አእመረ አሸብር “የቅዳሴ ሥርዓት” ሲያካሔድ በቁጥጥር ሥር ዋለ

 

“የቅዳሴ ሥርዓት” እየፈጸምን ነው በማለት ሲያጭበረብሩ

                                                                                                                            በእንዳለ ደምስስ

 በጥቅምቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በኑፋቄው ምክንያት የተወገዘው አእመረ አሸብር ከግብረ አበሮቹ ጋር በግለሰብ ቤት ውስጥ “የቅዳሴ ሥርዓት” ሲያካሔድ የካቲት ፲ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም በቁጥጥር ሥር ዋለ፡፡

 “መዳን በማንም የለም” በሚል ርእስ በ፳፻፲፩ ዓ.ም ባሳተመው የኑፋቄ መጽሐፉ በቅዱስ ሲኖዶስ ተወግዞ የተለየው አእመረ አሸብር በአርባ ምንጭ ከተማ በጫሞ ቀበሌ በግለሰብ መኖሪያ ቤት ውስጥ ከግብረ አበሮቹ ጋር ቅዳሴ እንቀድሳለን በማለት የቤተ ክርስቲያንን ንዋያተ ቅድሳት በመጠቀም ልብሰ ተክህኖ ለብሰው፣ ክክርስቶስ ሥጋና ደም ጋር የማይገናኝ ተራ ነገር በማቅረብ “ሥጋ ወደሙ” ነው በማለት፣ የመጾር መስቀል በመጠቀም “የቅዳሴ ሥርዓት” ሲያካሄዱ እንደነበር ከሥፍራው የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

     ከዓርብ የካቲት ፰ ቀን ጀምሮ እስከ እሑድ የካቲት ፲ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ጉባኤ ማዘጋጀታቸውንና ዓርብና ቅዳሜ የትምህርትና የምክክር ጉባኤ፣ እሑድ “ቅዳሴ” እናካሒዳለን በማለት ቀደም ብለው በማኅበራዊ ድረ ገጽ ላይ በለቀቁት ማስታወቂያ እንዲሁም ከተማው ላይ ማስታወቂያ በባነር አሠርተው በይፋ መስቀላቸውን የዓይን እማኞች ገልጠዋል፡፡

         የሀገረ ስብከቱ የፀረ ተሐድሶ እንቅስቃሴ ኮሚቴ፣ የአርባ ምንጭ ደ/መ/መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ፣ የስብከተ ወንጌል ኃላፊዎች እንዲሁም ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን በመሆን ወደ ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመሄድ ጉዳዩን አሳውቀዋል፡፡ ብፁዕነታቸውም ቅዳሜ የካቲት ፱ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም “የቤተ ክርስቲያንን ንዋያተ ቅድሳትን ስለማስከበር” በሚል ለሚመለከታቸው አካላት ጉዳዩን ትኩረት ሰጥተው መፍትሔ እንዲፈልጉ ለአርባ ምንጭ ከተማ ፖሊስ ጽ/ቤት፣ ለአርባ ምንጭ ከተማ ፍትሕና ፀጥታ ጽ/ቤት፣ ለጋሞ ጎፋ ዞን ፍትሕና ፀጥታ ጽ/ቤት፣ ለጋሞ ጎፋ ዞን ፖሊስ መምሪያ ጽ/ቤት በደብዳቤ አሳውቀዋል፡፡

   ብፁዕነታቸው ለሚመለከታቸው አካላት በላኩት ደብዳቤም ከዚህ ቀደም በኑፋቄያቸው በሀገረ ስብከቱ ተወግዘው የተለዩ ግለሰቦች ቅዳሴ እንቀድሳለን በማለት ቤተ ክርስቲያን ላይ በማላገጥና የራሷን የሆኑትን ቅዳሴዋንና ንዋያተ ቅድሳቷንና ከራሷ ያገኙትን መዓርግ በመያዝና በመጠቀም በ፲/፮/፳፻፲፩ ዓ.ም ፕሮግራም ሊያካሔዱ ማሰባቸውን ያስረዳል፡፡ ፕሮግራም እንደሚያካሄዱም በማኅበራዊ ድረ ገጽ ላይ በመልቀቅ ምእመናንና ቤተ ክርስቲያንን ያስቆጣ ድርጊት በአርባ ምንጭ ደ/መ/መድኃኔዓለም ሰበካ ጉባኤ የቀረቡ የሕዝብ አቤቱታዎች እንደደረሳቸው የገለጹት ብፁዕነታቸው የሚመለከተው አካል ለሰላም ሲባል ትልቅ ትኩረት በመስጠት መፍትሔ ሊሰጥ ይገባዋል በማለት አሳውቀዋል፡፡

ብፁዕነታቸው በተጨማሪም በዚሁ አቤቱታቸው “የዚህች ቤተ ክርስቲያንም ሆነ የሀገረ ስብከቱ አቋም ሰላምን መስበክ ነው” ያሉት ብፁዕነታቸው ከዚህች ቤተ ክርስቲያን እስከወጡ ድረስ የቤተ ክርስቲያኒቱን መገልገያ ንብረቶች (ንዋያተ ቅድሳት) ሥርዓቷንም ሆነ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ያገኙትን መዓርጋት ሊተዉና የራሳቸውን እምነት ሊያካሔዱ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ የራሳቸውን ፕሮግራም ማካሔዱን እንደማይቃወሙና የቤተ ክርስቲያን የሆኑትንም ንብረቶች እና ሥርዓቶች ሊመልሱ ይገባል ብለዋል፡፡

እሑድ ጠዋት በቦታው መረጃው የደረሳቸው የሕግ አካላት ባለመገኘታቸው ከፀረ ተሐድሶ እንቅስቃሴ ኮሚቴ፣ ከሰበካ ጉባኤ እንዲሁም ከስብከተ ወንጌል የተውጣጡ አባላትና ወጣቶች እንዲሁም ምእመናን ተሰባስበው ቅዳሴ ወደሚያካሔዱበት ቤት በመሔድ ግለሰቦቹ ሲጠቀሙባቸው የነበሩትን ንዋያተ ቅድሳት እንዲመልሱ ቢጠየቁም ፈቃደኛ ባለመሆናቸው የለበሱትን ልብሰ ተክህኖ በማስወለቅ፣ ከበሮ፣ መስቀል፣ መጻሕፍትና ሌሎች ንዋያተ ቅድሳት ይዘው ወደ አርባ ምንጭ ደ/መ/መድኃኔዓለም ሲመለሱ፣ የሕግ አካላትም በመድረስ ግለሰቦቹን በቁጥጥር ሥር በማዋል ወደ ፖሊስ ጣቢያ ተወስደዋል፡፡

ሰኞ ጠዋት የችግሩን አሳሳቢነት በመግለጽ አስፈላጊና ሕጋዊ መንገድ ተከትሎ የቤተ ክርስቲያኗ ጥያቄ እንዲመለስ በማለት በብፁዕነታቸው የተጻፈው ሁለተኛ ደብዳቤ በመያዝ ለሚመለከተው አካል ቢያመለክቱም የሚመለከተው አካል ደብዳቤውን ተቀብሎ ጉዳዩ ከባድ በመሆኑ ከዞኑና ከከተማው ኃላፊዎች ጋር መመካከር አለብን በማለቱ ክስ እስካሁን አለመመሥረቱ ተገልጿል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ሲኖዶስ እያከናወነ ስላለው  ጥረት ሲገልጹ “ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቲያናችን መገለጫ የሆኑትን ያሬዳዊ ዜማና ንዋያተ ቅድሳት ለማስጠበቅ ውይይቶችን ሲያደርግ እንደቆየና በአሁኑ ወቅትም የአእምሮ ንብረት በሚል ኮሚቴ ተቋቁሞ በጥናት ላይ ይገኛል” ብለዋል፡፡ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከትም በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ አማካይነት የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴ አዋቅሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ሥራዎችን እየሠራ እንደሚገኝ ለዝግጅት ክፍላችን ገልጠዋል፡፡

     በሕግ አካላት ቁጥጥር ሥር ውለው ከነበሩት ግለሰቦች ውስጥ አንዱ አእመረ አሸብር ሲሆን፣ ከዚህ ቀደም የሊቃውንት ጉባኤ አባል የነበረና በኑፋቄው ምክንያት የተወገዘ ግለሰብ  ነው፡፡ የካቲት ፲፩ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ጠዋት ከፖሊስ ጣቢያ እንደተለቀቁም የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

የቤተ ክርስቲያን ንዋያተ ቅድሳት እንዲከበሩ ሀገረ ስብከቱ          ለሚመለከታቸው አካላት የጻፈው ደብዳቤ

የነነዌ ሰዎች እምነት ንስሓና የጾም አዋጅ

 

መ/ር ቢትወደድ ወርቁ

ትንቢተ ዮናስ አራት ምዕራፎች ያሉት፤ እስከ ዓለም ፍጻሜ የሚነሣ ትውልድ ሁሉ ሊማርበትና ራሱን ሊያስተካክልበት የተጻፈ ታላቅ የትንቢት መጽሐፍ ነው፡፡ በዚህ የነቢዩ ዮናስ መጽሐፍ የተጠቀሱት ነቢዩ ዮናስን ጨምሮ የነነዌ ሰዎች ፣ንጉሡ ፣ዮናስ በየዋህነት ከእግዚአብሔር ፊት ወደ ተርሴስ ሊኮበልልበት የተሳፈረበት መርከብ ባለቤቶች /መርከበኞች/ እና ሌሎች ፍጥረታት ዓሣ አንበሪው፣የባሕር ማዕበሉ፣እግዚአብሔር ነቢዩ ዮናስን ያስተማረበት ትልና ቅሉ ሁሉ የነነዌ ሰዎች በኃጢአት ምክንያት ከመጣባቸው የጥፋት ዋዜማ አንስቶ ከኃጢአት ተመልሰው መዓቱ በምሕረት ቊጣው በትዕግሥት እሰከ ተለወጠላቸውና ከቅጣቱም እስከዳኑበት ጊዜ ድረስ የነበራቸው ተግባርና እግዚአብሔር የሠራላቸው የቸርነት ሥራዎች የተገለጡበት መጽሐፍ ነው፡፡

  መጽሐፉም እያንዳንዱ ቢዘረዘር ትልቅ መጽሐፍም ሊወጣው የሚችል ከመሆኑ አንጻር ያን ወደ ቤተክርስቲያን መጥተን ሊቃውንቱንና መምህራንን በመጠየቅ እንዲሁም ሌሎች ምሥጢራትን የሚያብራሩ  ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብ መረዳት እንችላለን፡፡ አሁን ግን ባለንበት ወቅት በግላዊ፤ ቤተሰባዊና ሀገራዊ አኗኗራችን ከገባንበትና ሊገጥመን ከሚችሉ ችግሮች አንጻር የነነዌ ሰዎችን ታሪክ መስተዋት አድርገን ራሳችንን እንመለከትበት ዘንድ ታሪካቸውን በአጭሩ መቃኘትና የንስሓ መንገዳቸውን መከተል ተገቢ ይሆናል ፡፡ በመጽሐፍ ያለው ታሪክ በሙሉ የተጻፈልን ለፍጹም ትምህርትና ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጀን እንሆን ዘንድ እንዲሁም ለተግሣጽ ልባችንንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ጥበብ ይጠቅማልና (፪ጢሞ ፫÷፲፮-፲፯)

                የነነዌ ሰዎች የጥፋት ዋዜማ

ለነነዌ ሰዎችና ለከተማይቱ ጥፋት ምክንያት ሊሆን የነበረው  ምን እንደነበር መጽሐፍ ሲነግረን “የእግዚአብሔር ቃል ወደ አማቴ ልጅ ወደ ዮናስ እንዲህ ሲል መጣ፤ ተነሥተህ ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፤ ክፋታቸውም ወደፊቴ ወጥቶአልና፤ በእርሷ ላይ ስበክ”(ዮናስ ፩÷፪ )ይላል፡፡ የነነዌን ከተማ “ታላቂቱ ከተማ” ያሰኛት ብልፅግናዋና እድገቷ ብቻ ሳይሆን በሥሯ የነበሩ ሰዎች ይፈጽሙ የነበረው ታላቅ ክፋት ነበር፡፡ስለዚህም የነዋሪዎቿ ክፋት እግዚአብሔርን አሳዝኖት ከክፋታቸው እንዲመለሱ የክፋት ሥራቸውን እንዲተውና ንስሓ እንዲገቡ ይነግራቸው ዘንድ ነቢዩ ዮናስን ወደ እነርሱ እንዲሄድ ላከው ፡፡ ባዕድ አምልኮትንና ጣዖትን ማስፈን፤ ለጣዖታት መስገድና መሠዋት ፣ ጥንቆላን ማስፋፋት ፣ሥር እየማሱ ቅጠል እየበጠሱ የሰዎችን አኗኗር ማጎሳቆልና ማዘበራረቅ ፣በዘፈንና አስረሽ ምችው ሰክሮ ዝሙትንና ሌሎች የሥጋ ፈቃዳትን በራስና በሌሎች ላይ ማንገሥ ነው፤ (ገላ ፭÷፲፯-፲፱)፡፡  የኃጢአት ሥራ  ከእግዚአብሔር ይልቅ ደስታና ተድላን በመውደድ ለዚያም በሰዎች መካከል ጠብን ከመዝራትና እንዲጋጩ ከማድረግ አንስቶ የራስን ጥቅም ብቻ በመመልከትም ማታለልን ሰዎች የሚጠፉበትንም መንገድ መቀየስና ለዚያም ቀንና ሌሊት በመትጋት ወደ ፍጻሜ ማድረስ ነው፤(ምሳ ፮÷፲፮-፲፱)፡፡ ክፉ ሰዎች የሚጠፉበትንና እግዚአብሔር የሚያሳዝኑበትን ሐሳብ ንግግርና ተግባራትን አጠቃሎ ይይዛል፡፡

   ክፋትንም የሚያደርግ ሁሉ በእግዚአብሔር  ዘንድ የተጠላ ነው፤ ዘዳ ፳፭÷፲፭፡፡  የነነዌ ሰዎችንም ለጥፋት ያቀረባቸውና ከተማይቱንም “በሦስት ቀን ውስጥ ትገለበጣለች” (ዮናስ ፫÷፬) እስከ መባል ያደረሳት ክፋታቸው ነው፡፡ ሰው ልቡናውን ከክፋት ካላራቀ ራሱም ይጠፋል፡፡ ክፋቱም በዙሪያው ላሉት ሁሉ ተርፎ ሌላ ጥፋትን ይወልዳል ፡፡ አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር በቀድሞው ዘመን ለእስራኤል ዘሥጋ ” ኢየሩሳሌም ሆይ ትድኚ ዘንድ ልብሽን ከክፉ ነገር እጠቢ”፤ (ኤር ፬÷፲፬ ) ማለቱም ለዚህ ነው፡፡ ዛሬም ከራሳችን አንስቶ ዙሪያችንን ስንመለከት እግሮቻችን ወደ ክፋት የሚሮጡ፤ እጆቻችንም ደምን ለማፍሰስ የሚፋጠኑና በራሳችንም የክፋት ሐሳብ እየተራቀቅን ጠቢባን ሆነናል የምንል ሰዎች በዝተናል (ምሳ ፩÷፲፮)፡፡ ልበ አምላክ ክቡር ዳዊት እንደተናገረውም “ከኃጢአታችን ተመልሰን ንስሓ ካልገባን ክፋታችን ይገድለናል”፤(መዝ ፴፫÷፳፩)፡፡ የነነዌ ሰዎች ጥፋታቸው እስኪነገራቸው ድረስ በኃጢአት ሥራ ጸንተው ይኖሩ እንደ ነበር፤ ዛሬም በክፉ ሐሳብ ንግግርና ተግባር ላይ ካለን እኛም በጥፋት ዋዜማ ላይ እንደሆን ልንረዳ ይገባናል ፡፡

                  የእግዚአብሔር ቸርነትና የንስሓ ጥሪ

የነነዌ ሰዎች በመጥፎ ምግባራቸውና ኃጢአታቸው ምክንያት ሊጠፉ ሲገባቸው የቸርነት ባለቤት አምላካችን እግዚአብሔር እንዳይጠፉ በነቢዩ ዮናስ አንደበት የቸርነቱን የንስሓ ጥሪ አሰምቷቸዋል፡፡ “ተነሥተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፤ የምነግርህንም ስብከት ስበክላት”(ዮናስ ፫÷፪) እንዲል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን እኛ ከኃጢአታችን ከተመለስን ከስሕተታችን ተምረን ለመታረምና ሕይወታችንን ለማስተካከል ከፈቀድን እንደ ወጣችሁ፤ እንደ ጠፋችሁና እንደ ረከሳችሁ ቅሩ አይልም፡፡ በበደላችንና በኃጢአታችን ካሳዘነው ይልቅ በኃዘንና በጸሎት ፍጹም በሆነ ንስሓ ከተመለስን ይደሰታል፡፡ እርሱ ብቻ ሳይሆን ቅዱሳን መላእክቱም በሰማይ ይደሰታሉ፤ “ንስሓ በሚገባ በአንድ ኃጢአተኛ ምክንያት በሰማይ መላእክት ዘንድ ታላቅ ደስታ ይሆናልና”(ሉቃ ፲፭÷፲) እንደተባለ፡፡ ስለሆነም ዛሬም በገባንበት የጥፋት መንገድ ፣ ተመቻችተንና ተደላድለን እየኖርን ካለንበት የኃጢአት መንደር በመውጣት ንስሓ በመግባት ሰላማዊ አኗኗርንና መንግሥተ ሰማያትን ገንዘብ እንድናደርግ ያስተምረናል ፡፡ “ንስሓ ግቡ፤ ኃጢአትም እንቅፋት እንዳይሆንባችሁ ከኃጢአታችሁ ተመለሱ፤ የበደላችሁትን በደል ሁሉ ከእናንተ ጣሉ፤ አዲስ ልብና አዲስ መንፈስም ለእናንተ አድርጉ፤ የእስራኤል ቤት ሆይ ስለምን ትሞታላችሁ ? የሟቹን ሞት አልፈቅድምና ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ ስለዚህ ተመለሱና በሕይወት ኑሩ” (ሕዝ ፲፰÷፴-፴፪ )እንዲል፡፡ዛሬም ቢሆን በኃጢአት እየኖርን የሚታገሠን ንስሓ እንድንገባ ነው፤ (፪ጴጥ ፫÷፱) ንስሓ ካልገባንም ቅጣት መምጣቱ የማይቀር መሆኑን ልብ ማለት ይገባናል፤(ሮሜ ፲፩÷፳፪)፡፡

የነነዌ ሰዎች መመለስ

የነነዌ ሰዎች ንስሓ እንደማይገቡና በልባቸው ትዕቢት ሞልቶ፤ ከጀመረ ይጨርሰኝ ካፈርኩ አይመልሰኝ፤ብለው በበደላቸው ጸንተው እንደሚኖሩ ሰዎች አልሆኑም ፡፡ ኃጢአታቸውና በደላቸው እንዲሁም ንስሓ ካልገቡ ሊመጣ ያለው ጥፋት ሲነገራቸው በዙፋን ካለው ንጉሥ በዐደባባይ እስካለው ችግረኛ ሁሉም በአንድነት ሆነው ነቢዩ ዮናስ የሰበከውን የንስሓ ስብከት በልቡናቸው አምነው ተቀበሉ፡፡ ማመናቸውንም ከንጉሣቸው ጋር በመሆን ለጾም አዋጅ በመንገር ገለጡ፡፡ እምነታቸውንና ጾማቸውንም በንስሓ አጅበው አለቀሱ፡፡በዚህም እግዚአብሔር ቊጣውን በትዕግሥት መዓቱን በምሕረት ለወጠላቸው ፡፡

 “የነነዌ ሰዎችም እግዚአብሔርን አመኑ፤ ለጾም አዋጅ ነገሩ፤ ከታላቁ ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ማቅ ለበሱ፤ንጉሡም ከዙፋኑ ተነሥቶ መጎናጸፊያውን አውልቆ ማቅም ለበሰ፤ በአመድም ላይ ተቀመጠ” (ዮናሰ ፫÷፭-፮) ተብሎ እንደ ተነገረ፡፡ ኃጢአታቸውን አምነው ንስሓ በማይገቡ ሰዎች እግዚአብሔር “የወደቁ አይነሡምን ? የሳተስ አይመለስምን ? ምን አድርጌሃለው ብሎ ከኃጢአቱ ንስሓ የገባ የለም …”(ኤር ፰÷፬) በማለት ይገረማል፤ ይደነቃልም፡፡ የነነዌ ሰዎች ግን በእምነታቸው፤በንስሓቸውና በጾማቸው እግዚአብሔርን አስደሰቱት፡፡ በዚህም በሐዲስ ኪዳን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ንስሓ በማይገቡ ላይ እንደሚፈርዱ ሲመሠክርላቸው “የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነሥተው ይፈርዱበታል፤ በዮናስ ስብከት ንስሓ ገብተዋልና ብሏል”፤ (ማቴ ፲፪÷፵፩)፡፡ ስለሆነም ከጥፋት እንድንድን ከክፉ ሐሳባችን፤ ንግግራችንና ተግባራችን ተመልሰን ንስሓ እንግባ ፡፡ “የንስሓ ኃዘን መዳንን፤ የዓለምም ኃዘን ሞትን ያመጣልና”፤(፩ ቆሮ ፯÷፲) እምነትን፤ ንስሓንና እውነተኛ ጾምን ገንዘብ አድርገን ለክብር ለመብቃት እንድንችል እግዚአብሔር በቸርነቱ ይርዳን፤ እመቤታችንም በምልጃዋ፤ ቅዱሳንም ሁሉ በጸሎታቸው አይለዩን አሜን!!

የሩቅ ምሥራቅ ግንኙነት ጣቢያ በህንድ ሀገር ፭ተኛ ዙር ሐዊረ ሕይወት አደረገ

         ሕይወት ሳልለው

 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ  የማኅበረ ቅዱሳን የሩቅ ምሥራቅ ግንኙነት ጣብያ በህንድ ሀገር የሚኖሩ አባላቱንና ምእመናንን በማስተባበር ከጥር ፲፭ እስከ ጥር ፳፩ ቀን  ፳፻፲፩ ዓ/ም ወደ ኬሬላ ፭ተኛውን ዙር የሐዊረ ሕይወት ጉዞ አካሄደ፡፡

በአባ ጂኦ ዮሴፍ መሪነት ፺፱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች መንፈሳዊ ጉዞ አድርገዋል፡፡ በህንድ ኬሬላ ግዛት ኮታይም ከተማ ወስጥ በሚገኙ ቅዱስ ጊዮርጊስና የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን  ማርታ ማርያም ኦርቶዶክስ ሴርያን ቤተ ክርስቲያን፣ የመነኮሳት ገዳም፣ ማር ባስልዮስ ገዳም እንዲሁም የኦርቶዶክስ ቲኦሎጂካል (ነገር መለኮት) ሴሚናሪ እና የማር ባስልዮስ ክርስቲያን የኢንጅነሪንግና ቴክኖሎጅ ኮሌጅንም በዋነኛነት ጎብኝተዋል፡፡

ኮትያም ወደሚገኘው ኦርቶዶክስ መንፈሳዊ ኮሌጅ በተደረገው ጉዞ ላይ ለምእመናኑ፤ “የቤተ ክርስቲያን ምሥጢራት” በሚል ርእስ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ከህንድ ቤተ ክርስቲያን ጋር ያነጻጸረ ትምህርት በዶ/ር ረጂ ማቲው ተሰጥቷል :: በዚሁ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በተማሪዎች የበገና መዝሙርና በህንዳውያን ዘማሪዎች በህንድ ቋንቋ የተዘጋጀ መዝሙር በጋራ ቀርቧል፡፡ በጉዞው ላይ የነበሩት አባ ኦ ቶማስም “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በባህልና በበርካታ ንዋያተ ቅድሳት የታጀበች ናት” ሲሉ አድነቀዋል፡፡  በሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ የተመሠረተችው ዘቫላካራ ማርታ ማርያም ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በቀድሞው የኢትዮጵያ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እንደተጎበኘ አባ ጂኦ ለምእመናኑ አስታውቀዋል፡፡፡፡

ከማእከሉ በአውቶብስ ሦስት ሰዓት፤ በጀልባ አንድ ሰዓት ተኩል የሚፈጀው እና በደሴት ወደተከበበው የቅዱስ ቶማስ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጉዞም ያደረጉ ሲሆን ቤተ ክርስቲያኗ በቁጥር ትንሽ አባላት እና ጥቂት አገልጋይ እንዳሏትም አስገንዝቧቸዋል፤ ከዚህ ባሻገር በቅዱስ ቶማስ የተመሠረተችው የቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በወቅቱ ሲጠቀሙበት የነበሩት ባህላዊ ቅርሶችና ንዋየ ቅድሳትን ጎብኝተዋል፡፡ የጉዞው ተሳታፊዎችም “ከቦታው በረከትን አግተኝናል” ሲሉም የምስክርነታቸውን ቀል ሰጥተዋል፡፡

በከበሮ፣ በጸናጽል፣ በመቋሚያና በበገና ህብር የቀረበው ያሬዳዊ ዝማሬ መርሐ ግብር ላይ ሰፊ ማብራሪያ የሰጠው መ/ር ሳምሶን ስለመሳሪያዎቹ ለህንድ አባቶችና ለምእመናን ገለጻ አድርጓል፡፡ ስለአጠቃላይ መርሐግብሩ ከተሳታፊዎች ሐሳብ ተሰብስቦ፣ የአጋጠማቸው ችግሮች ላይ ውይይት በማድርግና የመፍተሔ አቅጣጫ በመስጠት፣ ፭ተኛው ዙር ሐዊረ ሕይወት  በሰላም ተጠናቋል፡፡

 

 

በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ለስብከተ ወንጌል የሚሰማሩ ሰባክያነ ወንጌል ተመረቁ

 

                               ተመራቂዎች በከፊል

በእንዳለ ደምስስ

  በማኅበረ ቅዱሳን አዳማ ማእከል ሥር የሚገኘው የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል ከአዳአ ወረዳ ቤተ ክህነት፤ ከበጎ አድራጊ ምእመናንና ማኀበራት ጋር በመተባበር በሁለተኛ ዙር ገጠር ተኮር የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ለማጠናከር በአፋን ኦሮሞ ቋንቋ ለ፰ ወራት በሂዲ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወካህን መልከ ጼዲቅ አብያተ ክርስቲያናት ያሰለጠናቸውን ፴፬ ተተኪ ሰባክያነ ወንጌል ጥር ፭ ቀን ፳፻፲ወ፩ ዓ.ም የአድአ ወረዳ ቤተ ክህነት ሊቀ ካህን፤የየአጥቢያዎቹ አስተዳዳሪዎች፣ በጎ አድራጊ ምእመናንና የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል አባላት በተገኙበት አስመረቀ፡፡

ሰልጣኞቹ ከ፲ አጥቢያዎች የተመለመሉ ሲሆን፣፱ የትምህርት አይነቶችን ሲከታተሉ መቆየታቸውን፣አብዛኛዎቹ ሰልጣኞችም ካህናትና ዲያቆናት መሆናቸው አቶ ሀብታሙ ዘውዱ የወረዳ ማእከሉ ሰብሳቢ በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ ባቀረቡት ሪፖርት ገልጸዋል፡፡ካህናቱና ዲያቆናቱ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ስልጠናውን መውሰዳቸውም ለወደፊቱ ከስብከተ ወንጌል አገልግሎት በተጨማሪ የቤተ የመቅደስ አገልግሎትን ለማጠናከር መልካም አጋጣሚ እንደሆነና አብያተ ክርስቲያናቱም ለሥልጠና የሚሆኑ ቦታዎችን በማመቻቸት የነበራቸው ተሳትፎ ታላቅ እንደነበር ጠቅሰዋል፡፡

“የሥልጠናው ዋና ዓላማ ምእመናን በሚያውቁት ቋንቋ በማስተማር ከነጣቂ ተኲላዎች ለመጠበቅ ነው፡፡ የሥልጠናው ሙሉ ወጪም ብር 123,348.90 (አንድ መቶ ሀያ ሦስት ሺህ ሦስት መቶ ዐርባ ስምንትብር ከዘጠና ሳንቲም) በባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ የቀድሞ ግቢ ጉባኤ ተመራቂዎች የተሸፈነ ነው” ብለዋል፡፡ የቀድሞ ተመራቂዎቹ ያበረከቱት አስተዋጽኦ በአርአያነት የሚጠቀስ መሆኑን የጠቆሙት ሰብሳቢው ይህንን መልካም ተሞክሮ ሌሎችም ማኀበራት በመውሰድ ሊማሩበት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

ለተመራቂዎቹ ባስተላለፉት መልእክትም “ሰልጣኞች ከምረቃ በኋላ ትምህርት በቃን ሳትሉ ከሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እግር ሥር  ቁጭ ብላችሁ መማር፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ ይገባችኋል፡፡ ዋናው ዓላማችሁንም ባለመዘንጋት ስብከተ ወንጌል ባልተስፋፋባቸው ቦታዎች እየተዘዋወራችሁ ቤተ ክርስቲያን የጣለችባችሁን ኃላፊነት እንድትወጡ ይጠበቅባችኋል” በማለት በሪፖርታቸው አስገንዝበዋል፡፡

የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል አባላት ከግልና ከማኀበራዊ ጉዳያቸው ቅድሚያ ለሥልጠናው ልዩ ትኩረት መስጠታቸው፣ የአዳአ ወረዳ ቤተ ክህነት ለአገልግሎት የሚያስፈልጉ ነገሮችን በማሟላትና ለአጥቢያዎች መመሪያ በመስጠት ስልጠናው የተሳካ እንዲሆን ታላቅ አስተዋጽዖ ማበርከታቸውን በመግለጽ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

የወረዳ ቤተ ክህነቱ ሊቀ ካህን መልአከ ፀሐይ ቀሲስ እንዳለ ሐረገወይን ባስተላለፉት መልእክትም የወረዳ ማእከሉ ለስበከተ ወንጌል አገልግሎት መስፋፋት የሚሰጠውን አገልግሎት አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ያሳሰቡ ሲሆን ለተመራቂዎችም “በቋንቋ ምክንያት የሚጠፋውን ትውልድ ከሞት ወደ ሕይወት የመመለስ አደራ አለባችሁ” ብለዋል፡፡

የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል ከአድአ ወረዳ ቤተ ክህነት፣ ከበጎ አድራጊ ምእመናንና ማኅበራት ጋር በመተባበር በአፋን ኦሮሞ ቋንቋ ተተኪ ሰባኪያነ ወንጌል ለማፍራት ፕሮጀክት ቀርጾ በመጀመሪያው ዙር በድሬ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ከ፰ አጥቢያዎች የተመለመሉትን ፳፫ ሰልጣኞችን ለስምንት ወራት አሰልጥኖ የካቲት ፳፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በአባቶች ቡራኬ አስመርቋል፡፡

ምንጭ፤ምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 26ኛ ዓመት ቊ8ቅጽ 26ኛ ቊጥር 398 ከጥር 1-15 ቀን2011ዓ.ም

 

 

 

በቃጠሎ የወደመውን ቤተ ክርሰቲያን ለመገንባት እንቅስቃሴ ተጀመረ

 

በእንዳላ ደምስስ

ጥር 15 ቀን 2011 ዓ.ም በቃጠሎ የወደመውን የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያንን ለመገንባት እንቅስቃሴ መጀመሩን ሊቀ ኅሩያን መ/ር ወጋየሁ ደምሴ የባሌ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ዋና ጸሐፊ ገለጹ፡፡

“በቃጠሎው ቤተ ክርስቲያኑ ሙሉ ለሙሉ ወድሞ ነው የደረስነው፡፡ ሕዝቡም ከፍተኛ ሐዘን ነው የተሰማው፡፡ ሁላችንም ልባችን ተሰብሮ በዕንባ ስንራጭ ነበር፡፡ ነገር ግን ሕዝቡ አልቅሶ ብቻ አልተበተነም፡፡ዕንባውን አብሶ ገንዘብ የማሰባሰቡን ሥራ በመጀመር የመፍትሔ እርምጃ ነው የወሰደው፡፡” ሲሉ የገለጹት የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ ናቸው፡፡ሀገረ ስብከቱ ካህናቱን፣ የሰበካ ጉባኤ አባላትን፣ የወረዳ ቤተ ክህነት ተወካዮችንና የሀገር ሽማግሌዎችን በማሰባሰብ ዘጠኝ አባላት ያሉት የሕንጻ አሰሪ ኮሚቴ በማዋቀር ቤተ ክርስቲያኑን በድጋሚ ለመገንባት ገንዘብ የማሰባሰብ ሥራው መጀመሩንና እስከ አንድ ሚሊዮን ብር ማሰባበሰብ መቻሉንም ጠቁመዋል፡፡

ከገንዘብ በተጨማሪም ምእመናን የአንገት ሐብላቻውንና የጣት ቀለበታቸውን በመስጠት፣ እናቶች ከመቀነታቸው እየፈቱ በመንፈሳዊ ስሜትና ቁጭት አቅማቸው የፈቀደውን ያህል ማበርከታቸውን ለዝግጅት ክፍላችን ተናግረዋል፡፡

ሙስሊሙ ኅብረተሰብም በቤተ ክርሰቲያኑ መቃጠል ከፍተኛ ሐዘን እንደተሰማውና በቦታው በመገኘት ገንዘብ በመለገስ፣ እንዲሁም የግንባታ እቃዎችን ለመስጠት ቃል በመግባት መሳተፋቸውን፣ ቤተ ክርስቲያኑን ለማሠራትም በመስጊድ ውስጥ ሙስሊሙን በማስተባበር ገንዘብ ለማሰባበስብ ጥረት እያደረጉ እንደሚገኙ የሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ዋና ጸሐፊ ተናግረዋል፡፡

“በዛሬው ውሏችንም ለተቋቋመው የሕንጻ አሰሪ ኮሚቴ እወቅና ለመስጠት ሰበካ ጉባኤው ለወረዳው ቤተ ክህነት፣ የወረዳ ቤተ ክህነቱም ለሀገረ ስብከቱ ደረጃውን ጠብቆ በደብዳቤ በመጠየቅ እውቅና ተሰጥቷቸዋል፡፡” ያሉት ሊቀ ኅሩያን መ/ር ወጋየሁ የባንክ ሒሳብ (አካውንት) በመክፈትም ሕጋዊነት ባለው አሠራር ገቢ የማሰባሰብ ሂደቱ እንደቀጠለ ገልጸዋል፡፡

አገልግሎትን በተመለከተም ቤተ ክርስቲያኑ የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ስላለው ከሰበካ ጉባኤውና ከሕንፃ አሰሪ ኮሚቴው ጋር በመመካከር አዳራሹን በማመቻቸት ሙሉ የቤተ ክርስቲያኑ አገልግሎት ማለትም ኪዳንና ቅዳሴ ሳይቋረጥ መቀጠሉንና የቃጠሎውን መንስኤ በተመለከተም የሕግ አካላት እያጣሩ መሆኑን ለዝግጅት ክፍላችን ገልጸዋል፡፡

በባሌ ሀገረ ስብከት የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ተቃጠለ

በእንዳለ  ደምስስ

በባሌ ሀገረ ስብከት ሮቤ ከተማና አካባቢው ወረዳ ቤተ ክህነት ሥር የሚገኘው የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ዛሬ ጥር 15 ቀን 2011 ዓ.ም ከረፋዱ 5፡00 ሰዓት ላይ ለጊዜው ባልታወቀ መንስኤ መቃጠሉን መ/ር ያሬድ ገ/ማርያም የወረዳው ቤተ ክህነት ጸሐፊ ገለጹ፡፡

የቃጠሎው መንስኤና የደረሰውን ጉዳት በተመለከተ በመጣራት ላይ እንደሚገኝ የገለጹት መ/ር ያሬድ፤ ቤተ ክርስቲያኑ በቃጠሎው ምክንያት ሙሉ ለሙሉ መውደሙንና በአገልጋዮችና በአካባቢው ምእመናን ጥረት ታቦቱን ብቻ ማዳን መቻሉን ለዝግጅት ክፍላችን ተናግረዋል፡፡ዝርዝሩን እንደደረሰን እናቀርባለን፡፡

 

በጥምቀት በዓል የሃይማኖት አባቶች የሰላም ጥሪያቸውን አስተላለፉ!

                                                                                                        ሕይወት ሳልለው
የጥምቀት በዓል አከባበር በጃንሜዳ እና በተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት በድምቀት በተከበረበት ቀን፤ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ለቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ባስተላላፉት መልእክት ላይ ምእመናን በተለይም ወጣቶች በፍቅርና በመቻቻል መኖር እንዳለባቸው አሳሰቡ፡፡“የዛሬ ፵ ዓመት የሆነውን ዓይነት አካሄድና ታሪካዊ ስሕተት እንዳትፈጽሙ ተጠንቀቁ! የምትሹትንና የምትመኙትን ማግኘት የምትችሉት አንድነትና ሰላም እስካለ ብቻ ነው፡፡ አርቆ በማየትና አስተውሎ በመራመድ፤በትዕግሥትና በመቻቻል ሳይሆን በኃይልና በጉልበት የምንፈልገውን ማግኘት እንችላለን ብላችሁ ከሆነ ሁሉንም ልታጡ ትችላላችሁና አስተውሉ!” በማለት ገልጸዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ፤ብፁዕ አቡነ ኒቆዲሞስ ፤ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን ጨምሮ፤እንዲሁም የባሕልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶክተር ኂሩት ካሣው፤ ረ/ፕሮፌሰር ነቢዩ ባዬ የአዲስ አበባ ከተማ ባሕልና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት ኃላፊ እና ከተለያዩ ሥፍራዋች ለመጡ ምእመናን መልካም የጥምቀት በዓልን የተመኙት ፓትርያኩ፤ ይህ በዓል የንስሓ ጥሪ መሆኑንም አስታውሰዋል፡፡‹‹መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሓ ግቡ››፤ብሎ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ እንዳስተማረን፤በዚህ አስከፊ ዘመን የንስሓን አስፈላጊነት መረዳትና መተግበር እንዳለብን አሳስበዋል፡፡
በዓለ ጥምቀት በዋነኛ የመዳን ሥርዓት መጀመሪያ መሆኑና ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጥር ፲፩ ቀን በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቆ እኛ እንድንጠመቅ እንዳስተማረን ‹‹ወውእቱ ያጠምቀክሙ በመንፈስ ቅዱስ ወበእሳት፤ እርሱ በመንፈስ ቅዱስና በእሳት ያጠምቃችኋል፤››ተብሎ በሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ ፫ ቁጥር ፲፮ ላይ እንደ ተገለፀውም ለእኛ ድኅነት ሆኖልናል፡፡

‹‹ጥምቀት ማለት ሰፋ ያለ ትርጒም ቢኖረውም ምሥጢራዊ ትርጒሙን ጠቅለል አድርገን ስንመለከተው መንፃት፤መለወጥ፤ መሻገር፤ አዲስ ሕይወት፤ አዲስ ልደት፤ አዲስ ምሕረት የሚሉትን ሐሳቦች ያመሰጥራል›› በማለትም ቅዱስ ፓትርያርኩ አብራርተዋል፡፡ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ማርቶማ የሕንድ ማላንካራ ኦርቶዶክስ ሶርያ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ፤የቅዱስነታቸውን ሐሳብ በመደገፍ እንዲህ በማለት መልካም ምኞታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ማርቶማ

‹‹ይህ በዓል የብርሃን በዓል ቢሆንም እኛ እንደምናውቀው ዓለማችን በድቅድቅ ጨለማ የምትገኝ ሲሆን ለዚህ ጨለማ ብርሃን ያስፈልገዋል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለዓለም ተስፋ ናት፡፡ ምክንያቱም ይህን የመሰለ በዓል በየትኛውም ዓለም አይከበርምና፡፡እኛም በዚህ ታላቅ በዓል ወቅት በጸሎት ከእናንት ጋር ነን፤››በማለት ከማጽናናታቸውም በተጨማሪ በክርስቲያኖች መካከል መልካም የሆነና የጠነከረ ግንኙነት ሰላም እንዲኖር ያደረገ እግዚአብሔርን ዘወትር እንደሚያመሰግኑና እግዚአብሔር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንዲጠብቅልንና ኢትዮጵያን እንዲባርክ በመመኘት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የሊቃውንቱ ምንጭ እንዳይደርቅ ደቀ መዛሙርትን ማፍራት እንደሚገባ ተገለጸ

 

ተመራቂ ደቀ መዛሙርት

ዲ/ን ዘአማኑኤል አንተነህ

     የሊቃውንቱ ምንጭ እንዳይደርቅ ደቀ መዛሙርትን ማፍራት እንደሚገባ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርሰቲያን የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ገለጹ፡፡

ብፁዕነታቸው ይህንን ቃል የተናገሩት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በጎንደር ከተማ የደብረ ኃይል ወደብረ ጥበብ በዓታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ለሦስት ተከታታይ ዓመታት የአቋቋም ትምህርት ሲከታተሉ የቆዩ ፶፬ ደቀ መዛሙርት ጥር ፫ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም. ሲያስመርቅ ባስተላለፉት መልእከት ነው፡፡

በምርቃት መርሐ ግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስን ጨምሮ ብፁዕ አቡነ ዮሐንስ የብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ረዳት ሊቀ ጳጳስ የተገኙ ሲሆን፣ደቀ መዛሙርቱ ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳቱ እጅ የአቋቋም የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ለደቀ መዛሙርቱ ባስተላለፉት መልእክት “እናንተ የምድር ጨው ናችሁ! ተመርቃችሁ ስትወጡ ብዙ ነገር ይጠበቅባችኋል፡፡ ጨው ሁናችሁ ዓለሙን የማጣፈጥ ኃላፊነት አለባችሁ” በማለት ተመራቂ ደቀ መዛሙርቱ በተማሩት ትምህርት ወንበር ዘርግተው በማስተማርና ለምእመናን ትምህርተ ወንጌልን በመስጠት በተለይም ለገጠሪቱ ቤተ ክርስቲያን በመድረስ የተጣለባቸውን አደራ እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡

    ብፁዕነታቸው አያይዘውም “አሁን በዝታችሁ ትታያላችሁ፡፡ነገር ግን በአብያተ ክርስቲያናት ስትከፋፈሉ ቊጥራችሁ አነስተኛ ነው፡፡አሁንም ብዙ መሥራት፣መማር፣ ማስተማር እና የሊቃውንቱ ምንጭ እንዳይደርቅ ደቀ መዛሙርትን ማፍራት ይገባችኋል” ብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ዮሐንስ በበኩላቸው “ህየንተ አበዊኪ ተወልዱ ለኪ ደቂቅ፣ በአባቶችስ ፈንታ ልጆች ተወለዱልሽ” በማለት የቅዱስ ዳዊትን ቃል መነሻ በማድረግ ለደቀ መዛሙርቱ ባስተላለፉት መልእክት “እናንተ ደቀ መዛሙርት የዓለም ብርሃን ናችሁ፣ከዚህ ወጥታችሁ  አብያተ ክርስቲያናትን ሀገራችሁን በቅንነት በተሰጣችሁ አደራ እንድታገለግሉ አደራ እንላለን” ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የአቋቋም ምስክር ጉባኤ ቤቱ መምህር መጋቤ አእላፍ ክቡር ጥላሁን ያፈሯቸው ደቀ መዛሙርት የተማሩትን ትምህርት በተግባር ይተረጉሙ ዘንድ ከቤተ ክርስቲያን አባቶች ድጋፍ ሊደረግላቸው እንደሚገባ በመግለጽ “እነዚህ ደቀ መዛሙርት ዛሬ ተመርቀዋል፤ነገር ግን እየለመኑ ተምረው እየለመኑ መኖር የለባቸውም፡፡በርካታ ደቀ መዛሙርት ከትምህርት ገበታቸው የሚሰደዱት ሥራ አላገኝም እያሉ ነውና እንደ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች ሁሉ ቅዱስ ሲኖዶስ በየቤተ ክርስቲያኑ የሚመደቡበትን መንገድ ቢያመቻች ጥሩ ነው” ሲሉ አሳስበዋል፡፡

ክቡር መምህር መጋቤ አእላፍ  በጉባኤ ቤቱ የሚታየውን ችግር ሲያስረዱም “ማኀበረ ቅዱሳን ለጉባኤ ቤቱ ዘመናዊ ቤት ሰርቶልናል ነገር ግን አሁንም የሠርከ ኀብስቱ እጥረት አሳሳቢ ስለሆነ ለተማሪው ፍልሰት ምክንያት እየሆነብን ነውና መፍትሄ እንሻለን፡፡ደቀ መዛሙርቱ የሚማሩት ከየሀገራቸው ትንንሽ ልጆችን እያስመጡ ልጆቹ በየመንደሩ በመንቀሳቀስ “በእንተ ስማ ለማርያም”ብለው ምግብ ያመጡላቸዋል፡፡እነሱ ደግሞ እነዚህን ልጆች ያስተምሯቸዋል፡፡ አብያተ ክርስቲያናት ለአብነት ትምህርት ቤቶች ከዚህ በላይ ትኩረት ሰጥታ መሥራት አለባቸው ”ሲሉ ገልጸዋል፡፡

 ማኀበረ ቅዱሳን ለጉባኤ ቤቱ ባለ ሁለት ፎቅ ሕንፃ በ፳፻፰ ዓ.ም ሠርቶ ያስረከበ ሲሆን፣ ከሕንፃው በተጨማሪ ለ፶፭ ተማሪዎች ለእያንዳንዳቸው በየወሩ የ፫፻፹፭ ብር ድጋፍ ያደርጋል፤ ቤተ ክህነትም ለ፴ ተማሪዎች ለእያንዳንዳቸው ፹፬ ብር በየወሩ ይደጉማል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ለጉባኤ ቤቱ ያሠራው ሕንፃም ቤተ መጻሕፍት፣ ክሊኒክ፣ የመምህር ቢሮ፣ ምግብ ቤት፣ መማሪያ ክፍልና መኖሪያ ለደቀ መዛሙርቱ ማሟላቱም በደቀ መዛመርቱ የምርቃት መርሐ ግብር ላይ ተገልጿል፡፡

ጉባኤ ቤቱ በርካታ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን ያፈራ ሲሆን፤ ለአብነት ያህል አለቃ ገብረ ሐና፣መሪጌታ ሐሴት፣መሪጌታ ገብረ ማርያም፣ መሪጌታ ገብረ ዮሐንስ፣ መሪጌታ አሚር እሸቱ፣ መሪጌታ ላቀው፣ መምህር ክፍሌ ወልደ ፃድቅ፣ መጋቤ አእላፍ ሄኖክ ወልደ ሚካኤል እና አሁን በማስተማር ላይ የሚገኙት መጋቤ አእላፍ ክቡር ጥላሁን እና ሌሎችም ይጠቀሳሉ፡፡ በጉባኤ ቤቱም ማኅተሙን ለማግኘት ከሁለት እስከ ሦስት ዓመት ይፈጃል፡፡ በጉባኤ ቤቱ ከ፪፻ ያላነሡ ደቀ መዛሙርት በትምህርት ገበታ ላይ የሚገኙ ሲሆን፣ በየዓመቱም የደቀመዛሙርቱ ምርቃት አይቋረጥም፡፡

አሁን በማስተማር ላይ የሚገኑኙት መጋቤ አእላፍ ክቡር ጥላሁን ከመጋቤ እእላፍ ሄኖክ ወልደ ሚካኤል በ፲፱፻፺፯ ዓ.ም ወንበሩን በመረከብ እስከ አሁን ድረስ ከ፲፻ በላይ የሚሆኑ የአቋቋም መምህራንን አፍርተዋል፡፡

በብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ እና በብፁዕ አቡነ ዮሐንስ ትምህርተ ወንጌል እና ቃለ ምዕዳን፣ በተጨማሪም በደቀ መዛሙርቱ ቅኔ እና ያሬዳዊ ወረብ ቀርቧል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይም የሀገረ ስብከቱ የመምሪያ ሓላፊዎች፣ የአብነት መምህራን እና ምእመናንም ተገኝተዋል፡፡

 

የተሰጠህን አደራ ጠብቅ (፩ጢሞ. ፮:፳) (በእንተ ላ ሊበላ)

ብዙአየሁ ጀምበሬ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ለሀገራችን ያበረከተችው አስተዋጽኦ በብዙ ዐውድ የሚገለጽ እና መጠነ ሰፊ ነው፡፡ ከእነዚህም መካከል በቋንቋ፤ በባሕል፤ በአለባበስ፤በሥነ ጽሑፍ፤ በኪነ ጥበብ፤ በኪነ ሕንፃ እና በቅርጻ ቅርጽ ዘርፍ የተደረጉት አስተዋጽዖዎች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ይህች ስንዱ የሆነች ቤተ ክርስቲያን ተፈጥሮአዊ የሆኑ የዕፀዋት ዝርያዎችን በአግባቡ በመጠበቅ እና በመንከባከብ የሀገር ሕልውናን በማስጠበቅ እና ተፈጥሮ ዑደቱ ሳይዛባ እንዲቀጥል በማድረግም እጅግ የጎላ አገልግሎቷን በማስመዝገብ ላይ ናት፡፡ ዝርያቸው ሊጠፉ የተቃረቡ የዕፀዋት ዓይነቶችን ጠብቃ ያቆየች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ናት፡፡ በሥነ ጽሑፍ ዘርፍም ቢሆን ሀገራችን የራሷ ፊደል እንዲኖራት እና ለሥልጣኔ ጉልህ አስተዋጽዖ የሚያበረክቱ መጻሕፍት ባለቤት እንድትሆን ረድታለች፡፡

የንባብ ባሕልን ከሥር መሠረቱ በማጎልበት ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ምሳሌ ሊሆን የሚችል የአብነት ትምህርት ቤቶችን በማቋቋም አያሌ ምሁራን እንዲፈሩበት ጉልህ ሥራን ሠርታለች፡፡ በዜማውም ዘርፍ የዜማ ሥርዓትን ለዓለም በቀዳሚነት በማስተዋወቅ፣ ሰማያዊ ሥርዓት ያለውን ዜማ በሊቁ ቅዱስ ያሬድ አማካኝነት አበርክታለች፡፡ በኪነ ሕንፃ ዘርፍ ደግሞ በዓለማችን ታሪክ በየትኛውም ክፍላተ አህጉራት የማይገኙ እና ደግመው መሠራት ያልተቻሉ ልዩ ልዩ የኪነ ሕንፃ ጥበቦችን በውስጧ የያዘች፤ ያስተዋወቀች እና ጠብቃ ያቆየች ናት፡፡
ለምሳሌ ያህል የአክሱም ሐውልት፤ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት እና የንጉሥ ፋሲለደስን ግንብ መጥቀስ በቂ ነው፡፡ ይህች ቤተ ክርስቲያን እነዚህን ቅርሶች ለሀገራችን እና ለመላው ዓለም ብታበረክትም ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ለእነዚህ ቅርሶች ተገቢው ጥበቃ እና እንክብካቤ ባለመደረጉ የተነሳ ለከፍተኛ ጉዳት እየተጋለጡ ይገኛሉ፡፡ እንዴት እንደተሠሩ መረዳት እንኳን ግራ እስኪገባን ድረስ አስተውለንና የአሠራር ጥበባቸውን አድንቀን ሳናበቃ በቂ ጥበቃ እና እንክብካቤ ሳይደረግላቸው በመቅረቱ አብዛኞቹ ቅርሶች ለአደጋ እንዲጋለጡ እና ሥጋት ውስጥ እንዲገቡ ሆነዋል፡፡ ይህ ደግሞ የታሪክ ተወቃሽ እንድንሆን ያደርገናል፡፡ ከእነዚህ በአሳሳቢ ሁኔታ ውስጥ ካሉት ቅርሶች መካከል በአሁኑ ሰዓት በከፋና እጅግ በአሳሳቢ በሆነ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙት የላልይበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ናቸው፡፡

የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት የተፈለፈሉት በ፲፪ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በንጉሥ ላላሊበላ አማካኝነት ነው፡፡ ቅዱስ ላሊበላ ታኅሣሥ ፳፱ ቀን በ፲፪ ኛውመቶ ክፍለ ዘመን መግቢያ ከእናቱ ኪርወርና እና ከአባቱ ከዛን ሥዩም በላስታ ሮሐ ቤተ መንግሥት ዋሻ እልፍኝ ውስጥ ተወልዷል፡፡ በተወለደ ጊዜም በንብ ስለተከበበ እናቱ ማር ይበላል “ላል ይበላል” ብላ ስም መጠሪያ ይሆነው ዘንድ አውጥታለታለች፡፡ ማር ከፍተኛ ደረጃ ያለው ተወዳጅ ምግብ ስለሆነ መልካም፤ ስመ ጥር፤ ታላቅ ንጉሥ ይሆናል ስትል ላልይበላ ብላዋለች፡፡

በሌላ መልኩም “ላልይበላ ብሂል ንህብ አእመረ ጸጋሁ ብሂል፣ ላልይበላ ማለት ንብ ጸጋውን (ገዢውን) ዐወቀ” ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ላልይበላ የብሉያትን እና የሐዲሳትን የትርጓሜ መጻሕፍት ጠንቅቆ የተማረ ነው፡፡ ውቅር አብያተ ክርስቲያናቱን ከአንድ ወጥ ዓለት በመፈልፈል ያነጸው ንጉሡ ከዐሥራ አንዱ የዛጉዌ ሥርወ መንግሥት ነገሥታት መካከል አንዱ ሲሆን በኢትዮጵያ ለ፵ ዓመታት ያህል ነግሦ እንደነበር የታሪክ መዛግብት ያስረዳሉ፡፡(ምንጭ፡ ገድለ ቅዱስ ላልይበላ ሰኔ 2003 ዓ.ም ገጽ13)፡፡የቅዱስ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት በቊጥር ዐሥራ አንድ ሲሆኑ፣እነርሱም፡- ቤተ-ማርያም፤ ቤተ-መድኃኔ ዓለም፤ቤተ-ደናግል፤ ቤተ-መስቀል፤ ቤተ-ደብረሲና፤ቤተ-ጎልጎታ፤ ቤተ-አማኑኤል፤ቤተ-አባሊባኖስ፤ቤተ-መርቆሬዎስ፤  ቤተ-ገብርኤል ወሩፋኤል፤ ቤተ-ጊዮርጊስ የተሰኙ ናቸው፡፡
ቤተ-ደብረሲና በመባል የሚጠራው ፍልፍል ቤተ ክርስቲያን ቤተ-ሚካኤል በመባልም ጭምር ይታወቃል፡፡ ከእነዚህ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት መካከልም በቅድሚያ የታነጸው ቤተ-ማርያም የተሰኘው ሲሆን በወርኃ ታኅሣሥ በ፳፱ኛው ቀን የጌታችን የአምላካችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል እና የቅዱስ ላሊበላ የልደት በዓል “ቤዛ ኲሉ” የሚዘመርበት ቤተ መቅደስ ነው፡፡ ከእነዚህ ፍልፍል አብያተ ክርስቲያናት መካከል በመጠን ከሁሉም የሚልቀው እና ግዙፍ የሆነው ቤተ-መድኃኔዓለም ሲሆን በዚሁ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ”አፍሮ አይገባ” በመባል የሚታወቀው የመስቀል ይገኛል፡፡
የላሊበላ አብያተ ክርስቲያናት ሲነሱ በሁላችን አእምሮ የሚታወስና ትዝ የሚለን ከላይ ሲታይ በመስቀል ቅርጽ የታነጸው እና ከሌሎች በተለየ የኪነ ሕንፃ ጥበብ የተወቀረው ቤተ-ጊዮርጊስ ነው፡፡ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ተሠርተው ለመጠናቀቅ ፳፫ ዓመታትን ፈጅተዋል፡፡ ውቅር አብያተ ክርስቲያናቱ በዓለም ላይ በሰው ልጆች ታሪክ ውስጥ ከተገለጡት አስደናቂ የኪነ ሕንፃ ጥበቦች መካከል ወደር እና አቻ የማይገኝላቸው ናቸው፡፡
የአብያተ ክርስቲያናቱ የኪነ ሕንፃ ንድፍ (Design) እና ሥነ ውበት (Aesthetics) በአስደናቂ ሁኔታ ተጣምሮ የተዋሐደበት ልዩ የመንፈሳዊ ምሕንድስና አሻራም የታየበት ነው፡፡እስካሁን ባለው የኪነ ሕንፃ እና የምሕንድስና ታሪክ ውስጥ እንደ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ዓይነት የረቀቀ ጥበብ የታየበት ሥራ በየትኛውም የዓለም ክፍል ላይ እንዳልተሠራ መዛግብት ያስረዳሉ፡፡ ፡፡ የአሠራሩ መንገድ ከታች ከመሠረት ሳይሆን ከላይ ከጣራ መጀመሩ በዋነኛነት ልዩ ያደርገዋል፡፡ ከዓለት መፈልፈላቸው እና በሥራቸው የውኃ ማጠራቀሚያ ቋት መያዛቸውም በራሱ ለየት ያደርጋቸዋል፡፡ ንጉሥ ላሊበላ ይህንን አስደናቂ የኪነ ሕንፃ ሥራ ሲሠራ ከፈጣሪው ከልዑል እግዚአብሔር ባገኘው መንፈሳዊ ጥበብ እንደሆነ የታሪክ ድርሳናት ይገልጣሉ፡፡
እግዚአብሔር አምላክ ለመረጣቸው እና አካሄዳቸውን ከእርሱ ጋር ላደረጉ መልካም ሰዎች ጥበብን ያድላል፤ ለዚህም የባስልኤል እና የኤልያብን ታሪክ ከመጽሐፍ ቅዱስ ማስታወስ ያሻል፡፡ “ለመቅደስም ማገልገያ ሥራ ሁሉ ያደርጉ ዘንድ እንዲያውቁ እግዚአብሔር ጥበብንና ማስተዋልን የሰጣቸው ባስልኤልና ኤልያብ በልባቸው ጥበበኛዎችም ሆኑ፣ እግዚአብሔር እንዳዘዘው ነገር ሁሉ አደረጉ፡፡ ሙሴም ባስልኤልና ኤልያብን እግዚአብሔርም በልቡ ጥበብን ያደረገለትን በልብ ጥበበኛ ሰው ሁሉ ሥራውንም ለመሥራት ይቀርብ ዘንድ ልቡ ያስነሣውን ሁሉ ጠራቸው፡፡ (ዘጸ.፴፮፡፩-፩) እንዲል፡፡
የውቅር አብያተ ክርስቲያናቱ መሠረታዊ የጂኦሜትሪያዊ ልኬት(Geometric proportion) የንድፍ ሥርዓትን የጠበቁ ናቸው፡፡ በሥጋዊ ምርምር ሊደረስባቸው አይችልም፡፡ለዚህም ነው ልዩ የከበረና ዘመን የማይሽረው የኪነ ሕንፃ ቅርስ መሆን የቻለው፡፡ ለዚህም ነው የዓለም ዜጎች ያከበሩት እና በየጊዜው ለመጎብኘት ወደ ሀገራችን የሚመጡት፡፡ ስለ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት አስደናቂነት እና ዘመን የማይሽራቸው የታሪክ አካላት እንደሆኑ በተለያዩ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ሀገር ምሁራን ዘንድ ጥናት ተደርጓል፤ በግልጽም ተመስክሯል፡፡ ከእነዚህም መካከል ጥቂቶቹን እናንሳ ከ፲፭፻፲፪ ዓ.ም እስከ ፲፭፻፲፰ ዓ.ም ድረስ ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት አብያተ ክርስቲያናቱን የጎበኘው የፖርቹጋሉ ተወላጅ ፍራንሲስኮ አልቫሬዝ ስለ ላሊበላ ውቅር አቢያተ ክርስቲያናት ድንቅ ምስክርነት ሰጥቷል፡፡ ይህ ሰው የላሊበላን ውቅር አብያተ ክርስቲያናት የጎበኘ የመጀመሪያው አውሮፓዊ ዜጋ ሲሆን ጎብኝቶ ካጠናቀቀ በኋላም ስለ አብያተ ክርስቲያናቱ አስደናቂነት እጅግ ብዙ ጽፏል፡፡
በጽሑፉ ማጠናቀቂያ ላይም እንዲህ ብሏል “ስለ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ሥራዎች ብዙ ብጽፍም የሚያምነኝ ሰው መኖሩ በጣም ያስጨንቀኛል፤ ያሳስበኛልም እስካሁን ያልኩትም እንኳ ቢሆን ውሸት ነው የሚሉኝ፡፡ ነገር ግን የጻፍኩት በሙሉ እውነት ለመሆኑ በኃያሉ እግዚአብሔር ስም እምላለሁ፡፡ እንዲያውም ከዚህ በላይ ማለት ይቻል ነበር፡፡ ሆኖም ስሜ በቀጣፊነት እንዳይነሳ እሰጋለሁ … ይህን የሚመስል በዓለም እንደማይገኝ እገልጻለሁ፡፡” በማለት ድንቅ ምስክርነቱን በዚያን ዘመን ገልጿል፡፡ (ምንጭ፡ገድለ ቅዱስ ላሊበላ ሰኔ 2003 ዓ.ም ገጽ 15)፡፡
ከዚህም በተጨማሪ አንድርዜይ በርትኒስኪ እና ዮዓና ማንቴል ኒየችኮ የተባሉት የታሪክ ጸሐፍት የኢትዮጵያ ታሪክ በሚለው መጽሐፋቸው ላይ “ንጉሡ በስሙ በሚጠራው በላሊበላ ከተማ እስከ ዛሬም ድረስ ዝናቸው ያልደበዘዘውን ከዓለት ተፈልፍለው የታነጹ አብያተ ክርስቲያናት መሥራቱ ታላቅ የታሪክ ባለውለታ አድርጎታል” በማለት ገልጸውታል፡፡ (ምንጭ፡-የኢትዮጵያ ታሪክ አንድርዜይ በርትኒስኪ እና ዮዓና ማንቴል ኒየችኮ ትርጉም አለማየሁ አበበ ገጽ 32፤2003 ዓ.ም እትም)፡፡
ዓለም የተደነቀባቸው እና በእጅጉ ያወደሳቸው የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት በ፲፱፸፻፱ ዓ.ም በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የትምህርት፤ የሳይንስ እና የባሕል ድርጅት (UNSCO) አማካኝነት በዓለም ቅርስነት ተመዝግበው ይገኛሉ፡፡ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ለቤተ ክርስቲያን ከሚሰጡት መንፈሳዊ አገልግሎት ባሻገር ለሀገራችን ኢትዮጵያም ባለውለታ ናቸው፡፡ ይህም ሲባል ከተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች ቅርሶቹን ለመጎብኘት ከሚመጡ የውጭ ሀገራት ጎብኝዎች አማካኝነት በየዓመቱ ከፍተኛ ገቢ በቱሪዝም ዘርፍ ለመንግሥት እንዲገባ ማስቻሉ ነው፡፡ ከዚህም በላይ ደግሞ የሀገራችን አባቶች ዓለምን የሚያስደንቅ ረቂቅ የኪነ ሕንፃ አሻራ አስቀምጠውልን ማለፋቸው አስተዋይ ትውልዶች ከሆን የእነርሱን ፈለግ በመከተል በሥልጣኔ እድገት ከፍተኛ ማማ ላይ እንደምንቀመጥ አመላካች ነው፡፡

ለሀገር ውለታ የዋሉ እነዚህ ታሪካዊ ቅርሶች ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ግን ከፍተኛ የሆነ አደጋ ተጋርጦባቸው ይገኛል፡፡ ይኸውም በዕድሜ መግፋት እና ለቅርሶቹ ጥበቃ ተብለው በተሠሩት የብረት ጣሪያዎች(Shade structures) ምክንያት አብያተ ክርስቲያናቱ ላይ በግርግዳቸው በኩል የመሰንጠቅ አደጋ እየተስተዋለባቸው ይገኛል፡፡ ችግሩ በዚሁ ከቀጠለ እና አፋጣኝ እርምጃ መውሰድ ካልተቻለ ጉዳቱ አመዛኝ ሆኖ የቅርሶቹ ሕልውና ጥያቄ ውስጥ ሊገባ ይችላል፡፡ ለእኛ ለዚህ ትውልድ ሰዎች ደግሞ ከአባቶች በአደራ የተላለፉትን ዘመን የማይሽራቸውን ውድ ቅርሶች በአግባቡ ባለመጠበቅ የታሪክ ተወቃሽ ለመሆን እንበቃለን፡፡
ለመሆኑ ንጉሥ ላሊበላ ምን ይለን ይሆን? አባቶቻችንስ እንዴት ይታዘቡን ይሆን? እነዚያን የመሰሉ አይደለም ደግመን ለመሥራት ቀርቶ እንዴትስ እንኳን እንደተሠሩ ተመራምረን መድረስ ያልቻልንባቸውን ድንቅ የታሪክ አሻራዎች ሠርተው አስረክበውን እኛ እንዴት በኃላፊነት መጠበቅ እና በአግባቡ መንከባከብ ያቅተን? በሀገራችን የሚገኙ በኪነ ሕንፃውም በምሕንድስናውም ዘርፍ አንጋፋ ልምድ እና ዕውቀት ያላቸው የቤተ ክርስቲያን ብሎም የሀገሪቱ ምሁራንስ በዚህ ጉዳይ ለምን በአስቸኳይ መፍትሔ መስጠት አልቻሉም?
እንደ ሀገር የቤተ ክርስቲያን የሆኑትን ብቻ ሳይሆን በሀገሪቱ የሚገኙ ማንኛውም ሰው ሰራሽ እና ተፈጥሮአዊ ቅርሶች ላይ አደጋ ሲጋረጥ “የእከሌ ኃላፊነት ነው፣ እኔን አይመለከተኝም” በማለት ራስን ገለልተኛ ከማድረግ ይልቅ በመወያየት እና አግባብነት ያላቸውን ምክክሮች በማድረግ መፍትሔ ማምጣት ግድ ይለናል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን “እነርሱም አልሠሩትም፤ እነርሱም አልጠበቁትም” ተብለን የታሪክ ተወቃሽ ሆነን እናልፋለን፡፡
የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት፤ የሀገሪቱ የባሕል እና ቱሪዝም ኃላፊዎች፤ የኪነ ሕንፃ እና ምሕንድስና ምሁራን፤ በየሥልጣን ተዋረዱ የሚገኙ የመንግሥት ባለድርሻ አካላት ብሎም እያንዳንዱ ምእመን ችግሩ ይመለከተኛል በማለት አስቸኳይ እና ቀጠሮ የማይሰጠው መፍትሔ ማምጣት አስፈላጊ ነው፡፡ ከዚህም በላይ እያንዳንዱ ምእመን ፈጣሪ ሀገራችንን፤ ሕዝቦቿን እና ቅርሶቻችንን እንዲጠብቅልን ዘወትር በጸሎት መጠየቅም ይጠበቅበታል፡፡
ለወደፊቱ ተመሳሳይ ችግር በቅርሶቻችን ላይ እንዳያጋጥም እና ቢያጋጥም እንኳን ተገቢውን መፍትሔ ለመስጠት ያስችለን ዘንድ በኪነ ሕንፃ እና በምሕንድስና ላይ የተሰማሩ የቤተ ክርስቲያን ልጆችን በማስተባበር ሥርዓትን እና ሥነ መዋቅርን የተከተለ የቤተ ክርስቲያን ቴክኒካዊ ክፍል መዘርጋት እና ከባለድርሻ አካላት ጋር አብሮ መስራት ያስፈልጋል፡፡ የሲቪል መሀንዲሶች(Civil and Structural Engineers )፣ የኪነ ሕንፃ እና የከተማ ልማት ባለሙያዎች(Architects Urban planners and Architectural Historians)፤ የኮንስትራክሽን ግንባታ ባለሙያዎች (Construction TechnologyManagement)፤ የመካኒካል መሐንዲሶች(Mechanical Engineers)፤ የአፈር እና የድንጋይ ምርምር ባለሞያዎች(Geologists and Geo Tech Engineers)፤የቅርስን እና አካባቢ ጥበቃ ባለሞያዎች(Culture and Heritage professionals)፤ የሥነ ሰብእ ተመራማሪዎች(Anthropologists)፤ የታሪክ ምሁራን (Historian) እና የቤተ ክርስቲያን አባቶችን ያሰባሰበ ቡድን በማቋቋም ችግሩ የተከሰተበትን ምክንያት በማጥናት እና በምን መልኩ ጥገና እና ዕድሳት ይደረግለት የሚለውን ታሳቢ በማድረግ መፍትሔ ሊሰጠው ይገባል፡፡

ይህ የሞያተኞች ቡድን ወደፊትም ተመሳሳይ ችግር በቤተ ክርስቲያን እና በሀገር ቅርሶች ላይ ሲጋረጥ መፍትሔ ለማምጣት የሚሠራ የቤተ ክርስቲያን የአስተዳድር ወይም የቴክኒክ አካል ተደርጎ ሊመሠረት ያስፈልጋል፡፡ እንዲህ ባለመሥራታችን ተመሳሳይ ችግሮች በተከሰቱ ቊጥር የመፍትሔ ያለህ እያልን መጮህ እና የቅርሶቹን የእንግልት እና የአደጋ ሥጋት ጊዜ ማስፋት እና እስከወዲያኛውም ድረስ ላናገኛቸው እና ላይተኩ ሆነው እንዲጠፉ እናደርጋለን፡፡ ከዚህ በፊት ከኢትዮጵያ በጣሊያን አማካኝነት ተወስዶ የነበረውን የአክሱም ሐውልት ለማስመለስ የተደረገውን ጥረት ለአብነት እንደ ጥሩ ተሞክሮ አድርጎ ማንሳት ያስፈልጋል፡፡ በጊዜው በሁሉም ባለድርሻ አካላት የተደረገውን ዓይነት ርብርብ አሁን ላይም በመድገም ቅርሶቻችንን መታደግ ያስፈልጋል፡፡
በሌሎች ሀገሮች የሚገኙ የሃይማኖት ተቋማት የቅርስ ጥበቃ እና እንክብካቤ የሚያደርጉ ከዲዛይን፤ ምሕንድስና እና ግንባታ ዘርፎች የተወጣጡ አባላትን ያካተቱ የቴክኒክ ክፍሎችን በማዋቀር የቅርስ ጥበቃ እና እድሳት (Conservation and Restoration) እንደ አስፈላጊነቱ ያደርጋሉ፡፡ የእኛም ሀገር የሃይማኖት ተቋማት ከነዚህ ሀገራት አብያተ ክርስቲያናት እና ሌሎች እምነት ተቋማት ተሞክሮ በመውሰድ በቅርሶቻችን ላይ የተጋረጠውን አደጋ መቀነስ ብሎም ማስቀረት ያስፈልጋል፡፡ አባቶቻችን የሠሩልንን እና ያስረከቡንን የታሪክ ቅርሶች በአግባቡ ተቀብለን እና ጠብቀን ለትውልድ ማስተላለፍ እና ቅብብሎሹ እንዲቀጥል ማድረጉ ከእያንዳንዳችን ይጠበቃል፡፡ በቤተ ክርስቲያን የአስተዳድር ሥነ መዋቅርም ቢሆን እንደዚህ ዓይነት ችግሮች ሲከሰቱ ከመንግሥት ባለድርሻ አካላት ጋር በመነጋገር መፍትሔ ማምጣት ጊዜ የሚሰጠው ጉዳይ መሆን የለበትም፡፡

               ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ምንጭ፤ሐመር መጽሔት 26ኛ ዓመት ቁ7 ኀዳር2011 ዓ.ም

በትዳር ሕይወት የወላጆች ኃላፊነት

                                                                  ዲ/ን ተመስገን ዘገየ
መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር አምላክ ሰውን በአርአያውና በአምሳሉ ፈጠረው ይለናል (ዘፍ፪-፳፮) አዳም ብቻውን ይሆን ዘንድ ያልፈቀደውና ብቻውን ቢሆን መልካም እንዳልሆነ የሚያውቅ አምላካችን የምትረዳውን ሔዋንን ከጎኑ አጥነት ፈጥሮለታል፡፡እግዚአብሔር ወንድና ሴት አድርጎ መፍጠሩ ለበረከት፤ለመባዛት በመሆኑ”ብዙ ተባዙ ምድርንም ሙሉአት” በማለት ሕገ በረከትን ሰጥቷአቸዋል፡፡ስለዚህ ጋብቻ በሰው ፍላጎት ብቻ የተገኘ አይደለም፡፡ስለ ጋብቻ በኦሪትም በወንጌልም ሕግ ተሰርቷል፡፡የአዳምና የሔዋን ጋብቻ የሕጋዊ ጋብቻ መሠረት ነው፡፡ጋብቻን ያከበሩ በሕጋዊ ጋብቻ የነበሩ ደጋግ ቅዱሳን በሕገ ልቡና እንደነበሩ ሁሉ በሕገ ኦሪትም ነበሩ፡፡ለምሳሌ የኢያቄምና የሐና ጋብቻ ቅዱስ ጋበቻ ነበር፡፡የተቀደሰ ጋብቻ በመሆኑ የቅድስት ድንግል ማርያም ወላጆች የአምላካችን የመድኀኒታችን አያቶች ለመሆን በቅተዋል፡፡
እንዲሁም የዘካርያስና የኤልሣቤጥ ጋብቻ የተባረከ ጋብቻ ነበር፡፡ ቡሩክና ሕጋዊ በመሆኑም መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስን ማግኘት ችለዋል፡፡ጋብቻ የቅድስና ሕይወትን በሥርዓት የሚመሩበት የቤተሰብ መንግሥት በመሆኑ ክብሩና ልዕልናው ሊጠበቅ ይገባዋል፡፡ወላጆች ልጆችን መተካት አለባቸው ሲባል“መውለድ” ብቻ ማለት አለመሆኑን በሚገባ መረዳት ይገባል፡፡ቅዱስ ዳዊትም “ናሁ ጸጋሁ ለእግዚአብሔር ውሉድ ዕሤተ ፍሬሃ ለከርሥ፤ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታ ናቸው (መዝ፻፳፮፥፫) ልጆች ማደግ ያለባቸው በእግዚአብሔር ትእዛዝና መንገድ ነው፡፡ክቡር የሆነው የሰው ልጅ ቀርቶ አራዊትም እንኳን ልጆቻቻውን በሥርዓት ያሳድጋሉ፡፡ ለምሳሌ፤አናብስትና አናብርት አዳኝ የዱር እንሰሳት ልጆቻቻውን እንዴት እያደኑ ማደግ እንዳለባቸው ያስተምራሉ፡፡
ጠቢቡ ሲራክ “የሰው አነዋወሩ በልጆቹ ይታወቃል”ይላል (ሲራ፲፩፥፳፰) በ፳፩ኛው ክፍለ ዘመን የወጣቱ ሥነ-ምግባር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየዘቀጠ መምጣቱ እውነት ነው፡፡ለዚህም ዋናው መሠረታዊ ችግር ሕዝቡ ከእግዚአብሔር ጋር ያለው ግንኙነት በተለያየ ምክንያት እየዛለ መምጣ ነው፡፡ወላጆች ልጆቻቸውን ማስተማር ያላባቸው ቀዳሚ ትምህርት“እግዚአብሔርን መፍራት“ነው፡፡(ምሳ፩፥፯) ልጆች ለሚጠይቁት ጥያቄ እንደ ዐቅማቸው ማስረዳት ይገባል፡፡ ሕፃናትን የሚያስተምሩ ሰዎች በፍቅርና በደስታ ማቅረብ ይኖርባቸዋል፡፡ልጆች ከጣፈጭ ምግብ ይልቅ የሚረኩት ከወላጆች በሚያገኙት ፍቅር ነው፡፡ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “አባቶች ሆይ ልባቸው እንዳይዝል ልጆቻችሁን አታበሳጩ”ይላል (ቈላ፫፥፳፪) ልጆችን በፍቅር እንጂ በስድብ ፤በመደብደብ ፤በማበሳጨት፤በማስፈራራት ለማስተማር መሞከር እንደማይገባን ሐዋርያው አስተምሮናል፡፡
ሲራክ“የሰው አኗኗሩ በልጆቹ ይታወቃል (ሲራ፲፩፥፳፰) የላኪው ማንነት በተላከው እንደ ሚታወቅ የወላጆች ምንነት ማሳያ ልጆች ናቸው፡፡የኢትዮጵያ ሕዝብ ሥነ ምግባር የማይታይበት ልጅ ሲያጋጥማቸው”አሳዳጊ የበደለው” ይላሉ፡፡ስለዚህ ልጆችን በሥነ ምግባር ኮትኩቶ ማሳደግ ለነገ የማይባል ተግባር ነው፡፡አሁን አሁን በልጆቹ የሚደሰትና የሚጠቀም ወላጅ ሳይሆን በወለዷቸው ልጆች የሚያዝኑና የሚያለቅሱ ኢትዮጵያውያን ይበዛሉ፡፡ሲራክ “በሱ ጥፋት አንተ እንዳታፍር ልጅህን አስተምረው ያገለግልሃል”(ሲራ፴፥፲፫) ልጅን በሚገባ አስተምሮ ማሳደግ በጣም አስፈላጊ መሆኑን ቅዱሳት መጻሕፍት ያሰተምሩናል፡፡ የካህኑ የዔሊ ልጆች ፊንሐስና አፍኒን በታቦተ ጽዮን ድንኳን ሥር ያመነዝሩ ነበር ያሳፍራል፡፡ ዔሊ ልጆቹ ይህን የመሰለ ኃጢአት መፈጸማቸውን እያወቀ ባለመገሰጹ ቅጣት ተቀብሏል፡፡ልዑል እግዚአብሔር ዔሊን “ከእኔ ይልቅ ልጆችህን ለምን አከበርክ?(፩ኛሳሙ፪፥፳፱) በማለት ተቆጣው፡፡ሁለት ልጆቹንም ቀሰፋቸው፡፡ቅጣቱ በልጆቹና በእሱ ብቻ ተወስኖ አልቀረም፡፡ለሌላም ተረፈ አንጂ፡፡
ወላጆች ሆይ ልጆቻችንን እንዴት እናሳድጋቸው?
የነገው ትወልድ ሀገሩንና ቤተሰቡን የሚጠቅም በሥነ- ምግባር የታነጸ በሥራው የተመሰገነ ይሆን ዘንድ ዛሬ ያሉትን ልጆች በአግባቡ መያዝ ልዩ እንክብካቤ ማድረግ ይገባል፡፡ወላጆች ከማንም በላይ ሕፃናትን መልካሙንና ክፉንም በማሰተማር ቅርብ ናቸው፡፡እናትና አባት ከትምህርት ቤት ሲመለሱ ስለተማሩት ትምህርት መጠየቅ አለባቸው፡፡ልጆችም እንደሚጠየቁ ስለሚያውቁ ትኩረት ሰጥተው ይከታተላሉ፡፡ጥሩ ነገር በሠሩ ጊዜ ጥሩ ወጤት ባመጡ ጊዜ ሽልማት ማዘጋጀት ይገባል፡፡ወላጆች በቤት ውስጥ በቃል ሳይሆን በተግባር በክፉነት ሳይሆን በደግነት እያስተማሩ ሊያሳድጉ ይገባል፡እንዲህ ከሆነ የክፉ ምግባር ቦይ አይሆኑም፡፡አንድ ሰው በቅሎ ጠፋችበትና ወዲያ ወዲህ እየተንከራተተ ሲፈለግ በበቅሎ ሌብነት የሚጠረጠረው ሰው አብሮ ያፋልገው ጀመር፡፡ዘመድ መጥቶ “በቅሎህ ተገኘችልህ ወይ”ብሎ ቢጠይቀው አፈላላጊዬ የበቅሎዬ ሌባ ስለሆነ እንደምን አድርጌ በቅሎዬን ላገኛት እችላለሁ አለ ይባላል፡የልጆችን አእምሮዊ ዕድገት ለማሟላት ከሚደረጉ እንክብካቤዎች የሚከተሉት ይጠቀሳሉ
ተገጣጣሚ መጫዎቻዎችን በመጠቀም የቁጥር ስሌት እንዲያውቁ ማድረግ፤የቋንቋ ችሎታቸውን የሚያሳድጉ መንፈሳዊ ጹሑፎችን እንዲያነቡ ደጋግመው መንገርና ዕድሎችን ማመቻችት፡፡ወላጆች (ባልና ሚስቱ) በአንድነት ሁነው የቤተሰቡ መሪ በመሆናቸው ሊወስዱት የሚገባ ተግባር ይኖራል፡፡ልጆቻችንን በምግባር በማሳደግ የሚኖሩበትን ቤት የዕለት ከዕለት እንቅሰቃሴ እየተከታተሉ መሥመር በማስያዝ አገልጋዮች የሆኑ የቤት ሠራተኞችን ሳያማርሩ ሥራ ሳያበዙ በማሠራት መኖር ይጠበቅባቸዋል፡፡ወላጆች ይህንን ከባድ የቤተሰብ ኃላፊነት ሲወጡ በሚከተሉት ነጥቦች ቢመሩ መልካም ነው፡፡
፩.. በፍቅር፤ ልጆች ፍቅርን እንክብካቤን ከወላጆችና ከመምህራን ይፈልጋሉ፡፡የወላጆቹን ፍቅር እያገኘ ያደገ ልጅ መንፈሰ ጠንካራ፤ለሰው የሚያዝንና ታዛዥ ይሆናል፡፡አንዳንድ ወላጆች የቤተሰቡ ራስ መሆናቸውን በቊጣ በዱላ በመግለጽ ልጆቻቸውን በኃይል ብቻ ለመግዛት የሚሞክሩ አሉ ፡፡ይህ የተሳሳተ መንገድ ነውና ከስሕተት ጎዳና መመለስ ይኖርባቸዋል፡፡
፪..ትኩረት በመስጠት፣ ልጆች ከፍተኛ የሆነ ክትትልና ትኩረት ይፈልጋሉ፡፡የሚያከናውኑትን እያንዳንዱን ተግባራት እየተመለከተ በጎውን በጎ የሚላቸው ሲሳሳቱ የሚያርማቸው ይሻሉ፡፡ ልጆችን በንቃት መከታተል የወላጆችና የመምህራን ግዴታ ነው፡፡ወላጆች በዕረፍት ጊዜ ከልጆቻቸው ጋር መወያየት፣መመካከር፣የወደፊት ዕቅዳቸውን ምኞታቸውን በተመለከተ በግልጽነት መረዳት ይገባቸዋል፡፡
፫. በማስተማር፤ ንግሥት ዕሌኒ ቆስጠንጢኖስን በሥርዓት ኮትኩታ በማሳደጓ የሀገረ መሪ ለመሆን በቃ፡፡አሁንስ እኛ ልጆቻችንን እንዴት እያሳደግናቸው ነው? ሰው በሕፃንነቱ ተክል ማለት ነው፡፡ተክል የሚሆነውን ሁሉ ሊሆን ይችላል፡፡ቀጥ ብሎ ያድጋል ተወላግዶም ያድጋል የተወላገደውን ለማቃናት ብዙ ዋጋ ያስክፍላል፡፡ወላጆች በልጆቻቸው ዕድገት ትኩረት ሊሰጡት የሚገባ አንዱና ዋነኛው የልጆቻቸውን ተፈጥሮዊ ተሰጥኦ ማበልጸግ ነው፡፡ወላጆች ልጆችን የማሳደግ ክህሎት ለማዳበር ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ ይኖርብናል፡፡ከእኛ ቤት ሲገባ ግን መጸሕፍት ይኖር ይሆን? በተለያዩ የቤተሰብና የልጆች ነክ ጉደዮች በመሳተፍ ከተቻለ የሥነ ልቡና ባለሙያና የአብነት መምህራንን በማማከር የተሻለ ዕውቀት መጨመር ይቻላል፡፡
የልጆችን ተሰጥኦ ከልጅነታቸው ጀምሮ መረዳትና እውቅና መስጠት ለወላጆች ትልቅ ስኬትና አበረታች ነገር ነው፡፡ወላጆችና የአብነት መምህራን ልጆች ችሎታቸውን የሚያወጡበትን አማራጮችና ዕድሎችን ማመቻችት ይገባቸዋል፡፡በእኛ ሀገር ደረጃ ጥረህ ለፍተህ ብላ ኑር ነው እንጂ አማራጭ አንሰጥም ይህ ዘመንን አለመዋጀት ነውና መስተካከል ይኖርብናል፡፡የልጆችን እንቅስቃሴ በመከታተል የልጆችን ፍላጎት ማወቅ ይገባል፡፡ወላጆች ከትምህርት ስኬት ባሻገር የልጆቻቸውን ማኀበራዊ መንፈሳዊና ሥነ-ልቦናዊ ሕይወት መረዳት አለባቸው፡፡ወላጆችና መምሀራን ልጆችን ሲያናግሩ ሙሉ ትኩረት መስጠት አለባቸው፡፡
ልጆችን በልዩ ልዩ እንቅስቃሴዎች ማሳተፍ ይገባል
ወላጆች ልጆቻቸውን ሲያሳድጉ በትምህርታቸው ብቻ ስኬታማ ሆነው ትምህርታቸውን አጠናቀው እንዲመረቁ ብቻ ሳይሆን አጠቃላይ በመንፈሳዊ ሕይወታቸውም ስኬታማነት እንዲ ዘጋጁ የማደረግ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ልጆችን ከትምህርት ቤት መልስ በተለያዩ ተግባራት እንዲሳተፉ ማድረግ የሚከተሉት ጠቀሜታዎች ይኖሩታል፡፡
ቴሌቪዥን በመመልከትና ጌም በመጫዎት የሚያሳልፉትን ጊዜ በመገደብ በሠርክ ጉባኤና በሰንበት ትምህርት ቤት ከመደበኛው ከትምህርት ውጭ የሆኑ ተግባራት ሲሳተፉ ወሳኝና ለወደፊት ሕይወታቸው ከፍተኛ ጠቀሜታ ያላቸው ማኀበራዊ ክህሎቶችን እንዲያዳብሩ ይረዳቸዋል፡፡ በውኃ ውስጥ መዋኘትም ለልጆች የሚመች የእንቅስቃሴ አይነት ነው፡፡በሳምንት ሁለት ጊዜ (ቅዳሜና እሑድ) ቢዋኙ አካላዊ ብቃታቸውን ያሻሽላል፡፡የመተንፈስ እንቅስቃሴ በማሻሻል ሂደት ለልጆች ጤንነት የአካል ብቃት የላቀ አስተዋጽኦ አለው፡፡ከትምህርት ቤት መልስም ሆነ በዕረፍት ቀናት የእግር ኳስ እንቅስቃሴ ማድረግ ወላጆች አብረው በመጫወት ካልተቻለም ልጆች ሲጫወቱ በመከታተል ,.በተግባር በማሳየት፣ልጆች ከሚሰሙት ይልቅ በሚያዩት ይሸነፋሉ፡፡ ከተነገራቸው ይልቅ የተመለከቱት በእነርሱ ኀሊና ትልቅ ቦታ አለው፡፡ ወላጆች ተግባራዊ የሆነ ሕይወትን ለልጆቻቸው ሊያስተምሩ ይገባል፡፡አሁን በየቤታችሁ ልጆች ምንድን ነው የሚያዩት አንዳንድ ወላጆች ልጆቻቸውን እንዳይጠጡ እየመከሩ እነርሱ ጠጥተው የሚገቡ አሉ፡፡አሁን የዚህ ሰውየ ልጅ ምን ይሆናል? ልቡ ባዶ ቅርጫት ራሱ ባዶ ቤት እየሆነ ነው፡፡ ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ በማስገዛት ልጆችን መልካም የሆኑ ነገሮችን ማስተማር አለብን አንድ ወቅት ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ “ራሱን ያሸነፈ የጎበዝ ጎበዝ ነው ሌለውን ያሸነፈ ተራ ጎበዝ ነው” ብለው ነበር፡፡ በዘመናችን ራስን ማሸነፍ ሰማዕትነት ነው፡፡
• ልጆች ማኅበራዊ ሚዲያዎችን በአግባቡ መጠቀም ይኖርባቸዋል
የመረጃ ልውውጥ ከማደረግ (በጎን መጥፎውንም) ማኅበራዊ ግንኙት ከማጠናከር (የጠፉ ጓደኞችን) ከማገናኘት አንጻር በአግባቡ ከተጠቀሙበት ትልቅ አስተዋጽዖ አለው፡፡የማኅበራዊ ሚዲያዎች ጉዳት ተመልሶ የማይገኝ ጊዜን ያባክናል፡፡አጠቃቀማችን በአግባቡ ካልሆነ ለትዳር ጠንቅ ነው ራሳቸውን አግዝፎ ለማሳየትና ማኅበራዊ ሚዲያዎችን ለዝሙት የሚጠቀሙ አሉ፡፡ በዘመናችን ችግሩን መናገር በራሱ ችግር ነው እንጂ ቴክኖሎጂው እየተራቀቀ ሲመጣ የትውልዱም ጥያቄ እንዲሁ እየተበራከተ ይመጣል፡፡የ፳፩ኛውን ክ/ዘመን ትውልድ ሥነ ልቡና በመረዳት ወላጆች እንደ እባብ ብልህ በመሆን ትውልዱ ያለበትን ሁኔታ ቀድመው ምን እየመጣ እንደሆነ መመልከት ይኖርባቸዋል፡፡
የመረጃ ቴክኖሎጂ ዓለምን ወደ አንድ መንድር እየተቀረ በመምጣቱ ሀገራችንም የዚሁ ቴክኖሎጂ ተጠቃሚ በመሆኑ አደጋ አለው፤በአግባቡ መጠቀምና መቆጣጠር አለመቻል መሠረታዊ ችግር ነው፡፡ልጆቻችን ውጤታማና ስኬታማ እንዲሆኑ ለማድረግ የመረጃ ቴክኖሎጂ አጠቃቀማቸውን መገደብና መቆጣጠር የወላጆች ኃላፊነት ነው፡፡ልጆች በቪዲዮ ጌም መጫወት ካለባቸው በወላጆች በጥንቃቄ የተመረጡ፣አዝናኝና የልጆችን የፈጠራ ችሎታ የሚያበለጽጉ ፣ለዕድሜአቸውና ለሥነ-ልቡናቸው የሚመጥኑ ቁጣና ጥቃት ያልበዛባቸው መሆን እንዳለባቸው ባላሙያዎች አበክረው ይመክራሉ፡፡የሚያስፈሩ ቪዲዎችና ጌሞችን የሚጫወቱ ልጆች የበለጠ ቍጣና ጥላቻ የሚያሳዩ ይሆናሉ፡፡ልጆች ያለ ገደብ ቴክኖሎጂ ከተጠቀሙ የአእምሮ ዕድገታቸው ይጎዳል፡፡የትምህርት አቀባባል ድክመት ያጋጥማቸዋል፡፡ላልተፈለገ የሰውነት ውፍረት ያጋልጣል፡፡ ለማሰታወስ ችግር ያጋጥማችዋል፡፡የቴክኖሎጂ ሱሰኛ ያደርጋል፣የእንቅልፍ እጦት ያጋጥማቸዋል፡፡
የልጆች ሥነ- ምግባርና መንፈሳዊ ሕይወት በምን ምክንያት ሊበላሽ ይችላል-?
በቂ ቁጥጥር ካለማድረግና ወላጅ ልጆቹን ሥነ-ምግባር ስለማያስተምር ታላላቆቻቸው እና ቤተሰቦቻቸው ሥነ-ምግባርን በማስተማር ረገድ ደከሞች በመሆናቸው፡፡ ሕፃናቱ አብረው የሚውሉት አብረው የሚማሩት ሰው ማንነት እንዲሁም የሚውሉበት አካባቢ መጥፎ መሆን ለእነርሱ የማይገቡ የማይመጥኑአቸውን ፊልሞችና ድርጊቶች ስለሚመለከቱ አንዳንድ ትምህርት ቤቶች ሥነ- ምግባርን አስመልክቶ የሚያስተላልፉት መልእክት አነሳ መሆን የሚያስፈልጋቸውን ነገሮች ባለማግኘት ምክንያት አግባብነት ወደ ሌላቸው ቦታዎች ሊሄዱ በመቻላቸው ምክንያት ነው፡፡ ልጆቻችን መከራ እንዲቋቋሙ አድርገን እናሰልጥናቸው ችግር ሲመጣ የሚቋቋሙ አናድርጋቸው፡፡ሕፃናት በማይጠቅሙ ዓለማዊ ፊልሞች ጨዋታዎች ድራማዎች፤ፍቅር ሰጥመው ካደጉ በኋ ክፉ ነገር ተው ብንል እንዴት ይቻላል? ልጆቻቸውን በሥርዓት ያስተማሩና ከቅጣት ያዳኑ ደጋግ አባቶች ነበሩ፡፡መጽሐፍ “ከእግዚእበሔር ሕግ እንዳይወጡ ሴት ልጆቻቸውንና ወንድ ልጆቻቸውንም፡አስተምረው ነበርና፤የሚቀርባቸው ክፉ ጠላት አልነበረም (፩መ.መቃቢያን፲፱፥፲፫)

 ወላጆች ለልጆቻቸው የእግዚአብሔርን ድንቅ ተኣምራት ፤የጻድቃንና የሰማዕታት ገድልና የሀገራቸውን ታሪክ በሚገባቸው መጠን እያስጠኑ የማሳደግ ኃላፊነት አለባቸው፡፡ከወላጅ ወደ ልጆች መተላለፍ የነበረበት የቃል ትምህርት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየደበዘዘ በመምጣቱ በትውልዱ ዘንድ ክፍተቱ እየበዛ መጥቷል፡፡በጥንቱ ባሕል መሠረት ልጆች ወላጆቻቸውን ቁመው ማብላት ነበረባቸው፡፡በእራት ጊዜ የእንጨት መብራት ይዞ ያበላ ነበር፡፡ይህም ቢሆን ልጅ ለወላጅ ያለውን አክብሮት ለመግለጽ የሚደረግ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጥንተ መሠረት ያለው ነው፡፡(ሉቃ፲፯፥፰፤፳፪፥፳፯)
ወላጆች ልጆቻቸውን በሥነ-ምግባር ኮትኩተው በሥነ ሥርዓት አስተምረው የማሳደግ ኃላፊነት እንዳለባቸወ ሁሉ ልጆችም ወላጆቻቸውን የመታዘዝ፤የማክበር ግዴታ አላባቸው፡፡ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ”ልጆች ሆይ ይህ ለጌታ ደስ የሚያሰኝ ነውና ለወላጆቻችሁ ታዘዙ”ይላል( ቈላ፫፥፳)ከሁሉ በፊት እናትና አባቱን የሚያከብር ልጅ ዕድሜው ይረዝማል(ዘጸ፳፥፲፪) ምክንያቱም ይመረቃልና፡፡ወላጆቹ የመረቁት ልጅ በእግዚአብሔር ዘንድም የተወደደ ነው፡፡ በመንፈሳዊና በምድራዊ ሀብት የበለጸገ ይሆናል፡፡”ምርቃት ትደርስህ ዘንድ ቢጠራህ አቤት ቢልክህ ወዴት ብለህ አባትህን አክብረው “(ሲራ፫፥፱) በታዛዥነታቸው፤በትሕትናቸው በወላጆቻቸው ከተመረቁት መካከል ያዕቆብንና ርብቃን ለአብነት ማንሳት ይበቃል (ኩፋ፳፥፷፭፤ዘፍ፳፬፥፷ ፤ኩፋ ፲፬፥፴፱)
ዲድስቅልያ አንቀጽ ፲፩፥፩ ”እናንትም አባቶች የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ይጠብቁ ዘንድ የክርስቶስን ጎዳና ይከተሉ ዘንድ ልጆቻችሁን አስተምሯቸው እጅ ሥራ አገልግሎት ይማሩ ዘንድ እዘዟቸው ሥራ ፈት ሁነው እንዳይቀመጡ”ይላል፡፡ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ ሚያዝያ 23 ቀን 1982 ዓ.ም በሻሸመኔ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ተገኝተው ሲያሰተምሩ ”ልጆቻችሁ ከመዝሙር ጋር ደግሞ ሃይማኖታቸውን ፤ሥነ ምግባራቸውን እንዲማሩ ያስፈልጋል፡፡ወደ ቤተ ክርስቲያን ስትመጡ ልጆቻችሁን ይዛችሁ ኑ ብቻችሁን ከመጣችሁ የምተሠሩትን አያውቁም፤ወደየት እንደ ሄዳችሁም አያውቁም፡፡ወራሾቻችሁም አይሆኑም ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን ስትመጡ ልጆቻችሁን ይዛችሁ ኑ፤ሥዕሉን ይሳሙ፤ቅዳሴ ጠበሉን ይጠጡ ፡በእምነቱ አሻሹአቸው መስቀል እንዲሳለሙ አስተምሯቸው ዕጣኑንም ያሽትቱ የሚታጠነውን፤ሥጋወደሙን ይቀበሉ፤ቃጭሉን ይስሙ፤ደወሉ ሲደወል ይስሙ፤ቄሳቸው ማን እንደሆነ ቤተ ክርስቲያናቸው ማን እንደሆነች በውስጧም ምን ምን እንደሚሠራ ያጥኑ ፤ይማሩ፡፡ ወደ ሰንበቴም ስትሄዱ ይዛችኋቸው ግቡ ወደ ሰንበቴም ዳቦውን ተሸክመው ይምጡ እነርሱም ነገ ይህንን እንዲወርሱ የነገ ባለ አደራዎች መሆናቸውን እንዲያውቁ፡፡መመካት አይገባም የሚገባ ቢሆን እኛ ከዓለም ሁሉ የበለጠ መመካት ይገባን ነበር፡፡ምከንያቱም አባቶቻችንና እናቶቻችን ሥርዓታችንንና እምነታችንን ሁሉ ሰፍረው ቆጥረው ያስቀመጡልን ስለሆነ፤ይህ ትውልድ ይህንን ከቀበረ በኋላ ይህንን ካጠፋ በኋላ እንደገና ቤተ መዘክር እንዳይሄድ ነው ሃይማኖቱን ፍለጋ፤ታሪኩን ፍለጋ፤ስለዚህ እምነታችሁን፤ሥርዓታችሁንና መንፈሳዊ ውርሳችሁ እንድትጠብቁ አደራዬ የጠበቀ ነው”ብለው ነበር፡፡

ምንጭ፤ሐመር መጽሔት ፳፮ኛዓመት ቊ ፮ ጥቅምት ፳፻፲ወ፩ ዓ.ም