kedus kerkos eyeleta

ተራዳኢው መልአክ ቅዱስ ገብርኤል

ሐምሌ 18 ቀን 2007 ዓ.ም.

kedus kerkos eyeleta አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሐምሌ ዐሥራ ዘጠኝ በዚችም ቀን ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስና እናቱ ኢየሉጣ በሰማዕትነት መከራ ተቀበሉ፡፡

ይህም ሕፃን ዕድሜው ሦስት ዓመት ሲሆነው ከሮሜ አገር ወደ ሌላ ሀገር እናቱ ይዛው ሸሸች፤ በዚያም የሸሸችውን መኮንን እለ አስክንድሮስን አገኘችው፡፡

ሰዎችም ነገር ሠሩባት፤ ወደእርሱ አስቀረባትና ስለ አምልኮ ጠየቃት፡፡ እርሷም መኮንን ሆይ ዕድሜው ሦስት ዓመት የሆነው ሕፃን አለ፡፡ አማልክቶችህን ማምለክ መልካም እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ያስረዳን ዘንድ እርሱን ጠይቅ አለችው፡፡

ሕፃኑም ወደአለበት ጭፍራውን ልኮ ወደእርሱ አስመጣው፡፡ ሕፃኑንም ፊቱ ብሩህና ደስተኛ እንደሆነ አየውና አንተ ደስተኛ ሕፃን ሆይ እንዴት ነህ አለው፡፡ ሕፃኑም መልሶ አዎ ለእኔ ደስታ ተጠብቆልኛል፤ ላንተ ግን ኀዘንና ልቅሶ ጥርስ ማፋጨትም ነው፡፡ መጽሐፍ ለዝንጉዎች ተድላ ደስታ የላቸውም ብሏልና አለው፡፡ እግዚአብሔር ኃይልና ንግግርን ሰጥቶታልና ብዙ ተናገረ፡፡ በዚያም ያሉትን እስከ አስደነገጣቸው ድረስ ንጉሡን መኳንንቱንና ጣዖታቱን ረገማቸው፡፡ ከብርታቱም የተነሣ አደነቁ፡፡

መኮንኑም በአፈረ ጊዜ በውስጡ ሰም፤ ጨው፤ ባሩድ፤ሙጫ፤ የዶሮ ማር፤ እርሳስ፤ ብረት፤ ቅንጭብ፤ ቁልቋል፤ጨምራችሁ ታላቅ የብረት ጋን አምጡልኝ ብሎ ጭፍሮቹን አዘዛቸው፡፡

ጭፍሮቹም እንዳዘዛቸው ከአደረጉ በኋላ ያዘዝኸንን ሁሉ ፈጸምን እሳቱ ነዶ ፈልቷል፤ ድምፁ እንደነጎድጓድ ይጮሃል፤ ወላፈኑም እንደ ፀሐይ ነፀብራቅ በሩቅ ይጋረፋል፤ የፍላቱም ኃይል በዐሥራ ዐራት ክንድ ያህል ከፍታ ወደላይ ይዘላል፤ እንግዲህ በውስጡ የሚጣሉትን እዘዝ አሉት፡፡

በዚህ ጊዜ ሕፃኙ ቅርቆስና እናቱ እየሉጣ በክርስቶስ ስም ስለሚያምኑ አስረዋቸው ነበርና ከፍላቱ ይጨምሯቸው ዘንድ ከእሥር ቤት አወጧቸው፡፡ በዚያም ፍላቱ ወደላይ በሚዘል ብረት ጋን ውስጥ ለመጨመር ወሰዷቸው፡፡ የእነዚህን ቅዱሳን አሟሟት ያ ዘንድ በብዙ ሺሀሕ የሚቆጠሩ ሰዎች እንዲሰበሰቡ አዘዘ፡፡

በዚህ ጊዜ ቅድስት ኢየሉጣ የፍላቱን ጩኸት በሰማችና ባየች ጊዜ ተሸበረች፤ ተዘጋጅቶላት ከነበረውም ክብር ልታፈገፍግሞከረች፡፡ ልጇ ቅዱስ ቂርቆስ ግን የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ አደረበት፡፡ እናት ሆይ ከዚህ ከብረት ጋን ግርማ የተነሣ አትፍሪ፤ ድንጋፄም አይደርብሽ፤ አናንያንና አዛርያን ሚሳኤልንም እግዚአብሔር ከእቶነ እሳት እንዳወጣቸው ሁሉ እኛንም ከዚህ ከብረት ጋን ሊያወጣን ችሎታ ያለው መሆኑን አትጠራጠሪ፡፡ እናት ሆይ ከዚህ ከሚያልፈው ዓለም ጭንቅና መከራ ለመዳን ስትይ በማያልፈው በዘለዓለም እሳት ለመቀጣት ትመርጫለሽን፤ ይህስ አይሆንም ይቅርብሽ በአሁኑ ጊዜ እግዚአብሔር በመካከላችን አለና ይረዳናል፡፡ እናት ሆይ ሶስናን ከረበናት/ከመምህራነ አይሁድ/፤ ዳንኤልን ከአፈ አናብስት ያዳነ እሱ እኛንም ከዚህ የጋን ፍላት ያወጣናል፡፡

ይልቁንም በዚህ የብረት ጋን ውስጥ ግዳጃችንን ልንፈጽም ፈቅዶ ከሆነ ኢዮብ ንብረቱንና ገንዘቡን ልጆቹንና ሚስቱን በመጨረሻም የተፈጥሮ አካሉን ባሣጣው ጊዜ እግዚአብሔርን አመሰግነዋለሁ፤ እግዚአብሔር ሰጠ፤ እግዚአብሔር ነሣ/ወሰደ/፤ እግዚአብሔር እንደወደደ አደረገ ከማለት በስተቀር ምንም የተናገረው ነገር እንደሌለ ሁሉ እኛም የእሱን ዓለማ በመከተል ይህን መከራ ልንታገስ ይገባናል አላት፡፡

ነገር ግን እናቱ በዚህ ምክር ልትጽናና ባለመቻሏ ቅዱስ ቂርቆስ ዓይኑን ወደ ሰማይ አቅንቶ አቤቱ አምላኬ ሆይ ይህችን ባሪያህን ከርስትህ የምትለያት ከሆነ እኔን ከባለሟልነትህ መጽሐፍ ፋቀኝ፤ አቤቱ አዝመራውን አቃጥለህ ፍሬውን ልትባርክ ትወዳለህን፤ ይህን እንዳተደርግ ግን ቸርነትህ ትከለክልሃለች፡፡

አቤቱ እንጨቱን ቆርጣችሁ እንድዱት፤ ቅጠሉን ግን ጠብቁት ብለህ ልታዝዝ መለኮታዊ በሕርይህ አይደለም፤ ነገር ግን እንጨቱንም ቅጠሉንም ባንድ ጠብቁት ብለህ ታዝዛለህ እንጂ እንግዲህ በዚህ ምክንያት ይህን ያየ ሁሉ ማዳን የሚችል አምላክ ቢኖራቸውስ ኖሮ ከዚህ እሳት ባልሸሹም ነበር ብሎ አይጠራጠር፡፡

አቤቱ ዲያብሎስም ከባለሥልጣኑ ይልቅ እኔ በረታሁ፤ ቅዱሳኖቹንም ድል ነሳኋቸው ብሎ እንዳይመካ ከመንጋውም አንድ በግ ቀማሁ በማለት እንዳይደነፋ ለእናቴ ጽኑ የሆነ ኃይለ መንፈስ ቅዱስን ስጣት፤ ብሎ በጸለየ ጊዜ ዲያብሎስ ከኢየሉጣ አጠገብ ብን ብሎ ጠፋ፡፡

ከዚህ በኋላ ቅድስት እናቱ ለሰማያዊው መንግሥት አባት የሆንከኝ ልጄ ሆይ ከእንግዲህ አንተ አባቴ ነህ፡፡ እኔም ልጅህ ነኝ አለችው፡፡ ያቺ ከኔ የተወለድክባትም ቀን የተባረከች ናት አለች፡፡

ጌታህ ኃይልን ሰጥቶኛልና የሚጠብቀንን ገድላችንን ፈጽመን ድል እናድርግ እነሆ በብረት ጋኑ ውስጥ የሚነደውን እሳት በማይበት ጊዜ በለምለም ምንጭ ላይ እንደሚወርድ ጠል ሆኖ አይቼዋለሁና አለችው፡፡

እኒህም ቅዱሳን ሕህንን በሚነጋገሩበት ጊዜ በውስጡ አንገትን የሚቆለምም፤ ልብን የሚቀልጥ ሆድን የሚሰነጥቅ ሥርን የሚበጣጣስ መሣሪያ ካለበት የብረት ጋን ወስጥ ጨመሯቸው፡፡

ከዚህ በኋላ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወረደና የብረቱን ጋን እሳት አጠፋው፤ ከቅዱሳኑም አንዳቸውንም ሳያቃጥላቸው የብረቱን ጋን ማቃጠሉን መፍላቱም ፀጥ አለ፡፡

ወንድሞቻችን ሆይ እንግዲህ በጭንቃቸው ጊዜ ገድላቸውን እስኪፈጽሙ ድረስ ይህ መልአክ ከሰማዕታትና ከፃድቃን ጎን እንደማይለይ እወቁ፡፡

ለኃጥአንም ኃጢአታቸው ይቅር ይላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሄር ይጸልይላቸዋል፡፡ እኛም የዚህ የሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል በዓሉን በየወሩ እያከበርን አማላጅና ወዳጅ እናድርገዋ፤ በዚህም በሚበጣውም ዓለም ሊረዳን ይችላልና፡፡

ዳግመኛም እለ እስክንድሮስ ዐሳቡ ሳሳካለት ስለቀረ ዐሥራ ዐራ የሾሉና የጋሉ ብረት ችንካሮች አምጥተው ሰባቱን በእናቱ በኢየሉጣ አካል፤ ሰባቱን በራሱ በቂርቆስ አካል ማለትም ሁለቱን በጆሮዎቹ፤ ሁለቱን በዓይኖቹ፤ ሁለቱን በአፍንጫው፤ አንዱን በልቡ ይቸነክሯቸው ዘንድ ጭፍሮቹን አዘዘ፡፡

ዳግመኛም የሕፃኑን የእራስ ቆዳው ገፈው እሳት ውስጥ ይጨምሩት ዘንድ አዘዘ፡፡ አሁንም መልአኩ መጥቶ ይህንን መከራ ከእሱ አራቀለት፡፡ ቀጥሎም በመቃን ውስጥ ጨምረው በገመድ እንዲጎተቱ አዘዘ፤ ያን ጊዜም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ሕፃኑ ቂርቆስ ወርዶ አጽናናው፤ አረጋጋውም፡፡

ስሙን ለሚጠራና መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፤ እኛንም በቅዱስ ቂርቆስና በኢየሉጣ ጸሎት ይማረን፤ በረከታቸውም ትድረሰን፡፡ ለዘላለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡- ስንክሳር የሐምሌ 19፤ ድርሳነ ገብርኤል ሐምሌ 19