የዐቢይ ጾም ሳምንታት (ለሕፃናት) – ክፍል አንድ

በልደት አስፋው

የካቲት ፴ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ደኅና ናችሁ? እግዚአብሔር ይመስገን!፡፡ ልጆች! በልዩ ልዩ ምክንያት አልችል ብለን ዘግይተናል፡፡ በቅድሚያ በገባነው ቃል መሠረት ወቅቱን ጠብቀን ትምህርቱን ባለማቅረባችን እናንተን ይቅርታ እንጠይቃለን፡፡

ልጆች! የካቲት ፲፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ባቀረብንላችሁ ትምህርት ከሰባቱ አጽዋማት መካከል ዐቢይ ጾም አንዱ እንደኾነ፣ ዐቢይ ጾም ማለት ታላቅ ጾም ማለት እንደኾነ፣ ጾሙ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጾመው ጾም በመኾኑ ታላቅ እንደተባለ፣ ዕድሜአቸው ሰባት ዓመት ከኾናቸው ሕፃናት ጀምሮ ዅሉም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማኞች ዐቢይ ጾምን እና ሌሎችንም አጽዋማት መጾም እንደሚገባቸው፣ እንደዚሁም ስምንቱ የዐቢይ ጾም ሳምንታት (እሑዶች) ስማቸው ማን ማን እንደሚባል ነግረናችሁ ነበር፡፡

ልጆች! ሰባቱ አጽዋማት ማን ማን እንደሚባሉም ጠይቀናችሁ ነበር አይደል? መልሱንስ ጠይቃችሁ ተረዳችሁ? በጣም ጥሩ ልጆች! መልሱን እናስታውሳችሁ፤ ሰባቱ አጽዋማት የሚባሉት፡-

፩. ጾመ ነቢያት

፪. ጾመ ገሃድ (ጋድ)

፫. ጾመ ነነዌ

፬. ዐቢይ ጾም

፭. ጾመ ድኅነት (ረቡዕ እና ዓርብ)

፮. ጾመ ሐዋርያት

፯. ጾመ ፍልሰታ (የእመቤታችን ጾም) ናቸው፡፡

በአሁኑ ሰዓት ዐቢይ ጾምን እየጾምን ነው፡፡ የምንገኘውም ሦስተኛው ሳምንት ላይ ሲኾን ስሙም ‹‹ምኵራብ›› ይባላል፡፡ የሚቀጥለውና አራተኛው ሳምንት ደግሞ ‹‹መጻጕዕ›› ተብሎ ይጠራል፡፡

ልጆች! በዛሬው ዝግጅታችን ከመጀመሪያው እሑድ እስከ ሦስተኛው እሑድ (ከዘወረደ ጀምሮ እስከ ምኵራብ) ድረስ የሚገኙትን የዐቢይ ጾም ሳምንታት የሚመለከት ትምህርት ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡ ትምህርቱን እንድከታተሉት በአክብሮት ጋብዘናችኋል!

፩. ዘወረደ

ልጆች! ከዐቢይ ጾም ሳምንታት መካከል የመጀመሪያው ሳምንት ‹‹ዘወረደ›› ይባላል፡፡ ዘወረደ ማለት ከላይ የመጣ፣ የወረደ ማለት ነው፡፡ ይህም አምላካችን ዓለምን ለማዳን ሲል ሥጋ መልበሱን (ሰው መኾኑን) ያመለክታል፡፡ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማይ ወርዶ፣ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ፣ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቆ፣ ወንጌልን ለዓለም ካስተማረ በኋላ በፈቃዱ መከራ ተቀብሎ፣ በመስቀል ተሰቅሎ፣ ሞቶ፣ ከሙታን ተነሥቶ ዓለምን አድኗል፡፡ ልጆች! የመጀመሪያው ሳምንት የአምላካችን የማዳን ሥራ በስፋት የሚነገርበት ወቅት በመኾኑ ‹‹ዘወረደ›› ተብሎ ተሰይሟል፡፡

፪. ቅድስት

ሁለተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹‹ቅድስት›› ይባላል፡፡ ቅድስት ማለት የተለየች፣ የተመረጠች፣ የከበረች ማለት ነው፡፡ ልጆች! ለምን የተለየች፣ የተመረጠች፣ የከበረች እንደተባለች ታውቃላችሁ? ቅዱስ አምላካችን እግዚአብሔር ዓለምን (ሰውን) ለመቀደስ ሲል ወደ ምድር መምጣቱንና ዐቢይ ጾምን መጾሙን ለማስረዳት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የሰንበትን ክብር ለማስገንዘብ ነው፡፡ ሰንበት ቅድስት፣ የተለየች፣ የተመረጠች፣ የከበረች ዕለት ናት፡፡ ስለዚህም ልጆች! ሁለተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹‹ቅድስት›› ተብሎ ይጠራል፡፡

፫. ምኵራብ

ልጆች! ሦስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ደግሞ ‹‹ምኵራብ›› ይባላል፡፡ ምኵራብ ማለት አዳራሽ ማለት ነው፡፡ ምኵራብ ድሮ የነበሩ የእግዚአብሔር ሰዎች መንፈሳዊ ትምህርት ይማሩበት የነበረ  ሥፍራ ነው፡፡ በአንድ ወቅት ይህንን የጸሎት ሥፍራ ሰዎች የንግድ ቦታ አደረጉት፡፡ ይህንን ዓለማዊ ተግባር ሲፈጽሙ የነበሩትን ዅሉ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል፡፡ እናንተ ግን የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችሁት›› ብሎ ከምኵራብ አስወጣቸው፡፡ ከዚያም ቃለ እግዚአብሔር አስተማራቸው፡፡ ልጆች! የእግዚአብሔር ቤት የጸሎት ቤት እንጂ የንግድ መነገጃ ሥፍራ አለመኾኑን ከዚህ ታሪክ እንማራለን፡፡

ለዛሬው በዚህ ይቆየን፡፡ ቀጣዩን ትምህርት ደግሞ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በሚቀጥለው ዝግጅት ይዘንላችሁ እንቀርባለን፡፡ እስከዚያው ድረስ ሰላመ እግዚአብሔር ከዅላችን ጋር ይኹን!

ዐቢይ ጾም

በልደት አስፋው

የካቲት ፲፩ ቀን ፳፻፱ .

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ባለፈው ሳምንት ስለ ነቢዩ ዮናስ እና ስለ ነነዌ ሰዎች የጻፍንላችሁን ታሪክ አነበባችሁት? ጎበዞች፡፡ ከታሪኩ ውስጥ ያልገባችሁ ትምህርት ካለ ከቤተ ክርስቲያን መምህራን በመጠየቅ መረዳት ትችላላችሁ፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን ደግሞ ስለ ዐቢይ ጾም አጭር ትምህርት ይዘንላችሁ ቀርበናል፤

ልጆች! ‹‹ዐቢይ ጾም›› ማለት ታላቅ ጾም ማለት ነው፡፡ ዐቢይ ጾም በቤተ ክርስቲያናችን በዐዋጅ እንዲጾሙ ከታወጁ ከሰባቱ አጽዋማት መካከል አንዱ እና ዋነኛው ነው፡፡ ጾሙ ታላቅ የተባለበት ምክንያትም ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጾመው ጾም በመኾኑ ነው፡፡

ልጆች! ይኽንን ጾም ዕድሜአቸው ሰባት ዓመት ከኾናቸው ሕፃናት ጀምሮ ዅሉም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማኞች እንዲጾሙት የቤተ ክርስቲያናችን ሕግ ያዝዛል፡፡ እንዴት ነው ታዲያ ሰባት ዓመትና ከዚያ በላይ የኾናችሁ ሕፃናት አጽዋማትን እየጾማችሁ ነው አይደል? እየጾማችሁ ከኾነ በጣም ጎበዞች ናችሁ ማለት ነው፤ በዚሁ ቀጥሉ፡፡

ዕድሜአችሁ ለመጾም ደርሶ መጾም ያልጀመራችሁ ካላችሁ ደግሞ ከቤተሰቦቻችሁ ጋር ተመካክራችሁ እስከምትችሉበት ሰዓት ድረስ በመጾም ጾምን ከልጅነታችሁ ጀምራችሁ ተለማመዱ፤ የጾሙ ተሳታፊዎችም ኹኑ እሺ? በሕመም ምክንያት መድኀኒት የምትወስዱ ከኾነ ግን መድኀኒታችሁን ስትጨርሱ ትጾማላችሁ፡፡

ልጆች! የዘንድሮው (የ፳፻፱ ዓ.ም) ዐቢይ ጾም የሚጀመረው መቼ እንደ ኾነ ታውቃላችሁ? የካቲት ፲፫ ቀን ነው፡፡ የሚፈታው ማለትም የሚፈሰከው ደግሞ ከአምሳ አምስት ቀናት በኋላ ሚያዝያ ፰ ቀን ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ዓመት የፋሲካ በዓል ሚያዝያ ፰ ቀን ይውላል ማለት ነው፡፡

በዐቢይ ጾም ውስጥ የሚገኙት አምሳ አምስቱ ቀናት በስምንት ሳምንታት (እሑዶች) የተከፋፈሉ ናቸው፡፡ የእያንዳንዱ ሳምንት ወይም እሑድ መጠሪያ ስሞችም የሚከተሉት ናቸው፤

የመጀመሪያው ሳምንት (እሑድ) – ዘወረደ

ሁለተኛው ሳምንት (እሑድ) – ቅድስት

ሦስተኛው ሳምንት (እሑድ) – ምኵራብ

አራተኛው ሳምንት (እሑድ) – መጻጕዕ

አምስተኛው ሳምንት (እሑድ) – ደብረ ዘይት

ስድስተኛው ሳምንት (እሑድ) – ገብር ኄር

ሰባተኛው ሳምንት (እሑድ) – ኒቆዲሞስ

ስምንተኛው ሳምንት (እሑድ) – ሆሣዕና

ተብለው ይጠራሉ፡፡

የፋሲካ በዓል የሚከበርበት የመጨረሻው የዐቢይ ጾም እሑድ ደግሞ ትንሣኤ ወይም ፋሲካ ይባላል፡፡

ልጆች! እንደ እግዚአብሔር መልካም ፈቃድ እነዚህን ሳምንታት (እሑዶች) የሚመለከት ትምህርት በየሳምንቱ እናቀርብላችኋለን፡፡ እስከዚያው ድረስ ከቤተ ክርስቲያን መምህራን ወይም ደግሞ ከወላጆቻችሁ ጠይቃችሁ ሰባቱ አጽዋማት የሚባሉት ማን ማን እንደ ኾኑ አጥንታችሁ ጠብቁን እሺ?

በሉ እንግዲህ ልጆች በሌላ ዝግጅት እስከምንገናኝ ድረስ ሰላመ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይኹን፡፡

ይቆየን

ነቢዩ ዮናስ ክፍል ሁለት

በልደት አስፋው

የካቲት ፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም  

እንዴት ናችሁ ልጆች? እኛ እግዚአብሔር ይመስገን በጣም ደኅና ነን፡፡ በትናንትናው ዝግጅታችን እግዚአብሔር አምላካችን ነቢዩ ዮናስን አስተምር ብሎ ወደ ነነዌ ሰዎች እንደ ላከው፣ እርሱ ግን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ላለመቀበል በመርከብ ተሳፍሮ ወደ ሌላ አገር እንደ ሸሸ፣ በነቢዩ ዮናስ ምክንያትም መርከቡ እስኪሰጥም ድረስ ባሕሩ በማዕበል እንደ ተናወጠ፣ በዚህ የተነሣም ተሳፋሪዎቹ ዕጣ ተጣጥለው ነቢዩ ዮናስን ወደ ባሕሩ እንደ ጣሉት ነግረናችሁ ነበር፡፡ ልጆች! ቀጣዩን ክፍል ደግሞ እንደሚከተለው አቅርበንላችኋል፤

እናም ሰዎቹ ነቢዩ ዮናስን ወደ ባሕር ሲጥሉት እግዚአብሔር ያዘጋጀው ታላቅ ዓሣ ዋጠው፡፡ ነቢዩ ዮናስም በዓሣው ሆድ ውስጥ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት ቆየ፡፡ በዚያ ጨለማ በኾነ የዓሣ ሆድ ውስጥ ለሦስት ቀን መቆየት አያስፈራም ልጆች? በጣም ነው የሚያስፈራው፡፡ ነቢዩ ዮናስም እግዚአብሔር እንዲያወጣው በዓሣው ሆድ ውስጥ ኾኖ አብዝቶ ጸለየ፡፡ እግዚአብሔርም የነቢዩ ዮናስን ጸሎት ሰምቶ ዓሣውን እንዲተፋው አዘዘው፡፡ ዓሣውም ነቢዩ ዮናስን በየብስ (በደረቅ መሬት) ላይ ተፋው፡፡ ነቢዩ ዮናስም ‹‹ይህቺ አገር ማን ትባላለች?›› ብሎ የአካባቢው ነዋሪዎችን ሲጠይቅ አገሪቱ ነነዌ እንደ ኾነች ነገሩት፡፡ ይገርማችኋል ልጆች! ከዚህ በኋላ ነቢዩ ዮናስ የእግዚአብሔርን ቃል እሺ ብሎ ተቀብሎ ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ገብቶ ‹‹በሦስት ቀን ውስጥ ነነዌ ትገለባበጣለች (ትጠፋለች)›› ብሎ አስተማረ፡፡

የነነዌ ሰዎችም ቃሉን ሰምተው ከኀጢአታቸው ተመልሰው፣ ማቅ ለብሰው ንስሐ ገቡ፡፡ ከከንጉሡ ጀምሮ ሕፃናትም ጭምር፣ እንስሳትም ሳይቀሩ ምንም ምግብ ሳይቀምሱ፣ ውኀም ሳይጠጡ ለሦስት ቀን ጾሙ፡፡ እንዲምራቸውም ወደ እግዚአብሔር ጮኹ፡፡ እግዚአብሔርም ከክፉ መንገዳቸው መመለሳቸውንና ንስሐ መግባታቸውን አይቶ ይቅር አላቸው፤ ነነዌንም ከጥፋት አዳናት፡፡ ልጆች ነቢዩ ዮናስ እግዚአብሔርን አልታዘዝም ያለው ለምን መሰላችሁ? እኔ ነነዌ ትገለባበጣለች (ትጠፋለች) ብዬ ባስተምር ሕዝቡ ተጸጽቶ ይቅርታ ቢጠይቁ እግዚአብሔር ይቅር ሲላቸው እኔ ውሸታም ነቢይ እባላለሁ ብሎ ፈርቶ ነበር፡፡ ነገር ግን የነነዌ ሰዎች ነቢዩ ዮናስንም ውሸታም ነው አላሉትም፡፡ ትምህርቱን ተቀብለው ከጥፋት በመዳናቸው እግዚአብሔርን አመስግነዋል፡፡ እግዚአብሔር ምን ያህል ሩኅሩኅና ቸር እንደኾነ አያችሁ ልጆች? ምንም እንኳን እኛ ብንበድለውም፣ ብናሳዝነውም ተጸጽተን ንስሐ ከገባን የቀደመውን በደላችንን ደምስሶ ኀጢአታቻንን ይቅር ይለናል፡፡

ልጆች ነነዌ ከመቶ ሃያ ሺሕ የሚበልጡ ሰዎችና ብዙ እንስሳት የሚኖሩባት ታላቅ ከተማ ነበረች፡፡ እነኚህ ዅሉ ሰዎች ንስሐ ባይገቡ ኖሮ ነነዌን እሳት ይበላት ነበር፡፡ የነነዌ ሰዎች ከበደላቸው ተጸጽተው፣ ንስሐ ገብተው በመጾማቸውና በመጸለያቸው እግዚአብሔር ከጥፋት አድኗቸዋል፡፡ ልጆች! እኛም ዛሬ እግዚአብሔርን ብንበድለውና እርሱ የማይወደውን ክፋት ብንፈጽም እንደ ነነዌ ሰዎች ተጽጽተን ንስሐ ከገባን አምላካችን ቸር፣ ታጋሽ እና ይቅር ባይ አምላክ ስለኾነ ኀጢአታችንን ይቅር ብሎ ከጥፋት ያድነናል፡፡ እኛ ክርስቲያኖች በየዓመቱ ጾመ ነነዌን የምንጾመውም እግዚአብሔር ኀጢአታቻንን ይቅር እንዲለን ነው፡፡ በሉ እንግዲህ ልጆች በሌላ ጊዜ በሌላ ታሪክ እስከምንገናኝ በደኅና ቆዩ፡፡ ሰላመ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይኹን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ነቢዩ ዮናስ ክፍል አንድ

እንደምን አላችሁ ልጆች? ከአሁን በፊት ለእናንተ የሚኾኑ ትምህርታዊ ጽሑፎችን በድረ ገጻችን ስናቀርብላችሁ ነበር፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን በልዩ ልዩ ምክንያት ዝግጅቱን አቋርጠን ቆይተናል፡፡ ለዚህም እናንተን ይቅርታ እየጠቅን ከዛሬ ጀምሮ ወቅታዊ ይዘት ያሏቸውን ትምህርታዊ ጽሑፎች በየጊዜው እንደምናቀርብላችሁ ቃል እንገባለን፡፡ በዛሬው ዝግጅታችንም የነቢዩ ዮናስንና የነነዌ ሰዎችን ታሪክ ይዘንላችሁ ቀርበናል፤ መልካም የንባብ ጊዜ ይኹንላችሁ!

ነቢዩ ዮናስ ክፍል አንድ

በልደት አስፋው

የካቲት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ልጆች! እግዚአብሔር ለሕዝቡ መልእክት ለማስተላለፍ ሲፈልግ ወደ ሕዝቡ ከሚልካቸው ነቢያት መከካል አንዱ ነቢዩ ዮናስ ነው፡፡ ታዲያ አንድ ቀን ምን ኾነ መሰላችሁ ልጆች፣ ወደ አንዲት ታላቅ ከተማ ሔዶ እንዲሰብክ የእግዚአብሔር ቃል ለነቢዩ ዮናስ መጣለት፡፡ ልጆች ይህች ታላቅ ከተማ ነነዌ ትባላለች፡፡ በዚህች በነነዌ ከተማ የሚኖሩ ሰዎች ኀጢአታቸው እጅግ በዝቶ ነበር፡፡ ርኅሩኁ አምላካችን እግዚአብሔር የሰውን መዳን እንጂ ጥፋቱን ስለማይፈልግ ንስሐ ግቡ ብሎ እንዲያስተምራቸው ነቢዩ ዮናስን ወደ ነነዌ ላከው፡፡ ነቢዩ ዮናስ ግን የፈጣሪውን ትእዛዝ ላለመፈጸም ሊኮበልል አሰበ፡፡ ከዚያም ተርሴስ ወደምትባል አገር የምታልፍ መርከብ አግኝቶ በእርሷ ተሳፈረ፡፡ ልጆች ከእግዚአብሔር ፊት መኮብለል ወይም መሸሽ ይቻላል? አይቻልም አይደል? እስቲ ነቢዩ ዮናስ የተሳፈረባት መርከብ ምን እንደ ገጠማት እንመልከት፤

ነቢዩ ዮናስ በመርከብ ተሳፍሮ ሲሔድም እግዚአብሔር ታላቅ ነፋስን አምጥቶ በባሕሩ ላይ ታላቅ ማዕበልን አስነሣ፡፡ በዚህ ጊዜ መርከቢቱ ልትሰበር ደረሰች፡፡ ለምን እንደዚህ እንደኾነ አወቃችሁ ልጆች? ነቢዩ ዮናስ ከእግዚአብሔር ፊት ለመሸሽ በማሰቡ ነው፡፡ መርከቢቷ ውስጥ ያሉ ሰዎችም እጅግ ፈሩ፡፡ መርከቧ ክብደት ስለበዛባት ነው ብለው አስበው በውስጧ የነበረውን ዕቃ ዅሉ ወደ ባሕር ቢጥሉትም መርከቢቱ ግን ልትረጋጋ አልቻለችም ነበር፡፡ ማዕበሉም አልቆም አለ፡፡ ልጆች ይህ ዅሉ ሲኾን ግን ነቢዩ ዮናስ ተኝቶ ነበር፡፡ ከዚያም የመርከቡ አለቃ ወደ እርሱ ቀረበና ‹‹ምነው ተኝተሃል? እንዳንጠፋ እግዚአብሔር ያስበን እንደኾነ ተነሥተህ አምላክህን ጥራ›› አለው፡፡ በመርከቡ ውስጥ ያሉት ሰዎችም ‹‹ይህ ክፉ ነገር በማን ምክንያት እንዳገኘን እናውቅ ዘንድ ኑ ዕጣ እንጣጣል›› ተባብለው ዕጣ ሲጣጣሉ ዕጣው በነቢዩ ዮናስ ላይ ወጣ፡፡ ሰዎቹም ነቢዩ ዮናስን ‹‹ይህ ክፉ ነገር በማን ምክንያት እንዳገኘን እባክህ ንገረን?›› አሉት፡፡

ነቢዩ ዮናስም ከእግዚአብሔር ፊት መኮብለሉን በነገራቸው ጊዜ ሰዎቹ በፍርኀት ኾነው ‹‹ይህ ያደረግኸው ምንድን ነው?›› አሉት፡፡ ባሕሩንም ሞገዱ እጅግ ያናውጠው ነበርና ‹‹ባሕሩ ጸጥ እንዲል ምን እናድርግብህ?›› ሲሉ ጠየቁት፡፡ እርሱም ‹‹ይህ ታላቅ ማዕበል በእኔ ምክንያት እንዳገኛችሁ አውቃለሁ፡፡ አንሥታችሁ ወደ ባሕር ጣሉኝ፡፡ ባሕሩም ጸጥ ይልላችኋል፤›› አላቸው (ትንቢተ ዮናስ ፩፥፩-፲፫)፡፡ ሰዎቹም ነቢዩ ዮናስን ወደ ባሕሩ ጣሉት፡፡ በዚህ ጊዜ ባሕሩ ከመናወጥ ጸጥ አለ፡፡ ልጆች! ባሕሩ ሲናወጥ የነበረው ለምን እንደኾነ ተረዳችሁ? ዮናስ እግዚአብሔር ያዘዘውን ትቶ ለመሸሽ በመርከቡ በመሳፈሩ ነው! እግዚአብሔርን ሳንታዘዝ ያሰብንበት ቦታ መድረስ የምንችል ይመስላችኋል ልጆች? አንችልም አይደል? አዎ፤ አንችልም፡፡ ምክንያቱም ዓለሙን ዅሉ የፈጠረ እግዚአብሔር ነውና በባሕርም ኾነ በየብስ (በደረቅ መሬት) ብንጓዝ ከእርሱ መሰወር ፈጽሞ አይቻለንም፡፡ እግዚአብሔር የሌለበት ቦታና ከእርሱ እይታ የተሰወረ ምንም ነገር የለምና፡፡

ልጆች! ቀጣዩን ክፍል ነገ ይዘንላችሁ እንቀርባለን እሺ? ለዛሬው ከዚህ ላይ ይቆየን፡፡

ጰራቅሊጦስ (ለሕፃናት)

ሰኔ 14 ቀን 2005 ዓ.ም.

በቤካ ፋንታ

 

  • እግዚአብሔር የሠራት ቀን ይህች ናት/ መዝ 118፥24/

ይህች ታላቅ ዕለት  ከቅድስት ሥላሴ አንዱ አካል የሆነው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ለቅዱሳን ሐዋርያት፣ ለቅዱሳን አርድእትና ለቅዱሳት ሴቶች የተገለጠባት ዕለት ናት፡፡    እነዚህ ሁሉ በጸሎት ተግተው በሚጸልዩበት ወራት መንፈስ ቅዱስ  በተከፋፈሉ የእሳት ልሳን አምሳል የወረደበት ቅዱስ ቀን ነው፡፡

አስቀድሞ ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱሳን ሐዋርያት ደብረ ዘይት በተባለ ታላቅ ተራራ ላይ ሳሉ እንዲህ ብሎ አስተምሯቸው ነበር “ኀይልን ከላይ ከአርያም እስክልክላችሁ ድረስ በኢየሩሳሌም በጸሎት ቆዩ፡፡”/ሉቃ 24፡36/ መቶ ሃያው ቤተሰብም በኢየሩሳሌም ሀገር በምትገኝ በቤተ መቅደስ በአንድነት ሆነው በጸሎት በመትጋት ቆዩ፡፡ ልጆችዬ መቶ ሃያው ቤተሰብ የሚባሉት 12ቱ ሐዋርያት፣ 72ቱ አርድእት/አገልጋዮች/ እና 36ቱ ቅዱሳን አንስት/ሴቶች/ ናቸው፡፡

ከዕርገት በኋላ በአሥረኛው ቀን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሐዋርያት ወዳሉበት፣ በጸሎትና በምሥጋና ወደ ሚተጉበት ሥፍራ በእሳት አምሳል /ምሳሌ/ ወርዶ በእያንዳንዳቸው ላይ ተቀመጠባቸው፡፡ ይሄንንም  ሁኔታ ተከትሎ  ምስጢር ተገለጠላቸው፣ ይፈሩ የነበሩት ሐዋርያትም ወንጌልን ለማስተማር ደፋሮች ሆኑ፣ በተለያየ ቋንቋዎች እንዲናገሩ እውቀት ተሰጣቸው፤ የእግዚአብሔርንም ጸጋ ተቀበሉ፡፡ ይህንን ታላቅ ኀይል እና ሰማያዊ ስጦታን የሰጣቸውን እግዚአብሔርን በታላቅ ዝማሬና እልልታ አመሰገኑት፡፡

በዓለ ሃምሳ የሚባለውን የአይሁድን በዓል ለማክበር ከተለያዩ ሀገራት የመጡ በጊዜው  የነበሩ ቁጥራቸው በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ  ሰዎች የሐዋርያቱን ታላቅ የዝማሬና የእልልታ ድምፅ ሰሙ፡፡ ከመቶ ሃያው ቤተሰብ መካከል አንዱ የሆነው  ቅዱስ ጴጥሮስ የተሰበሰቡት ሁሉም እንዲሰሙት ድምፁን ከፍ አድርጎ ቃለ እግዚአብሔርን እንዲህ ብሎ አስተማራቸው፡፡ “እናንተ የእስራኤል ሰዎች ሆይ እኛን የሰው ልጆችን ለማዳን እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆኖ ወደ ምድር መጥቶ ከክፉ ሥራ ተመለሱ፣ ኀጢአትን አታድርጉ፣ በቅድስና ኑሩ፣ ወደ እኔም ተመለሱ ቢላችሁ፤ እናንተ ግን ምንም በደል ሳይኖርበት ገረፋችሁት፣ አንገላታችሁት፣ በመስቀል ላይም ሰቀላችሁት፡፡ እርሱ ግን እግዚአብሔር ነውና ሞትን ድል አድርጎ ተነሣ፡፡ እርሱ ግን አሁንም ይቅር ባይ ነውና ከኀጢአታችሁ ተመለሱ ንስሐም ግቡ ፡፡” በማለት አስተማራቸው፡፡

የተሰበሰቡት ሰዎች ሁሉ ተገረሙ፡፡ ምክንያቱም ሐዋርያት በፊት የሚያውቁት አንድ ቋንቋ ብቻ ነበረ፡፡ በዚህ ሰዓት ግን ሰባ ሁለት ቋንቋን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ገልጦላቸው ለሁሉም በየቋንቋቸው አስተማሯቸው፡፡ ይህንንም ድንቅ ተአምር ከተመለከቱት ብዙዎች እግዚአብሔርን አመሰገኑት፡፡ ወደ ሐዋርያትም ቀርበው “አባቶቻችን እናንተ የእግዚአብሔር አገልጋዮች ናችሁና ምከሩን፡፡ እንደ እናንተ የእግዚአብሔር ልጆች እንድንሆንና በቅድስና እንድንኖር ምን እናድርግ?”በማለት ጠየቁ፡ በዚያች ቀን ቁጥራቸው  ሦስት ሺ ያህል ሰዎች በቅዱስ ጴጥሮስ ትምህርት አምነው  ክርስቲያን ለመሆን ቀረቡ፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም እንዲህ አላቸው፡፡ “እነሆ ሁላችሁም ንስሐ ግቡ፡፡ በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት አምናችሁ ተጠመቁ፡፡” አላቸው በዚያው ዕለትም ሦስት ሺ ሰዎች ወደ ሐዋርያት በመቅረብ ኀጢአታቸውን ተናገሩ፤ ሐዋርያትም እግዚአብሔር ይፍታችሁ እያሉ ልጅነትን የሚያሰጣቸውን ጥምቀት አጠመቁዋቸው፡፡

ከዚያ ቀን ጀምሮም በየዓመቱ ይህችን ታላቅ የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን የምትባለውን በዓለ ጰራቅሊጦስን ክርስቲያኖች በታላቅ ደስታና ምሥጋና እናከብራታለን፡፡ እናንተም ልጆችዬ እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት በቤተ ክርስቲያን ተገኝታችሁ ቅዳሴ በማስቀደስ፣ መዝሙር በመዘመር እና በመጸለይ ይህችን ታላቅ በዓል ልታከብሯት ይገባል፡፡

የእግዚአብሔር አብ ጸጋ የእግዚአብሔር ወልድ ቸርነት የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ አንድነት ከሁላችን ጋር ይሁን  አሜን፡፡

ዕርገት(ለሕፃናት)

ሰኔ 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

በአብርሃም ቸርነት/ዘገዳመ ኢየሱስ/

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ በተነሣ በአርባኛው ቀን ቅዱሳን ሐዋርያት በጸሎት ይተጉ ወደነበረበት ቤት በመሄድ ደቀመዛሙርቱን ይዟቸው ከቤት በመውጣት መንገድ ጀመረ፡፡ እርሱ ከፊት ከፊት እየመራቸው እነርሱ እየተከተሉት ወደ ረጅሙና በረጃጅም ዛፎች ወደ ተሞወው ደብረ ዘይት ተራራ ይዟቸው ወጣ፡፡

በተራራው ጫፍ /አናት/ ላይ ሲደርሱ፤ በመካከላቸው ቆሞ ሐዋርያትን እንዲህ ብሎ መከራቸው “ከእኔ የተማራችሁትን ትምህርት ጠብቁ በቤተ ክርስቲያንም ጸንታችሁ ኀይልን ከሰማይ እስክልክላችሁ ቆዩ” ብሎ አዘዛቸው፡፡ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ አሥራ ሁለቱን ሐዋርያት እጁን በላያቸው ጭኖ (በአንብሮተ ዕድ) ሾማቸው፡፡

ይህንንም እየነገራቸው ከምድር ወደ ሰማይ ከፍ፣ ከፍ፣ ከፍ አለ፡፡ ነጭ የሆነችና ለዓይን በጣም የምታምር ብሩህ ደመናም አምላካችንን ተቀበለችው፡፡ ከዓይናቸውም እየራቀ፣ እየራቀ፣ ከእይታቸው ተሰወረባቸው፡፡
ሐዋርያትም ኢየሱስ ክርስቶስን በጣም ይወዱት ስለነበረ ሲለያቸው አዝነው አተኩረው ሰማይ ሰማዩን ለረጅም ሰዓት ተመለከቱ፡፡ ድንገትም ነጫጭ ልብስ የለበሱ ሁለት ቅዱሳን መላእክት በአጠገባቸው ቆመው ታዩአቸው፡፡ መላእክቱም ሐዋርያትን እንዲህ አሏቸው፡፡ “እናንተ የገሊላ ሰዎች ሆይ ወደ ሰማይ እያያችሁ ለምን አዝናችሁ ቆማችሁ፡፡ ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ ያረገው ኢየሱስ ከእናንተ ወደ ሰማይ ሲያርግ እንዳያችሁት እንዲሁ ዳግመኛ ወደ ምድር ይመጣል፡፡” አሏቸው፡፡

ሐዋርያቱም የመላእክቱን ማረጋጊያ ቃል ከሰሙ በኋላ ፈጥነው በኢየሩሳሌም ወደምትገኘው ቤተ መቅደስ በመሄድ እግዚአብሔር ቃል የገባላቸውን ኀይል ከሰማይ እንዲልክላቸው ቀን ከሌሊት በአንድነት ሆነው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምንም ከመካከላቸው አድርገው በጸሎት እየተጉ ቆዩ፡፡
ጥቅስ፡- ሉቃ.24፥50-53፣ ሐዋ.1፥9-14

hosaena

ሆሣዕና(ለሕፃናት)

ሚያዚያ 17 ቀን 2005 ዓ.ም.

በቤካ ፋንታ

hosaenaበኢየሩሳሌም ሀገር ውስጥ በምትገኝ በአንድ ትንሽ መንደር ውስጥ ነው የምኖረው፡፡ ከተወለድኩ ዛሬ 5 ዓመት ሞልቶኛል፡፡ ቀኑ ሰንበት ነው እቤት ውስጥ እየተጫወትኩ እናቴም በጓዳ ሥራ እየሠራች ድንገት የብዙ ሰዎች የእልልታ ድምጽ ሰፈሩ ውስጥ ተሰማ፡፡ እናቴም በፍጥነት ከጓዳ ሮጣ ወጥታ “ልጄ ልጄ ነይ እንሂድ ብላ በጀርባዋ ላይ አዝላኝ ሮጣ ከቤት ወጣች፡፡ እኔም በሁኔታው ተገርሜያለሁ፡፡

በሰፈር ውስጥ ያሉ ጓደኞቼ ሁሉ በእናታቸው ጀርባና በአባታቸው ትከሻ ላይ ሆነው ደስ ብሏቸው እንደ ወላጆቻቸው እልል ይላሉ፡፡ ወላጆቻችን ሁሉ ተሰብስበው ከሰፈራችን መውጫ ጋር ወዳለ ትልቅ የዘንባባ ዛፍ ተያይዘው አመሩ፡፡ ከዚያም የዘንባባ ዝንጣፊውን እየቆረጡ ሁሉም ያዙ ለእኛም ሰጡን፡፡ ከዚያ እልል እያልን በደስታ ወደ ቤተ መቅደስ እሮጥን፡፡
በመንገድ ላይ በጣም ብዙ ሕዝብ አየሁኝ ሁሉም ደስ ብሏቸው እነርሱም እንደኛ ወደ ቤተ መቅደስ ይሮጣሉ፡፡ የሕፃናቶቹን ብዛት ሳይ ውስጤ በጣም ደስ አለው፡፡ የገረመኝ ደግሞ የሚያለቅስ ልጅ አንድ እንኳን የለም፡፡ “ዛሬ የኛ የደስታና የዝማሬ ቀን ነው” ማለት ነው ብሎ ልቤ በደስታ ፈነደቀ፡፡

ወደ ቤተ መቅደስ ለመድረስ ጥቂት መንገድ ሲቀረን በርቀት ወደ ቤተ መቅደሱ የሚጓዙ በጣም በጣም ብዙ ሕዝብ ተመለከትኩኝ፡፡ እንደኛ እነርሱም ዘንባባ ይዘዋል፡፡ በመካከላቸው አንድ ትልቅ አህያ አየሁኝ፣ ከአህያይቱም ጋር ልጇ ውርንጫዋ አለች፡፡ የሚያማምር ልብስ በአህያዎቹ ጀርባ ላይ ተነጥፏል፡፡ በውርንጫዋም ላይ የሁላችን ፈጣሪ፣ ንጉሣችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተቀምጦ ስመለከት በደስታ ዘለልኩኝ፡፡ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር መሆን በጣም ያስደስታል፡፡

ምክንያቱም እኛ ሕፃናትን ሲያይ ደስ ይለዋል፡፡ እቅፍ አድርጎ ስሞን በጉልበቱ ላይ ቁጭ አድርጎን ያስተምረናል፣ ይመክረናል፡፡ በዙሪያውም ላሉት ሰዎች እንደነዚህ ሕፃናት ንጹሃን ሁኑ፣ ኀጢአት አትሥሩ፣ እነርሱ አይዋሹም፣ እያለ ይመክራቸዋል፡፡

ከዚያ ምን ሆነ መሰላችሁ፤ እልል እያለ የሚያመሰግነው ሕዝብና በእናትና በአባቶቻችን እቅፍ ውስጥ ያለነው ሕፃናት በአንድነት ሆነን ጮክ ብለን የዘንባባውን ቅጠል ወደ ቀኝ ወደ ግራ፣ ወደ ቀኝ ወደ ግራ እያውለበለብን መዝሙር መዘመር ጀመርን፡፡ መዝሙሩም እንዲህ የሚል ነው፡፡ “ሆሣዕና በአርያም ለዳዊት ልጅ፤ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፤ ሆሣዕና በአርያም፣ ሆሣዕና በአርያም፣ ሆሣዕና በአርያም” የመዝሙሩ ድምጽ በኢየሩሳሌም ከተማ ከጫፍ እስከ ጫፍ ተሰማ፡፡ በጣም ደስ ያለኝ ደግሞ የእኛ የሕፃናቱ ድምጽ ከትልልቆቹ በልጦ መስማቱ ነው፡፡ ጌታችንን በአህያዋ ላይ ተቀምጦ ባየሁት ጊዜ ትዝ ያለኝ አባዬ መጽሐፍ ቅዱስ እያነበበ ያስተማረኝን ታሪክ ልንገራችሁ “አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ እጅግ ደስ ይበልሽ አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ እልል በይ እነሆ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው ትሑትም ሆኖ በአህያም፣ በአህያይቱ ግልገል በውርንጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል” ት.ዘካ.9፥9፡፡

የዝማሬውን ድምጽ ሲሰሙ አባታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የማይወዱት እና የሚያሳድዱት በከተማው ውስጥ ያሉ ጨካኝ ሰዎች እኛ ተሰብስበን እየዘመርን ወደአለንበት መጡ፡፡ ሲመለከቱ ሕዝቡ ሁሉ ደስ ብሏቸው እየዘመሩ እልል እያሉ የዘንባባውን ቅጠል እያውለበለቡ ኢየሱስ ክርስቶስን በአህያዋ ውርንጫ ላይ አስቀምጠው እያመሰገኑት ወደ ቤተ መቅደስ ሲሄዱ ተመልክተው ጨካኞቹ ሰዎች በጣም ተናደው ሕዝቡን “ዝም በሉ” ብለው ተቆጧቸው፡፡ ትልልቆቹ ሁሉ ፈርትው ዝም አሉ፡፡

እኔና ጓደኞቼ ግን በእናታችን ጀርባ ላይ ካሉት ሕፃናት ጋር አብረን ሆነን ጮክ ብለን “ሆሣዕና በአርያም” የሚለውን መዝሙር መዘመር አላቆምንም ነበር፡፡ የገረመኝ ደግሞ ከእኔ የሚያንሱት ገና የተወለዱትም ሕፃናት መዝሙሩን ጮክ ብለው ሲዘምሩት በመስማቴ ነው፡፡ “እግዚአብሔር ሆይ መናገር የማንችለውን እኛን እንድንዘምርልህ ስለፈቀድክልን ተመስገን፡፡” ብዬ አመስግኜ መዝሙሩን መዘመር ቀጠልኩኝ “ሆሣዕና፣ ሆሣዕና፣ ሆሣዕና በአርያም….”

እነዚህ ጨካኞቹ ሰዎች ግን እናትና አባቶቻችንን ዝም አስብሏቸው ብለው ሲያስፈራሩዋቸው ወላጆቻችን ፈርተው የሁላችንንም አፋችንን ይዘው ዝም አስባሉን፡፡ አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያዋ ውርንጫ (በትንሿ አህያ) ላይ ቁጭ ብሎ ለጨካኞቹ ሰዎች እንዲህ አላቸው “ከሕፃናት ከሚጠቡት አፍ ምስጋናን ለራሴ አዘጋጅቻለሁ፡፡ የእነርሱንም አፍ ይዛችሁ ዝም ብታስብሏቸው በዙሪያዬ ያሉት ድንጋዮች ያመሰግኑኛል፡፡ የፈጠርኳችሁ ድንጋዮች ሆይ ሕፃናት እንደዘመሩ እናንተም በመዝሙር አመስግኑኝ፡፡” በማለት በታላቅ ድምጽ ሲናገር፤ ትልልቁም ድንጋይ፣ ትንንሹም ድንጋይ ከመሬት ወደ ላይ እየተነሡ “ሆሣዕና በአርያም ለዳዊት ልጅ ለኢየሱስ ክርስቶስ እናቀርባለን ምስጋና…” እያሉ በጣም ደስ በሚል ድምጽ መዘመር ጀመሩ፡፡ በዚህን ጊዜ ጨካኞቹ ሰዎች አፍረውና ፈርትው ሄዱ፡፡

እኛም ወላጆቻችንም በዙሪያችንም ያሉትም ድንጋዮች አምላካችንን ከበን በእልልታ እየዘመርን ለአህያዎቹ መርገጫ ልብሳችንንና የዘንባባውን ዝንጣፊ እያነጠፍን ወደ ቤተ መቅደስ ገባን፡፡ በዚያም ፈጣሪያችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደስ የሚል ትምህርት አስተማረን፡፡

በመጨረሻም ሆሣዕና ብለን ምስጋና ላቀረብነውና በቤተ መቅደስ ተገኝተን ቃሉን ለምንሰማው ሕፃናት እንዲህ ብሎ መከረን “ልጆቼ በመዝሙራችሁ ተደስቻለሁ፣ ሁል ጊዜ ወደ ቤቴ ወደ ቤተ ክርስቲያን ኑና ዘምሩልኝ፡፡ አፋችሁ በመዝሙር ይዘምር እንጂ ዘፈን እንዳይዘፍን አደራችሁን፡፡ ዘፈን መዝፈን ኀጢአት ነው፡፡”

ትምህርቱን ጨርሰን ከእናቴ ጋር ደስ እያለን ወደ ቤት ተመለስን፡፡ ታዲያ ሁል ጊዜ ይህችን የሆሣዕናን በዓል በውስጤ አስባታለሁ፣ መዝሙሩን መዘመር በጣም ያስደስተኛል፡፡ አምላኬ ኢየሱስ ክርስቶስ በመጨረሻ የመከረኝንም ምክር ጠብቄ ዘፈን የሚባል በአፌ ሳልዘፍን መዝሙር እየዘመርኩኝ እግዚአብሔርን እያመሰገንኩኝ አደኩኝ፡፡

ልጆችዬ ዛሬ የምታነቡት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የሚሆነው ማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 21 እስከ ቁጥር 16 እና ማርቆስ ወንጌል ምዕራፍ 11 ከቁጥር 1 እስከ 17 ያለውን ይሆናል፡፡ ሆሣዕና በአርያም ብለን እንድናመሰግነው ኀይሉን የሰጠን እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን አሜን፡፡፡

ዳግመኛ መወለድ(ለሕፃናት)

ሚያዚያ 10 ቀን 2005 ዓ.ም.

በቤካ ፋንታ

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች፡፡ ዛሬ የምንማረው የእግዚአብሔር ልጆች ሁሉ ለሁለተኛ ጊዜ እንደሚወለዱ ነው፡፡

አንድ መምህር በኢየሩሳሌም ነበረ፣ ስሙም ኒቆዲሞስ ይባላል፡፡ ቀን ቀን ተማሪዎቹን ሲያስተምር ይውልና ማታ ፀሐይዋ ስትጠልቅ በጨለማ ወደ አምላካችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ይመጣል፡፡ ከዚያ እግሩ ሥር ቁጭ ብሎ ይማራል፡፡ ያልገባውን እየጠየቀ በደንብ ስለሚከታተል ጌታችንም እስኪገባው ድረስ ግልጽ አድርጎ ያስረዳውና የጠየቀውን ይመልስለታል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ኒቆዲሞስ የእግዚአብሔርን ቃል ለመማር ከቤቱ ተነሥቶ በሌሊት ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ መጣ፡፡ አምላካችንም በዚያ ሌሊት ለኒቆዲሞስ ያስተማረው ትምህርት እንዲህ የሚል ነበር፡፡ “ኒቆዲሞስ ሆይ፥ እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ወደ መንግሥተ ሰማያት አይገባም፡፡”

ኒቆዲሞስም በጣም ደንግጦ “ዳግመኛ? መወለድ እንዴት ይቻላል? ሰው ደግሞ የሚወለደው አንዴ አይደለም እንዴ? ደግሞስ አንድ ሰው ካደገ ትልቅ ከሆነ በኋላ እንደገና ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ ሊወለድ እንዴት ይችላል?” እያለ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ጠየቀው፡፡ ጌታችንም የጠየቀውን ጥያቄ በደንብ አድርጎ መለሰለት፡፡

ልጆች አሁን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ መለሰለት መልስ ከመሄዳችን በፊት ኒቆዲሞስ የጠየቀውን ጥያቄ ደግሜ ልጠይቃችሁ፡-

  1. የሰው ልጆች የምንወለደው ስንት ጊዜ ነው?

  2. ሁለተኛ ጊዜ የምንወለደው እንዴት ነው?

  3. ዳግመኛ የምንወለደው የት ነው?   

 

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእግሩ ሥር ቁጭ ብለው ከሚማሩት ተማሪዎች መካከል ይህንን ጥያቄ ለጠየቀው ለኒቆዲሞስ “ዳግመኛ ልትወለዱ ያስፈልጋችኋል ስላልኩ እታድንቅ፡፡ የእኔ ልጆች እንድትሆኑ ዳግመኛ የምትወለዱት እንዴት፣ መቼ እና የት እንደሆነ አስረዳሃለሁ” ብሎ ድምፁን ከፍ አድርጎ ያስተማራቸው ትምህርት እንዲህ የሚል ነው፡-

ተማሪዎቼ ሆይ የሰው ልጆች በእናታቸው ማኅፀን ዘጠኝ ወር ከ5 ቀን ከቆዩ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ይወለዳሉ፡፡ ዳግመኛ የሚወለዱት ደግሞ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም በመጠመቅ ነው፡፡ ሕፃናት ወንዶች እና ሴቶች ከተወለዱ በኋላ ወንድ ከሆነ በ40 ቀን ሴት ከሆነች 80 ቀን ሲሞላት እናትና አባታቸው አቅፈዋቸው ቅድስትና ንጽሕት ወደ ሆነች ወደ እግዚአብሔር ቤት ወደ ቤተ ክርስቲያን ይሄዳል፡፡ ከዚያ ሲደርሱ የእግዚአብሔር አገልጋዮች ቀሳውስትና ዲያቆናቱ ደስ ብሏቸው ሕፃናቱን ተቀብለው ወደ መጠመቂያው ቤት ይዘዋቸው ይገባሉ፡፡

በመጠመቂያው ቤት ቄሶቹ ልብሰ ተክህኖ ለብሰው፣ ትልቅ መስቀል ይዘው፣ ወንጌሉን ዘርግተው ቅዱሱን ወንጌል ካነበቡ በኋላ ቄሱ በትልቁ መስቀል ሕፃናቱ የሚጠመቁበትን በገንዳ ውስጥ ያለውን ውኃ “በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የተባረከ ይሁን” እያሉ ሲያማትቡበት ውኃው ተለውጦ ጸበል ይሆናል፡፡ ከዚህ በኋላ ሕፃናቱን በገንዳው ጸበል ውስጥ ሦስት ጊዜ ብቅ ጥልቅ፣ ብቅ ጥልቅ፣ ብቅ ጥልቅ እያደረጉ “በአብ ስም በወልድ ስም በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠምቅሃለሁ” እያሉ ካህኑ ሲያጠምቋቸው ሕፃናቱ ለሁለተኛ ጊዜ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ይወለዳሉ፡፡

ከጸበሉ ሲወጡ ዲያቆኑ ሕፃናቱን ከፍ አድርጎ ሲይዝ ቄሱ በነጭ፣ በጥቁርና በቀይ ክሮች የተገመደውን ማኅተብ በመስቀል ከባረኩት በኋላ በሕፃኑ አንገት ላይ ያስሩለታል፡፡ መላ ሰውነቱንም ቅባ ሜሬን በተባለው ቅዱስ ቅባት እየቀቡት የልጁን ሰውነት ይባርኩታል፡፡ በመጨረሻም በእናት እና በአባታቸው እቅፍ ሆነው ወደ ቤተ መቅደስ ገብተው የአምላካችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ይቀበላሉ፡፡

ይህንንም የተቀደሰ ሥርዓት በመፈጸም ዳግመኛ በመወለድ የእግዚአብሔር ልጅ የሆነ ሰው ወደ መንግሥተ ሰማያት ይገባል፡፡ በማለት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሚያስተምራቸውና ጥያቄውን ለጠየቀው ለኒቆዲሞስ አስተማራቸው፡፡

ጌታችን ኢየሱሱ ክርስቶስ እንዳስተማረን ትምህርት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሁል ጊዜ ይህን ታላቅና ቅዱስ ሥርዓት ለልጆችዋ እየፈጸመች ዳግመኛ ተወልደን የሥላሴ ልጆች እንድንሆን ታደርገናለች፡፡ ይህም ድንቅ ሥርዓት ለአንድ ሰው አንድ ጊዜ ብቻ የሚፈጸም ነው፡፡ ሥርዓቱም ምሥጢረ ጥምቀት በመባል ይጠራል፡፡

ልጆቹ እንድንሆን ዳግመኛ በጥምቀት የወለደን እግዚአብሔር ስሙ የተመሰገነ ይሁን አሜን፡፡

ዳግም ምጽአት(ለሕፃናት)

መጋቢት 26 ቀን 2005 ዓ.ም.

ቤካ ፋንታ

ልጆች እንደምን ሰነበታችሁ፡፡ በእኩለ ጾም /በጾሙ አጋማሽ/ ለምናከብረው ለደብረ ዘይት በዓል እንኳን በሰላም አደረሳችሁ፡፡ ልጆች ዛሬ የምንማረው ስለ ደብረ ዘይት በዓል ሲሆን ትምህርቱ በዋናነት ስለ ዳግም ምጽዓት ያስረዳል፡፡

 

ዳግም ምጽአት ማለት ለሁለተኛ ጊዜ መምጣት ማለት ነው፡፡ ይህም ማለት አምላካችን ፈጣሪያችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደገና ወደ እኛ የሚመጣበትን ቀን ያመለክታል፡፡ ልጆችዬ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማያት ሰማያት ወርዶ ከእናታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደ ጊዜ ለፍጥረታት ሁሉ ለመጀመሪያ ጊዜ በግልጽ ታይቷል፡፡ በዳግም ምጽአት ጊዜ ደግሞ ሁሉም ሰዎች እያዩት እንደገና ስለሚመጣ ያቺ ቀን ዳግም ወደ እኛ የሚመጣበት ስለሆነች ዳግም ምጽአት ተባለች፡፡

ከታላቁ የመለከት ድምጽ በኋላ ቅዱሳን መላእክት በሙሉ ከቅዱሳን ሰዎች ጋራ ከእነ ቅዱስ አባታችን አብርሃም፣ ቅዱስ ዳዊት፣ ከቅዱሳን ሐዋርያት፣ ከእነ ቅዱስ ያሬድ፣ ከአባታችን አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጋራ ሁሉም ቅዱሳን ሆነው እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም በመካከል ሆና ፈጣሪያችንን እግዚአብሔርን በመዝሙር እያመሰገኑት ከበሮን እየመቱ፣ መለኮቱን እየነፉ፣ እልል እያሉ ከሰማይ ውስጥ ይመጣሉ፡፡ ያን ጊዜ ሁላችንም አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ፊት ለፊት በዓይናችን እንመለከተዋለን፡፡

 

ከዚያ በኋላ አንድ ታላቅ ቅዱስ መልአክ ከምድር ጫፍ እስከ ምድር ጫፍ ድረስ የሚሰማውን የመጨረሻውን የመለከት ድምፅ ሲያሰማ የሞቱት ሰዎች ሁሉ ከተቀበሩበት ይነሣሉ፡፡ ተነሥተውም በእግዚአብሔር ፊት ይቆማሉ፡፡ መልካም የሠሩትና እግዚአብሔርን የሚወዱት ሰዎች ነጭ ለብሰው በቀኙ ይቆማሉ፡፡ በምድር ላይ ሲኖሩ ጨካኞችና ክፉ ሥራን በመሥራት የኖሩት ደግሞ ጥቁር ለብሰው በግራ በኩል ይቆማሉ፡፡

 

እግዚአብሔር አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስም በስተቀኝ በኩል ለቆሙት “በምድር ላይ ስትኖሩ እኔን አምናችኋል፡፡ ኀጢአት አልሠራችሁም ልጆቼ ሆይ እኔ እንዳዘዝኳችሁ እናት አባቶቻችሁን አክብራችኋል፣ ለተቸገሩ ሰዎችም የሚበሉትን ምግብ፣ የሚጠጡትን መጠጥ፣ የሚለብሱትንም ልብስ ሰጥታችኋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን እንዳስተማረቻችሁ አሥርቱ ትእዛዛትን፣ ስድስቱ ቃላተ ወንጌልን በመጠበቅ መልካምና ደግ ልጆቼ ስለሆናችሁ ታላቅ ሽልማት እሸልማችኋለሁ፡፡ ሽልማታችሁም መንግሥተ ሰማያት ነች፡፡” በማለት በቀኙ የሚቆሙትን ቅዱሳኑን እና ደጋጋ ክርስቲያኖችን ደስ ያሰኛቸዋል፡፡

 

እግዚአብሔር ለደጋግ ሰዎች ያዘጋጃት መኖሪያ መንግሥተ ሰማያት እጅግ የተዋበች በውስጧም በጣም ባማረና በከበረ እንቁ የተጌጠች ነች፡፡ በዚያች ሰማይ ሁል ጊዜ ብርሃን ያለማቋረጥ ይበራባታል፤ ጨለማም ከቶ የለም፣ የሚያስፈራ ነገር የለም፣ ድካም የለም፣ ራብ የለም በመንግሥተ ሰማያት ዘወትር ደስታ፣ ዝማሬ እልልታ ይሆናል፡፡ መንግሥተ ሰማያት በታላቅ ረጅም ቅጥር የታጠረች ናት፡፡ አሥራ ሁለት በሮች አሏት፡፡ በውስጧ የሚገቡ ሰዎች ክፉ ነገርን የማያደርጉ፣ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ የጠበቁ እና ዕለት ዕለት እግዚአብሔርን ለማመስገን ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚሄዱ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ በዚያ ሲኖሩ ሁል ጊዜ ደስ እያላቸው እግዚአብሔርን ፊት ለፊት እያዩት ከእርሱ ጋር ይኖራሉ፡፡ በዚያ እጅግ የምንወዳት እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከሁሉም ቅዱሳን ጋር አለች፡፡

 

በመጨረሻም አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በግራ በኩል ለቆሙት ሰዎች “በምድር ላይ ስትኖሩ ያዘዝኳችሁን ትእዛዝ አልጠበቃችሁም፣ እናት አባታችሁን አላከበራችሁም፣ የኀጢአትን ሥራ ሠርታችችኋልና ወደ መንግሥተ ሰማያት አትገቡም፡፡ የእናንተ መኖሪያ ገሃነመ እሳት ነው ከፊቴ ሂዱ፡፡” በማለት ይናገራቸዋል፡፡ እነርሱም ወደ ዘለዓለማዊ እሳት ይጣላሉ፡፡

 

ልጆች ዳግም ምጽአት ምን ማለት እንደሆነ አሁን በደንብ ተረዳችሁ አይደል፡፡ እንግዲህ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዳግመኛ በሚመጣበት ጊዜ በቀኙ እንድንቆምና መንግሥተ ሰማያትን እንድንወርስ ሁላችንም እግዚአበሔር እንዳዘዘን መልካምና፣ ደግ ሰዎች ልንሆን እና በቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔርን ቃል እየተማርን ልናድግ ይገባል፡፡

 

እግዚአብሔር አምላካችን ዳግም በሚመጣበት ጊዜ ከቅዱሳኑ ሁሉ ጋራ መንግሥተ ሰማያትን ያወርሰን ዘንድ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡

የጸሎት ቤት/ለሕፃናት/

መጋቢት 12 ቀን 2005 ዓ.ም.

ቤካ ፋንታ

ልጆችዬ እንኳን ለዐቢይ ጾም ሦስተኛ ሳምንት በሰላም አደረሳችሁ፡፡ ይህ ሦስተኛው ሳምንት ምኲራብ ተብሎ ይጠራል፡፡ ዛሬ የምንማረውም ትምህርት በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ ሁለት ከቁጥር 12 እስከ 17 ያለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያን ማለት የክርስቲያኖች ቤት ማለት ነው፡፡ የእግዚአብሔር ልጆች በአንድነት ተሰብስበው እግዚአብሔርን የሚያመሰግኑበት፣ ከእግዚአብሔር ጋር የሚነጋገሩበት ቤት ስለሆነች የጸሎት ቤት ወይም የእግዚአብሔር ቤት እየተባለች ትጠራለች፡፡

በአንድ ወቅት ምን ሆነ መሰላችሁ፥ ጌታችን መድኀኒታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ቅዱሳን ሐዋርያትን ይዞ ወደ ምኲራብ መጣ፡፡ በድሮ ጊዜ ምኲራብ ትባል ነበር፤ አሁን ግን ቤተ ክርስቲያን ተብላ ትጠራለች፡፡ ጌታችንም ወደ ምኲራብ ሲገባ በቤቱ ዙሪያ ብዙ ነጋዴዎች፣ ሻጮች እና ለዋጮች ግቢውን ሞልተው ሲሸጡ ሲነግዱ አያቸው፡፡ አንዳንዱ በሬ ይሸጣል፣ ሌላው በግ፣ ሌላው ዶሮ፣ ሌላው ደግሞ እርግብ…. እየሸጡ የጸሎት ቤት የነበረውን የእግዚአብሔርን ቤት የገበያ ቦታ አደረጉት፡፡ የሰዎቹ ድምጽ፣ የእንስሳቱ ጩኸት ብቻ ምን ልበላችሁ ግቢው በጣም ተረብሿል፡፡ በዛ ላይ አንዳንዶቹ ይጣላሉ፣ ይሰዳደባሉ፣ በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ሆነው ክፉ ነገርን ይነጋገራሉ፡፡

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔርን ቤት ንቀው የጸሎት ቤት የሆነችውን መቅደስ የገበያ ቦታ እንዳደረጉት ሲመለከት ወዲያው ረጅም ጅራፍ ሠራ፡፡ በጅራፉም እየገረፈ በሬዎቹን በጎቹን ሁሉንም ከግቢ አስወጣቸው፡፡ በታላቅ ቃልም ጮኸ “ቤቴ የጸሎት ቤት ናት፥ እናንተ ግን የንግድ ቤት፣ የወንበዴዎች መደበቂያ አደረጋችሁት” ብሎ በአለንጋ እየገረፈ አባረራቸው፡፡

ኢየሱስ ክርስቶስም ሁሉንም አስወጣ ጸጥታ ሆነ ለተሰበሰቡት ሕዝብ ካሁን በኋላ እንዲህ አታድርጉ፡፡ በእግዚአብሔር ቤት መጸለይ፣ መስገድ፣ መዘመር፣ መማር እንጂ መሸጥ፣ መግዛት፣ መረበሽ፣ መሳደብ፣ መጣላት፣ ክፉ ነገር ማድረግ መጮኸ አይፈቀድም ብሎ አስተማራቸው፡፡ ሕዝቡም አጥፍተናል ይቅርታ አድርግልን ሁለተኛ ይህን ጥፋት አናጠፋም ብለው ቃል ገቡ፡፡

ከዚያም ለተሰበሰቡት የእግዚአብሔር ልጆች ያስተምራቸው ጀመረ፡፡ የሚማሩትም ሰዎች በጣም ደስ ብሎዋቸው ከእግሩ ሥር ቁጭ ብለው ተማሩ፡፡ ዐይናቸው የማያይላቸው ሰዎችም ወደ እርሱ ቀርበው አምላካችን ሆይ እባክህ አድነን ሲሉት፣ እጁን ዘርግቶ ዐይናቸውን ሲነካው ሁሉም ማየት ጀመሩ፡፡ የታመሙ ሰዎች ሁሉ ወደ እርሱ መጡ፣  ሁሉንም አዳናቸው፡፡

ልጆችዬ በእግዚአብሔር ቤት በቤተ ክርስቲያን ስንገባና ስንወጣ ተጠንቅቀን መሆን እንዳለብን አስተዋላችሁ አይደል፡፡ ምክንያቱም የእግዚአብሔር ቤት የተቀደሰና፣ ሁሌም መላእክት እግዚአብሔርን የሚያመሰግኑበት የተባረከች ንጽህት ሥፍራ ስለሆነች ነው፡፡  ልጆችዬ ወደ ቤተ ክርስቲያን ስንገባም ሆነ ስንወጣ ተጠንቅቀን ሌሎችን ሳንረብሽ፣ ሳንሮጥ፣ ሳንጮኸ መሆን አለበት፡፡ በሰንበት ትምህርት ቤትም ከወንድሞቻችንና ከእኅቶቻችን ጋራ ስለ እግዚአብሔር እየተነጋገርን፣ እየተማማርን ልናሳልፍ ይገባናል፡፡

እግዚብሔር አምላካችን በቅድስናና በንጽሕና በቤተ ክርስቲያን እንድንኖር ይርዳን አሜን፡፡