like kahenate hayle selasa

ስለ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ምርጫ ምን ይላሉ?

ታኅሣሥ  11 ቀን 2005 ዓ.ም.

  • “እግዚአብሔር ከእኛ በላይ የሚመለከታቸው አባቶች አሉ”

ሊቀ ካህናት ኃይለ ሥላሴ ዓለማየሁ

ከሰሜን አሜሪካ ከኮሎራዶ ስቴት

like kahenate hayle selasaቤተ ክርስቲያን የሚጠብቅ የሚመራ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት ቅዱስ አባታችን በማረፋቸው የተነሣ ሀገራችን ትልቅ ሐዘን ላይ ናት፡፡ በዚህ ወቅት ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው  የጸሎቱ ጉዳይ ነው፡፡ እግዚአብሔር በመንበሩ ደግ አባት እንዲያስቀምጥ በጸሎት ሊለመን ይገባል፡፡ አሁን ቤተ ክርስቲያን ጥንቃቄ ልታደርግበት ይገባል ብዬ የማስበው በሰው ሰውኛ መንገድ በመጓዝ ለቤተ ክርስቲያን የሚሆነውን አባት ለመምረጥ ከተሞከረ ነው፡፡ እግዚአብሔር ሙሴን፣ አሮንን እንደጠራቸው ሁሉ የሚመረጡት አባት እግዚአብሔር የጠራቸው አባት እንዲሆኑ መጸለይ ያስፈልጋል፡፡ ሁላችንም ኢትዮጵያውያን ነን፤ ሁላችንም የቤተ ክርስቲያን ልጆች ነን፤ ሁሉም አባቶቻችን የቤተክርስቲያን አባቶች ናቸው፡፡ «እገሌ ከእገሌ» ሳይባል መንፈስ ቅዱስ የጠራው አባት ለዚህች ቤተ ክርስቲያን መሪ እንዲሆን መጸለይ ያስፈልጋል፡፡

 

በሰው ሰውኛውን ተመልክተን “አቡነ እገሌ” ቢሆኑ ይሻላል የምንለው የሚጠቅም አይሆንም፡፡ እግዚአብሔር ከእኛ በላይ የሚመለከታቸው አባቶች ስለሚኖሩ “እገሌ ከእገሌ” ይሻላል ብሎ መምረጥ ያለበት እግዚአብሔር ነው፡፡ መብቱን ለመንፈስ ቅዱስ ከሰጠነው ትክክለኛ አባት ሊመርጥ ይችላል፡፡ ስለዚህ ሁላችንም በኅብረት ሆነን ሥራው ውጤታማ እንዲሆን መተባበር በምንችለው አቅም ማገልገል፣ መጸለይ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ሥራ የሚጠቅም ይመስለኛል፡፡ ነገ ሊጸጽተን የሚችል ሥራ መሥራት የለብንም፡፡ ነገ የሚጸጽተን ሥራ መሥራት ቤተ ክርስቲያናችንን ሊጎዳ ይችላል፡፡ ሰው ይጠቅመኛል ብሎ የሚያስቀምጠው ሰው ሰውኛውን ይሆንና ቤተ ክርስቲያንን ሊጎዳ ይችላል፡፡ ትልቁ ነገር ቤተ ክርስቲያንን የማይጎዳ ሥራ መሥራት ነው፡፡ ይህ ሲሆን ነው እግዚአብሔር የሚያግዘን፣ በረከቱን የሚያበዛልን፡፡

 

እግዚአብሔር ፈቅዶ በዚህ መንበር የሚያስቀምጣቸው አባት ቀዳሚ ሥራቸው እግዚአብሔር የሰጣቸውን መንጋ መሰብሰብ ነው፡፡ የትናንትናው ዘመን ከዛሬው ዘመን የተለየ ስለሆነ ዘመኑን መዋጀት ያስፈልጋል፡፡ ዘመኑን መዋጀት ሲባል አንድ አባት ብቻቸውን የሚሠሩት ነገር አይደለም፡፡ የመንፈሳዊ አባታችን እጅ፣ እግር፣ ዐይን እኛ ልጆቻቸው ስለሆን ልጆቻቸውን አስተባብረው አንድ አድርገው ሊመሩ ይገባል፡፡ ይህች ቤተ ክርስቲያን የአንድነት፣ የሰላም ምሳሌ ናት፡፡ ለኢትዮጵያ አንድነቷ፣ ሰላሟ፣ መሠረቷ ይህች ቤተ ክርስቲያን ስለሆነች፤ ሰላሙ ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል፡፡ ማንም ቢሆን ከዚህች ቤተ ክርስቲያን እንዲወጣ የሚፈልግ የለም፡፡ ክርስቶስ ደሙን ያፈሰሰው፣ መሥዋዕት የሆነው፣ ቀራንዮ ላይ የዋለው ለዓለሙ ሁሉ እንጂ ለተወሰኑ ሰዎች አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ጠላቶች የሏትም ሁሉም የእግዚአብሔር ልጆች ናቸው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ጠላት የሆኑ ካሉ ደግሞ በተቻለ መጠን ማስተማር ቅድሚያ ይሰጠዋል፡፡

 

ተመራጩ ፓትርያርክ ቅዱስ  ሲኖዶስን አስተባብረው ቤተ ክርስቲያንን የሚጠብቁ ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ ዛሬ የምትጠብቃቸው ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ ከእነዚህም አንዱ የውጪ መንጋ ነው፡፡ ከዚህ በተጓዳኝ የአብነት ትምህርት ቤቶች፣ ስብከተ ወንጌል አገልግሎት፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ወዘተ የመጠበቅ ትልቅ ሓላፊነት አለባቸው፡፡ ፓትርያርኩ ከቅዱስ ሲኖዶስ ጋር ተባብረው ቅዱስ ሲኖዶስ በሚያወጣው ሕገ ደንብ መሠረት በመገዛት የቅዱስ ሲኖዶስ ወሳኔ አስፈጻሚ እየሆኑ ይህን ተግባር ማከናወን ይጠበቅባቸዋል፡፡ ስለዚህ ተመራጩ አባት ያለባቸው ሓላፊነት ቀላል አይደለም፡፡ ይህንንም ከአንድ ሰው ብቻ የምንጠብቀው ነገር አይደለም፡፡ ሁላችንም ተባብረን የድርሻችንን ስንወጣ የሚመረጡት አባት ሓላፊነታቸውን መወጣት ይችላሉ፤ ትልቁ ሓላፊነት የቅዱስ ሲኖዶስ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡

 

  • “በሁለቱም አባቶች ዘንድ እርቁ ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል”

መላከ ጽዮን በላቸው ወርቁ

በሰሜን አሜሪካ በኒዮርክና

አካባቢው ሀገረ ስብከት የራችስተር

ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም

ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ

የቤተ ክርስቲያኒቱ የእርቅና የሰላም ጉዳይ እጅግ በጣም አንገብጋቢና ወሳኝ ጉዳይ ነው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ አባቶች በአስተዳደራዊmelake tsyone ምክንያት ተለያይተው በተፈጠረው ችግር በአሜሪካን በሚኖሩ ካህናት፣ ወጣቶች ምእመናን ዘንድ እጅግ በጣም ከፍ ያለ የመለያየት መንፈስ ፈጥሯል፡፡ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መጠናከር በአንድነት መሥራት ሲገባ፤ በአንጻሩ ክፍተት ተፈጥሮ እርስ በርስ ካለመግባባት የተነሣ ለቤተ ክርስቲያን ጠላቶች በር የከፈተ ጉዳይ ሆኗል፡፡ እርቀ ሰላሙን ለመፈጸም የማንም ተፅዕኖ ሳይኖር በአባቶች ተነሣሽነት ቁርጥ ውሳኔ ያስፈልጋል፡፡ ለትውልድ፣ ለታሪክ ሲባል በፍቅር፣ በሰላም፣ በአንድነት ቤተ ክርስቲያንን እንዲያገለግሉ ሕዝቡን ለማዋሐድ በአባቶቻችን በኩል የተፈጠረውን ችግር በእነርሱ በኩል መፍትሔ እንዲያመጣ መከናወን አለበት፡፡

 

በአሜሪካን ሀገር በእርቅ ኮሚቴው የሚሳተፉ ሰዎች በአቀረቡልን ጥያቄ መሠረት የማኅበረ ቅዱሳን አባላት፣ በየቀጠና ማእከላቱ በየአጥቢያው የገንዘብም የዐሳብም አስተዋጽኦ እያደረጉ ነው፡፡  ባለን ሚዲያ፣ በድረ ገጽም ሆነ በሌሎች ለእርቁ ትኩረት በመስጠት ጽሑፎችን በማዘጋጀት፤ በትምህርተ ወንጌሉም በዚሁ ርእሰ ጉዳይ ላይ አተኩረን  እየሠራን ነው፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በማረፋቸው በዐቃቤ መንበር የሚመራ በቅዱስ ሲኖዶስ ተሠይሟል፡፡ በዚህ ሂደትም ውስጥ ተጀምሮ የነበረው እርቅ ትኩረት ተሰጥቶት በሁለቱም አባቶች ዘንድ የመጀመሪያ አጀንዳ ሆኖ እርቁ ቢፈጸም ሁላችንንም የሚያስደስት ነው፡፡

 

ቤተ ክርስቲያን የራሷ ቀኖና አላት፡፡ መንፈሳዊ አባቷን በቀኖናዋ መሠረት ምርጫዋን ትፈጽማለች፡፡ ከምርጫው በፊት ሊታዩ የሚገባቸው ነገሮች አሉ፡፡ እነዚህም የቤተ ክርስቲያን ሕግ፣ ደንብና መመሪያው ለምርጫው በግልጽ ተቀምጦ (መስተካከል ካለበት የሚስተካከለው ታይቶ) በአግባቡ ምሉዕ እንዲሆን ያስፈልጋል፡፡ እግዚአብሔር ሙሉ በሙሉ ኖሮበት ምርጫው እንዲከናወን ቢደረግ፡፡ ሌላው ከምርጫው በፊት ሌሎች ሊከናወኑ የሚገባቸው ሂደቶችም ካለፈው የተማርናቸው ስሕተቶች ምንድን ናቸው) ብሎ ቅዱስ ሲኖዶስ ሊያያቸው የሚገባቸው ነገሮች አሉ፡፡ ለምሳሌ የቅዱስ ፓትርያርኩ የሥራ ሓላፊነት ዝርዝራቸው በቀኖናው ላይ ተጠቅሷል፡፡ በግልጽ ያልሰፈረ ካለ ከምርጫው በፊት የቤተ ክርስቲያኒቷ ሕግ ከመንበረ ፓትርያርኩ ጀምሮ በአደረጃጀቱ፣ በአወቃቀሩ ታች ድረስ ምሉዕ ሆኖ የሥራ ሓላፊነቱ ጭምር በግልጽ ተዘጋጅቶ ቢጸድቅ፤ የማንም ተፅዕኖ ሳይኖርበት የሚመረጠው አባት እግዚአብሔር ያስቀመጠው ስለሚሆን ሊፈጠሩ ይችላሉ ብለን የምንሰጋቸው ክፍተቶች  ይቀንሳሉ፡፡ በዚህም በኩል የምእመናን ተሳትፎ የጎላ መሆን አለበት፡፡ ቃለ  ዐዋዲው በአጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባኤ ምእመናን ያላቸውን ቦታ ያመለክታል፡፡ ከሁሉም በላይ ምርጫው እስኪከናወን ድረስ ሱባኤ ገብተው ለእግዚአብሔር ጸሎት ማድረስ አለባቸው፡፡ እግዚአብሔር ምርጫውን ሙሉ በሙሉ ገብቶ እንዲያከናውነው፣ እንዲያስፈጽመው መደረግ አለበት፡፡

 

ቀጣዩ ተሿሚ ፓትርያርክም ቦታ መንፈሳዊ ልጆቹን  በሰላም፣ በፍቅር፣ በአንድነት የሚያስተሳስር፤ የቤተ ክርስቲያኒቱን ዶግማና ቀኖና በትክክል ጠብቆ ለትውልድ እንዲተላለፍ የሚያደርግ፣ ትምህርተ ወንጌልን የሚያስፋፋ፣ ስብከተ ወንጌልን የሚያጠናክር የቀደሙት የቤተ ክርስቲያን አባቶች ጀምረዋቸው የነበሩ ሥራዎች ማጠናከር በተለይም ገዳማትና የአብነት ትምህርት ቤቶች መርዳት ይጠበቅባቸዋል፡፡

 

በገጠር በካህን እጥረት ምክንያት ብዙ አብያተ ክርስቲ ያናት እየተዘጉ ነው፡፡ በአንጻሩ ደግሞ በከተማ አካባቢ በርካታ ካህናት ተከማችተው ይታያሉ፡፡ የገጠሯ ቤተ ክርስቲያን እንዳትዘጋ ትኩረት መስጠት ካህናቱ ማእከላዊ በሆነ አስተዳደር እንዲተዳደሩ ማድረግ፤ ተተኪው ትውልድ ወጣት ከመሆኑ አንጻር ጊዜውን፣ ጉልበቱን፣ ሕይወቱን ሰጥቶ ቤተ ክርስቲያን ላገልግል የሚለውን በመምራት፣ መንገድ ማሳየት ይጠቅቸዋል፡፡ ለቤተ ክርስቲያን የውስጥ ጠላት የሆኑ መናፍቃን፣ ተሐድሶዎች  ቀዳዳ፣ ክፍተት ፈልገው የበግ ለምድ ለብሰው ቤተ ክርስቲያን በመግባት ሃይማኖቷን፣ ዶጋማዋን እንዳይቆነጻጽሉ ሥርዐቷን እንዳያፈርሱ መጠበቅ ያስፈልጋል፡፡

 

ዘመኑን በተከተለ የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር እንዲኖራት ትኩረት ሰጥቶ የገንዘብና የንብረት አስተዳደሯን በአግባቡ በሕግና በሥርዐት የሚመራ ባለሙያዎችን በየደረጃው ማስቀመጥ ይኖርባቸዋል፡፡ በአጠቃላይ ከላይ የተጠቀሱትንና ቤተ ክርስቲያኒቱንና አሁን የጀመረቻቸውን መልካም እሴቶች የሚያበረታታ፤ ካህናቱ ከምእመናኑ ጋር ያላቸው ውሕደትና ጥምረት አጣጥሞ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደ 21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የማሻገር ሓላፊነት ከአዲሱ ቅዱስ ፓትርያርክ የሚጠበቁ ናቸው ብዬ አምናለሁ፡፡

 

  • “ኦርቶዶክስ ተዋሕዶን በገጠር የሚያስፋፋት አባት እንጠብቃለን”

ቀሲስ ታምራት

ከጎሬ

kesis tamerateየፓትርያርክ ምርጫ ቤተ ክርስቲያናችን በመንፈስ ቅዱስ ስለምትመራ ነገሮቹን ሁሉ ለመንፈስ ቅዱስ አሳልፎ መስጠት ያስፈልጋል፡፡ ያ ማለት ደግሞ ከካህናት አባቶች፣ ከእያንዳንዳዱ ክርስቲያን፣ ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ከሰባክያን ብሎም ከሲኖዶስ ምርጫው የተሳካ ይሆን ዘንድ በጸሎት ድጋፍ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡

 

በዚህ ዘመን ለቤተ ክርስቲያን የሚበጃት ዓለሙን ሊዋጅ የሚችል ታሪኳን፣ ትውፊቷን፣ ሃይማኖቷን  ጠብቆ ለሚቀጥለው ትውልድ ማስተላለፍ የሚችል አባት እንዲመረጥ እያንዳንዱ ሰው ገንቢ ያልሆነ አስተያየት ከመስጠትና ከዘረኝነት ነጻ ሆኖ እግዚአብሔርን ብቻ አስቦ ምርጫው በተስፋ ሊጠብቅ ይገባል፡፡

 

አሁን የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን የሚመሩ አባት ፓትርያርክ እንደሚታወቀው ከፊት ለፊታችንጠ እግዚአብሔር ቢፈቅድ ይመረጣል፡፡ የሚመረጡት አባት ደግሞ ምን ማድረግ አለባቸው) ከሚመረጡት አባት ምን ይጠበቃል) የሚለውን ጉዳይ  እኔ በሁለት መልኩ ነው የማየው፡፡ የመጀመሪያው በሞት ያለፉት ቅዱስነታቸው ጀምረዋቸው ያሉ መልካም እሴቶች አሉ፡፡ ከእነዚህም አንዱ ቤተ ክርስቲያናችንን በዓለም ደረጃ ዕውቅና እንድታገኝ አድርገዋታል፡፡ የሚመረጡት ፓትርያርክ ይህንኑ ተግባር ለዓለም የማሳወቅ፣ የማስቀጠል ሥራ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ሁለተኛው ቤተ ክርስቲያኒቱ ባሳለፈችው ሁለት ሺሕ  ዓመታት ውስጥ ሐዋርያዊ ተልእኮዋ ስንመለከት እንደ ዕድ ሜዋ የሚያረካ አገልግሎት ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍል ያደረሰ አይደለም፡፡ ያም ከተለያዩ ምክንያቶች  የተነሣ ሊሆን ይችላል፡፡ ስለዚህ አሁን ተመራጩ ፓትርያርክ ይህንን ክፍተት ለመሙላት እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ የሚችሉትን ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡

 

በገጠር አካባቢ የሚገኙ ምእመናን የተጠናከረ አገልግሎት አላገኙም፡፡ የገጠሯ ቤተ ክርስቲያንም ተዘግታ ያለችበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በሰፊው እየተካሔደ ያለው በከተማ አካባቢ በመሆኑ፤ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የከተማ ሃይማኖት እየሆነች አገልግሎቷ በከተማ ብቻ እንዲወስን የሚያደርጋት አጋጣሚ እየመጣ ነው፡፡ እኛ ከተማ ከተማውን  እየሠራን ሌሎች ቤተ እምነቶች ደግሞ ገጠር ገጠሩን እየሠሩ ቤተ ክርስቲያናችን ከተማ ላይ እየቀረች ገጠሩን ለሌሎች አሳልፈን እየሰጠን ነው፡፡

 

ስለዚህ ቅዱስ ሲኖዶስ አሁን የሚመረጡት አባት የቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ መዋቅር አስተካክለው ቤተ ክርስቲያን ያላትን የገንዘብም ሆነ የሰው ሀብት ልማት በትክክል በሥራ ላይ ማዋል፤ አገልግሎቷም በገጠር እንዲስፋፋ የሚያደርጉ አባት ቢሆኑና ሲኖዶሱም ሕገ ደንቡን አክብሮ የሚመራ መሆን አለበት፡፡ ይህን የሚያደርግ አባት እግዚአብሔር እንደሚሰጠን አምናለሁ፡፡

 

  • “ጥሩ አሠራር የሚዘረጋ አባት ያስፈልገናል”

ኅብስተ ኪዳነ ማርያም

ከደሴ

hebesta kidanemaryameቅዱስ አባታችን በማረፋቸው ምክንያት ቅዱስ ሲኖዶስ ፓትርያርክ ለመምረጥ በዝግጅት ላይ መሆኑ ይታወቃል፡፡ በዚህ ሂደት ምእመናንና ካህናቱን የሚያስተዳድር አባት እግዚአብሔር እንዲሰጠን መጸለይ አለብን፡፡

 

በፓትርያርክ ምርጫ ላይ ወገንተኛ መሆን ተገቢ አይደለም፡፡ ምእመናን፣ ወጣቶችም አንዱን ወገን መደገፍ ሳይሆን ለቤተ ክርስቲያን የትኛው ይጠቅማል የሚለውን ማሰብ አለብን፡፡ ስለዚህ ችግሮችን የሚፈቱ ጥሩ አሠራር የሚዘረጉ አባት እንዲመረጡ እግዚአብሔርን በጸሎት እንጠይቃለን፡፡

 

ስለ ግብፅ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የተጻፉ መጻሕፍትን ስናነብ ግብፃውያን  አባቶችና ምእመናኑ ያላቸው ግንኙነት፣ አባቶች ያላቸው ትጋት፣ ምእመናኑ እንዴት እንደሚጠብቁትና እንደሚንከባከቡት  ስናነብ በጣም ያስቀናል፡፡ እኛስ መቼ ነው እንደዚህ የምንሆነው የሚል ቁጭት በውስጤ አለ፡፡ የእኛም አባቶች ለወጣቱ ትውልድ ቤተ ክርስቲያን በደንብ የማሳወቅ፣ አባቶችና የንስሐ ልጆች ግንኙነት እንዲጠናከር፣ በቤተ ክርስቲያኒቱ ያለው አሠራር ግልጽ እንዲሆን ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡ የሚመረጠው ፓትርያርክ ከላይ እስከታች አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ድረስ ያለው ምእመናን ቤተ ክርስቲያን በቂ አገልግሎት እንዲያገኝ ምእመኑም በመንፈሳዊ ሕይወቱ አዲስ አሠራር መዘርጋት አለባቸው፡፡ ይህን ያህል ፐርሰንት አስገብተዋል፣ ይህን ያህል አማኞች አሉ የሚለው የቁጥር ሪፖርት በቂ አይደለም፡፡ በእውነት የተመዘገቡ ቤተ ክርስቲያን የምታውቃቸው ምእመናን፣ አስተዋጽኦቸው በአግባቡ እያበረከቱ ያሉ ምን ያህል ክርስቲያኖች አሉ? ስንቶችን ካለማመን ወደ ማመን አምጥተናል? የሚሉ ጉዳዮች ትኩረት ሊሰጥባቸው የሚገቡ ናቸው፡፡

 

ከዚህም በተጨማሪ ቅዱስ ሲኖዶስ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን ማጠናከር፣ ሰበካ ጉባኤ በልማት እንዲሳተፉ፣ ትምህርት ቤቶች፣ አጸደ ሕፃናት እንዲስፋፋ ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡ በአንዳንድ ቦታዎች አብነት ትምህርት ቤቶች እየተዘጉ፤ መምህራኑ ጉባኤያቱን እያጠፉ ወደ ከተማ እየተሰደዱ ነው፡፡ ይህን በደንብ አጥንቶ ሊሟሉ የሚገባቸውን ነገሮች በማሟላት ጉባኤያቱ እንዳይፈቱ ማድረግ ከተመራጩ ፓትርያርክና ከቅዱስ ሲኖዶስ የሚጠበቅ ተግባር ነው፡፡

  • ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት 20ኛ ዓመት ቁጥር 5 መሰከረም 2005 ዓ.ም.