መንክር ስብሐተ ልደቱ፤ የመወለዱ ምሥጢር ድንቅ ነው

{gallery count=1 width=350 height=300 counter=1 links=0 alignment=center animation=3000}ledete2004{/gallery}

«እግዚአብሔር የሠራት ቀን ይህች ናት፤ ሐሴትን እናድርግ፤ በእርስዋም ደስ ይበለን፡፡» መዝ. 117·24 ይህች ዕለት ዕለተ ኃይል፣ ዕለተ አድኅኖ፣ ዕለተ ብሥራት፣ ዕለተ ቅዳሴ፣ ዕለተ ልደት፣ ዕለተ አስተርዕዮ ናትና ዓለም ሳይፈጠር አስቀድሞ ከአብ ባሕርይ ዘእምባሕርይ፣ አካል ዘእምአካል፣ የተወለደ ወልድ ዋሕድ ኋላም ከድንግል አካል ዘእምአካል ባሕርይ ዘእምባሕርይ በዚህች ዕለት በኅቱም ድንግልና ተወልዷልና ዕለተ ኃይል ትባላለች፡፡ መላእክት በጎል ተጥሎ፣ በጨርቅ ተጠቅልሎ አይተው ስብሐት ለእግዚአብሔር ብለው አመስግነውበታልና ዕለተ ቅዳሴ፣ መድኅነ ዓለም ክርስቶስ ዓለምን ለማዳን በጎል ተገኝቶበታልና ዕለተ አድኅኖ፣ ቅዱስ ገብርኤል እነሆ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ ብሎ ተናግሯባታልና ዕለተ ብሥራት ትባላለች፡፡ «እግዚአብሔርም አለኝ አንተ ልጄ ነህ እኔም ዛሬ ወለድሁህ» መዝ 2·7 በተዋሕዶ፣ በቃል ርስትነት ተብሎ የተነገረለት ቀድሞ ብቻውን እግዚአብሔር ከብቻው እግዚአብሔር እንደተወለደ፣ በኋለኛውም ዘመን ብቻውን የሚሆን የእግዚአብሔር ልጅ ብቻዋን ከምትሆን ከዳዊት ልጅ ተወለደ፡፡

በመጀመሪያ የማይታይ እሱ ከማይታየው ተወለደ፤ በኋላም የማይያዝ የሕይወት እስትንፋስ ከምትዳሰስ ሥጋ ተወለደ፡፡
በመጀመያ የአኗኗሩ መጀመሪያ ሳይታወቅ ተወለደ፤ በኋላም የዘመናት ፈጣሪ ዓመታትን የሚወስን እርሱ ዕድሜዋ ዐሥራ አምስት ከሆነ ከታናሽ ብላቴና ተወለደ፡፡
የመጀመሪያ ልደቱን ምሥጢር፣ የኋለኛ ልደቱንም ድንቅ በማድረግ ተወለደ፡፡
በቅድምና የነበረው የአብ አካላዊ ቃሉ በምልዓት ሳለ ተፀነሰ፤ በጌትነቱ በጽርሐ አርያም ሳለ ሰው ሆነ፤ ማኅተመ ድንግልናን ሳይለውጥ የእኛን ባሕርይ ተዋሕዶ ተወለደ፡፡
የሰውን ልጅ በጥንተ ተፈጥሮ የፈጠረ የእግዚአብሔር አብ ልጅ እግዚአብሔር ወልድ አሁን ደግሞ በሐዲስ ተፈጥሮ ለመፍጠር ሰው ሆኖ ተወለደ፡፡ «ሰው ሆይ አስተውል እሱን አስመስሎ ይወልድህ ዘንድ አንተን መስሎ ተወለደ ስለዚህ ነገር ቅዱስ ጳውሎስ መላእክትን የተቀበለ አይደለም፤ የአብርሃምን ዘር ከፍ ከፍ አደረገ እንጂ» እንዳለ ዕብ 2·16 የሰውን ልጅ ክብር ወደ ቀደመ ማንነቱ ለመመለስ እንዲህ ባለ ድንቅ ልደት ዛሬ ተወልዷልና ዕለተ ልደት ትባላለች፡፡
«በሀገራቸው ትንቢት የተነገረላቸው በዕብራይስጥ ልሳንም የተጻፈላቸው እስራኤል ምንም ባያውቁህ ከዓለም አስቀድሞ የልዑል እግዚአብሔር ልጅ እንደሆንህ ደግሞ ከዳዊት ዘር ከምትሆን ቅድስት ድንግል ተወልደህ የሰው ልጅ መባልህን አወቅሁ» ማቴ 16·13-18
ትንቢቱስ ምን ነበር እግዚአብሔር፤ አዳምን ከአራቱ ባሕርያት ፈጥሮ ከእንስሳት ከአራዊት ለይቶ በነባቢት ነፍስ አክብሮ ልጅነትን ሰጥቶ ሥራ ሠርቶ ሊጠቀምበት መንፈሳዊ ዕውቀትን አድሎ በአርአያው በአምሳሉ የፈጠረው ነውና የባሕርዩን በጸጋ ሰጥቶ የሁሉ ገዥ አድርጎ በገነት ሹሞ አኖረው፡፡ ነገር ግን የገዥና የተገዥ ምልክት የምትሆን ዕፀ በለስን እንዳይበላ አዘዘው፡፡ ይኸውም የንፍገት አይደለም፤ ከሹመቱ እንዳይሻር፣ ከልዕልናው እንዳይዋረድ፣ ከልጅነት እንዳይወጣ፣ ክብርን እንዳያጣ ነው እንጂ፡፡ ሆኖም ግን የራሱን ክብር ልዕልና በራሱ ያጣ ዲያብሎስ በአዳም ክብርና ልዕልና ቀና፡፡ በሥጋ ከይሲ ተሠውሮ በሽንገላ መጣ፡፡ ክፋትን በተመላ ደስ የሚያሰኝ በሚመስል አነጋገር የሞት ሞት የምትሞቱ አይምሰላችሁ የዕፀ በለስ ፍሬ ብትበሉ የአምላክነት ዕውቀት ይሰጣችኋል፡፡ ክፉውንም ደጉንም ታውቃላችሁ፤ አሁን ካላችሁበት ክብርና መዓርግ ከፍ ትላላችሁ በማለት አታለላቸው፡፡ እነርሱም እውነት መሰላቸው፡፡ ከፈጣሪያቸው ትእዛዝ ወጡ፡፡ ራሳቸውን አጥፊ ሆኑ፤ የቀደመ ማንነታቸውን አጥተው ኃሣር፣ መርገም፣ ድንጋፄ፣ ረዓድ ወደሚበዛበት፣ ክፉና መልካም ወደሚሠራበት፣ ቢያገኙት ቁንጣን፣ ቢያጡት ቀጠና ወደ ሆነበት ዓለም ወረዱ፡፡ ቢሆንም ግን አዳም በፍታዊነቱ አንጻር መሐሪነቱን ተረድቶ በደሉን በማመን አዘነ፤ አለቀሰ፤ በልብ መታሰቡ በቃል መነገሩ ከፍ ከፍ ይበልና ጸዋትወ መከራውን አይቶ አዘነለት፡፡ የሚድንበትን ተስፋ ትንቢት ሰጠው፡፡ አምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ ብሎ ከዚህም አያይዞ ከልጅ ልጁ ተወልዶ የሚያድነው ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል መሆኑን፣ እርሱን ለማዳን ስሙን ባሕርዩን ገንዘብ የሚያደርገው ወልድ ኢሳ 9·6 መሆኑንም ጨምሮ ነግሮታል፡፡ ዘፍ 3·22 ይህ የሚፈጸምበትን ቀጠሮም አስረድቶታል፡፡ ገላ 4·4 ከዚያ ቀጥሎ በየጊዜው ለተነሡ ልጆቹ ትንቢቱን በማስነገር፣ ምሳሌውን በማስመሰል፣ እስከ ጊዜው ደርሷል፡፡ ለዚህም ነው በዘመነ አበው የምድር አሕዛብ ሁሉም በዘርህ ይባረካሉ ተብሎ የሃይማኖት መሠረት ለሆነው ለአብርሃም የተነገረው ዘፍ 22·18
በዘመነ መሳፍንትም አምላክህ እግዚአብሔር ከአንተ መካከል ከወንድሞችህ እንደኔ ያለ ነቢይ ያስነሣልሃል፤ እርሱንም ታደምጣለህ ተብሎ በሙሴ ለእስራኤል ሕዝብ በሙሉ አዋጅ ታውጇል፡፡ ዘዳግ 18·15
በዘመነ ነገሥት ከሆድህ ፍሬ በዙፋንህ ላይ አስቀምጣለሁ ብሎ ለዳዊት የገባው ልዩ ቃል ኪዳን አለ፡፡
ስለዚህ እወቅ አስተውልም ኢየሩሳሌምን መጠገንና መሥራት ትእዛዙ ከሚወጣበት ጀምሮ እስከ አለቃው እስከ መሢሕ ድረስ ተብሎ በነቢዩ ዳንኤል 9·25 ተነግሯል፡፡
ያዕቆብም በምርቃት የገለጸው ልጆቹን ለእያንዳንዳቸው እንደሚገባቸው የጸጋ ሀብት በረከታቸውን ባሳየ ጊዜ የይሁዳን መንግሥት ከይሁዳ አይጠፋም፤ ግዛትም ከወገኑ ገዥ የሆነው እስኪመጣ ድረስ እርሱም የአሕዛብ ተስፋቸው ነው፡፡ ዘፍ 49·10 ከይሁዳ ወደ ዳዊት እየቀረበ ሲመጣም እርሱም አባቴ አንተ ነህ ይለኛል እኔም በኩር አደርገዋለሁ፡፡ መዝ 88·20 1ሳሙ 16·1-13 በማለት ሥጋ (አካለ) ዳዊትን በተለየ መልኩ እንደመረጠው ፈጣሪው ሲሆን ልጁ ለመባል እንደወደደ እየገለጠው እያቀረበው መጣና ወደ ልጁ አለፈ፡፡
ዳዊትንም ልጁን ለዚህ ታላቅ ምሥጢር እንዲያዘጋጅ በትንቢት አነሣሣው፡፡ እርሱም ልጁን እንዲህ አላት፤ «ልጄ ሆይ የምልሽን ስሚ፤ እይ፤ ጆሮሽንም ወደ ምሥጢሩ ቃል አዘንብይ፤ ወገንሽን ያባትሽንም ቤት እርሺ፤ ያለምንም የልብ መከፈል ራስሽን ለርሱ ስጪ፤ ንጉሥ ውበትሽን ይኸውም ንጽሕናሽን፣ መዓዛሽን፣ ቅድስናሽን ወዷልና፡፡ እርሱ ሌላ አይደለም፤ ለታላቁ ምሥጢር የመረጠሽ ጌታሽ ነውና፡፡» መዝ 44·10-12 አላት፡፡ ደስ በሚያሰኝ የተስፋ ቃል ትንቢቱን ተናገረ፡፡ እርሱም ይሁንልኝ ብላ የአባቷን ምክር ተቀብላ የአምላክ እናት ለመሆን በቃች፤ ትንቢቱም ደርሶ የገባውን ቃል ኪዳን ይፈጽም ዘንድ ወደደ፡፡
ደም ግባቷን በወደደ ጊዜም በጽርሐ አርያም እናት ትሆነው ዘንድ ወደ ሰማይ አላሳረጋትም፤ እርሱ ራሱ ወደእርሷ ወረደ እንጂ፡፡ በዚያ ትፀንሰው ዘንድ በኪሩቤል ሠረገላ ላይ አላስቀምጣትም፤ ናዝሬት በተባለች በገሊላ ሀገር ሳለች እርሱ ራሱ በማሕፀኗ አደረ እንጂ፡፡ ገብርኤልንም ዘጠኝ ወር በማሕፀኗ እንድትሸከመኝ ወደዚህ አምጣት አላለም፤ እርሱ ራሱ ትሕትናዋን ተሳተፈ እንጂ፡፡ ይልቁንም መልክተኛውን በትንቢት ወደ መረጣት የዳዊት ልጅ ላከ፡፡ እርሱም ደስ ያለሽ ሆይ ደስ ይበልሽ፤ እግዚአብሔር ካንቺ ጋር ነው፤ እነሆ ኢሳይያስ ድንግል በድንግልና ፀንሳ በድንግልና ትወልዳለች እንዳለ ትፀንሻለሽ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፤ ስሙንም አማኑኤል ትይዋለሽ፤ ትርጓሜውም እግዚአብሔር ከሥጋችን ሥጋን፣ ከነፍሳችን ነፍስ ነስቶ አንድ አካል አንድ ባሕርይ ሆነ፤ በተዋሕዶ አንድ አካል አንድ ባሕርይ የሆነውም ኢየሱስ ተባለ፤ ትርጓሜውም ወገኖቹን የሚያድናቸው ማለት ነው፡፡ ይህ እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውሃ ፈሳሽ የሆነ ሳይሆን ከጥንቱ ሲነገር ሲያያዝ የመጣ ነው አላት፡፡ እርሷም እንዲህ ያለ ሰላምታ እንደምን ይቀበሏል አለች፡፡ በትሕትና መልአኩም በእግዚአብሔር ዘንድ የእናትነት ባለሟልነትን አግኝተሻልና ደስ ይበልሽ፤ የምትወልጅውም የልዑል እግዚአብሔር አብ የባሕርይ ልጅ ይባላል፤ እግዚአብሔር የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል፤ በያዕቆብ ወገን ለዘለዓለም ነግሦ ይኖራል፡፡ ለጌትነቱ ፍጻሜ የለውም አላት፡፡ ነገሩስ መልካም ነበር፤ ነገር ግን ወንድ ሳላውቅ መፅነስ መውለድ እንደምን ይሆንልኛል? በውኑ ምድር ያለ ዘር ታፈራ ዘንድ ሴት ያለወንድ ትፀንስ ዘንድ ይቻላልን? ሴት ያለ ወንድ ዘር መውለድ ከዚህ በፊት አልሆነምና አለችው፡፡
እውነት ነው ከዚህ በኋላም አይሆንም ነገር ግን ያንች ፅንስ እንደ ሌሎች ፅንስ አይደለም፤ መንፈስ ቅዱስ ያድርብሻል፤ ኃይለ ልዑል ወልድ ሥጋሽን ይዋሓዳል፤ ለሱ የሚሳነው ነገር የለም፤ ሁሉን ማድረግ ይቻለዋል አላት፤ እርሷም ጊዜ በፍጹም እምነት ቃለ ብሥራቱን ተቀብላ አቤቱ እነሆ እኔ የእግዚአብሔር አገልጋዩ ነኝ እንደ ቃልህ ይደረግልኝ ባለች ጊዜ ፈቃዷን ምክንያት አድርጎ የዓለሙ ሁሉ መድኃኒት የሚሆን ዋሕድ ቃለ እግዚአብሔር በማሕፀኗ ተቀርፆ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን የማይወስነው በማሕፀኗ ተወስኖ ሊወለድ የማይቻለው ተወለደ፡፡ በሰው ዘር ያልሆነ ነገር ግን እንደ ሰው የሆነውን ልደቱን እናምናለን፡፡
አምላክ ሲሆን መወለዱን፣ ወደዚህ ዓለም መምጣቱን፣ ከረቂቃን የረቀቀ ድንቅ ነው ከድንግል መወለዱ ፍጹም ሰው ቢሆንም ያለ ዘር በኅቱም ድንግልና ተጸንሶ በኅቱም ድንግልና መወለዱ ግን የመንፈስ ቅዱስ ሥራ በመሆኑ ፍጹም አምላክ መሆኑን ያመለክታል፡፡ ይህ ልደት እጅግ አስደናቂ ልደት ነው፡፡ በኅቱም ድንግልና ተፀንሶ በኅቱም ድንግልና መወለድ ለዘለዓለም አዲስ ሥራ ቢሆንም በድንግልና መጸነሱም ሆነ መወለዱ በእርሱ ለእርሱ ብቻ እንጂ በማንም ሥልጣን ለማንም እስካልሆነ ድረስ ከማድነቅ ውጪ እንዴት ሊሆን ቻለ ማለት አይገባም፡፡ ይልቁንም ልደቱን በመመራመር ማወቅ አይቻልም በማመን እንጂ፤ እነዚህም ሁለት ልደታት ናቸው፡፡
1. ከዘመናት በፊት ዓለማት ሳይፈጠሩ ከእግዚአብሔር አብ ያለ እናት አካል ዘእምአካል ባሕርይ ዘእምባሕርይ የተወለደው፡፡ መዝ 10·3 ይህ የመጀመሪያው ልደት ሲሆን፤
2. በኋላኛው ዘመን ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ያለ አባት አካል ዘእምአካል ባሕርይ ዘእምባሕርይ በድንግልና የተወለደው ሁለተኛ ልደት ነው፡፡ ኢሳ 7·19 9·6 ማቴ 1·22-23 2·1 ገላ 4·4 ይህን ድንቅ ምሥጢር ሊቁ እንዲህ በማለት ይገልጠዋል፤ «አቤቱ ሆይ በአኗኗርህ የአብ ልጅ፣ በሰውነትህ የድንግል ልጅ፣ በመለኮትህ የአብ ልጅ፣ በትስብእትህ የሰው ልጅ፣ ለወለደህና ለወለደችህ አንድ ልጅ እንደሆንህ አመንሁብህ፡፡ አቤቱ ጌታዬ የላይኛው ቀዳማዊ ልደት ሌላ፣ የታችኛው ሁለተኛው ልደት ሌላ፣ ሰማያዊ ልደት ሌላ፣ ምድራዊ ልደት ሌላ፣ የልዕልና ልደት ሌላ፣ የትሕትና ልደትህ ሌላ፣ የፊተኛው ልደትህ ከሕይወት እሳት የተገኘ የሕይወት እሳት፣ የኋለኛው ልደት ከሴት የተወለደ አካላዊ ቃል የፊተኛውን ፈለግሁት አላገኘሁትም፤ የኋለኛውን አሰብሁት አደነቅሁት፤ የፊተኛውን ሳልደርስበት አመሰገንሁት፤ የኋለኛውን በአብራከ ልቡናዬ ሰግጄ እጅ ነሣሁት፡፡ የፊተኛው ልደት በኋለኛው ልደት ታወቀ ተረዳ፡፡ የመለኮት ወገን በድንግል ወገን ተመሰገነ፡፡ ከድንግል ከተወለድህ ወዲህ ከአብ የመወለድህ ሃይማኖት ተገልጸልን፤ ከድንግል መወለድህን በሚናገር ትንቢት ከአብ መወለድ ተረዳ፡፡ ስለዚህ ባለመጠራጠር አመንሁ» ይላል አባ ጊዮርጊስ፡፡
ምን ጊዜም የልደቱ ነገር ድንቅ ምሥጢር ነው፤ ቅዱስ ኤፍሬም እንደሚለው ሰው የሆነ እርሱን አምላክ እንደሆነ በተረዳ ነገር አውቀነዋልና ልዩ ከሆነች ድንግል ማርያም ይህ የአምላክ መወለድ ምን ይረቅ ረቂቅ ነው፤ ድንቅ ነው፡፡ ቃልን ወሰነችው፤ ልደቱንም ዘር አልቀደመውም፡፡ በመወለዱም ድንግልናዋን አለወጠም፤ ቃል ከአብ ያለ ድካም ወጣ፤ ከድንግልም ያለ ሕመም ተወለደ፡፡ ለዮሴፍ የታየው መልአክም ከእርሷ በመንፈስ ቅዱስ የሚወለደው ያለመለወጥ ሰው የሚሆነው የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ ይኸውም ከባሕርያችን እርግማንን የሚያጠፋልን ያለወንድ ዘር የተወለደልን፣ አዳም ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ የተባለውም እነሆ ዛሬ ከቅድስት ድንግል ነፍስን ሥጋን ነሥቶ በተዋሕዶ በተገለጠ ጊዜ ተፈጸመ፡፡
አብርሃም ቀኔን ያይ ዘንድ ተመኘ፤ ቀኔንም /ልደቴን/ አይቶ ተደሰተ ተብሎ የተተነበየለት ዕለተ ምሥጢር ዕለተ ልደት ይህች ናት፡፡ እኛም ያየናት የድኅነት መጀመሪያ የዕለታት በኩር እንደሆነች ተረድተን የምናከብራት ደስታችንን የምንገልጽባት ይህች ዕለት ዕለተ አስተርዕዮ ናት፤ የማይታየው የታየባት፣ የማይዳሰሰው የተዳሰሰበት፣ የማይያዘው የተያዘባት፣ የማይታወቀው የታወቀባት፣ በትንቢት መነፅር አበው ያዩት ረቂት ብርሃን በአካል የተገለጠባት የአብንም ወላዲነት የተረዳንባት ዕለት ናት፡፡ በዚያ በአባቱ ቀኝ ሳለ በዚህ ከእናቱ ዕቅፍ ውስጥ ታየ፣ በዚያ ተሸካሚዎቹ እሳታውያን የሚሆኑ አራቱ እንስሳ ናቸው፡፡ በዚህም የተሸከመችው የፀሠራ አምስት ዓመት ብላቴና ድንግል ማርያም ናት፡፡ በዚያ ያለ እናት፣ አባት አለው፤ በዚህም ያለ ምድራዊ አባት፣ እናት አለችው፡፡
በዚያ በጽርሐ አርያም የሚደነቅ ከማይመረመር ከማይታይ አብ የመወለድ ምስጋና አለው፤ በዚህም በቤተ ልሔም የሚደነቅ ከድንግል የመለወድ ምስጋና አለው፡፡
በዚያ ኪሩቤልና ሱራፌል ከግርማው የተነሣ ይንቀጠቀጣሉ፤ በዚህ ግን ድንግል አቀፈችው፡፡ ሰሎሜም አገለገለችው፡፡ በዚያ የእሳት ዙፋን አለ፤ በዚህም የድንጋይ በረት አለው፤ በዚያ የትጉሃን ሥፍራ በሰማያት ያለች ኢየሩሳሌም አለችው፤ በዚህም የእንስሳት ጠባቂዎች ማደሪያ በዓት አለችው፡፡ በዚያ ገብርኤል በፍርሃት ይቆማል፤ በዚህም በሐሤት የምሥራች ይናገራል፡፡
በዚያ የእሳት ወላፈን ከአዳራሹ ይወጣል፤ በዚህም አህያና ላህም በእስትንፋሳቸው አሟሟቁት፡፡
እነሆ ከሰማይ ትጉሃን ይልቅ የሰው ልጅ ከበረ፤ እግዚአብሔር ከድንግል ማርያም ተወልዷልና፡፡ አንዱ የመወለዱ ምሥጢርም ይህ ነው፤ የሰውን ልጅ ከወደቀበት አንሥቶ በክብር ሰገነት ላይ ለማኖር የሰው ልጅም በጥንተ ተፈጥሮ ካገኘው ክብር የዛሬው በአዲስ ተፈጥሮ የሚያገኘው ክብር በልጧልና፡፡ የፊቱ በአምሳል በመፈጠር የተገኘ ነው፤ የአሁኑ ግን በተዋሕዶ በመወለድ የሚገኝ ነውና፡፡ የፊተኛው ሥጋ በጸጋ ከብሮ የተገኘ ነበር፤ አሁን ግን ሥጋ የባሕርይ አምላክ ሆኖ የተገኘ ከብር ነውና፡፡ የፊቱ ያለ ባሕርይ (በጸጋ) መከበር ነበር፤ ዛሬም በራስ ባሕርይ መከበር ነውና፡፡
ከአቂበ ሕግ በመውጣት ከወረደበት በታች የወረደበት ውርደት የለም፤ ዛሬም በተዋሕዶ በተደረገው ምሥጢር ከከበረበት በላይ ክብር የለም፤ በልዑል ዙፋን እስከመቀመጥ ደርሷልና፡፡
ትናንት ያልነበረ ሰውነት ከዘመን በኋላ የተገኘ ሲሆን፣ መለኮትን በመዋሓድ ሁሉን ግዙ ተብሎ ጥንት በጸጋ ከተሰጠው ግዛት በላይ ግዛቱ ድንበር የማይመልሰው ዘመን የማይለውጠው ከምድር እስከ ሰማይ የመላ ግዛት ሆነለት፡፡ መለኮት ወደሱ የመጣበት አመጣጥ ድንቅ የወደደበት ፍቅር ልዩ፣ በባሕርይ መወለዱም ዕፁብ ነውና ይህም ልደቱ ያለ ዘር የተደረገ ነው፡፡ ስለምን ቢሉ ቀዳማዊ ልደቱ የሚገለጥበት ነውና አምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ከእመቤታችን ያለአባት ያለዘር መወለዱ ቅድመ ዓለም ያለእናት ለመወለዱ ምሥክር መታወቂያ ነውና፡፡ ለዚህም ነው የመጀመሪያው ልደት በሁለተኛው ልደት ታወቀ የሚባለው፡፡ የሁለተኛው ልደት ክብርና ምሥጢርም ከአእምሮ በላይ በመሆኑ በመጀመሪያ ልደት ታወቀ ተረዳ፡፡ ድንቅ የሚሆን ልደቱም በምድር ላይ አባት ስለሌለው ሰው የመሆን መንገድ የጐደለው አይደለም፤ ብቻዋን ከምትሆን ከድንግል ፍጹም ሰው ሆኖ ተወለደ እንጂ ከአዳም ጐን እናት ሳይኖራት ፍጽምት ሴት እንደወጣች ፍጹም ሰው ሆነ፡፡ ማቴ 2·1-12 ሉቃ 2·8-16
የአብ ልጅ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው በሆነ ጊዜ የሕፃናትን ጠባይ ሳያስቀር የሰውነትን የጠባይ ሥርዓት እየፈጸመ ከዕለተ ፅንሰ ጀምሮ እስከ ዕለተ ልደት ድረስ በየጥቂቱ በማሕፀነ ማርያም ውስጥ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ቆይቶ ሕፃናት ሲወለዱ የሚሰማቸው ሳይሰማው ተወለደ፡፡ ሲወለድም በግብረ መንፈስ ቅዱስ በድንግልና እንደተፀነሰ በድንግልና ተወለደ እንጂ እናቱንም የድንግልና መለወጥ፣ በወሊድ ጊዜ ጭንቅና ምጥ አላገኛትም፡፡ ሕዝ 34·1 የመውለዷ ክብር ገናንነትም ከአእምሮ በላይ ነው፤ ይህ ተብሎ ሊነገር አይችልም፤ ያለ ምጥ ወልዳዋለችና፡፡
የዲያብሎስና የተከታቹን ሥነ ልቡና የሰበረ በፍርሃት እንዲዋጡ ማንነታቸውን እንዲያጡ ያደረገው አስደናቂው ልደት ጌታ በቤተ ልሔም ሲወለድ ቤተ ልሔም በብርሃን ተከባ፣ በመላእክት ምስጋና ደምቃ፣ በምሥራች ተመልታ ባየ ጊዜ የሰው ልጅ ጠላት ዲያብሎስ ይህን የልደት ምሥጢር ለማወቅ ለመመራመር ወደ ላይ ወደ ዐየር ወጣ፤ ከመሬት በታች ወደ አለው አዘቅት ወረደ፤ ዓለምን በሙሉ ዞረ፤ ግን ሊያውቅ አልቻለም፡፡ ባለማወቅ ሠወራቸው ተብሎአልና መርምሮ ማወቅ ባይቻለው የፍርሃት ጥርጥር መጠራጠር ጀምረ እንዲህ በማለት፤ የኢሳይያስ ድንግል የድንግልና ልጇን ወለደች፤ ተአምረኛው ሙሴ ሲወለድ እንዲህ ያለ ችግር አልገጠመኝም ብዙ ክብር ያላቸው ነቢያት ተወልደዋል፤ እንደዚህ ማንነቴን የሚያሳጣ ከዕውቀቴ በላይ የሆነ ችግር አልገጠመኝም ነበር፡፡ ዛሬ ግን ዓለምን በሙሉ ዞርኳት፤ ይልቁንም ቤተ ልሔምን፡፡ ነገር ግን በእሷ የተደረገ የዚህን ልደት ምሥጢር ተመራምሬ ልደርስበት አልቻልኩም፡፡ ድካሜም ውጤት አልባ ሆኖአል ብሎ ወደ ወገኖቹ ቢመለስ በግምባራቸው ፍግም ብለው ወድቀው አገኛቸው፡፡ ለጊዜው እነሱን አይዟችሁ መንግሥቴ ከእኔ አታልፍም አላቸው፡፡ ከተደረገው ተአምራት ሁሉ በላይ ተአምር ቢደረግም አልፈራም ነበር፡፡ ትንቢቱ ቢደርስ ድንግል ልዑሉን ብትወልድ ይሆናል እንጂ እንዲህ ያለ ኃሣርና ውድቀት ያገኘን ምን አልባት ቤተ ልሔም አምላክ ተወልዶብሽ ይሆን ብሎ ተስፋ ባለመቁረጡ ተመልሶ ሄደ፡፡ መላእክት በአንድነት ሆነው በሰማይ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እነሆ በምድር ላይ ለሰው የሰላም መሠረት ተጥሏልና እያሉ ሲያመሰግኑ፣ ደግሞ መልአኩ ለእረኞች እነሆ ለእናንተ ደስታ የሚሆን ምሥራች እነግራችኋለሁ፡፡ የዓለም መድኃኒት የሚሆን ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በዳዊት ባሕርይ በዳዊት ሀገር ተወልዷልና፤ ምልክቱም አንዲት ድንግል ልጅ ሕፃኑን በክንዷ ታቅፋ ታገኛለችሁ ሲል ሰምቶ በሐዘን ላይ ሐዘን ተጨመረበት፡፡ ቢሆንም ግን እርግጡን ለማወቅ የልደት ዘመን መቼ እንደሆነ ለመረዳት የነቢያትን መጻሕፍት ትርጓሜ ወደሚያውቁ ወደ አይሁድ ሊቃውንት ዘንድ ፈጥኖ ሄዶ ስለ ክርስቶስ መወለድ አንሥቶ ያስረዱት ዘንድ አጥብቆ ጠየቃቸው፡፡ የጠየቃቸውን እንደማይሸሸጉት ተስፋ አድርጓልና እነሱም በይሁዳ አውራጃ በምትገኝ በቤተ ልሔም የዓለም መድኃኒት ይወለዳል ብለው ተናግረዋል ብለው መለሱለት፡፡ ሚክ 5·2 የዳንኤል ሱባዔስ ደርሷል? አላቸው፡፡ «አዎ» አሉት፡፡ «ይህ ሁሉ እንደደረሰ በምን አውቃለው?» አላቸው፡፡ የልደቱ መታወቂያ የጊዜው መድረስ የሚታወቅበት ከልደቱ ጋር ቀጠሮ ያለው ልደቱን የሚጠባበቅ ስምዖን የሚባል አለ፡፡ እሱን ጠይቀህ ተረዳ አሉት፡፡ ስምዖን ለልደቱ ምልክት የሆነበት ምክንያት ምንድ ነው? አላቸው፡፡ ለንጉሡ በጥሊሞስ መጻሕፍት ከእብራይስጥ ወደ ፅርዕ ሲተረጉም ኢሳይያስ እነሆ ድንግል በድንግልና ፀንሳ በድንግልና ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ትለዋለች ባለው የትንቢት ቃል በተሰነካከለ ጊዜ የእግዚአብሔርም መልአክ ሕፃኑን ሳታይ አትሞትም ብሎታልና ሉቃ 2·26 አሉት፡፡ ሒዶ አንተ የተባረክህ ሽማግሌ ተስፋ የምታደርገው መድኅን ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም መምጫው ደርሷልን? አለው፡፡ አዎ መጥቷል፤ አለው፡፡ በምን አወቅህ? አለው፡፡ በኢሳይያስ ትንቢት በተሰነካከልኩ ጊዜ በሕማም ታሥሮ የነበረው እጄ ተፈትቷልና በዚህ አወቅሁ አለው፡፡ በመልክተኞቹ ይህን ከሰማ በኋላ እውነትም ዛሬ ገና የእኔ ክብር የሚዋረድበት፤ ያዋረድሁት አዳም ከእኔ ባርነት ነጻ የሚወጣበት ቀን ደርሰ አለ፡፡ የአዳም ልጅ ሆይ ጠላት ዲያብሎስ ላይጠቅመው ላይረባው ይህን ያህል ስለ ልደቱ ምሥጢር ለማወቅ አቀበቱን ከወጣ ቁልቁለቱን ከወረደ፣ ዓለምን በመዞር ከተንከራተተ፣ አንተማ ምን ያህል ልትደክም አይገባህ? የማንነትህ ህልውና ነውና የልደቱን ነገር ልታውቅ ይገባሀል፡፡ ግን በምርምር አይደለም፤ እንደ እረኞች በእምነት ነው እንጂ፡፡ እረኞች በምርምር ሳይሆን በምልክት ተረድተው ልደቱን አወቁ፤ አገኙትም፡፡ አንተም ከመጻሕፍት አንብበህ ከመምህራን ተረድተህ የእረኞች ምሥራች የእኔ ነው ብለህ ነው እንጂ በልደት የሠለጠነ አምላክ በጎል ተጥሎ፣ በጨርቅ ተጠቅልሎ፣ በግርግም ተኝቶ አይቶ ዲያብሎስ ፈራ፡፡ አዳም ግን የልዑልን ትሕትና አይቶ ኦ ወዮ ለዚህ ምሥጢራዊ ልደት አንክሮ ይገባል፤ መርምረው ሊያውቁት አይቻልምና፡፡ አምላኬ ለእኔ ሲል የተወለደው ይህ ልደት ብቸኛ ነው ብሎ አመሰገነ፡፡ ብቸኛ ያሰኘውም በዚህ ዓለም እናት አባት አንድ ካልሆኑ ልጅ አይወለድም፤ እሱ ግን ከአባት ያለ እናት ከእናት ያለ አባት ተወልዷልና፤ የዚህ ዓለም ልጅ በዘር በሩካቤ ይወለዳል፤ እሱ ግን ያለ ዘር ያለ ሩካቤ ተወልዷልና፡፡
የዚህ ዓለም ልጅ ልጅ ተብሎ ኑሮ የወለደ ጊዜ አባት ይባላል፤ እሱ ግን ለዘለዓለም ወልድ እየተባለ ይኖራልና፡፡
ይህች ዕለት ለፍጡራን የሚሆን ሁሉ ዕረፍት የሚሆን ወልድ ሰውነቱን በልደት የገለጠበት ዕለት ስለሆነች ፍጡራን ሁሉ መልካም ዜና ሰሙ፤ ደስም አላቸው፡፡ ደስታቸውንም ገለጡ፡፡ ሊቁ እንዳለው ሰው በመሆንህ ሥጋን በመዋሓድህ ወደዚህ ዓለም በመምጣትህ ፍጥረት ሁሉ ደስ አላቸው እንዳለ፡፡
መላእክት ባጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ በድንግል እቅፍ አይተው ወሰላም በምድር ሥምረቱ ለሰብእ አሉ፡፡
ሰዎችም የፍጥረት ባለቤት እነሱን ለማዳን ልዑል ሲሆን በራሳቸው ባሕርይ በትሕትና ተወልዶ አይተው ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት አሉ፤ እንሰሳት አራዊት ለሰው በተደረገው ይቅርታና ክብር እስትንፋሳቸውን አምኀ አቀረቡ፡፡ ስሙን እየጠሩ ለዓለም መሰከሩ፡፡ ለምሳሌ ያህል ሚዳቋን ብንወስድ እንኳ ዮም ተወልደ መድኅነ ዓለም፤ ዮም ተወልደ ከሣቴ ብርሃን፤ ዮም ተወልደ ቤዛ ኵሉ ዓለም የዓለም መድኃኒት ዛሬ ተወለደ እያለች ስትዘምር ታይታለች፡፡ አስተዋይ አዕምሮ ካለ ይህ ድንቅ ምሥጢር ነው
ፊተኛ ልደቱ ፍጡራን የማያውቁት፣ በምሥጢር መሠወሪያ የተሠወረ ነው፡፡ ኋለኛ ልደቱ ግን ለእረኞች ተገለጠ፡፡ ለጥበብ ሰዎችም ታየ፡፡ በዓለምም ተሰማ፡፡ ልጄ ወንድሜ ሆይ ቃል /ወልድ/ በምድራችን ተሰማ፤ መታየቱም የታመነ ሆነ፡፡ በአባቱ መልክ /በአምላክነት ባሕርይ/ ተመላለሰ እንዳለ፡፡ መኃ 2·12-13 ጌትነቱን ለሚያምን ሁሉ አባቶቻችን በእሳት አምሳል ያዩትን እኛ ተገልጦ አየነው፤ ቃሉንም ሰማነው እያልን እንመሰክራለን፡፡ ከዚህ ሁሉ ጋር ሰው ሆነም ስንል በፍጹም ተወሕዶ ነው፤ ተዋሕዶ ማለት አንድ መሆን መዋሐድ አለመለያየት፣ የማይታየው ከሚታየው፣ የማይወስነው ከሚወሰነው፣ ጋር አንድ ሆኖ ለዘለዓለም ለመኖር አካላዊ ቃል እግዚአብጠር ወልድ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ሳይለይ በማሕፀነ ማርያም አድሮ ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ መወለዱን ነው፤ ወንጌላዊው ዮሐንስም ቃል ሥጋ ሆነ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ ያለው ይህን ፍጹም ተዋሕዶ ነው፡፡ ይህም ተዋሕዶ አካላዊ መሆኑን ይገልጻል፤ ሰው ሆኖ ተወልዷልና፡፡
ስለዚህ በተዋሕዶ ለተፈጸመው ለልደት ምሥጢር አንክሮ ይገባል፡፡ ያለዘርዓ ብእሲ መፀነስ፣ ያለ ተፈትሖ መወለድ፣ ዘመን በማይቆጠርለት ሕፃን አፍ ከድንግል ጡት ወተት መፍሰስ፣ እግዚአብሔር ለመረጣቸው ለመቅደስ ካህናት ያልተደረገ ለከብት እረኞች ሰማያዊ ምሥጢር መገለጥ፣ ከሩቅ ምሥራቅ ተነሥተው የጥበበኞች በኮከብ እየተመሩ ወደ ቤተልሔም መሔድ፣ አንክሮ ይገባል፤ ከነገሥታት እጂ ወርቅ፣ ዕጣንና ከርቤ መቀበልም ድንቅ ያሰኛል፡፡ በዚያ ሰማያውያን ካህናት በወርቅ ማዕጠንት ያቀረቡትን የዕጣን መዓዛ ይቀበላል፡፡ በዚህም ዛሬ ከሰብአ ሰገል ይህን ተቀበለ፤ መላእክትና እረኞች ዝማሬን፣ እንስሳት እስትንፋሳቸውን፣ ኮከብ ብርሃኑን አቀረቡ፡፡ እኛም ይህን ተረድተን አሕዛብ ሁላችሁ በእጃችሁ አጨብጭቡ፤ በደስታም ቃል ለእግዚአብሔር እልል በሉ፤ ስሙንም አመስግኑ፤ ለጌትነቱም ምስጋና አቅርቡ እንላለን፡፡ መዝ 65·1
በአዳም በደል ያልተጸጸተ በኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ያልተደሰተ የለምና የዚህ ልደት ዓላማም ሰውን ከስሕተቱ መልሶ የእግዚአብጠር ለማድረግ ነው ዮሐ 1·12-14 ይህንም ሲያደርግ አስደናቂውን ምሥጢር እያደረገ ነው፡፡ በተወለደ ጊዜ በቤተልሔም ወተትን ከድንግልና አምላክነትን ከሰውነት፣ ሕቱም ማሕፀን ከእናትነት ጋር አንድ አድርጎ አሳይቷናል፡፡ በአምላክነት ሥራ ካልሆነ በስተቀር ወተትና ድንግልና፣ እናትነትና አገልጋይነት፣ አምላክነት እና ሰውነት፣ በአንድነት ሊገኙ አይችሉምና እግዚአብሔርን አመስግኑት ሥራህ ግሩም ድንቅ ነው በሉት እንላለን፡፡ መዝ 65·3 በሥጋዊ ጥበብ ተራቀው ሥጋዊውን ዓለም ያወቁ የአግዚአብሔርንም ሕልውና በእምነት ሳይሆን በጥበባቸው እናውቃለን ለሚሉ ሁሉ ከሰብአ ሰገል ተምረው በእምነት ሊያውቁት ይገባል፤ የተወለደው ለእነሱም ነውና፡፡
ሆኖም ግን መምጣቱን በተስፋ ለሚጠባበቁ የልደቱን ነገር በፍጹም እምነት ለተቀበሉ ሁሉ እነሆ ያማረ የምሥራች በጨለማና በሞት ጥላ ውስጥ ለሚኖሩት ሁሉ የሕይወት ብርሃን ተወልዷልና ደስ ይበላችሁ፡፡ በብርሃኑ ጨለማ ተወግዷልና እግዚአብሔር በይሁዳ ታወቀ፡፡ ስሙም በእስራኤል ታላቅ ነው ተብሎ እንደተነገረ የእስራኤል ንጉሥ በእስራኤል ልጅ አድሮ የዳዊት አምላክ ከዳዊት ልጅ ሥጋን ተዋሕዶ ከቀድሞ ጀምሮ ቅዱሳን ነቢያት ከእግዚአብሔር ተልከው መንፈስ ቅዱስ እንዳናገራቸው ዓለምን ለማዳን ከጽዮን የሚወጣ ከያዕቆብ በደልን የሚያርቅ ጌታ ይወርዳል፤ ይወለዳል በማለት በየወገናቸው በየዘመናቸው የተናገሩት ትንቢት እነሆ ዛሬ ተፈጸመ፡፡ እሱም እናንተን ከመውደዴ የተነሣ ሰው ለመሆን ወደናንተ መጣሁ፡፡ በሕፃንም መጠን ተወለድኩ፤ በጨርቅም ተጠቀለልኩ፤ ፍቅሬንም ገለጥኩላችሁ ብሏልና፣ እርስ በርሳችሁ የምትፋቀሩ የወንጌል ልጆች ወንድሞች ሆይ ይህን ትሕትናና ፍቅር አይተን እርስ በርሳችን እንፋቀር፡፡ ዮም ተወልደ ፍቅር ወሰላም ዮም ተወልደ ቤዛ ኵሉ ዓለም እግዚእ ወመድኅን ዮም ተወልደ ከሣቴ ብርሃን እያልንም እንዘምር፡፡

– ስብሐት ለእግዚአብሔር አብ
– ልጁን ውረድ ተወለድ ብሎ ለሰደደው ለአብ ወላዲ አሥራፂ ተብሎ መመስገን ይገባዋል፡፡
– ለወልድም ተወለደ ተብሎ መመስገን ይገባዋል፡፡
– ማሕየዊ ለሚሆን ለመንፈስ ቅዱስም ሠራፂ ተብሎ መመስገን ይገባዋል
– ሥጋን ላጸናው ለአብ ለተዋሓደ ለወልድ ላዋሓደ ለመንፈስ ቅዱስ ዛሬም ዘወትር በእውነት ምሥጋና ይገባዋል፡፡
– ለዓለሙ ሁሉ ሕይወትን ለወለደች ለድንግል ማርያም ምስጋና ይገባል፤ የድኅነታችን መመኪያ ናትና

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 ከደቀ መዝሙር አባ ሳሙኤል ንጉሤ ታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም አዳሪ ት/ቤት የሊቅ ተማሪ

መንፈሳዊ ኮሌጆችና “ደቀ መዛሙርቱ” ምን እና ምን ናቸው?

ኅዳር 21 ቀን 2008 ዓ.ም

ክፍል አምስት

የተሐድሶ መረብ አድማስና የትኩረት አቅጣጫዎች በሚል ባለፉት ሁለት ዕትሞች ስለ አዲስ አበባ፣ ስለ ሰሜን ኢትዮጵያ፣ ስለ ምዕራብና ደቡብ ኢትዮጵያ የተሐድሶ መናፍቃን አቅርበንላችሁ ነበር፡፡ ዛሬ ደግሞ መንፈሳዊ ኮሌጆችን መሠረት ያደረገውን የተሐድሶ መናፍቃንን ዒላማ ከብዙው በጥቂቱ፣ ከረጅሙ በአጭሩ ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡ መልካም ንባብ፡፡

ተሐድሶ መናፍቃን ቤተ ክርስቲያንን ፕሮቴስታንት የማድረግ ዕቅዳቸውን ዕውን ለማድረግ ትኩረት ካደረጉባቸው ተቋማት መካከል የመጀመሪያዎቹና ግንባር ቀደሞቹ የመንፈሳዊ ኮሌጆች ደቀ መዛሙርት€ ናቸው፡፡ እስካሁን በማኅበር ደረጃ የሚንቀሳቀሱት ከሃያ አምስት በላይ የተሐድሶ መናፍቃን ድርጅቶች ቀላል የማይባሉ አባሎቻቸው በመንፈሳዊ ኮሌጆች ተምረው ያለፉ፣ ይሠሩ የነበሩ ወይም በመሥራት ላይ የሚገኙ እንዲሁም የሚማሩ ናቸው፡፡ በመንፈሳዊ ኮሌጆች ውስጥ የሚታየው የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ ከተማሪዎች ምልመላ እና ተማሪዎቹ ወደ ኮሌጆቹ ሲገቡ ከሚደረግላቸው ቅበላ ጀምሮ የሚሠራ ነው፡፡ የገንዘብ እጥረት የሚያጋጥማቸውን ደቀ መዛሙርት ደግሞ በድጋፍ ስም ይቀርቧቸዋል፡፡ መጻሕፍትንና ሌሎች አስፈላጊ የትምህርት መርጃ መሣሪያዎችን በመዋዋስ ስም ግንኙነት በመፍጠር ኦርቶዶክሳዊ ተማሪዎችን ወደ ቡድናቸው ያስገባሉ፡፡

ከተለያዩ መንፈሳዊ ኮሌጆች የተመረቁ €œደቀ መዛሙርት€ ኅቡዕ ቡድን መሥርተው በቤተ ክርስቲያን ላይ ሰፋ ያለ ዘመቻ ከፍተዋል፡፡ ቡድኑ ዓላማውን ለማሳካት በተለያዩ ቦታዎች ላይ ተወካይ በማስቀመጥ ሥራውን ይሠራል። ይህ ስውር ቡድን በመጨረሻ ላይ ለማሣካት ዓላማ አድርጌ ተነሣኋቸው የሚላቸው የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ በራሳቸው መንገድና የኑፋቄ አቅጣጫ በመለወጥ ፕሮቴስታንታዊ ለማድረግ ካስቀመጣቸው የማስመሰያ ግቦች፡-

ክርስቲያኖች የእግዚአብሔር ቃል በምልዓት እንዲኖርባቸው ማድረግ፣

በሥነ መለኮት ትምህርት ገንቢ ዕውቀት ያላቸውን አገልጋዮች በማደራጀት የወንጌልን እን ቅስቃሴ ማስፋፋት፣

 በቤተ ክርስቲያኒቷ ውስጥ ከስንዴ ጋር አብረው የገቡትን ትምህርቶችና መጻሕፍት (አስተምህሮዎች) ማስወገድ፣

 ቤተ ክርስቲያን ምንም ከማይጠቅም ወግ፣ ልማድ እና በብልሃት ከተፈጠሩ ተረታዊ ትምህርቶች ተለይታ እውነት የሆነው ክርስቶስ እንዲሰበክ ማድረግ፣

 የኢትዮጵያ አብያተ ክርስቲያናት በክርስቶስ ጥላ ሥር ተሰብስበው እንዲያመልኩና በአንድ እንዲተባበሩ ማድረግ፣

 ወንጌል በእያንዳንዱ ቤት አንኳኩቶ በመግባት መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ለውጥ እንዲመጣ ማድረግ፣

 ወጥና ተከታታይ ትምህርትን በማዘጋጀት ወጣቶችን፣ ሕፃናትንና አረጋውያንን በማነቃቃት ለዓለም ብርሃን የሆነውን የጌታን ቃል ለሁሉም እንደየአቅማቸውና እንደየደረጃቸው ማዳረስ፣

 በቤተ ክርስቲያኒቱ አገልጋዮች ላይ ልዩ ትኩረት በመስጠት መሥራት፣

 የወንጌልን ተልእኮና ለውጥ ሊያፋጥን በሚቻል መልኩ የተለያዩ ተቋማትን ማእከል በማድረግ መንቀሳቀስ፣

 የቤተ ክርስቲያን ለውጥና ዕድገት የሚሹትን ሁሉ ማደራጀት፣

 በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እራሱን የቻለ ማኅበር ማቋቋም የሚሉ ናቸው፡፡ (ምንጭ፡- የተሐድሶ መናፍቃን ዘመቻ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ ገጽ ፺፬)

እነዚህን እና የመሳሰሉትን ምክንያቶች በመደርደር €œቤተ ክርስቲያናችን እስካሁን ድረስ ዘመናትን የፈጀችው ወንጌልን ስትሰብክ ሳይሆን ስለ ቅዱሳን ስታስተምር ነው፤ አሁን መስበክ ያለብን ክርስቶስን ነው€ የሚለውን ተሐድሶ መናፍቃን ያራምዱት የነበረውን የፕሮቴስታንት አስተምሮ ይዞ የተነሣ ነው። ለቅዱሳን የማስተማር ጸጋ ስለሰጣቸው ስለ ክርስቶስ ማስተማር መሆኑን መረዳት ይገባቸዋል ቤተ ክርስቲያን ጉልላቷ ስለሆነው ስለ ክርስቶስ ሳታስተምር የዋለችበት ዕለት ያለ ለማስመሰል መሞከራቸው ስሕተት ነው፡፡ ዓላማዬን ያሳኩልኛል ብሎ ካሰማራቸው ሰዎች ሲገልጽ ደግሞ እንዲህ ብሏል፡፡ ሥራውን የሚሠራው መንፈስ ቅዱስ ሆኖ የለውጥ መሪ የሚሆኑ በእምነትና በዕውቀት የታመነባቸው የነገረ መለኮት ተማሪዎች፣ ልዩ ልዩ መምህራን፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚያገለግሉ ቀሳውስትና ዲያቆናት፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶች፣ ምእመናን፣ ልዩ ልዩ ድርጅቶች ናቸው፡፡ ይህ ሲባል በመንፈሳዊ ለውጥ የሚሠሩትን አካላትም ያካትታል፡፡

ቡድኑ በዋነኝነት በመንፈሳዊ ተቋማት ያሉና ተመርቀው የሚወጡ ተማሪዎችን ቢያማክልም በግላቸውና በማኅበር ተጀራጅተው ከሚንቀሳቀሱ ማኅበራት ጋር አብሮ ይሠራል። ይህ ማኅበር ዓላማውን ለማሳካት የምንፍቅናውን መርዝ ለመርጨት ያሰበባቸው ቦታዎች መንፈሳዊ ኮሌጆች ብቻ ሳይሆኑ፤ የካህናት ማሠልጠኛ ሥፍራዎች፣ ገዳማትና የአብነት ትምህርት ቤቶች፣ የቤተ ክህነት መሥሪያ ቤቶች፣ የመንግሥት የትምህርት ተቋማት እና ማኅበራት ናቸው፡፡

ለእንቅስቃሴው አስተዋጽኦ ያደረጉ ሁኔታዎች

በመንፈሳዊ ኮሌጆች ውስጥ ያለው የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ እንዲስፋፋ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ አስተዋጽኦ የሚያደርጉ ሁኔታዎች አሉ፡፡ ምክንያቶች ብዙ ቢሆኑም ጠቅለል ባለ መልኩ ሲታዩ ከኮሌጆቹ አስተዳደራዊ መዋቅርና አሠራር እንዲሁም ከተማሪዎች ክትትል ጋር የተያያዙ ናቸው፡፡

፩.አስተዳደራዊ ችግሮች

መንፈሳዊ ኮሌጆች ላይ የሚከሠቱት የአብዛኛዎቹ ችግሮች መነሻቸው አስተዳደራዊ ችግር ነው፡፡ ይህ የሁሉም ችግሮች ምንጭ ነው፡፡ መንፈሳዊ ኮሌጆች አስቀድመው አስተዳደራዊውን ችግር ቢፈቱ ሌሎችን በቀላሉ መፍታት ይችላሉ፡፡ ከገንዘብ አያያዝ፣ ከተማሪዎች ጋር ባለው መልካም ግንኙነት፣ ከመምህራን ቅጥር እና ከአስተዳደር ሓላፊዎች ምደባ ጋር ተያይዞ ብዙ ችግሮች ይታያሉ፡፡ እነዚህ አስተዳደራዊ ችግሮች ተቋሙ ዋና ጉዳዩ የሆኑት ደቀ መዛሙርትን ዘንግቶ ሌሎች ጉዳዮች ላይ እንዲጠመድ ያደርጉታል፡፡ ተሐድሶ መናፍቃኑ ደግሞ ይህንን ክፍተት በደንብ እየተጠቀሙበት ነው፡፡ አስተዳደራዊውን ችግር ሃይማኖታዊ አስመስሎ ከማቅረብ ጀምሮ በየጊዜው ለአስተዳደሩ የቤት ሥራ የሆኑ ጉዳዮችን በመብት ስም እያነሡ እነርሱ የውስጥ ዓላማቸውን ለማስፈጸም ይተጋሉ፡፡

፪.የገንዘብ እጥረትና የአጠቃቀም ችግር

ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እንደ አንድ ችግር የሚነሣው የገንዘብ እጥረት ነው፡፡ በእርግጥ ቤተ ክርስቲያን ከማንኛውም አካል በላይ የሆነ ሀብት አላት፡፡ ይህም ሀብት የልጆቿ ዕውቀት፣ ጉልበትና ገንዘብ ነው፡፡ ይህንን በአግባቡ አቀናጅቶ የሚያሠራ መዋቅር፣ አሠራርና ስልት ባለመዘርጋቱ ግን ብዙ አብያተ ክርስቲያናት አገልግሎት የሚሰጥባቸው ጠፍቶ ሲዘጉ ይታያሉ፡፡ ከተማ ላይ አብያተ ክርስቲያናት በሚልዮንና ቢሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ሲያንቀሳቅሱ፣ እያንዳንዳቸው ከአንድ መቶ በላይ አገልጋዮች ሲኖሯቸው በገጠር ያሉ አብያተ ክርስቲያናት ደግሞ በአንጻሩ ዕጣንና ጧፍ እንዲሁም ቤተ ክርስቲያን የሚከፍት አንድ ካህን አጥተው ሲቸገሩ ይታያል፡፡ ይህም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ማእከላዊ የሆነ የገንዘብ አያያዝ ባለመኖሩ የተከሠተ ችግር ነው፡፡

የዚህ ችግር ውጤትም በአጥቢያዎች ውስጥ ብቻ ሳይሆን በቤተ ክርስቲያን መዋቅር ውስጥ በሚገኙ ተቋማትም የሚታይ ነው፡፡ መንፈሳዊ ኮሌጆች በዚህ ከሚፈተኑት የቤተ ክርስቲያን ተቋማት መካከል ናቸው፡፡ ኮሌጆቹ እንደ ተቋም ለአገልግሎቱ አስፈላጊ የሆኑ ቁሳቁሶችን ለማሟላት የገንዘብ እጥረት ያጋጥማቸዋል፡፡ ይህ ክፍተት ደግሞ በእርዳታ ስም መናፍቃኑ ወደ ተቋማቱ እንዲገቡ በር ከፈተላቸው፡፡ በመንፈሳዊ ኮሌጆች የሚማሩ ደቀ መዛሙርትም ወደ ሌላ እምነት እንዲገቡና የተሐድሶ መናፍቃኑን ጎራ እነዲቀላቀሉ ከሚያደርጓቸው ችግሮች አንዱ የገንዘብ እጥረት ነው፡፡

፫.የምልመላ መስፈርት

ተማሪዎች ወደ ኮሌጆች የሚገቡት ከዚህ በፊት የነበራቸው ሰብእና (ማንነትና ምንነት) ተጠንቶና ታውቆ ሳይሆን ሀገረ ስብከት ላይ ወደ መንፈሳዊ ኮሌጆች ለመላክ ሓላፊነት ካላቸው አካላት ጋር ባላቸው ቅርበት ነው፡፡ ለቤተ ክርስቲያን ብዙ አገልግሎት ሊሰጡ የሚችሉ፣ ትልቅ አቅም ያላቸው ሰዎች እየቀሩ በጓደኝነት፣ በዝምድና፣ አለፍ ሲልም በጥቅማ ጥቅም ወደ ኮሌጆች የሚገቡት ተማሪዎች በርካታ ናቸው፡፡ በዚህ መልኩ ወደ ኮሌጆች የሚገቡ ሰዎች ደግሞ ዐዋቂ ቢሆኑ እንጂ ክርስቲያን መሆን አይችሉም፡፡ ዐዋቂነትና መራቀቅ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ዓላማ አይደለም፡፡ ለቤተ ክርስቲያን በንባብ ላይ ከሚራቀቀው ዐዋቂ ይልቅ፣ እየተንተባተበ ወልድ ዋሕድ ብሎ የሚመሰክር ኦርቶዶክሳዊ ደቀ መዝሙር ያስፈልጋታል፡፡

በተጨማሪም ወደ ኮሌጆች የሚገቡበት የትምህርት መስፈርት ተመሳሳይ ባለመሆኑ በክፍል ውስጥ የሚሰጠው ትምህርት ለአንዳንዶቹ የሚጠጥርባቸው ለሌሎቹ ደግሞ የሚመጥናቸው አልሆን ይላል፡፡ ለምሳሌ በኮሌጆች ውስጥ በመደበኛው ዲፕሎማ መርሐ ግብር ከዐሥረኛ ክፍል ጀምሮ እስከ ዲግሪ ድረስ፣ ከፊደል ተማሪ እስከ መጻሕፍት መምህራን ድረስ አንድ ላይ በአንድ ክፍል የሚማሩበት ዕድል አለ፡፡ ባለዲግሪው በእንግሊዝኛ የሚሰጡ ትምህርቶች ላይ የተሻለ ግንዛቤ ሊኖረው ሲችል፣ ዐሥረኛ ክፍል የጨረሰው ከትምህርቱ በላይ ፈታኝ የሚሆንበት እንግሊዝኛ ቋንቋ ማጥናቱ ይሆናል፡፡ ወደ ግእዝ ቋንቋ ስንመጣም ችግሩ ተመሳሳይ ነው፡፡ የቅኔ እና የመጻሕፍት መምህራን ግእዝን ካልቆጠረው ጋር አብረው ይማራሉ፡፡

፬.የትምህርት አሰጣጥ

ኮሌጆች ውስጥ የሚሰጠው ትምህርት አብዛኛው ዕውቀት ተኮር እንጂ ምግባር ተኮር አይደለም፡፡ የትምህርት አሰጣጡም ተማሪዎች ጉዳዩን ዐውቀውት ማስተማር እንዲችሉ ማድረግን እንጂ እንዲኖሩት ማድረግን ዓላማው ያደረገ አይደለም፡፡ የነገረ መለኮት ምሩቅ ከሌሎች ሰዎች የሚለየው በዕውቀቱ እንጂ በሕይወቱ እንዲሆን የተሠራው ሥራ አናሳነው፤ ወይም የለም፡፡ ይህ ደግሞ ለቤተ ክርስቲያንም ሆነ ለግለሰቡ ሕይወት አንዳች ረብ የሌለው መጻሕፍትን ይዞ እንደማይጠቀምባቸው ቤተ መጻሕፍት መሆን ነው፡፡

ትምህርቱም በመምህራን እውነተኛነት፣ ታማኝነትና ክርስትና ላይ የተመሠረተ እንጂ የኮሌጆቹ አስተዳደሮች ስለሚሰጠው ትምህርት የሚያደርጉት ክትትል የለም፡፡ ኮሌጆቹ አንድ መምህር ክፍል መግባት ወይም አለመግባቱን፣ ገብቶ የሚያስተምረው የትምህርት ይዘት ኦርቶዶክሳዊ ዶግማና ቀኖናን የተከተለ መሆን አለመሆኑን የሚቆጠ ጣጠሩበት ሥርዓት የላቸውም፡፡ ይህ ደግሞ ማስተማር መንፈሳዊ አገልግሎት ሳይሆን የገንዘብ ማግኛ ሥራ አድርገው የሚቆጥሩ ብዙ መምህራን እንዲኖሩ የሚያደርግና ያደረገ አሠራር መፍጠር ችሏል፡፡

፭.የተማሪ አያያዝ

ኮሌጆች ምግብ፣ ልብስ፣ መጠለያና ሌሎች አስፈላጊ ጉዳዮችን አሟልተው በመደበኛው የቀን መርሐ ግብር የሚያስተምሯቸው ተማሪዎች ባላቸው ትርፍ ጊዜ የት እንደሚሔዱ፣ ምን እንደሚሠሩ፣ ከማን ጋር እንደሚውሉ ወዘተ የሚደረገው ቁጥጥር በጣም የላላ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ትምህርት የማይሰጥባቸውን ዕለታት ተማሪዎች መገኘት ከማይገባቸው አልባሌ ቦታዎች ጀምሮ ወደ መናፍቃን አዳራሽ ሳይቀር ይሔዳሉ፡፡ ለምሳሌ በከሣቴ ብርሃን መንፈሳዊ ኮሌጅ ሲማሩ ከነበሩ የተወሰኑ ተማሪዎች መካከል እሑድ ከዐራት ሰዓት ጀምሮ የሚሔዱበት የመናፍቃን አዳራሽ አለ፡፡ ሰፊ እረፍት ሲኖራቸው ደግሞ አዲስ አበባ እንዲመጡ በማድረግ በአሸናፊ መኮንን ሰብሳቢነት በኮሌጁ ውስጥ ስለሚሠሩት የኑፋቄ ሥራ ሥልጠና ይሰጣቸዋል፡፡ የተለያዩ የመናፍቃን መጻሕፍትን በኮሌጁ ውስጥ በነጻ ያድላሉ፣ “የአሸናፊ መኮንንን መጻሕፍት ያላነበበ ተማሪ የነገረ መለኮት ተማሪ አይባልም” የተባለ እስከሚመስል ድረስ በነፍስ ወከፍ ለሚከተሏቸው ሰዎች ሁሉ ይታደላል፡፡ ይህ ሁሉ የሚያሳየው የኮሌጆቹ አስተዳደሮች የሚያስተምሯቸው ሰዎች ሕይወት ገዷቸው የሚሠሩት ሥራ እንደሌለ ነው፡፡

፮.ከወጡ በኋላ ያለው ክትትል ማነስ

ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ከሦስቱም መንፈሳዊ ኮሌጆች ልጆችን ታስመርቃለች፡፡ ነገር ግን በኮሌጆች ውስጥ ቆይተው መውጣታቸውን እንጂ በትክክል የሚገባቸውን ነገር (ዕውቀትን ከሥነ ምግባር አስተባብረው) ይዘው መውጣታቸውን፣ ከወጡም በኋላ በተመደቡበት ሀገረ ስብከት ቤተ ክርስቲያን የምትፈልግባቸውን ያህል እየሠሩ መሆኑን፣ የሚያስተምሩት ትምህርት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን መሠረተ እምነት የተከተለ መሆኑን የምታውቅበት ሥርዓት አልዘረጋችም፡፡ እስካሁን ስንት ደቀ መዛሙርት ተመረቁ? ከተመረቁት ውስጥ ስንቶች በአገልግሎት ላይ አሉ?፣ ስንቶች በሃይማኖታቸው ጸንተው፣ በምግባራቸው ቀንተው እያገለገሉ ነው? ስንቶች አገልግሎት አቁመዋል? ስንቶችስ ወደ ሌላ እምነት ገብተዋል? ወደ ሌላ እምነት እንዲገቡ ያደረጋቸው ገፊ ምክንያት ምንድን ነው? አሁን ያሉበት አቋም ምን ይመስላል? የሚሉት ጉዳዮች ለኮሌጆችም ሆነ ለቤተ ክርስቲያን ጉዳዮች መሆን አልቻሉም፡፡ ይህ ክፍተት እነሱን መሣሪያ አድርገው ለመጠቀም ሌት ከቀን ለሚተጉት መናፍቃን ጥሩ ዕድል ሆኗ ቸው ውጭ ሆነው ለሚሠሩት የጥፋት ሥራ የውስጥ ዐርበኛ ሆነው የሚያገለግሏቸው ኦርቶ-ጴንጤ€ የኮሌጅ ምሩቃን ሰባኪ፣ የስብከተ ወንጌል ሓላፊና የደብር አስተዳዳሪ ሆነው እንዲቀመጡ አድጓል፡፡

፯.የትኩረት ማነስ

በመንፈሳዊ ኮሌጆች ውስጥ በዓላማና በረቀቀ ዘዴ እየተሠራ ያለውን የተሐድሶ እንቅስቃሴ መኖሩን ካለመቀበል ጀምሮ እንቅስቃሴውን ለማስቆም የተሠሩ ሥራዎች አለመኖራቸው ለጉዳዩ የተሰጠው ትኩረት አነስተኛ እንደሆነ ያሳያል፡፡ በመንፈሳዊ ኮሌጆች ውስጥ የነበሩ አንዳንድ ሰዎች እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ተሐድሶ ማኅበረ ቅዱሳን የፈጠረው የመወደጃ ፍረጃ€ እንጂ ቤተ ክርስቲያንን ለማጥፋት የተሸረበ ሥውር ሴራ መሆኑን አልተረዱትም፣ ወይም ሊረዱት ፈቃደኛ አይደሉም፡፡ ይህ አቋም ሁለት ዓይነት ትርጉም ይኖረዋል፡፡ አንደኛው በአስተዳደር ሓላፊነት ላይ ካሉት አካላት ውስጥ ተሐድሶን የሚደግፉ፣ የውስጥ ዐርበኛ ሆነው የሚሠሩና በዓላማ የተሰማሩ ሰዎች አሉ ማለት ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ ለቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ትኩረት የማይሰጡ፣ ክርስትናን በጊዜያዊ ነገር የሚለውጡ፣ የሚነገራቸውን ነገር ላለመስማት ጆሯቸውን የደፈኑ እና ምን እየተሠራ እንደሆነ እንኳን መረጃው የሌላቸው ሰዎች በሓላፊነት ላይ እንደተቀመጡ የሚያስገነዝብ ነው፡፡

እንቅስቃሴው በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሰው ጉዳት

፩.ሃይማኖታዊና ሥነ ምግባራዊ ችግር

አንድ መናፍቅ ምንም ትምህርት የሌለውን ክርስቲያን ከማታለል ይልቅ ከመንፈሳዊ ኮሌጅ የተመረቀ ሰባኪን ማሳመን ይቀለዋል፡፡ ለዚህም ነው በተሐድሶ መናፍቃን ማኅበራት ውስጥ ከምእመኑ ይልቅ ከመንፈሳዊ ኮሌጆች ከተመረቁት ደቀ መዛሙርት መካከል የሚበዙት መናፍቅ የሆኑት፡፡ ብዙ ተመራቂዎች እንደሚናገሩት ከመንፈሳዊ ኮሌጅ የተመረቀ ሰው የመጀመሪያ የምስጋና ጸሎቱ €œአቤቱ መናፍቅ ሳልሆን እንድወጣ ስላደረግኸኝ አመሰግንሀለሁ የሚል ነው፡፡ በአንዳንድ ቦታዎች ላይ የመንፈሳዊ ኮሌጅ ምሩቅና መናፍቅ አቻ ለአቻ የሚነገሩ ቃላት ናቸው፡፡ እንዲህ ዓይነት ንግግሮች መንፈሳዊ ኮሌጆችና €œደቀ መዛሙርቱ€ ምን እና ምን ናቸው? የሚለውን ጥያቄ እንድንጠይቅ ያስገድዱናል፡፡

ለብዙ የተሐድሶ መናፍቃን መፈጠር፣ ለብዙ ምእመናን ከአገልግሎት መውጣትና ከሃይማኖት መራቅ የዋናውን ድርሻ የሚወስዱት እነዚሁ €œደቀ መዛሙርት€ ናቸው፡፡ ሃይማኖቱን በመተውም ቅድሚያውን የሚይዘውም ያልተማረው ኅብረተሰብ ሳይሆን እነዚሁ ናቸው፡፡ የዚህ ምክንያቱ መጀመሪያ የነበራቸው የትምህርት መሠረት ወይም የትምህርት አሰጣጡ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የመናፍቃኑ የመጀመሪያ €œጥቅሶች€ (ማሳያዎች ማለታችን ነው) መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃላት ሳይሆኑ ከእነዚህ መንፈሳዊ ኮሌጆች አፈንግጠው የወጡ ሰዎች ናቸው፡፡ የደቀ መዛሙርቱ በሃይማኖትና በምግባር መውጣት የቤተ ክርስቲያን ችግር ተደርጎ ተወስዶ ለብዙ ምእመናን ከመንገዳቸው ለመውጣት ምክንያት ሆኗል፡፡

፪.ሁሉንም እንዲጠሉ ማድረግ

ከመንፈሳዊ ኮሌጆች ተመርቀው የወጡ በቃልም በሕይወትም የሚያስተምሩ፣ ሃይማኖትና ምግባር እንደ ድርና ማግ አስተባብረው የያዙ የቤተ ክርስቲያን የቁርጥ ቀን ልጆች መኖራቸው እውነት ነው፡፡ በገጠር ያለችው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እንዲጠናከር አምሳና መቶ ኪሎ ሜትር በእግራቸው እየሔዱ፣ ወጣቶችን እየሰበሰቡና እያስተማሩ ሌት ከቀን የሚደክሙ ደቀ መዛሙርት አሉ፡፡ እንደእነዚህ ያሉ ደቀ መዛሙርት ያሉትን ያህል ደግሞ፣ ከርሳቸው እስከሞላ ድረስ ለሌላው መዳን አለመዳን ግድ የሌላቸው የቤተ ክርስቲያን የብብት እሳት የሆኑም አሉ፡፡ በሥጋና በመንፈስ መግባ ያሳደገቻቸውን ቤተ ክርስቲያን ከጠላቷ ከአርዮስ ጋር ወግነው ሊያፈርሷት የሚሯሯጡ የእናት ጡት ነካሾች በቁጥር እየበዙ መሔዳቸው ምእመናን እውነተኞችን አገልጋዮች እንዲጠራጠሩ፣ ከመጥፎዎቹ ጋር አብረው ደምረው እንዲጠሉ በር እየከፈተ ነው፡፡

፫.የሰውና የገንዘብ ኪሳራ

የቤተ ክርስቲያን ገንዘቧ ሰው እንጂ ብርና ወርቅ አይደለም፡፡ በመምህራን እግር ተተክተው መንጋውን እንዲጠብቁ ለብዙ ዓመታት የደከመችባቸው ልጆቿን ከማጣት በላይ ለቤተ ክርስቲያን ሌላ ኪሳራ የለም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ያጣችው ልጆቿን ብቻ አይደለም፤ ለእነዚህ ሰዎች ያባከነችውን ገንዘብ፣ የሰው ኃይልና ጊዜ ጭምር እንጂ፡፡ ከመንፈሳዊ ኮሌጆች የሚመረቁ እውነተኞቹ ደቀ መዛሙርት ከመድረኩ ርቀው የቢሮ ሥራ ላይ ተጠምደዋል፡፡ ይህም ለቤተ ክርስቲያን ሁለት መንታ ችግሮችን አስከትሏል፡፡ አንደኛው ቤተ ክርስቲያን ስትለፋባቸው የኖረቻቸው ልጆቿ ዓላማዋን ሳያሣኩላት መቅረታቸው ሲሆን፤ ሁለተኛውና አሳዛኙ ደግሞ ሌሎች የተሐድሶ አቀንቃኞች ቦታውን እንዲይዙት ማድረጉ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ቦታውን መያዛቸው ብቻ ሳይሆን እውነተኞቹ ከመድረኩ ስለጠፉ እነርሱ እውነተኛ መስለው መታየታቸው የበለጠ ቤተ ክርስቲያንን እየጎዳት ነው፡፡ ምክንያቱም በአሁኑ ጊዜ ተሰሚነት ያለው የሚናገር፣ የሚጽፍ ወይም የሚዘምር ሰው ስለሆነ ነው፡፡

የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ በሁሉም ኮሌጆች ያለ መሆኑን ከየኮሌጆቹ በተለያዩ ጊዜያት የተባረሩ የተሐድሶ መናፍቃን አቀንቃኞች፣ ምክርና ተግሣጽ ተሰጥቷቸው የቀጠሉ ተማሪዎች ማስረጃዎች ናቸው፡፡ እንቅስቃሴው በሦስቱም መንፈሳዊ ኮሌጆች ያለ ነው፡፡ በየኮሌጆቹ ማሳያዎችን በመጥቀስ ጉዳዮችን ማብራራት ተገቢ ይሆናልና ወደዚያ እንለፍ፡፡

ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ አዲስ አበባ መሆኑና መንፈሳዊ ኮሌጆች ላይ መሠረት አድርጎ የሚሠራውን የውጪውን የተሐድሶ መናፍቃን ድርጅትም ትኩረት የሳበ በመሆኑ ብዙ እንቅስቃሴዎች ይደረጉበታል፡፡ ከውጪ እስከ አገር ውስጥ መረባቸውን የዘረጉ የተሐድሶ መናፍቃን ድርጅ ቶች ሰፋ ያለ መሠረት ለመጣል ሲሞክሩ ነበር፣ አሁንም እየሠሩ ነው፡፡ እንቅስቃሴው በአብዛኛው የቀን መደበኛ ተማሪዎችን ትኩረት ያደረገ ነው፡፡ በዚህ ምክንያት ከኮሌጁ ተመርቀው በተሐድሶ መናፍቃን መረብ ውስጥ ያሉ ደቀ መዛሙርት€ አሉ፡፡ ከእነዚህ በተጨማሪ በትምህርት ላይ ያሉ ወደ መናፍቃን አዳራሽ የሚሔዱ፣ ከአሸናፊ መኮንን ጋር የሚማሩ ብዙ ተማሪዎች አሉ፡፡ ፳፻ወ፮ ዓ.ም ላይ ቁጥራቸው ዐሥር የሚደርሱ ተማሪዎች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮን የሚነቅፍና የክህደት ትምህርት ሲያሠራጩ በኮሌጁ ደቀ መዛሙርት መረጃ ቀርቦባቸዋል፡፡ ጉዳያቸውም ለኮሌጁ ቀርቦ እየታየ ሲሆን፤ የድምጽና የሰው ማስረጃ የቀረበባቸው የኑፋቄ ትምህርቶቻቸው የሚከተሉት ናቸው፡፡

፩.አማላጃችን ኢየሱስ ነው እንጂ ሌላ አማላጅ የለም፤

፪.በጸጋው አንዴ ድነናል፣ ስለዚህ ሥራ ለምስክርነት ነው እንጂ ለመዳናችን ምንም አያስፈልግም፤

፫.ኅብስቱ መታሰቢያ ነው እንጂ፣ ሕይወት የሚሰጥ አማናዊ የጌታ ሥጋና ደም አይደለም፤

፬.ለፍጡር አድኅነኒ አይባልም፣ ማርያም አታድንም፤

፭.በጸሎት ቤት ስለ ድንግል ማርያም ክብር ትምህርት ሲሰጥ “ተረታ ተረትህን ተውና ውረድ” ብሎ መቃወም፤

፮.ጻድቃን፣ ሰማዕታት፣ መላእክት እያልን ወንጌልን አንሸቃቅጥ፤

፯.ጻድቃን ሰማዕታት፣ መላእክት አያማልዱም፣ አያድኑም፣ አያስፈልጉም፣ አንድ ጌታ አለን፤

፰.ለቅዱሳን ስግደት አይገባም፣ የአምልኮ እንጂ የጸጋ የሚባል ስግደት የለም፤

፱.ቤተ ክርስቲያን ክርስቶስን አትሰብክም፣ የምትሰብከው ፍጡራንን ነው፤

፲.ቤተ ክርስቲያን የምትጠቀምባቸው መጻሕፍት በሙሉ ኮተቶች ናቸው፤

፲፩.እኛ የሐዲስ ኪዳን ልጆች ነን የአንድምታ መጻሕፍት አያስፈልጉንም፤

፲፪.በሐዲስ ኪዳን ካህን አያስፈልግም፣ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፣ ንስሐም መናገር ያለብን ለጌታ ብቻ ነው፤

፲፫.በጳጳሳት፣ በመነኮሳት፣ በቀሳውስት፣ በዲያቆናት እንዲሁም ኦርቶዶክሳዊ ትምህርት በሚያስተምሩትና በሚማሩት፣ በሚጾሙትና በሚያስቀድሱት የኮሌጁ ደቀ መዛሙርት ላይ ጸያፍ ስድብና ዘለፋ መናገር፡፡ ከሚናገሯቸው የስድብ ቃላት ውስጥ፡- ግብዞች፣ በጨለማ የሚኖሩ፣ ዶማዎች፣ ደንቆሮዎች፣ ያልበራላቸው፣ የጌታ ጠላቶች፣ ወዘተ ይገኙበታል፡፡

፲፬.ታቦት ጆሮ ስለሌለው አይሰማም፣ ስለዚህ አያስፈልግም ፣

፲፭.ሕዝቡን ለብዙ ሺሕ ዘመናት ለጣዖት ስናሰግደው ኖረናል፣

፲፮.አሁን ካለንበት የጨለማ ጫካ መውጣት አለብን፣

፲፯.ቤተ ክርስቲያን፡- ዘረኝነትንና ጽንፈኝነትን ታስፋፋለች፣ የተወሰነ ጎሳ ናት፣

፲፰.አንደኛ ዓመት ተማሪዎችን ሲያገኟቸው €œቲዮሎጂ መማር ከፈለግህ የበላኸውን መትፋት አለብህ€፣ ወዘተ በማለት መዝለፍና ክፉ ምክር መምከር የሚሉት ናቸው፡፡

ይህ የሚያሳየው ከዚህ ኮሌጅ ተመርቀው የተሐድሶ መናፍቃኑን ጎራ የተቀላቀሉት ሰዎች ኮሌጁን በሚፈልጉት መልኩ ለመቅረፅ ሰፋ ያለ ሥራ እየሠሩ መሆኑን ነው፡፡ ይህም ፍሬ ኮሌጁ በእነዚህ ደቀ መዛሙርት ላይ እንደሆነው በየጊዜው እያጠራ ካልሔደ ችግሩን ውስብስብ እና ከባድ ያደርገዋል፡፡

ሌላኛው ኮሌጅ የተሐድሶ መናፍቃን አቀንቃኞች “ብዙ ሰዎችን ያፈራንበት ቤታችን ነው ብለው በድፍረት የሚናገሩለት” ሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ነው፡፡ ተሐድሶዎችና መናፍቃኑ ከዚህ ኮሌጅ ተመርቆ ኦርቶዶክሳዊ ሆኖ መገኘት የተአምር ያህል የሚቆጠር እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ እነርሱም ከዚህ ኮሌጅ የተመረቀ መሆኑን ያረጋገጡትን ሰው በልበ ሙሉነት ይቀበላሉ፡፡ በኮሌጁ የኑፋቄው ጠንሳሽ መሠረት ስብሐት ለአብ ነው፡፡ የእርሱን ፈለግ ተከትለው ብዙ ጥፋት ያደረሱት ደግሞ በ፳፻ወ፬ ዓ.ም ተወግዘው የተለዩት ጽጌ ሥጦታውና ግርማ በቀለ ናቸው፡፡ ከ፲፱፻፺ ዓ.ም ጀምሮ የተከሉት እሾህ ዛሬም ድረስ ቤተ ክርስቲያንን እያደማ ይኖራል፡፡ ከዚህ ኮሌጅ ተመርቀው አንዳንዴ ፕሮቴስታንት፣ ሌላ ጊዜ ሙስሊም አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ኦርቶዶክስ ሆነው የሚተውኑ ደቀ መዛሙርት€ አሉ፡፡

ከሣቴ ብርሃን መንፈሳዊ ኮሌጅ በተሐድሶ መናፍቃን ብዙ ተጽእኖ የደረሰበት ኮሌጅ ነው፡፡ ለብዙ ዓመታት በኮሌጁ እንደ ሐሰተኛ የሚቆጠሩትና አንገታቸውን ደፍተው የሚሔዱት የነበሩት ኦርቶዶክሳውያን ነበሩ፡፡ ይህ የሆነው በሓላፊነት ላይ የነበሩት መሪዎች ድጋፍ የሚሰጡት ከትክክለኞቹ የቤተ ክርስቲያን ልጆች ይልቅ ለተሐድሶ መናፍቃኑ ስለ ነበር ነው፡፡ ይህ የሆነውም እንቅስቃሴውን የሚደግፉ ተጽእኖ ፈጣሪ ሰዎች ከጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጀምሮ በተለያዩ ቦታዎች ላይ ስለሚያግዟቸው ነው፡፡ ይህ ጉዳይ ካለፉት ጥቂት ዓመታት ጀምሮ ለውጦች እየታዩበት ነው፡፡ የዚህ መንፈሳዊ ኮሌጅ የተሐድሶ ጠንሳሽ በኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር የመቀሌ ቅርንጫፍ ሰብሳቢ የነበረ ሰው ነው፡፡ አዳዲስ ተማሪዎች ሲገቡ አጥምደው ወደ ቡድናቸው ያስገቡ ነበር፡፡ በ፳፻ወ፮ ዓ.ም ያለውና በዛብህ የሚባሉ ቀንደኛ የተሐድሶ መናፍቃን አቀንቃኞች ከዚህ ኮሌጅ ኑፋቄያቸው ተደር ሶበት ተባረዋል፡፡

የተሐድሶ መናፍቃን ተላላኪ የሆኑት የኮሌጁ ተማሪዎች በዕረፍት ሰዓታቸው ወደ አዲስ አበባ መጥተው በአሸናፊ መኮንን አስተባባሪነት ይሰበሰባሉ፡፡ ለቡድናቸው አባላት መጽሐፍ ቅዱስ፣ የአሸናፊ መኮንን መጻሕፍት እና ሌሎችም ተሐድሶዎች የጻፏቸው መጻሕፍት ይታደላሉ፡፡ ፳፻ወ፯ ዓ.ም ላይ በኮሌጁ ተማሪዎች በተደረገ የመረጃ ማጠናቀር የተደረሰበት በኮሌጁ ከሚማሩት ተማሪዎች ውስጥ ሃምሳ በመቶ ያህሉ ተሐድሶዎችና የተሐድሶ መናፍቃን ደጋፊዎች ናቸው፡፡ እነዚህ የኮሌጁ ተማሪዎች ግንባር ቀደም የተሐድሶ አንቀሳቃሾች ናቸው፡፡

ስለ መንፈሳዊ ኮሌጆች ስንናገር መንፈሳዊ ኮሌጆች በእምነት የጸኑ፣ በምግባር የቀኑ ደቀ መዛሙርትን አላፈሩም ማለታችን አለመሆኑን መረዳት ተገቢ ነው፡፡ ከተመሠረቱበት ዓላማ አንጻር የምርቱን ያህል ግርዱም እየበዛ ማስቸገሩን ለማሳየት አቅርበናል፡፡ እንኳን ትልቅ ተቋም አንድ ግለሰብም የወለዳቸው ልጆች ሁሉ መልካሞች፣ ያስተማራቸው ተማሪዎች ሁሉ ዐዋቂዎች ወይም መንፈሳውያን እንደማይሆኑለት ይታወቃል፡፡ ይህ የነበረ፣ ያለና የሚቀጥል እውነት ነው፡፡ ከጌታችን እግር ሥር ቁጭ ብለው ከተማሩት ሐዋርያት መካከል ይሁዳ በስንዴ መካከል የበቀለ እንክርዳድ ነበር፤ በተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ እግር ሥር ቁጭ ብለው ከተማሩት ደቀ መዛሙርት መካከልም አርዮስ በቅሏል፡፡

ነገር ግን በመንፈሳዊ ኮሌጆች ውስጥ እየታየ ያለው ንጹሕና የተቀላቀለ ስንዴ አስገብቶ እንክርዳድ የማምረቱ ጉዳይ እየጨመረ መምጣቱን አህጉረ ስብከትም እየገለጡ ነው፡፡ እዚህ ላይ ለማስገንዘብ የምንፈልገውም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አቅሟን የምታጠናክርባቸው፣ ተተኪ ሊቃውንትን የምታፈራባቸው መንፈሳዊ ካሌጆች፤ የተሐድሶ መናፍቃን መፈልፈያ ለማድረግ በዓላማ ሌት ከቀን እየተሠራ ያለውን ተግባር ምን ያህል አውቀነዋል በሚል እንጂ፤ በየኮሌጆቹ ውስጥ ሆነው አቅማቸው በፈቀደ፣ ይህን ሥውር ደባና ዘመቻ ለማጋለጥ የሚተጉ ደቀ መዛሙርት የሉም ለማለት አይደለም፡፡፡ ሆኖም ግን ተፅዕኖውና ዘመቻው ከእነሱ አቅም በላይ ስለሆነ፤ በመዋቅሩ ደረጃ ችግሩን ለመቅረፍ መሠራት የሚኖርባቸውን ተግባራት ለማመላከትና የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆች የሆኑ በየኮሌጆቹ የሚገኙ ደቀ መዛሙርትም በፅናት ሆነው የተሐድሶ መናፍቃን ዓላማ ግቡን እንዳይመታ ጥረታቸውን እንዲቀጥሉ ለማሳሰብ ነው፡፡

እውነተኞቹ ደቀ መዛሙርት እኩይ ተግባራቸውን ስለገለጡባቸው ተሐድሶ መናፍቃንም ተነካን በሚል የዋሃንን አስተባብረው ለመጮህ ወደ ኋላ የማይሉ መሆናቸውን ለማስገንዘብ ነው፡፡ ስለዚህ ደግመን እንጠይቃለን መንፈሳዊ ኮሌጆችና €œደቀ መዛሙርት ምን እና ምን ናቸው?€ ይህንን የምንለው ከላይ የተዘረዘሩት ችግሮች ተቀርፈው ኦርቶዶክሳውያን ደቀ መዛሙርት እንዲበዙና ወጥተውም በተማሩት ሙያ እንዲያገለግሉ የሚያ ደርግ ሥራ መሥራት እንደሚገባን ለማመልከት ነው፡፡

ስንክሳር፡- መስከረም ስድስት

መስከረም 6 ቀን 2008 ዓ.ም

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም ስድስት በዚች ቀን ታላቅ ነብይ የአሞጽ ልጅ ኢሳይያስ ዐረፈ፡፡

ይህም ነቢይ ለይሁዳ በነገሡ በአምስቱ ነገሥታት ዘመን አስተማረ ትንቢትም ተናገረ፣ እሊህም ኦዝያን፣ ኢዮአታም፤ አካዝ፤ ሕዝቅያስና ምናሴ ናቸው፡፡

በአካዝ ዘመንም እንዲህ ብሎ ትንቢት ተናገረ፡፡ እነሆ ስለዚህ እግዚአብሔር ምልክትን ይሰጣችኋል፡፡ እነሆ ድንግል ፀንሳ ወንድ ልጅን ትወለወዳለች ስሙንም አማኑኤል ትለዋለች፡፡

ትርጓሜውም እግዚአብሔር ከእኛ ጋር አንድ ሆነ ማለት ነው፡፡

እርሱም በኃጢአታቸው ከሚመጣባቸው ፍዳ ወገኖቹን የሚያድናቸው ወደ ሃይማኖቱም የሚያስገባቸው እንደሆነ የእስራኤልንም ልጆች መስዋዕታቸውንና ክህነታቸውን እንደሚሽር ከሐዲስ ወገኖችም የሚያመሰግኑት ካህናትን እንደሚሾም ተናገረ፡፡

የፋርስ ንጉሥ ሰናክሬምም ኢየሩሳሌምን ከቦ የስድብ ቃልን በክብር ባለቤት በእግዚአብሔር ላይ በተናገረ ጊዜ የፋርስ ንጉሥ ሰናክሬምን ያጠፋው ዘንድ እግዚአብሔር እንዳለው ለሕዝቅያስ ትንቢትን ተናገረ፡፡

በዚያች ሌሊትም እግዚአብሔር የላከው የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ወደ ሰናክሬም ሠፈር መጥቶ ከፋርስ ሠራዊት መቶ ሰማንያ አምስት ሺሕ አርበኞችን ገደለ፡፡ የለኪሶ ሰዎች ሲነጋ በተነሱ ጊዜ የሞቱትን ሰዎች ሬሳ ሁሉ አዩ፡፡

ሕዝቅያስም ታሞ ለሞት በተቃረበ ጊዜ የአሞጽ ልጅ ኢሳይያስ ወደ እርሱ መጥቶ እግዚአብሔር ትሞታለህ አንጂ አትድንም ብሏልና ቤትህን አዘጋጅ አለው፡፡

ሕዝቅያስም ፊቱን ወደ ግድግዳው መልሶ ወደ እግዚአብሔር ለመነ፣ ፈጽሞ ጽኑ ልቅሶንም አለቀሰ፡፡ ይህን ከነገረው በኋላ የእግዚአብሔር ቃል ወደ ነብዩ ወደ ኢሳይያስ መጣ፣ ሒደህ ለሕዝቅያስ የአባትህ የዳዊት ፈጣሪ እግዚአብሔር ጸሎትህን ሰማሁ፣ ዕንባህንም አየሁ፡፡ እነሆ በዘመንህ ላይ ዐሥራ አምስት ዓመት ጨመርኩልህ አለ በለው፡፡

ዳግመኛም ስለ እስራኤል መማረክና ከምርኮ ስለመመለሳቸው ትንቢት ተናገረ፡፡ የፈሳሽ ውኃን ምንጭ በማፍሰስ በእጆቹ ላይ እግዚአብሔር ምልክትን ገለጠ፡፡

ክብር ይግባውና ስለመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መከራ ትንቢት ተናገረ፣ እንዲህም አለ፡፡ እርሱም በመከራው ጊዜ ነገርን አልተናገረም እንደ በግ ይታረድ ዘንድ መጣ፣ በግ በሚሸልተው ሰው ፊት እንደማይናገር እንዲሁ በመከራው ጊዜ አልተናገረም፡፡

ከዚህም በኋላ ደግሞ በሕዝቅያስ ልጅ በምናሴ ላይ ትንቢት ተናገረ፣ ጣዖትን ስለማቆሙና ስለማምለኩ ገሠጸው፡፡ ስለዚህም ንጉሥ ምናሴ ተቆጥቶ በዕንጨት መሰንጠቂያ መጋዝ በራሱና በእግሮቹ መካከል ሠነጠቀው፣ ምስክርነቱንም በዚህ ፈጸመ፡፡

ትንቢት እየተናገረ የኖረበትም ዘመን ሰብዓ ዓመት ከዚያም በላይ ይሆናል፡፡ እርሱም ያስተማረው ክብር ይግባውና ጌታችን ከመምጣቱ በፊት በዘጠኝ መቶ ዐሥራ ሦስት ዓመት ነው፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከሁላችን ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡- መጽሐፈ ስንክሳር ከመስከረም እስከ የካቲት፣ አዲስ አበባ፤ ትንሣኤ ማሳተሚያ ደርጅት፣ 1994 ዓ.ም፣ ገጽ 23-25፡፡ 

ስንክሳር፡- መስከረም አምስት

መስከረም 5 ቀን 2008 ዓ.ም

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም አምስት በዚች ቀን የከበረች ሶፊያ ከሁለት ልጆቿ አክሶስና በርናባ ከሚባሉት ጋር በሰማዕትንት ሞተች፡፡

ይችም ቅደስት አስቀድማ አረማዊ ነበረች፣ ወላጆቿም ጣዖታትን የሚያመልኩ ናቸው፡፡ እርሷም በልቧ አስተዋለች፣ መረመረችም፣ የወላጆቿ ሃይማኖት ከንቱ እንደሆነ ተረዳች፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ መኖፌ ኤጲስ ቆጶስ ሔዳ ክብር ይግባውና በክርስቶስ ታመነች፡፡ እንዲህም አለችው፤ በሕያው አምላክህ አምኛለሁና አጥምቀኝ እርሱም ሃይማኖትን፣ የቤተ ክርስቲያንም ሕግ አስተማራት፡፡ ከዚህም በኋላ ከልጆቿ ጋር በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃት፡፡

ከዚህም በኋላ የሀገር ሰዎች ለአማልእክት መስገድን ትታ ክርስቲያን እንደሆነች በገዢው በክላድያኖስ ዘንድ ወነጀሏት፡፡ ገዢውም ወደ እርሱ አስቀርቦ መረመራት፡፡ እርሷም ክብር ይግባውና በክርስቶስ አመነች እንጂ አልካደችም፣ ከልጆቿም ጋር ብዙ ሥቃይን አሠቃያት፡፡

በሥቃይም ውስጥ ላሉ ልጆቿ ታስታግሳቸውና ታጽናናቸው ነበር፣ እንዲህም ትላቸው ነበር፡፡ ልጆቼ ጠንክሩ፣ ጨክኑ የአንጌቤንዋን እመቤት ሶፍያን እመስላታለሁ፤ እናንተም ጲስጢስ፤ አላጲስ አጋጲስ የተባሉ ልጆቿን ምሰሉ፣ እነርሱም እንዲህ ብለው መለሱላት፣ እናት ሆይ እኛ ፍለጋሽን እንከተላለንና ስለእኛ አትፈሪ ይህንንም በሚባባሉ ጊዜ ከእናታቸው ጋር ተሳሳሙ፡፡

ገዢውም ሲሳሳሙ አይቶ ደናግል ልጆቿ እንዲፈሩ እናታቸውን በጅራፍ ይገርፏት ዘንድ አዘዘ፡፡ ያን ጊዜም የእግዚአብሔር መልአክ ከሰማይ ወርዶ እናታቸውን ከግርፋት ሲሠውራት አዩ፡፡

ዝንጉዎችም ይገርፏት ዘንድ ባራቆቷት ጊዜ በዚያን ሰዓት እንዲህ በማለት ትጮህ ነበር፡፡ ዓለሙን ሁሉ በፈጠረ በእውነተኛ አምላክ በእግዚአብሔር የማምን ክርስቲያናዊት ነኝ፣ ያን ጊዜም ገዢው ምላሷን ከሥሩ እንዲቆርጡ አዘዘ፡፡ እርሷ ግን መጮህንና መናገርን አላቋረጠችም፡፡

ከዚህም በኋላ ገዢው ወደ እሥር ቤት እንዲወስዷት አዘዘ፤ ትሸነግላትም ዘንድ ሚስቱን ወደእርሰዋ ላከ፡፡ እርሰዋ ግን ምንም አልመለሰችላትም፡፡ ራሷንም በሰይፍ ይቆርጧት ዘንድ አዘዘ፤ የድል አክሊልም ተቀበለች፡፡ አንዲት ሴትም መጥታ ሥጋዋን በጭልታ ወሰደች፣ ወደ ቤቷም አስገብታ በፊቷ መብራትን አኖረች፡፡

ከዚህም በኋላ ልጆቿን ጠርቶ እሺ ይሉት ዘንድ አስፈራራቸው፣ እምቢ ባሉትም ጊዜ እያከታተለ ራሳቸውን አስቆረጠ፣ ምሥክርነታቸውንና ተጋድሏቸውንም ፈጸሙ፡፡ ከመቃብራቸውም በሽታውንና ደዌውን ሁሉ የሚፈውሱ ብዙ የሆኑ ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ፡፡

ደግ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስም ዜናቸውን በሰማ ጊዜ የቅዱሳት ሰማዕታትን ሥጋቸውን ወደ ቁስጥንጥንያ አፍልሶ ወሰደ፡፡

የሶፍያንና የልጆቿን ዜና ከመስማቱ በፊት ታላላቅና ሰፊ የሆኑ ቤቶች እንዲሠሩ በላይዋም ይቺ ቤት የንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ናት ብለው ጽሑፍ እንዲቀርጹበት አዘዘ፡፡ እነርሱም ንጉሡ እንዳዘዘ ወደ ማታ ሲሆን ይጽፋሉ፣ የእግዚአብሔርም መልአክ ወርዶ ያንን ደምስሶ ይቺ ቤት የሶፍያ ናት ብሎ ይጽፋል፡፡ የሕንፃውም ባለሙያዎች የሚያደርጉትን አጡ፣ መጻፋቸውንም ተዉ፡፡

በአንዲት ቀንም የንጉሥ ልጅ ብቻውን ሲጫወት መልአክ ተገለጸለትና የዚች ቤት ስሟ ማነው አለው፡፡ ሕፃኑም አላወቅሁም አለው፣ መልአኩም ሁለተኛ እንዲህ አለው አባትህን የሶፍያ ቤት ብለህ ሰይማት ብለህ ንገረው ሕፃኑም ተመልሼ እስክመጣ ትጠብቀኛለህን አለው፣ መልአኩ አዎን እጠብቅሃለሁ አለው፡፡

አባቱም ይህን ሰምቶ መልአክ እንደሆነ ዐወቀ፡፡ ሕፃኑንም በመጠበቅ ምክንያት ያ መልአክ ከዚያች ቦታ እንዳይሄድ ብሎ ንጉሡ ልጁን ገደለው፡፡ መልአኩም ሕፃኑን እየጠበቀ እስከዛሬ ድረስ አለ፡፡

የዚያች ቤተ ክርስቲያም ርዝመቷ ሰባት መቶ ዘጠኝ ክንድ ሆነ፣ አግድመቷም ሦስት መቶ ሰባት ክንድ፣ ምሰሶዎቿም ዐራት መቶ፣ ጠረጴዛዎቿም ስምንት፣ የሚያበሩ ዕንቁቿ ዐራት ናቸው፣ ከአጎበሩ በላይ የተቀረጹ ኪሩቤልም በየሁለት ክንፎቻቸው የእግዚአብሔር ሕግ የተጻፈበትን ታቦት ይጋርዳሉ፡፡

ሥጋቸው በውስጡ ያለበትን የቅድስት ሶፍያንና የልጆቿን ሳጥን በታላቅ ምስጋናና ክብር ወደዚያ አስገብተው አኖሩ፡፡

በድኖቻቸውን የሰበሰበች ያቺንም ሴት ከእርሳቸው ጋር ቀበሯት፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡- መጽሐፈ ስንክሳር፣ ከመስከረም እስከ የካቲት፣ አዲስ አበባ፤ ትንሣኤ ማሳተሚያ ደርጅት፣ 1994 ዓ.ም፣ ገጽ 20-21፡፡

የእመቤታችን ዕርገት

ነሐሴ 15 ቀን 2007 ዓ.ም

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ነሐሴ ዐሥራ ስድስት በዚች ቀን አምላክን የወለደች እመቤታችን ድንግል ማርያም ሥጋዋ ወደ ሰማይ ያረገበት መታሰቢያዋ ሆነ፡፡

ከዕረፍቷም በኋላ ከእርሳቸው ስለመለየቷ ሐዋርያት ፈጽሞ እያዘኑ ነበር፡፡

ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ተገለጠላቸው እርሷን በሥጋ ያዩ ዘንድ እንዳላቸውም ተስፋ ሰጣቸው፡፡

ወንጌላዊ ዮሐንስም እስያ በሚባል አገር እያስተማረ ሳለ በነሐሴ ወር ዐሥራ ስድተኛ ቀን ተድላ ደስታ ወደአለባት ገነት በመንፈስ ቅዱስ ተነጠቀ፡፡ የክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን የእመቤታችን ማርያም ሥጋዋ ካለበት ከዕፀ ሕይወት ዘንድ ተቀምጦ አየው፡፡ የንጽሕት እናቱንም ሥጋ ታወጣ ዘንድ ምድርን እንዲጠሩዋት ሰባቱን የመላእክት አለቆች አዘዛቸው እነርሱም የንጽሕት እናቱን ሥጋ ታወጪ ዘንድ እግዚአብሔር አዞሻል አሏት፡፡

ያን ጊዜም ከዕፀ ሕይወት በታች ካለ መቃብር የእመቤታችን ማርያም ሥጋዋ ወጣ፡፡

የክብር ባለቤት ጌታችንም እንዲህ እያለ አረጋጋት፤ የተወደድሽ የወለድሽኝ እናቴ ሆይ ዘላለማዊ ወደ ሆነ መንግሥተ ሰማያት አሳርግሽ ዘንድ ነዪ፡፡

ያን ጊዜም በገነት ያሉ ዕፅዋት ሁሉም አዘነበሉ፤ መላእክት፤ የመላእክት አለቆች ጻድቃን ሰማዕታትም እየሰገዱላትና ፈጽሞ እያመሰገኗት አሳረጓት፡፡

አባቷ ዳዊትም ንግሥት እመቤታችን ወረቀ ዘቦ ለብሳ ደርባ ደራርባ በቀኝህ ትቀመጣለች እያለ በበገና አመሰገናት፡፡

በኪሩቤል ሠረገላ ተቀምጣ ከዐረገች በኃላ በልጆችዋና በፈጣሪዋ ቀኝ በታላቅ ክብር ተቀመጠች፡፡

ወንጌላዊ ዮሐንስም ከእርሷ በረከትን ተቀብሎ ሰግዶላት ተመልሶ ከሰማይ ወረደ፤ ሐዋርያትን ተሰብስበው ስለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋ ፈጽሞ ሲያዝኑና ሲተክዙ አገኛቸው፡፡ እርሱም እንዳየ እንደሰማ ሥጋዋንም በታላቅ ክብር በምስጋና እንዳሳረጓት ነገራቸው፡፡

ሐዋርያትም በሰሙ ጊዜ ዮሐንስ እንዳየና እንደሰማ ባለማየታቸውና ባለመስማታቸው እጅግ አዘኑ፡፡

ከዚህም በኋላ እያዘኑ ሳሉ እነሆ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገለጠላቸውና የፍቅር የአንድነት ልጆች ሰላም ይሁንላችሁ ስለ እናቴ ማርያም ሥጋ ለምን ታዝናላችሁ፡፡ እነሆ እኔ እርስዋን በሥጋ ላሳያችሁ ልባችሁም ደስ ሊለው ይገባዋል አላቸው፡፡ ይህንንም ብሎ ከእርሳቸው ዘንድ ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡

ሐዋርያትም ዓመት ሙሉ ቆዩ የነሐሴም ወር በባተ ቀን ለሐዋርያት ዮሐንስ እንዲህ አላቸው፡፡ አምላክን የወለደች የእመቤታችንን ሥጋዋን ለማየት የተዘጋጀን አድርጎ ያሳየን ዘንድ ኑ ይህን ሁለት ሱባዔ በጾም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንለምነው በልጅዋ በወዳጅዋ ቀኝ ተቀምጣ አይተን በእርሷ ደስ እንዲለን፡፡

በዚያን ጊዜም ዮሐንስ እንዳላቸው በጾም በጸሎት ሱባዔ ያዙ፤ የነሐሴ ወር እንደዛሬ ዐሥራ ስድስተኛ ቀን በሆነ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉንም ሐዋርያት ወደ ሰማይ አወጣቸው፡፡ በታላቅ ክብር በተወደደ ልጅዋ ቀኝ ተቀምጣ ከሥጋዋ ተዋሕዳ ተነሥታ እመቤታችን ማርያምን አዩዋት፡፡ እጆቿንም ዘርግታ የከበሩ ሐዋርያትን እያንዳንዳቸውን ባረከቻቸው በልባቸውም እጅግ ደስ አላቸው፡፡

የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በከበረ ሥጋውና ደሙ ላይ ሠራዔ ካህን ሆነ፡፡ እስጢፋኖስም አዘጋጀ፤ ዮሐንስም በመፍራት ቁሙ አለ፡፡ ሁሉም ሐዋርያት በመሰዊያው ዙሪያ ቆሙ፤ በዚያን ጊዜ ከቶ እንደርሱ ሆኖ የማያውቅ ታላቅ ደስታ ሆነ፡፡

ጌታችንም የቅዳሴውን ሥርዓት በፈጸመ ጊዜ ሥጋውንና ደሙን አቀበላቸው፡፡

ከዚያም በኪሩቤልና በሱራፌል ሠረገላ ተቀምጣ በምታርግ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እናቱን  እመቤታችን ማርያምን እንዲህ ብሎ ተናገራት፡፡ በዚች ቀን የሆነ የዕርገትሽን መታሰቢያ በዓለም ውስጥ እንዲሰበኩ ልጆችሽ  ሐዋርያትን እዘዣቸው፡፡ መታሰቢያሽን የሚያደርገውን ሁሉ ተጠብቆም በዚች ቀን ቅዱስ ቁርባን የሚቀበለውን ኃጢአቱን እደመስስለታለሁ፡፡ የእሳትን ሥቃይ ከቶ አያያትም መታሰቢያሽን ለሚያደርግ ሁሉ በዚች ቀን ለድኆች በስምሽ ለሚመጸውት ቸርነቴ ትገናኘዋለች ይህም ሥጋሽ ወደ ሰማይ ያረገበት ነው፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ክብር ይግባውና ጌታችንን እንዲህ አለቸው ልጄ ሆይ እነሆ በዓይኖቻቸውም አዩ፤ በጆሮዎቻቸውም ሰሙ፤ በእጆቻቸው ያዙ ሌሎችም ታላላቅ ድንቆች ሥራዎችን አዩ፡፡

እመቤታችንም ይህን ስትናገር ጌታችን ሰላምታ ሰጥቷቸው በታላቅ ደስታ ወደ ደብረ ዘይት ተመለሱ፡፡

የተወደዳችሁ ወንድሞች ሆይ በፍጹም ደስታ መታሰቢያዋን እናደርግ ዘንድ ይገባናል፡፡ እርሷ ስለ እኛ ወደተወደደ ልጅዋ ሁልጊዜ ትማልዳለች፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት ይማረን፡፡ በረከቷም ሐዋርያት በሰበሰበዋት ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆች ከሁላችን ጋር ይሁን ለዘላለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡-ስንክሳር ዘወርኀ ነሐሴ

ተራዳኢው መልአክ ቅዱስ ገብርኤል

ሐምሌ 18 ቀን 2007 ዓ.ም.

kedus kerkos eyeleta አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሐምሌ ዐሥራ ዘጠኝ በዚችም ቀን ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስና እናቱ ኢየሉጣ በሰማዕትነት መከራ ተቀበሉ፡፡

ይህም ሕፃን ዕድሜው ሦስት ዓመት ሲሆነው ከሮሜ አገር ወደ ሌላ ሀገር እናቱ ይዛው ሸሸች፤ በዚያም የሸሸችውን መኮንን እለ አስክንድሮስን አገኘችው፡፡

ሰዎችም ነገር ሠሩባት፤ ወደእርሱ አስቀረባትና ስለ አምልኮ ጠየቃት፡፡ እርሷም መኮንን ሆይ ዕድሜው ሦስት ዓመት የሆነው ሕፃን አለ፡፡ አማልክቶችህን ማምለክ መልካም እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ያስረዳን ዘንድ እርሱን ጠይቅ አለችው፡፡

ሕፃኑም ወደአለበት ጭፍራውን ልኮ ወደእርሱ አስመጣው፡፡ ሕፃኑንም ፊቱ ብሩህና ደስተኛ እንደሆነ አየውና አንተ ደስተኛ ሕፃን ሆይ እንዴት ነህ አለው፡፡ ሕፃኑም መልሶ አዎ ለእኔ ደስታ ተጠብቆልኛል፤ ላንተ ግን ኀዘንና ልቅሶ ጥርስ ማፋጨትም ነው፡፡ መጽሐፍ ለዝንጉዎች ተድላ ደስታ የላቸውም ብሏልና አለው፡፡ እግዚአብሔር ኃይልና ንግግርን ሰጥቶታልና ብዙ ተናገረ፡፡ በዚያም ያሉትን እስከ አስደነገጣቸው ድረስ ንጉሡን መኳንንቱንና ጣዖታቱን ረገማቸው፡፡ ከብርታቱም የተነሣ አደነቁ፡፡

መኮንኑም በአፈረ ጊዜ በውስጡ ሰም፤ ጨው፤ ባሩድ፤ሙጫ፤ የዶሮ ማር፤ እርሳስ፤ ብረት፤ ቅንጭብ፤ ቁልቋል፤ጨምራችሁ ታላቅ የብረት ጋን አምጡልኝ ብሎ ጭፍሮቹን አዘዛቸው፡፡

ጭፍሮቹም እንዳዘዛቸው ከአደረጉ በኋላ ያዘዝኸንን ሁሉ ፈጸምን እሳቱ ነዶ ፈልቷል፤ ድምፁ እንደነጎድጓድ ይጮሃል፤ ወላፈኑም እንደ ፀሐይ ነፀብራቅ በሩቅ ይጋረፋል፤ የፍላቱም ኃይል በዐሥራ ዐራት ክንድ ያህል ከፍታ ወደላይ ይዘላል፤ እንግዲህ በውስጡ የሚጣሉትን እዘዝ አሉት፡፡

በዚህ ጊዜ ሕፃኙ ቅርቆስና እናቱ እየሉጣ በክርስቶስ ስም ስለሚያምኑ አስረዋቸው ነበርና ከፍላቱ ይጨምሯቸው ዘንድ ከእሥር ቤት አወጧቸው፡፡ በዚያም ፍላቱ ወደላይ በሚዘል ብረት ጋን ውስጥ ለመጨመር ወሰዷቸው፡፡ የእነዚህን ቅዱሳን አሟሟት ያ ዘንድ በብዙ ሺሀሕ የሚቆጠሩ ሰዎች እንዲሰበሰቡ አዘዘ፡፡

በዚህ ጊዜ ቅድስት ኢየሉጣ የፍላቱን ጩኸት በሰማችና ባየች ጊዜ ተሸበረች፤ ተዘጋጅቶላት ከነበረውም ክብር ልታፈገፍግሞከረች፡፡ ልጇ ቅዱስ ቂርቆስ ግን የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ አደረበት፡፡ እናት ሆይ ከዚህ ከብረት ጋን ግርማ የተነሣ አትፍሪ፤ ድንጋፄም አይደርብሽ፤ አናንያንና አዛርያን ሚሳኤልንም እግዚአብሔር ከእቶነ እሳት እንዳወጣቸው ሁሉ እኛንም ከዚህ ከብረት ጋን ሊያወጣን ችሎታ ያለው መሆኑን አትጠራጠሪ፡፡ እናት ሆይ ከዚህ ከሚያልፈው ዓለም ጭንቅና መከራ ለመዳን ስትይ በማያልፈው በዘለዓለም እሳት ለመቀጣት ትመርጫለሽን፤ ይህስ አይሆንም ይቅርብሽ በአሁኑ ጊዜ እግዚአብሔር በመካከላችን አለና ይረዳናል፡፡ እናት ሆይ ሶስናን ከረበናት/ከመምህራነ አይሁድ/፤ ዳንኤልን ከአፈ አናብስት ያዳነ እሱ እኛንም ከዚህ የጋን ፍላት ያወጣናል፡፡

ይልቁንም በዚህ የብረት ጋን ውስጥ ግዳጃችንን ልንፈጽም ፈቅዶ ከሆነ ኢዮብ ንብረቱንና ገንዘቡን ልጆቹንና ሚስቱን በመጨረሻም የተፈጥሮ አካሉን ባሣጣው ጊዜ እግዚአብሔርን አመሰግነዋለሁ፤ እግዚአብሔር ሰጠ፤ እግዚአብሔር ነሣ/ወሰደ/፤ እግዚአብሔር እንደወደደ አደረገ ከማለት በስተቀር ምንም የተናገረው ነገር እንደሌለ ሁሉ እኛም የእሱን ዓለማ በመከተል ይህን መከራ ልንታገስ ይገባናል አላት፡፡

ነገር ግን እናቱ በዚህ ምክር ልትጽናና ባለመቻሏ ቅዱስ ቂርቆስ ዓይኑን ወደ ሰማይ አቅንቶ አቤቱ አምላኬ ሆይ ይህችን ባሪያህን ከርስትህ የምትለያት ከሆነ እኔን ከባለሟልነትህ መጽሐፍ ፋቀኝ፤ አቤቱ አዝመራውን አቃጥለህ ፍሬውን ልትባርክ ትወዳለህን፤ ይህን እንዳተደርግ ግን ቸርነትህ ትከለክልሃለች፡፡

አቤቱ እንጨቱን ቆርጣችሁ እንድዱት፤ ቅጠሉን ግን ጠብቁት ብለህ ልታዝዝ መለኮታዊ በሕርይህ አይደለም፤ ነገር ግን እንጨቱንም ቅጠሉንም ባንድ ጠብቁት ብለህ ታዝዛለህ እንጂ እንግዲህ በዚህ ምክንያት ይህን ያየ ሁሉ ማዳን የሚችል አምላክ ቢኖራቸውስ ኖሮ ከዚህ እሳት ባልሸሹም ነበር ብሎ አይጠራጠር፡፡

አቤቱ ዲያብሎስም ከባለሥልጣኑ ይልቅ እኔ በረታሁ፤ ቅዱሳኖቹንም ድል ነሳኋቸው ብሎ እንዳይመካ ከመንጋውም አንድ በግ ቀማሁ በማለት እንዳይደነፋ ለእናቴ ጽኑ የሆነ ኃይለ መንፈስ ቅዱስን ስጣት፤ ብሎ በጸለየ ጊዜ ዲያብሎስ ከኢየሉጣ አጠገብ ብን ብሎ ጠፋ፡፡

ከዚህ በኋላ ቅድስት እናቱ ለሰማያዊው መንግሥት አባት የሆንከኝ ልጄ ሆይ ከእንግዲህ አንተ አባቴ ነህ፡፡ እኔም ልጅህ ነኝ አለችው፡፡ ያቺ ከኔ የተወለድክባትም ቀን የተባረከች ናት አለች፡፡

ጌታህ ኃይልን ሰጥቶኛልና የሚጠብቀንን ገድላችንን ፈጽመን ድል እናድርግ እነሆ በብረት ጋኑ ውስጥ የሚነደውን እሳት በማይበት ጊዜ በለምለም ምንጭ ላይ እንደሚወርድ ጠል ሆኖ አይቼዋለሁና አለችው፡፡

እኒህም ቅዱሳን ሕህንን በሚነጋገሩበት ጊዜ በውስጡ አንገትን የሚቆለምም፤ ልብን የሚቀልጥ ሆድን የሚሰነጥቅ ሥርን የሚበጣጣስ መሣሪያ ካለበት የብረት ጋን ወስጥ ጨመሯቸው፡፡

ከዚህ በኋላ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወረደና የብረቱን ጋን እሳት አጠፋው፤ ከቅዱሳኑም አንዳቸውንም ሳያቃጥላቸው የብረቱን ጋን ማቃጠሉን መፍላቱም ፀጥ አለ፡፡

ወንድሞቻችን ሆይ እንግዲህ በጭንቃቸው ጊዜ ገድላቸውን እስኪፈጽሙ ድረስ ይህ መልአክ ከሰማዕታትና ከፃድቃን ጎን እንደማይለይ እወቁ፡፡

ለኃጥአንም ኃጢአታቸው ይቅር ይላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሄር ይጸልይላቸዋል፡፡ እኛም የዚህ የሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል በዓሉን በየወሩ እያከበርን አማላጅና ወዳጅ እናድርገዋ፤ በዚህም በሚበጣውም ዓለም ሊረዳን ይችላልና፡፡

ዳግመኛም እለ እስክንድሮስ ዐሳቡ ሳሳካለት ስለቀረ ዐሥራ ዐራ የሾሉና የጋሉ ብረት ችንካሮች አምጥተው ሰባቱን በእናቱ በኢየሉጣ አካል፤ ሰባቱን በራሱ በቂርቆስ አካል ማለትም ሁለቱን በጆሮዎቹ፤ ሁለቱን በዓይኖቹ፤ ሁለቱን በአፍንጫው፤ አንዱን በልቡ ይቸነክሯቸው ዘንድ ጭፍሮቹን አዘዘ፡፡

ዳግመኛም የሕፃኑን የእራስ ቆዳው ገፈው እሳት ውስጥ ይጨምሩት ዘንድ አዘዘ፡፡ አሁንም መልአኩ መጥቶ ይህንን መከራ ከእሱ አራቀለት፡፡ ቀጥሎም በመቃን ውስጥ ጨምረው በገመድ እንዲጎተቱ አዘዘ፤ ያን ጊዜም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ሕፃኑ ቂርቆስ ወርዶ አጽናናው፤ አረጋጋውም፡፡

ስሙን ለሚጠራና መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፤ እኛንም በቅዱስ ቂርቆስና በኢየሉጣ ጸሎት ይማረን፤ በረከታቸውም ትድረሰን፡፡ ለዘላለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡- ስንክሳር የሐምሌ 19፤ ድርሳነ ገብርኤል ሐምሌ 19

ስንክሳር በሰኔ አሥራ ሁለት ቀን የሚነበብ

ሰኔ 12ቀን 2007 ዓ.ም.

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሰኔ ዐሥራ ሁለት በዚች ዕለት የከበረ የመላእክት አለቃ የመልአኩ የሚካኤል የመታሰቢያውን በዓል ያከብራሉ፡፡

“ወበ እንተዝ ኢየኃፍር እግዚአብሔር ከመ ይትበሃል አምላኮሙ”

(ክፍል 2)

ሰኔ 8 ቀን 2007 ዓ.ም.

በቀሲስ ይግዛው መኰንን

4. ሰማያዊውን ሕይወት ናፋቂዎች ስለሆኑ

ክቡር ዳዊት “በቤትህ የሚኖሩ ሁሉ የተመሰገኑ ናቸው፤ ለዓለምና ለዘለዓለምም ያመሰግኑሃል፡፡ አቤቱ እርዳታው ከአንተ ዘንድ የሆነለት በልቡም የላይኛውን መንገድ የሚያስብ ሰው ምስጉን ነው፡፡” በማለት ሰማያዊውን መናፈቅ እንደሚያስመሰግን በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ተናገረ፡፡ መዝ. 83፥4

ቅዱስ ጳውሎስም የሚጠበቅበትን አገልግሎት ካከናወነ በኋላ “ልሄድ ከክርስቶስም ጋር ልኖር እናፍቃለሁ፤ ከሁሉ ይልቅ እጅግ የሚሻል ነውና፤” በማለት ምድራዊ ያይደለ ሰማያዊ ሕይወት ምን ያህል እንደሚናፈቅ ገልጿል፡፡ ፊል.1፥23 ለዚህ ነው ቅዱሳን በሥጋ የምኞት ፈረስ እንዲጋልቡ፥ በኃጢአት ባሕር እንዲዋኙ፥ በክፉ አሳብ ጀልባ እንዲቀዝፉ የሚፈታተናቸውን ርኩስ መንፈስ በመልካም ሥራቸው በመቃወም ድል የሚያደርጉት፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ “ለእኛም ይገለጥ ዘንድ ካለው ክብር ጋር ቢመዛዘን የአሁኑ ዘመን ሥቃይ ምንም እንዳይደለ አስባለሁ፡፡” በማለት የአሁኑን ችግርና ፈተና ከሚመጣው ጋር በማመዛዘን የተናገረው፡፡ ሮሜ.8፥18

ቅዱስ ኤፍሬምም በውዳሴ ማርያም ጸሎቱ “ሰማዕታት በእውነት የዚህን ዓለም ጣዕም ናቁ፤ ስለ እግዚአብሔርም ሲሉ ደማቸውን አፈሰሱ፤ ስለመንግሥተ ሰማያትም ሲሉ መራራ ሞትን ታገሡ፡፡” በማለት የዚህን ዓለም መከራ መታገሥ ሰማያዊውን ክብር በማስታወስና የሚገኘውን ዋጋ በማመን እንደሆነ ገልጿል፡፡ /የሐሙስ ውዳሴ ማርያም/ ለዚህም ነው ሰማእታት እሳቱን ስለቱን፣ ጻድቃን ግርማ ሌሊቱን፥ ጽምፀ አራዊቱን፣ ጸብአ አጋንንቱን ታግሰው ሥጋቸውን ለነፍሳቸው አስገዝተው የኖሩበት ዐቢይ ምሥጢር፡፡

ሰማዕታት የሚታሰሩበትን ገመድ፣ የሚሰቀሉበትን ግንድ ይዘው ወደ ሞት ሲነዱ ጻድቃንም አስኬማቸውን ደፍተው፣ ደበሎአቸውን ለብሰው፣ ከምግበ ሥጋ ተለይተው ርሃቡን ጥሙን ችለው ሲኖሩ ደስ ይላቸዋል፡፡ ምክንያቱም ከፈጣሪያቸው እንደሚያገኙ ያውቃሉና ነው፡፡ መሬት ፊቷን ወደ ፀሐይ ስታዞር ብርሃን እንደምታገኝ፣ ፊቷን ስትመልስ ደግሞ ጨለማ እንደሚሆን ሳይንሱ ይነግረናል፡፡ የሰው ልጅም ፊቱን ወደ እግዚአብሔር ካዞረ ብርሃን ይሆንለታል፤ ፊቱን ከፈጣሪው ካዞረ ግን ይጨልምበታል፡፡ ኑሮው፣ ትዳሩ፣ መንገዱ ሁሉ የተሳካ እንዲሆን፣ የውስጥ ሰላምን እንዲያገኝ፣ በሚያገኘው ተደስቶ እንዲኖር፣ ሰላም፣ ጤና በረከት ከቤቱ እንዳይርቁ፣ አሸሼ ገዳሜ በሉ፣ አይዟአችሁ ጨፍሩ የሚለውን የጥንት ጠላት የአጋንንት ስብከት በመልካም ሥራ በዝማሬ በማኅሌት በሰዓታት በቅዳሴ፣ በኪዳን ተጠምዶመቃወም ያስፈልጋል፡፡

የዘወትር ስብከት “ሥጋችሁ በነፍሳችሁ ላይ ትንገሥ” የሚል ስለሆነ እኛ ግን ነፍሳችንን በሥጋችን ላይ ልናነግሣት እንደ አባቶቻችን ቅዱስን ሰማያዊውን ናፋቂዎች ልንሆን ያስፈልጋል፡፡ “ድንኳን የሚሆነው ምድራዊ መኖሪያችን ቢፈርስ በሰማይ ያለ በእጅ ያልተሠራ የዘለዓለም ቤት የሚሆን ከእግዚአብሔር የተሠራ ሕንፃ እንዳለን እናውቃለንና፡፡ በዚህ ውስጥ በእውነት እንቃትታለንና፣ ከሰማይም የሚሆነውን መኖሪያችንን እንድንለብስ እንናፍቃለንና ለብሰን ራቁታችንን አንገኝም፡፡” እንዲል፡፡ 2ቆሮ.5፥1

5. ለሌላው አሳቢዎች በመሆናቸው

ለሌላው ማሰብ፥ ለሌላው መጨነቅ፥ ከሚደሰቱ ጋር መደሰት፥ ከሚያዝኑ ጋር ማዘን፥ ችግር የወደቀባቸውን ሰዎች የችግራቸው ተካፋይ መሆን ፈጣሪን መምሰል ነው፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ “በአንድ አሳብ ተስማሙ፣ አንድ ፍቅር፣ አንድም ልብ፣ አንድም አሳብ ይሁንላችሁ፤ ለወገኔ ይጠቅማል በማለት ወይም በከንቱ ውዳሴ ምክንያት አንድ እንኳ አታድርጉ፤ ነገር ግን እያንዳንዱ ባልንጀራው ከራሱ ይልቅ እንዲሻል በትሕትና ይቁጠር፤ እያንዳንዱ ለራሱ የሚጠቅመውን አይመልከት፡፡ ለባልንጀራው ደግሞ እንጂ፡፡

በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረ ይህ አሳብ በእናንተ ዘንድ ደግሞ ይሁን፡፡” በማለት ከራስ ይልቅ ለሌላው ማሰብን እንድናስቀድም ያስተምረናል፡፡ ፊልጰ.2፥1 ታላቁ ሊቅም በሰቆቃወ ድንግል ላይ “ኢየሱስ ስዱድ ተስፋሆሙ ለስዱዳን፡፡ ኢየሱስ ግፉዕ ምስካዮሙ ለግፉዓን፡፡ እግዚአብሔር ማኅደር ዘአልቦ ከመ ነዳያን..” በማለት የጌታችን መሰደድ የተሰደደውን የሰውን ልጅ ለመመለስ እንደሆነ፤ ጌታችን ያለ በደሉ የተገፋው የተገፋ የሰውን ልጅ ሊያድን እንደሆነ፤ እግዚአብሔር ተስፋ፣ ላጡ ተስፋ ማረፊያ ቤት ለሌላቸው ማረፊያ እንደሆነ ይነግረናል፡፡ ይህንን ስለሚያውቁ ቅዱሳን ከራሳቸው በላይ ለሌላው ያስባሉ፡፡

“ይህንን ኀጢአታቸውን ይቅር በላቸው፤ ያለዚያ ግን ከጻፍኸው መጽሐፍ እባክህ ደምስሰኝ አለ፡፡” የሚለውን የታላቁን ሰው የሙሴን ልመና ስንመለከት ምን ያህል ለሌላው ማሰብ እንደሚገባ እንማራለን ዘፀ.32፥32 ዛሬ ቢሆን ምናልባት ሌላውን ደምስሰህ እኔን ጻፍ ሳይባል ይቀራል ትላላችሁ፡፡ ቅዱሳን ግን እንደፈጣሪያቸው ለሌላው አሳቢወች በመሆናቸው “እግዚአብሔር አያፍርባቸውም” ተባለ፡፡

ዛሬም ሰው ለድሃ እጁን ሲዘረጋ እግዚአብሔር ደግሞ የምሕረት እጁን ይዘረጋለታል፡፡ የወደቀ ባልንጀራውን ሲያነሣ እግዚአብሔር እርሱን ከወደቀበት ያነሣዋል፡፡ የተጨነቀውን ሲያጽናና፥ የተጨቆነውን ነጻ ሲያወጣ ተስፋ ለቆረጠው ሲደርስለት በእውነት ዋጋው አይጠፋበትም፡፡ ለዚህ ነው ክቡር ዳዊት “ለችግረኛና ለምስኪን የሚያስብ ምስጉን ነው፤ እግዚአብሔር ይጠብቀዋል፤ ሕያውም ያደርገዋል፡፡” በማለት ያስተማረን፡፡ መዝ. 40፥1 ስለዚህ በዘመናችን ያለውን የወገንተኝነት፥ የትዕቢትና የሥጋዊነትን አስተሳሰብና አመለካከት በወንጌል መሣሪያነት አፈራርሶና ንዶ ለራስ ነጻ በመውጣት ለሌላውም መትረፍ ያስፈልጋል፡፡ ከነዚህ ክፉ ተግባራት ካልተለየን ገና ዛሬም በጨለማ ውስጥ ስላለን እንጠንቀቅ፡፡

“ልጄ ድሃውን ምጽዋቱን አትከልክለው ከሚለምንህ ከድሃውም ዓይኖችህን አትመልስ፡፡ የተራበች ሰውነትን አታሳዝን ያዘነ ሰውንም አታበሳጭ፡፡ ያዘነ ልቡናን አታስደንግጥ፣ የሚለምንህን ሰው አልፈኸው አትሂድ፡፡ የሚገዛልህ ቤተ ሰብህን አትቆጣ፤ ከድሃም ፊትህን አትመልስ፡፡” ካለ በኋላ ቀጥሎ “ከሚለምንህ ሰው ፊትህን አትመልስ፤ በልቡናው አዝኖ ቢረግምህ ፈጣሪው ልመናውን ይሰማዋልና፡፡”

በማለት ምስካየ ኅዙናን፣ ረዳኤ ምንዱባን የሆነ እግዚአብሔር የድሃውን ኀዘን ሰምቶ እንደሚበቀል ይነግረናል፡፡ ሲራ.4፥2 ስለዚህ የነዚህ ቅዱሳን ልጆች የሆን እኛ ፍትሕ ተጓድሎባቸው የሚሰማቸው አጥተው የሚገባቸውን፣ ተነፍገው፣ መከበር ሲገባቸው ተዋርደው ከሰው በታች ሆነው ለሚቆዝሙ ወገኖች ፈጥነን ልንደርስላቸው ይገባል፡፡ “ሳትሞት ለባልንጀራህ በጎ ነገርን አድርግ፡፡” ተብለን ተመክረናልና፡፡ ሲራ.14፥13

6. ለመከራ ራሳቸውን ያዘጋጁ በመሆናቸው

ከላይ እንዳየነው እምነታቸው በማዕበል ቢመታ የማይፈርስ እውነተኛ እምነት ስለሆነ ለመከራ አይበገሩም፡፡ ከእሳቱ ከሰይፉ ከመከራው በስተጀርባ የሚወርድላቸው አክሊለ ሕይወት ስለሚታያቸው ወደሞት ሲነዱ ደስ እያላቸው ይሄዳሉ፡፡ ራሳቸውን ለሞት ራሳቸውን ለስቅላት፣ ራሳቸውን ለእንግልት አዘጋጅተው በሃይማኖት ስለሚኖሩ፣ ፈጣሪ ያዝንላቸዋል፡፡ ደስ ይሰኝባቸዋልም፡፡ ያለ መከራ ዋጋ እንደማይገኝም ስለሚያውቁ “አቤቱ ቅጣኝ ነገር ግን እንዳታዋርደኝ በመጠን ይሁን እንጂ በቁጣ አይሁን፡፡” እያሉ ድሎትን ሳይሆን መከራ ሥጋን ይለምናሉ፡፡ ኤር.1፥24 ሥጋ ሲጎሰም ለነፍስ እንደሚገዛ ይረዳሉ፡፡

“ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል መከራ ወይስ ጭንቀት ወይስ ስደት፣ ወይስ ረሃብ ወይስ ራቁትነት፣ ወይስ ፍርሃት፣ ወይስ ሰይፍ ነውን “ስለ አንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን፣ እንደሚታረዱ በጎች ተቆጥረን” ተብሎ እንደተጻፈ ነው፡፡ በዚህ ሁሉ ግን በወደድን በእርሱ ከአሸናፊዎች እንበልጣለን፡፡ ሞት ቢሆን፣ ሕይወትም ቢሆን፣ መላእክትም ቢሆኑ ግዛትም ፍጥረትም ቢሆን፣ በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ካለ ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየን እንዳይችል ተረድቼአለሁ፡፡” የሚለው የቅዱስ ጳውሎስም ትምህርት የሚያስተምረው ራስን ለመከራ ማዘጋጀትን ነው፡፡ ሮሜ.8፥35

ገበሬ ብርዱን፣ ዝናቡን፣ ፀሐዩን ታግሦ እሾሁን ነቅሎ መሬቱን አለምልሞ ተክል የሚተክለውና ከበቀለም በኋላ የሚኮተኩተው የሚያርመው ፍግ እያስታቀፈ የሚንከባከበው ውኃ እያጠጣ፣ ፀረ ተባይ መድኀኒት እየረጨ ከተባይ የሚጠብቀው፣ ቅጥር ምሶለት፣ አጥር አጥሮለት ከእንስሳት የሚያስጠብቀው በአጠቃላይ ብዙ የሚደክምለት መልካም ፍሬን ለማግኘት ነው፡፡ እንዲህ ከለፋ በኋላ አመርቂ ውጤት ቢያገኝ በልፋቱ ይደሰታል፡፡ በሚቀጥለውም ከመጀመሪያው የበለጠ እንክብካቤ ያደርግለታል፡፡ ካልሆነ ግን ያዝናል፡፡ ተክሉ ፍሬ አልባ ቢሆን ወይም ደግሞ ጣፋጭ ፍሬን እየጠበቀ መራራ ፍሬን ቢያፈራ ከማዘንም አልፎ እንዲቆረጥ ያደርገዋል፡፡ ዮሐ.15፥5፣ ማቴ.21፥18

ሰውም የእግዚአብሔር ተክል ነው፡፡ በቃለ እግዚአብሔር በምክረ ካህን ተኮትኩቶ በረድኤተ እግዚአብሔር አጥርነት ተጠብቆ የሚኖር የእግዚአብሔር የእጁ ሥራ ነው፡፡ ታዲያ ይህንን ስለሚያውቁ ቅዱሳን መልካም ፍሬን አፍርተው በመገኘታቸው እግዚአብሔር ተደስቶባቸዋል፡፡

ፍሬአቸው መራራ የሆኑ ተክሎች /ሰዎች/ ጨለማን ተገን አድርገው ሰው አየን አላየን ብለው ኀጢአትን የሚፈጽሙትን ያህል በእግዚአብሔር ቤት የተተከሉ፣ ፍሬአቸው ያማረ ቅዱሳን ጨለማው ሳይከለክላቸው ጽድቅን ሲሠሩበት ያድራሉ፡፡ በዓለም ላይ ለ5 ሺሕ 5 መቶ ዘመናት ኀጢአት በዓለም ላይ ነግሦ ይኑርም እንጂ በዚህ ኀጢአት በነገሠበት ዘመን ጽድቅን ሲሠሩ የኖሩ አባቶችና እናቶች ነበሩ፡፡ ዛሬም ኀጢአት በዓለማችን ላይ ጠፍንጎ ይዞ እያስጨነቀን እንዳለ ብንረዳም የነዚህ የቅዱሳን አበው በረከት ያደረባቸው በየገዳማቱ ወድቀው ለጽድቅ ራሳቸውን ሲያስገዙ እንመለከታለን፡፡

ማጠቃለያ

አንድን መንፈሳዊ ሥራ መጀመር ብቻውን የጽድቅ ምልክት አይደለም፡፡ ከላይ ያየናቸው የቅዱሳን ሕይወት ጽድቃቸው ከሰውም አልፎ በእግዚአብሔር የተመሰከረላቸው ከመጀመሪያው ይልቅ መጨረሻቸው በማማሩ ነው፡፡ ጀምረው ያቋረጡማ የሚነገርላቸው ማቋረጣቸው እንጂ ጽድቃቸው አይደለም፡፡ እንደሚታወቀው ሳጥናኤል የመላእክት አለቃ ነበር፡፡ አርዮስ ካህን፣ ይሁዳ ከሐዋርያቱ ጋር ተቆጥሮ የነበረ፣ ዴማስ ከአርድዕተ ክርስቶስ ከነ ሉቃስ ጋር ተደምሮ የነበረ እንደሆነ እናውቃለን፡፡ ታዲያ እነዚህ ሰዎች የጀመሩትን መንፈሳዊ አገልግሎት ችላ ማለታቸው ከሰማይ ወደ ምድር፣ ከክብር ወደ ውርደት፣ ከሹመት ወደ ሽረት፣ ከማግኘት ወደ ማጣት ተወረወሩ እንጂ ምን ጠቀማቸው? በትናንት ማንነት ብቻ ድኅነት አይገኝም፡፡ ዛሬ የማያሳፍር ሥራን መሥራት እንጂ፡፡

ትናንት ዘመነኞች፣ ቅንጦተኞች፣ ኩሩዎች፣ የነበሩ ነገሥታት ወመኳንንት ዛሬ የት አሉ? በሀብታቸው የሚኩራሩ፣ በሥልጣናቸው የሚንጠራሩ፣ ፊታቸውን ከፈጣሪ ያዞሩ ሁሉ ጊዜ አልፎባቸው ገንዘባቸው፣ ሥልጣናቸው፣ ወገናቸው አላድናቸው ብሎ በጸጸት አለንጋ ከመገረፍ ውጪ ምንም አላገኙም፡፡ ስለዚህ ከዚህ መማር የዘመኑ ትውልድ ድርሻ ነው፡፡ በሃይማኖት ቁመው ከተጠቀሙት በሃይማኖት የመቆምን ጥቅም፣ ወድቀው ከተጎዱት የመውደቅን አስከፊነትና ጉዳት መማር እንችላለን፡፡

ስለዚህ ቆም ብለን ራሳችንን እንመርምር፡፡ በየመሥሪያ ቤታችን የምንሠራው ሥራ ሰውንና እግዚአብሔርን የሚያስደስት ነው ወይስ የሚያሳዝን፣ በአርአያውና በአምሳሉ ፈጥሮ በተለይ በሐዲስ ኪዳን “ከአሁን በኋላ ባሮች አልላችሁም፣ ልጆች ብያችኋለሁ፡፡” በማለት ያቀረበውን ፍጹምም የወደደውን የሰው ልጅ እንዴት እያየነው ነው? እውነት የምንሠራው ሥራ አሳፋሪ ነው ወይስ የሚያስደስትና የሚያስከብር? የሚለውን ጠይቀን ለራሳችን ምላሽ ልንሰጥ ያስፈልጋል፡፡ ያለ እግዚአብሔር መልካም ፈቃድ መልካምን ማድረግም አይቻልምና ለመልካም ሥራ እንዲያነሣሣን ኃይሉን ብርታቱንም እንዲሰጠን መልካም ፈቃዱ ይሁንልን፡፡

የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል፡፡ (ዮሐ.16፡13)

ግንቦት 23ቀን 2007ዓ.ም

ዲ/ን ሚክያስ አስረስ

ይህች ዓለም ከእውነትን የራቀች መኖሪያዋን ሐሰት ያደረገች መሆኗ ይታወቃል፡፡ ሰው ማንነቱን አጥቶ በበደል ምክንያት በሐሰት ሰጥሞ ኖሯል፡፡ ሰው በፈቃዱ ጥመት ምክንያት ከሚፈጽማቸው በደሎች ትልቁ በደል ውሸት ነው፡፡ ውሸት ተሸንፎ ይወድቃል፤ ከሕይወት ይርቃል፡፡ የኀጣውእ ሁሉ ራስ ሐሰት ናት፡፡ ለዚህ ነው ክፋትን ከራሱ አንቅቶ የበደለ ዲያብሎስ አቡሃ ለሐሰት፤ የሐሰት አባት(ዮሐ.8፡44) የተባለው፡፡

አዳም እና ሔዋንን ለሞት ያደረሰ ያልሆኑትን፤ ሊሆኑ የማይችሉትን እንሆናለን ብሎ ከሐሰት ጋር መተባበራቸው ነው፡፡ ሐሰት የሆኑትንና የተሰጣቸውን እንደዘነጉ አድርጎ ማግኘት የማይችሉትን የባሕርይ አምላክነትን አስመኛቸው፡፡ እነርሡ በበደል ወድቀው፤ ከገነት ርቀው ልጆችን በመውለድ ሲባዙ ሐሰት ግዛቷን አስፍታ በኃይል በርትታ እውነት እስኪገለጥ ድረስ ቆየች፡፡ እውነት እግዚአብሔር በሰው ባሕርይ ሲገለጥ የእውነት መንገድን (ሃይማኖትን) ዳግመኛ ሰጠ፡፡ የዓለም መድኃኒት ክርስቶስ ከፈጸመው ድኅነት ለመሳተፍ ሰው ሐሰት ከተባሉ አምልኮ ጣዖት፣ ራስ ወዳድነት እና ሴሰኝነት ርቆ በእውነት ሊኖር የግድ ነው፡፡ እርሡ ሁሉ እንዲድኑ እውነትንም እንዲያውቁት ይወዳልና፡፡(1.ጢሞ 2፡4) እንደተባለ ሰውም ቢሆን በእውነት ጸንቶ ለመኖር በመፍቀድ ከእግዚአብሔር ጋር በፈቃድ አንድ መሆን አለበት፡፡

የአንድነት ሦስትነት ምሥጢር የተገለጠው አምላክ ሰው በመሆኑ ነው፡፡ ይልቁንም ሰው ወደዚህ እውነት እንዲመጣ የሚያደርገው መንፈስ ቅዱስ ወደ ደቀመዛሙርት የወረደው ሰው የሆነ አምላክ ክብሩን በመስቀል ሞት ሲገልጽ ነው፡፡ ክርስቶስ ስለእኛ ብሎ በመስቀል ላይ ባይሞት መንፈስ ቅዱስ አይወርድም ነበር፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ ሕይወቱ መንፈስ ቅዱስ እንደሚመጣ አካሉ ለሆነች ለቤተ ክርስቲያንም ሕይወት እንደሚሆናት የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል(ዮሐ 16፡13) በማለት አስቀድሞ ተናገረ፡፡ መንፈስ ቅዱስ መምጣቱ አምላክ ሰው ሆኖ የፈጸመውን ለመረዳት እና ለማመን ለማስቻል ነው፡፡ ክርስቶስን በመድኃኒትነቱ ለመግለጽ ነው፡፡ ለዚህ ነው የተወደደ ሐዋርያ ዮሐንስ መነሻ ያደረግነውን ኃይለ ቃል ከተናገረ በኋላ ወውእቱ ኪያየ ይሴብሕ፤ እርሱ እኔን ይገልጻል፡፡(ዮሐ.16፡14) ያለው፡፡ እንዲሁ በበደል ከወደቀ በኋላም በሥላሴ ፈቃድ በወልድ ሰው መሆን በመንፈስ ቅዱስ መሠጠት ከወደቀበት ተነሥቶ ድኅነት (ሁለተኛ ተፈጥሮ) ተፈጸመለት፡፡ አዳም ሲፈጠር መንፈስ ቅዱስን ተቀብሎ እንደከበረ (ዘፍ.2፡1) እንዲሁ ይኸው መንፈስ ቅዱስ በእሳት አምሳል ለክርስቶስ ደቀመዛሙርት ወረደ፡፡ ጸጋ ሆኖ ተሠጣቸው፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ሰማይ ከማረጉ በፊት የአብን ተስፋ መንፈስ ቅዱስን ደጅ እንዲጸኑ ይኸንንም በኢየሩሳሌም በአንድነት በመቆየት እንዲያደርጉ አዘዛቸው፡፡ (ሉቃ 24፡49) ደቀ መዛሙርቱም መቶ ሃያ ሆነው በኢየሩሳሌም በማርቆስ እናት ቤት አስቀድሞ ምሥጢረ ቁርባን በተመሠረተበት ቦታ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እናት እመቤታችንን በመሐል አድርገው በጸሎት በአንድነት በኢየሩሳሌም ቆዩ፡፡ (ሐዋ.1፡14)፡፡ እመቤታችን ባለችበት መንፈስ ቅዱስ ይወርዳልና፤ አስቀድሞ በወንጌል ቅድስት ኤልሳቤጥ እመቤታችን ወደ እርሷ ስትሄድ “መንፈስ ቅዱስ ሞላባት” (ሉቃ.1፤41 ) ተብሎ እንደተነገረላት፡፡ ከዚያም ረቂቅነቱን እና ኃያልነቱን ሲያጠይቅ መንፈስ ቅዱስ ከወደ ሰማይ እንደ ዐውሎ ነፋስ ባለ ድምፅ መጣ፡፡ ደቀመዛሙርት ባሉበት ቤት ገብቶ ሲመላው የተከፋፈሉ የእሳት ልሳኖች ሆኖ ታያቸው፤ በሁሉም አደረባቸው (ሐዋ.2፡3) ሁሉም ኃይልን ዕውቀትን አገኙ፤ በአገራትም ሁሉ ቋንቋዎች ተናገሩ፡፡ ስለ እውነት ደፋሮች ሆኑ፡፡ በነቢይ እሰውጥ እምነ መንፈስየ ዲበ ኩሉ ዘሥጋ፤ በሥጋ ለባሽ ሁሉ ላይ ከመንፈሴ አፈሳለሁ(አዩ 3፡1) ተብሎ የተነገረው ዛሬ ተፈጸመ፡፡

አንዲት ቤተክርስቲያንን በአንድነቷ ለዘለዓለም የሚያኖራት እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ እንዲህ ስንል አብን እና ወልድን በመተው አይደለም፡፡ የሦስቱም ማደርያ ትሆናለች እንጂ፡፡ ዛሬም በቤተ ክርስቲያን ምሥጢራትን ይገልጥልን ዘንድ አለ፡፡ â€Ãƒ‚¹ÃƒÃ‚¢€Ãƒ‚¹እኛስ የክርስቶስ ልብ አለን፡፡â€Ãƒ‚ºÃƒÃ‚¢€Ãƒ‚º (1ቆሮ.2፡16) እንዳለ ብርሃን ቅ/ጳውሎስ፡፡ የክርስቶስ ልብ የሆነ እግዚአብሔር አብ â€Ãƒ‚¹ÃƒÃ‚¢€Ãƒ‚¹እኛâ€Ãƒ‚ºÃƒÃ‚¢€Ãƒ‚º በተባልን በቤተ ክርስቲያን አለ ማለቱ ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተለየ አካሉ ሰው ሆኖ በሕማሙ እና በሞቱ፤ በትንሣኤውና በዕርገቱ ድኅነትን ፈጸመ፡፡ አሁንም በቤተ ክርስቲያን እርሱ ሊቀ ካህናት ኢየሱሰ ክርስቶስ በአባቶች ካህናት ላይ በረድኤት አድሮ ምሥጢራትን ይፈጽማል፡፡ â€Ãƒ‚¹ÃƒÃ‚¢€Ãƒ‚¹ኦ እግዚኦ በከመ አሜሃ ዘንተ ኅብሰተ ባርክ ወቀድስ ወወሃብ፤ አቤቱ እንደዚያን ጊዜ ይህን ኅብስት ባርከው ሥጋህን አድርገው ቁረሰው እንዲሁ ስጥâ€Ãƒ‚ºÃƒÃ‚¢€Ãƒ‚º (ቅዳሴ ማርያም) የተባለውን ማስተዋል በቂ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ የአንድነት መንፈስ ነውና፡፡

ከእግዚአብሔር ጋር አንድ የሚያደርጉንን ምሥጢራት ራሱ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ያከናውናቸዋል፡፡ ካህኑ ውኃውን ሲባርኩት በዕለት ዓርብ ከጌታ ጎን የፈሰሰውን ውሃ ያደርግላቸዋል በዚያ ማየገቦ (የጎን ውሃ) አዲስ አማኝ ተጠምቆ የእግዚአብሔርን ልጅነት አግኝቶ ከእርሱ ጋር አንድ ይሆናል፡፡ ካህናቱ የከበረውን የቅዳሴ ጸሎት ሲጀምሩ ያቀረቡትን ኅብስት እና ወይን እንዲህ ነው በማይባል አኳኋን የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋ እና ደም የሚያደርገው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ከእርሱ ጋር አንድነትን እናገኛለን፡፡ ሰው ንስሐ እንዲገባ በበደሉ እንዲጸጸት በሰው ውስጥ ሆኖ የንስሐን ደወል የሚያሰማው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ይህን የንስሐ ጥሪ በእሽታ ቢቀበል ዳግመኛ ከቤተ ክርስቲያን ተደምሮ ከእግዚአብሔር ጋር በአንድነት ይኖራል፡፡ ጥሪውን በእንቢታ አልፎ እስከ ሞት ድረስ በዚህ ቢጸና መንፈስ ቅዱስን ተሳድቧልና ኃጢአቱ አይሠረይለትም፤ ከሞት በኋላ ንስሐ የለምና፡፡ (ማቴ. 12፡32) ለተቀበሉት ግን አሁንም መንፈስ ቅዱስ አንድነትን የሚያድል መሆኑን እናስተውል፡፡ እኛ እርስ በእርስ በአንዲት ሃይማኖት ተባብረን ከአንድ መሥዋዕት ተካፍለን አንድ ርስትን ተስፋ በማድረግ አንድ የሚያደርገን እርሱ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡

በቅዳሴያችን ሀበነ ንኅበር በዘዚአከ መንፈስ ቅዱስ፤ ባንተ ህልውና ባለ መንፈስ ቅዱስ አንድ አድራጊነት አንድ እንሆን ዘንድ አንድ መሆንን ሰጠን፡፡ በማለት አንድ አድራጊያችን እርሱ እንደሆነ እንመሠክራለን፡፡ አንድ ሆነን በአንድነት ከጸናን እንደ ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ለመቀበል የበቃን የተዘጋጀን ስለምንሆን ቀጥለን ፈኑ ጸጋ መንፈስ ቅዱስ ላዕሌነ፤ በእኛ ላይ ጸጋ የሚባል መንፈስ ቅዱስን ላክበማለት እንለምናለን፡፡ በዚህ በግዙፉ ዓለም ባለች ሰማያዊ መንግሥት በቤተ ክርስቲያን እንደተባበርን በዚያች ለምድራውያን ሰዎች ዓለም ሳይፈጠር በተዘጋጀችው መንግሥት አንድ እንሆናለን፡፡ ሐዋርያው መንግሥተ ሰማያትን የእግዚአብሔር መንግሥት በመንፈስ ቅዱስ የሆነ ደስታ እንጂ መብል መጠጥ አይደለምና(ሮሜ.14፡17) በማት ይናገርላታል፡፡

መንፈስ ቅዱስ በወረደላቸው ዕለት ደቀ መዛሙርት ምሥክርነታቸውን ማሠማት ጀመሩ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ህዝቡ በተሰበሰቡበት በዚያን ዕለት መንፈስ ቅዱስ መውረዱና እነርሱ በቋንቋዎች መናገራቸው እንዲሁ እንደ እንግዳ ደርሶ የመጣ ሳይሆን አስቀድሞ በነቢያት ትንቢት የተነገረ መሆኑን አስታወቀ፡፡ ዳግመኛም ክርስቶስ በነቢያት እንደተነገረለት ሞቶ ከሙታን እንደተነሣ ሰበከላቸው፡፡ የሚሰሙት ሕዝቡ እርሱ የተናገራቸው ከልባቸው ስለገባ ምን እናድርግ አሉ (ሐዋ 2፡37)፡፡ ነስሑ ወተጠመቁ ኩልክሙ በስሙ ለኢየሱስ ክርስቶስ፤ ንስሐ ግቡ ሁላችሁም በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አምናችሁ ተጠመቁ(ሐዋ 2፡38) ብሎ ቅዱስ ጴጥሮስ መለሰ፡፡ እንዲህ ባለ ሁኔታ ነፍሳት ወደ ቤተክርስቲያን እየተደመሩ ቤተክርስቲያን ከኢየሩሳሌም እስከ ዓለም ዳርቻ ምሥክርነቷን አደረሠች፡፡ እንዲሁ ሰው የክርስትናን ጥምቀት ተጠምቆ ጸጋ መንፈስ ቅዱስን ገንዘብ ካደረገ ከሚኖርበት ከቤቱ ጀምሮ ምሥክር ሆኖ ወደ ዓለም መውጣት እንዳለበት መገንዘብ ይቻላል፡፡ 

ቤተ ክርስቲያን ከእግዚአብሔር ምሥጢራት ተሳትፋ ጸጋ ነሣእነ ወሕይወተ ረከብነ፤ ጸጋን ተቀበልን ሕይወትንም አገኘን፡፡ብላ በዚያው ባለችበት አትቀመጥም፡፡ ምእመናን ይህን የእግዚአብሔርን ቸርነት እንደቀምሱ ለዓለሙ ሁሉ ምሥክር እንዲሆኑ በቅዳሴ ምክንያት ወደ ሰማይ በሕሊና የወጣችው እትዉ በሰላም፤ በሰላም ወደቤታችሁ ግቡ ትላቸዋለች፡፡ በዓለም ሲኖሩ ከፈቃዱ ባይተባበሩ እንደ ክርስቶስ በፍቅር ያገለግሉ ዘንድ፡፡ የቀመሱትን የእግዚአብሔር ፍቅር በምግባራቸው ለዓለም ይመሠክራሉ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ 20

ሚያዝያ 17 ቀን 2007 ዓ.ም.

ስለ ሰማዕታት፤ ስለ አማንያን፤ ስለ ከሃድያን

ቍ.744፡- ብፁዕ ኤጲስ ቆጶስ ያዕቆብና ቅዱስ እስጢፋኖስ በእኛ ዘንድ የከበሩ እንደሆኑ ሰማዕታት በእናንተ ዘንድ የከበሩ ይሁኑ፡፡ እነዚህም በእግዚአብሔር ዘንድ የተመሰገኑ ናቸው፡፡ ትሩፋታቸውም የማይገኝ ነው፡፡

ቍ.747፡- ሰማዕታትም እኔን በሰው ፊት ያመነኝን ሰው ግን እኔም በሰማይ አባቴ ፊት አምነዋለሁ ብሎ ክርስቶስ ስለእነርሱ የተናገረላቸው እነዚህ ናቸው፡፡/ማቴ.10፤32/ በመከራቸው ጊዜ ብትመስሏቸው ስለ ቁርጥ አሳባችሁ ሰማዕትነት ይቆጠርላችኋል፡፡

ቍ.748፡- ሰማዕታትን ከሚረዱዋቸው ወገን አንዱ መከራ ቢያገኘው ብፁዕ ነው፡፡ እርሱ የሰማዕታት ተባባሪያቸው ነውና፡፡ በመከራዎቹም ክርስቶስን መስለው እኛንም ከካህናት ብዙ መከራ አገኘን፡፡ ከእነርሱም ዘንድ ደስ እያለን ወጣን፡፡ ስለመድኃኒታችን ስለ ክርስቶስ መከራን እንቀበል ዘንድ አድሎናልና፡፡ /የሐዋ. 5፤41/ እናንተም እንደዚህ መከራ በተቀበላችሁ ጊዜ ደስ ይበላችሁ፡፡ እናንተ በፍርድ ቀን ትመሰግናላችሁና፡፡

ቍ.749፡- ስለሃይማኖት የሚያሳድዷቸውን ስለጌታችን ትእዛዝ ከአገር ወደ አገር የሚሸሹትን ተቀበሏቸው፤ አሳርፏቸውም፤ ጥቀሟቸውም፤ እንደ ሰማዕታትም አድርጋችሁ አክብሯቸው፡፡ በተቀበላችኋቸውም ጊዜ እናንተ ደስ ይበላችሁ፡፡ ጌታ ክርስቶስ ስለ እኔ ባሳደዷችሁ ጊዜ እናንተ ብፁዓን ናችሁ፤ ፈጽሞ ደስ ይበላችሁ፤ ዋጋችሁ በሰማይ ታላቅ ነውና፡፡ እንደዚሁም ከእናንተ አስቀድመው የነበሩ ነቢያትን አሳደዷቸው፡፡ እኔን ካሳደዱ ግን ዳግመኛ እናንተን ያሳድዷችኋል፡፡ ከዚች አገር ቢያሳድዷችሁ ወደ ሌላይቱ አገር ሂዱ ብሏልና፡፡ /ማቴ. 5፤11-12፣ ማቴ. 10፤23/

ቍ.750፡- ዳግመኛም እንዲህ አለ፤ በዚህ ዓለም መከራና ኀዘን ያገኛችኋል፡፡ ወደ አደባባይ ያገቧችኋል፡፡ ለእናንተ ምስክር ሊሆንላችሁ ስለ እኔ ወደ ነገሥታቱና ወደ መኳንንቱ ያደርሷችኋል፡፡ እስከ መጨረሻው የታገሠ እርሱ ይድናል፡፡ ለክርስቶስ እንዳልሆነ የሚክድ ከእግዚአብሔርም ይልቅ ፈጽሞ ራሱን የወደደ ሰው ግን ይቅርታን አያገኝም፡፡ የእግዚአብሔር ጠላት የሰዎች ወዳጅ ሊሆን ወድዷልና፡፡ ስለተባረከችውም መንግሥት ፈንታ የዘለዓለም እሳትን ወድዷልና፡፡ /ማቴ. 10፤17-23/ ስለእርሱም ጌታችን በሰው ፊት የካደኝን ስሜንም የለወጠውን እኔም በሰማያዊ አባቴ ፊት እክደዋለሁ፡፡ እለውጠዋለሁም አለ፡፡ /ሉቃ. 12፤8-9/

ቍ.751፡- እንደዚህም ለእኛ ለደቀ መዛሙርቱ ከእኔ ይልቅ አባቱንና እናቱን ወይም ወንድ ልጁንና ሴት ልጁን የሚወድ እኔን አይመስለኝም፡፡ የሞቱንም መከራ ተሸክሞ ያልተከተለኝ እኔን አይመስለኝም አለ፡፡ ሰውነቱን የሚወድ ይጣላት፤ ሰውነቱን የጣላ ግን በእኔ ዘንድ ያገኛታል፡፡ ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢገዛ ነፍሱን ካጣ ምን ይጠቅመዋል? ሰው ለነፍሱ ቤዛ ምን በሰጠ ነበር፡፡ /ማቴ. 10፤37-39፣ ማቴ. 16፤22-27/ ዳግመኛም ሥጋችሁን የሚገድሉትን ሰዎች አትፍሯቸው፡፡ ነፍሳችሁን ግን መግደል አይቻላቸውም፡፡ ነፍስና ሥጋን አንድ አድርጎ በገሃነም እሳት መቅጣት የሚቻለውን ፍሩት እንጂ አለ፡፡ /ሉቃ. 12፤4-5፣ ማቴ. 10፤28/

ቍ.754፡- ብንጨነቅም ኃላፊውን ዘመን ስለመፍራት ሃይማኖታችንን አንለውጥ፡፡ አንዱስ እንኳ አለኝታውን ቢክድ ይኸውም የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ለጥቂትም ዘመን ከሚሆነው ሞት የተነሣ ቢፈራ ድኅነት በሌለበት በጸና ደዌ ነገ ቢያዝ ከዚች ሕይወት የተለየ ይሆናል፡፡ የወዲያውንም ዓለም ያጣል፡፡ ልቅሶ፤ ጥርስ ማፋጨት ባለበት በጨለማ ውስጥ ለዘለዓሙ ይኖራል፡፡ /ማቴ. 8፤13/

ቍ.755 እና 756፡- ያልተጠመቀ ሰውም ልቡ አይዘን፡፡ ስለ ክርስቶስ የተቀበለው መከራ የተመረጠ ጥምቀት ይሆንለታልና፡፡ የሞቱን ምሳሌ በተቀበለ ጊዜ በጌታ አምሳል ሞቷልና፡፡ ሁለት ልብ አይሁን፡፡ እነርሱ ቢገድሉት እርሱም ቢገደል ይጸድቃልና፤ በደሙ ብቻ ተጠምቋልና፡፡

ቍ.761፡- በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አምነው ደማቸውን ላፈሰሱ ሁሉ ባረፉበት ቀን መታሰቢያቸውን ያድርጉላቸው፡፡

ቍ.765:- በሰማዕታት በዓል የሚሰበሰቡትን ሰዎች የሚንቃቸው ሰው ትዕቢትን የተመላ ነውና የተወገዘ /የተለየ/ ይሁን፡፡

ቍ.766፡- ምእመናን የክርስቶስን ሰማዕታት ትተው ዓላውያን ሰማዕታ ወደሚሏቸው ቦታ መሄድ አይገባቸውም፡፡ ስለ ክርስቶስ ፍቅር መጋደላችን እንዴት መሆን እንደሚገባው እነሆ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ጻፈ፤ ወደ ሮሜ ሰዎች በላከው መልእክቱ እንዲህ አለ፤ የክርስቶስን ፍቅር ማን ያስተወናል? መከራ ነውን፤ እስራት ነውን፤ ስደት ነውን ረሃብ ነውን፤ መራቆት ነውን መጣላት ነውን፤ ሰይፍ ነውን፤ ስለአንተ ዘወትር ይገደላሉና እንደሚታረዱም በጎች ን ተብሎ እንደተጻፈ፡፡ በዚህ ሁሉ መከራ የወደደን በመውደዳችን እኛ ድል እንነሳለን፤ እኔም ሊለየኝ የሚችል እንደሌለ አምናለሁ፡፡ ሞት ቢሆን፤ ሕይትም ቢሆን፤ መላእክት ቢሆኑ፤ አለቆችም ቢሆኑ፤ አሁን ያለውም ይመጣም ዘንድ ያለው ሥራ ሁሉ ቢሆን ኃይለኞችም ቢሆኑ፤ ላይኛውም ቢሆን፤ ታችኛውም ቢሆን በኢየሱስ ክርስቶስ ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየኝ አይችልም፡፡ /ሮሜ. 8፤35-39/