የቀኝ ዐይን – ድንግል ማርያም

በዲ/ን ብርሃኑ አድማስ

አፍጣኒተ ረድኤት ማርያም በጊዜ  ምንዳቤ ወአጸባ ለዐይን እምቀራንባ፤ አንቲ ውእቱ ረዳኢተ ያዕቆብ በቤተ ላባ፤ በኩሉ ኅሊናሃ ወበኩሉ አልባባ፤ዘኢታፈቅረኪ ነፍስ ትሠሮ እምሕዝባ፡፡

 የነገረ ማርያም ሊቅ(Marian Doctor)እየተባለ የሚጠራው ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ እመቤታችንን በብዙ ምሳሌ እየመሰለ፣ እየተረጎመና እያመሰጠረ ብዙ ጊዜ አመስግኗታል፡፡ ምንም እንኳን እኛ የምናውቀው የምስጋና ድርሰቱ ለጸሎት የምንጠቀምበት ውዳሴ ማርያም ቢሆንም ከትርጓሜና ከስብከቶቹ ውጪ ከሦስት ሚሊዮን በላይ ስንኝ ያላቸው የምስጋና ድርሰቶችን(Hymns) መድረሱን ታሪክ ጸሐፊው ሶዝመን መዝግቦልናል፡፡ ከነዚህ የምስጋና ድርሰቶቹ መካከልም ‹‹በእንተ ልደት››(On Nativity) እና ‹‹በእንተ ቤተ ክርስቲያን››(On the Church)በተባሉ ትልልቅ ድርሰቶቹም እመቤታችንን ደጋግሞ ያመሰግናታል፡፡

በተጠቀሱት ሁለቱም ድርሰቶቹ እመቤታችንን ለማመስገን ከተጠቀመባቸው ምሳሌዎች ውስጥ አንዱ “ዐይን” ነው፡፡ ሊቁ ስለ ቤተክርስቲያን በደረሰው የምስጋና መዝሙሩ ውስጥ እንዲህ ይላታል፤ ‹‹ዐይን ጥርት የሚለው ከፀሐይ ብርሃን ጋር ተዋሕዶ ከብርታቷ ኃይልን ከውበቷም ነጸብራቅን ሲቀበል ነው፤ በዚህ ጊዜ በግለቷ ይሰነገላል፣ያበራል፤ በውበቷም ያጌጣል፤… ልክ እንደዚሁ ማርያም ዐይን ናት፤ብርሃን (ጌታ) ማደሪያውን በእርሷ አዘጋጀና መንፈሷን ጽሩይ አደረገ፤አሳቦቿን አጠራ፣ኅሊናዋንም ንጹሕ አደረገ፤የድንግልናዋንም ክብር አበራው ››/Hymns on the Church, 36, 1-2/፡፡ ሊቁ በዚሁ ድርሰቱ ውስጥ ሌላ ቦታ ላይ ደግሞ፤ ‹ለዚህ ዓለም ሁለት ዐይኖች ተሰጡት፤ ማየት ያልተቻላት የግራ ዐይን ሔዋን ስትሆን፣ የምታበራው የቀኝ ዐይን ደግሞ (እመቤታችን) ማርያም ናት፡፡በማታየው በጨለማዋ ዐይን ምክንያት መላው ዓለም ጨለመ፤ ስለዚህም ሰዎች በጨለማ ጥላ ውስጥ ሆነው ሲዳብሱ ያገኙት ሁሉ አምላክ ፣ ሐሰቱም እውነት መሰላቸው፡፡ነገር ግን ዓለም እንደገና በሌላ ዐይኑ ባበራና (ባየና) ሰማያዊው ብርሃንም በዚች ዐይን ሰሌዳ ውስጥ ባንጸባረቀ ጊዜ ሰዎችም ቀድሞ ያገኙትን(ያመለኩትን) የኑሮአቸው ውድቀት(የባሕርያቸው መጎስቆል) መሆኑን ተረድተው ወደ ማንነታቸው ተመለሱ (አንድነታቸውን አገኙ)›› ይላል /Ibid, 37, 5-7/::

 

በዚህ መሠረት የእመቤታችን ልደት ዓለም ማየት የጀመረበት ዕለት ነው ማለት ነው፡፡ በርግጥም በነገረ ማርያም መጽሐፋችን ላይ እንደተገለጸው እመቤታችን በቴክታና በጥሪቃ(ሰባተኛ ቅድመ አያቶቿ) በታየው ሕልም መሠረት ዓለምን ሰፍኖበት ከነበረው ድቅድቅ የኃጢኣት ጨለማ እፎይታ የሰጠችው ጨረቃ እርሷ ናት፡፡ በጨለማ ሲያዩት የሚያስፈራውና ሌላ ሌላ የሚመስለው ጉቶው፣ ቁጥቋጦው ፣ ድንጋዩ ፣ ጉብታው….ሁሉ ተራ ነገር መሆኑ የተጋለጠባት፤ ሰዎችም የሰገዱለት ሁሉ አምላክና ጌታ መሆኑ ቀርቶ ድንጋይ ጉብታ መሆኑን ማየት የጀመሩባት፣ ከደገኛው ፀሐይ ክርስቶስ መውጣት በፊት ከረጂሙ ዘመን ጨለማ ጭንቀት የተገላገልንባት ጨረቃ፣ ብርሂት የቀኝ ዐይን እመቤታችን ማርያም ናት፡፡ ስለዚህም ልደቷን የጨለማችን መገፈፍ፣ የዐይናችን ማየት፣ የብርሃናችንም መውጣት ነውና በፍጹም ደስታ እናስበዋለን፤ እናከብረዋለንም፡፡

 

ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬምን የምናስታውሰውም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ብዙ በማመስገኑ ብቻ ሳይሆን ግሩም አድርጎ በማመስጠሩና እንዲህ ያለ ልዩ ልዩ ነገር በማምጣቱም ጭምር ነው፡፡ ለነገሩ ሰው የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ ከሆነ በኋላ ይህን ሁሉ ማድረጉ አያስደንቅም፡፡ የሆነው ሆኖ የእርሱን ያህል በልዩ ልዩ ሕብረ-አምሳል ያመሰገናት ያለ አይመስልም፡፡ሊቁ በልደት ድርሰቱም‹‹እናትህ አስደናቂ ናት፤ ጌታ ወደ እርሷ ገባና አገልጋይ ሆነ፤ እየተናገረ ገብቶ በእርሷ ውስጥ ግን ዝም አለ፤ ወደ እርሷ በነጎድጓድ ድምፅ ገብቶ በእርሷ ውስጥ ጸጥታን አሳደገ፤ የዓለሙ እረኛ ገብቶ በግ ሆኖ ተወለደ፤ እንደ በግም ‹ባ› እያለ ተገለጠ ››/On Nativity, 11, 6/ እያለ አስደናቂነቷን እየደጋገመ ይናገርላታል፡፡አንድ ብቻ ጨምሬ ወደ በዓሉ ልመለስ ፤ቅዱሱ ሊቅ ጌታን እንዲህ ይለዋል፤ ‹‹አንተና እናትህ ብቻ ተወዳዳሪ የሌላችሁ ውቦች ናችሁ፤ በአንተ ላይ ምንም ምን ትንታ(mark) በእናትህም ላይ እንከን(stain) የለም››/Carmina Nisibena, 27,8/፡፡ምንኛ ግሩም ምስጋና፣ እንዴትስ ያለ ፍቅር፣ እንደምንስ ያለ መረዳት ነው? መብቃት ነዋ! መብቃት! ከሌላ ከምን ይገኛል? እርሱ ካልገለጸ፡፡

 

ከቅዱስ ኤፍሬም ሌሎች ድርሰቶች የተነሣሁትና ርእሴንም በእርሱ ምስጋና ያደረግሁት እንዲሁ አይደለም፡፡ በአሁኑ ጊዜ ውዳሴ ማርያም እየተጣጣለና ድርሰቱም የእርሱ ሳይሆን የኢትዮጵያውያን ነው (ምነው በሆነና ነበር) ፤ ወይም ደግሞ እርሱ ስለ ሌላ የደረሰውን የእኛ ሰዎች የማርያም ምስጋና ነው ብለው ነው እንጂ እርሱስ እንዲህ አይልም መባል ስለተጀመረ እርሱ ስለ እርሷ ከደረሰዉ ወደ ግእዝ የተተረጎመዉ ትንሽ መሆኑንና ከላይ ለምሳሌነት ካቀርብኳቸው በላይ በውዳሴ ማርያም ምን አዲስ ነገር አለ ለማለት ነው፡፡ ይህችን ታህል ጥቆማ ከሰጠሁ ቦታውም ጊዜውም የጽሑፉም ዓላማ በዚህ ጉዳይ ላይ መከራከር አይደለምና ወደ እናታችን በዓለ ልደት በረከት ላምራ፡፡

 

በርግጥም ፍጹም ልዩ

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በማይጠረጠር መልኩ ከፍጥረት ሁሉ ልዩ ናት፡፡ በድንግልና ላይ እናትነት፣ በክብረ ድንግልና ላይ ክብረ ወሊድ፣ በድንጋሌ ሥጋ ላይ ድንጋሌ ነፍስና ድንጋሌ ኅሊና የተሰጠው ከእርሷ በቀር ማንም የለም፡፡ ይህም ብቻ አይደለም፤ ምንም እንኳ ‹‹በልቧ ትጠብቀው ነበር››/ሉቃ.2፡51/ ተብሎ እንደተጻፈው አትናገረው እንጂ ከፍጥረት ወገን እንደ እመቤታችን እርሱን ለማወቅ የተቻለው ፍጥረት የለም፡፡ ሊቁ ኦሪገን በሉቃስ ወንጌል ትርጓሜው ላይ እንደገለጸው ስለ አምላክ ፍጥረት ሊያውቀው የሚቻለው የመጨረሻው የእውቀት ደረጃ ላይ የደረሰችው እመቤታችን ብቻ ናት፡፡ እንደ እርሱ ትርጓሜ እመቤታችን ፍጡር ለፈጣሪው ክብር ሊጨምርለት እንደማይቻለው እያወቀች  ‹‹ተዐብዮ ነፍስየ ለእግዚአብሔር – ነፍሴ እግዚአብሔርን ታከብረዋለች›› ያለችው ፍጡር ሊረዳው የሚቻለው የመጨረሻው ደረጃ ላይ ደርሳ በዚያ መጠን ማመሰገኗን ስትገልጽልን ነዉ ይላል፡፡በርግጥም በዚህ መጠን ከርሷ በላይ ሊደርስ የሚቻለው እንዴት ሊኖር ይችላል? ይህ የሚያመለክተውም ገና በምድር ሳለች ለፍጥረት የሚገባው ለዚህ የመጨረሻ ብቃት ከደረሰች ከዚህ ዓለም ከሔደች በኋላማ ይልቁንም እንዴት ያለውን የተወደደውንና ከፍጥረት ሁሉ የላቀውን ምስጋና ታቀርብልን ይሆን? ምን ጥርጥር አለው? ልዩ የሆነውን ልታቀርብ የሚቻላት ልዩ እናት፡፡

 

ለዚህም የበቃችው ራሷን ለሰው በሚቻለው ከፍተኛው መጠን እንደምትጠብቅ አስቀድሞ የሚያውቅ ፈጣሪ እርሱም ደግሞ ጠበቃትና ከፍጥረት ወገን ልዩ ሆነች፡፡ ቀድም ብለን የተመለከትናቸው የቅዱስ ኤፍሬም ጥቅሶች የሚያረጋግጡልንም ይህንኑ ነው፡፡ ብርሂት የሆነች ዐይን ለሰውነት መብራት የምትሆነው የፀሐይ ብርሃን ሲዋሐዳት እንደሆነው ሁሉ እርሷም በራሷ ብርሃነ ዐይን ንጽሐ ሥጋ ወኅሊና ላይ የብርሃን ጌታ ብርሃን የተባለ ጸጋዉን አሳድሮ ንጽሕናዋን ወደር የለሽ አደረገዉ፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ርብቃ ለይስሐቅ የታጨችበትን የሚናገረዉ አንቀጽ ላይ ‹‹ብላቴናይቱም መልክዋ እጅግ ያማረ፥ ወንድ የማያውቃት ድንግልም ነበረች››/ዘፍ. 24፣16/ የሚለውን ሲተረጉም ‹ወንድ የማያውቃት› የሚለውን ለሥጋ ድንግልናዋ ከሰጠ በኋላ ‹ድንግልም ነበረች› ያለው ደግሞ ለመደጋገም ሳይሆን በኅሊናዋም ያልባከነች የተጠበቀች ነበረች ሲል ነው ይላል፡፡ ይሁን እንጂ እንደዚህ ያለችው ድንግል ርብቃ ድንገት(ለርሷ) ያገኘችውና ማንነቱን እንኳ በውል የማታውቀው ሽማግሌ (የአብርሃም መልክተኛ) ቤተሰቦቿን በጠየቀው መሠረት ወላጆቿ ጠርተው ‹‹ከዚህ ሰው ጋር ትሄጃለሽን?›› ብለው በጠየቋት ጊዜ ሳታንገራግር ‹‹እሔዳለሁ›› አለች፤ መሰስ ብላም ተከተለችው፡፡/ዘፍ 24፣58/ እመቤታችን ግን የከበረ መልአክ ተገለጾ ሲያነጋግራት እንኳ የልቡናዋ በር ለወሊድ አልተንኳኳም፡፡ ለልማዱ ሴት ልጅ ‹‹ትጸንሻለሽ፣ ትወልጃለሽ›› ቢሏት ምንም ብትመንን መልአክ ተገልጾ ከነገራት ‹‹ይህ እንዴት ይሆናል?›› ልትል አትችልም፤ እንዴት እንደሚሆንማ ጠንቅቃ ታውቃለችና፡፡ እመቤታችን ከነዚህ ሁሉ ልዩ ስለሆነች ‹‹እፎኑ ይከውነኒ ዝንቱ›› ስትል ፈጽሞ በታተመና እርሱን በሚያልፍ ኅሊና መልአኩን አስጨነቀችው፡፡

 

እርሱም‹‹ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለም›› የምትል ጥቅስ አግኝቶ ፈተናዉን ተገላገለ፡፡ ሌላዉ ቀርቶ በዚህ ጥቅስ ተረትታ ብሥራቱን ስትቀበልም ‹‹ይኩነኒ በከመ ትቤለኒ- እንዳልከው ይሁንልኝ›› ያለች አንት እንዳልከው የአምላኬ ፈቃዱ ሆኖ እንበለ ዘርዕ፣ እንበለ ሩካቤ ከሆነና ተጸንሶ የሚወለደውም እርሱ ከሆነ ይሁን ይደረግ አለች እንጂ ለሌላው ነገርማ ኅሊናዋ እንደታተመ ነው የቀረው፡፡‹‹ ልጄ ሆይ ስሚ፣ እዪ ጆሮሽንም አዘንብዪ፤ ወገንሽን የአባትሽንም ቤት እርሽ፣ ንጉሥ ውበትሽን ወድዶአልና፤ እርሱ ጌታሽ ነውና›› (መዝ 44÷12) ሲል አባቷ ዳዊት በትንቢት እንደተናገረው እርሷ ከሔዋናዊ ጠባይ ተለይታለችና፡፡ ሰሎሞንም‹‹ወዳጄ ሆይ ሁለንተናሽ ውብ ነው ፤ ነውርም የለብሽም፤ ልቤን በፍቅር አሳበድሽው….›› ያለው ለዚህ  ነበር፡፡

 

ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ ‹‹የታተመች ደብዳቤ›› ያላትም ለዚህ ነው/ኢሳ 28 ፤ 12/፡፡ ምክንያቱም ለልማዱ ደብዳቤ ከተጻፈ በኋላ ይታሸጋል፡፡ ስለ እርሷ የተነገረው ግን  ከታተመ ወይም ከታሸገ በኋላ ተጻፈበት የሚል ነው፡፡ አብ በድንግልና አትሞ ሲያበቃ በውስጧ አካላዊ ቃልን የጻፈባት ማንበብ የሚችሉም(እሥራኤል) ማንበብ የማይችሉም(አሕዛብ) እናነበው ዘንድ አንችልም ታትሟልና (በድንግልና በንጽሕና በክብር በምስጢር) አሉ ብሎ የተናገረላት ደብዳቤ እርሷ ናትና፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ጸጋ ለተሰጣቸው ሰዎች ብሥራት ሊያደርስ ሲመጣ ይህ የመጀመሪያው አልነበረም፤ ይሁን እንጂ ለዳንኤልም ሆነ ለጻድቁ ካህን ለዘካርያስ ለእርሷ እንዳደረገው ለእነርሱ መች አደረገ? እነርሱ እጅ ነሱት ሰገዱለት እንጂ እርሱ መቼ እጅ ነሳ ሰገደላቸው? ከዚህ በላይ ልዩ መሆን በእውነት ወዴት ይገኛል፡፡

 

ፍጹም ልዩ መሆኗን ለማስረገጥ ያህል አንድ ነገር ብቻ ላክል፡፡ የጥንቶቹ የቤተክርስቲያን ሊቃዉንት ጌታ ለሐዋርያት ቤተ ክርስቲያንን ይጠብቋት ዘንድ  የሰጠው ሁለት ጊዜ ነው ይላሉ፡፡ አንደኛው ብዙ ጊዜ ሲጠቀስ የምንሰማው ለቅዱስ ጴጥሮስ የተሰጠው ነው፡፡ይህም ‹‹በጎቼን አሰማራ፣ ጠቦቶቼን ጠብቅ እና ግልገሎቼን አሰማራ››/ዮሐ 21፣15-17/የሚለው ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ከዚህ ቀደም ብሎ በመስቀል ላይ የሰጠው ነው፤ በመስቀል ላይ ጌታ ለዮሐንስ ‹‹እነኋት እናትህ›› ሲል የሰጠው እርሷን ብቻ ሳይሆን ቤተ ክርስቲያንንም ነው ይላሉ፡፡

 

በእነዚህ ሊቃዉንት ትርጓሜ መሠርት  ሁለቱም ራሳቸውን የቻሉ ምስጢራትን ይዘዋል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ሕጋዊ ስለነበር(በጋብቻ የተወሰነ ማለት ነው) የተሰጠውም አደራ ይህንኑ የሚመለከትና በጎቹን እስከ ገላግልቶቻቸው(ምእመናን) የሚመለከት ነው፡፡ጌታ በወንጌል ‹‹በጎቼ ድምጼን ይለያሉ›› እንዳለው እነዚህ ድምጽ እንጂ ቃል መለየት የማይቻላቸው ምእመናን ናቸው፡፡  የቅዱስ ዮሐንስ ግን ከዚህ ሁሉ በእጅጉ ይለያል፡፡ምክንያቱም እመቤታችን ራሷ የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ብቻ ሳትሆን የፍጹማን ደናግልም ምሳሌ ናት፡፡ ስለዚህ ከድምጽ ያለፈ ቃላትን ምስጢራትን መለየት የሚቻላቸው ፍጹማንን የሚመለከተው አደራ የተሰጠዉ ለበቃው ብቻ ሳይሆን ለፍጹሙ ድንግል ለዮሐንስ ነዉ፡፡ ስለዚህ እመቤታችንን መግፋት ቤተክርስቲያንን መግፋት ነው፡፡እርሷንም በቤቱ ማስተናግድ የሚቻለው ዮሐንስን የመሰለ ንጹሕ ድንግል ነው፡፡

 

ቅዱስ  ቅዱስ አትናቴዎስ እንደሚለው ጌታ የሰጠው ድንግሊቱን ለድንግል፣ ድንግሉንም ለድንግል፤ ንጹሕንም ለንጹሕ ነው፡፡ መላእክት ሲጠብቋት ከኖሩ በኋላ መልአክ ለመሰለ ሰው ሰጣት እንጂ ለሌላ አልተሰጠችም፤ ሊቀበላት የሚቻለውም የለም፡፡በተለይ ኦሪገን ይህንኑ በተረጎመበት አንቀጹ ስለ ቅዱሱ ብቃት ሲናገር  ለእርሷም ‹‹እነሆ ልጅሽ›› አላት እንጂ ‹‹ልጅ ይሁንሽ›› አላላትም፤ ምክንያቱም ዮሐንስ በዚያ የመከራና የጭንቀት የፍርሃት ቀን በዕለተ ስቅለት ሳይፈራ ሳይሰቀቅ በእግረ መስቀሉ የተገኘው ቅዱስ ጳዉሎስ ‹‹እኔም አሁን ሕያዉ ሆኜ አልኖርም፤ ክርስቶስ ግን በእኔ ይኖራል›› /ገላ 2፣20/ እንዳለዉ ዮሐንስ ራሱን ክዶ ስለነበር ለራሱ እየኖረ አይደለምና በእርሱ የሚኖረው ጌታ ነው፡፡ ‹‹አነሆ ልጅሽ›› ያላትም በእርሱ አድሬ ያለሁት እኔ ነኝ ማለቱ ስለሆነ ከእርሷ ሰው ከሆነ በኋላ ለማንም አልሰጣትም፤ በዮሐንስ አድሮ የተቀበላትም ራሱ ነው፤ ከዚያ በኋላ እርሷን ሊቀበል የሚቻለው የለምና ይላል፡፡ ስለዚህ አንድ ሰው እንኳንስ የእርሷን ነገር ለመንቀፍ ቀርቶ ለማመስገንም ትሰጠው ዘንድ ከፈለገ እንደ ዮሐንስ ራሱን በንጽሕና ይጠብቅ ፣ራሱንም ፈጽሞ ይካድ ባይ ነው፡፡

 

የአሁኖቹ ሰዎች እርሷን ባይቀበሉ፣ በእርሷ አማላጅነት ባያምኑ ለምን እንደነቃለን? እነዚህ በትንሽ ነገር እንኳን መታመን የማይቻላቸው የእርሷን ነገር ይረዱ ዘንድ ታላቁንና ሰማያዊውን ምስጢር ማን አደራ ሊሰጣቸው ይችላል? አንዳንድ የዋኃን ደግሞ መሠርይ ተሐድሶዎች ስለ እርሷ የዘመሯቸውን መዝሙር ተብየ ዘፈኖች እየተመለከቱ ይታለላሉ፡፡ ይህ መናፍቃኑ ስለ እርሷ የሚሉትን መንገድ የተከተለ በእነርሱ ወዝ የታሸ ስለሆነ ተወዳጅ መሥዋዕት አይደለም፡፡ በኦሪት አንበሳው፣ ተኩላው፣ ቀበሮው፣ … የመሳሰለው  አውሬ የገደለውን ሁሉ እንኳን ለመሥዋዕት ልናቀርበው ቀርቶ ልንበላውም የተከለከለ ነው፡፡ ይህም ማለት በመጽሐፍ ቅዱስ የተጠቀሱት አውሬዎች የተባሉት (አጋንንት፣ ርኩሳን መናፍስት፣ መናፍቃን፣…. ደሙን ያፈሰሱትን ወይም በእነርሱ) የተሰዋውን ሁሉ እንኳን ለእግዚኣብሔር ማቅረብ ለእኛም መንካት መርከስ ነው ማለት ነው፡፡ ‹አውሬ የቧጨረውንም አትንካ› የሚል ንባብም ይገኛል፤ ይህ ሁሉ ከእነርሱ የተነካካውን በዚህ ዓለም የዘፈንና የረከሰ መንፈስ የጎሰቆለውን ምንም ለዐይንህ ቢያምርህ (በዘፈን ላደገ ሁሉ የእነርሱ የሚያምረው መሆኑ አይጠረጠርም) ፈጽመህ አትንካ ተብለን ታዘናልና መልከስከስ አስፈላጊ አይደለም፡፡ ግጥሙ በኑፋቄ ዜማው በዘፈን ርኩሰት የተቧጨረ ርኩስ ነውና፡፡እርሷ ቤተ ክርስቲያን ናት፤ የቤተክርስቲያናችንም ስጦታ ስለሆነች በእውነት ልዩ ናትና ይህን በመሰለ መልኩ የተቧጨረውን አናቀርብም፡፡

 

እንግዲህ ዛሬ ተወለደች የምንለው ይህችን ልዩ ድንግል ነው፡፡ስለዚህም የእርሷን በዓለ ልደት ማክበር ከዚህ ሁሉ በረከት መሳተፍ ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔር በእርሷ በኩል ለባሕርያችን ያደረገውንም ክብር ማወቅና መቀበል ጭምር ነው፡፡

 

ከበዓሉ ምን እናገኛለን? የእርሷስ በዓል አልበዛምን?

አንዳንድ ሰዎች በእኛ ቤተክርስቲያን የጌታ በዓል አንሶ የእመቤታችን የበለጠ፤ እኛም ከርሱ ይልቅ ለርሷ የምናደላ የሚመስላቸው ቁጥራቸው በርከት ማለት ጀምሯል፡፡ ያለማወቅ ነውና አይፈረድባቸውም፡፡ ለነቀፋም የተሰለፉ ስለሆነ በ‹ምሰለ ፍቁር ወልዳ-ከተወደደው ልጇ ጋራ› በምንለው ሥዕል ውስጥ እንኳን በሥዕሉ መጠን እየመሰላቸው ጌታ ያነሰ የሚመስላቸው ማስተዋል የራቃቸው ስለሆኑ በእነርሱ አንገረምም፡፡በቤተ ክርስቲያናችን ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፮ ድረስ ከእናቱ ጋር መሰደዱን፣ ከኅዳር ፲፬ ጀምሮ እስከ ልደቱ ይወርዳል ይወለዳል ሲሉ ትንቢት የተናገሩ የነቢያትን ጾም እየጾምን እርሱን እናስባለን፡፡ ከልደት እስከ ዐቢይ ጾም ድረስም በሥጋዌ፤ በአንድነት በሦስትነት መገለጡ አስተርእዮ እየተባለ ይታሰባል ይሰበካል፡፡ ከዚያም ዐቢይ ጾም ይገባል፤ ሁለንተናችን እርሱን በማሰብ ይሰበሰባል፤ ቃለ እግዚአበሔሩም ይህንኑ ያዘክራል፡፡ በትንሣኤውም ሃምሳ ቀናትን እንደ አንድ ቀን እንደ ዕለተ ትንሣኤው በመቁጠር ትንሣኤውን እንሰብካለን፡፡ ከዚህ በማስከተልም ርዕደተ መንፈስ ቅዱስን በዓለ ጰራቅሊጦስን በጾም እናከብራለን፡፡በየወሩም በዓለ እግዚእ፣ መድኃኔዓለም፣ ኢየሱስ፣ አማኑኤል…. እያልን ከዘጠኙ ዓበይትና ከዘጠኙ ንዑሳን በዓላት በተጨማሪ በየአጥቢያቸው የሚታሰቡት ትዝ አይሏቸውም፡፡ ሌላው ቀርቶ በየሳምንቱ ሁለት ቀናትን (ረቡዕ እና አርብ) በጾም ሁለት ቀናትን (ቀዳሚትንና እሑድን) በበዓል ለክርስቶስ መታሰቢያ የሰጠች ብቸኛ ቤተ ክርስቲያን የእኛይቱ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ብቻ መሆኗን አያስተውሉም፡፡ ይህ ሁሉ ሆኖ ሳለ የማርያም በዓል ከጌታ በዓል ይበልጣል ማለትን ምን ዓይነት አለማስተዋል ልንለው እንችላለን? ቢሆንስ በቅዱሳን በዓል ዋናው ተከባሪ ተመሰጋኝ ማን ሆነና ነው ይሄ ሁሉ ጩኸት? ስለዚህ በዚህም ስም አደረግነው በዚያ እግዚአብሔር በአከበራቸው ቅዱሳን ስም እስካደረግነው ድረስ በዓሉ ሁሉ የእግዚአብሔር ነው፡፡

 

የእመቤታችን በዓለ ልደትም በዚሁ መንፈስ የሚከበር በዓል ነው፡፡ነቢዩ ኢሳይያስ ቀደም ብሎ ‹‹ትወጽእ በትር እምሥርወ እሴይ-ከእሴይ ሥር ወይም ግንድ በትር ትወጣለች››/ኢሳ 11፤6/ ብሎ ስለ ልደቷም ተናግሮላታል፡፡ ይህንንም ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴ ማርያም ዘቀዳሚት ድርሰቱ፤ ‹‹ በትረ ሃይማኖት ዘኢትጸንን ምስማኮሙ ለቅዱሳን-የቅዱሳን መደገፊያቸው ግያዝ የሱነማዊቷን ልጅ ከሞት ያስነሣባት ዘንድ ከነቢዩ ከኤልሳ ተቀብሎ እየተጠራጠረ እንደወሰዳት ያይደለሽ ጽነት ጥርጣሬ የሌለብሽ የሃይማኖት በትር አንቺ ነሽ›› ብሎ ተርጎሞልናል፡፡ አባ ጀሮምም ይህን የነቢዩን ትንቢት በትር ከግንዱ ላይ ተስተካክሎ የሚወጣ ግዳጂ ለመፈጸም የሚፈልግ ስለሆነ የእመቤታችን ልዩ መሆን ያሳያል ይላል፡፡

 

በርግጥም ሊቃውንቱ እንዳሉት ለቅዱሳን መደገፊያ ለአጋንንት ለመናፍቃን ደግሞ ማባረሪያ የሆነች በትር፤ ድንግል ማርያም፡፡ስለዚህ የእርሷን በዓል ማክበር ከዚህ ጥርጣሬ ከሌለው በረከት መሳተፍ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በአጠቃላይ የበዓላት ይልቁንም በክርስትና ጥቅማቸው ምንድን ነው የሚለውን እንመልከትና እንፈጽም፡፡

 

በዓላትን በብዛት እንድናከብር ያዘዘን እግዚአብሔር ነው፡፡የምናከብራቸውም ዝም ብለን አይደለም፡፡በተለይም በብሉይ ኪዳን በዓላት ብዙ የመሥዋዕት እንስሳትን ማቅረብና መሠዋት በጥብቅ የሚፈጸም ትእዛዝ ነበረ፡፡ የዚያ ሁሉ መሥዋዕትም ዓላማ ሥርየተ ኃጢኣትን ማስገኘት ነበር፡፡/ዘሌ ፲፯፣፲፩/ በአጭሩ በዓላቱን የማክበሩ ዓላማ ሥርየተ ኃጢኣትን ማሰገኘት ነው ማለት ነው፡፡በዚህ መሠረታዊ ምክንያት በእያንዳንዱ የኦሪት በዓል እጅግ ብዙ የመሥዋዕት እንስሳት ይቀርቡ ነበር፡፡በኦሪት በየዕለቱ ሁለት ሁለት ጠቦቶች፣ በየሰንበቱ ሁለት ተጨማሪ የበግ ጠቦቶች፣በየመባቻው ደግሞ ለየዕለቱ ከሚቀርበው በተጨማሪ ሁለት ወይፈኖች፣ አንድ አውራ በግ፣ ሰባት የአንድ ዓመት የበግ ጠቦቶች፣ አንድ ፍየል ይቀርብ ነበር፡፡ የዓመታዊ በዓላት ደግሞ ከዚህ ሁሉ ይለያል፡፡ለምሳሌ የዳስ በዓሉን ብቻ ብንመለከት ከዕለቱ፣ ከሰንበቱና ከመባቻው እንዲሁም በፈቃድ ከሚቀርቡት በተጨማሪ 73 ወይፈኖች፣ 136 አውራ በጎችና ጠቦቶች፣ 10 አውራ ፍየሎች ይቀርቡ ነበር፡፡ ይህ ሁሉ ግን የእህሉን ቁርባንና ሌላውን መሥዋዕት(ለኃጢኣት ፣ ለበደል፣….የሚባሉትን) ሳይጨምር ነዉ/ዘጸ ፳፱፣፴፰፣ ዘሌ ፳፬፣፭-፱፣ ዘኁ ፳፰፣፱-፲፭፣ዘኁ ፳፱/፡፡

 

‹‹ሕጉ ሊመጣ ያለው የበጎ ነገር እውነተኛ አምሳል ሳይሆን የነገር ጥላ አለውና››/ዕብ 10፣1 / ተብሎ እንደተጻፈ እነዚህ ሁሉ ግን ምሳሌዎች ነበሩ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ከጊዜው የተነሳ አስተማሪዎች ልትሆኑ ሲገባችሁ፥ አንድ ሰው ስለ እግዚአብሔር ቃላት መጀመሪያ ያለውን የሕፃንነትን ትምህርት እንዲያስተምራችሁ እንደ ገና ያስፈልጋችኋልና፤ የሚያስፈልጋችሁም ወተት ነው እንጂ ጠንካራ ምግብ አይደለም።ወተት የሚጋት ሁሉ ሕፃን ስለ ሆነ የጽድቅን ቃል አያውቅምና፤ጠንካራ ምግብ ግን መልካሙንና ክፉውን ለመለየት በስራቸው የለመደ ልቡና ላላቸው ለፍጹማን ሰዎች ነው።›› /ዕብ 5፣ 12-15/ እንዳለው ሊቃውንቱ ለእኛ ወተት ወተቱን እየመገቡ ጠንካራውን ምግብ አላቀረቡልንም ነበር፡፡ አሁን ግን እስኪ ይህን እንኳ እንሞክረው፡፡

 

በኦሪት እንደተጻፈው በፋሲካ የሚሠዋው ልዩ የድኅነት መሥዋዕት በግ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡‹‹በነገው ደግሞ ዮሐንስ ከደቀ መዛሙርቱም ሁለት ቆመው ነበር፥ኢየሱስም ሲሄድ ተመልክቶ። እነሆ የእግዚአብሔር በግ አለ›› /ዮሐ 1፣ 26/።ተብሎ ተጽፎአልና፡፡በሌሎቹ በዓላት የምናቀርባቸው ደግሞ ቀደም ብለን እንዳየነው ወይፈኑ፣ አውራ በጉ፣ ፍየሎቹ(ወንድም ሴትም ነው የሚቀርበው)፣ ሌላው ሁሉ የማን ምሳሌ ነው ማለታችን አይቀርም፡፡ ይህ ሁሉ የበዓል መሥዋዕት የቅዱሳን ምሳሌ ነው፡፡ ‹‹እንደ በጎች ሊበሉን ሰጠኸን፥ ወደ አሕዛብም በተንኸን›› /መዝ 44፣12/ ተብሎ ትንቢትም ተነግሮላቸዋልና።ጌታም በወንጌል ‹‹ስለዚህ፥ እነሆ፥ ነቢያትንና ጥበበኞችን ጻፎችንም ወደ እናንተ እልካለሁ፤ ከእነርሱም ትገድላላችሁ ትሰቅሉማላችሁ፥ ከእነርሱም በምኵራባችሁ ትገርፋላችሁ ከከተማም ወደ ከተማ ታሳድዳላችሁ፤ከጻድቁ ከአቤል ደም ጀምሮ በቤተ መቅደስና በመሠዊያው መካከል እስከ ገደላችሁት እስከ በራክዩ ልጅ እስከ ዘካርያስ ደም ድረስ በምድር ላይ የፈሰሰው የጻድቅ ደም ሁሉ ይደርስባችሁ ዘንድ።እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ በዚህ ትውልድ ላይ ይደርሳል›› /ማቴ 23፣35/ ሲል እንደተናገረው ቅዱሳን ለእምነታቸው መሥዋዕት ሆነው ቀርበዋል።ደማቸውንም አንዱ እንደ ፍየል፣ ሌላው እንደ ወይፈን፣ ሌላውም እንደ አውራ በግ አፍስሰዋል፡፡ እነዚህ ሁሉ የመሥዋዕት ዓይነቶች ለተለያየ የኃጢኣት ማስተሥረያ እነደነበሩት እነዚህም ድኅነትን ለመፈጸም ከተሰዋው በግ ከጌታ በኋላ ለምናምን ሁሉ ሥርየተ ኃጢኣትን እናገኝ ዘንድ የሚማልዱ ስለኛም ጭምር ደማቸውን ያፈሰሱ ናቸው፡፡ ይሁን እንጂ የሌላው ጊዜ የመሥዋዕት እንስሳ የፋሲካቀውን በግ ሊተካው እንደማይችልና የመሥዋዕቱም ዓይነት ፈጽሞ የተለያየ እንደ ሆነው ሁሉ የቅዱሳኑ መሥዋዕትነትና ሰማዕትነትም እንዲሁ የተለያየ መሆኑና የእነርሱም የጌታችንንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሊተካ የማይችል መሆኑ ሊዘነጋ አይገባውም፡፡እርሱ ኃጢኣትህ ተሠረየልህ(ሽ) እያለ ይቅር ሲል እነርሱ ግን የሚያስተሠርዩልን እየጸለዩ ነውና፡፡ ከዚህ በመለስ ግን የጥንቶቹ ሊቃውንት እንደተረጎሙልን የእነርሱ ተጋድሎና ሰማዕትነት የእኛ የሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች መሥዋዕቶች ናቸው፤ ስለእነርሱም ሥርየተ ኃጢኣትን እንቀበላለን፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹በመሥዋዕት እንደሚደረግ፥ የእኔ ሕይወት ይሠዋልና፥ የምሄድበትም ጊዜ ደርሶአል  ››/ዕብ 4፣6/ ሲል የተናገረዉው ይህን የሚያረጋግጥልን ነው፡፡

 

ቀደም ብለን እንዳየነው የመሥዋዕቱ እንስሳት የበዙት ለእሥራኤል ለኃጢኣታቸው አስፈላጊ በመሆኑ እንደሆነው ሁሉ በሐዲስ ኪዳን ለምንኖር ለእኛም ብዙ ቅዱሳን መኖራቸው ይጠቅመናል፣ ኃጢኣታቸንም ያስተሠረይልናል፡፡ የመሥዋእቱ እንስሳት በሙሉ የተቆጠሩና የታወቁ እንደሆነው ሁሉ ቅዱሳኑም ምን ቢበዙም እንዲሁ የታወቁና የተቆጠሩ ናቸው፡፡

 

ዳዊት አባታችን ‹‹ዘይኌልቆሙ ለክዋክብት በምልኦሙ፣ ወይጼዉዖሙ ለኩሎሙ በበአስማቲሆሙ- ክዋክብትን በምልዓት ይቆጥራቸዋል፣ ሁሉንም በየስማቸዉም ይጠራቸዋል››/መዝ 146፣4/ ሲል እንደተናገረዉ ክዋክብት የተባሉ ቅዱሳን ሁሉ በእርሱ ዘንድ በባለሟልነት በቃል ኪዳን የታወቁ በመሥዋዕትነትም የተቆጠሩ ናቸዉ፡፡ ያ ሁሉ የ መሥዋዕት እንስሳ ፣ የጧቱና የሰርኩ፣ የሰንበቱና የመባቻዉ፣ የዓመት በዓላቱ፣ የየግለሰቡ የኃጢኣቱ፣ የበደሉ፣ የመንጻቱ፣…በዓይነት በዓይነት እንደሚታወቅ በእርሱም ዘንድ ተቀባይነት እንዳለዉ ሁሉ የየዕለቱ ቅዱሳንም እንዲሁ ይተወቃሉ፤ ጸሎታቸዉና ምልጃቸዉም በእርሱ ዘንድ የከበረ ነዉ፡፡ እመቤታችን ደግሞ ከነዚህ ሁሉ በግንባር ቀደምነት የምትጠራ ልዩ መሥዋዕታችን ናት፡፡በሁለተኛዉ ክፍለዘመን መጨረሻ የነበረዉ የሰረዴሱ መልይጦን/Melito of Sardis/  በፋሲካ መዝሙሩ ላይ እመቤታችንን የመሥዋዕቱን በግ የወለደችልን ንጽሕት ሴት በግ (fair ewe) ይላታል፡፡ ስለዚህ የእመቤታችን በዓለ ልደት ከብሉይ ኪዳን ሰዎች የተሻለ ሥርየተ ኃጢኣት የምናገኝበት ነዉና ከነዚያ በተሻለ በዓላችንን መንፈሳዊ አድርገን እናክብር፤ ከመንፈሳዊ በረከትም እንካፈል፡፡የደራሲዉንም ምስጋናና ምልጃ በመሰለ ምስጋና እንዲህ እንበላት፤‹‹ምንተኑ አዐስየኪ ዕሴተ፤በእንተ ኩሉ ዘገበርኪ ሊተ፤ማርያም ሠናይት ዘታፈቅሪ ምሕረተ፤ሶበሰ ተታአቀቢ ዘዚኣየ ኃጢኣተ፤ እምኢሐየዉኩ አሐተ ሰዓተ›› እያልን ለእርሷ በሚገባ ምስጋና እናመስግናት፡፡ ከዚህ የወጣ ሰዉ በመጀመሪያ እንደተመለከትነዉ ብርሂት ቀኝ ዐይኑን እንደገና እያሳወረ መሆኑን ሊገነዘብ ይገባዋል፡፡ እኛስ ለባሕርያችንን መመኪያ እርሷን የሰጠንን እግዚአብሔርን ‹‹ብርሂት የቀኝ ዐይን ድንግል ማርያምን ›› በዚህ ዕለት የሰጠኸን፣ ከዚህ ዓለም የድንቁርናና የኃጢኣት ጨለማም የገላገልከን ክብር ምስጋና ለአንተ ይሁን፤ አንተ ለመረጥካትና ላከበርካት ለእናትህም ምስጋና ይድረሳት እያልን አፋችንን ሞልተን እናመሰግናለን፡፡ ቀይ ዕንቁ እምነት ገንዘባቸዉ ያልተሰረቀባቸዉ ወይም በአዉሬዉ ዲያብሎስ ያልተቧጨሩት ሁሉ አብረዉን ያመሰግናሉ፡፡ ቀኝ ዐይናችን ሆይ ዛሬም በአንቺ ብርሃን እናያለንና እናመሰግንሻለን፡፡ እንኳን አንቺን አባትሺን አብርሃምን የሚባርኩት እንደሚባረኩ ልጂሽ አስቀድሞ በሙሴ በኩል በኦሪት ነግሮናልና፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

“አብዝቶ የመመገብ ጣጣው”

(በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)

ግንቦት 30/2003 ዓ.ም.

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

መግቢያ

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የዮሐንስን ወንጌል በተረጎመበት በ21ኛው ድርሳኑ “ ጌታችን በእናታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ጥያቄ በቃና ሰርግ ላይ ስለምን ውሃውን ወደ ወይን ጠጅነት እንደቀየረው  ከአብራራ በኋላ ከዛሬ 1500 ዓመት በፊት በአሁኑ ጊዜ እንደ አዲስ ግኝት ተደርገው የሚታዩትን አብዝቶ በመመገብ የሚመጡትን የጤና ጉድለቶች ጽፎልን እናገኛለን ፡፡ ጽሑፉ ተተርጉሞ እንዲህ ቀርቦአል።


ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ውሃውን ወደ ወይን ጠጅነት ያኔ እንደቀየረ ዛሬም እኛን ድካማችንንና እንደ ወራጅ ውሃ በአንድ ቦታ ጸንቶ መቆየት የተሣነውን የሥጋ ፈቃዳችንን ከመቀየር አልተቆጠበም ፡፡ ዛሬም አዎን ዛሬም ልክ እንደ ወራጅ ውሃ ቀዝቃዛ ፣የፈጠነና ፣ ያልተረጋጋ ጠባይ ያላቸው ሰዎች አሉ ፡፡ እነዚህን ፈቃዶቻችንን ወደ ጌታችን እናምጣቸው ፤ እርሱ ወደ ወይንነት ይቀይራቸዋል፡፡ ከዚያም በኋላ ውኃ ሆነው ከእንግዲህ አይቀጥሉም ፡፡ ነገር ግን ለራሳቸውና ለሌሎች ደስታን የሚሰጡ አካላት ይሆናሉ ፡፡

ባልተረጋጋ ውሃ የተመሰሉት እነማን ናቸው ? ለዚህ ከንቱ ዓለም ሕሊናቸውን ያስገዙ ወገኖች ፣ የዚህን ዓለምን ቅምጥልነት ፣ አለቅነትንና ክብርን የሚሹ ናቸው፡፡ እነዚህ ፍቃዶቻችን እንደውኃ የሚፈሱ ፣ ፈጽሞ ያልተረጋጉ ፣ ለአመፃ የሚፋጠኑ ቁልቁል የሚምዘገዘጉ ውኆች ናቸው ፡፡

 

ዛሬ ሀብታም የነበረው ነገ ደሃ ይሆናል ፡፡ በአንድ ወቅት ዝናው ሲነገርለት፣ የተጌጠና የተንቆጠቆጠ ልብስ ለብሶ በሰረገላ ላይ የሚሄድና ብዙ አጃቢዎች የነበሩት ሰው ፣ ያለፈቃዱ ያን የተዋበ መኖሪያውን ተቀምቶ ወደ ወይኒ ተጥሎ ይገኛል ፡፡ ለሥጋው ደስታ የሚተጋው ሆዳሙ ደግሞ የሥጋ ፈቃዱን ከሞላ በኋላ ሆዱ ሳይጎድልበት ለአንድ ቀን መቆየት አይቻለውም ፡፡ ነገር ግን እነዚህ ምግቦች ከሆዱ ሲጠፉ ወደ ቀድሞው ምቾቱ ለመመለስ ሲል ከፊት ይልቅ አብዝቶ ይመገባል ፡፡ አመጋገቡም ሁሉን ጠራርጎ እንደሚበላ እንደጎርፍ ውሃ ነው ፡፡ በዝናብ ወቅት የሚነሣው ጎርፍ አስቀድሞ የነበረ ውሃ በከፈተለት ጎዳና ገብቶ ቦታውን ሁሉ ያጥለቀልቀዋል ፡፡ እንዲሁ በሆዳሙም ዘንድ እንዲህ ይሆናል ፡፡ አስቀድሞ የነበረው ሲጠፋ እርሱ በቀደደው ሌሎች  የሥጋ ፍቃዶች በዝተው ይገባሉ ፡፡

 

ምድራዊው ነገር ይህን ይመስላል ፤ መቼም ቢሆን የተረጋጋ አይደለም ፡፡ መቼም ቢሆን አንዱ ሌላውን እየተካ የሚፈስ እና የሚቸኩል ነው ፡፡ ነገር ግን የቅምጥልነትን ኑሮ በተመለከተ ጣጣው በከንቱ መባከን ወይም መቻኮል ብቻ አይደለም ፡፡ ሌሎችም እኛን ከመከራ የሚጥሉን ችግሮችም አሉበት ፡፡ ቅምጥልነት ባመጣብን ጣጣ የሰውነት አቅማችን ይዳከማል ፣ እንዲሁም የነፍስ ጠባይዋም ይለወጣል ፡፡ ከባድ ጎርፍ ወንዙን በደለል ወዲያው እንደማይሞላው  ፣ ቀስ በቀስ ግን እንዲሞላው ፣ እንዲሁ ቅምጥልነትና ዋልጌነት እንደ አልማዝ ብርቱ የሆነውን ጤንነታችንን ቀስ በቀስ ውጦ ያጠፋዋል ፡፡

 

ወደ ሐኪም ዘንድ ሄደህ ብትጠይቅ የበሽታዎች ሁሉ ምንጫቸው አብዝቶ ከመመገብ እንደሚመነጩ ይነግሩሃል ፡፡ ጠግቦ አለመብላትና ለሆድ የማይከብዱ ምግቦችን መመገብ ለጤንነት እናት ነው ፡፡ ስለዚህም የሕክምና ባለሙያዎች የጤንነት እናት ብለው ይጠሩታል ፡፡ እናም ጠግቦ አለመብላት የጤንነት እናት ከሆነ  ፣ አብዝቶ መመገብ ደግሞ የበሽታዎች ሁሉ እናት እንደሆነ በዚህ ይታወቃል፡፡ አብዝቶ መመገብ ሰውነታችንን አዳክሞ በሕክምና ባለሙያ እንኳ ለማይድን በሽታ አጋልጦ ይሰጠናል ፡፡

 

አብዝቶ መመገብ ለሪህ ፣ ለአእምሮ ውስጥ የደም መፍሰስ ፣ ለዐይን የማየት ኃይል መቀነስ ፣ ለእጅ መዛል ፣ ለአካል ልምሾነት  ፣ ለቆዳ መንጣት (ወደ ቢጫነት መቀየር  ፤ በተለምዶ የጉበት በሽታ ለምንለው ምልክት ነው ተብሎ ይታመናል ) ስጉና ድንጉጥ መሆን ፣ ለኃይለኛ ትኩሳት እና ከጠቀስናቸው በላይ ለሆኑ ሌሎች ሕመሞች ያጋልጣል ፡፡ በዚህ የሚመጡትን የጤንነት ጠንቆች በዚች ሰዓት ውስጥ ዘርዝሮ ለመጨረስ ጊዜው አይበቃም ፡፡ እነዚህ ሁሉ ሕመሞች በተፈጥሮአችን ላይ የሚከሰቱት መጥኖ በመብላት ወይም በጾም አይደለም ፡፡ ነገር ግን ከሆዳምነታችንና ከአልጠግብ ባይነታችን የተነሣ የሚመጡብን ናቸው ፡፡ በእነዚህ ምክንያቶች የተነሣ በነፍሳችን ላይ የሚከሰቱብንን  በሽታዎች ብንመለከት ዋዘኝነት ፣ ስንፍና ፣ ድንዛዜ ፣ የሥጋ ፍትወቶቻችን ማየል፣ እነዚህንና የመሳሰሉ ሕመሞች ነፍሳችንን ያጠቁዋታል ፡፡ ለእነዚህ ሁሉ ምንጫቸው ሳይመጥኑ አብዝቶ መመገብ ነው ፡፡ ከእንዲህ ዐይነት ቅጥ ያጣ አመጋገብ  በኋላ የቅምጥሎች ነፍስ ክፉ አውሬዎች ሥጋዋን ተቀራምተው ከተመገቡዋት አህያ ያልተሻለች ትሆናለች ፡፡ ቅምጥሎችን ስለሚጠብቃቸው  ሕመሞችና ስቃዮች ጨምሬ ልናገርን ? ከብዛታቸው የተነሣ ዘርዝሬ መጨረስ አይቻለኝም ፡፡

 

ነገር ግን በአንድ ማጠቃለያ አሳብ ሁሉንም ግልጽ አድርጌ ማስረዳት እፈልጋለሁ ፡፡ እንዲህ ከሚያደርጉ ከቅምጥሎች ማዕድ ማንም ደስ ብሎት አይመገብ ፡፡ አስቀድመን እንደተነጋገርነው ጾምና መጥኖ መመገብ የደስታና የጤንነት ምንጮች ሲሆኑ ያለቅጥ መመገብ ግን የበሽታና የደስታ ማጣት ሥር እና ምንጭ ናቸውና ፡፡

 

ሁሉ ነገር ከተሟላልን ፍላጎት የለንም ፡፡ ፍላጎት ከሌለ ደግሞ እንዴት ደስታን ልናገኛት እንችላለን ? ስለዚህም ድሆች ከባለጠጎች ይልቅ የተሻለ ማስተዋልና ጤና ያላቸው ብቻ አይደሉም ፣ ነገር ግን ታላቅ በሆነ ደስታ ውስጥ የሚኖሩ ጭምር ናቸው ፡፡ ይህንን ከተረዳን ከመጠጥና ከቅምጥልነት ሕይወት ፈጥነን እንሽሽ ፣ ከማዕዱ ብቻ አይደለም ፣ ከዚህ ሕይወት ከሚገኙት ፍሬዎች ሁሉ እንሽሽ ፡፡  እነርሱን በመንፈሳዊ ሕይወት በሚገኘው ደስታ ለውጠን በቅድስና እንመላለስ  ፡፡ ነቢዩ “ በእግዚአብሔር ደስ ይበላችሁ እርሱ የልብህን  መሻት ይሰጥሃል”(መዝ.36፥4)  እንዳለው በጌታ ደስ ይበለን ፡፡ በዚህም ዓለም በሚመጣውም ዓለም በእርሱ በእግዚአብሔር መልካም ስጦታ ደስ ይለን ዘንድ የሰው ልጆችን በሚያፈቅረው በኩል ለእርሱ ለእግዚአብሔር አብ ለመንፈስ ቅዱስም ክብር ይሁን  እስከዘለዓለሙ ፡፡ አሜን !!

 

በነገራችን ላይ የሕክምና ባለሙያዎች እንዲሁም የፍልስፍና ምሁራን(ተማሪዎች) በዚህ በቅዱስ ዮሐንስ ገለጻ ላይ ምን ይላሉ ? በ mkwebsitetechnique@gmail.com ጻፉልን።

 

የትንሣኤው ትርጉም በዓሉና አከባበሩ

ከሊቀ ትጉሃን ኀ/ጊዮርጊስ ዳኘ
በጠ/ቤተ ክህነት የዕቅድና ልማት መምሪያ ምክ/ሓላፊ

  • «ትንሣኤ» የሚለው ቃል የግእዝ ቋንቋ ነው፡፡

  •  መገኛ ቃሉም «ተንሥአ» = ተነሣ የሚለው ግሥ ይሆናል፡፡

  • «ትንሣኤ» ማለት ታዲያ = መነሣት፣ አነሣሥ ሐዲስ ሕይወት ማግኘት ማለትን ያመለክታል፡፡

  •  «ትንሣኤ» በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በየመልኩ፣ በየዐይነቱ ሲተረጐም ዐምስት ክፍል አለው፡፡

  • «ትንሣኤ» የሚለው ቃል የግእዝ ቋንቋ ነው፡፡

  • መገኛ ቃሉም «ተንሥአ» = ተነሣ የሚለው ግሥ ይሆናል፡፡

  • «ትንሣኤ» ማለት ታዲያ = መነሣት፣ አነሣሥ ሐዲስ ሕይወት ማግኘት ማለትን ያመለክታል፡፡

  • «ትንሣኤ» በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በየመልኩ፣ በየዐይነቱ ሲተረጐም ዐምስት ክፍል አለው፡፡

  • አንደኛው «ትንሣኤ» ኅሊና ነው፡፡ ይህም ማለት ተዘክሮተ እግዚአብሔር ነው፡፡

  •  ሁለተኛውም «ትንሣኤ» ልቡና ነው፡፡ የዚህም ምስጢሩ ቃለ እግዘብሔርን መስማትና በንስሐ እየታደሱ በሕይወት መኖር ነው፡፡

  •  ሦስተኛው «ትንሣኤ» ለጊዜው የሙታን በሥጋ መነሣት ይሆናል፡፡ ነገር ግን ድጋሚ ሞት ይከተለዋል፡፡

  • አራተኛው «ትንሣኤ» የክርስቶስ በገዛ የባሕርይ ሥልጣኑ ሞትን ድል አድርጎ መነሣት ነው፡፡ የእርሰ ትምህርታችንም መሠረት ይኸው እንደሆነ ይታወሳል፤ ብለን ተስፋ አናደርጋለን፡፡

  • ዐምስተኛውና የመጨረሻው «የትንሣኤ» ደረጃም የባሕርይ አምላክ የጌታችን የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን «ትንሣኤ» መሠረት ያደረገ «ትንሣኤ ዘጉባኤ» ነው፡፡ ይህም ከዓለም ኅልፈት በኋላ ሰው ሁሉ እንደየሥራው ለክብርና ለውርደት፣ ለጽድቅና ለኩነኔ በአንድነት የሚነሣው የዘለዓለም ትንሣኤ ይሆናል፡፡

  • ወደተነሣንበት ዐላማ ስንመለስ የትንሣኤ በዓል በቃሉም ምስጢር በይዘቱም ስለሚመሳሰሉ ጥላው ምሳሌውም፣ ስለሆነ «ፋሲካ» ተብሎ ይጠራል፡፡

  • «ፋሲካ» ማለት በዕብራይስጥ ቋንቋ «ፌሳሕ» በጽርእ በግሪክኛው «ስኻ» ይባላል፡፡ ይህም ወደ እኛው ግእዝና ዐማርኛ ቋንቋችን ሲመለስ ፍሥሕ ዕድወት = ማዕዶት፣ በዓለ ናእት = የቂጣ በዓል፣ እየተቸኮለ የሚበላ መሥዋዕት፣ መሻገር መሸጋገር ማለት ነው፡፡ ነጮቹ በእንግሊዝኛው «ስኦቨር» ይሉታል የዚህም ታሪካዊ መልእክቱ በዘመነ ኦሪት ይከበር የነበረው በዓለ ፋሲካ እስራኤል ዘሥጋ ከግብጽ የባርነት ቀንበር ወደነፃነት የተላለፉበት፣ ከከባድ ሐዘን ወደ ፍጹም ደሰታ፣ የተሸጋገሩበት በዓል ነበር፡፡ በዚህ ኦሪታዊ ምሳሌ በዓል አሁን አማናዊው በዓል «ትንሣኤ» ተተክቶበታል፡፡

  • ፋሲካ፣ በዓለ ትንሣኤ በዘመነ ሐዲስ እስራኤል ዘነፍስ የሆኑት ምእመናነ ክርስቶስ ትንሣኤውን የሚያከብሩበት ዕለት ሆኖ በእርሱ ትንሣኤ

  • ከኀጢአት ወደ ጽድቅ፣

  • ከኀሳር = ከውርደት ወደክብር፣

  • ከጠላት ሰይጣን አገዛዝ ወደ ዘለዓለማዊ ነፃነት፣

  • ከአደፈ፣ ከጐሰቆለ አሮጌ ሕይወት ወደ ሐዲሰ ሕይወት የተሻገሩበት ታላቅ መንፈሳዊ የነፃነት በዓል ነው፡፡

– ክርስቲያኖች የትንሣኤን በዓል በታላቅ ደስታና መንፈሳዊ ስሜት ያከብሩታል፡፡ ስለዚህም ከበዓላት ሁሉ የበለጠ ሆኖ ይታያል፡፡
– መድኀኒታችን ሞትን በሞቱ ድል መትቶ፣ ስሙና መቃብርን አጥፍቶ በሥልጣኑ የተነሣው መጋቢት 29 ቀን በ34 ዓ.ም እንደሆነ ታሪከ ቤተ ከርስቲያን ያስረዳል፡፡
– የትንሣኤ በዓል መከበር የጀመረው በቅዱሳን ሐዋርያትና በሰብዐ አርድእት፣ ኋላም በየጊዜው በተነሡት ተከታዮቹ ምእመናን ነው፡፡ ድምቀቱና የአከባበር ሥርዐቱ ይበዛ ይቀነስ እንደሆን እንጂ መከበሩ ተቋርጦ አያውቅም፡፡ «እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው አደረሰን»
– ሲወርድ ሲወራረድ ከዚህ በደረሰው ትውፊት መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ግብረ ሕማማቱን ስታነብ ሰንብታ ለትንሣኤ እሑድ አጥቢያ ማታ በ2 ሰዓት «ለጸሎት ተሰብሰቡ» የደወል ድምፅ ታሰማለች፡፡

– ካህናቱ ተሰብስበው ሥርዐቱን በጸሎት ይጀምራሉ፡፡ ሕዝቡም ይሰበሰባል፡፡ ቤተ ክርስቲያኑንም ይሞላዋል፡፡

– ካህናቱ ሁሉ ለጸሎተ ፍትሐትም፣ ለሥርዐቱም መዝሙረ ዳዊት፣ ነቢያት፣ ሰሎሞንና ውዳሴ ማርያም ከደገሙ በኋላ «ተፈሥሒ ማርያም ለአዳም ፋሲካሁ» የሚለውን ግጥማዊ የደስታ መዝሙር ይዘምራሉ፡፡
– ቀጥሎም ምንባባቱና ሌላውም ሥርዐት ከተፈጸመ በኋላ ጸሎተ አኰቴት ተደርሶ ዲያቆኑ «ወተንሥአ እግዚአብሔር ከመ ዘንቃህ እምንዋም፣ ወከመ ኀያል ወኅዳገ ወይን፣ ወቀተለ ፀሮ በድኅሬሁ = እግዚአብሔር ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ፤ የወይን ስካር እንደተወው ኀያል ሰውም፣ ጠላቱን በኋላው ገደለ፡፡» የሚለውን የዳዊት መዝሙር ለመስበክ = ለመዘመር ነጭ ልብሰ ተክህኖ ለብሶ አክሊል ደፍቶ፣ የመጾር መስቀል ይዞ፣ እንደእርሱው ነጭ ልብሰ ተክህኖ በለበሱ ደማቅ የጧፍ መብራት በሚያበሩና ድባብ = ጃንጥላ በያዙ ሁለት ዲያቆናት በግራ በቀኝ ታጅቦ ከመቅደስ ብቅ ብሎ በቅድስት ይቆማል፡፡ መዝ. 77-65 ይህም በጌታችን መቃብር በራስጌና በግርጌ በታዩት መላእክት ምሳሌ ነው፡፡ ዮሐ.20-12
– ዲያቆኑ ከላይ የተጠቀሰውን ምስባክ በረጅም ያሬዳዊ ዜማ በሰበከ ጊዜ ካህናቱ ከበሮ እየመቱና በእርጋታ እያጨበጨቡ ተቀብለው ይዘምራሉ፡፡

– ሕዝቡም የቻለው በዝማሬው ያለበለዚያም በጭብጨባና በልልታ የደስታ ዝማሬው ተሳታፊ ይሆናል፡፡ ይህ ምስባኩ በዲያቆኑ 2 ጊዜ በመላው ካህናትም 2 ጊዜ ለመጨረሻ ጊዜ ዲያቆኑም መላው ካህናትም አንድ ጊዜ ብለው 5 ጊዜ ይሆናል፡፡ 5500 ዘመን ሲፈጸም በጌታችን ሞትና ትንሣኤ ዓለም ለመዳኑ ምሳሌያዊ ማስረጃ ነው፡፡

– ቀጥሎም ካህኑ ትንሣኤውን የሚያበሥር ወንጌል ከማቴዎስ፣ ከማርቆስና ከሉቃስ አውጥቶ ያነባል፡፡ ከዮሐንስ ወንጌል ያለው የትንሣኤው ወንጌል ኋላ ለቅዳሴው ጊዜ ይቆያል፡፡ ዮሐ. 20-1-09
– በማስከተል የዲያቆኑን መስቀል ጨብጦ ከሊቃውንቱ መዘምራን ሥራው የሚመለከተው ወይም የተመደበው ባለሙያ መዘምር «ትንሣኤከ ለእለ አመነ» የሚለውን እስመ ለዓለም ከቃኘ በኋላ ለበዓሉ ተስማሚ የሆነው 2 አርያም ተመርቶ በመቋሚያ ይዘመማል፤ በማስከተልም «ዮም ፍሥሐ ኮነ በሰንበተ ክርስቲያን፣ እስመ ተንሥአ ክርስቶስ እሙታን = ክርስቶስ ከሙታን ቀድሞ ተለይቶ ተነሥቷልና በሰንበተ ክርስቲያን ዛሬ ደስታ ሆነ፡፡…» የሚለውን አንገርጋሪ ያመለጥናል = ይመራል፡፡ በግራ በቀኝ እየተነሣ መዘምራኑም ይዘምሙታል ይጸፉታል፤ ያለዝቡታል፤ ወዲያውም «ብርሃነከ ፈኑ፤ ለእለአመነ = ለአመነው ብርሃንህን ላክልን፡፡» የሚለውን እስመ ለዓለም እየወረቡ መብራት እያበሩ ዑደት ያደርጋሉ = ቤተ ክርስቲያኑን በውስጥ ይዞራሉ፡፡
– በዚህ ጊዜ «በጨለማ የነበራችሁ ሕዝቦች ኑ የትንሣኤውን ብርሃን እዩ፣ ብርሃኑንም ወስዳችሁ የብርሃኑ ተካፋይ ሁኑ፡፡» እያለች ቅ/ቤተ ክርስቲያን ስታዘጋጅ የሰነበተችውን ጧፍ እያበራች ታድላቸዋለች፡፡ ሕዝቦቹም ካህናቱን ተከትለው በታላቅ ደስታና ድምቀት ዑደት ያደርጋሉ፡፡
– መዘምራኑና ካህናቱ ከዑደት ሲመለሱ «ይእቲ ማርያም» የተባለው የኪዳን ሰላም ይጸፋና ኪዳን ተደርሶ ሲያበቃ እንደ ቦታው ደረጃ ፓትርያርኩ ወይም ሊቀ ጳጳሱ ወይም ደግሞ አለቃው፣ ቆሞሱ፣ ካህኑ ዘለግ ባለ ድምፅ በንባብ «ክርስቶስ ተንሥአሙታን = ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡» ሲል ካህናቱና መዘምራኑ በዐቢይ ኀይል ወሥልጣን = በታላቅ ኀይልና ሥልጣን፡፡» ብለው ይቀበላሉ፡፡
– አሁንም ካህኑ «አሰሮ ለሰይጣን = ሰይጣንን አሰረው» ባለ ጊዜ መላው ካህናት «አግዐዞ ለአዳም = አዳምን ሐርነት ነጻነት አወጣው» ይላሉ፡፡ ቀጠል አድርጎ ቄሱ «ሰላም፣ ፍቅር፣ አንድነት» ሲላቸው ሁሉም ካህናት «እምይእዜሰ = ከዛሬ ጀምሮ» ብለው ይቀበላሉ፡፡ ቄሱም «ኮነ ፍሥሐ ወሰላም = ሰላምና ደስታ ሆነ» ብሎ ሦስት ጊዜ ዐውጆ ሲያበቃ «ነዋ መስቀለ ሰላም» እያለ መስቀል ሲያሳልም ካህናትና ሕዝቡም «ዘተሰቅለ ቦቱ መድኀኔዓለም» እያሉ ይሳለማሉ፡፡ ካህኑም «እግዚአብሔር ይፍታ» ይላል፡፡ ግብረ ሕማማት ሲነበብበት ከሰነበተው ጠበልም ይረጫል፡፡ የተረፈውንም ጠበል ሕዝቡ ለበረከት ወደየቤቱ ይወስደዋል፡፡
– ከዚያም ልኡካኑ ለቅዳሴ እየተዘጋጁ ሊቃውንት መዘምራኑ ምስማክ መወድሱን ካዜሙ በኋላ በመቋሚያ ይዘምሙታል፡፡ አያይዞም በዓመት ሦስት ጊዜ የሚዘመረውን «ይትፌሣሕ» የተባለውን መዝሙር ቃኝተው ከዘመሙ በኋላ «ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ፤ ተኀፂባ በደመ ክርስቶስ = ምድርም በክርስቶስ ደም ታጥባ ፋሲካውን ታደርጋለች፡፡» እያሉ ይጸነጽላሉ፡፡ አያይዘውም የመዝሙሩን ሰላም ይጸፋሉ፡፡
– ወዲያው መንፈቀ ሌሊት ሲሆን ቅዳሴ ተቀድሶ ይቆረባል፡፡ ከዚያም ዕጣነ ሞገር = በዕጣን ፈንታ ቅኔው ተቁሞ ሠርሖተ ሕዝብ = የሕዝብ ስንብት ከሆነ በኋላ ለመፈሰክ ሕዝቡ ወደየ ቤቱ ይሔዳል፡፡
– ሕዝቡ በየቤቱ፣ ካህናቱም ከቤተ ክርስቲያን በየአካባቢው ባህል በተለይ አክፋዮች መጀመሪያ ቅባት አጥቶ የሰነበተ ሆድ እንዲለሰልስ የተሞቀ የተልባ ጭልቃ ይጠጣና የሹሮ ወጥ በቅቤ፣ በአይብ፣ የበረታም በዶሮ ወጥ፣ ወይም በበግና በከብት ሥጋ ወጥ ይገድፋል፡፡
– በእርጎ፣ በአይብ የተደራረበ እንጀራ በግፍልፍል የሚገድፉም አሉ፡፡ በአንዳንድ የሰሜኑ ሀገራችን ደግሞ የተልባ፣ የኑግና የሱፍ ጭልቃ ከማር ጋር ታሽቶ ከተጠጣ በኋላ በእርጎ፣ በአይብ፣ በወተት፣ በቅቤና ድልህ በተቀባ እንጀራ ይገድፋሉ፡፡
– ሲነጋም ከጾሙ አጋማሽ ጀምሮ ወንዱ ለእርድ የሚሆነውን ሰንጋውን፣ ሲቀልብ፣ በጉን ፍየሉን ሲሞክት ዶሮውን ሲመርጥ፣ ሲገዛ ሲለውጥ፣ ሰንብቶ ነበርና በግልም በኅብረትም ያ ይታረዳል፡፡
– ሴቶችም ቅቤውን ሲያነጥሩ፣ በርበሬውን ሲደልሁ፣ ለእንጀራና ዳቦ የሚሆነውን ዱቄት ሲያዘጋጁ ለጠላ የሚሆነውንም እኸል ሲያሰናዱ አይቡን በልዩ ልዩ ቅመም መጣጣ ሲያደርጉና ባዶ ማለትም ወገሚት የተባለውን በሽንኩርት፣ በጤና አዳም፣ ጣዕሙ እንዳይለወጥ ሲቀምሙ ሰንብተው ዝግጅቱ ተከናውኖ ነበር፡፡
– ጧትም ይህ የመግደፊያ ዝግጅት በየቤታቸው ለሌላቸው ድኾች በየመንደሩ እየተዞረ «እንኳን ጾመ ልጓሙን ፈታላችሁ» እየተባለ ከሥጋውም፣ ከአይቡም፣ ከቅቤውም ከመጣጣሙም፣ ከእርጐውም ይታደላል፡፡
– ከትንሣኤ እሑድ ጀምሮ እስከ ዳግም ትንሣኤ ድረስ ሕዝበ ክርስቲያኑ «እንኳን ጾመ ልጓሙን ፈታላችሁ» እየተባባለ በመጠራራት ዐብሮ ሲበላ ሲጠጣ ልዩ ልዩ ጨዋታ ሲጨዋወት ለንስሐ አባትና ለሽማግሌዎች ለወዳጅ ዘመድም የአክፋይ ዳቦ፣ ወይም የሥጋ ወጥ ግፍልፍል ሲወስድ ይሰነብታል፡፡
– ይህ በዚህ እንዳለ ከትንሣኤ እሑድ ቀጥለው ያሉት ዕለታት ሰሙነ ፋሲካ ወይም ትንሣኤ እየተባሉ የየራሳቸው ምስጢራዊ ስያሜ አላቸው፡፡ ይኸውም፡-
ሰኞ = ጌታችን በሞትና ትንሣኤው ነፍሳትን ከሲኦል አውጥቶ ወደ ገነት አሻግሮ ለማስገባቱ መታሰቢያ ሆና «ፀአተ ሲኦል ማዕዶት» ትባላለች፡፡ ዮሐ. 19-18 ሮሜ. 5-10-17 የዳግም ትንሣኤው ማግሥት ያለችው ግን ገበሬው፤ ወንዶቹ እርሻ ቁፋሮውን፣ ንግዱን፣ ተግባረ እዱን ሁሉ ሴቶቹ ወፍጮውን፣ ፈትሉን፣ ስፌቱን የሚጀምሩባት ዕለት ስለሆነች «እጅ ማሟሻ» ሰኞ ትባላለች፡፡
ማክሰኞ = የትንሣኤው ዕለት እሑድ ማታ ጌታችን በዝግ ቤት ገብቶ ለሐዋርያት ሲገለጽ ቶማስ ሐዋርያ አልነበረም ኋላ ከሔደበት ሲመጣ ሌሎቹ ሐዋርያት ትንሣኤውን ቢነግሩት እኔ ሳላይ አላምንም በማለቱ በዚህ ጥያቄው መሠረት በሳምንቱ ጌታችን በድጋሚ ስለተገለጸ ለዚህ መገለጹ መታሰቢያ ሆና ዕለቲቱ «በቶማስ» ተሰየመች፡፡ ዮሐ. 20-24-30
– ረቡዕ = ከሞተና ከተቀበረ አራት ቀን በኋላ ከመቃብር ጠርቶ ላሥነሣው፣ አላዓዛር መታሰቢያ የእርሱንም ተነሥቶ በማየት በጌታችን ብዙ ሕዝብ ስለአመነበት ቀኒቱ «አላዓዛር» ተብላ ትታሰባለች፡፡ ዮሐ. 11-38-46
ኀሙስ = ከላይ በጸሎተ ኀሙስ ሐተታ ላይ እንደተገለጸው የአዳም ተስፋው ተፈጽሞለት ከነልጅ ልጆቹ ወደቀደመ የገነት ክብሩ ለመግባቱ መታሰቢያ ሆና «የአዳም ኀሙስ» ተብላ ይኸው ትከበራለች፡፡ ሉቃ. 24-25-49
– ዐርብ = በክርስቶስ ደም ተዋጅታ በተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታላቅ መታሰቢያ በመሆኗ በሰሙነ ፋሲካው ያለችው ዐርብ «ቤተ ክርስቲያን» ተብላ ትጠራለች፡፡ ማቴ. 26-26-29 የሐ. ሥራ. 20-28 ይህች ዕለትም እንደ ዕለተ ኀሙስ ሦስት ስያሜዎች አሏት፡፡ ይኸውም እንደኛው ከሆሳዕና ቅዳሜ በፊት ያለችው ዐርብ የጌታችን አርብዓው ጾም የሚፈጸምባት የጾመ ድጓው ቁመትም የሚያበቃባት፣ በመሆኗ በቤተ ክርስተያን «ተጽዒኖ» ስትባል በሕዝቡም ዘንድ በሕማማትና ሰሙነ ትንሣኤው ከባዱን ሥራ ስለሚያቆምባት «የወፍጮ መድፊያ፣ የቀንበር መስቀያ» ትባላለች፡፡
– ሁለተኛውም በመጀመሪያ የሰው አባትና እናት አዳምና ሔዋን ስለተፈጠሩባት፣ ኋላም በሐዲስ ኪዳን ጌታችን ለቤዛ ዓለም መከራ ተቀብሎ ስለተሰቀለባትና የማዳን ሥራውን ስለፈጸመባት «ዕለተ ስቅለት አማናዊቷ ዐርብ» ትባላለች፡፡
– ሦስተኛውም ይኸው በሰሙነ ትንሣኤው ያለችው ደግሞ «ቤተ ክርስቲያን» ትባላለች ማለት ነው፡፡
– ቀዳሚት = በሰሙነ ፋሲካው ያለችው ቀዳሚት ሕዝቡ ከአንዳንዱ በስተቀር ገበያ እንኳን ስለማይገበይባት «የቁራ ገበያ» የገበያ ጥፊያ ስትባል በቤተ ክርስቲያን ግን በዘመነ ሥጋዌው በገንዘባቸውና ጉልበታቸው ለአገለገሉት በስቅለቱ ዋይ ዋይ እያሉ እስከ ቀራንዮ ለተከተሉት፣ የትንሣኤው ዕለት ገና ከሌሊቱ ወደ መቃብሩ ሽቱና አበባ ይዘው በመገሥገሣቸው ትንሣኤው ከሁሉ ቀድሞ ለተገለጸላቸው ቅዱሳት አእንስት መልካም መታሰቢያ ሆና «አእንስት» ተብላ ትጠራለች፡፡ ሉቃ. 23-27-33፣ 24-1-01፣ ማቴ. 25-1-11
 

የዋናው ትንሣኤ ሳምንት እሑድ…

 
በዚች ሰንበት ከላይ እንደተጠቆመው የትንሣኤው ዕለት ጌታችን ለቅዱሳን ሐዋርያት በዝግ በር ገብቶ በመካከላቸው ተገኝቶ «ሰላም ለሁላችሁ ይሁን» ብሎም ትንሣኤውን ሲገልጽላቸው ሐዋርያው ቶማስ አልተገኘም ነበር፡፡ በኋላ ከሔደበት ሲመጣ የጌታችንን መነሣትና እንደተገለጸላቸው በደስታ ሲነግሩት «በኋላ እናንተ ዐየን ብላችሁ ልትመሰክሩ፣ ልታስተምሩ፣ እኔ ግን «ሰምቼአለሁ» ብዬ ልመሰክር፣ ላስተምር? አይሆንም እኔም ካላየሁ አላምንም» በማለቱ የሰውን ሁሉ፤ ይልቁንም የመረጣቸው ወዳጆቹን የልብ ሐሳብ ምክንያቱን ለይቶ የሚያውቀው፣ ቸርነቱ ወሰን የሌለው የባሕርይ አምላክ መድኀኔዓለም ክርስቶስ ልክ እንደመጀመሪያው ትንሣኤ ዕለት አበው ሐዋርያት በአንድነት በተዘጋ ቤት እንዳሉ በሩን ሳይከፍት ገብቶ «ሰላም ለሁላችን ይሁን» በማለት በመካከላቸው ቆመ፤ ቶማስንም «ያመንክ እንጂ ተጠራጣሪ አትሁን እነሆ የተቸነከሩ እጆቼንና እግሮቼን፣ የተወጋ ጐኔንም ናና እይ» ብሎ አሳየው፡፡ እርሱም ምልክቱን በማየቱ በመዳሰሱ ትንሣኤውንና አምላክነቱን እንደፍላጎቱ በመረዳቱ «ጌታዬ አምላኬ ብሎ መስክሮ» አመነ፡፡
– እንግዲህ ይህ የትንሣኤው ምስጢር ለሁለተኛ ጊዜ ለሐዋርያት የተገለጠበት ዕለት ስለሆነ «ዳግም ትንሣኤ» ተብሎ ሰንበቱ ይጠራበታል፤ ይከበርበታል፡፡ ዮሐ. 20-24-30
– በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚፈጸመው መንፈሳዊና ሐዋርያዊ አገልግሎት ሁሉ ከቅዳሴው ውጭ ከሚፈጸመው «ድኅረ ቁርባን» በስተቀር ልክ እንደመጀመሪያው የትንሣኤ ዕለት ሆኖ ይከናወናል፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ለብርሃነ ዕርገቱም በሰላም ያድርሰን፡፡ አሜን!!

“ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን፤ በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን፤ አሰሮ ለሰይጣን፤ አግዐዞ ለአዳም፤ ሠላም እምይዕዜሰ፤ ኮነ፤ ፍስሐ ወሠላም፡፡”

በመ/ር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

“ክርስቶስ በታላቅ ኃይልና ሥልጣን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ ዲያብሎስን አሰረው አዳምን ነጻ አወጣው ሠላም ከዛሬ ጀምሮ ሰላም ሆነ” ይህ ቃል የትንሣኤው የምሥራች ለምእመናን የሚታወቅበት ነው የሚቀድስ ካህን፣ ሰባኪ በዘመነ ትንሣኤ ከስብከቱ አስቀድሞ በዚህ ቃል የክርስቶስን መነሣት ያውጃል፡፡ የሚቀድሰው ካህንም በኪዳን ጊዜ ህዝቡን ከመባረኩ አስቀድሞ ይህንኑ ቃል ይናገራል ሰላምታ የሚቀባበሉ ምእመናንም ሰላምታ ከመስጠት አስቀድሞ ይህን ቃል በመናገር የትንሣኤውን አዋጅ ማወጅና መመስከር ይገባቸዋል፡፡ እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው አደረሰን አደረሳችሁ፡፡

የክርስቶስ ትንሣኤ እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውኃ ፈሳሽ አይደለም ከጥንት በነቢያት የተነገረ ኋላም እርሱ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ ከመሞቱ አስቀድሞ ያስተማረው ደግሞም በመነሣት የገለጠው ሐዋርያትም በግልጥ ለዓለም የመሰከሩት ነው፡፡

ትንሣኤ በትንቢተ ነቢያት

“እግዚአብሔር ይነሣል ጠላቶቹም ይበተናሉ” “እግዚአብሔር ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ የወይን ስካር እንደተወው እንደ ኃያልም ሰው ጠላቶቹንም በኋላው መታ” መዝ.77፥6 “እኔ ተኛሁ አንቀላፋሁም እግዚአብሔር አሥነስቶኛልና ተነሣሁ” መዝ.3፥5 “እግዚአብሔር አሁን እነሣለሁ ይላል መድኀኒት አደርጋለሁ

ቅዱስ ዳዊት በዚህ መልኩ የክርስቶስን ከሙታን መነሣት ተናግሯል፡፡ እርሱን መሰል ነቢያት ክርስቶስ እንዲሞት በ3ኛው ቀን ከሙታን ተለይቶ እንደሚነሣ ገልጸዋል፡፡ ምሳሌ ተመስሏል፤ ትንቢትም ተነግሯል፤ ዮናስ ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት በአሣ አንበሪ ሆድ ውስጥ እንደ አደረ ክርስቶስም ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት በከርሰ መቃብር አድሮ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ ብርሃነ መለኮቱን ገልጾ እንደሚነሣ ራሱ ባለቤቱ እግዚአብሔር ወልድ ተናግሯል፡፡ ዮና.2፥1 ማቴ.12፥4ዐ ነቢየ እግዚአብሔር ሆሴዕ “ከሁለት ቀን በኋላ ያድነናል፡፡ በሦስተኛው ቀን ያስነሣናል በፊቱም በሕይወት እንኖራለን” ሆሴ.6፥2 ብሎ የአምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ ለእኛም ትንሣኤያችን፣ ሕይወታችን መሆኑን ገልጾ ተናግሮታል፡፡ ሆሴዕ በተጨማሪም “ሞት ሆይ መውጊያህ ወዴት አለ? ሲኦል ሆይ /መቃብር/ ድል መንሳትህ ወዴት አለ?” ሆሴ.13፥14 ብሎ ሞት እና መቃብር ሥልጣናቸው እንደተሻረ ይዘው ማስቀረታቸው እንደቀረ በክርስቶስ ትንሣኤ የሰው ልጆች ትንሣኤ እንደተገለጸ ይነግረናል “ልጄ ሆይ ከመሰማሪያህ /ከመቃብር/ ወጣህ እንደ አንበሳ ተኛህ አንቀላፋህም እንደ አንበሳ ደቦል የሚቀሰቅስህ የለም” ዘፍ.49፥9 ከላይ በተመለከትነው ጥቅስ የሚቀሰቅስህ የለም የሚለው ክርስቶስ በገዛ ሥልጣኑ አስነሽ ሳይሻ የተነሣ መሆኑን ይነግረናል ይህንም ክርስቶስ በራሱ ሥልጣን እንደሚነሣ ሲያስተምር እንዲህ ይላል፡፡ “እንደገና አስነሣት ዘንድ እኔ ነፍሴን እሰጣለሁና ከእኔ ማንም አይወስዳትም ነገር ግን እኔ በፍቃዴ እሰጣታለሁ እኔ ላኖራት ሥልጣን አለኝ መልሼ እወስዳት ዘንድ ሥልጣን አለኝና” ዮሐ.10፥17 ይህ የሚያስረዳን ክርስቶስ በፈቃዱ ለዓለም ቤዛ ሆኖ እንደ ሞተ በሥልጣኑ እንደተነሣ ነው፡፡

የክርስቶስ ትንሣኤ በሐዲስ ኪዳን

አራቱም ወንጌላውያን ትንሣኤውን እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው በወንጌል ጽፈውታል፡፡ ቅዱስ ማቴዎስ በወንጌሉ ምዕራፍ 28፥1-16 በሰንበትም ማታ ለእሑድ አጥቢያ ማርያም መግደላዊትና ሁለተኛዋ ማርያም መቃብሩን ሊያዩ መጡ እነሆ ታላቅ የምድር መናወጥ ሆነ የእግዚአብሔር መልአክ ከሰማይ ወርዷልና ቀርቦም በመቃብሩ አፍ ላይ ድንጋይዋን አንከባሎ በላይዋ ተቀመጠ” ይላል በዕለተ ትንሣኤ የክርስቶስን ትንሣኤ ለማየት መላእክት እንዲሁም ቅዱሳት አንስት ተገኝተዋል ሲወለድ የመወለዱን ዜና ለዕረኞች የተናገሩ መላእክት በትንሣኤው ዕለትም ዜና ትንሣኤውን ለቅዱሳት አንስት ለመንገር በመቃብሩ አካባቢ ተገኝተው የትንሣኤው ምስክሮች ሆነዋል፡፡
“ወእምግርማሁ ተሀውኩ ወኰኑ ከመ አብድንት እለ የአቅቡ መቃብረ “እርሱን ከመፍራት የተነሣ መቃብሩን የሚጠብቁት ታወኩ እንደ በድንም ሆኑ” ማቴ.28፥4 መልአኩም መልሶ ሴቶችን እንዲህ አላቸው “እናንተስ አትፍሩ የተሰቀለውን ኢየሱስን እንደምትሹ አውቃለሁና በዚህ የለም እርሱ እንደተናገረው ተነሥቶአል፡፡ ነገር ግን ኑና የተቀበረበትን ቦታ እዩ ፈጥናችሁም ሂዱ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ ብሎ የትንሣኤውን የምስራች ለሴቶች መግለጡን ጽፎአል፡፡

ቅዱስ ማርቆስም በምዕራፍ 16፥1-16 ትንሣኤውን አስመልክቶ ቅዱስ ማቴዎስ የተናገረውን መሰል የትንሣኤ መልእክት ሲናገር ቅዱስ ሉቃስ በምዕራፍ 24፥1-24 ዜና ትንሣኤውን ጽፎልናል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም በወንጌል አጻጻፍ ስልቱ ከሦስቱ ወንገላውያን ረቀቅ ያለ ስልት ያለው ቢሆንም ትንሣኤው በመመስከር ከሦስት ወንጌላውያን ጋር ተባብሯል፡፡ ዮሐ.20፥1 ማርያም መግደላዊትና ሌሎች ሴቶች ወደመቃብሩ ገስግሰው በመሄድ ትንሣኤውን ለማየት እንደበቁ ለደቀ መዛሙርቱም የምሥራቹን እንደተናገሩ ዘግቦልናል፡፡ ከሦስቱ ወንጌላውያን በተለየ መልኩ ክርስቶስ ከተነሣ በኋላ በዝግ ደጅ ደቀ መዛሙርቱ ወደ አሉበት መግባቱን ትንሣኤው እንደገለጠላቸው ሰላም ለእናንተ ይሁን ብሎ የሰላም አምላክ ከሀዘናቸው እንዲጽናኑ ፍርሀታቸውን አርቆ አይዞአችሁ አትፍሩ እኔ ነኝ እጄን እግሬን እዩ በማለት ፍጹም ፍቅሩን ገልጾላቸዋል፡፡

ትንሣኤው ምትሐት አለመሆኑን ይገልጥላቸውም ዘንድ “ደቂቅየ ቦኑ ብክሙ ዘንበልዕ” ጥቂት የሚበላ አላችሁን? ብሎ ለደቀ መዛሙርቱ ተናግሯል የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ በሕቱም መቃብር መግነዝ ፍቱልኝ መቃብር ክፈቱልኝ ሳይል የተፈጸመ ኀይሉን የገለጠበት ነው ጌታ ባረገ በስምንት አመት የተጠራው ቅዱስ ጳውሎስም ትንሣኤውን ሐዋርያትን መስሎ መስክሮአል “ስለ ኃጢአታችን የተሰቀለውን ሊያስነሳንና ሊያጸድቀን የተነሣውን ጌታችንን ኢየሱስን ከሙታን ለይቶ ባስነሣው ስለምናምን ስለ እኛም ነው እንጂ” ሮሜ. 4፥25 በዚህ መልእክቱ ትንሣኤው ለእኛም ትንሣኤያችን መሆኑን ይነግረናል ትንሣኤው ለእኛ ሕይወት መሆኑንም ጭምር ሲነግረን “እርሱ ክርስቶስ በአባቱ ጌትነት ከሙታን ተለይቶ እንደተነሣ እኛም እንደ እርሱ በሐዲስ ሕይወት እንኖራለን” ሮሜ.6፥4 እንግዲህ በሞቱን ሞትን እንደሻረ በትንሣኤው ትንሣኤያችን ያበሠረ መሆኑን ደግሞም የትንሣኤያችን በኩር ጀማሪ እንደሆነ እኛ በሞቱ ብንመስለው የትንሣኤ ተካፋዮች መሆናችንን ያሳየናል፡፡

ጌታችን በአምስት ነገር በኩራችን መሆኑን መጻሕፍት ይነግሩናል
  1. በጥንት ዓለም ሳይፈጠር ዘመን ሳይቆጠር ኖሮ እኛን ፈጥሮ ለማስገኘት በኩራችን ነው፡፡
  2. በተቀድሶ/በመመስገን/ በኩራችን ነው፡፡ ቅዱሳን የጸጋ ምስጋና የሚመሰገኑት እርሱን በኩር አድርገው ነውና፡፡
  3. በትንሣኤ በኩራችን ነው፡፡ እርሱን በኩር አድርገን እንነሣለንና “አሁንም ክርስቶስ ከሞቱ ሰዎች ሁሉ አስቀድሞ ተነሥቶአል በመጀመሪያው ሰው ሞት መጥቶአል በሁለተኛው ሰው ትንሣኤ ሙታን ሆነ” 1ቆሮ.15፥20፡፡
  4. በዕርገት በኩራችን ነው፡፡ ቅዱሳን አረጉ መባሉ እርሱን በኩር አድርገው ነውና፡፡ “አርገ ከመ ያሌቡ ዕርገተ ጻድቃን ንፁሀን” የንፁሀን ጻድቃንን ዕርገት ያስረዳ ዘንድ አረገ ቅዳሴ ዩሐንስ ወልደ ነጎድጓድ”
  5. ነፍሳትን ከሲዓል አውጥቶ ምርኮን ማርኮ ገነት መንግሥተ ሰማያት በመግባት በኩራችን ነው፡፡
ስለዚህ በአለ ትንሣኤውን ስናከብር የእኛም ትንሣኤያችን መሆኑን አውቀን ተረድተን ትንሣኤ ልቡና ተነሥተን መልካም ሥራ በመሥራት መሆን አለበት እኛ ትንሣኤ ልቡና ሳንነሣ በየዓመቱ ትንሣኤን ብናከብር ፈሪሳውያንን ወይም ትንሣኤ የለም ፈርሰን በስብሰን እንቀራለን ብለው የሚያምኑ ሰዱቃውያን መምሰል ይሆናል፡፡
ትንሣኤውን ስናከብር እንዴት ማክበር እንደሚገባን ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል
ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችሁ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኛ ተቀምጦ ባለበት በላይ ያለውን እሹ የላይኛውን አስቡ በምድር ያለውንም አይደለም እናንተ ፈጽማችሁ ሞታችኋልና ሕይወታችሁም ከክርስቶስ ጋር በእግዚአብሔር ዘንድ የተሠወረች ናትና ሕይወታችሁ ክርስቶስ በሚገለጥበት ጊዜ ያን ጊዜ ከእርሱ ጋር በፍጹም ክብር ትገለጣላችሁ” ቆላ.3፥1-4 የክርስቶስ ትንሣኤ ትንሣኤያችን ነው ብለን ለምናምን ሁሉ ከምድራዊ ዐሳብ ነጻ ሆነን ተስፋ የምናደርገው ትንሣኤ እንዳለን በማሰብ ከሞት በኋላ ሕይወት ከትንሣኤም በኋላ የዘለዓለም ሞት መኖሩን ሳንዘነጋ ማክበር እንደሚገባን ይመክረናል፡፡ ላይኛውን የማያስቡ መልካም ሥራ የማይሰሩ ሰዎች ትንሣኤ ምን እንደሚመስል መድኅነ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ሲያስተምር እንዲህ ብሏል፡፡ “በመቃብር ያሉ ሁሉ ቃሉን የሚሰሙበት ጊዜ ይመጣል፡፡ ስለዚህ አታድንቁ መልካም የሠሩ ለሕይወት ትንሣኤ ክፉ የሠሩም ለፍርድ ትንሣኤ ይነሣሉ” ዮሐ.5፥28 የትንሣኤያቸው በኩር ክርስቶስን አብነት አድርገው ቃሉን ሰምተው ሕጉን ጠብቀው ትዕዛዙን አክብረው ትንሣኤ ልቡና ተነሥተው የትንሣኤን ዕለት የሚያከብሩ ሥጋውን በልተው ደሙን ጠጥተው በንስሐ ተሸልመው በፍቅረ እግዚአብሔርና በፍቅረ ቢፅ /ወንድምን በመውደድ/ ጸንተው ቢኖሩ ላይኛውን ማሰብ ትንሣኤውን ማክበር ማለት ይህ ነው፡፡ የትንሣኤውን ትርጉም አውቀዋልና፡፡ ከትንሣኤ ሥጋ ትንሣኤ ልቡና ተነሥተን ሥጋውን በልተን ደሙን ጠጥተን መንግሥቱን እንድንወርስ ስሙን እንድንቀድስ እግዚአብሔር አምላካችን ይፍቀድልን፡፡
መልካም ትንሣኤ ያድርግልን አሜን፡፡

ቅዳሴን በካሴት ማስቀደስ ይቻላል?

ሚያዚያ 3/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ኅሩይ ባየ

እድሜ ለቴክኖሎጂ ይድረስና ድካምን የሚቀንሱ በርካታ የሥልጣኔ ውጤቶች እየተከሰቱ ነው፡፡ ከእነዚህ ውስጥ አንዱ መቅረጸ ድምጽ ሲሆን ያለፈን ለማስታወስ የለው ጠቀሜታ የጎላ ነው፡፡ መዝሙሮች ቅዳሴዎች፣ ትምህርቶች እና የአባቶች ምክር በካሴትና በሲዲ በምስልና በድምጽ እየተዘጋጁ የሚሰጡት አገልግሎት እጅግ ከፍ ያለ ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያን ከምትገለገልበት ሥርዐተ አምልኮ መካከል ቅዳሴ አንዱ ሲሆን በካሴት ተቀርጾ በገበያ ላይ ይሸጣል፡፡ እኔም ቅዳሴን በካሴት ከቤት ውስጥ ሆኖ ማስቀደስ ይቻላል ወይስ አይቻልም? የሚል ጥያቄ በውስጤ ይመላለሳል፡፡

 

እባካችሁ ቅዳሴን በካሴት በቤት ውስጥ ሆኖ ማስቀደስ ይቻል ወይም አይቻል እንደሆነ መልስ ስጡኝ?”

 

የተከበሩ ጠያቂያችን በቅድሚያ ስላቀረቡልን ጥያቄ ምስጋናችንን ስናቀርብ ከልብ ነው፡፡ ማንነትዎንና ያሉበትን ቦታ ስላልገለጡልን ለምንመልሰው መልስ አቅጣጫ ለመጠቆም አልረዳንም፡፡ ቢሆንም መሠረታዊ የሆነው ጥያቄዎ ስለተገለጠ አስቸጋሪ ነገር አይኖረውም፡፡

 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ አዘጋጅ የሆኑትን ሊቀ ጠበብት ሐረገወይን አገዘን እና በማኅበረ ቅዱሳን የመጻሕፍት ዝግጅት ክፍል አርታኢ የሆኑትን መምህር ተስፋ ሚካኤል ታከለ  ለቀረበው ጥያቄ ምላሽ እንዲሰጡን ጋብዘናቸዋል፡፡

 

ሊቀ ጠብብት ሐረገወይን “ቅዳሴን በካሴት በቤት ውስጥ ሆኖ ማስቀደስ ይገባል?” የሚለውን ጥያቄ ሲመልሱ እንዲህ ይላሉ፡፡ “የቅዳሴ ዓላማው አንድ ነው፡፡ እሱም ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ፈትቶ ለምእመናን ማቅረብ ሲሆን አባቶች እንደሚሉት ቅዳሴ የሕዝብ ነው፡፡ ሰዓታት የሚባለውን የቤተ ክርስቲያን ጸሎት ካህናት ሲያደርሱ ምእመናን ቢሳተፉበት በረከተ ሥጋና በረከተ ነፍስን ያገኙበታል፡፡ ማኅሌት ሲቆም ኪዳን ሲደርስ ምእመናን ቢገኙ በረከትን ያገኛሉ፡፡

 

ቅዳሴ ግን ለሕዝብ የሚፈጸም ሥርዐተ ጸሎት በመሆኑ ቀዳስያኑ እና ምእመናኑ ፊት ለፊት እየተያዩ ሥጋ ወደሙን ለመቀበል ደጅ ሲጠኑ ይታያሉ፡፡ ሥርዐተ ቅዳሴ ሲፈጸምም በካህናትና በምእመናን ተሳትፎ ይከናወናል፡፡ ቴክኖሎጂው በወለደልን ጥበብ ተጠቅሞ መዝሙርን ማዳመጥ ቅዳሴውን መስማት ይቻላል፡፡የተቀረጸውን መስማት ብቻ ሳይሆን ልንማርበትም እንችል ይሆናል፡፡ ከዚህ አልፎ የቤተ ክርስቲያኑን ጸሎተ ቅዳሴ በካሴት በተቀረጸ ድምጽ ማስቀደስ አይቻልም፡፡

 

በአሕዛብ አገር የሚኖሩ ሰዎች በአንድ የጸሎት ቤት ተሰብስበው ቅዳሴ በቴፕ ያስቀድሱ እንደነበረ ሰምቻለሁ እነዚህ ምእመናን ከቤታቸው ወጥተው መንገድ ሔደው ቆመው ቅዳሴውን በቴፕ እየሰሙ “እትው በሰላም” /በሰላም ወደቤታችሁ ግቡ/ ሲባሉ ይሰነባበታሉ፡፡ ይህ በጎ አሳባቸውን እግዚአብሔር ተመልክቶ ቤተ ክርስቲያን እንዲሠሩ ካህናቱም ቀድሰው እንዲያቆርቧቸው ረድቷቸዋል፡፡ የብሉይ ኪዳን ካህናት ያቀርቡት የነበረው መሥዋዕተ ኦሪት ለሐዲስ ኪዳኑ (አማናዊው) መሥዋዕት ምሳሌ ሆኖ እንዳደረሳቸው ከችግር አንጻር ቅዳሴን ለማስቀደስ ካላቸው ልባዊ ፍላጎት ተነሣሥተው ያን ማድረጋቸው አያስወቅሳቸውም፡፡ ያም ሆኖ ግን በመኖሪያ ቤታቸው ሳይሆን ከቤታቸው ወጥተው መንገድ ተጉዘው የፈጸሙት ተጋድሎ የሚበረታታ ነው፡፡ ይህ ሳይሆን ዝም ብሎ ተኝቶ ቅዳሴን ሰምቶ አስቀድሻለሁ ማለት ድፍረት ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን የቴክኖሎጂ ቅዳሴ የላትም ቅዳሴውም በምንም ዐይነት መንገድ በቴፕ ድምጽ አይተካም፡፡ በአሁኑ ሰዓት ቤተ ክርስቲያን ያልታነጸችበት ቦታ አለ ለማለት ትንሽ ያስቸግራል ስለዚህ ቅዳሴን ማስቀደስ የሚገባው በቤተ ክርስቲያን ተገኝቶ ነው”

 

መምህር ተስፋም በማያያዝ ምክራቸውን እንዲህ ሲሉ አስተላልፈዋል፡፡ “ሊቀ ጠበብት የሰጡት አባታዊ ትምህርት እንደተጠበቀ ነው፡፡ የተለየም ዐሳብ የለኝም ቅዳሴ የሚቀደሰው በተቀደሰ ቦታ ነው፡፡ ይህ ማለት ታቦት ባለበት፣ ካህናት በተገኙበት፣ ውግረተ እጣን በሚደርስበት፣ ቡራኬ በሚፈጸምበት ቅዱስ ቦታ ይከናወናል፡፡ በቅዳሴው ጊዜ እጣን አለ፤ ጧፍ ይበራል፤ መሥዋዕት ይሰዋል፡፡ እነዚህ ነገሮች ባልተሟሉበት ሁኔታ ቅዳሴን ማስቀደስ ፈጽሞ አይቻልም፡፡ ይህ ካልሆነ ቅዳሴው ቅዳሴ አይሆንም እላለሁ፡፡”

 

ማጠቃለያ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዐተ እምነቷን ዶግማዋን እና ትውፊቷን ጠብቃ ጸሎተ ቅዳሴን ታከናውናለች፡፡ ጸሎተ ቅዳሴ ተግባራዊ የሆነ አምልኮ የምንፈጽምበት፣ መሠረታዊ እምነታችንን የምንገልጥበት ወደ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን /ምሥጢረ ቊርባን/ የምንደርስበት በምድር ያለ ሰማያዊ ሥርዐት ነው፡፡ በዕለተ ሰንበት በዐበይት በዓላት የሚቻለው አስቀድሶ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ይቀበላል፡፡ በንስሓ ራሱን ያላዘጋጀ ምእመን ደግሞ አስቀድሶ ጠበል ጠጥቶ መስቀል ተሳልሞ ወደ ቤቱ ይመለሳል፡፡

 

ሥርዐተ ቅዳሴ በካህናት መሪነት በዲያቆናት አስተናባሪነት በምዕመናን ተሳትፎ በኅብረት የሚፈጸም ሥርዐት ነው፡፡ ሠራኢ ካህን ከመንበሩ በስተምዕራብ ቆሞ፣ ፊቱን ወደ ምሥራቅ መልስ ንፍቁ ካህን ከመንበሩ በስተደቡብ ፊቱን ወደ ሰሜን መልሶ፣ ሠራኢ ዲያቆኑ በስተምሥራቅ ፊቱን ወደ ምዕራብ፣ ንፍቁ ዲያቆን በሰሜን ፊቱን ወደ ደቡብ በመቆም መንበሩን ይከቡታል፡፡ አምስተኛው ልዑክም ከሠራኢው ካህን በስተግራ ቆሞ ለካህኑ መብራት ያበራለታል፡፡ መጽሐፉ በመንበር ላይ የሚቀመጥ ስለሆነ ሲገልጥ ጠሚችለው ንፍቁ ቄስ ወይም ሌላ ቄስ ብቻ ነው፡፡ ይህ መደበኛ አቋቋማቸው ሲሆን ሥርዐተ ቅዳሴው በሚከናወንበት ጊዜ ለቡራኬ ለጸሎተ እጣን ለስግደት ከቦታ ወደ ቦታ ይንቀሳቀሳሉ፡፡

 

በቅኔ ማኅሌት በቅድስትና በመቅደስ ቆመው የሚያስቀድሱና የሚያገለግሉ የምእመናን ወገንና ካህናት አሉ፡፡ በቅኔ ማኅሌት በሰሜናዊ ምሥራቅ አቅጣጫ ያለ የአገልግሎት ክፍል ወንዶች ምእመናን ቆመው ያስቀድሱበታል፡፡ በቅድስት ምዕራባዊ ክፍል ቆሞሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት ያስቀድሱበታል፡፡ በስተደቡብ በኩልም ደናግል መነኮሳይያት የካህናት የዲያቆናት ሚስቶችና የሚቆርቡ ምእመናን ቆመው ያስቀድሱበታል፡፡ በዚህ ክፍል ቆመው ያስቀደሱ ምእመናን ሥርዐተ ቁርባን ይፈጽሙበታል፡፡ ይህ የቤተ መቅደሱ አሠራር ቤተ ንጉሥ የሆነ እንዳልሆነ ነው፡፡ በመቅደሱ ክፍል ልኡካኑ የሚቀድሱበት ሥጋ ወደሙ የሚፈትቱበት ካህናት ብቻ የሚገቡበት ልዩ ቦታ ነው፡፡

 

በእነዚህ ቦታዎች ከላይ ያስቀመጥናቸውና ያልገለጥናቸው ልዩ ልዩ አገልግሎቶች ይከናወኑበታል፡፡ ሥርዐተ ቅዳሴ ሲፈጸም ካህናትና ምእመናን የድርሻቸውን ቃለ እግዚአብሔር እየተቀባበሉ እየሰገዱ እየተባረኩ ሥርዐቱ ይከናወናል፡፡ ለዚህም ነው ሥርዐተ ቅዳሴ የሚታይ የሚዳሰስ የሚጨበጥ የሚሰማ ክዋኔ አለው የምንለው፡፡ ቅዳሴን በካሴት መስማት /ማዳመጥ/ ይቻል ይሆናል እንጂ ቡራኬ የማስገኘት የምሥጢራት ተካፋይ የማድረግ እድል አያሰጥም፡፡ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንም እንደታደዘዘው ካህኑ ቅዳሴን ከመጀመሩ በፊት ሊያስተውል ከሚገባው ጉዳዮች አንዲ ምዕመናን መሰባሰባቸውን ማረጋገጥ ነው፡፡

 

የእግዚአብሔር ዐይኖች በቤተ መቅደስ ነው፡፡ ጆሮዎቹም ወደ ምእመናን ጸሎት ነው፡፡ በመሆኑም እግዚአብሔር ዐይኑንና ልቡን በመቅደሱ ሊያኖር ቃል ስለገባልን ወደ ቤተ ክርስቲያን መሔድ የምሥጢራቱም ተካፋይ መሆን ይጠበቅብናል፡፡ “በጎ እንደሆነ አውቆ ለማይሠራው ለዚያ ሰው ኀጢአት ነው” ያዕ.4፥17 እንዳለው ሐዋርያው ማስቀደስ ንስሓ መግባት ሥጋ ወደሙ መቀበል መልካም ነገር ማድረግ በጎ እንደሆነ እያወቁ ያን አለመፈጸም ኀጢአት ነው፡፡ “በዚህ ሥፍራ ለሚጸለይ ጸሎት ዐይኖቼ ይገለጣሉ፡፡ ጆሮቼም ያዳምጣሉ አሁንም ስሜ ለዘላለም በዚያ ይኖር ዘንድ ይህን ቤት መርጫለሁ ቀድሻለሁም ዐይኖቼና ልቤም ዘወትር በዚያ ይሆናል” 2ዜና.7፥15-17 ተብሎ እንደተጻፈ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሔደን የምንጸልየው ጸሎት የምንፈጽመው ሥርዐተ አምልኮ በረከት የሚያሰጥ እንደሆነ አምላካችን ነግሮናል፡፡ አበው ሐዋርያትም ጸሎትን በቤተ መቅደስ በመገኘት ያደርጉ ነበር፡፡ “ጴጥሮስና ዮሐንስም በዘጠኝ ሰዓት ለጸሎት በአንድነት ወደ ቤተ መቅደስ ወጡ፡፡ ሐዋ.3፥6 ስለዚህ በአንድነት ለጸሎት በቤተ ክርስቲያን መሰብሰብ ሐዋርያት ትምህርት ነውና ልንፈጽመው ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

Zeqwala

A Burning Heaven in This World – Mt. Zeqwala Monastery

March 20/2012                                                                                  Hiruy Simie

ZeqwalaThe area of Mt. Zeqwala is a product of intense volcanic activity during a quaternary period. The cooling age produced a well preserved cone structure form of the volcanic eruption. The vent formed after the cooling of the eruption was filled by rain to become a huge crater lake. Written Church sources came to mention the place after the coming of his holiness Abune Gebre Menfes Kidus and his founding of the monastery that is still dedicated to him in 1168 Ethiopian calendar. However, the story of a church built by King Gebre Meskel and St. Yared on the mountain which vanished miraculously is told by the local monks. (read more)
Abuye [Ethiopic for our father] st. Gebre Menfes Kidus [means the salve of the Holy Spirit] was born of Egyptian parents called Simon and Aklisia on November 28, 868 E.C. From the moment he was born he praised the lord and refused to suckle the breast of his mother being separated from the ways of men for the glory of the lord. He has not as a result eaten a worldly food all his life. When he became three years old the Angle of God (St. Gabriel) took him from his parents and gave him to a saintly monk by the name ‘the relative of Light’ in an Egyptian Coptic monastery. He thus started to learn the Holy Scriptures until he was old enough to be made a deacon and a priest by a Bishop called Abraham. After that he was called by God to depart to a jungle and live the life of an anchorite. He faithfully obeyed and lived in a locality called ‘Gebota’ [most probably in Upper Egypt]. There he stayed for 300 years and his cloth wore out and he became perfectly naked suffering from the fierce heat and the terrible cold for in the rainy seasons. God seeing his fortitude and struggle against the weakness of the flesh gave him a white fur as thick as the wool of sheep. At last after 300 years our God Jesus Christ came to him followed by His holy mother and the Apostles including the heavenly angels and gave him his first covenant of forgiveness for the people of Gebota.
After that he was ordered by our Lord and God Jesus Christ to go and continue his prayers and struggle against evil spirits in Ethiopia. Being blessed and made strong by the Holy Spirit Saint Gebre Menfes Kidus came to Ethiopia, sitting on a cloud with his pets of 60 lions and leopards. He reached Ethiopia during the reign of St. Lalibela, and gave the saintly king his blessings. King Lalibela was exceedingly happy and bowed to the saint many times. These two saints then traveled side by side like father and son to Zeqwala. After reaching the mountain, saint Abune Gebre Menfes Kidus decided to stay, told King Lalibela to depart to a place called Adadi and build a church in the name of Holy Mary. The saintly king then went and did just as the holy father had told him.            

During his stay on Mount Zeqwala, our father entered the crater lake upside down, and prayed for Ethiopia and the whole world for 100 years. Then, millions of devils came and began to pound his bones until they became  powder and dissolve in the water. After the end of these years, our Lord Jesus Christ appeared, and told him that he would forgive the sins of the Ethiopian people.  The saint rejoicing traveled to Arabia and met a king who worshiped idols there. As soon as the king and his people saw the saint, a great fear came up on them and they asked him whether he was a beast or a human being because of the fur which covered him from head to toe. Then our father answered saying ‘Yes … I am a man and more a Christian.’ The evil king hearing this wanted to kill him but he and his people became dead instead. Our Father then prayed to God and raised them from the dead. This put the fear of the lord in their hearts and even the evil king became a changed man. Abune Gebre Menfes Kidus then baptized them all and made them Christians and came back to Ethiopia happy. Then he returned back to Ethiopia and stood for many years to pray at a place called Medre Kebd. Then the devil came in the shape of a craw and pulled out his eyes by his beak. Then God ordered the angels St. Gabrieal and Michael to come to him and breathe on his eyes and he was made as he was before. Then he was told by God to travel to the top of Zeqwala and destroy the devils his enemies who live in the heart of evil men who oppose all those who belong to God. He then traveled on a cloud and destroyed 700,000 devils.  Being an anchorite none saw him except a dozen anchorites who recorded his hagiography and others whom he preached the words of God and lived with since his birth.
Abune GebreMenfeskidusSt. Gebre Menfes Kidus lived on the mountain for 262 years after establishing his Monastery. It is said that the saint lived on the place right up to his death in the 15th century. After that the then king of Ethiopia called Endreyas [Hisbe Nagn], built five churches (for St. Michael, for Saint Gabriel, for Holy Mary, for Savior of the world and the last for Abune Gebre Menfes Kidus) on and around the mountain in honor of the saint. These churches continued giving function up to the time of ‘Ahmed the left handed’ who destroyed it in the 16th century. Then Zeqwala and the famous monastery became a ruin for more than 400 years. After that a saintly saint anchorite and monk reached the place in the grace of the Holy Spirit and asked the Showa king Sahile Selassie to build a church on top of the mountain. The king sent soldiers who fought against the lions and bores which populated the place and cleared enough space to build a church. The place was made an important traditional worship site of the Oromo late in the 19th century during the founding of the Monastery once again by a saintly monk by the name Aba Gebre Hiwot. Even today a visitor might encounter these traditional worshipers on the mountain. St. Abo is said to have told a monk that such people will inherit the depth of hell for not believing in Christ seeing the wonders he has done and is doing on the monastery.
After the elapse of this time Emperor Minilik built the present church and dedicated his time and power to preserve the forest on and around the mountain. In that effort, he gave fifes to the monastery and a tax collecting right. Observing the forest fires on the area he is said to have given the monks and priests thirty slaves who serve the monastery. There whose sole duty was to stop forest fires, bury the dead monks and serve the monastery in manual labor. The present people of Zeqwala are descendants of these faithful individuals.
During the Italian invasion a great miracle has occurred on mount Zeqwala. The Catholic Italians accusing that the monastery as a fort of patriots sent a jet to bombard the church. The pilot reaching the area tried to bomb the church but saw a being standing on the mountain and reaching the jet and pushing the bombs away from the Church and scared pilot then beat a hasty retreat. A monk also saw the event and was able to recognize Abune Gebre Menfes Kidus.

The well preserved and intact nature of the mountain natural forest, Crater Lake, wild life be it mammals or birds is still remembered by the elders up to the beginning of the second half of the 20th century. The reverse began to happen with the land proclamation of 1966 E.C. This policy has its own effect at the local level by creating a power vacuum in the area.  As a result with the reigning of chaos the forest on whole area was destroyed. To make matters worse Lutheran Mission was established on the area in 1989 E.C. and converted most of the farming society into Protestants with a deep hostility to the monastery. The so called ‘aid and development’ it planned to do was limited only with a modern headquarters and a huge seedlings of Eucalyptus yearly given to the peasant for free. Thus, the crippled, dependant and perverted peasants (those living at the surrounding lands away from Wanber kebele in most cases) still lead a life of poverty and apathy burning the forest now and then evil for themselves and others with no hope for a better tomorrow.

Today, the extremely dedicated monks in the likeliness of their father Abune Gebre Menfes kidus protect the forest from the surrounding people on and around Zeqwala thirsting for water during the summer months and shivering for warmth in the winter. Therefore, the Children of the EOTC must pay for pipe system to bring water to the place from the town at the base, build a modern hall for the priests and assist them to start apiculture. Helping them to build an all weather gravel road from Dire to the mountain is another area open for the kind laity seeking the blessing of Abune Gere Menfes Kidus. Therefore, all the laity and priests of the Ethiopian Orthodox Church are called to save this wonderful and national heritage from destruction. May the blessing of our God Christ rest on Yuhanis of Debre Wifat the writer of this hagiography in the 15th Century hearing it told from the holy Gebre Menfes Kidus himself and all of us who love the saint.  

Glory to God and to His Holy Mother
Amen!

IMG_0715

ጦምን አስመልክቶ የቅዱሳን አባቶች አስተምህሮ

የካቲት 9/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

“በጦም ወቅት አንድ ክርስቲያን  በፈቃደኝነት አንድ በጎ ሥራን  ጎን ለጎን ቢፈጽም መልካም ነው፡፡ ነገር ግን ከሰዎች ምስጋናን ወይም አንዳችን ነገር ሽቶ የሚጦም ከሆነ ግን ጦሙ በእግዚአብሔር ዘንድ የማይወደድ ጦም ይሆንበታል፡፡ ማንኛውም በጎ ሥራ ስንሠራ ለእግዚአብሔር አምላካችን ካለን ፍቅር የመነጨ ይሁን፡፡ እንዲያ ካልሆነ ግን እግዚአብሔርን ደስ ልናሰኝ አይቻለንም፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስን ጌታችን በመንጎቹ ላይ ሲሾመው ለእርሱ ያለውን ፍቅር ተመልከቶ ነበር፡፡ እግዚአብሔን የሚያፈቅር ሰው የሚፈጽማቸው የትኞቹም በጎ ሥራዎች በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደዱለት ይሆኑለታል፡፡ ፍጹማንም ናቸው፡፡ ስለዚህም ማንኛውንም በጎ ሥራዎቻችንን ስነሠራ እርሱን በማፍቀር ላይ የተመሠረቱ ይሁኑ፡፡”

“አንድ ሰው ምንም እንኳ መላ የሕይወት ዘመኑን በትኅርምት ሕይወት መምራት ያለበት ቢሆንም በዚህ በዐቢይ ጦም ግን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ኀጢአቱን  ለካህን ተናዝዞ ለድሆች ምጽዋትን በማድረግ በአግባቡ ሊጦም ይገባዋል፡፡ እነዚህን ዐርባ የጦም ቀናት በአግባቡ በጎ ሥራዎች አክለንባቸው የጦምናቸው እንደሆነ ቸሩ ፈጣሪያችን ዓመት ሙሉ ባለማወቅ የፈጸምናቸውን ኀጢአቶቻችንን ይደመስስልናል፡፡ (ዮሐንስ አፈወርቅ )

IMG_0715ነገር ግን ብዙዎቻችን በጦም ራስን መግዛትን ከምንለማመድ ይልቅ ለሥጋ ምቾቶቻችን መትጋታችን የሚያስገርም ነው፡፡ እኛ ለራሳችን የተጠነቀቅን መስሎን ደስታን ይፈጥሩልናል የምንላቸውን ምግቦችንና መጠጦችን አብዝተን እንበላለን እንጠጣለን፡፡ … ነገር ግን መጨረሻችን ሕማምና ስቃይ ይሆንብናል፡፡ የሥጋን ምቾት የናቁና በጦም በጸሎት እንዲሁም በትኅርምት ሕይወት መንፈሳዊ ሕይወታቸውን የሚመሩ ቅዱሳን ግን ሥጋና ነፍሳቸውን ሕያዋን አድርገው በመልካም ጤንነት ያኖሯቸዋል፡፡ በተድላና በምቾት ይኖር የነበረው ሰውነታችን በሞት ሲያንቀላፋ ከውስጡ ከሚወጣው ክፉ ጠረን የተነሣ ሽቶ በራሱ ላይ እናርከፈክፍበታለን፡፡ ነገር ግን የቅዱሳን ሰውነት በሕይወት ሳሉም ቢሆን በሞት ከሥጋቸው መልካም መዓዛ ይመነጫል፡፡ ይህ እጅግ ድንቅ የሆነ ነገር ነው ፡፡ እኛ ለሥጋችን ምቾት በመጠንቀቅ ራሳችንን ስናጠፋ እነርሱ ግን ሥጋቸውን ለነፍሳቸው በጦምና በጸሎት በማስገዛታቸው ሥጋቸውን ይቀድሷታል፡፡ የነፍሳቸውን በጎ መዓዛ በመጠበቃቸውም ሥጋቸው መልካም መዓዛን እንድታፈልቅ ሆነች፡፡

ነፍሳችን ንጽሕናዋን በጦም ካልጠበቀች በቀር ቅድስናዋን በኀጢአት ምክንያት ማጣቱዋ የማይቀር ነው፡፡ ያለጦም የነፍስን ንጽሕና ጠብቆ መቆየት የማይሞከር ነው፡፡ ሥጋም መንፈስ ለሆነችው ነፍሳችን መገዛትና መታዘዝ አይቻላትም፡፡ አእምሮአችንም በምድራዊ ምቾቶቻችን ስለሚያዝብን ከልብ የሚፈልቅ ጸሎትን ማቅረብ አይቻለንም፡፡ ስለዚህ ሥጋችን ነፍሳችንን በስሜት ስለሚነዳት ነፍስ እውር ድንብሯ በፍርሃት ወደ ማትፈቅደው ትሔዳለች፡፡ በአእምሮአችን ውስጥ ክፉ ዐሳቦች ተቀስቅሰው ኅሊናችንን ያሳድፉታል፡፡ ስለዚህም የእግዚአብሔር ጸጋ ከእኛ ትወሰዳለች፡፡ ስለዚህም በግልጥ አጋንንት እንደ ፈቀዱት ነፍሳችንን ተሳፍረው ወደ ኀጢአት ይመሩዋታል፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዐርባ ቀንና ዐርባ ሌሊት ከጦመ በኋላ ተራበ፡፡ ሰይጣንም ወደ እርሱ ይቀርብ ዘንድ መራቡን ገለጠለት፡፡ እንዲህ በማድረግም ጠላታችንን እንዴት ድል እንደምንነሳው በእርሱ ጦም አስተማረን፡፡ ይህ አንድ ጦረኛ ላይ የሚታይ የአሰለጣጠን ስልት ነው፡፡ ለተማሪዎቹ ጠላትን እንዴት ድል መንሳት እንደሚቻል ሊያስተምር ሲፈልግ ለጠላቱ ደካማ መስሎ ይታየዋል፡፡ ጠላቱም የተዳከመ መስሎት ሊፋለመው ወደ እርሱ ይቀርባል፡፡ እርሱም በተማሪዎቹ ፊት ከጠላቱ ጋር ውጊያን ይገጥማል፡፡ ጠላትን በምን ድል መንሳት እንደሚችል በእውነተኛ ፍልሚያ ጊዜ በተግባር ያስተምራቸዋል፡፡ በጌታ ጦም የሆነውም ይህ ነው፡፡ ጠላት ሰይጣንን ወደ እርሱ ለማቅረብ መራቡን ገለጠ፡፡ ወደ እርሱም በቀረበ ጊዜ የእርሱ በሆነ ጥበብ በመጀመሪያውም፣ በሁለተኛውም፣ በሦስተኛው፣ ፍልሚያ በመሬት ላይ ጥሎ ድል ነሳው፡፡

እየጦምህ ነውን? ጦምህን በሥራ ተግብረህ አሳየኝ፡፡ ድሀ አይተህ እንደሆነ ራራለት፡፡ ወዳጅህ ከብሮ እንደሆነ ቅናት አይሰማህ፡፡ አፋችን ብቻ አይጡም፤ ዐይናችንም፣ ጆሮአችንም፣ እግራችንም፣ እጃችንም፣ የሰውነት ክፍሎቻችንም ሁሉ ክፉ ከመሥራት ይጡሙ፡፡ እጆቻችን ከስስት ይጡሙ፤ እግሮቻችን ኀጢአትን ለመሥራት ከመፋጠን ይጡሙ፡፡ ዐይናችም የኀጢአት ሥራዎችን ከመመልከት ይጡሙ፡፡  ጆሮዎቻችንም ከንቱ ንግግሮችንና ሐሜት ከመስማት ይከልከሉ፡፡ አንደበቶቻችንም የስንፍና ንግግርንና የማይገቡ ትችቶችን ከመሰንዘር ይቆጠቡ፡፡ ወንድማችንን እያማን ከዓሣና ከእንስሳት ተዋጽኦዎች መከልከላችም ምን ይረባናል? (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)

የነነዌ ሰዎች የንስሐ ምስክሮች

በዲ/ን በረከት አዝመራው

የነነዌ ጾም ከሰባቱ የቤተክርስቲያን አጽዋማት አንዱና የዐቢይ ጾም ማዘጋጃ ደወል ነው፡፡ ይህ የነነዌ ሰዎች የንስሐ ታሪክ በቤተክርስቲያናችን በጣም ታላቅ ዋጋ ያለውና የራሱ መዝሙር የሚዘመርለት፣ ቅዳሴ የሚቀደስበት ታላቅ መታሰቢያ ያለው ታሪክ ነው፡፡ ራሱ ጌታችንም የነነዌ ሰዎችን የንስሐ ታሪክ በመጥቀስ አይሁድን ገስጾበታል፤ በፍርድ ቀንም በዚያ ትውልድ ዘንድ እንደሚፈርዱበት ተናግሯል፡፡ ይህም የሆነበት የነነዌ ሰዎች ደስ የሚያሰኝ የንስሐ ታሪክ ስላላቸው ነው፡፡ በዚህ ጽሑፍ ይህን አስደሳች የንስሐ ታሪክ በጾመ ነነዌ ከሚነበቡ የቅዳሴ ምንባባት አንጻር ለመመርመር እንሞከራለን፡፡

 

ኃጢአት ከእግዚአብሔር መለየት እንደሆነ ሁሉ ንስሐ ደግሞ ወደ እግዚአብሔር መመለስ ነው፡፡  በዚህ ከእግዚአብሔር ሊለዩ የሚችሉ ብዙ ፈተናዎች ባለቡት ዓለም እስካለን ድረስ ሕይወታችን ሁሉ የንስሐ ጊዜ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ከሁሉም ጊዜ በተለየ ወደ እግዚአብሔር የምንመለስባቸው የጾም ወቅቶች ሲሆኑ ከእነዚህም ታላቁና ዋነኛው ዐቢይ ጾም ነው፡፡

ቅድስት ቤተክርስቲያናችን በዐቢይ ጾም ከእያንዳንዱ ምእመን ልቦና የንስሐ ፍሬን ትፈልጋለች፤ ያለትንሣኤ ልቦና /ንስሐ/ የክርስቶስን ትንሣኤ በእውነትና በደስታ ማክበር አይቻልምና፡፡ ለመሆኑ ከንስሐ የሚያሰናክሉን ነገሮች ምን ምን ናቸው? የነነዌ ሰዎች ታሪክ ስለዚህ ምን ያስተምረናል?

1.    ቅንጦትን መውደድ

ምንም እንኳን በደፈናው ገንዘብ የኃጢአት ምንጭ ነው ባንልም እንደ ወንጌል ትእዛዝ በክርስቲያናዊ መንገድ ካልተያዘ ግን እግዚአብሔርን ሊያስረሳና የኃጢአት ማስፈጸሚያና ምክንያት ሊሆን ይችላል፡፡ ብዙ ጊዜም ገንዘብና ባለጸግነት ከእግዚአብሔር በመለየታችን ያጣነውን ሰላምና ደስታ ለማግኘት ተስፋ የምንጥልበት ጣኦት ሆኖ ሊቀየር ይችላል፡፡ በሀብታችን በምናገኘው ጊዜያዊ ደስታና ሰላም ዘላለማዊውንና ፍጹምን የእግዚአብሔር ስጦታ መፈለግ፣ ወደ እግዚአብሔር መመለስን መናፈቅ ልናቆም እንችላለን፡፡ በዚህ መልኩ ብልጽግና ከንስሐ የሚያሰናክል ወጥመድ ይሆናል ማለት ነው፡፡

እግዚአብሔር ሀብት እንኳ ቢሰጠን ለተቸገረ በመመጽወት፣ ልጆቻችን በክርስቲያናዊ መንገድ በማሳደግ፣ የቤተክርስቲያንን አገልግሎት በማፋጠን የእውነተኛ ደስታና የጽድቅ መንገድ እንድናደርገው እንጂ እግዚአብሔርን የተጠማች ነፍሳችንን ጥሪዋን በማደናቀፍና ጩኸቷን በማፈን በሥጋ ድሎት ውስጥ የምንደበቅበት መሣሪያ እንድናደረገው አይደለም፡፡ ለ«ታላቂቷ ከተማ» ነነዌም የጥፋት መንገድ የሆናት በብልጽገናዋና በታላቅነቷ እግዚአብሔርን ረስታ የኃጢአት ከተማ መሆኗ ነው፡፡ በነቢዩ በዮናስ ታሪክ ውስጥ ገንዘብ ለዮናስ ከእግዚአብሔር የመከለያ መሣሪያ ሲሆን እናገኘዋልን፡፡ «. ..  ከእግዚአብሔርም ፊት ኮብልሎ ከእነርሱ ጋር ወደ ተርሴስ ይሔድ ዘንድ ዋጋ ሰጥቶ ወደ እርሷ /ወደ መርከቧ/ ገባ» እንዲል /ዮና፤1-3/፡፡

በዚህ ሰዓት ለዮናስ ገንዘብ ባይኖረው ይሻል ነበር፡፡ እኛም ቢሆን ከንስሐ የሚመልስ፣ ለኃጢአት መሣሪያ የሚሆን ሀብት ከሚኖረን በድኅነት ብንኖር ይሻለናል፡፡ ምንም እንኳ በቤተክርስቲያናችን ትውፊት ዐቢይ ጾም አብዝተን የምንጸልይበት፣ በጾም በስግደትና በምጽዋት ልናሳልፈው የሚገባ ወቅት ቢሆንም ፤ አሁን አሁን ግን ገንዘብ ማግበስበሻ እየሆነ እንደሆነ እናያለን፡፡ በመሠረቱ በጾም ወቅት ከሆዳችን የምንቀንሰው ገንዘብ እንድናጠራቅመው ሳይሆን እንድንመጸወተው የሚገባ ነው፡፡ ለማጠራቀምማ የማያምኑ ሰዎችስ ምግብ ይቀንሱ የለ? ለዚህ ነው በነነዌ ጾም በመጀመሪያው ቀን /ሰኞ/ የሚነበበው የቅዱስ ያዕቆብ መልእክት «አሁንም እናንተ ባለ ጠጎች ስለሚደርስባችሁ ጭንቅ ዋይ ዋይ እያላችሁ አልቅሱ፡፡ ሀብታችሁ ተበላሽቷል፣ ልብሳችሁም በብል ተበልቷ፡፡ ወርቃችሁም ብራችሁም ዝጓል፤ ዝገቱም ምስክር ይሆንባችኋል፤ ሥጋችሁንም እንደ እሳት ይበላል፡፡ ለኋለኛው ቀን መዝገብን አከማችታችኋል፡፡ እነሆ እርሻሁን ያጨዱት የሠራተኞች ደመወዝ በእናንተ ተቀምቶ ይጮኻል፣የአጫጆችም ድምፅ ወደ ጌታ ጸባዖት ጆሮ ገብቷል፡፡ በምድር ላይ ተቀማጥላችኋል፤ በሴሰኝነትም ኖራችኋል፤ ለእርድ ቀን እንደሚወፍር ልባችሁን አወፍራችኋል፡፡» በማለት አስፈሪ ተግሳጽ የሚያስተላልፈው፡፡ ስለዚህ በዐቢይ ጾም አብዝተን የምንመጸውትበት፣ ከእግዚአብሔር የሆነውን ስጦታ የምንፈልግበት፣ የንስሐ ጊዜ ሊሆን ይገባል፡፡

2.    ለኃጢአት ሌላ ተጠያቂ መፈለግ

ሌላው ከንስሐ ሲያርቀን የሚገኘው ምክንያት በሰዎች መፍረድ ነው፡፡ በሰዎች የሚፈርድ ሰው ራሱን የሚያጸድቅ ነው፡፡ ራሱን ያጸደቀ ደግሞ ንስሐ መግባትና ከኃጢአት መመለስ ዳገት ይሆንበታል፡፡ ከነነዌ ሰዎች የንስሐ ታሪክ ውስጥ ለንስሐ በጣም አስቸጋሪ የነበረው ነቢዩ ዮናስ ነው፡፡ መርከበኞቹና የነነዌ ሰዎች በጥቂት ሰዓታት ውስጥ ወደ እግዚአብሔር ሲመለሱ ዮናስ ግን ከታሪኩ መጀመሪያ እስከ መጨረሻዋ ጊዜ ድረስ በእግዚአብሔር ያጉረመርም ነበር፡፡ ለዚህም ምክንያቱ ከእግዚአብሔር መኮብለሉና የነነዌ ሰዎችን ድኅነት መቃወሙን እንደ  ስህተት እንጂ እንደራሱ ስህተት አለመቁጠሩ ነው፡፡  ለዚህ ነበር ከእግዚአብሔር ኮብልሎ ሲሔድ እንኳ ምንም ዓይነት ጭንቀት ሳይሰማው «በከባድ እንቅልፍ» ተኝቶ የነበረው /ዮና.1-5/፡፡ በተመሳሳይ መልኩ አንዳንድ ሰዎች ለራሳቸው ኃጢአት እግዚአብሔርን ተጠያቂ ሲያደርጉ ሌሎች ደግሞ ሰዎችን ተጠያቂ ያደርጋሉ፡፡ በዚህም በራሳቸው ከመፍረድ ይልቅ በሰዎች መፍረድ ይጀምራሉ፤ ወይም የኃጢአታቸው ምክንያት እግዚአብሔርን አድርገው ይገኛሉ፡፡ ነቢዩ ዮናስ የራሱን ክብር ፈላጊነት ሳይሆን የእግዚአብሔርን ምሕረት የኃጢአቱ ምክንያት ማድረጉ የሚያስገርም ነው፡፡ ይህም ለብዙ ጊዜ ከንስሐ እንዳዘገየው ከታሪኩ እንማራለን፡፡ በተቃራኒው ለንስሐ ቅርብ የሆኑት መርከበኞች በዮናስ ላይ ለመፍረድ ምን ያህል እንደተጨነቁ ስናይ ቀድሞውኑ በዮናስ አለመታዘዝ ምክንያትም ቢሆን እግዚአብሔር ወደ ንስሐ ሊመልሳቸው የፈለገ ይህን አይቶ መሆኑን እንገነዘባለን፡፡

በጾመ ነነዌ የመጀመሪያው ቀን /ሰኞ/ የሚነበበው የቅዱስ ጳዉሎስ መልእክትም የሚያስተምረን ይህንኑ ነው፡- «ስለዚህ አንተ የምትፈርድ ሰው ሁሉ ሆይ፣ የምታመካኘው የለህም በሌላው በምትፈርድበት ነገር ራስህን ትኮንናለህና፡፡ አንተም ፈራጁ እነዚያን ታደርጋለህና፡፡ እንደዚህም በሚያደርጉት ላይ የእግዚአብሔር ፍርድ እውነተኛ እንደሆነ እናውቃለንና፡፡ . . . ወይስ የእግዚአብሔር ቸርነት ወደ ንስሐ እንዲመራህ ስታውቅ የቸርነቱንና የመቻሉን የትዕግሥቱንም ባለጠግነት ትንቃለህን? ነገር ግን እንደ ጥንካሬህና ንስሐ እንደማይገባ ልብህ የእግዚአብሔር ቅን ፍርድ በሚገለጥበት በቁጣ ቀን ቁጣን በራስህ ላይ ታከማቻለህ»/ሮሜ.2-1-5/፡፡ በተቃራኒው ግን በሰው ላይ ከመፍረድ በራሳቸው ላይ መፍረድን የሚመርጡ ሰዎች ለንስሐ ቅርብ ናቸው፡፡ በሚቀጥለው ቀን ማክሰኞ የሚነበበው የቅዱስ ጳውሎስ መልእክትም የሚያብራራው ይህንኑ ነው/1ቆሮ.4-1/፡፡

3.    የእግዚአብሔርን ተግሳጽ አለመቀበል

በነነዌ ሰዎች የንስሐ ታሪክ እግዚአብሔር በተለያየ መንገድ ሰዎችን ሲገስጽ እንመለከታለን፡፡ ነቢዩ ዮናስን በማዕበል፣ ወደባሕር እንዲወረወር በማድረግ፣ አሳ አንበሪ እንዲውጠው በማድረግ እግዚአብሔር ወደ ትክክለኛ መንገዱ ሊመልሰው ቢጥርም በዚህ ሁሉ ሊመለስ አልቻለም፤ ከአሳ አንበሪ አፍ ወጥቶ ሔዶ ቢሰብክም እግዚአብሔር ይቅር ሲላቸው ግን በእግዚአብሔር ላይ ማጉረምረም ጀምሯልና፡፡ ድሮም ቢሆን በፍርሃት እንጂ ስህተቱን ተቀብሎ አልነበረም ወደ ነነዌ ሔዶ የሰበከው፡፡ ግዕዛን የሌላቸው ፍጥረታት /ነፋስ፣ አሳ አንበሪ፣ ትል፣ ፀሐይ/ እንዴት እንደሚታዘዙለት እርሱ ግን ታላቅ ነቢይ ሲሆን አልታዘዝም ማለቱን በማሳየትም ገስጾታል፡፡ በመጨረሻም ለንስሐ በቅቷል፡፡ መርከበኞቹም በመርከባቸው ላይ የተነሣው ማዕበል ተግሳጽ ሆኗቸው ወደ ንስሐ ተመልሰዋል፡፡ ከዘላለም ሕይወት እንዳንለይ አጥብቆ የሚፈልገው እግዚአብሔር ልዩ ልዩ መከራዎችንም በማምጣት ወደ ንስሐ እንድንመለስ ያደርጋል፡፡ ለዚህ ተግሳጽ ግን በትክክለኛ ወይም በተሳሳተ መንገድ መልስ ልንሰጥ እንችላለን፡፡ ካወቅንባቸውና ከተጠቀምንባቸው ችግሮችና መከራዎች ወደንስሐ የሚመሩ መንገዶች ናቸው፡፡ የነነዌ ታሪክም የሚነግረን ይህንኑ ነው፡፡ በነነዌ ጾም በቅዳሴ የሚነበቡት የሚከተሉት ምንባባትም በአጽንኦት የሚገልጹት ይህንኑ ነው፡፡

 

ምስባክ:- «ማዕበልህና ሞገድህ ሁሉ በላዬ አለፈ፡፡
እግዚአብሔር በቀን ቸርነቱን ያዛል በሌሊትም ዝማሬው በእኔ ዘንድ ይሆናል
የእኔ ስዕለት ለሕይወቴ አምላክ ነው፡፡»
/መዝ.41-7-8/

መልእክት:- «. .  . ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በብዙ መከራ እንገባ ዘንድ ያስፈልገናል. . .» /ሐዋ.14-22/፡፡

 

በሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ አሳዛኙ ነገር ሰው ካለፈ ሕይወቱ አለመማሩ ነው፡፡ በነቢዩ በዮናስ ታሪክም የምናገኘው ይህንኑ ነው፡፡ እግዚአብሔር የተሳፈረበትን መርከብ ካናወጠ፣ ዮናስ በአሳ አንበሪ እንዲዋጥ ካደረገ በኋላ እንኳ እግዚአብሔር በነነዌ ሰዎች ላይ ያሳየው ምሕረት ዮናስ ሞትን እስኪመኝ ድረስ እንዲያዝንና በእግዚአብሔር ላይ እንዲያጉረመርም አድርጎታልና፡፡ በእኛም ሕይወት ተመሳሳይ ተግሳጻት ከእግዚአብሔር ዘንድ ቢመጣም ከኃጢአት ባለመመለስ ከዮናስ ያልተለየ መልስ ነው የምንሰጠው፡፡ ይህም የሆነበት ምክንያት ራሳችንን የምናይበት፣ በሕይወታችን ያደረጋቸውን የእግዚአብሔር ሥራዎች የምንመረምርበት፣ በውስጣችን ያደፈጡትን አውሬዎች የምናድንበት የተረጋጋና ሰፋ ያለ ጊዜ ስለሌለን ነው፡፡ ይህን አጥብቃ የተረዳችው ቅድስት ቤተክርስቲያናችን በልዩ ልዩ መንገድ የሚጠራንን የእግዚአብሔር ድምፅ የምናዳምጥበት፣ በመልካም ምክንያቶች የተሸፈኑ ነገር ግን መልካም ያልሆኑና መልካም ልንሠራበት የምንችለውን የሕይወት ጊዜዎችን የሚያቃጥሉ ከንቱ ምኞቶቻችን፣ የማይጨበጡና የማይደረስባቸው «ክፉ ተስፋዎቻችን» ሁሉ የምንመረምርበት፣ መልካሟንና እውነተኛዋን ነገር ግን አስቸጋሪዋንና ጠባቧን የሕይወት መንገዳችን አጉልተን «የምናስምርበት» ሰፋ ያለ ጊዜ ሰጥታናለች፤ ይህም ዐቢይ ጾም ነው፡፡ በዚህ ጊዜ በአግባቡ ከተጠቀምንበትም የዚህን አስቸጋሪና አወናባጅ ዓለም በድል የተወጡ ሰዎች የሚያዩትን የዘለዓለማዊን ሕይወት «ቀብድ» የትንሣኤውን ብርሃን እናያለን፡፡ ዐቢይ ጾምን እንደሚገባ ያላሳለፈ ክርስቲያን ግን የትንሣኤን ድግስ በልቶ ሆዱን ይሞላ እንደሆነ እንጂ የትንሣኤን ታላቅ ደስታ መቅመስ አይችልም፡፡ ስለዚህም ዐቢይ ጾም ለክርስቲያን ታላቅ ስጦታ መሆኑን ልናውቅ ይገባል፡፡ ለዚህም ነው ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ስለጾም በጻፉት መጽሐፋቸው «በዐቢይ ጾም ሕይወቱን ያልቀየረ ክርስቲያን በሌሎች አጽዋማት ይቀይራል ማለት ይከብዳል» በማለት የጻፉት፡፡

4.    ክፉ እኔነት

በዮናስ ታሪክ ውስጥ ከብዙ የዮናስ ስህተቶች ጀርባ የነበረውና ንስሐውን ያዘገየበት ታላቁ መሰናከል ክፉ እኔነት ነው፡፡ በመቶ ሺሕዎች የሚቆጠሩ የነነዌ ሰዎችን ድኀነት ሳይሆን የራሱን ክብር እንዲመለከት ያደረገው በዮናስ ሕይወት ውስጥ በጥልቅ የተተከለ ክፉ እኔነቱ ነው፡፡ በዚያ ሁሉ ታሪክ ውስጥ በርግጥም ዮናስ ስለራሱ እንጂ ስለሰዎች ሲያስብ አልታየም፡፡ ነቢዩ ዮናስ «እኔ ሐሰተኛ ነቢይ ከምባል የነነዌ ሰዎች መጥፋት ይሻላል»«የዮናስ አምላክ ቃሉን ይቀይራል ከምባል የነነዌ ሰዎች ይጥፉ» ብሎ ያስብ እንጂ እግዚአብሔር ግን አላለም፡፡ አመድና ትቢያ የሆነው የሰው ልጅ ስለክብሩ ሲጨነቅ ክብር የባሕሪዩ የሆነ ሩህሩህ አምላክ ግን ማንም እንዲጠፋ አልፈቀደም፡፡

በርግጥ የነነዌ ሰዎች በመዳናቸው የዮናስም የእግዚአብሔርም ቃለ አልታበለም፡፡ ዮናስ «ነነዌ በሦስት ቀን ውስጥ ትጠፋለች» ብሎ ሰበከ፡፡ አመጸኛዋ ነነዌ ግን በቁጣ እሳት ከመጥፋቷ በፊት በንስሐ ራሷን አዋረደች፡፡ በዚያን ጊዜ ነነዌ በንስሐ አዲስ ፍጥረት የሆነች፣ እግዚአብሔር የሚያጠፋት ሳትሆን የሚወዳት ሌላ ነነዌ ሆነች፡፡ ዮናስ ሆይ በንስሐ የታደሰችው ነነዌ የእግዚአብሔር ቅን ፍርድ እንደማያጠፋስ ለምን አላሰብክም? ታላቁ የእግዚአብሔር ነቢይ ሆይ ንስሐ የገባችዋን ነነዌን ማጥፋት አምላክህን አያስነቅፈውምን? በነቢዩ በዮናስ ውስጥ ያለው እኔነቱ በርግጥም እግዚአብሔርንም፣ የነነዌ ሰዎችንም እንዳያስብ መጋረጃ ሆኖበት ነበር፡፡

በነቢዩ በዮናስ ሕይወት ውስጥ ክፉ እኔነቱ በዚህ መልክ ቢገለጥም፣ በእያንዳንዳችን ሕይወት ውስጥ ግን በተለያየ መንገድ ሊገለጥ ይችላል፡፡ አንዳንዶቻችን «እኔ ቅዱስ ነኝ» የማለት ክፉ እኔነት ተጠናውቶናል፡፡ ኃጢአታችን ለንስሐ አባታችንና ለጓደኞቻችን ስንናገር እንኳ «ኃጢአትን የመናገር ቅድስና» እንጂ ኃጢአተኝነታችን አይሰማንም፡፡ «እኔ ርኩስ ነኝ» ስንልም ራስን በፈቃድ ኃጢአተኛ የማድረግ «ቅድስና» እንጂ ልባዊ የሆነ ንስሐ አይሰማንም፡፡ ሌሎቻችን ደግሞ «እኔ አዋቂ ነኝ» የማለት ክፉ እኔነት ይዞናል፡፡ «እኔ እኮ ምንም አላውቅም» ብለን ስንናገር እንኳን በልባችን ራስን ዝቅ ማድረግን «እያስተማርን» ነው በፍቅር ከተሰባሰቡ መንፈሳውያን ወንድሞችና እኅቶች መካከል እንኳን «ወርቃማ መንፈሳዊ ምክሮችን» ለመለገስ እንጂ መች ፍቅርን ‘ከታናናሾቻችን’ ለመማር እንቀመጣለንና፡፡ በዚህም በባዶነታችን እንኖራለን፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መድኃኒት መሆኑ እውነት ነው፤ ነገር ግን «ሕመምተኞች እንጂ ጤነኞች መድኃኒት አያስፈልጋቸውም» ብሏል፡፡ ሕመምተኞች መሆናችን አውቀን በንስሐ ብንቀርብ መድኃንኒት ይሆነናል፤ ራሳችንን አጽድቀንና «ቅዱስ ነኝ» ብለን በውሸት የጤንነት ስሜት መድኃኒት መፈለግ ከተውን ግን ከነኃጢአታችን እንሞታለን፡፡ ጌታችን ለእውራን ብርሃን፣ ዕውቀት ለሌላቸው ሰማያዊ ጥበብን የሚሰጥ ራሱ የእግዚአብሔር ጥበብ መሆኑ እውነት ነው፤ ነገር ግን ራሳችን በአዋቂዎች ተራ ከመደብን መምህር አልፎን ይሔዳል፡፡ ጌታ አለማወቃቸውን ያወቁትን ከእግዚአብሔር ዘንድ ሰማያዊ ጥበብን የሚፈልጉትን ሲያስተምር እንጂ «ምሁራንን» ሊያስተምር አልመጣምና፡፡ በኃጢአት መኖር እንደ ሀሞት መሮት፣ እንደጨለማ ከብዶት ከልቡ የሚጮኽን ተነሣሒ ለመቀደስ፣ እግዚአብሔር የዕውቀት ምንጭ የሕሊና ብርሃን መሆኑን አውቀው ከጥልቅ ከልቦናቸው ዕውቀትን የሚፈልጉትን ለማስተማር መጥቷልና እንደዚሁ ካልሆንን ከዚህ ጸጋ ዕድል ፈንታ አይኖረንም፡፡

ይህን ሁሉ የሕይወታችን ውጥንቅጥ እንመረምርበት ዘንድ ታላቁ የቤተክርስቲያን ስጦታ ዐቢይ ጾም እነሆ፡፡

የእውነተኛ ንስሐ ውጤቶች በነነዌ ሰዎች ታሪክ

1.    የዘላለም ሕይወት ተስፋ

ነነዌ የጥፋት ፍርድ ከተፈረደባት በኋላ የመኖር ተስፋ የተሰጣት ከተማ ናት፡፡ በሌላ አነጋገር ነነዌ ሞታ የተነሣች ከተማ ናት ማለት ይቻላል፡፡ ነቢዩ ዮናስም ወደ ባሕር ከተጣለ፣ በአሳ አንበሪ ሆድ ውስጥ ካደረ በኋላ የመኖር ተስፋ የተሰጠው ሰው ነው፡፡ መርከበኞችም መርከባቸው በማዕበል ከተመታች በኋላ፣ ማዕበሉ ካሸነፋቸው በኋላ በእግዚአብሔር ምሕረት ሌላ የመኖር ተስፋ የተሰጣቸው ሰዎች ናቸው፡፡ በአጠቃላይ የነነዌ ታሪክ የተስፋ ታሪክ ነው፡፡

ንስሐም በኃጢአት ከሞቱ በኋላ እንደገና የመኖር ተስፋ ነው፡፡ ብዙ ሰዎች የዘለዓለም ሕይወትን ተስፋ ማድረግ ይከብዳቸዋል፤ ለዚህም ምክንያቱ በንስሐ አለመኖራቸው ነው፡፡ ሰው ያላየውን ነገር እንዴት ይናፍቃል? የማያውቀውን ነገርስ እንዴት ተስፋ ያደርጋል? በንስሐ የሚኖር ሰው ግን የዘለዓለም ሕይወት ቀብድ የሆነ ትንሣኤ ልቦናን ይነሣልና የዘለዓለም ሕይወትን በተስፋ ይናፈቃሉ፡፡ ዐቢይ ጾምንም በንስሐና ራስን በመመርመር ያሳለፈ ሰው በትንሣኤው ትንሣኤን ይቀምሳልና ዘለዓለማዊውን ትንሣኤ በተሰፋ ይናፍቃል፡፡

በነነዌ ጾም የሚነበቡ የቅዳሴ ምንባባትም ይህን እንደሚከተለው ይገልጻሉ፡-

«. . .  ትዕግሥትም ፈተናን፣ ፈተናም ተስፋን እንዲያደርግ እያወቅን በመከራችን ደግሞ እንመካለን፡፡ በተሰጠንም በመንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ፍቅር በልባችን ስለፈሰሰ ተስፋ አያሳፍርም፡፡» /ሮሜ.5-4-5/፡፡

«እናንተ ግን፣ ወዳጆች ሆይ ከሁሉ ይልቅ በተቀደሰ ሃይማኖታችሁ ራሳችሁን ለማነጽ እየተጋችሁ በመንፈስ ቅዱስም እየጸለያችሁ፣ ወደ ዘለዓለም ሕይወት የሚወስደውን የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ምሕረት ስትጠባበቁ በእግዚአብሔር ፍቅር ራሳችሁን  ጠብቁ፡፡» /ይሁዳ.1-20/፡፡

2.    በእግዚአብሔር ዘንድ መከበር

በንስሐ የተመለሰችው ነነዌ በእግዚአብሔር ዘንድ እጅግ ከብራለች፡፡ የነነዌ ሰዎች ንስሐ በማይገቡ ዘንድ በትውልዱ ሁሉ ምስክር ይሆኑ ዘንድ እግዚአብሔር ፈቅዷል፡፡ «የነነዌ ሰዎች በፍርድ ከዚህ ትውልድ ጋር ተነሥተው ይፈርዱበታል፤ በዮናስ ስብከት ንስሐ ገብተዋልና፣ እነሆም «ከዮናስ የሚበልጥ ከዚህ አለ» እንዲል /ሉቃ.11-32/፡፡ የነቢዩ የዮናስ ታሪክም እንደዚሁ ነው፡፡ የንስሐ ሰባኪ የሆነው ራሱም ከብዙ የእግዚአብሔር ትዕግሥት በኋላ በንስሐ የተመለሰው ዮናስ የክርስቶስ ምልክት እንዲሆን እግዚአብሔር መፍቀዱ እግዚአብሔር ለተነሳሕያን የሚሰውን ክብር ያሳያል፡፡

ምንም እንኳን በዚህ ምድር ያለን ሰዎች የተነሣሕያንን ክብር ባናውቅም በሰማይ ያሉ መላእክት ግን በአንድ ኃጢአተኛ ንስሐ መግባት ታላቅ ደስታ ማድረጋቸው የንስሐን ክብር ያሳያል፡፡ ለዚህ ነው ለንስሐ የተዘጋጀ ልብን በማየት እግዚአብሔር አስቀድሞ ነነዌን «ታላቂቷ ከተማ» ብሎ የጠራት /ዮናስ.1-2/፡፡ ተነሣሕያን የእግዚአብሔር ይቅርታና ፍቅር የሚገለጥባቸው ሰዎች ናቸውና በእግዚአብሔርና በቅዱሳኑ ዘንድ የከበሩ ሰዎች ናቸው፡፡

3.    የእግዚአብሔርን ኃይል ማየት

በነነዌ ሰዎች የእግዚአብሔር ኃያልነት በግልጥ ተገልጧል፡፡ የእግዚአብሔር ኃያልነትም በትዕግሥቱ፣ በፍቅሩ፣ ፍጥረትን በመግዛቱ፣ ለሰው ልጆች በሰጠው ድንቅ ነፃነት ወዘተ ተገልጧል፡፡ በዚህ ታሪክ ውስጥ አንዲትም ነፍስ ሳትጠፋ ሁሉም ይድኑ ዘንድ እግዚአብሔር ያሳየው የትዕግሥቱ ኃያልነት እንዴት ድንቅ ነው! የእግዚአብሔርን ፈቃድ ያስተምር ዘንድ ነቢይ የሆነው ዮናስ እንኳ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ትቶ ሲኮበልል በሔደበት ሁሉ እየተከተለ በተለያየ መንገድ ወደ መንገዱ እንዲመለስ ይሠራ ነበር፡፡ ምናልባትም ሰው ዮናስን ይህን ያህል አይታገሰውም፡፡ ሰዎች እግዚአብሔርን ‘የመምከር’ ዕድል ቢሰጠን «ጌታ ሆይ አንተ ሁሉን ማድረግ ትችላለህ፤ ከነዚህ ድንጋዮት እንኳ ለአብርሃም ልጆች ማስነሣት ትችላለህ፡፡ ለምን ዮናስን ትለምነዋለህ? ተወው ሌላ ነቢይ ወደ ነነዌ ላክ፡፡ ዮናስን ርግፍ አድርገህ ተወው ከነነዌ ሰዎች የራሱን ክብር አስቀድሟልና፡፡» እንል ይሆናል፡፡ በባሕሪዩ ታጋሽ የሆነው እግዚአብሔር ግን ዮናስ በንስሐ ይመለስ ዘንድ ጠብቆታል፤ በመጨረሻም ለክርስቶስ ምሳሌ የሚሆን ታላቅ ነቢይ አድርጎታል፡፡

በነነዌ ታሪክ የእግዚአብሔር የፍቅሩ ታላቅነትም ተገልጧል፡፡ የእስራኤል አምላክ ይባል እንጂ ከአሕዛብ መካከል ለንስሐ የተዘጋጀ ሕዝብ ሲያይ ነቢዩን ልኮ ሕዝቡ አድርጓቸዋል፡፡ ቀና ልብ ያላቸው፣ ዮናስ ሲተኛ እንኳ ለማያውቁት አምላክ ሲጸልዩ የነበሩትን መርከበኞችንም በዮናስ  ምክንያት እንዲያውቁት አድርጓል፡፡ በርግጥም እግዚአብሔር ወደርሱ የምታይን ነፍስ፣ እርሱን የተጠማችን ልቦና አይተዋትም፡፡

በነነዌ ሰዎች ታሪክ የታየው ሌላው የእግዚአብሔር ኃይል በፍጥረቱ ላይ ያለው ሥልጣን ነው፡፡ ግዕዛን የሌላቸው ፍጥረታት /ፀሐይ፣ ማዕበል፣ ትል፣ ዛፍ፣ አሳ አንበሪ. . . / የእግዚአብሔርን ፈቃድ ያለምንም ተቃውሞ ሲፈጽሙ እናያለን፡፡ በዚህም እግዚአብሔር ለሰው ልጆች የሰጠውን ታላቅ ስጦታ ‘ነፃነትን’ እናደንቃለን፡፡ ፍጥረታት የሚታዘዙለት ኃይል እግዚአብሔር በነፃነት የፈጠረው የሰው ልጅ ፈቃዱን ሲጥስ ይመለስ ዘንድ በሚታዘዙት ፍጥረታት፣ በነቢያት. . . ይናገራል እንጂ ልቦናን በኃይሉ ቀይሮ እንደፈቃዱ እንዲኖር አያደርግም፡፡ ከዚህም በተጨማሪ መቀየር የፈለገን ልብ መቀየር የሚችል የሁሉ ፈጣሪ መሆኑን ፍጥረታቱን በማዘዝ አሳይቷል፡፡

ከዚህ ታሪክ ለእኛ የሚሆን ብዙ ነገሮችን እናገኛለን፡፡ የመጀመሪያው በንስሐ የምንኖር ከሆነ ወደዚህ ሕይወት እንደርስ ዘንድ እግዚአብሔር የታገሰባቸውን ያለፉትን የኃጢአት ዘመናት አስተውለን የእግዚአብሔርን የትዕግሥቱን ብርታት በሕይወታችን እናውቃለን፡፡ ከዚህ በኋላ ስለ እግዚአብሔር ታጋሽነት ሰዎች ሊነግሩን አያስፈልግም፤ በሕይወታችን አይተነዋልና፡፡

ከዚህም በተጨማሪ ወደ እርሱ እንመለስ ዘንድ በሕይወታችን ውስጥ የሠራውን የፍቅሩን ብርታትም እናውቃለን፡፡ ምንም እንኳ በዚህ ምድር ላይ ከቢሊዮኖች መካከል አንድ ብንሆንም በእግዚአብሔር ዘንድ ግን በንስሐ መመለሳችን ሁሌ በእግዚአብሔር ሕሊና ውስጥ ሲታሰብ የኖረ፣ በሰማያት ካሉ ቅዱሳን ይልቅ የአንድ ኃጢአተኛ መመለስ ለሰማያትና ለእግዚአብሔር ደስታ የሚሰጥ መሆኑን ስናውቅ በርግጥም እግዚአብሔር እንዴት ሰውን ወዳጅ ነው? ነፍሳችንስ በእግዚአብሔር ዘንድ ምን ያህል የምትወደድ ናት? እንላለን፡፡

ከዚህ ሌላ ፍጥረታት የእግዚአብሔር ሁሉን የማድረግ ሥልጣን በመታዘዝ እንዳሳዩ ሁሉ በንስሐ የተመለሰ ኃጢአተኛም የእግዚአብሔር ሁሉን ቻይነት የሚታይበት ይሆናል፡፡ በኃጢአት የኖረን፣ አያሌ ዘመናትን በዲያብሎስ ምክር በጠማማ መንገድ የኖረን ልቦና መቀየር ከኃያሉ ከእግዚአብሔር በቀር ለማን ይቻለዋል? ኃጢአተኛን ‘ቅዱስ’ ማድረግ የእግዚአብሔር የብቻው የኃያልነቱ ውጤት ነውና፡፡ ለዚህ ነው ‘ተነሳሕያን’ ሰማዕታት ናቸው የሚባለው፤ የእግዚአብሔርን ሥራ በሕይወታቸው ይመሰክራሉና፡፡ ጥንታውያን ክርስቲያኖች በደማቸው የእግዚአብሔርን ክብር መስክረው ከሆነ ለዚህ ትውልድ ደግሞ «የንስሐ» ሰማዕትነት ቀርቶለታል፡፡

በአጠቃላይ ከነነዌ ሰዎች ታሪክ ስለንስሐ ብዙ እንማራለን፡፡ ለዚህም ነው ከብዙ የንስሐ ታሪኮች መርጣ ቅድስት ቤተክርስቲያን በተለየ ክብር የምታስበው፡፡ ለዚህም ነው ለታላቁ የንስሐ ወቅት ለዐቢይ ጾም ማዘጋጃ መግቢያ ያደረገችው፡፡ እኛም ከዚህ ታሪክ ተምረን፣ የተማረነውንም በንስሐ ወቅታችን /በአሁኑ ጾም/ በተግባር ልናውለው ይገባል፡፡ ለዚህም የተነሳሕያን አምላክ ልዑል እግዚአብሔር ይርዳን! አሜን፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ጾመ ነነዌ!!

ጥር 25/2004 ዓ.ም.

በገብረእግዚአብሔር ኪደ

ነነዌ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ታሪካቸው በስፋት ከተጻፈላቸው የሜሶፖታምያ ከተሞች አንዷ ናት፡፡ ብዙ የሥነ መለኲት ምሁራን ከዛሬዋ የሞሱል ከተማ በተቃራኒ ከባግዳድ ሰሜን ምዕራብ 350 ኪ.ሜ. ርቀት ላይ እንደ ነበረች ይስማማሉ፡፡ ምንም እንኳን በ4000 ቅ.ል.ክ. ገደማ በናምሩድ በኩል ብትቆረቆርም /ዘፍ.10፡11-12/ የአሦራውያን ዋና ከተማ የሆነችው ግን በ1400 ቅ.ል.ክ. ነው /2ነገ.19፡36/፡፡ በከተማዋ በጣም ታዋቂ የነበረው የጣዖት ቤተ መቅደስ የአስታሮት ቤተ መቅደስ ይባላል፡፡
በዚህች ከተማ የሚኖሩት ሰዎች የሚሠሩት ክፋትና ኃጢአት እጅግ ከመብዛቱ የተነሣ ጽዋው ሞልቶ መጥፊያቸው ስለ ደረሰ ለፍጥረቱ ርኅራኄ ያለው እግዚአብሔር ግን ንስሐ ይገቡ ዘንድ ነብዩ ዮናስን ልኮላቸዋል፡፡ ይህ ነብይ ከአሕዛብ ወደ አሕዛብ የተላከ ነብይ ነው፡፡ አላላኩም  አንድ ነብይ ወደ እስራኤላውያን ተልኮ እንደሚያደርገው ለመገሰጽ ሳይሆን ወደ ንስሐ ይጠራቸው ዘንድ ነበር፡፡ ነገር ግን ነብዩ ወደዚያች ከተማ እንዲሄድ በእግዚአብሔር ቢታዘዝም ወደ ተርሴስ ሲኮበልል እንመለከተዋለን፡፡ ቅዱስ ጄሮም ነብዩ ለምን እንዲህ እንዳደረገ ሲናገር፡- “ዮናስ አሕዛብን ከመጥላቱ የተነሣ ሳይሆን መዳን ከእስራኤል እየራቀ መሆኑን በትንቢት መነጽር ሲመለከት ወደ ነነዌ አልሄድም አለ፡፡ ይኸውም ሙሴ ይህን ሕዝብ ከምታጠፋው እኔን ከሕይወት መጽሐፍህ ደምስሰኝ ያለው ዓይነት ነበር /ዘጸ.32፡31-32/፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም “ስለ እነርሱ እርሱ ቢረገም እንደሚመርጥ እንደሰማነው” ብሏል /ሮሜ.9፡3/፡፡ በእርግጥም በዘመነ ሐዲስ አሕዛብ በክርስቶስ አምነው ሲጠመቁ እስራኤል ግን መጻሕፍትን ብቻ ይዘው ቀርተዋል፤ እስራኤል ነብያትን ብቻ ይዘው ሲቀሩ አሕዛብ ግን የነብያቱን የትንቢት ፍጻሜ ይዘዋል /ማቴ.12፡42/፡፡
ልብና ኩላሊት ያመላለሰውን የሚያውቅ አምላክ ግን ዮናስ ላለመታዘዝ ብሎ እንዳላደረገው ስላወቀ በልዩ ጥበቡ ሲወስደው እናያለን፡፡ አስቀድሞ ታላቅ ነፋስን በመርከቢቱ ላይ አመጣ፤ ዮናስን የሚውጥ ታላቅ ዓሣ አሰናዳ፤ ቀጥሎም ዓሣው በየብስ እንዲተፋው አደረገ፡፡
ዮናስ ወደዚያች ከተማ ከደረሰ በኋላ ግን ምንም እንኳን የሦስት ቀን መንገድ ዙሮ መስበክ ቢጠበቅበትም የአንድ ቀን መንገድ ያህል ወደ ከተማይቱ ውስጥ ሊገባ ጀመረ፤ ጮኾም በሦስት ቀን ውስጥ ነነዌ ትገለበጣለች አለ። የነነዌም ሰዎች እግዚአብሔርን አመኑ፤ ለጾም አዋጅ ነገሩ፥ ከታላቁም ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ማቅ ለበሱ። ወሬውም ወደ ነነዌ ንጉሥ ደረሰ፤ እርሱም ከዙፋኑ ተነሥቶ መጐናጸፊያውን አወለቀ ማቅም ለበሰ፥ በአመድም ላይ ተቀመጠ።  አዋጅም አስነገረ፥ በነነዌም ውስጥ የንጉሡንና የመኳንንቱን ትእዛዝ አሳወጀ፥ እንዲህም አለ፡- “ሰዎችና እንስሶች ላሞችና በጎች አንዳችን አይቅመሱ፤ አይሰማሩም ውኃንም አይጠጡ፤ ሰዎችና እንስሶችም በማቅ ይከደኑ፥ ወደ እግዚአብሔርም በብርቱ ይጩኹ፤ ሰዎችም ሁሉ ከክፉ መንገዳቸውና በእጃቸው ካለው ግፍ ይመለሱ። እኛ እንዳንጠፋ እግዚአብሔር ተመልሶ ይጸጸት እንደ ሆነ፥ ከጽኑ ቍጣውም ይመለስ እንደ ሆነ ማን ያውቃል?” ሰው ወዳጁ ጌታም ከክፉ መንገዳቸው እንደተመለሱ ሥራቸውን አየ፤ ያደርግባቸው ዘንድ በተናገረው ክፉ ነገር ተጸጽቶ አላደረገውም። በእርግጥም እግዚአብሔርን የሚፈራ ልቡና የትምህርት ጋጋታ አያስፈልገውም፤ የቀናት ብዛት አያስፈልገውም፡፡
እኛ ክርስቲያኖችም ይህን በማዘከር “ንስሐ ብንገባ እንደ ነነዌ ሰዎች ከተቃጣው ማንኛውም መቅሰፍት እንድናለን” በማለት በየዓመቱ ከዓብይ ጾም መግቢያ ሁለት ሳምንት አስቀድማ ካለችው ሰኞ ጀምሮ እስከ ረቡዕ ድረስ “ጾመ ነነዌ” በማለት እንጾማታለን፡፡ ዘንድሮም ዓብይ ጾም የካቲት 12 ስለሚገባ የአሁኑ ሰኞ ጥር 28 እስከ ረቡዕ ጥር 30 እንጾማታለን፡፡
እግዚአብሔር የመረጠውን ዓይነት ጾም እንድንጾም ከተቃጣው ማንኛውም ዓይነት ፈተናም እንድናመልጥ ሰውን በመውደድ ሰው የሆነው ክርስቶስ ይርዳን አሜን!!
0015

ተዋሕዶ ያለ ጥርጥር ታላቅ ምስጢር /1ኛጢሞ 3፥16/

ጥር 23/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ኅሩይ ባየ

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የሁለት ዓመት የዕሥር ጊዜውን ጨርሶ ከሮም ከተማ ከወጣ በኋላ ጥቂት የአገልግሎት ጊዜ ሲያገኝ በ66 ዓ.ም የመጀመሪያዋን የጢሞቴዎስ መልእክት ጽፏል፡፡

0015“እግዚአብሔር ዓለምን ከፈጠረበት ጥበቡ ዓለምን ያዳነበት ጥበቡ ይበልጣል” እንደሚባለው  በግብር በቃል በሐሳብ ሥነ ፍጥረትን ከፈጠረበት አምላካዊ ጥበቡ ይልቅ ሰው በወደቀ ጊዜ ከወደቀበት የተነሣበት የአምላክ ሰው መሆን ምስጢር ታላቅ በመሆኑ ይኸ ምስጢር ያለጥርጥር ታላቅ ነው ተብሎ ተጽፏል፡፡ “በሥጋ የተገለጠ በመንፈስ የጸደቀ ለመላእክት የታየ በአሕዛብ የተሰበከ በዓለም የታመነ በክብር ያረገ” ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጠባብ ደረት በአጭር ቁመት ተወሰኖ እኛን ያዳነበት ጥበቡ ታላቅ ነው፡፡

አዳም የ30 ዘመን ጎልማሳ ሆኖ ተፈጥሮ በገነት 7 ዓመት ከኖረ በኋላ በምክረ ከይሲ ተታልሎ ልጅነቱን ቢያጣም ኢየሱስ ክርስቶስ ፈቃደ ሥጋን በጾም ድል ነሥቶ ሰው በእንጀራ ብቻ እንደማይኖር አስተምሮ ስስትን ድል አደረገ፡፡ የአዳም እግሮች ወደ ዕፀ በለስ ተጉዘው በእጁ ቆርጦ ቢበላ ኢየሱስ ክርስቶስ ከሊቶስጥራ እስከ ቀራንዮ ተጉዞ እጆቹና እግሮቹን ተቸንክሮ ተሰቅሎ አዳነው፡፡ አዳም ከጸጋ ልብሱ ቢራቆት ኢየሱስ ክርስቶስም የብርሃን ልብሱ እንዲመለስለት እርቃኑን ሆኖ ተሰቀለ፡፡ ይህ ሁሉ የማዳን ሥራው በሥጋ በመገለጡ የተደረገ እንደሆነ ልንረዳ ይገባል፡፡ የአዳምን ሞት ወሰዶ የእሱን ሕይወት ሰጥቶ የመቃብርን ኀይል ሽሮ ሞትን ድል አድርጎ እኛን ያዳነበት ጥበቡ ያለጥርጥር ታላቅ ነው፡፡

የእግዚአብሔር ምስጢሩ ታላቅ መሆኑን ቅዱስ አትናቴዎስ ሲያስረዳ “ስለ እግዚአብሔር አንድነትና ሦስትነት መረዳት /ማወቅ/ የልብሱን ጠርዝ ብቻ እንደማወቅ ነው፡፡ ስለ ምስጢረ መለኮት የበለጠ በመረመርኩ ቁጥር የበለጠ ምስጢር ይሆንብኛል” ይላል፡፡ እውነትም የእግዚአብሔርን አንድነትና ሦስትነት መመርመር የአምላክ ሰው የመሆንን ምስጢር መረዳት ለሰው አእምሮ የረቀቀ ነው፡፡

አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆኖ አዳምን እና ልጆቹን ያዳነበት ምስጢር ያለጥርጥር ታላቅ በመሆኑ በቸርነቱ ያዳነንን አምላክ ከማመስገን በቀር ምን ልንል እንችላለን?

በኦርቶዶክሳዊ ተዋሕዶ ትምህርታችን አምላክ ሰው ሆኖ አዳምንና ልጆቹን አዳናቸው ብለን እናስተምራለን አምላክ ሰው ሆነ፤ ሰውም አምላክ ሆነ ስንል በምስጢረ ተዋሕዶ ነው፡፡ በ431 ዓ.ም በኤፌሶን ጉባኤ ንስጥሮስን ከክህደቱ ለመመለስ 200 የሚሆኑ ሊቃውንት ሲሰበሰቡ የሊቃውንቱ አፈ ጉባኤ የነበረው ቅዱስ ቄርሎስ ተዋሕዶ የሚለውን ቃል አጉልቶ ተጠቅሞበታል፡፡ ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ኦርቶዶክስ ከሚለው ቃል ጋር ተዋሕዶ የሚለው ቃል የበለጠ መታወቅ ጀምሯል፡፡

አምላክ ሰው ሆነ ስንል መለኮት ወደ ሥጋነት ሥጋም ወደ መለኮትነት ተለወጠ ማለታችን አይደለም፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ የሎጥ ሚስት የጨው ዓምድ /ሐውልት/ ሆናለች /ዘፍ.19፥26/፡፡ በቃና ዘገሊላም በገቢረ ተአምር ውኃው ወደ ወይን ጠጅ ተለውጧል /ዮሐ.2፥1/፡፡ የሎጥ ሚስት የጨው ሐውልት እንደሆነችው፤ ማየ ቃናም ፍጹም የወይን ጠጅ እንደሆነው አምላክ ሰው ሆነ ስንል አምላክነቱን ለውጦ ፍጹም ሰው ብቻ ሆነ ማለታችን አይደለም፡፡ እንዲሁም አምላክ ተለውጦ ሰው ቢሆንማ ኖሮ የእሩቅ ብእሲ ደም ድኅነትን ሊያሰጥ ስለማይችል በኢየሱስ ክርስቶስ ያገኘነውን ፍጹም ድኅነት ከንቱ ያደርግብናል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን በባሕርዩ እንደማይለወጥ በነቢዩ በሚልክያስ አድሮ “እኔ እግዚአብሔር አልለወጥም” ብሏል /ሚል.3፥6/፡፡ በመሆኑም አምላካችን ሰው የሆነበት ምስጢር ቃል /መለኮት/ በሥጋ ሥጋም በቃል ሳይለወጥ ሳይጠፋፉ መሆኑን ማስተዋል ይገባል፡፡

“ቃል ሥጋ ሆነ…. በእኛም ላይ አደረ” /ዮሐ.1፥1-14/ የሚለው ገጸንባብ መጽሐፍ በማኅደር ውኃ በማድጋ እንዲያድር መለኮት በሥጋ ላይ አደረበት ማለት አይደለም፡፡ “የእግዚአብሔር ልጅ ከድንግል ማርያም በተወለደው በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ አደረበትና የጸጋ አምላክ አደረገው እንጂ ሥጋን አልተዋሐደም” ብሎ ንስጥሮስ ያስተማረው  የኅድረት /ማደር/ ትምህርት በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የተወገዘ ክህደት ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በፈለገ ዮርዳኖስ በእደ ዮሐንስ ሲጠመቅ አብ በደመና ሆኖ “በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት” /ማቴ.3፥17/ አለ እንጂ “የልጄ ማደሪያ የሆነውን እርሱን ስሙት አላለም”፡፡ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ መሆኑን ነቢዩ ሲያስረዳ “…ስሙም ድንቅ መካር ኃያል አምላክ…” /ኢሳ. 9፥6/ ብሏል፡፡ ለዚህም ቤተ ክርስቲያናችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተዋሕዶ ሰው የሆነ አምላክ ነው እያለች ታስተምራለች፡፡

አምላክ ሰው የሆነው መለኮትና ሥጋ ተቀላቅለው ነው አንልም፡፡ መቀላቀል /ቱሳሔ/ መደባለቅንና ከሁለቱም የተለየ ማእከላዊ ነገር መፍጠርን የሚያመለክት ቃል ነው፡፡ ውኃና ወተት ሲቀላቀሉ ስም ማእከላዊ መልክ ማእከላዊና ጣእም ማእከላዊን ያመጣሉ፡፡ ስም ማእከላዊ ውኃ ከወተት ጋር ቢቀላቀል ፈጽሞ ውኃ ፈጽሞም ወተት ባለመሆኑ አንጀራሮ የተባለ ሌላ ስም ይሰጠዋል፡፡ መልክ ማእከላዊ ስንልም ውኃው እንደወተቱ ባለመንጣቱ እንደ ውኃውም ባለመጥቆሩ መካከለኛ የሆነ መልክ ይይዛል፡፡ ጣእም ማእከላዊ ውኃውም ወተቱም የቀደመ ጣእማቸውን ለቀው እንደ ውኃ ባለመገረም/ባለመክበድ/ እንደ ወተቱ ባለመጣም ማእከላዊ የሆነ ጣእም ያመጣል፡፡ የአምላክ ሰው የመሆን ምስጢር ግን ሥጋ የሥጋን ባሕርይ ሳይለቅ መለኮትም የመለኮትነትን ባሕርይ ሳይለቅ በተአቅቦ /በመጠባበቅ/ ባለመጠፋፋት ነው፡፡ መለኮትና ሥጋ ሳይቀላቀሉ ሥጋ የመለኮትን ባሕርይ የራሱ አድርጎ መለኮትም የሥጋን ባሕርይ ገንዘቡ አድርጎ በተዋሕዶ ሰው ሆነ፡፡

አምላክ ሰው ሆነ፤ ሰው አምላክ ሆነ ስንል ልብስ በልብስ ላይ እንደሚደረብ መለኮትና ሥጋ እንደዚሁ በትድምርት /በመደራረብ/ ሰው ሆነ ማለት አይደለም፡፡ በቆሎና ስንዴ ቢቀላቀሉ ይህ በቆሎ ነው ይህ ስንዴ ነው ብለን እንደምንለያቸው የመለኮትና የሥጋ ተዋሕዶ በመለያየት /በቡአዴ/ ከቶ አልሆነም፡፡

ማኅተመ አበው ቅዱስ ቄርሎስ ምስጢረ ተዋሕዶን ባስተማረበት ትምህርቱ አምላክ ሰው ሆነ፤ ሰው አምላክ ሆነ ስንል በተዋሕዶ እንደሆነ በምሳሌ ገልጦ አስተምሯል፡፡ ተዋሕዶውም ነቢዩ ሙሴ በኮሬብ ተራራ በጎቹን ሲጠብቅ ነበልባሉ ሐመልማሉን ሳያቃጥል ሐመልማሉም በነበልባሉ ሳይጠፋ እንዳልተጠፋፉት መለኮት ሥጋን ሳያቀልጠው መለኮትም በሥጋ ሳይጠፋ በተዋሕዶ አንድ ሆነ እንላለን፡፡ በእሳት ውስጥ የገባ ብረትም የባሕርዩ ያልነበረውን ብሩህነት በእሳቱ ያገኛል፤ ቀድሞ አይፋጅ የነበረው ብረት ይፋጃል፡፡ አካል ያልነበረው እሳትም በብረቱ ሆኖ ቅርጽ ይኖረዋል፡፡ አይጨበጥ የነበረው እሳት ይጨበጣል፤ አይዳሰስ የነበረው እሳት ይዳሰሳል፡፡ አንጥረኛው በጉጠት ብረቱን ይዞ ፍህም የሆነውን ብረት ይቀጠቅጠዋል፡፡ ብረቱ ሲደበደብ የተመታው እሳቱ ነው፡፡ ወይም ደግሞ ብረቱ ነው አይባልም፡፡ እሳትና ብረት በተዋሕዶ አንድ ስለሆኑ ብረቱ ሲመታ እሳቱ አለ፤ እሳቱ ሲመታም ብረቱ አለ፡፡ እሳቱ ሲፋጅም /ቢያቃጥልም/ ብረቱ አለ፡፡የመለኮትና የሥጋ ተዋሕዶም በዚህ መልክ ስለሆነ መለኮት ሥጋን በመዋሐዱ መከራን ተቀብሎ ሞቶ አዳነን ብለን እናምናለን፡፡

በዮሐንስ ወንጌል እንደተጻፈው ዐይነ ስውሩን ሰው አምላካችን ሊያድነው በፈቀደ ጊዜ ምራቁን ወደመሬት እንትፍ ብሎ በጭቃ ዐይኑን ቀብቶ አድኖታል /ዮሐ.9፥1/ ምራቅ ብቻውን ዐይንን በማብራት ተአምር መሥራት የማይችል የሥጋ ገንዘብ ነበረ፡፡ መለኮት ብቻውንም ምራቅ ማውጣት አፈር ማራስ አይስማማውም ሥጋ ከመለኮት ጋር ተዋሕዷልና በምራቁ ዕውርን አበርቷል፡፡ ገቢረ ተአምራቱም የተከናወነው በሥጋ ብቻ ነው ወይም በመለኮት ብቻ ነው አይባልም፡፡

ከሦስቱ አካላት አንዱ ወልድ ሰው በመሆኑ በባሕርዩ ተዋራጅነት የለውም በላይ በሰማያት ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እየተመሰገነ በምድር ዞሮ አስተምሮ መከራን ተቀብሎ ፍጹም ድኅነትን ሰጥቶናል፡፡ በሥጋ ተርቧል፣ ተጠምቷል አንቀላፍቷል፡፡ አምላክ ነውና ሙት አንሥቷል ድውይ ፈውሷል፡፡ በመሆኑም አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ ሆነ የምንለው በተዋሕዶ ነው፡፡ በተዋሕዶ አንድ ባሕርይ በመሆኑ የሥጋንም የመለኮትንም ሥራ ባለመለያየት ባለመነጣጠል ሠራ በቅዱስ መጽሐፍ “በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቋት ዘንድ፡፡” /ሐዋ.26፥28/ ተብሎ መጻፉ መለኮት በባሕርዩ ሥጋ ደም ኖሮት አይደለም፡፡ ይህ የሐዋርያው ቃል መለኮት የሥጋን ባሕርይ ባሕርዩ አደረገ ደሙን አፈሰሰ ሥጋውን ቆረሰ ብለን ለምናስተምረው የተዋሕዶ ትምህርት የታመነ ምስክር ነው፡፡ እግዚአብሔር “በገዛ ደሙ” ቤተ ክርስቲያንን የዋጃት በተዋሕዶ ሰው በመሆን ነውና በእውነት ይህ ምስጢር ታላቅ ነው፡፡

አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ስለምስጢረ ሥጋዌ እንዲህ ይላል” ሐዋርያ ሊሆን የተጠራ የኢየሱስ ክርስቶስ አገልጋይ ጳውሎስ በነቢያቱ አፍ በቅዱሳት መጻሕፍት አስቀድሞ ስለልጁ የተናገረ በሰብአዊ ሥጋ ከዳዊት ዘር ስለተወለደ በአብና በመንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ እንዲሆን ዐሳየ ዳግመኛም ነቢዩ እንባቆም እንዲህ አለ፤ እግዚአብሔር ከቴማን ቅዱሱም ከፋራን ተራራ ይመጣል፡፡ ፋራን በጣዕዋ /በጥጃ/ ይተረጎማል ጣዕዋ በንጽሕት ድንግል ይተረጎማል፡፡ ክብሩ ሰማያትን  ከድኗል፡፡ ይህም በመለኮት ኀይል ከአባቱ ጋር እኩል ትክክል በመባል ይተረጎማል፡፡ ምስጋናውም ምድርን ሞልቷል ይህም በአጽናፈ ዓለም በተሰበከው ገቢረ ተአምራት ይተረጎማል በምድር ሁሉ ነገራቸው ወጣ፡፡ እስከ አጽናፈ ዓለም ንግግራቸው ደረሰ፤ ተብሎ በነቢዩ እንደተነገረ፤ ዳግመኛ በነቢይ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩክ ነው ተብሎ እንደተነገረ፤ ዳግመኛም ከእግዚአብሔር ቤት መረቅናችሁ፤ ጌታ እግዚአብሐር ተገለጠልን፤ እንደገና በኪሩቤል የሚቀመጥ ተገለጠ፤ ተብሎ እንደተነገረ ያለሥጋዌ እግዚአብሔርን ያየ ማነው? ሙሴን “ፊቴን ዐየቶ በሕይወት የሚቆይ የለም” እንዳለው ነው” ይላል፡፡ /ሮሜ.1፥33፣ ዕብ.1፥1፣ ዕን.3፥3፣ መዝ.18፥4፣ መዝ.117፥26-27፣ መዝ.79፥1፣ ዘፀ.33፥1/ (መጽሐፈ ምስጢር 2000፥82 በአማኑኤል ማተሚያ ቤት ኀይለ ማርያም ላቀው /መ/ር/ እንደተረጎመው)

ተዋሕዶ ከሚጠት /ከመመለስ/፣ ከውላጤ /ከመለወጥ/፣ ከቱሳሔ /ከመቀላቀል/፣ ከትድምርት /ከመደረብ/ ከቡዐዴ /ከመቀራረብ/ በራቀና በተለየ ሁኔታ አምላክ ሰው የሆነበት ምስጢር ነው፡፡ መለኮትና ሥጋ አንዱ አንዱን ሳያጠፋው፣ ሳይለውጠው፣ ያለ መለያየት፣ ያለመከፋፈል ያለ መጠፋፋት ያለ መቀላቀል በተዐቅቦ /በመጠባበቅ/ የተዋሐዱበት አምላክ ሰው የሆነበት ይህ ምስጢር ድንቅ ነው፡፡

ቅዱስ ቄርሎስ የተዋሕዶን ምስጢር በምሳሌ ሲያስረዳ እንዲህ ይላል “የሚረዳህስ ከሆነ የትስብእትና /የሥጋ/ የመለኮትን ተዋሕዶ በእኛ ነፍስና ሥጋ ተዋሕዶ መስለን እንነግርሀለን፤ እኛ በነፍስና በሥጋ የተፈጠርን ነንና፤ አንዱን የሥጋ አንዱን የነፍስ ብለን ሁለት አካል ሁለት ባሕርይ አናደርገውም፤ ሰው ከሁለት አንድ በመሆኑ አንድ ነው እንጂ፡፡ ከሁለቱም ባሕርያት አንድ በመሆኑ ሁለት ሰው አይባልም፡፡ በነፍስ በሥጋ የተፈጠረው ሰው አንድ ነው እንጂ፡፡ ይህንንስ ካወቅን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተዋሕዶ በፊት እርስ በርሳቸው አንድ ካልነበሩ ከተዋሕዶ በኋላም ከማይለያዩ ከሁለት ባሕርያት አንድ እንደሆነ እናውቃለን” /ሃይማኖተ አበው ዘቄርሎስ.78፥19/

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በነሣው ሥጋ በምድር ላይ በመገለጡ ከባሕርዩ የጎደለበት ነገር የለም፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በላይ በሰማያት በመላእክት እየተመሰገነ በምድር ዞሮ አስተማረ፤ መከራ ተቀበለ ብለን እናምናለን፡፡ ለዚህ አስተምህሮ ምስክር የሚሆነን የቅዱሳን መላእክትና የቅዱስ ያሬድ የምስጋና ቃል ነው፡፡መላእክቱ “ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ” አሉ /ሉቃ.2፥14/፡፡ ቅዱስ ያሬድም “ፍጥረትን ሁሉ የሚመግብ ጌታቸው በብብትሽ /በክንድሽ/ ተቀምጦ እንደ ሕፃን ጡትሽን ሲጠባ መላእክት ባዩት ጊዜ በአርያም ፈለጉትና በዚህ ዓለም እንደ ቀድሞው ከአባቱና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አገኙት” ብሎ አመስጥሮታል፡፡ ፀሐይ ባለችበት ሆና ምድርን እንደምታሞቅ እርሱም በዙፋኑ ተቀምጦ /ዓለምን እየገዛ/ በምድር በሥጋ ማርያም ተገለጠ፡፡ ሥጋን ተዋሕዶ ዞሮ አስተማረ” /አንቀጸ ብርሃን ዘቅዱስ ያሬድ/

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆኖ እኛን ያዳነበት ጥበቡ በልባችን ስናስበው በአንደበታችን ስንናገረው ምስጢሩ ድንቅ በመሆኑ ሐዋርያው ይህ ምስጢር ያለጥርጥር ታላቅ ነው ይላል፡፡ ነቢዩ ሙሴም የእግዚአብሔር ሥራ ግሩም በመሆኑ አምነን ከመቀበል ውጭ መርምረን መድረስ ስለማንችል “ምስጢሩ ለአምላካችን ለእግዚአብሔር ነው” ዘዳ.29፥29 እንድንል ያስታውሰናል፡፡

ሎቱ ስብሐት ለዘበስብሐተ አቡሁ ይሴባሕ ወሎቱ ቅድሳት ለዘበቅድሳተ መንፈሱ ይትቄደስ ለዓለመ ዓለም አሜን ወአሜን፡፡በአባቱ ምስጋና ለሚመሰገን ለእርሱ ምስጋና ይገባል፡፡ በመንፈሱ ቅድስና ለሚቀደስ ለእርሱ ምስጋና ይገባል ለዘለዓለሙ አሜን፡፡