የዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተና

የተከበራችሁ አንባብያን በዘመናችን ቤተ ክርስቲያን ያለችበትን ሁኔታና በየአካባቢው እና በየክልሉ በቤተ ክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ እየተፈጸመ ያለውን ጥቃት አስመልክቶ  ክፍል አንድ፤ክፍል ሁለት እና ክፍል ሦስት ጽሑፍ ማቅረባችን ይታወቃል፡፡ክፍል አራትን እነሆ ብለናል፡፡

አሁን እየተፈጸመ ያለውም አስቀድሞ ሲፈጸም ለኖረው ቀጣይ ይመስላል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ላይ እየተፈጸመ ያለውን ውድመት፤ ዜና ቤተ ክርስቲያን፡- የግራኝ አህመድ ዘመን ተመልሶ እንዳይመጣ እንዲህ በማለት አሳስቧል፡፡ «አሁን በቅርቡ ባሳለፍነው በ፳፻፲ ዓ.ም መገባደጃ ላይ አገር የሆነችውን ወይም ሁለንተናዊ ጠቀሜታዋና ትሩፋቷ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ባለውለታ የሆነችውን አንጋፋዋን ቤተ ክርስቲያን ከሌላው ነጠሎ ለመምታትና የተከታዮቿን የምዕመናንን አሻራ ከገጸ ምድር ለማጥፋት ወይም አሳምኖ የራሱ ተከታዮች ለማድረግ የረጅም ጊዜ ዕቅድ ባለው የሱማሌ ክልል ፀረ ክርስትና ቡድን በፈጸመው ጥቃት በክልሉ ውስጥ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያንን በሙሉ አውድሟቸዋል፤ ሀብታቸውን፣ ንብረታቸውንና ቅርሶቻቸውንም ዘርፏቸዋል፤ አገልጋዮቿንም እንደ ካህኑ ዘካርያስ በየቤተ መቅደሳቸው ውስጥ አርዷቸዋል»፡፡ ይህ የሚያሳየው በቤተ ክርስቲያን ላይ እየተፈጸመ ያለው ጥፋት ጊዜያዊ ጥቃትና ተራ ጥፋት አለመሆኑን ነው፡፡ በ፳፻፱ ዓ.ም በለገጣፎ የሚገኘውን የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን የንግሥ በዓል በሚያከብሩበት ወቅት የከተማው ማዘጋጃ ቤት የላካቸው አፍራሽ ግብረ ኃይል ሰኔ ፴ ቀን በግሬደር አፍርሶታል፡፡ ሰላምን ማስፈን፣ ዜጎቹን በእኩል አይን ማየት የማገባው የሕዝብ አስተዳደር አካል ይህን ማድረጉ የሚያስገርም ነበር፡፡ በያዝነው ዓመትም በዚያው አካባቢ ቤታቸው የፈረሰባቸው ዜጋዎች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሲጠለሉ ቤተ ክርስቲያን ለምን ለችግረኞች መጠጊያ ሆነች የሚሉ ወገኖች ካህናትን ማስፈራራታቸው በመገናኛ ብዙኃን ተገልጧል፡፡

«መጋቢት ፲፫ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም በሂደቡ አቦቴ ወረዳ ኤጄሬ ከተማ የመጥምቀ መለኮት ትዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያንን ቁልፍ ሰብረው በመግባት ታቦቱንና ንዋያተ ቅድሳቱን ዘርፈው ንዋያተ ቅዱሳቱን ሹንቁራ በሚባለው ተራራ ላይ አቃጥለውታል፡፡ መጋቢት ፲፮ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም በዚሁ ወረዳ የሚገኘውን የአድዓ ቅዱስ በዓለወልድ ቤተ ክርስቲያን ቀን ላይ በእሳት አቃጥለውት ንዋያተ ቅዱሳቱ ሲቃጠል ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑ በምእመናን ርብርብ ተርፏል»፡፡ ቤተ ክርስቲያን በዚህ ሁሉ መከራ መካከል ሳትጠፋ የምትኖር ቢሆንም፣ አብረውን የሚኖሩ ወገኖቻችን እንዲህ ዓይነት የጭካኔ ተግባር የሚያሳዝንም የሚያስገርምም ነው፡፡

 ለ. የቤተ ክርስቲያን ይዞታ መነጠቅና ደን መቃጠል፣ ቤተ ክርስቲያን የዓደባባይ በዓላትን የምታከብርባቸው የመስቀል ደመራና የጥምቀት ማክበሪያ ቦታዎቿ ችግር እየገጠማቸው ነው፡፡ ከጥቂት ዓመታት ወዲህ ይዞታዋን እየነጠቁ ለባለሀብቶች መስጠት፣ ለሌለ እምነት ተቋም ማሸጋገር የተለመደ ሆኗል፡፡ በጎንደር፣ በባሕርዳር፣ በአርባምንጭ፣ እና በሌሎችም ለጥምቀተ ባሕር የሚሆኑ ቦታዎች ለባለሀብቶች ተሰጥተው በተፈጠረ ብጥብጥ ብዙ ሰው ሞቷል፤ ብዙዎች ለእስር ተዳርገዋል፡፡ የአየር ጤና ኪዳነ ምሕረት የጥምቀተ ባሕር ማክበሪያ ቦታ በወቅቱ የከተማዋ ከንቲባ በነበረው ግለሰብ ትእዛዝ ለሌላ ቤተ ዕምነት ተሰጥቷል፡፡ መንግሥት በሰጣቸው ሥልጣን እምነታቸውን የሚያስፋፉ፣ በተገኘው አጋጣሚ የቤተ ክርስቲያን የነበረውን ቦታ ሁሉ ለራሳቸው በማድረግ እንቅልፍ የሌላቸው ምእመናን ይዞታቸውን ለማስመለስ ሲነሡ ለእስር የሚዳርጉ፤ በጥይትና በዱላ እንዲደበደቡ የሚያደርጉ ወገኖች ብዙ ናቸው፡፡

 «የካቲት ፳፻፭ ዓ.ም በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊበን ዝቋላ ወረዳ አዱላላ ከተማ በሚገኘው የዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም መንሥኤው ያልታወቀ እሳት ተነሥቶ በከባድ የነፋስ ኃይል እየተገዛ ወደ ገዳሙ እንዳይስፋፋ ተሰግቶ ነበር፡፡ ገዳሙ ከዚህ በፊትም መጋቢት ፲ ቀን ፳፻፩ ዓ.ም በደረሰው የእሳት ቃጠሎ አርዘሊባኖስ፣ የሐበሻ ጥድ እና መሰል ሀገር በቀል ዛፎች ወድመዋል፡፡ መጋቢት ፰ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም በተቀሰቀሰ ቃጠሎ ገዳሙ ጉዳት ደርሶበታል፡፡» ቃጠሎውን የፈጸመው ባይታወቅም የእኛ ጥያቄ የሀገር ሀብት የሆነው ደን ሲወድም የቤተ ክርስቲያን በመባል ብቻ ትኩረት ሳይሰጠው መቅረቱ ተገቢ አለመሆኑን ለመግለጽም ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ስለሆነ ብቻ ትኲረት ሳይሰጠው መቅረቱ ተገቢ አለመሆኑን መረዳት ተገቢ ነው፡፡ በአንድ አካባቢ በቤተ ክርስቲያን ላይ ችግር ሲፈጠር በወቅቱ መረጃው እንዳይወጣ ይደረግ የነበረው ጫና ቀላል አልነበረም፡፡

ምእመናን የተናገሩትን፣ መነኮሳት የተሰማቸውን አካቶ ዜና ለመሥራት የነበረው ችግር ቀላል አልነበረም፡፡ ሀገራችን ዘመናዊ የእሳት ማጥፊያ እንደሌላት ይታወቃል፡፡ በሚችሉት መርዳት፣ በአሳብ መደገፍ፣ ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶ በምንችለው ሁሉ ተረባርበን እናጠፋለን፡፡ ይህ የቤተ ክርስቲያንና የሀገር ሀብት የሆነው ቋሚ ቅርስ ለጉዳት ሲጋለጥ ሃይማኖት ዘርና ቀለም ሳንለይ ችላ አላልንም በማለት የባለቤትነት ስሜት እንዳን ሁላችንም ማሳወቅ ይኖርብናል፡፡ ይህ ጉዳት በታላቁና በጥንታዊው የአሰቦት ደብረ ወገግ ሥላሴ ገዳምም ተፈጽሟል፡፡ የገዳሙን ደን አክራሪዎች ባስነሡት እሳት መቃጠሉ በወቅቱ ተዘግቧል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ላይ፣ ችግር ሲፈጠር ከክርስቲያኖቹ ያላነሰ ልባቸው የሚያዝን፣ አቅማቸው የፈቀደውን ሁሉ የሚያደርጉ የሌላ ከክርስትና ውጪ ያሉ ዕምነት ተከታዮት እንዳሉ አንክድም፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ማየት የማይፈልጉ በሐሰት መረጃ የተሞሉ ጥፋት አድራሾችም እንደዚሁ፡፡ እየተፈጸመ ያለው ጥፋት በንፁህ ኅሊና መለስ ብለን ማየት ካልቻልን፣ ትኩረት አለመስጠታችንና ጆሮ ዳባ ለበስ ማለታችን የበለጠ ጥፋት ያስከትላል፡፡

ከታሪክ ምሁራን፣ ከቤተ ክርስቲያን፣ ከመገናኛ ብዙኀንና ከመንግሥት አካላት ስለ ቤተ ክርስቲያን በስሕተት ሲዘራ የኖረውን ታሪክ ማስተካከልና ትክክለኛውን መረጃ መስጠት ያስፈልጋል፡፡ ለምን ገዳማት በዙ፣ ለምን ቱሪስቶችን የሚስቡት የክርስቲያኖች የተጋድሎ ውጤቶች ሆኑ የሚሉ ወገኖች በቅናት ታሪክ ለመቀየር እየሠሩ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ምሁራን ለሚጻፉ የሐሰት ጽሑፎች መልስ መስጠት፣ የመረጃቸውን ፍሬ ቢስነት ማጋለጥ ይኖርባቸዋል፡፡ እንደፈለጋቸው ሲሳደቡ ቤተ ክርስቲያን ከዛሬ ነገ ይታረማሉ በማለት በትዕግሥተ ስላለፈችው፡፡ ስታልፈው በጥሞና የራስን ምግባር ማየት ይገባል እንጂ በጥፋት ላይ ጥፋት መፈፀም ሰብዓዊነት አይደለም፡፡ ይህ መሰተካከል ይኖርበታል፡፡ የራሳቸው እምነት ተከታይ ሆነው ሚዛናዊ ጽሑፍ ያቀረቡትን የሚያጣጥሉ፣ ምንጭ የሌለው የጥላቻ ጽሑፍ የሚጽፉትን ታላቅ ነገር እንዳገኙ ሁሉ እየጠቀሱ ሲያሞካሹ ሕሊናቸውን እይቆጠቁጠውም፡፡ ኦርቶዶክሳውያንም ብቻ ሳይሆኑ ሌሎች ምሁራንም ምርቱን ከገለባው፣ እውነቱን ከሐሰት በመለየት ለአንባብያን ማድረስ አለባቸው፡፡

በየጊዜው እነዚህ ጥፋቶች ተፈፀሙ ስንል፣ በጥፋቱ ላይ የተሠማሩ ሰዎች ወደ ኅሊናቸው እንዲመለሱ እንጂ እሳትን በእሳት አጥፉ ለማለት አይደለም፡፡ በቤተ ክርስቲያን ላይ በዚህ አምሳ ዓመት የተፈጸመው በዓላማ መሆኑን የሚያሳየው በአንድ ወቅት በሀገሪቱ ከፍተኛ የሥልጣን ርከን ላይ የነበሩ ሰው «ሥልጣኑን ከአማራና ከኦርቶዶክስ አርቀነዋል» በማለት ጠቅላይ ሚኒስቴር ኃይለ ማርያም የተመረጡ ሰሞን መናገራቸው ማሳያ ነው፡፡ እንደዚያ ማለት መብታቸው ቢሆንም፣ በመንግሥት ኃላፊነት ላይ ሆኖ ለሀገር ባለውለታ የሆነችን፣ ቅርሶቿ በዓለም የምርምር መድረክ ግንባር ቀደም ሚና የምትጫወትን ቤተ ክርስቲያን ማጥፋት ወይም አጥፊዎች ሲያወድሟት ቆሞ ማየት ተገቢ ነው ብለን አናምንም፡፡ በመሆኑም እንዲህ ዓይነት ሰዎችና አካላት ቤተ ክርስቲያን ለማጥፋት ብለው ሲሠሩ ኦርቶዶክሳውያን እና የሚያመዛዝኑ ወገኖች ደግሞ ቢችሉ በመገሠጽና በማረም ቢይችሉ የጥፋት ተባባሪ ባለመሆን የቤተ ክርስቲያን እና የሀገር ሀብት እንዳይጠፋ ማስጠበቅ ይኖርባቸዋል፡፡ በህዝብ አስተዳደር ላይ የሚገኙ አካላትም በታሪክ ላለመጠየቅ ከሕሊና ፍርድም ነፃ ለመሆን ቤተ ክርስቲያን ሲቃጠል ምእመናን ሲሳደዱና ሲገደሉ ሕጋዊ ርምጃ መውሰድ ይኖርባቸዋል፡፡ የራሳቸው በሆነ ስሜት ውስጥ ሆነው የሚነጐዱ ሰዎች ለከፋና ዕውነታውን ከመቀበል ይልቅ፣ ለበለጠ ነገር በእልክ መሔድን የሚመረጡ ስለሆነ ‹‹ጨርሰን ባንበገር›› ቢቀር?

 ማንኛውም የዕምነት ተቋም ተከታዮች ሲሞቱ የሚያሳርፍበት ቦታ ሕጋዊ በሆነ መንገድ ጠይቆ ማግኘት መብቱ ቢሆንም፤ በሲዳሣ ሀገረ ስብከት የወንዶ ገነት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያንን የቀብር ቦታ ፕሮቴስታንቶች ሕገ ወጥ በሆነ መንገድ ወስደው የራሳቸው የቀብር ቦታ አድርገውታል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ይዞታዋን ለማስመለስ እስከ ሰበር ሰሚ ችሎት ተከራክራ ይዞታዋ ቢወሰንላትም የፍርድ ቤቱን ውሳኔ የሚያስተገብር በመጥፋቱ ጉዳዩ ወደ ፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ተሸጋግሮ ይገኛል፡፡ በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ለቤተ ክርስቲያን መሥሪያ ቦታ ሲጠየቅ በጎ ምላሽ አለመገኘቱ የልማት ቦታም በሊዝ ካልሆነ ማግኘት አለመቻሉ ተገልጧል፡፡»ክርስቲያኖችም ከስሜታዊነት ወጥተን በማስተዋል እንመላለስ፡፡ አካባቢያችንንም እንጠበቀ፣ ለመንግሥት አካላትም ትክክለኛውን መረጃ እናድርስ፡፡ የሚፈጸሙ ጥፋቶች እንዲቆሙ ድምፃችንን እናሰማ ጥፋቶችንም መዝግበን እንያዝ፡፡

ይቆየን

ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከሰኔ ፩-፲፭ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም