ ሐሳቦችን በማንሳት ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡
በመጨረሻም የማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከሉ ከቤተ ክርስቲያናችን ሊቃውንትና ከተመራማሪ ምሁራን የሚቀርቡለትን ጥናቶች ጠቃሚነታቸውን መርምሮ ለውይይት ማቅረቡን እንደሚቀጥል፤ አቅሙ ያላቸው ተመራማሪዎች ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅሙ ምርምሮችንና ጥናቶችን እንዲያቀርቡ ማእከሉ እንደሚያበረታታ የማእከሉ ሰብሳቢ ዶ/ር አባተ መኩሪያው ገልጸዋል፡፡
ነሐሴ 30 ቀን 2006 ዓ.ም.
ዶ/ር አምሳሉ ተፈራ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ
የፊሎሎጂ ትምህርት ክፍል ሓላፊ
ቤተ ክርስቲያን በዓላውያን ነገሥታት አሰቃቂ ስደት በደረሰባት የመጀመሪያዎቹ ሦስት ምዕት ዓመታት ውስጥ ከተነሱት የቤተ ክርስቲያን አበው መካከል አንዱ የሆነውና ለዛሬው የተጋድሎውን ዜና በአጭሩ የምንመለከተው ሰማዕት ቅዱስ ሰራባሞን ዘኒቅዩስ ነው። አባቱ አብርሃም ይባላል፤ አያቱ የቀዳሜ ሰማዕት እስጢፋኖስ አጎት ሲሆን የተወለደው በ3ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በኢየሩሳሌም ነው። ሲወለድ ወላጆቹ “ስምዖን” ብለው ስም አወጡለት፤ “ሰራባሞን” የጵጵስና ስሙ ነው። የዐረብኛ እና የግዕዝ መጻሕፍት “ሰራባሞን” ሲሉት፣ የቅብጥና እንግሊዝኛ ምንጮች ደግሞ “ሰራፓሞን” ብለው ይጠሩታል።
በተወለደበት በኢየሩሳሌም ሳለ ክርስቲያን መሆን አጥብቆ ይፈልግ ነበር። እመቤታችን በራእይ ተገልጻ ወገኖቹ አይሁድ እንዳይገድሉት ወደ ግብፅ ሄዶ እንዲጠመቅና አገልግሎቱንም በዚያ እንዲፈጽም ስለነገረችው ቤተሰቦቹን ጥሎ መነነ። ግብፅ ሲደርስ እመቤታችን የእስክንድርያ 16ኛ ፓትርያርክ የነበረውን አቡነ ቴዎናስን (282-300) ባዘዘችው መሠረት አስተምሮ አጠመቀው። የቅዱሳት መጻሕፍትን ትርጓሜያት፣ የነቢያትንና ሐዋርያትን መጻሕፍት ተማረ፣ የአግናጥዮስ ምጥው ለአንበሳን እና የበልኪሮስን ድርሳናት በአጭር ጊዜ ውስጥ አጠና።
ከዚያም ከእስክንድርያ ከተማ ውጭ በሆነ እልሐብጡን በተባለ በአባ ሳዊሮስ ገዳም ውስጥ መነኮሰ። ከዘመናት በኋላ በተፍጻሜተ ሰማዕት ጴጥሮስ ዘመን (300-311) የኒቅዮስ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ዮሐንስ ሲያርፍ በእርሱ ምትክ የኒቅዮስ ሊቀ ጳጳስ ሆኖ ቤተ ክርስቲያንን መራ፤ ከገድሉ እንደምናነበው ወደ ተመደበበት ሀገረ ስብከት ሲገባ የተደረገለት አቀባበል የደመቀ ከመሆኑ የተነሣ ጌታ በሆሣዕና ወደ ኢየሩሳሌም ታጅቦ ሲገባ እንደተደረገለት የሚመስል ነበረ። በቅዱስ ሰራባሞን አገልግሎት በኒቅዮስና በአጎራባች ከተሞች የነበሩ ጣዖታት ተሰባብረው ወድቀዋል፤ በእጁ በርካታ ገቢረ ተአምራት ተደርገዋል፤ በመስቀሉ አጋንንትን አባሯል።
ይህ ቅዱስ አባት ስለ ወንጌል ብዙ መከራን ተቀብሏል፤ ከአጽራረ ቤተ ክርስቲያን መናፍቃን ብዙ ዘለፋ ደርሶበታል። አርዮስ፣ ሰባልዮስ እና ሚሊጦስ በእርሱ ዘመን የነበሩ መናፍቃን ናቸው። የአርዮስ ዋና ክህደት “ወልድ (ክርስቶስ) ፍጡር ነው” የሚል ሲሆን ሚሊጦስ ደግሞ “ከማርያም የተወለደው ክርስቶስ በምትሐት ነው እንጂ በእውነት አይደለም” የሚል ነበር። ሰባልዮስ “እግዚአብሔር አንድ ገጽ ነው” ብሎ የሚያስተምር ሲሆን፤ ሰራባሞን ሁሉንም ተከራክሮ ረቷቸዋል።
በዚህ የተነሣ በተደጋጋሚ ለእስር ተዳርጓል። አርዮስና ሚሊጦስ የሚያስተምረውን ባለመቀበላቸው በክፋታቸው ጸንተው ብዙዎችን እያሳቱ፣ በትዕቢታቸውም ልባቸውን እያኮሩ ቢያገኛቸው በኃይለ መንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ የአርዮስና ሚሊጦስን አንገታቸውን በመሐረብ ይዞ “እናንተ አባታችሁን ዲያብሎስን በክህደት የምትመስሉ እስከ መቼ ድረስ ነው በዚህ ክህደታችሁ ሰውን የምታጠፉ?” ብሎ ገስጿቸዋል (ገድለ ሰራባሞን፣ ቅጠል 130-137)። አርዮስ ከክሕደቱ የማይመለስ ከሆነ አንጀቱ ተበጣጥሶ እንደሚሞት፣ ሚሊጦስም ካልተመለሰ ሥጋውን በቁሙ ዕፄያት እንደሚበሉት ትንቢት ተናግሮባቸዋል። እምቢ በማለታቸው በሁለቱም ላይ ይኸው ተፈጽሞባቸዋል።
ንጉሠ ነገሥት ዲዮቅልጥያኖስ (284-305) የሚያፈርሳትን ቤተ ክርስቲያን ሰረባሞን ሲሰራ፣ ጣዖት የሚያመልኩትንም ሰዎች በክርስቶስ ስም ሲያሳምናቸው ንጉሡ እና መኳንንቱ ስጋት ጨመረባቸው። ሰራባሞን እንዲታሰር እና ስለ ክርስቶስ ፈጽሞ እንዳያስተምር በእስክንድርያው ገዢ አውጣኪያኖስ፡ ኮሞስ፡ ትዕዛዝ ተሰጠ።
ሰራባሞን ግን ከአቋሙ አልተናወጸም። ስለዚህ እስር ቤቱን አንዴ በታሕታይ ግብጽ አንዴ ደግሞ በላዕላይ ግብጽ በበረሃው ሁሉ በማፈራረቅ አሰቃዩት። እርሱ ግን ስቃዩንና ዛቻውን ከምንም ሳይቆጥር በእስር ቤት ውስጥም ወንጌልን በመስበክ ብዙዎችን አሳምኗል። የላዕላይ ግብፅ ገዢ የነበረው አርያኖስ (ከከሐዲው አርዮስ የተለየ እና የሀገረ እንጽና ገዢ የነበረ) ብዙ ካሠቃየው በኋላ በኒቅዩስ ከተማ ወደብ አቅራቢያ አንገቱን እንዲቆርጡት ትዕዛዝ ሰጠ። የሚጓዙበት መርከብ ግን አልንቀሳቀስም አለ። ቅዱስ ሰራባሞንን ከመርከቡ ሲያወርዱት በሰላም ሄዱ። በዚህ ሁኔታ እያለ እንኳን ወንጌልን መስበክና ትንቢት መናገርን አልተወም።
ይህ በእርሱ ላይ የሞት ውሳኔ የሰጠበት አርያኖስ በኋላ ዲዮቅልጥያኖስን ክዶ ክርስቲያን እንደሚሆን በመጨረሻም ሰማዕትነትን ተቀብሎ እንደሚሞት፣ እንዲሁም የእስክንድርያው ፓትርያርክ ቅዱስ ጴጥሮስም በሰማዕትነት እንደሚሞትና “ተፍጻሜተ ሰማዕት” እንደሚሆን እንዲህ ብሎ ተንብዮአል፥ “ወበከመ፡ ጴጥሮስ፡ ቀዳማየ፡ እምሐዋርያት፡ ከማሁ፡ አንተኒ፡ ትከውን፡ ተፍጻሜተ፡ ሰማዕት። ናሁ፡ አቅደምኩ፡ ነጊሮተከ፡ ዘይከውን፡ በጊዜሁ።” (ገድለ ሰራባሞን፣ ቅጠል 158)። እንደ ትንቢቱም ሁሉም ተፈጽሟል። በመጨረሻም ከሀገረ ስብከቱ ኒቅዩስ በስተደቡብ በምትገኘው ቦታ ወስደው ኅዳር 28 ቀን (በቅብጥ አቆጣጠር ሐቱር 28 ቀን) አንገቱን በሰይፍ ቀሉት።
ደቀመዛሙርቱ አስከሬኑን በመንገድ ላይ እንዳልባሌ ነገር ተጥሎ ሲያዩት በመረረ ሐዘን ተውጠው እያለቀሱ “እረኛችን ሆይ ለማን ታስጠብቀናለህ? አባታችን ሆይ እንግዲህ ማን ይሰበስበናል? አውሬ ከቦናል፣ በወንጌል ኮትኩተህ ያሳደግከው ተክልህን ከእንግዲህ ማን ይንከባከበው?” እያሉ መሪር እንባን ያነቡ ነበር። ከብዙ ለቅሶ በኋላ አስከሬኑን ወስደው በኒቅዩስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በክብር አሳረፉት (ገድለ ሰራባሞን፣ ቅጠል166)።
ከገድሉ እንደምናነበው ሰራባሞን ባደረገው ተጋድሎና በጽንአቱ በርካታ የክብር ስሞችና ቅጽሎች ተሠጥተውታል። ዋና ዋናዎቹም፥ “ብፁዕ ወቅዱስ ሰማዕት”፣ “ለባሴ መንፈስ”፣ “ለባሴ፡ አምላክ”፣ “ዓምደ ቤተ ክርስቲያን”፣ “ሐረገ ወይን”፣ “ሐዲስ ዳንኤል”፣ “ላዕከ መንፈስ ቅዱስ”፣ “ሙሴ ሐዲስ”፣ “ጳውሎስ ዳግመ”፣ “ዮሐንስ ሐዲስ”፣ “መስተጋድል ዐቢይ” የሚሉት ናቸው።
በኮፕቲክ ቤተ ክርስቲያን በስሙ ብዙ አብያተ ክርስቲያናት እና ገዳማት ታንጸዋል፣ ገድል ተጽፎለታል፣ በስንክሳርም ይዘከራል። ገድሉ እና የሰማዕትነቱ ዜና በቅብጥ እና ዐረብኛ ቋንቋ የተጻፈና የተተረጎመ ሲሆን ሁሉም ግን ሙሉ በሙሉ ተጠቃሎ አልተገኘም። የቅብጡ ቅጂ በHyvernat, (ገጽ. 304-31) የታተመ ሲሆን የዐረብኛው ደግሞ (Kairo 27 በሚል ዝርዝር) በKraf (1934:12) ካታሎግ ተሠርቶለታል። በቅርቡ ደግሞ Youssef (2013: 263-280) የሚባል ተመራማሪ “ሰራባሞንን የሚመለከቱ የቤተ ክርስቲያን ምንባባት” ብሎ ጥናታዊ ጽሑፍ አውጥቷል።
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርሰቲያነ የቅዱስ ሰራባሞን ዜና ሕይወት እና ተጋድሎ እንደ ሌሎቹ ቅዱሳን እምብዛም ጎልቶ የሚታወቅ ባይሆንም በሕዳር 28 ስንክሳር ይታወሳል። ከዚህም በላይ በ15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ገድሉ ከዐረብኛ ወደ ግዕዝ በደብረ ሊባኖስ ገዳም በአቡነ መርሐ ክርስቶስ ዘመን (1408-1497) ተተርጉሞ ይገኛል። ይህም ገድል አሁን ከሚገኙት የቅብጥና ዐረብኛ ቅጂዎች ይልቅ የተሟላ እና ይዘቱም ሰፊ ነው። ይህ ገድል በ1970ዎቹ ውስጥ (EMML 6533) በሚል መለያ ማይክሮ ፊልም ተነስቷል።
ብራናው አጠቃላይ 168 ቅጠል ያለው ሲሆን ከመጀመሪያ እስከ 118 ድረስ የሐዋርያው ጳውሎስ ገድል፣ ከቅጠል 119-167 ድረስ ደግሞ የሰማዕቱ ሰራባሞንን ገድል ይዟል። የሰራባሞን ገድሉ አራት ክፍሎችን ይዟል፤ እነዚህም፥ 1) ድርሳን (ከቅጠል 119-131)፣ 2) ገድል (ከቅጠል135-142)፣ 3) ተአምር (ከቅጠል 132-149)፣ 4) ስምዕ (ከቅጠል 150-167) የሚሉ ናቸው። ይህም ስለ ሰራባሞን የሚጠናውን ጥናት ይበልጥ የተሟላ የሚያደርግና በተለይ ለቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ለዜና አበው እና ለነገረ ቅዱሳን የጥናት መስክ የጎላ ድርሻ ይኖረዋል። ከስንክሳሩና ከገድሉ በተጨማሪም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስለ ቅዱስ ሰራባሞን የተዘጋጁ ልዩ ልዩ አርኬዎች (Chaîne ቁ. 48 እና Wein፣ Athiop. 19 [በN.Rhodokanakis አማካይነት ካታሎግ የተሠራላቸው])፣ እንዲሁም ሁለት የተለያዩ መልክአት (Chaîne ቁ. 158 እና 325) ተዘጋጅተዋል። በኢትዮጵያው የገድል ቅጅ ላይ እስካሁን የተደረገ ጥናት የለም። የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ መነሻ ጥናት አድርጎ ገድሉንም እየተረጎመ ይገኛል።
ይህን ጽሑፍ የምንደመድመው በቪየና የሚገኘው ብራና (Vienna ms f.62v-63r) ስለ ቅዱስ ሰራባሞን ከሚያመሰግነው አርኬ ውስጥ አንዱን በማንበብ ይሆናል፤
ለከ፡ ስነ፡ ሰረባሞን፡ ዘኤፍራታ፤
ነጺሮሙ፡ ጥቀ፡ ለሕሊናሁ፡ ጥብዓታ፤
ከመ፡ ይከውን፡ ሰማዕት፡ ውስተ፡ ዓውደ፡ ግሩም፡ ሐተታ፤
ገደፈ፡ አብ፡ እጓሎ፡ ወእም፡ ወለታ፤
ወሐማትኒ፡ ሐደገት፡ መርዓታ።
የሰማዕቱ ሰራባሞን በረከት ይድረሰን!!!
ስምዓት
መጽሐፈ ስንክሳር – በግዕዝና በአማርኛ (ከመስከረም እስከ የካቲት)፣ ትንሣኤ ማሳተሚያ ድርጅት፣ አዲስ አበባ፣ 1994 ዓ.ም.
ገድለ ጳውሎስ ወሰራባሞን – (EMML 6533)- ደብረ ሊባኖስ ገዳም የሚገኝ፣ በ15ኛው መ/ክ/ዘ/ የተጻፈ ብራና (እስካሁን አልታተመም)።
Amsalu Tefera, 2013, “Gädlä Särabamon: the case of the Ethiopic version”, a paper read on a workshop titled “EMML@40: The Life and Legacy of the Ethiopian manuscript microfilm Library” organized by Hill Museum & Manuscript Library, Saint John’s University, Collegeville, MN, USA, July 25-26, 2013.
Budge, Wallis, 1928, The Book of the Saints of the Ethiopian Church: a translation of the Ethiopic Synaxarium መጽሐፈ፡ ስንክሳር፡ made from the manuscripts Oriental 660 and 661 in the British Museum, vol. I, Cambridge at the University Press.
Chaîne, M., 1912, “Catalogue des manuscrits Ethiopiens de la collection Antoine d’Abbadie”, Paris.
Chaîne, M., 1913, “Répertoire de salam et Melke’e contenus dans les manuscrits éthiopiens des bibliotheques d’Europe” in Revue de L’Orient Chrétien, , deuxieme Serie, Tome viii, no. 2
Colin, G. 1988, “Le Synaxaire Éthiopien mois de Ḫedār” in Patrologia Orientalis, Tome 44, fascicule3, no. 99)
Coptic Synaxarium, reading on Hatour 28, – retrieved online –http://popekirillos.net/EN/books/COPTSYNX.pdf, accessed on May 14, 2012.
Hayvernat, Henry, Les Actes des martyrs del’Égypte, retrieved online from http://www.archive.org.detailes/lesactesdesmarty01hyve – accessed on November 6, 2012.
Kraf, George, 1934, Catalogue de manuscrits Arabes Chrétiens conserves au Caire, studi e testi 63, Città del Vaticano Biblioteca Apostolica Vaticana
Rhodokanakis, N. 1906, Die Äthiopischen Handscriften der K. K. Hofbibliothek zu Wein, Wein Athiop. 19.
Youssef, 2013, “Liturgical Texts Relating to Sarapamon of Nikiu”, Peeters Online Journal, pp. 263-280.
ሐምሌ 28 ቀን 2006 ዓ.ም.
ምዕራፍ 7 ካለፈው የቀጠለ
ሠ. ሰፊ ደጅ የተባለች ባለጸጋን መጽውት ድኃን ጹም ማለት ነው፡፡
ሰፊ ደጅ የተባለች ፈቃደ ሥጋ ናት ወደ ሰፊው ደጅ የሚገቡ ብዙዎች ወደ ጠባቧ ደጅ የሚገቡ ደግሞ ጥቂቶች መሆናቸው ጌታን አያስቀናውም፡፡ ምክንያቱም ጥቂት ዕንቁ ያለው ደግሞ ብዙ ወርቅ ባለው፤ ጥቂት ወርቅ ያለው ብዙ ብር ባለው፤ ጥቂት ብር ያለው ብዙ ብረት ባለው፤ ጥቂት ብረት ያለው ብዙ ሸክላ ባለው አይቀናም፡፡
6. ስለ ሐሰተኞች ነቢያት
የበግ ለምድ ለብሰው ይመጣሉ የተባሉት ነጣቂ ተኩላዎች መንፈሳውያን መስለው የሚመጡ ሥጋውያን፤ ሃይማኖታውያን መስለው የሚመጡ መናፍቃን ናቸው፡፡ ጌታችን “በውስጣቸው ግን ነጣቂዎች ተኩላዎች ናቸው፡፡” ማለቱ ቢመረምሯቸው ሰውን ከመንጋው/ ከማኅበረ ምእመናን/ መካከል እየነጠቁ ወደ ገሃነም የሚያወርዱ መሆናቸውን ሲያጠይቅ ነው፡፡ እነዚህም ወይንና በለስ የማይገኝባቸው እሾሆችና ኩርንችቶች በመሆናቸው ከፍሬያቸው እንደሚታወቁ ተናግሯል፡፡ ይህም “ሥራቸውን አንሠራም ትምህርታቸውን ግን ብንማር ምን ዕዳ ይሆናል? ትሉኝ እንደሆነ ከመናፍቅ መምህር ሃይማኖት፣ ከሐሰተኛ መምህር እውነተኛ ትምህርት ቃል አይገኝም ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ወይን ወይንን ኮሶ ደግሞ ኮሶን ያፈራል እንጂ ወይን ኮሶን፣ ኮሶ ደግሞ ወይንን አያፈራም፡፡ መልካም ፍሬ የማያደርግ ዛፍ ተቆርጦ ወደ እሳት እንዲጣል መናፍቃንንም ሥላሴ በገሃነም እሳት ፍዳ ያጸኑባቸዋል፡፡
ጌታችን ከዚህ አያይዞ “ሁሉ ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ ይሉሃል፤ ታዲያ ወደ መንግሥትህ የሚገባውንና የማይገባውን በምን እናውቃለን? ትሉኝ እንደሆነ የሰማይ አባቴን ፈቃድ የሠራ ይገባል እንጂ ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ የሚለኝ ሁሉ ወደ መንግሥተ ሰማያት አይገባም፡፡ በዚያን ጊዜም ከቶ አላውቃችሁም፤ እናንተ ዓመፀኞች ከእኔ ራቁ ብዬ እመሰክርባቸዋለሁ” ብሏል፡፡ ትንቢት መናገርማ በለዓምም ትንቢት ተናግሯል፡፡ ዘኁ.20፡4፣17፡፡ አጋንንትን ለማውጣት ደቂቀ አስቄዋ አጋንንትን አውጥተዋል የሐዋ.19፡14፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ስለእነዚህ ሰዎች ሲናገር “እንደ እነዚህ ያሉ ሰዎች የክርስቶስን ሐዋርያት እንዲመስሉ ራሳቸውን እየለወጡ ውሸተኞች ሐዋርያትና ተንኰለኞች ሠራተኞች ናቸውና፡፡
ይህም ድንቅ አይደለም፤ ሰይጣን ራሱ የብርሃንን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣልና፡፡ እንግዲህ አገልጋዮቹ ደግሞ የጸድቅን አገልጋዮች እንዲመስሉ ራሳቸውን ቢለውጡ ታላቅ ነገር አይደለም፤ ፍጻሜአቸውም እንደ ሥራቸው ይሆናል፡፡” ሲል አስጠንቅቋል 2ኛ ቆሮ.11፡13-15፡፡ በኦሪቱም “በመካከልህም ነቢይ ወይም ሕልም አላሚ ቢነሣ ምልክትም ተአምራትም ቢሰጥህ እንደነገረህም ምልክቱ ተአምራቱም ቢፈጸም እርሱም ሄደን የማታውቃቸውን ሌሎች አማልክት እንከተል እናምልካቸውም ቢልህ፣ አምላካችሁን እግዚአብሔርን በፍጹም ልባችሁ በፍቡጸምም ነፍሳችሁ ትወድዱት እንደሆነ አምላካችሁ እግዚአብሔር ሊፈትናችሁ ነውና የዚያን ነቢይ ቃል ወይም ያን ሕልም አላሚ አትስሙ” ተብሏል ዘዳ.13፡1-3፡፡
7. በዓለት ላይ ስለተመሠረተውና በአሸዋ ላይ ስለተሠራው ቤት፡፡
ጌታችን በዚህ በመጨረሻው አንቀጽ ላይ ቃሉን ሰምቶ እንደ ቃሉ የሚኖረውን ልባም ሰው በዓለት ላይ በተመሠረተ ቤት መስሎታል፡፡ በዓለት ላይ የተመሠረተውም ቤት ዝናብ ወርዶ በጐርፍ፣ ነፋስ ነፍሶ በነፋስ ተገፈቶ አልወደቀም ብሏል፡-
ዓለት ለኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወልድ ዋሕድ ብለው ለሚታመንበት ሁሉ መንፈሳዊ መጠን የሚገኝበትና መንፈሳዊ መሠረት የሚቆምበት ዓለት ነው 1ኛ.ቆሮ.10፡4፡፡ ለማያምኑት ግን የማሰናከያ ዓለት ተብሎአል ኢሳ.8፡14፣ 1ኛ.ጴጥ.2፡8፡፡ ጌታችን ቅዱስ ጴጥሮስንም ዓለት ነህ ብሎታል ማቴ.16፡16-18፡፡ ዝናም ነፋስ የባለ መከራ ነው፡፡
ከምሳሌው የምንረዳው ዋነኛው ምሥጢር እንደሚከተለው ነው፡፡
ሃይማኖትን በበጎ ልቡና ይዘው እንደ ቃሉ የሚኖሩ ሰዎች ዓላውያን መኳንንት መከራ ቢያጸኑባቸው፣ ቤተሰቦቻቸውም ንጉሥ የወደደውን ዘመን የወለደውን ይዛችሁ ኑሩ ብለው ቢገፋፏቸው ምንም ይሁን ምን በክህደት አይወድቁም፡፡ እነዚህ ሃይማኖታቸውንና ምግባራቸውን እንደ ኢዮብ ባለ ሰውነት ይዘው የሚኖሩ ሰዎች የልጅ ሞት፣ የሀብት ውድመት እና የአልጋ ቁራኛ የሚያደርግ ደዌ ቢያጋጥማቸውም በምስጋና ይኖራሉ እንጂ ሃይማኖታቸውን አይለውጡም፡፡
ሃይማኖትን በበጎ ልቡና ይዘው እንደቃሉ የሚኖሩ ሰዎች በምክረ ካህን በፈቃደ ካህን ስለሚኖሩ አጋንንት በጎ አስመስለው ገፋፍተው ከክፉ ወጥመድ አይጥሏቸውም፡፡ እንዲህ ዓይነቶቹን ሰዎች አጋንንት በአሳብ ይዋጓቸዋል፡፡ እነዚህ ሰዎች እንደ እንጦንስ እንደ መቃርስ ንጽሕ ጠብቀን ከሴት ርቀን እንኖራለን የሚል አሳብ ሲመጣባቸው ቸኩለው አይወስኑም፡፡ ፈጥነው ለመምህረ ንስሐቸው ይነግራሉ፡፡ እነርሱም ቆዩ ይሏቸዋል፡፡ ደግሞም እንደ እንጦንስ እንደ መቃርስ ንጽሕ ጠብቀን ከሴት ርቀን መኖር አይቻለንም፤ እንደ ኢዮብ እንደ አብርሃም በሕግ ጸንተን እንኖራለን የሚል አሳብም ሲመጣባቸው ለመምህረ ንስሐቸው ይነግሩታል፡፡ እርሱም የሰይጣን ፆር እንደሆነ ዐውቆ ቆዩ ይላቸዋል፡፡ በመጨረሻም አጋንንት ሁሉም አይሆንልንም አሰኝተው ሃይማኖቱን ለማስለቀቅ ይገፋፏቸዋል፡፡ ይሁን እንጂ እነዚህ ሰዎች በምክረ ካህን በፈቃደ ካህን በእግዚአብሔር ቃል ላይ ተመሥርተው ስለሚኖሩ አይወድቁም፡፡
ጌታችን ቃሉን ሰምቶ እንደቃሉ የማይኖረውን ሰው ደግሞ በአሸዋ ላይ በተሠራ ቤት መስሎታል፡፡ ይህንንም ቤት ጐርፍ ነፋስ በገፉት ጊዜ አወዳደቁ የከፋ ሆኗል፡፡ እነዚህም ሃይማኖታቸውን በበጎ ልቡና ያልያዙ ሰዎች ናቸው፡፡ እንደ ቃሉ ይኖሩ መከራውን ተሰቅቀውና በወሬ ተፈትነው በክህደት ይወድቃሉ፡፡ ለጊዜው በጌታ ዐፀደ ወይን በቤተ ክርስቲያን ቢበቅሉም ፀሐይ ሲወጣ ግን ይጠወልጋሉ ማቴ.13፡5-6፣20፡፡
ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህን አስተምህሮ ከፈጸመ በኋላ ሕዝቡ ትምህርቱን አደነቁ፡፡ ምክንያቱም እንደ ጻፎቻቸው ሳይሆን እንደ ባለሥልጣን ያስተምራቸው ነበረ፡፡ ይህም ማለት ንጉሥ እንዲህ ይላችኋል እንደሚሉ ሹማምንት ያይደለ እኔስ እላችኋለሁ እያለ አስተምሯቸዋልና ነው፡፡
“ከመዝ ይቤ እግዚአብሔር” እንደሚሉ ዐበይት ነቢያት ያይደለ ሠራዔ ሕግ እንደ መሆኑ እኔስ አላችኋለሁ እያለ አስተምሯቸዋል፡፡ “ከመዝ ይቤ ሙሴ፤ ከመዝ ይቤ ሳሙኤል፣” እንደሚሉ ደቂቀ ነቢያት ያይደለ ፈጻሜ ሕግ እንደመሆኑ አስተምሯቸዋል፡፡
“ከባድና አስቸጋሪ ሸክም ተብትበው በሰው ትከሻ ይጭናሉ እነርሱ ግን በጣታቸው ስንኳ ሊነኩት አይወዱም፡፡” እንዳላቸው ጸሐፍት ፈሪሳውያን ያይደለ እንደ ጌትነቱ በርኅራኄ አስተምሯቸዋል፡፡ ከወርቁ የጠራውን፣ ከግምጃ ያማረውን፣ ከላሙ የሰባውን እንደሚሉ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ያይደለ የቸርነቱን ሥራ እየሠራ አስተምሯቸዋል፡፡
የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን አሜን፡፡
ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 4ኛ ዓመት ሰኔ 1989 ዓ.ም.
ነሐሴ 28 ቀን 2006 ዓ.ም
እንዳለ ደምስስ
ማኅበረ ቅዱሳን በ2006 ዓ.ም. ከዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ግቢ ጉባኤያት በርካታ ተማሪዎችን አስመርቋል፡፡ በዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ቆይታቸው ያስመዘገቡት ውጤት ከፍተኛ በመሆኑም በርካቶች የተሸለሙትን ዋንጫና ሜዳልያ በሥጦታ ለማኅበሩ በማበርከት ላይ ይገኛሉ፡፡
ከእነዚህ ተመራቂዎች መካከል በወሎ ዩኒቨርስቲ ደሴ ካምፓስ በእንስሳት ሳይንስ ትምህርት የተመረቀው ዲያቆን ቶሎሳ ታዬ አንዱ ነው፡፡ በዩኒቨርስቲ ቆይታው የግቢ ጉባኤው ሰብሳቢ የነበረ ሲሆን፤ በርካታ ውጣ ውረዶችን ተቋቁሞ 4 ነጥብ እና 18A+ በማምጣት የዩኒቨርስቲው አጠቃላይ አሸናፊ በመሆን ዋንጫና ሜዳልያ ለመሸለም በቅቷል፡፡
የተሸለመውን ዋንጫ በማኅበረ ቅዱሳን ጠቅላላ ጉባኤ ላይ በመገኘት ለማኅበሩ ሲያስረክብ፤ ሜዳልያውን ደግሞ ከሕፃንነት ጀምሮ ሲያገለግልበት ለነበረው ለምእራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት በለስ ወረዳ ዳቡስ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን እንዲሰጥለት በጉባኤው ላይ ለተገኘው የወረዳ ማእከሉ ተወካይ እንዲያደርስለት አስረክቧል፡፡
ዲያቆን ቶሎሳ ዋንጫና ሜዳልያውን ካበረከተ በኋላ ባስተላለፈው መልእክት “ወሎ ዩኒቨርስቲ ስገባ ማኅበሩ ባዘጋጀው የእንኳን ደህና መጣችሁ አቀባበል መርሐ ግብር ላይ ተገኝቼ የጉባኤ ቃና ጋዜጣን ገዝቼ ዶክተር እንግዳ በጅማ ዩኒቨርስቲ ሲመረቁ ያገኙትን ሜዳልያ ለማኅበሩ እንደሰጡ አነበብኩ፡፡ ወዲያውኑ እኔም ለዚህ ክብር እግዚአብሔር ቢያበቃኝ ያገኘሁትን ሽልማት ለማኅበሩ ለመሥጠት ቃል ገባሁ፡፡ እግዚአብሔርም ምኞቴን አሳካልኝ፡፡ ለኔ ይህ ዋንጫ ትልቁ ሀብቴ ነው፤ ሰው ሀብቱ ባለበት ልቡ ይኖራልና ዋንጫውን ሳስብ ማኅበሬን አስባለሁ፤ ተግቼም እንዳገለግል ያደርገኛል፡፡ የማልተካውንና በሕይወቴ አንድ ጊዜ ብቻ የማገኘውን ሀብቴ ለማይተካው የማኅበሬ አገልግሎት መሥጠት ለኔ ታላቅ ደስታ ነው” ብሏል፡፡
በጠቅላላ ጉባኤው ላይ የተገኙት ፕሮፌሰር ጥላሁን ተሾመ ዋንጫውንና ሜዳልያውን ከዲያቆን ቶሎሳ በመረከብ ለማኅበሩ ሰብሳቢና ለወረዳ ማእከሉ ከሠጡ በኋላ የተሰማቸውን ደስታ ሲገልጹ “ይህ ውጤት በሀገራችን በሚገኙ ዩኒቨርስቲዎች ታሪክ በጥቂቶች ብቻ ሊመዘገብ የሚችል ከፍተኛ ውጤት ነው፡፡ ካስመዘገበው ውጤት ይልቅ ደግሞ ታማኝ አገልጋይ ሆኖ በሕይወቱ አንድ ጊዜ ብቻ ሊገጥመው የሚችለውን እድል ውድ ሥጦታ ለማኅበሩ መሥጠቱ አስደንቆኛል፡፡ ብዙዎቻችንንም ያስተማረ ነው፡፡ ወደፊትም በሕይወቱ የተሳካ ጊዜ አሳልፎ ለሌሎች አርአያ እንዲሆን እመኛለሁ” ብለዋል፡፡
የማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ሰሙ ሥጦታውን ከተቀበሉ በኋላ የተሰማቸውን ሲገልጹም “ይህ ሥጦታ ጠቅላላ ጉባኤውንና ማኅበራችንን ወክዬ ነው የተቀበልኩት፡፡ እኛም ይህንን ታሪክና ሀብት ለመጠበቅ፤ አገልግሎቱንም ለማገዝ አብሮንም በአገልግሎት እንዲዘልቅ የምንችለውን ሁሉ እናደርጋለን፤ አደራውንም ተቀብለናል” ብለዋል፡፡
የደሴ ማእከል የማኅበረ ቅዱሳን ጸሐፊ ዲያቆን ሰሎሞን ወልዴ በሠጠው ምሥክርነትም ዲያቆን ቶሎሳ የግቢ ጉባኤው ሰብሳቢ ሆኖ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች መሠብሠቢያ አዳራሽ በማሠራት፤ በአቅራቢያው ቤተ ክርስቲያን በማሳነጽና በመምራት፤ የሥራ አስፈጻሚና በዩኒቨርስቲው የሚካሔዱ አገልግሎቶችን በማስተባበር ተጠምዶ ስለሚውል ለዚህ ክብር ይበቃል የሚል ግምት አልነበረንም፡፡ ሆኖም ለግቢ ጉባኤውና ማኅበሩ ለሚያከናወነው አገልግሎት አርአያ እንዲሆን ስናበረታታው ቆይተናል፡፡ እግዚአብሔር መልካም ነገር አደረገልን፡፡ በወረዳ ማእከላችን ከሚገኙ 8 ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ውሰጥ ከተዘጋጁት ሜዳልያዎች ሰባቱን የወሰዱት የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ናቸው ብሏል፡፡
ከዚሁ ጋር በተያያዘ በወልዲያ ዩኒቨርስቲ በደሴ ካምፓስ በትምህርትና እቅድ አስተዳደር ከፍተኛ ውጤት በማምጣት ሜዳልያ ተሸላሚ የሆነው አሰፋ አደፍርስ፤ በደብረ ታቦር ማእከል የፈቃደ እግዚእ ኮሌጅ ተመራቂዎቹ ዘውዴ ደሴና ከፍያለው ስመኝ ለማኅበሩ ማእከላት ሜዳልያቸውን አስረክበዋል፡፡ እንዲሁም ከሐረር የሜንሽን አግሮ ቴክኒካል ኮሌጅ ግቢ ጉባኤ ሰብሳቢ የሆነው ቃል ኪዳን ዓለሙ ሜዳልያውን በማእከሉ በኩል ለኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን እንዲሰጥለት አበርክቷል፡፡
ነሐሴ 27 ቀን 2006 ዓ.ም.
እንዳለ ደምስስ
የማኅበረ ቅዱሳን 11ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ ነሐሴ 24 እና 25 ቀን 2006 ዓ.ም. በማኅበሩ ሕንፃ መሰብሰቢያ አዳራሽ የሀገር ውስጥና የውጭ ማእከላት፤ የወረዳ ማእከላትና ግንኙነት ጣቢያዎች፤ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያት ተወካዮች፤ የማኅበሩ ሥራ አመራርና ሥራ አሥፈፃሚ አባላት፤ የማኅበሩ ልዩ ልዩ ክፍል ተጠሪዎች፤ ጥሪ የተደረገላቸው ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት አካሄደ፡፡
የጠቅላላ ጉባኤው ተሳታፈዎች ከነሐሴ 23 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ የእንኳን ደህና መጣችሁ አቀባበል የተደረገላቸው ሲሆን፤ የጸሎት፤ የመርሐ ግብር ትውውቅና ማስገንዘቢያ በጠቅላላ ጉባኤው አዘጋጅ አብይ ኮሚቴ ሰብሳቢ በዶክተር ዳኝነት ይመኑ ቀርቧል፡፡ የእጽበተ እግር መርሐ ግብርም ተከናውኗል፡፡
ነሐሴ 24 ቀን 2006 ዓ.ም. ጠዋት ጉባኤው በጸሎተ ወንጌል ተጀምሮ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክትና የማኅበሩ የሁለት ዓመታት የዕቅድ ክንውን ዘገባ በማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ ቀርቧል፡፡ በቀረበው ዘገባም የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ፤ የአብነት ትምህርት ቤቶችና ገዳማትን በማጠናከር ረገድ፤ የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ አገልግሎት ለማጠናከር ከአህጉረ ስብከቶች ጋር እየተሠሩ ስለሚገኙ በርካታ ተግባራት ፤ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያትን በማጠናከር ረገድ፤ የማኅበሩን ተቋማዊ አቅም ለማሳደግ እየተሠሩና በመሠራት ላይ የሚገኙ ሥራዎች፤ ያጋጠሙ ችግሮችና የተወሰዱ መፍትሔዎችን በዝርዝር አቅርበዋል፡፡
የ2005 ዓ.ም. የማኅበሩ የሒሳብ ሪፖርት በማኅበሩ ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ፤ እንዲሁም የኦዲትና ኢንስፔክሽን ሪፖርት በአቶ የሺዋስ ማሞ የቀረቡ ሲሆን፤ የ2004 ዓ.ም. እና የ2005 ዓ.ም. የሁለቱን ዓመታት የኦዲት ሪፖርት ዓለም አቀፍ እውቅና ባለው የውጭ ኦዲተር በማስመርመር በድርጅቱ ሓላፊ የኦዲት ሪፖርቱ ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርቧል፡፡ ጠቅላላ ጉባኤውም በቀረቡት ሪፖርቶች ላይ ውይይት በማካሔድ አጽድቋቸዋል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን ከ1996 ዓ.ም. በማኅበሩ ሥራ አመራር ጉባኤ ጸድቆ ሲሠራበት የቆየው የማኅበረ ቅዱሳን ጠቅላላ ጉባኤ ዝግጅትና የምርጫ ሥነ ሥርዓት መመሪያ በአሁኑ ወቅት ማኅበሩ ከደረሰበት የእድገት ደረጃና የአገልግሎት ስፋት አንጻር ሊጣጣም ባለመቻሉ መመሪያውን ማሻሻል በማስፈለጉ በሥራ አመራር ጉባኤው የተሰየመው ኮሚቴ የጥናቱን ረቂቅ ለጠቅላላ ጉባኤው አቅርቧል፡፡ በቀረበው የጠቅላላ ጉባኤ ዝግጅትና የምርጫ ሥነ ሥርዓት መመሪያ ማሻሻያ ረቂቅ ላይ በተሳታፊዎች ውይይት ተካሒዶበት ለማሻሻያ የሚጠቅሙ በርካታ ሃሳቦች ተነስተዋል፡፡ አጥኚ ኮሚቴውም የቀረቡለትን ገንቢ ሃሳቦች በማካተት ለመደበኛ ሥራ አመራር ጉባኤ እንዲያቀርብ፤ ሥራ አመራር ጉባኤውም የቀረበለትን ማሻሻያውን መርምሮ ውሳኔ እንዲያሳልፍ ጠቅላላ ጉባኤው መመሪያ ሰጥቷል፡፡
ጠቅላላ ጉባኤው በሁለተኛ ቀን ውሎው ብፁዕ አቡነ ሰላማ የምሥራቅ ሐረርጌ ሊቀ ጳጳስ የተገኙ ሲሆን፤ በሰጡት ቃለ ምእዳን “ያሰባሰባችሁ እግዚአብሔር ነው፤ በእናንተ ኃይል አልተሰባሰባችሁም፡፡ ፈቃደ እግዚአብሔር አስነስቷችኋልና በጉዟችሁ ፈተና ሊገጥማችሁ ይችላል፡፡ ፈተና ደግሞ ያለ ነው፤ ይጠቅማል እንጂ አይጎዳም፡፡ ከሚወድህ ይልቅ የሚጠላህ ይጠቅምሃል እንዲሉ አባቶቻችን ካልተፈተኑ ክብር አይገኝም፡፡ በአገልግሎታችሁ እንደጸናችሁ ሳትበሳጩ ልትጓዙ ያስፈልጋል፡፡ እግዚአብሔር ማኅበሩን ይባርክ” ብለዋል፡፡
በቀጣይነትም ጠቅላላ ጉባኤው የግቢ ጉባኤያት የእድገትና ውጤታማነት መርሐ ግብር ስልታዊ አቅጣጫና እቅድ በሚቀጥሉት ዐሥር ዓመታት /ከ2007 – 2017/፤ እንዲሁም የማኅበረ ቅዱሳን ስልታዊ እቅድ አጋማሽ ዘመን ግምገማ በሚሉ ሁለት ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ተወያይቷል፡፡
የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት እድገትና ውጤታማነት ስልታዊ አቅጣጫና እቅድ ለሚቀጥሉት ዐሥር ዓመታት ተግባራዊ ለማድረግ በቀረበው ጥናት ላይ ተሳታፊዎችን በ23 ቡድን በመከፋፈል ውይይት ተደርጓል፡፡ በቡድን ውይይቱ የተነሱ በርካታ ነጥቦችን በግብአትነት በመያዝ በዋናነት በተያዙ የጥናቱ ክፍሎች ተከፋፍለዋል፡፡ በዚህም መሠረት የተነደፉት ግቦች፤ ዓላማዎች፤ ስልቶችና ተግባራት ስልታዊ እቅዱን ከማሳካት አንጻር፤ የግቢ ጉባኤያትን ስልታዊ እቅድ ከማስፈጸም አንጻር መዋቅራዊ አደረጃጀቱ ምን መምሠል እንዳለበት፤ በቀረበው ሰነድ ላይ የተጠቀሰው ገንዘብ ማግኛ ስልትና ምንጭ ተገቢ መሆኑን መመልከት፤ የግቢ ጉባኤያት ሁኔታ በአገልግሎት ክፍሎች በዋና ጉዳይነት አካቶ መሥራት በሚሉት ነጥቦች ሥር ለይቶ በመያዝ ለመደበኛ ሥራ አመራር ጉባኤ ለውሳኔ በማቅረብ፤ ሥራ አመራር ጉባኤው የቀረበለትን ሠነድ መርምሮ በማጽደቅ ተግባራዊ እንዲሆን ጠቅላላ ጉባኤው ወስኗል፡፡
የማኅበረ ቅዱሳን ስልታዊ እቅድ አጋማሽ ዘመን ግምገማ በማስመልከት ከጥር 2005 ዓ.ም. እስከ ግንቦት 2006 ዓ.ም. የተከናወኑትን ሥራዎች ተገምግመው ሓላፊነት በወሰደው አጥኒ ቡድን ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርበዋል፡፡ ጠቅላላ ጉባኤውም ውይይት በማድረግ አቅጣጫ ሰጥቷል፡፡ በዚህም መሠረት ቀጣይ አፈጻጸማችን ምን መምሰል እንደሚገባው ለማሳየት ቢሞከር፤ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ከስትራቴጂክ እቅዱ አንጻር አስታርቆ ማስኬድ፤ የክብደት አሥራር ሥርዓቱን ግልጽ ማድረግ፤ ግምገማው ከስልታዊ እቅዱ ጋር በደንብ ቢታይ የሚሉና ሌሎችም ጠቃሚ ነጥቦች ከተካተቱት ውስጥ ይገኙበታል፡፡ የጥናት ቡድኑ ከጠቅላላ ጉባኤው በተሰጡት ሃሳቦች መሠረት የግምገማውን ውጤት በአጭር ጊዜ ውስጥ ለመደበኛ ሥራ አመራር ጉባኤ እንዲያቀርብ፤ ሥራ አመራር ጉባኤውም አጽድቆ በሚመለከታቸው አካላት ተግባራዊ እንዲደረግ እንዲያስተላልፍ ውሳኔ ላይ ተደርሷል፡፡
በጠቅላላ ጉባኤው ማጠቃለያ ላይም የዝግጅቱ አብይ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዶክተር ዳኝነት ይመኑ ለጉባኤው መሳካት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደረጉ ድርጅቶችንና በጎ አድራጊ ምእመናንን በዝርዝር በመጥቀስ በጠቅላላ ጉባኤው ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡ እንዲሁም የጠቅላላ ጉባኤው ተሳታፊዎች ጉባኤው እሰኪጠናቀቅ ድረስ ላሳዩት አርአያነት ላለው ሥነ ምግባር የተላበሰ ታዛዥነትና ተሳትፎ አመስግነዋል፡፡
በጉባኤው ማጠቃለያም ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ የጠቅላላ ጉባኤው ተሳታፊዎች ለሦስት ቀናት በትዕግስት፤ በታዛዥነትና በንቁ ተሳታፊነት ለአገልግሎት ጠቃሚ የሆኑ ሃሳቦችን በማምንጨት ላበረከቱት አስተዋጽኦ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡
በጠቅላላ ጉባኤው ከ650 በላይ ተወካዮች ተሳትፈዋል፡፡
ነሐሴ 22 ቀን 2006 ዓ.ም.
ምዕራፍ 7
በማቴዎስ ወንጌል በምዕራፍ ሰባት ውስጥ የሰውን ነውር ከማጋነን ይልቅ የራስን ባሕርይ መቆጣጠር አስፈላጊ መሆኑን በሰፊው እንማራለን፡፡ ዋና ዋና አሳቦቹም የሚከተሉት ናቸው፡፡
ስለ ፍርድ
የተቀደሰውን ለውሾች መስጠት እንደማይገባ
ዕንቁን በእሪያዎች ፊት ማስቀመጥ እንደማይገባ
ስለ ልመና
ስለ ጠባቧ ደጅ እና ስለ ሰፊው ደጅ
ስለ ሐሰተኞች ነቢያት
በዐለት ላይ ስለተመሠረተውና በአሸዋ ላይ ስለተመሠረተው ቤት
1. ስለ ፍርድ፡-
ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሌላው ላይ መፍረድ እንደማይገባ አስተምሯል፡፡ በዚህ ትምህርቱም “እንዳይፈረድባችሁ አትፍረዱ፤ በምትፈርዱበት ፍርድ ይፈረድባችኋልና፡፡” ብሏል፡፡ ይህም ንጹሕ ሳትሆኑ ወይም ሳትሾሙ ብትፈርዱ ይፈረድባችኋል ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ተሾመው የፈረዱ አሉና፡፡ ለምሳሌ፡- ሙሴ በስለጰዓድ፣ ኢያሱ በአካን፣ ቅዱስ ጴጥሮስ በሐናንያና ሰጲራ፣ ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ በበርያሱስ ፈርደዋል ዘኁ.27፡1-15፣ 36፡2-12፣ ኢያ.7፡1-26፣ የሐዋ.5፡1-11፣ 13፡4-12፡፡ አንድ ሰው ንጹሕ ሳይሆን በፈረደው ፍርድ እንደሚፈረድበት ከንጉሡ ከዳዊት ሕይወት መማር ይቻላል 2ኛ ሳሙ.12፡1-15፡፡
ቅዱስ ጳውሎስም በመልእክቱ “ስለዚህ አንተ የምትፈርድ ሰው ሁሉ የምታመካኘው የለህም፤ በሌላው በምትፈርድበት ነገር ራስህን ትኰንናለህና፤ አንተው ፈራጁ እነዚያን ታደርጋለህና፡፡ እንደዚህም የሚያደርጉት ላይ የእግዚአብሔር ፍርድ እውነተኛ እንደሆነ እናውቃለን፡፡ አንተም እንደዚህ በሚያደርጉ የምትፈርድን ያንን የምታደርግ ሰው ሆይ አንተ ከእግዚአብሔር ፍርድ የምታመልጥ ይመስልሃልን?” ብሏል፡፡
ለዚህም ነው ጌታችን በወንድምህ ዓይን ያለውን ጉድፍ ከማውጣትህ በፊት በዓይንህ የተጋረድውን ምሰሶ አስወግድ ያለው፡፡ ጉድፍ የተባሉት ጥቃቅን ኃጢአቶች ሲሆኑ ምሰሶ የተባሉት ደግሞ ታላላቅ ኃጢአቶች ናቸው፡፡ ይህም ጥቃቅኗን ኃጢአቶች እየተቆጣጠርክ በባልንጀራህ ከመፍረድህ በፊት አንተው ራስህ ታላላቆቹን ኃጢአቶችህን በንስሐ አስወግደህ እንዳይፈረድብህ ሁን ማለት ነው፡፡
እዚህ ላይ የባልንጀራ ኃጢአት ትንሽ የራስ ኃጢአት ደግሞ ትልቅ የተባለበት ምክንያት ሰው የባልንጀራውን ኃጢአት የሚያውቀው በከፊል የራሱን ግን የሚያውቀው ሙሉ በሙሉ በመሆኑ ነው፡፡ ስለዚህ ከዚህ ተላልፎ እገሌ እንዴት ኃጢአት ይሠራል ብሎ በሌላው መፍረድ ፈሪሳውያንን መሆን ነው ማቴ.23፡1-39፡፡
2. የተቀደሰውን ለውሾች መስጠት እንደማይገባ፡-
ጌታችን “በእግራቸው እንዳይረግጡት፣ ተመልሰውም እንዳይነክሱአችሁ፣ የተቀደሰውን ለውሾች አትስጡ” ብሏል፡፡ ለመሆኑ ውሾች የተባሉት ሥራይን የሚያደርጉ፣ ሴሰኞች፣ ነፍሰ ገዳዮች ጣዖትን የሚያመልኩና የሐሰትን ሥራ ሁሉ የሚወዱ ናቸው ራእ.22፡15፡፡ እነዚህም ከቶ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት አይገቡም፡፡ ዕድል ፈንታቸው ጽዋ ተርታቸው በዲንና በእሳት በሚቃጠል ባሕር ነው፡፡ ይኸውም ሁለተኛው ሞት ነው ራእ.21፡8፣ 27፡ 1ኛ.ቆሮ.6፡9-10፡፡
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተቀደሰውን ለውሾች አትስጡ ማለቱ የተቀደሰውን ሥጋዬንና የከበረውን ደሜን ለእነዚህ አታቀብሉ ማለቱ ነው፡፡ አንድም ቋንቋችን ከቋንቋችሁ፣ መጽሐፋችን ከመጽሐፋችሁ አንድ ነው፡፡ እያሉ እንዳይከራከሯችሁና እንዳይነቅፏችሁ ሃይማኖታችሁን ለመናፍቅ አትንገሩ ማለቱ ነው፡፡ መናፍቃንም ውሾች ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ውሾች የተባሉ ወደ ቀደመ ግብራቸው የሚመለሱ በደለኞች ናቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታችንን እና መድኃኒታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን ከማወቅ ጋራ ከዚህ ዓለም ኃጢአት ከተለዩ በኋላ ዳግመኛ በእርስዋ ተጠላልፈው የሚሸነፉ ከሆነ ከቀደመ በደላቸው ይልቅ የኋላው በደላቸው የጸና የከፋ ይሆናል፡፡ አውቀዋት ከተሰጠቻቸው ከቅድስት ትእዛዝ ከሚመለሱ ጥንቱኑ የጽድቅን መንገድ ባላወቋት ይሻላቸው ነበር፡፡
ምክንያቱም እንደ ውሻ ወደ ትፋት መመለስ ነውና ብሏል 2ኛ.ጴጥ.2፡20-22፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ሰላም የሚያውኩ ሰዎችም ውሾች ናቸው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ለፊልጵስዩስ ሰዎች ጺፍላቸው በኒያ ለከፍካፎች መናፍቃን እወቁባቸው ብሏቸዋል ፊል3፡2፡፡ አንድም የተቀደሰ የተባለ ሥጋውና ደሙ ነው፡፡ ስለሆነም ከኃጢአት ለመመለስ ላልወሰኑ በደለኞችና በክህደት ለጸኑ መናፍቃን ሥጋውንና ደሙን ማቀበል አይገባም፡፡
3. ዕንቁን በእሪያዎች ፊት ማስቀመጥ እንደማይገባ፤
ጌታችን “ዕንቁዎቻችሁን በእሪያዎች ፊት አትጣሉ” ያለበትም ምክንያት አለው፡፡ ከአገራቸው ቀን ዋዕየ ፀሐይ ይጸናል፡፡ ሌሊት ዕንቁ ከተራራ ላይ አኑረው የሚጽፍ ሲጽፍ፣ አውሬ የሚያድንም ሲያድን ያድራል፡፡ እሪያ /አሳማ/ መልከ ጥፉ ነው፡፡ በዕንቁው አጠገብ ሲሄድ የገዛ መልኩን አይቶ ደንግጦ ሲሄድ ሰብሮት ይሄዳል፡፡
ዕንቁ የጌታ እሪያ የአይሁድ ምሳሌ ናቸው፡፡ በገዛ ኃጢአታቸው ቢዘልፋቸው የዕንቁ መስተዋት ሆኖ መልከ ጥፉ ኃጢአታቸውን ቢያሳያቸው ጠልተው ተመቅኝተው ገድለውታል፡፡ አንድም እሪያ የተባሉ ወደ ቀደመ ኃጢአታቸው የሚመለሱ ሰዎች ናቸው፡፡ “የታጠበች እሪያ በጭቃ ለመንከባለል ትመለሳለች እንደሚባል እውነተኞች ምሳሌዎች ሆኖባቸዋል” 2ኛ.ጴጥ.2፡22፡፡
አንድም እሪያዎች የአጋንንት ማደሪያዎች ሆነው ወደ እሳት ባሕር ለሚገቡ ሰዎች ምሳሌዎች ናቸው ማቴ.8፡32፡፡ አንድም እሪያዎች የተባሉ መናፍቃን ናቸው፡፡ ስለሆነም ዕንቁ የሆነ ሃይማኖታችንን፣ ሥርዓታችንን፣ ታሪካችንን እና ትውፊታችንን በእነርሱ ፊት ልናቀርብ አይገባንም፡፡
4. ስለ ልመና፡-
“ለምኑ ይሰጣችሁማል፡፡” ጌታችን እንዲህ ማለቱ የበቃውንና ያልበቃውን በምን እናውቀዋለን ትሉኝ እንደሆነ “ለምኑ ይሰጣችኋል” ማለቱ ነው፡፡ ለምነው ያገኙ ዮሐንስ ዘደማስቆና ድሜጥሮስ የበቃና ያልበቃ ለይተው ያቀብሉ ነበር፡፡ ምክንያቱም መንፈሳዊ ሰው ሁሉን ይመረምራልና 1ኛ.ቆሮ.2፡15፡፡ ፈልገው ያገኙና አንኳኩተው የተከፈተላቸው ሰዎች ብዙዎች በመሆናቸውም “የሚለምነው ሁሉ ይቀበላልና፣ የሚፈልገውም ያገኛል፣ መዝጊያንም ለሚያንኳኳ ይከፈትለታል” አለ፡፡ ከቀደሙ ሰዎች አብርሃም ከኳላ ሰዎች ደግሞ ሙሴ ጸሊም በፀሐይ በሥነ ፍጥረት ተመራምረው አምነዋል፡፡ በክርስቶስ ቀኝ የተሰቀለው ወንበዴ በመለመኑ በመፈለጉ እና በማንኳኳቱ የገነት በር ተከፍቶለታል፡፡ “ጌታ ሆይ በመንግሥትህ በመጣህ ጊዜ አስበኝ አለው፡፡ ኢየሱስም እውነት እልሃለሁ ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ አለው” ሉቃ.23፡42፡፡
በተጨማሪም፡- ለባሕርያችሁ ክፋት ጥመት የሚስማማችሁ ስትሆኑ እናንተ ለልጆቻችሁ በጎ ነገርን የምታደርጉላቸው ከሆነ ቸርነት የባሕርይ የሚሆን ሰማያዊ አባታችሁማ በጎ ነገርን ለሚለምኑት እንደምን በጎ ነገርን ያደርግላቸው ይሆን አላቸው፡፡
5. ስለ ጠባቧ ደጅ እና ሰፊው ደጅ፡-
ሀ/ ወደ ሕይወት የምትወስድ ጠባብ ደጅ እና ቀጭን መንገድ የተባለች ሕገ ወንጌል ናት፡፡ ምክንያቱም “ቀኝ ጉንጭህን በጥፊ ለሚመታህ ሁሉ ሁለተኛውን ደግሞ አዙርለት፤ እንዲከስህም እጀ ጠባብህንም እንዲወስድ ለሚወድ መጐናጸፊያህን ደግሞ ተውለት፤ ማንም ሰው አንድ ምዕራፍ ትሔድ ዘንድ ቢያስገድድህ ሁለተኛውን ከእርሱ ጋር ሒድ፡፡ ጠላቶቻችሁን ውደዱ፣ የሚረግሙአችሁንም መርቁ፣ ለሚጠሉአችሁም መልካም አድርጉ፣ ስለሚያሳድዱአችሁም ጸልዩ፤ ትላለችና፡፡
ለ/ ጠባብ ደጅና ቀጭን መንገድ የተባለች ባለጸጋን ጹም ድኃን መጽውት ማለት ነው፡፡
ሐ/ ጠባብ በር የተባለች ፈቃደ ነፍስ ናት
መ/ ወደ ጥፋት የሚወስድ ሰፊ ደጅና ትልቅ መንገድ የተባለች ኦሪት ናት፡፡ ምክንያቱም የገደለ ይገደል፣ ዓይን ያጠፋ ዓይኑ ይጥፋ ጥርስ የሰበረ ጥርሱ ይሰበር፣ እጅ የቆረጠ እጁ ይቆረጥ፣ እግር የሰበረ እግሩ ይሰበር፣ ያቃጠለ ይቃጠል፣ ያቆሰለ ይቁሰል፣ የገረፈ ይገረፍ ትላለችና ዘጸ.21፡23፣ ማቴ.5፡38፡፡
ይቀጥላል
ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 4ኛ ዓመት ሚያዚያ 1989 ዓ.ም.
ነሐሴ 19 ቀን 2006 ዓ.ም.
አውሮፓ ማእከል
በግሪክ አቴንስ ምክሓ ደናግል ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤና ሰንበት ትምህርት ቤት ከማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል ጋር በመተባበር ከነሐሴ 9 እስከ 11 ቀን 2006 ዓ.ም. ዐውደ ርእይ ተካሔደ፡፡
ለተከታታይ ሦስት ቀናት የቆየው ዐውደ ርእይ በበርካት ምእመናን የተጎበኘ ሲሆን፤ የቤተ ክርስቲያን ጥንታዊ ታሪክ፣ የገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ወቅታዊ ሁኔታ፣ የማኅበረ ቅዱሳን አመሠራረትና መንፈሳዊ አገልግሎት በተመለከተ ገለጻ ተደርጓል፡፡ ዐውደ ርእዩን የተመለከቱ በመቶዎች የሚቆጠሩ ምእመናንም አስተያየታቸውን በቃልና በጽሑፍ ሰጥተዋል፡፡
በተለይም ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ያሉበትን ነባራዊ ሁኔታ ከቀረበው ገለጻ መረዳታቸውንና ማዘናቸውን የገለጹት ምእመናን፤ በገዳማትና በአብነት ትምህርት ቤቶች ላይ የሚታየው ችግር ለመፍታት ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር በመሆን አቅማቸው የፈቀደውን ድጋፍ ለማድረግ ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡
በዚህም መሠረት ማኅበረ ቅዱሳን አብነት ትምህርት ቤቶችን ለመርዳት የቀረጸውን የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የነጻ ትምህርት እድል ፕሮጀክት ለመርዳት የገንዘብ ድጋፍ አድርገዋል፡፡ ፕሮጀክቱም በተያዘለት እቅድ መሠት እስኪፈጸም ድረስ ድጋፋቸውን አጠናክረው ለመቀጠል ቃል ገብተዋል፡፡
በተጨማሪም ገዳማትንና አብነት ትምህርት ቤቶችን በጋሪ ለመርዳት እንዲያስችል ማኅበረ ቅዱሳን በግሪክ አቴንስ ከተማ ማእከል እንዲያቋቁምላቸው ምእመናን ጥያቄ አቅርበዋል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን በቅርቡ በጀርመን ካስል ደብረ ቀራንዮ መድኃኔዓለም እና በኮሎኝ ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል አብያተ ክርስቲያናት ዐውደ ርእይ አዘጋጅቶ እንደነበር መዘገባችን የሚታወስ ሲሆን፤ ዐውደ ርእዩ በቤልጂየም ብራስልስ አብያተ ክርስቲያናትም ይቀጥላል፡፡
ነሐሴ 14 ቀን 2006 ዓ.ም.
በጀርመን ቀጠና ማእክል
በማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል ሐምሌ 26 እና 27 2006 ዓ.ም በጀርመን ካስል ደብረ ቀራንዮ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ያሉበትን ሁኔታ፣ የማኅበረ ቅዱሳንን ታሪክ፣ አገልግሎትና በየጊዜው ያጋጠሙትን ችግሮች እንዲሁም የቤተክርስቲያን አገልግሎት በአውሮፓ በተለይም በጀርመን ያለበትን ሁኔታ፣ የአመሠራረት ታሪከ እና መንፈሳዊ እንቅስቃሴ የሚያስቃኝ ዐውደ ርእይ ተካሔደ።
ዐውደ ርእዩ በካስል ደብረ ቀራንዮ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ በመጋቤ ምሥጢር ኅሩይ ኤርምያስ ተከፍቷል። ምእመናን ዐውደ ርእዩን ከተመለከቱ በኋላ ስለ ማኅበረ ቅዱሳን አመሠራረት፣ ገዳማትና የአብነት ትምህር ቤቶችን ለመደገፍ እያደረገ ስላለው እንቅስቃሴ በቂ መረጃ ማግኘታቸውን ገልጠው የማኅበሩን አገልግሎት ለመደገፍ ፍላጎት እንደላቸው ገልጸዋል። መጋቤ ምሥጢር ኅሩይ ኤርምያስ በበኩላቸው ራሳቸው ያለፉበት የአብነት ትምህርት ቤት ለቤተክርስቲያንም ሆነ ለሀገር ያበረከቱት አስተዋጽኦ ተመልካች ሊረዳው በሚችል መልኩ መቅረቡን አድንቀው ማእከሉ ዐውደ ርእዩን በደብሩ ስላካሔደ በስበካ ጉባኤው ስም ምሥጋና አቅርበዋል፤ የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት የቤተክርስቲያን አገልግሎት በመሆኑ አቅማቸው የፈቀደውን ሁሉ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል::
ዐውደ ርእዩ ነሐሴ 3 እና 4 ቀን 2006 ዓ.ም በኮሎኝ ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ላይ በአጥቢያው ሰበካ ጉባኤና በሊቀ ካህናት ዶ/ር መርዓዊ ተበጀ በጀርመን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሓላፊ ፈቃድ ለምእመናን ለመታየት በቅቷል። ዐውደ ርእዩን የከፈቱት ሊቀ ካህናት ዶ/ር መርዓዊ ተበጀ ሲሆኑ በዕለቱ የቀረበው ዐውደ ርእይ ጥንታዊ ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ያሉበትን ሁኔታ ምእመናን እንዲረዱት የሚያደርግ በመሆኑ ማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእዩን በዚህ ቤተክርስቲያን ማካሔዱ ያስደሰታቸው መሆኑን ተናግረዋል። በመቀጠልም የድጓ እና የአቋቋም መምህር የሆኑት እና ከካርል ስሩህ አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተክርስቲያን የመጡት ሊቀ ጠበብት ተክሌ ሲራክ ስለአብነት ትምህርት ቤቶች ሥርዓተ ትምህርት እና በአሁኑ ወቀት ተማሪዎች ስላሉባቸው ቸግሮች ሰፊ ገለጻ አድርገዋል፡፡ ችግሮቹን ለመፍታት አባቶች፣ ምእመናንና ማኅበራት ሊያደርጓቸው ይገባል ያሏቸውን የመፍትሔ ሐሳቦች ጠቁመዋል::
በኮሎኝ ደ/ሰ/ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን የሚገኙ ምእመናን ዐውደ ርእዩን ከተከታተሉ በኋላ ማኅበረ ቅዱሳን በገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ላይ ከፍተኛ ሥራ መሥራቱን የሚያሳይ መረጃ ሳያገኙ የቆዩ መሆናቸውን ገልጸው ወደ ፊት ግን ከማኅበሩ ጋር በመተባበር በጋራ ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶችን ለመርዳት ቃል ገብተዋል። ዐውደ ርእዩ ለሁለት ቀናት ክፍት ሆኖ በምእመናን የተጎበኘ ሲሆን ከ150 በላይ የሚሆኑ የአጥቢያው ምእመናን እንደጎበኙት የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ በነበሩ አንዳንድ ክፍተቶች ማኅበረ ቅዱሳን በአጥቢያው ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ ሳያደርግ የቆየ ቢሆንም ከዚህ በኋላ ግን በአዲስ መልክ ከደብሩ አስተዳዳሪ፣ ከሰበካ ጉባኤው እንዲሁም ከምእመናን ጋር ለመሥራት ከስምምነት ላይ ተደርሷል። ከዚህ በፊት በማኅበሩ ላይ ቅሬታ የነበራቸው ምእመናንም ከዐውደ ርእዩ በኋላ ጥያቄና አስተያየት አቅርበው በቂ ማብራሪያና ምላሽ በማግኘታቸው በቀጣይ ከማኅበሩ ጋር ለመሥራት በጎ ፍላጎት ያላቸው መሆኑን ተናግረዋል።
ተመሳሳይ የዐውደ ርእይ ዝግጅቶች በግሪክ አቴንስና በቤልጂየም ብራስልስ አብያተ ክርስቲያናት የሚካሔድ መሆኑ ተጠቅሷል።
ነሐሴ 9 ቀን 2006 ዓ.ም.
ምዕራፍ ስድስት
በዚህ ምዕራፍ ውስጥ የሚከተሉት አሳቦች ተጠቃልለው ይገኛሉ፡፡
የምጽዋት ሥርዓት
ጠቅላላ የጸሎት ሥርዓት
የአባታችን ሆይ ጸሎት
ስለ ይቅርታ
የጾም ሥርዓት
ስለ ሰማያዊ መዝገብ
የሰውነት መብራት
ስለ ሁለት ጌቶች
የዕለት ጉርስና የዓመት ልብስ
1. የምጽዋት ሥርዓት፡- ጌታችን በዚህ ትምህርቱ እንደ ግብዞች መመጽወት እንደማይገባ ተናግሯል፡፡ ግብዞች የሚመጸውቱት ሰው ሰብስበው፣ ቀን ቀጥረው በተመሳቀለ ጉዳና በአደባባይ ነው፡፡ የሚመጸዉቱትም ለመጽደቅ ሳይሆን ለውዳሴ ከንቱ ስለሆነ፤ ስለዚህም አንተ በምትመጸውትበት ጊዜ ቀኝ እጅህ የምትሠራውን ግራ እጅህ አትወቀው ብሏል፡፡ እንዲህም ያለበት ምክንያት፡-
ሀ. በቀኝ አጅህ የያዝኸውን በግራ እጅህ አትያዘው ማለቱ ነው፡፡ ምክንያቱም ግራ ደካማ ስለሆነ ጥቂቱን ብዙ አስመስሎ ልቀንስለት ይሆን ያሰኛል፡፡ ቀኝ ግን ኃያል ስለሆነ ብዙውን ጥቂት አስመስሎ አንሷል ልጨምርበት ያሰኛል፡፡
ለ. ግራ እጅ የተባለች ሚስት ናት፤ ሚስት በክርስትና ሕይወት ካልበሰለች ሀብቱ እኮ የጋራችን ነው፣ ለምን እንዲህ ታበዛዋለህ? እያለች ታደክማለች፡፡ ከሰጠ በኋላ ግን ከሚስት የሚሰወር ነገር ስለሌለ ይነግራት ዘንድ ይገባል፡፡ ብትስማማ እሰየው፤ ባትስማማ ግን መለየት ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም ጥንቱን የተጋቡት እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው ሰጥተው መጽውተው ለመጽደቅ ነውና፡፡
ሐ. ግራ እጅ የተባሉት ልጆች ናቸው፤ የአባታችን “የቁም ወራሽ የሙት አልቃሽ” እያሉ ያደክማሉና፡፡
መ. ግራ እጅ የተባሉት ቤተሰቦች ናቸው፤ የጌታችን ወርቁ ለዝና፣ ልብሱ ለእርዝና እህሉ ለቀጠና እያሉ ያዳክማሉና፡፡
ይህን ሁሉ አውቀን ተጠንቅቀን የምንመጸውት ከሆነ በስውር ስንመጸውት የሚያየን ሰማያዊ አባታችን በጻድቃን፣ በሰማዕታትና በመላአክት ፊት ዋጋችንን በግልጥ ይሰጠናል፡፡
2. የጸሎት ሥርዓት፡- ግብዞች የሚጸልዩት ለታይታ ነው፤ አንተ ግን ከቤትህ ገብተህ ደጅህን ዘግተህ በስውር ላለው አባትህ ጸልይ፡፡ በስውር የሚያይ አባትህም በግልጥ ያስረክብሃል፡፡ ብሏል፡፡ ይህም ማለት የምትጸልይበት ጊዜ ሕዋሳትህን ሰብስበህ፣ በሰቂለ ልቡና ሆነህ ወደ ሰማያዊ ወደ እግዚአብሔር አመልክት፤ ተሰውረህም ስትጸልይ የሚያይ አባትህ ዋጋህን ይሰጥሃል ማለት ነው፡፡ ይህ የግል ጸሎትን የተመለከተ ነው እንጂ በቤተ ክርስቲያን የሚደረግ የማኅበር ጸሎትን አይመለከትም፡፡
3. የአባታችን ሆይ ጸሎት፡- ጌታችን ማንም ቢሆን ሲቆምና ሲቀመጥ፣ ሲተኛና ሲነሣ ሊጸልይ የሚችለውን አጭር የኅሊና ጸሎት አስተማረ፡፡ ይህንንም በዝርዝር እንመለከተዋለን፡-
ሀ. አባታችን ሆይ፡- ጌታችን ከግብርናተ ዲያብሎስ /ከዲያብሎስ ባርነት/ ነጻ እንዳወጣን፣ አጥተነው የነበረውን ልጅነት እንዳገኘን ሲያጠይቅ አቡነ /አባታችን/ በሉኝ አለ፡፡ ጌታ ሎሌውን መምህር ደቀመዝሙሩን ምን ቢወደው ያበላዋል፣ ያጠጣዋል፣ የልቡናውን ምሥጢር ያጫውተዋል እንጂ ርስቱን አያወርሰውም፡፡ ርስቱን የሚያወርሰው ለልጁ ነው፡፡ እርሱ ግን ጌታችን እና አምላካችን ሲሆን የማታልፍ ርስት መንግሥተ ሰማያትን የሚያወርሰን ስለሆነ አቡነ በሉኝ አለ፡፡ አባት ለወለደው ልጁ እንዲራራ የሚራራልን ስለሆነ አቡነ በሉኝ አለ፡፡
ለ. በሰማያት የምትኖር፡- እንዲህ ማለቱ ራሱ ከምድራዊ አባት ሲለይ ነው፡፡ ምድራዊ አባት ሲወልድ በግዘፍ ሲያሳድግ በግዘፍ ነው፡፡ ኋላም ሓላፊ ርስቱን ያወርሳል፡፡ ጌታችን ግን ሲወልደን በረቂቅ፣ ሲያሳድገንም በረቂቅ ነው፡፡ ኋላም የማታልፍ ርስቱን መንግሥተ ሰማይን ያወርሰናል፡፡ በተጨማሪም ጌታ በሁሉ ምሉዕ ሲሆን ስለ ልዕልናው በሰማይ የምትኖር ይባላል፡፡
ሐ. ስምህ ይቀደስ፡- ይህም “ስምየሰ መሐሪ ወመስተሠፀል” ስሜ መሐሪና ይቅር ባይ ነው፡፡” ያልኸው ይድናልና፤ መላእክት ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ብለው ስምህን አመስግነው ቅድስናህን ተሳትፈው እንዲኖሩ፣ እኛም ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ ብለን አመሰግነንህ ቅድስናህን ተሳትፈን እንድንኖር አድርገን በሉ ሲለን ነው፡፡
መ. መንግሥትህ ትምጣ፡- መንግሥተ ሰማይ ትምጣልን ልጅነት ትሰጠን በሉ ሲል ነው፡፡ እንዲህም ማለቱ መንግሠተ ሰማይ ከወዲያ ወዲህ የምትመጣ፣ ከወዲህም ወዲያ የምትሔድ ሆና ሳይሆን ትገለጽልን በሉ ማለቱ ነው፡፡
ሠ. ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነ እንዲሁም በምድር ይሁን፡- መላእክት በሰማይ ሊያመሰግኑህ ፈቃድህ እንደሆነ እኛም በምድር ያለን ደቂቀ አዳም እናመሰግንህ ዘንድ ፈቃድህ ይሁን፡፡ ኋላ ሙተን ተነሥተን እንድናመሰግንህ ዘንድ ፈቃድህ ይሁን በሉ ሲል ነው፡፡
ረ. የዕለት እንጀራችንን ስጠን ዛሬ፡- በዚህ ዓለም ሳለን ለዕለት የሚሆነን ምግባችንን ስጠን በሉ ሲል ነው፡፡
ሰ. በደላችንን ይቅር በለን እኛም የበደሉንን ይቅር እንደምንል፡- ማረን፣ ይቅር በለን፣ ኃጢአታችንን አስተስርይልን፣ በደላችንን ደምስስልን መተላለፋችንን ሁሉ ይቅር በለን፤ ይቅርታን እናገኝ ዘንድ እኛም የበደሉንን ሁሉ ይቅር እንላለን ሲል ነው፡፡
ሸ. አቤቱ ወደ ፈተናም አታግባን፡- ከክፉ ሁሉ አድነን እንጂ ወደ ኃጢአት፣ ወደ ክህደት፣ ወደ መከራ፣ ወደ ገሃነም አታግባን ከዚህ ሁሉ አድነን እንጂ በሉኝ ሲል ነው፡፡
ቀ. መንግሥት ያንተ ናትና፡- መንግሥተ ሰማያት ያንተ ገንዘብህ ናትና በሉኝ ሲል ነው፡፡
በ. ኃይል ምስጋናም ለዘላለሙ፡- ከሃሊነት፣ ጌትነት፣ ለዘላለሙ ገንዘብህ ናትና፤ አሜን በእውነት በሉኝ ሲል ነው፡፡
4. ስለ ይቅርታ የሰውን ኃጢአት ይቅር ባትሉ የሰማይ አባታችሁ እናንተንም ይቅር አይላችሁም፡፡ የሰውን ኃጢአት ይቅር ብትሉ ግን እናንተም የሰማይ አባታችሁ ይቅር ይላችኋል ብሏል፡፡
5. የጾም ሥርዓት፡- ግብዞች በሚጾሙበት ጊዜ ሰው እንዲያውቅላቸው ፊታቸውን አጠውልገው፣ ግንባራቸውን ቋጥረው፣ ሰውነታቸውን ለውጠው የታያሉ፡፡ እነዚህም በዚህ ዓለም የሚቀረውን ውዳሴ ከንቱ በማግኘታቸው የወዲያኛውን ዓለም ዋጋ ያጡታል፡፡ እናንተስ በምትጾሙበት ጊዜ ራሳችሁን ተቀቡ፣ ፊታችሁንም ታጠቡ፡፡ የተቀባ የታጠበ እንዳይታወቅበት አይታወቅባችሁ አለ፡፡ ይህስ በአዋጅ ጾም ነው ወይስ በፈቃድ ጾም ነው ቢሉ በፈቃድ ጾም ነው እንጂ በዓዋጅ ጾምስ ምንም ውዳሴ ከንቱ የለበትም ምክንያቱም ሁሉ ይጾመዋልና፡፡ አንድም በገዳም ነው ወይስ በከተማ ቢሉ በከተማ ነው እንጂ በገዳምስ ምንም ውዳሴ ከንቱ የለበትም፡፡ የምሥጢራዊ መልእክቱም ታጠቡ ንጽሕናን ያዙ፣ ተቀቡ ደግሞ ፍቅርን ገንዘብ አድርጉ ማለት ነው፡፡ እንዲህም በማድረጋችሁ ማለት ጾመ ፈቃድን ተሰውራችሁ በመጾማችሁ ተሰውሮ የሚያያችሁ አባታችሁ በቅዱሳን መካከለ ዋጋችሁን ይሰጣችኋል አለ፡፡
6. ሰማያዊ መዝገብ፡- ጌታችን ሰማያዊ መዝገብ ያለው አንቀጸ ምጽዋትን ነው፡፡ ኅልፈት፣ ጥፋት ያለበትን፣ ብል የሚበላውን ነቀዝ የሚያበላሸውን ምድራዊ ድልብ፤ ሌቦች ግንቡን አፍርሰው ግድግዳውን ምሰው የሚወስዱትን ቦታ አታደልቡ አለ፡፡ ይህም ስለ ሦስት ነገር ተናግሮታል፡፡
ሀ. እህሉን፡- ነዳያን ከሚበሉት ብለው ብለው፣ ልብሱንም ነዳያን ከሚለብሱት ብለው አኑረውት ብል ቢበላው ወይም ነቀዝ ቢያበላሸው ምቀኝነት ነውና፡፡
ለ.ለክፉ ጊዜ ይሆነኛል ብሎ ሰስቶ ነፍጎ ማኖር በዝናብ አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ የሚመግበውን ለጋስ አምላክ እግዚአብሔርን ከዳተኛ ማድረግ ነውና፡፡
ሐ. ምንም እጅ እግር ባያወጡለት ገንዘብን ማኖር ጣዖትን ማኖር ነውና ስለሆነም ኅልፈት ጥፋት የሌለበትን፣ ሰማያዊ ድልብ ሌቦች ግንቡን አፍርሰው ግድግዳውን ምሰው ከማይወስዱት ቦታ አደልቡ፤ ገንዘባችሁ ካለበት ዘንድ ልባችሁ በዚያ ይኖራልና አለ፡፡ ምሥጢራዊ መልእክቱም ውዳሴ ከንቱ ያለበትን ውዳሴ ከንቱ የሚያስቀርባችሁን፣ ሌቦች /አጋንንት/ በውዳሴ ከንቱ የሚያስቀሩባችሁን ምጽዋት አትመጽውቱ፤ ውዳሴ ከንቱ የማያስቀርባችሁን፣ ውዳሴ ከንቱ የሌለበትን ሌቦች /አጋንንት/ በውዳሴ ከንቱ የማያስቀሩባችሁን ምጽዋት መጽውቱ፤ መጽውታችሁ ባለበት ልባችሁ ከዚያ ይኖራልና ማለት ነው፡፡
7. የሰውነት መብራት፡- የሥጋህ ፋና ዓይንህ ነው፤ ዓይንህ ነው፤ ዓይንህ ብሩህ ይሆናል፤ ዓይንህ የቀና እንደሆነ ሥራህ ሁሉ የቀና ይሆናል፡፡ ዓይንህ የታመመ ከሆነ ጨለማ እንደምን ይጸናብህ? የታመመው ዓይንህ የታመመ ከሆነ ጨለማ እንደምን ይጸናብህ የታመመው ዓይንህ እንደምን ያይልሃል አለ፡፡ ምሥጢራዊ መልእክቱም እንደሚከተለው ነው፡፡
ሀ. ብርሃን የተባለው አእምሮ ጠባይዕ ነው፤ እዕምሮ ጠባይህ ያልቀና እንደሆነ ሥራህ ያለቀና ይሆናል፤ በተፈጥሮ የተሰጠህ አእምሮ ጠባይህ እንደምን መክበሪያ መጽደቂያ ይሆንሃል ማለት ነው፡፡
ለ. ብርሃን የተባለው ምጽዋት ነው፤ ምጽዋትህ ውዳሴ ከንቱ የሌለበት እንደሆነ ሥራህ ሁሉ የቀና ይሆናል፡፡ ምጽዋትህ ግን ውዳሴ ከንቱ ያለበት እንደሆነ ሥራህ ሁሉ ያልቀና ይሆናል፤ ከአንተ የሚሰጥ ምጽዋትህ ውዳሴ ከንቱ ያለበት ከሆነ ፍዳ እንደምን ይጸናብህ ይሆን እንዴትስ መክበሪያ መጽደቂያ ይሆንልሃል ማለት ነው፡፡
8. ስለ ሁለት ጌቶች፡- ለሁለት ጌታ መገዛት አይቻለውም፤ ይህም ባይሆን ማለት እገዛለሁም ቢል አንዱን ይጠላል ሌላውን ይወዳል፤ ለአንዱ ይታዘዛል ለሌላው አይታዘዝም ምክንያቱም አንዱ ቆላ ውረድ ሲለው ሌላው ደግሞ ደጋ ውጣ ቢለው ከሁለት ለመሆን ስለማይችል ነው፡፡ እንደዚህም ሁሉ ለእናንተም ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አይቻላችሁም አለ፡፡
9. የዕለት ጉርስና የዓመት ልብስ ነፍሳችሁ በምትበሉትና በምትጠጡት ወይም ስለ ሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፤ ነፍስ ከመብል ሰውነትም ከልብስ አይበልጥምን ምግብ ከመስጠትማ ነፍስን እም ኀበ አልቦ አምጥቶ መፍጠር አይበልጥምን ልብስ ከመስጠትማ ሥጋን ከአራቱ ባሕርያት አዋሕዶ መፍጠር አይበልጥምን ነፍስንና ሥጋን አዋሕጄ የፈጠርኳችሁ እኔ ትንሹን ነገር ምግብና ልብስን እንዴት እነሳችኋለሁ አለ ምሥጢራዊ መልእክቱም እንደሚከተለው ነው፡፡
ሀ. ምግብ ከመስጠትማ ነፍስን ካለችበት ማምጣት አይበልጥምን ልብስ አይበልጥምን ታዲያ ነፍስን ካለችበት አምጥቼ ሥጋን ከመቃብር አስነሥቼ አዋሕጄ በመንግሥተ ሰማይ በክብር የማኖራችሁ እንዴት ምግብና ልብስ እነሳችኋለሁ ማለት ነው፡፡
ለ. ሥጋዬን ደሜን ከመስጠትማ ነፍስንና ሥጋን ማዋሐድ አይበልጥምን ታዲያ ነፍስንና ሥጋን ተዋሕጄ ሰው የሆንኩላቸው እኔ እንዴት ሥጋዬንና ደሜን እነሳችኋለሁ ማለት ነው፡፡
ስለሆነም ዘር መከር የሌላቸውን፣ በጎታ በጎተራ በሪቅ የማይሰበስቡትን፣ ሰማያዊ አባታችሁ የሚመግባቸውን አዕዋፉን አብነት አድርጉ፡፡ እናንተ ከእነርሱ አትበልጡምን ከተፈጥሮ አዕዋፍ ተፈጠሮተ ሰብእ አይበልጥምን ለኒያ ምግብ የሰጠ ለእናንተ ይነሣችኋልን አለ፡፡ ምሥጢራዊ መልእክቱም እግዚአብሔር በምድረ በዳ የመገባቸውን እሥራኤል ዘሥጋን አስቡ፤ በዘመነ ብሉይ ከነበሩት ከእነርሱ በዘመነ ሐዲስ ያላችሁት እናንተ እስራኤል ዘነፍስ የተባላችሁት አትበልጡም ለእኒያ የሰጠሁ ለእናንተ እነሳችኋለሁን ማለት ነው፡፡
ስለ ልብስስ ለምን ትጨነቃላችሁ የሜዳ አበቦች እንዴት እንዲያድጉ ልብ አድርጋችሁ ተመልከቱ፤አይደክሙም አይፈትሉም ነገር ግን እላችኋለሁ ሰሎሞንስ እንኳ በክብሩ ሁሉ ከነዚህ እንደ አንዱ አልለበሰም፡፡ እግዚአብሔር ግን ዛሬ ያለውን ነገርም ወደ ዕቶን የሚጣለውን የሜዳን ሣር እንዲህ የሚያለብሰው ከሆነ እናንተ ሃይማኖት የጎደላችሁ ለእናንተማ እንዴት ልብስ ይነሳችኋል ስለሆነም ምን እንበላለን ምን እንጠጣለን ምን እንለብሳለን ብላችሁ አትጨነቁ፡፡ ይህንንስ ሁሉ ሃይማኖትና ምግባር የሌላቸው አሕዛብ ይፈልጉታል፡፡ እናንተስ አስቀድማችሁ መንግሥቱንና ጽድቁን እሹ፡፡ አስቀድማችሁ ሃይማኖት ምግባርን፣ ልጅነትንና መንግሥተ ሰማያትን ፈለጉ የዚህ ዓለምስ ነገር ሁሉ በራት ላይ ዳራጐት እንዲጨመር ይጨመርላችኋል፡፡ ነገ ለራሱ ይጨነቃልና አትጨነቁ፤ ለቀኑ ክፋቱ ይበቃዋል አለ ይህም ለነገ ያጸናናል ብላችሁ አብዝታችሁ አትመገቡ የነገውን ነገ ትመገቡታላችሁና አንድም ነገ እንናዘዘዋለን ብላችሁ ኃጢአታችሁን አታሳድሩ የነገውን ነገ ትናገራላችሁ ማለት ነው፡፡