የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በጸሎት ተከፈተ!

በሕይወት ሳልለው

በዓመት ፪ ጊዜ የሚካሔደው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ግንቦት ፲፬ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም. በጸሎት ተከፈተ! በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ እየደረሰባት ያለውን ችግር ለመፍታት ከአሁን ቀደም ጸሎተ ምሕላው በአግባቡ ያልተካሔደ መሆኑን በመግለጫቸው ያሳወቁት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት «በአክሱምና በሌሎች ጥቂት ገዳማትና አድባራት በዕንባና በልቅሶ የታጀበ ጸሎተ ምሕላ ቢደረግም፤ በርእሰ ከተማ ከአዲስ አበባ ጀምሮ በብዙ ቦታ ጸሎተ ምሕላው ተጠናክሮ እንዳልተካሄደ ለማወቅ ተችሏል» በማለት አስታውቀዋል፡፡

ሁላችንም ከእህልና ውኃ በመለየት መጸለይና ፈጣሪያችንን  መማጸን እንዳለብንም ቅዱስ ፓትርያርኩ አስገንዝበዋል፡፡ «ሁሉን ማድረግ የሚቻለው፤ ምንም ምን የሚሳነው የሌለ፤ እግዚአብሔር አምላካችን ብቻ ነውና፤ እሱ በመሠረተልን ስልት እጃችንን ወደ እግዚአብሔር እንድንዘረጋ፤ ሕዝቡም ሁሉ፤ ሀገሪቱም በአጠቃላይ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር እንድትዘረጋ፤ እኛም በየሀገረ ስብከታችን ተገኝተን፤ራሳችን መሪዎች ሆነን ጸሎተ ምሕላውን እንድንመራ፤ ትምህርተ ወንጌሉን እንድንሰጥ፤ቂም በቀል እንዲከስም፤ ይቅርታ እንዲያብብ፤ ያለማቋረጥ የሽምግልና ሥራን መሥራት ከሁላችን ይጠበቃል» ሲሉም መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

እንዲሁም አያይዘው በሀገራችን ውስጥ ያለውን ጦርነት በመንቀፍ፤ ቅዱስ ሲኖዶሱ ከሕዝቡ ጋር በመወያየት በሰላማዊ መንገድ ያሉትን ችግሮች ለመፍታት፤ ማንኛውንም አይነት ግጭት በመቃወምና አንድነትን በመፍጠር፤ ዘላቂ መፍትሔ ለማግኘት እንደሚጥር ገልጸዋል፡፡ ከዚህም በአሻገር ተፎካካሪ ፓርቲዎች ኃይለ ቃል ከመጠቀምና ስም ከማጥፋት እንዲታቀቡ በእግዚአብሔር ስም አሳስበዋል፡፡

በመጨረሻም የዚህ ዓመት የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ  በአቤቱታ ከተመለሱት የቤተ ክርስቲያኗ ታላላቅና ሁለት መለስተኛ ሕንጻዎች ማግስት በመከናወኑ ከሌላው ዓመት እንደሚለይ አስታውቀዋል፡፡