እግዚአብሔር ዝም ይላልን?
በየግል ሕይወታችን ችግር ሲገጥመን መፍትሔ ለማግኘት ወደ እግዚአብሔር እንደምንጮኸው ሁሉ በቤተ ክርስቲያን ላይ መከራ ሲመጣም እንዲሁ ከርሱ መፍትሔ እንጠብቃለን። በእኛ መረዳት የዘገየ ወይም ዝም ያለ ሲመስለን “ለምን?” እንላለን። “ካህናት እየታረዱ፣ አብያተ ክርስቲያናት እየተቃጠሉ፣ ምእመናን እየተፈናቀሉ፣ ቅዱሳት መጻሕፍት እየተቆነጸሉ፣ ቤተ መቅደሱ እየተደፈረ፣ እንዴት እግዚአብሔር ዝም ይላል?” እንላለን። እንደዚህ የምንለው ምናልባትም አንዳች መቅሠፍት ወርዶ እንዲህ የሚያደርጉ ሰዎችን ያጠፋቸው ይሆናል ብለን ስለምንጠብቅና እንዳሰብነው ሳይሆን ሲቀር ሊሆን ይችላል። ምንም እናስብ ብቻ እኛ በጠበቅነው መንገድ ነገሮች ስላልሆኑ ግራ እንጋባለን፤ ከዚያም አልፈን ተስፋ እንቆርጣለን።