Emebetachin-Eriget

“አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፥ አንተና የመቅደስህ ታቦት” /መዝ.131፥8/

ነሐሴ 14 ቀን 2006 ዓ.ም.

መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

Emebetachin-Erigetሰላም ለፍልሰተ ሥጋኪ መካነ ፍሥሐ ምጡቀ ፤ በአእባነ ባህርይ ዘተነድቀ ፤ማርያም ደብተራ እንተ ኢትትከደኒሠቀ፤እመቤቴ ማርያም ሆይ ምጡቅና ሩቅ ወደሚሆን የደስታ ቦታ ላረገ ሥጋሽ ሰላምታ ይገባል ፡፡ ይኸውም ኅብሩ ሊመረምሩት በማይቻል ዕንቊ የታነፀ ሕንፃ ይገኝበታል፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አዳም አባታችን እግዚአብሔርን በድሎ፣ ክብሩን አጥቶ፣ ሞተ ሥጋ ሞተ ነብስ ተፈርዶበት፣ ከገነት ሲባረር ፤ ምህረትና ቸርነት የባህሪው የሆነው አምላክ ይቅር ይለው፣ ወደ ቀደመ ክብሩ ይመልሰው ዘንድ ተማጽኗል፡፡ እግዚአብሔር አምላክም የአዳምን ማዘን፣ መጸጸት ፣ ንስሀ መግባት ተመልክቶ 5500 ዘመን ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ ስደትህን በስደቴ፣ ሞትህን በሞቴ አጥፍቼ የቀደመ ክብርህን መልሼ ያጣኸውን ርስት ገነት መንግስተ ሰማያት አወርስሃለሁ፡፡ገላ4፡4 በማለት ቃል ኪዳን ገብቶለታል፡፡

አዳም አባታችን ቃል ኪዳን በተገባለት መሠረት የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ ለእግዚአብሔር ወልድ ማደሪያነት የተመረጠች፣ ለአዳም እና ዘሩ መዳን ምክንያት የሆነች የልጅ ልጅ የተባለችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዳ 15 ዓመት ሲሆናት በቅዱስ ገብርኤል ብስራት የእግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ ማደሪያ ሆነች፡፡ ልጇን በወለደች ወቅት የሰብዓ ሰገልን “የተወለደው የአይሁድ ንጉስ ወዴት አለ” የሚለውን ዜና የሰማ ሄሮድስ የተወለደውን ህጻን ለመግደል አዋጅ አወጀ ፡፡ እመቤታችንም ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስን ለማዳን ወደ ግብጽ ይዛው ተሰደደች ማቴ.2፡12፡፡

የስደት ዘመኑ አልቆ ወደ ኢየሩሳሌም ከተመለሱ በኋላ ኢየሱስ ክርስቶስ 30 ዘመን ሲሆነው ስለመንግስተ እግዚአብሔር ስለ ሰው ልጆች ነጻነት ይሰብክ ጀመር፡፡ ኃላም የአዳም ዘር ሞት ለማጥፋት ፣ባርነትን አጥፍቶ ነጻነትን ለማወጅ በመስቀል ተሰቅሎ ሞተ ፡፡ በሦስተኛው ቀን ተነስቶ ነጻነትን አወጀ፡፡ በዚህ ሁሉ የድኅነት ጉዞ ውስጥ ያልተለየችና ምክንያተ ድኂን የሆነችው እመቤታችን የሰው ልጆች ድኅነት ሲረጋገጥ በተወለደች በ64 ዓመቷ ጥር 21 ቀን አረፈች፡፡

a ergete mariam 2006 1ሐዋርያት መጽናኛቸው እናታቸው ቅድስት ድንግል ማርያም ብታርፍባቸው ሥጋዋን ባጎበር አድርገው ወደ ጌቴ ሴማኒ ይዘዋት ሄዱ አይሁድ “ቀድሞ ልጇን ሰቅለን ብንገድለው ደቀ መዛሙርቱ ተነሣ፣ ዐረገ” እያሉ ሲያውኩን ኖሩ፤ ዛሬ ደግሞ እርሷን ተነሣች፣ ዐረገች እያሉ ሊያውኩን አይደለምን? በእሳት እናቃጥላታለን” ብለው ተነሡ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ ተራምዶ አጎበሩን ጨበጠው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል የታውፋንያን ሁለት እጁን በሰይፍ መትቶ ቀጣው፡፡ በዚህም የታውፋንያ ሁለት እጁ ከአጎበሩ ተንጠልጥሎ ቀረ፡፡

ከዚያ በኋላ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌላዊውን ቅዱስ ዮሐንስ ጨምሮ በደመና ነጥቆ ከገነት በዕፀ ሕይወት ሥር አኖራት፡፡ዮሐንስ ከገነት ሲመለስ ለሐዋርያት “ የእመቤታችንን ሥጋ ወደ ገነት መወሰድ ነገራቸው፡፡ “ዮሐንስ የእመቤታችንን ሥጋ ገነት ማረፍ አይቶ እኛ ሳናይ” ብለው፤ ከነሐሴ 1 ቀን – ነሐሴ 14 ቀን ጾመዋል፡፡ “ሰላም ለፍልሰተ ሥጋኪ መካነ ፍሥሓ ወኑዛዜ፡ ኀበ ኢይሬእይዎ ለላህ ወኢይሔይልዎ ለትካዜ፡ ማርያም ህሉት ዉስተ ልበ ኣምላክ እምቅድመ ግዜ፡ ትፍሥሕትሰ ተፈሣሕኩ ብፍልሰትኪ ይእዜ፣ ገጸ ዚኣኪ እሬኢ ማዕዜ”ይላል መልክዓ ፍልሰታ፡፡

እግዚአብሔር ሀዘናቸውን ተመልክቶ መጽናናትን ይሰጣቸው ዘንድ ከነሐሴ 1 ቀን -ነሐሴ 14 ቀን ሐዋርያት በአንድ ልብ ሆነው ሱባኤ ያዙ (በጾም በጸሎት ተወስነው ) እግዚአብሔርም የልብ መሻታቸውን አይቶ ነሐሴ 14 ቀን ጌታ የእመቤታችንን ሥጋ ታወጣ ዘንድ ምድርን እንዲጠሩዋት ሰባቱን የመላእክት አለቆች አዘዛቸው፡፡ እነርሱም ትወጪ ዘንድ እግዚአብሔር አዞሻል አሏት፡፡ ያን ጊዜም ከዕፅ ሕይወት በታች ካለ መቃብር የእመቤታችን የማርያም ሥጋዋ ወጣ፡፡ ሐዋርያት ገንዘው በክብር ቀብረዋታል፡፡ ስለ ግንዘቷም “ሰላም ለግንዘተ ሥጋኪ ብእደ ሓዋርያት ኣርጋብ፤ ብአፈወ ዕፍረት ቅዱው ዘሐሳብ ሴቱ ዕጹብ፤ ማርያም ድንግል ውለተ ህሩያን ሕዝብ፤ ረሰይኩኪ እግዝእትየ ህየንተ እም ወኣብ፤ ይኅጽነኒ ከመ ጥብ ፍቅርኪ ሓሊብ።” ያለው ለዚህ ነው፡፡

ቅዱስ ያሬድ በዝማሬ ድርሰቱ “በስብሐት ውስተ ሰማያት መላእክት ወሊቃነ መላእክት ወረዱ ለተቀብሎታ፣ እብለኪ ወእሙ ለእግዚእየ እብለኪ ዳዊት አቡሃ ምስለ መሰንቆሁ ሙሴኒ እንዘ ይፀውር ኤፉደ መጽኡ ሃቤሃ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ሐዋርያት አጠኑ ሥጋሃ በማዕጠንተ ወርቅ፣ ሱራፌል ወኪሩቤል ሰፍሑ ከነፊሆሙ ላዕሌሃ፣ ወረደ ብርሃን እምሰማያት ወመብረቀ ስብሐት እምውስተ ደመናት፣ ተለዓለት እምድር ውስተ አርያም በስብሐት ወበህየ ነበረት ዘምስለ ወልዳ በየማነ አብ ወመንፈስ ቅዱስ” ብሏል፡፡

ጌታችንም ዘላለማዊ ወደሆነ መንግሥተ ሰማያት መላእክት እና ሰማዕታት እየሰገዱላት አሳረጓት፡፡ ንጉሥ ዳዊት “በወርቅ ልብስ ተጐናጽፋ ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች” እንዳለ /መዝ 44¸9/፡፡ ወንጌላዊ ዮሐንስም ከእርሷ በረከትን ተቀብሎ ተመልሶ ከሰማይ ወረደ፡፡ ሐዋርያት ተሰብስበው ስለ እመቤታችን ሥጋ ፈጽሞ ሲያዝኑና ሲተክዙ አገኛቸው፡፡ እርሱም እንዳየ እንደሰማ ሥጋዋም በታላቅ ክብር ማረጉን ነገራቸው፡፡

መላእክትና ሊቃነ መላእክት ቅዱስ ሥጋዋን ለማሳረግ በታላቅ ምሥጋና ከሰማይ ወረዱ፤ አባቷ ዳዊት ከመሰንቆው ጋር ሙሴም የአገልግሎት ልብሱን ለብሶ፣ ሐዋርያት ጴጥሮስና ጳውሎስም ወደ እርሷ መጡ ሥጋዋንም በወርቅ ማዕጠንት አጠኑ፡፡ ሱራፌልና ኪሩቤልም በላይዋ ክንፎቻቸውን ዘረጉ /ጋረዱ/፡፡ ከሰማያት ብርሃን የምስጋና መብረቅም ከደመናት ውስጥ ወጣ፡፡ ከምድር ወደ ሰማያት በምስጋና ከፍ ከፍ አለች ከልጇ ጋርም በአብና በመንፈስ ቅዱስ ቀኝ ተቀመጠች” ማለት ነው፡፡ ይህም “በወርቅ ልብስ ተጎናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች፡፡” መዝ.44፥9 ተብሎ የተነገረላትን ቃለ ትንቢት የተፈጸመላት መሆኑን ያመለክታል፡፡

ከሐዋርያት ወገን የሆነው ቅዱስ ቶማስ ለወንጌል አገልግሎት ሄዶ በወቅቱ አልነበረም፡፡ ደመና ጠቅሶ ከሀገረ ስብከቱ ሕንድ ሲመጣ ስታርግ አገኛት፡፡ “ወፈቀደ ይደቅ እምደመናሁ” ይላል፤ ተበሳጨ፡፡ “ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ፤ ዛሬ ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁኝ” አለ፡፡ በዚህ ጊዜ የልቡናን ሐዘን የምታቀል እመቤታችን፡- አይዞህ አትዘን እኒያ ትንሣኤዬን ዕርገቴን አላዩም፡፡ አንተ አይተሃል፡፡ ተነሣች፣ ዐረገች ብለህ ንገራቸው፡፡” ብላ የያዘችውን ሰበን ሰጥታ ሰደደችው፡፡

ከዚህ በኋላ ሄዶ፤ “የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ?” አላቸው “ሥጋዋን አግኝተን ቀበርናት” አሉት፡፡ እርሱም “ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር ተዉ ይህ ነገር አይመስለኝም” አላቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ እንጂ ልማድህ ነው፡፡ አንተ ብቻ ተጠራጥረህ አትቀርም፤ አንተ እየተጠራጠርህ ሰውን ሁሉ ስታጠራጥር ትኖራለህ” አለው፡፡ እርሱም የያዘውን ያውቃልና ጸጥ ብሎ ይሰማቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ ተቆጥቶ ሂዶ መቃብሩን ቢከፍተው የእመቤታችን ሥጋዋን አጥቷል፡፡ በዚህም ምክንያት ደንግጦ ቆመ፡፡ ይህን ጊዜ ቅዱስ ቶማስ “አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ተነሣች ዐረገች” አላቸው፡፡

a ergete mariam 2006 2ቅዱስ ቶማስ የያዘውንም ሰበን እያሳያቸው፡- “ቅዱስ ሥጋዋን የገነዛችሁበት ጨርቅ /ሰበን/ ይህ አይደለምን” ብሎ ሰበኑን ሰጣቸው፡፡ ይህንንም ለበረከት ተካፍለውታል፡፡ ከዚህ በኋላ በዓመቱ “ቶማስ ትንሣኤሽን ዕርገትሽን አይቶ እኛ ሳናይ በማለት ጾም ጀመሩ፡፡

በ16ኛው ቀን አምልካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጾ እመቤታችንን መንበር ቅዱስ ጴጥሮስን ንፍቅ ቄስ፣ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ራሱ ቀድሶ አቁርቧቸዋል፡፡ሐዋርያት ከዚህ በኋላ ሐዋርያዊ አገልግሎታቸውን በብቃት ለመወጣት ቻሉ፡፡ ይህንን ዐቢይ ምሥጢር አስመልክቶ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ተንሥአ እግዚኦ” ውስተ ዕረፍትከ፡፡ አንተ ወታቦተ መቅደስከ፤ አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ አንተና የመቅደስህ ታቦት” /መዝ.131፡8/፡፡

“ወትቀውም ንግሥት በየማንከ በአልባሰ ወርቅ ዑጽፍት ወኁብርት፤ በወርቅ ልብስ ተጎናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች” /መዝ.44፡9/ ሲል በ ቅዱስ ዳዊት የተናገረው ቃለ ትንቢት በንጽሐ ሥጋ፣ በንጽሐ ነፍስ፣ በንጽሐ ልቡና የጸናች የቅድስት ድንግል እመቤታችንን ዕረፍትና ትንሣኤ እንዲሁም ፍለሰት /ዕርገት/ በምሥጢር ከማሳየቱም ሌላ ወላዲተ አምላክ በልጇ በወዳጇ በኢየሱስ ክርስቶስ መንግሥት በክብርመኖሯንም ያስረዳል /ራእ.11፡19/፡፡

 

a ledeta mariam 2006 01

አድርሺኝ

ነሐሴ 12 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

a ledeta mariam 2006 01በጎንደር ከተማ በፍልሰታ ለማርያም ጾም ወቅት በካህናቱ፤ በሰንበት ትምህርት ቤት አባላትና በምእመናን አማካይነት በየዓመቱ የሚከናወን የተለመደ ሥርዓት አለ፡፡ ይህም ሥርዓት “አድርሺኝ” በመባል ይታወቃል፡፡

በጎንደር ከነገሡት ነገሥታት መካከል ከ1703-1708 ዓ.ም. ለአምስት አመታት በንግሥና የቆዩት ዐፄ ዮስጦስ የጎንደር መካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያንን በመትከል የሚታወቁ ሲሆን፤ አድርሽኝ የተሠኘውንም ሥርዓት በእርሳቸው እንደተጀመረ ይነገራል፡፡

ስለ ሥርዓቱ አጀማመር አባቶች ሲናገሩ፣ ዐፄ ዮስጦስ ተቀናቃኞቻቸው የከፈቱባቸውን ጦርነት ለመመከት ወደ ጦርነት ሲዘምቱ “ልደታ ለማርያም ሳትለዪኝ በድል ብትመልሺኝ፤ ለዚህም ታላቅ ክብር ብታደርሺኝ በየዓመቱ በፍልሰታ ለማርያም ሱባኤ ካህናቱን፤ መኳንንቱንና ምእመናንን ሰብስቤ ግብዣ አደርጋለሁ” በማለት ብፅዐት ይገባሉ፡፡ እርሳቸውም ድል አድርገው በመመለሳቸው በቃላቸው መሠረት በጎንደር መካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ደጀ ሰላም ሕዝቡን ሰብስበው ግብዣ ማድረጋቸውን ቀጠሉ፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑም እርሳቸውን ተከትሎ በየዓመቱ በጾመ ፍልሰታ ወቅት ይህንን ሥርዓት ይተገብሩት ጀመር፤ ስያሜውም “አድርሺኝ” ተባለ፡፡

አድርሺኝ በመላው ጎንደር በየአብያተ ክርስቲያናቱና በየአካባቢው በፍልሰታ ጾም ወቅት ይከናወናል፡፡ ምእመናን ከቅዳሴ መልስ ሱባኤው እስኪጠናቀቅ በመረጡት አንድ ቤት ውስጥ ተሰብስበው ቆሎና ጠላ አዘጋጅተው በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስም ጽዋ ይጠጣሉ። በተለይም መነኮሳይያት እናቶች በሚታደሙበት ጽዋ ላይ “ኦ! ማርያም” የሚለውን የተማጽኖ መዝሙር ይዘምራሉ። ይህ መዝሙር በሚዘመርበት ጊዜ ያለ ምንም ጥርጥር እመቤታችን ፊት ለፊት ትቆማለች ተብሎ ስለሚታሰብ በፍጹም ተመሥጦና በመንበርከክ ያከናውኑታል።

የጎንደር መካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ-ኤስድሮስ ሰንበት ት/ቤት ወጥነት እንዲኖረው በማሰብ ይህንን የእናቶች የምሕላ ዝማሬ ለተተኪ ትውልድ ለማስተላለፍ እንዲቻል አሰባስቦ አዘጋጅቶታል፡-

ኦ! ማርያም

ኦ! ማርያም እለምንሻለሁ ባሪያሽ፤

እስኪ አንድ ጊዜ ስሚኝ ቀርበሽ፤ ከአጠገቤ ቆመሽ፤

ፅኑ ጉዳይ አለኝ ላንቺ የምነግርሽ፤

የዓለሙን መከራ ያየሽ፤

በእናትሽ በአባችሽ ሀገር፤

በምድረ ግብፅ ዞረሽ ውሃ የለመንሽ፡፡

ከሁሉ ሁሉ ጤፍ ታንሳለች፤

ከጭቃ ወድቃ ትነሳለች፤

ስትነሳ /2/ የአዳም ልጅ ሁሉ ሞትን ረሳ፤

የአዳም ልጅ ሁሉ ሰነፈና የኑሮ ቤቱን ረሳና፤

ተው አትርሳ /2/ ተሠርቶልሃል የእሳት ሳንቃ፡፡

ያን የእሳት ሳንቃ፤ የእሳት በር፤

እንደምን ብዬ ልሻገር፤

ተሻገሩት አሉ የሠሩ ምግባር፤

እኔ ባሪያሽ እንዴት ልሁን? ሰላም ሰጊድ /2/

በመሥቀሉ ሥር ያያትን ተሰናበታት እናቱን፤

እናትዬ ለምን ታለቅሻለሽ ተሰቅዬ፤

ይስቀሉኝ ሐሰት በቃሌ ሣይገኝ፡፡

ንፅሕት የወልደ እግዚአብሔር እናት፤

ንፅህት በፍቅሯ ወዳጆቿን ስትመራ፤

ንፅሕት በቀኝ ወዳጆቿን ስትጎበኝ፤

የእኛስ እመቤት ያች ሩኅሩኅ፤

ከለላችን ናት እንደ ጎጆ፤

እርሷን ብለው ጤዛ ልሰው ኖሩ ትቢያ ለብሰው /2/

ኪዳነ ምሕረት ሩኅሩኅ ተይ አታቁሚኝ ከበሩ፤

የገነሃም እሣት መራራ ነው አሉ፤

እኔ ባሪያሽ እንዴት ልሁን? ሰላም ሰጊድ /2/

ድንግል ማርያም ንፅሕት፤

የምክንያት ድኅነት መሠረት፤

እንለምንሻለን ወደ አንቺ አንጋጠን፤

ከፈጣሪ በይ አማልጅን ሰላም ሰጊድ /2/

ኃያል /2/ ቅዱስ ሚካኤል ኃያል፤

የለበሰው ልብሱ የወርቅ ሐመልማል፤

ይህም ተጽፏል በቅዱስ ቃል ሰላም ሰጊድ /2/

ጊዮርጊስ ስልህ ዘንዶ ሰገደ ከእግርህ፤

እፁብ ድንቅ ይላሉ ገድልህን የሰሙ፤

አንተ አማልደኝ ከሥልጣኑ ሰላም ሰጊድ /2/

አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ደግ አባት፤

መጥቼልሃለሁ ከደጋ፤

ስንቄንም አድርጌ አጋምና ቀጋ፤

አንተ አማልደኝ ከፈጣሪ ሰላም ሰጊድ /2/

ፃድቅስ ባያችሁ ተክለ ሃይማኖት፤

በአንድ እግር ቆመው ሰባት ዓመት፤

በተአምኖ ሰባት ባቄላ ምግብ ሆኖት /2/

ተክለ ሃይማኖት አባቴ፤

መሠላሌ ነህ ለሕይወቴ፤

የዓለሙን ኑሮ መጥፎነቱን፤

የፈጣሪያችን ቤዛነቱን፤

አስተውለኸው አጥንተኸው፤

ደብረ ሊባኖስ የተሰዋኸው፡፡

ክርስቶስ ሠምራ እናታችን፤

ከአምላካችን ፊት መቅረቢያችን፤

ሣጥናኤልን አሸንፈሽ፤

ከግዛቱ ውስጥ ነፍስን ማረክሽ፡፡

ክርስቶስ ሠምራ ቅድስቷ፤

ለጽድቅ ሕይወት አማላጇ፤

እንለምንሻለን ወደ አንቺ አንጋጠን፤

ከፈጣሪ በይ አማልጅን ሰላም ሰጊድ /2/

ኦ! አባቴ አንተ ረኃቤ ነህ ጥማቴ፤

የኔ መድኃኒት ኃያል ተመልከተን ዝቅ በል፤

የነገሩህን የማትረሳ፤

የለመኑህን የማትነሳ፤

አምላኬ አንተ ነህ አምባዬ፤

የሕይወት ብርሃን ጋሻዬ፡፡

ማርያም ስሚን ወደ ሕይወት መንገድ ምሪን፤

ከአጠገባችን ቁጭ ብለሽ አድምጭን፤

ይደረግልን ልመናሽ ስትመጪ /2/

አንቺ እናቴ ሆይ /2/ የሔድሽበትን ትቢያ ቅሜ፤

ያረፍሽበትን ተሳልሜ፤

በሞትኩኝ /2/ የኋላ ኋላ ላይቀር ሞት፡፡ /2/

 

በፍልሰታ ለማርያም ጾም ወቅት ዘወትር ከቀኑ 11፡00 ጀምሮ በቤተ-ኤስድሮስ ሰንበት ት/ቤት ካለፉት 21 ዓመታት ጀምሮ ጸሎት ዘዘወትር፣ ውዳሴ ማርያም፣ ይዌድስዋ መላእክት፣ መዝሙረ ዳዊት 50 እና 135፣ ጸሎተ ምናሴ፣ መሐረነ አብ ጸሎት በዜማ ከተጸለየ በኋላ ኦ! ማርያም የምሕላ መዝሙር ይዘመራል፡፡

  • ማስታወሻ፡- መረጃውን በመስጠት የተባበሩንን ዲያቆን ሙሉቀን ብርሃኑ እና የጎንደር መካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ- ኤስድሮስ ሰንበት ትምህርት ቤትን በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን፡፡

 

ክረምት

ነሐሴ 7 ቀን 2006 ዓ.ም.

ዕጉለ ቋዓት፥ ደስያት

ይህ ወቅት ከነሐሴ 10 እስከ ነሐሴ 27 ቀን ድረስ ያሉት 17 ዕለታት የሚጠሩበት ነው፡፡ ፍጥረታትና በባሕር የተከበቡ ደሴቶች የሚታወሱበት ጊዜ ሲሆን ወቅቱም ዕጓለ ቋዓት ደስያት ዐይነ ኩሉ ይባላል፡፡ ዕጓለ ቋዓት የሚለው ቃል ቁራን ሲያመለክት፣ ቁራ ሲወለድ ያለ ፀጉር በሥጋው ብቻ ይወለዳል፡፡

 

እናትና አባቱም እነርሱን ባለመምሰሉ ደንግጠው ይሸሻሉ፤ በዚህ ጊዜ የሚንከባከበው ሲያጣ እግዚአብሔር በረድኤት አፉን ከፍቶ ምግብ ሲሻ ተሐዋስያንን ብር ብር እየደረገ ከአፉ ያስገባለታል፡፡ “ልጆቹ ወደ እግዚአብሔር ሲጮኹ፥ የሚበሉትም አጥተው ሲቅበዘብዙ፥ ለቁራ መብልን የሚሰጠው ማን ነው? ” (ኢዮ.38፥41) ተብሎ እንደ ተገለጠው እግዚአብሔር የሰጠውን እየተመገበ ቆይቶ ሲጠነክር እንደ እናትና አባቱ ያለ ፀጉር ያወጣል፡፡ በዚህ ጊዜ እናትና አባቱ ቀርበው ይንከባከቡታል፡፡ በሥነ ፍጥረት አቆጣጠር ግን በክንፍ የሚበሩ አዕዋፍን ሁሉ ይወክላል፡፡

 

ይህም አምላካችን እግዚአብሔር ለፍጥረቱ ሁሉ የሚያስብ በመሆኑ ይህን ዘመን ርኅርሔ ለተመላው አምላክነቱ ሥራው መታሰቢያ እንዲሆን ቤተ ክርስቲያን ዕጓለ ቋዓት በማለት ታስታውሰዋለች፡፡

ደስያት ማለት በውኃ የተከበቡ ቦታዎች ማለት ነው፡፡ እነዚህን ቦታዎች በውኃ እንዲሸፈኑ አድርጎ በውስጣቸው ያሉትን ሰዎች እንስሳት አራዊት አዕዋፍ ሁሉ የሚጠብቃቸው፣ በተስፋና በእምነት አበርትቶ የሚያኖራቸው እግዚአብሔር ነው፡፡ ይህን ድንቅ ሥራ ያዩ በውስጥ በውጭ ያሉት ሰዎች እግዚአብሔርን ያመሰግኑታል፡፡ በደሴት (በቤተ ክርስቲያን) የተጠጉ ሁሉ ከሞተ ሥጋና ከሞተ ነፍስ ይጠበቃሉ፡፡

በዚህ ወቅት፡- ክፍለ ክረምቱ እንደተገባደደ፥ ውኃው እየጠራ፣ መሬቱ እየረጋ፣ ደመናውና ጉሙ እየተቃለለ፣ የወንዞች ሙላት እየቀነሰ፣ የክረምት ምግባቸውን ይዘው በየዋሻው የከረሙ ጭልፊቶችን አሞራዎች ድምፃቸውን እየሰሙ ምግብ ፍለጋ ሲወጡ የሚታዩበት ወቅት ነው፡፡

በተጨማሪም ከነሐሴ 27-29 ያለው ጊዜን “ሞተ አበው” በመባል ይታወቃል፡፡ ከ22ቱ አርእስተ አበው የአብርሃም ይስሐቅና ያዕቆብ ቤተሰቦቻቸው ዕረፍት ይታሰባል፡፡ ቅዱስ መጽሐፋችንም “አብርሃም ልጁን ይስሐቅን ሊሰዋ ወጣ፤ እግዚአብሔር ቤዛ አድርጎ ቀንዱ በዕፀ ሳቤቅ የተያዘ በግ አወረደለት” በማለት የአብርሃምን ታዛዥነት የይስሐቅን ቤዛነት ያወሳል፡፡ የተቀበሉትም ቃል ኪዳን “ወተዘከረ ሣህሎ ዘለዓለም ዘሠርዓ ለአብርሃም ወመሐለ ለይስሐቅ ወዐቀመ ስምዐ ለያዕቆብ ያርኁ ክረምተ ይገብር ምሕረተ እም ሰማይ ይሁብ ወእምድር በረከተ ያጸግብ ነፍስ ርኅብት” በማለት ይዘመራል፡፡

 

ፍልሰታና ሻደይ

ነሐሴ 5 ቀን 2006 ዓ.ም.

ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ በኋላ በመላው ዓለም የክርስትና እምነት በሐዋርያቱ መሰበክ ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ በኢትዮጵያ ሀገራችን የክርስትና እምነት ተሰብኳል፡፡  በተለይም ሀገራችን የሰሜኑ ክፍል  ህዝበ ክርስቲያኑ ለረጅም ዘመናት ሥርዓተ አምልኮ ሲፈጽምባቸው እንደነበሩና አሁንም አገልግሎት እየሰጡ እንደሆነ በአካባቢው የሚገኙ በርካታ ጥንታዊ አብያተ ክርስቲያናትና መንፈሳዊ ቁሶች ያስረዳሉ። እነዚህም የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ መንፈሳዊ ቅርሶች ናቸው። ከማይዳሰሱ መንፈሳዊ ቅርሶች መካከል የተለያዩ መንፈሳዊ በዓላት የሚከበሩበት ሥርዓት አንዱ ነው።

asendya 01በዋግ ኽምራ ሀገረ ስብከት ከሚከበሩ በዓላት መካከል የሻደይ ምስጋና / ጨዋታ አንዱ ሲሆን ልጃገረዶች በአማረ ልብስ ደምቀው አሸንድዬ በሚባል ቄጠማ ጉንጉን ወገባቸውን አስረው የሚያከብሩት ነው። በዓሉ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃማኖታዊ ይዘት አለው። በዓሉ ከነሐሴ 16 ጀምሮ እስከ ነሐሴ 21 ቀን ድረስ ይከበራል። ይህ በዓል በዋግ ኽምራ ሻደይ፣ በላስታ አሸንድዬ፣ በትግራይ አሸንዳ፣ በቆቦ አካባቢ ሶለል፣ በአክሱም አካባቢ ደግሞ ዓይነ ዋሪ እየተባለ ይጠራል።

የሻደይ በዓል ከኦርቶዶክስ ተዋሐዶ እምነት ጋር እየተያያዘ የመጣ ሲሆን አጀማመሩ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መነሻ አለው፡፡ ከነዚህም መካከል የአዳም ከገነት መባረር፣ የኖኅ ዘመን የጥፋት ውኃ፣ ከዘመን መለወጫ፣ ከመጥመቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ አንገት መቆረጥ፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ (ፍልስታ) እና ከመስፍኑ ዮፍታሔ ልጅ ታሪክ ጋር በማስተሳሰር የሚያስቀምጡት ሲሆን በማኅበረስቡ አባቶችና ሊቃውንቱ ዘንድ ጎልቶ የሚነገረውና የሚተረከው ግን የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ (ፍልስታ) በዓልን መሠረት ያደረገ ነው።

አባታችን አዳም በገነት ሳለ ሕግ በመተላለፉ ጸጋ እግዚአብሔር ርቆት እርቃኑን በሆነ ጊዜ አካሉን ለመሸፈን ቅጠል መጠቀሙን ለማሰብ ያች አዳምና ሔዋን ክብራቸውን ተገፈው ከገነት የተባረሩባትን ዕለት በማሰብ በወቅቱ ያገለደሙትን ቅጠል በምልክትነት በመውሰድ የሻደይ ቅጠልን በገመድ ላይ ጎንጉነው በወገባቸው አገልድመው/አስረው/ አዳምና ሔዋን ከገነት ከመውጣታቸው በፊት ግብረ ሥጋ ግንኙነት ያልጀመሩ ደናግላን ስለነበሩ ያንን በመከተልና በምሳሌነት በመውሰድ ያላገቡ የአገው ልጃገረዶች ተሰባስበው ያችን ዕለት ወይም ቀን በመታሰቢያነት ለመቁጠር ወይም ለመዘከር የሻደይ ጨዋታን መጫወት ወይም ማክበር እንደጀመሩ ይናገራሉ።

ከኖኅ ዘመን ታሪክ ጋር ያለው ግንኙነት ደግሞ ከጥፋት ውኃ በኋላ ውኃው የመጉደሉን ምልክት ርግብ ለኖኅ የለመለመ የወይራ ቅጠል ይዛ በመምጣት በምድር ሰላም እነደሆነ የምሥራች አብሥራለች። ከዚሁ ጋር በተገናኘ በዓሉን ያንን ለምለም ቅጠል ወገባቸው ላይ በማሰር ከጨለማ ወደ ብርሃን ተሸጋገርን ሲሉ ማክበር እንደጀመሩ ከታሪኩ ጋር አያይዘው ያስቀምጡታል።

ከመስፍኑ ዮፍታሔ ታሪክ ጋርም ቢሆን የሻደይ በዓል እንዴት ግንኙነት እንዳለው ሲያስቀምጡ ዮፍታሔ ወደ ጦርነት በሔደ ጊዜ በድል ከተመለስ ለአምላኩ መሥዋዕትን ለማቅረብ ስዕለት ገበቶ ነበር። ይህም ከቤቱ ሲመለስ መጀመሪያ የሚቀበለውን እንደሚሠዋ ሲሆን በዚህ ጊዜ ያለ ወትሮዋ ልጁ እየዘፈነች ልትቀበለው ወጣች በዚህም በጣም አዘነ። ልጁም ለአምላኩ የገባውን ስዕለት እንዳያስቀር ሁለት ወር ስለ ድንግልናዋ አልቅሳ ስዕለቱን እንዲፈጽም ጠይቃው ከሁለት ወር በኋላ ስዕለቱን የፈጸመ ሲሆን አባቷ የገባውን ቃል ኪዳን እንዳያጥፍ ያበረታታችውንና መሥዋዕትነትን ለሀገር፣ ለህዝብ፣ ለአባትና ለፈጣሪዋ የከፈለችውን የዮፍታሔን ልጅ በየዓመቱ ለአራት ቀናት ሙሾ በማውጣት አስበው ይውላሉ፡፡ በዚህ መሠረት በበዓሉ ላይ ከሚፈጸሙ ተግበራት ጋር አዛምደው መነሻው ከዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ እንደሆነ ይናገራሉ። “ጽዮንን ክበቡዋት በዙሪያዋም ተመላለሱ…በብርታትዋ ልባችሁን አኑሩ፣ ለሚመጣው ትውልድ ትነግሩ ዘንድ” መዝ 48፥12

 

የሻደይ በዓል አጀማመርን በተመለክተ ከላይ ከተቀመጡት ታሪኮች በተጨማሪ በአካባቢው ሕዝብና በቤተ ክርስቲያን ሊቃውንቶች ዘንድ ተደጋግሞ የሚነሣው ታሪክ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ በዓል ሲሆን ይኸውም እግዚአብሔር አምላክ ለአዳምና ሔዋን ከ5500 ዘመን በኋላ ወደዚህ ዓለም አንድያ ልጁን ልኮ ከኃጢያት እሥራት ነጻ እንደሚያወጣቸው በገበላቸው ቃልኪዳን መሠረት አምላክ የተወለደባት እና ትንቢቱ የተፈጸመባት፣ በሔዋን ስህተት ከገነት የተባረረው የሰው ልጅ በእርሷ ምክንያት ከኃጢያት ባርነት ነጻ የወጣባትና ወደ ቀድሞ ቤቱ ገነት እንዲመለስ ምክንያት የሆነችው የሰው ልጅ መመኪያ የተባለች እመቤት፣ እንደማንኛውም ሰው የተፈቀደላትን እድሜ በምድር ከኖረች በኋላ ሞተ ሥጋን እንደ ሞተች ከመጽሐፍት እንረዳለን፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከዚህ በኋላ ሞትን ድል አድርጋ ከመቃብር ተነሥታ ወደ ሰማይ አረገች፡፡

በፍልሰታ ወቅት በዓሉ መከበሩም ለሻደይ ተጨዋቾች ተምሳሌትና የድንግልናቸው አርዓያ የሚያደርጓት ድንግል ማርያም አካላዊ ሥጋዋ ከጌቴሰማኔ ወደ ገነት መፍለሱን እንዲሁም በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር ከነበረበት መነሣቱን ምክንያት በማድረግ እንደሆነ የዋግ ኽምራ ሀገረ ስብከት ስብከተ ወንጌል መምሪያ ሓላፊ የሆኑት መጋቢ ምስጢር ገብረ ሕይወት ኪዳነ ማርያም “በዓሉ በልጃገረዶች ዘንድ ተወዳጅ የሆነው በሄዋን ምክንያት የተዘጋው ገነት በእመቤታችን አማካኝነት በመከፈቱ ነው። መመኪያቸው ስለሆነች ልጃገረዶች በዓሉን ያከብሩታል ድንግልናቸውንም አደራ የሚሉት በእርሷ ነው” ሲሉ ይናገራሉ።

ዕርገቷን መላዕክት በእልልታ፣ በሽብሸባና በዝማሬ ነጫጭ ልብስ ለብሰው አጅበዋት ነበር፡፡ ዕለቱን ፍስለታ ብለን የምንጠራውም ማርያም ከሞት ተነሥታ ማረጓን፣ ሙስና መቃብር አፍልሳ መነሣትዋን ወይም ዕርገቷን በማሰብ ነው፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት እመቤታችን በነሐሴ 16 ቀን እንደ አዲስ በመላዕክት ሽብሸባ፣ እልልታ፣ ዝማሬና ዝማሜ ታጅባ ከምድር ወደ ሰማይ ስታርግ እንዳዩ፡፡ በታላቅ ፍስሃ ይመለከቱና በታዓምራቱ ይደነቁም ነበር፡፡ ከዛን ዕለት ጀምሮ ደናግል ቅዱሳን ከመላእክቱ በተመለከቱት ሥርዓት መነሻነት ባህላዊ ነጫጭ ልብሶችን ለብሰው፣ አምረውና አጊጠው፣ የወቅቱ መታሰቢየ የሆነውን ለምለሟን ከምድር ሳሮች ሁሉ ረዘም ያለችውን የሻደይ ቅጠል በወገባቸው አስረው እንደ መላአክቱ አክናፍ ወገባቸውን ከግራ ወደ ቀኝ እያመላለሱ በማሽከርከር እያሸበሸቡ፣ በአንደበታቸው እየዘመሩና በእጆቻቸው እያጨበጨቡ በአንድነት ተሰባሰባስበው በፍቅርና በሐሴት ከነሐሴ 1 ቀን ጀምሮ በመጾም ጾሙ ከሚፈታበት ከዳግም ዕርገቷ ነሐሴ 16 ጸሎታቸው ተሰምቶላቸው የፈለጉትን ማየታቸውን ምክንያት በማድረግ እስከ ነሐሴ 21 ቀን ድረስ በየዓመቱ ማክበር እንደተጀመረ ይነገራል፡፡

እናቶችና እኅቶች በአደባባይ ወጥተው የድንግል ማርያምን ሞትን ድል አርጎ መነሣት ትንሣኤዋንና ዕርገቷን እንደ ነጻነታቸው ቀን ቆጥረው የተለያዩ አልባሳትን በማድረግና ለበዓሉ ክብር በመስጠት ከበሮ አዘጋጅተው አሸነድዬ የተባለውን ቄጠማ በወገባቸው ታጥቀው ምስጋና በማቅረብ በዓሉን ይዘክራሉ፡፡ በዚህም መሠረት የሻደይ ጨዋታ የፍስልታ በዓል መከበር ከጀመረበት ጊዜ አንሥቶ እንደተጀመረና በምእመኑ ለረጅም ጊዜ እየተከበረ የኖረ ሃይማኖታዊ በዓል እንደሆነ ይታመናል፡፡

የሻደይ ልጃገረዶች የቡድን አመሠራረት ደብርን መሠረት ያደረገ ነው፡፡ የሻደይ ጨዋታ በዓል በሚያከብሩበት ጊዜ ልጃገረዶች የተለያዩ ባህላዊ አልባሳትን ለብሰው ከበሮ እና ለምስጋናው የሚያስፈልጉ ነገሮችን በማሟላት ተጠራርተው በመጀመሪያ ወደ አጥቢያቸው በመሄድ የቤተ ክርስቲያኑን ደጁን አልፈው ይዘልቃሉ፡፡ የቤተ ክርስቲያኑን ደጅ ከተሳለሙ በኋላ የተለያዩ ጣዕመ ዝማሬ እያሰሙ ሦስት ጊዜ ይዞሩና ደጃፉን ተሳልመው በቅጥር ግቢው አመቺ ቦታ ፈልገው ምስጋናቸውን ይጀምራሉ፡፡ ከበሮአቸውን እየመቱ፣ የታቦቱን ስም እየጠሩ በሚያምር ድምፃቸው፣ ሽብሻቦ፣ ውዝዋዜ፣ ጥልቅ መልእክትን በያዙ ግጥሞች፣ ለዚህ ያደረሳቸውን አምላክና ታቦት ያወድሳሉ፣ ያሞግሳሉ፣ ያከብራሉ፣ ይለማመናሉ፡፡ ምስጋናው ለዚህ ዓመት ያደረሳቸውን አምላክ የሚያመስግኑበት እና ቀጣዩ ዓመትም እንደዚሁ የሰላም፣ የጤና የተድላ እንዲሆን የሚማጸኑበት፣ ተስፋቸውን የሚገልጹበትና ስለት የሚሳሉበት በመሆኑ ምስጋናውን ሞቅ፣ ደመቅ አድርገው ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ በፍቅር፣ በደስታ፣ በመተሳሰብና በሰላም ይጫወታሉ፡፡ እያንዳንዱ አባል ለእግዚአብሔርና ለደብራቸን ታቦት ያልሆነ እያሉ ጉልበታቸውን፣ ችሎታውንና ልምዳቸውን ሳይቆጥቡ በምስጋናው ይሳተፋሉ።

ከቤተ ክርስቲያን መልስ በአካባቢው ወዳሉት ትልልቅ አባቶች ዘንድ ሄደው በመዘመር ምርቃን ይቀበላሉ። ከዚያ መልስ ወደ ተራራማ ስፍራ በመውጣት ክብ ሠርተው ይዘምራሉ፡፡ ከዝማሬያቸው ውስጥ ግጥሞቹ መንፈሳዊ ይዘት ያላቸው ግጥሞች ከግለሰባዊ ስሜት ወይም ከግለሰብ ውዳሴ የራቁ ናቸው፡፡ የቡድን አመሠራረታቸው ደብርን መሠረት ያደረገ በመሆኑ አንዱ ቡድን ከሌላው ቡድን የተሻለ መሆኑን ለማሳየት ፣ የደብሩን ኃያልነት፣ ደብራቸውን እንደማያስደፍሩና እንደሚጠብቁ በምስጋናቸው ይገልጻሉ፡፡

የወከሉትን ደብር ታቦት ስም እየጠሩ ለአባት እናት፣ ለቤተሰብ ጤና፣ ጸጋ፣ ሀብት፣ ሰላም በአጠቃላይ መልካሙን ሁሉ እንዲያድላቸው ይማጸናሉ፡፡ አደራውን ለታቦቱ ይሰጣሉ፡፡ ለዚህም ዜማውና ግጥሙ ተመሳሳይ ቢሆንም የወከሉትን ደብር ስም ብቻ በማቀያየር በተመሳሳይ ዜማና መወደስ እና መማጸን በሁሉም የሻደይ ተጨዋች ቡድኖች ይታይል፡፡ ልጃገረዶቹ በዚህ የምስጋና ጊዜ የሚሰበሰቡትን ሥጦታዎች ሁሉ ለቤተ ክርስቲያን ይሰጣሉ።

የሻደይ ምስጋና/ጨዋታ በዚህ መልኩ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በማመስገን ከፍከፍ በማድረግ ዕርገቷን በማሰብ የአምላክ እናት አማልጅን እያሉ ስሟን በመጥራትና በማክበር የሚከናወን በመሆኑ ይህንን ሃይማኖታዊ መሠረትነት ያለውን ትውፊት የመጠበቅና የማስጠበቅ ሓላፊነት ከሁላችን ይጠበቃል። የእመቤታችን አማላጅነት አይለየን፡፡

  • ምንጭ፡-ሰቆጣ ማእከል ሚዲያ ክፍል

 

ደብረ ታቦርና ቡሄ

 ነሐሴ 5 ቀን 2006 ዓ.ም.

መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

የኢትየጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከምታከብራቸው ዘጠኝ ዓበይት በዓላት አንዱ የደብረ ታቦር በዓል ነው። በየዓመቱ ነሐሴ ፲፫ ቀን የሚከበረው ይህ በዓል መሠረቱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ደብረ ታቦር ኢየሱስ ክርስቶስ ሦስት ደቀመዛሙርቱን ይዞ ወደ ተራራው የወጣበትና ፊቱ እንደ ፀሐይ የበራበት፣ ልብሱም እንደብርሃን ነጭ የሆነበት፣ ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት ተራራ ነው።

ከስድስት ቀንም በኋላ ኢየሱስ ጴጥሮስንና ያዕቆብን ወንድሙንም ዮሐንስን ይዞ ወደ ረጅም ተራራ ብቻቸውን አወጣቸው። በፊታቸውም ተለወጠ፥ ፊቱም እንደ ፀሐይ በራ፥ ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ ሆነ። እነሆም፥ ሙሴና ኤልያስ ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ታዩአቸው። ጴጥሮስም መልሶ ኢየሱስን ጌታ ሆይ፥ በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው፤ ብትወድስ፥ በዚህ ሦስት ዳስ አንዱን ለአንተ አንዱንም ለሙሴ አንዱንም ለኤልያስ እንሥራ አለ። እርሱም ገና ሲናገር፥ እነሆ፥ ብሩህ ደመና ጋረዳቸው፥ እነሆም፥ ከደመናው። በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት የሚል ድምፅ መጣ። ደቀ መዛሙርቱም ሰምተው በፊታቸው ወደቁ እጅግም ፈርተው ነበር።

 

ኢየሱስም ቀርቦ ዳሰሳቸውና፡ ተነሡ አትፍሩም አላቸው። ማቴ. ፲፯፡፩-፭ በቤተ ክርስቲያን ደብረታቦር ከቤተክርስቲያን ውጭ አከባበሩ ቡሄ እየተባለ የሚከበረው በዓል በሀገራችን በየዓመቱ ነሐሴ ፲፫ ቀን በታላቅ ድምቀት ይከበራል፡፡ ቡሄ ማለት ብራ፣ ብርሃን፣ ደማቅ ገላጣ፣ የተገለጠ ማለት ነው፡፡ ቡሄ ሲመጣ የክረምቱ ጨለማነት አልፎ ወደ ብርሃን፣ ወደ ጥቢ የሚያመራበት፣ ወደ መፀው የሚዘለቅበት ወገግታ ፣ ሰማይ ከጭጋጋማነት ወደ ብሩህነት የሚለወጥበት፣ የሚሸጋገርበት ወቅት በመሆኑ ከቡሄ በኋላ የጠነከረ ክረምት አይኖርም፡፡ በዚህ መሰረት የክረምቱ አፈና ተወግዶ የብርሃን ወገግታ የሚታየውም በዚህ በዓል አካባቢ ስለሆነ ይቺ ዕለት ‘ቡሄ’ የሚለውን ስያሜ አገኘ። ቡሄ ማለት ገላጣ፣ የተገለጠ ማለት ነው፡፡ ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት፣ ብረሃን የታየበት ድምጸ መለኮት የተሰማበት ስለሆነ፤ ችቦ ስለሚበራ የብርሃን በዓል በማለት የቡሄ በዓልም ይባላል፡፡

 

በገጠርም ሆነ በየከተማው ልጆች ጅራፋቸውን ገምደው ሲያጮሁ ይሰነብታሉ። እናቶችም ለበዓሉ ዝግጅት ስንዴ ሲለቅሙ፣ ሲፈትጉ፣ ሲፈጩ ይሰነብታሉ። መነሻ የሆናቸው ትውፊት ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት ዕለት ጊዜው ምሽት ነበር፡፡ እረኞችም ከብርሃኑ የተነሣ እየተገረሙና እየተደነቁ ወደ ቤት አልተመለሱም ነበር፡፡ የልጆቹን መዘግየት ያዩ ወላጆች ችቦ አብርተውና ዳቦ ይዘው ፍለጋ ወጥተዋል ፡፡ያንን ለማስታወስ «ቡሄ» ለሚሉ ልጆች ሙልሙል ዳቦ የሚሰጠውና ችቦ በማብራት በዓሉን የሚከበረው ከዚህ በመነሣት ነው፡፡ የንጋት ወጋገን ሲፈናጠቅ ልጆች በከባድ ድምጽና በጅራፍ ጩኸት የሚታጀብ፣ በገደላገደል ስር እንዲያስተጋባ ተደርጎ ብዛት ባላቸው ህጻናት በከፍተኛ ድምጽ የሚዘመር ነው ቡሄ ። የጅራፉ ጩኸትም እግዚአብሔር አብ “የምወደው ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት” ሲል ሐዋርያት ራሳቸውን ስተው የወደቁበትን የመለኮት ድምፅ ለማስታወስ ነው፡፡

 

ደብረታቦር ወይም ቡሄ በአብነት ተማሪዎች “ስለ ደብረ ታቦር” እያሉ እህል፣ ፣ ጌሾ ለምነው ጠላውን ጠምቀው፣ ዳቦውን ጋግረው፣ ቆሎውን ቆልተው ለደብረ ታቦር ዕለት ሊያስቀድሱ የመጡትን ምዕመናን በመጋበዝ በታላቅ ድምቀት ያከብራሉ፡፡ ይህ ትውፊት መምህረ ሐዋርያት የነበረው ኢየሱስ ክርስቶስ ሦስቱን ተማሪዎቹን ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ወንድሙንም ዮሐንስን ይዞ ወደ ደብረ ታቦር ይዞ ሄዶ የተገለጠ ምስጢር ስለሆነ ከመምህራቸው ጋር በመሆን በዓለ ደብረ ታቦርን /ቡሄን ያከብራሉ፡፡ ስሙን ይጠራሉ፡፡

የደብረ ታቦር ወይም የቡሄ ግጥሞች

ድምጽህን ሰማና በብሩህ ደመና
የቡሄው ብርሃን ለኛ መጣና

ያዕቆብ ዮሃንስ ሆ! እንዲሁም ጴጥሮስ
አምላክን አዩት ሆ! ሙሴ ኤልያስ
አባቱም አለ ሆ! ልጄን ስሙት
ቃሌ ነውና ሆ! የወለለድኩት

ድምጽህን ሰማና በብሩህ ደመና
የቡሄው ብርሃን ለኛ መጣና።
መጣና መጣና ደጅ ልንጥና

መጣና ባመቱ እንዴት ሰነበቱ፣
ክፈት በለዉ በሩን የጌታዪን
ክፈት በለዉ ተነሳ ያንን አንበሳ፣

የመሳሰሉት

 

kedus kerkos eyeleta

“መላእክት ሁሉ ረቂቃን አይደሉምን የዘላለም ሕይወትን ይወርሱ ዘንድ ላላቸው ለአገልግሎት ይላኩ የለምን” ዕብ.1፡14

 ሐምሌ 17 ቀን 2006 ዓ.ም.

kedus kerkos eyeleta

መላእክት እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን የሰማይንም ሠራዊት ፈጠረ በሚለው አንቀጽ እንደተጠቀሰው፤በመጀመሪያው ቀን በዕለተ እሑድ በእግዚአብሔር ቃል ተፈጥረዋል፡፡ እግዚአብሔር አፈጣጠሩ ድንቅ ነውና መላእክትን እንደ እሳትና ነፋስ የማይዳሰሱ የማይታዩ አድርጎ ፈጥሯቸው ያመሰግኑታል፡፡ ዘፍ.1፡1 መዝ.108፡4፣ ዕብ.1፡12

እግዚአብሔር የፈጠራቸው 20 ዓለማት ሲኖሩ ሦስቱ፤ ኢዮር፣ ራማ፣ ኤረር የመላእክት ከተሞች ናቸው፡፡

 

መላእክት በ30 ነገድ በ10 አለቃ ተከፋፍለው እግዚአብሔርን የሚያመሰግኑ ለፍጥረታት ሁሉ ምሕረትን የሚለምኑ ናቸው፡፡ 10ሩ ነገድ መኳንንት ይባላሉ፡፡ እነዚህ መላእክት ዓለትን ተራራን ሠንጥቀው የሚሄዱ፣ ቀስት መሳይ ምልክት ያላቸው፣ በትንሣኤ ዘጉባኤ ጊዜ ነፍስና ሥጋን የሚያዋሕዱ መላእክት ሲሆኑ አለቃቸው ሰዳክያል ይባላል፡፡

10ሩ ነገድ ሊቃናት ሲባሉ የእሳት ሠረገላ ያላቸው፣ ኤልያስን በሰረገላ የወሰዱት መላእክት ሲሆኑ አለቃቸው ሰላትያል ይባላል፡፡ 10ሩ ነገድ መላእክት ይባላሉ፡፡ ሕይወት የሌለውን ነገር ሁሉ በሥርዓት እንዲቆዩ የሚጠብቁ ሲሆኑ አለቃቸው አናንያል ይባላል፡፡ የኃይላት አለቃቸው ቅዱስ ሚካኤል ሲሆን የአርባብ አለቃቸው ደግሞ ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡

መላእክት ብርሃናዊ መልአክ ስለሆኑ የሚያግዳቸው የለም፡፡ አለት ተራራን ሰንጥቀው የመግባት አንዱ በአንዱ የማለፍ ችሎታ አላቸው፡፡ እንደ መብረቅ እንደ እሳት የመሆን ባሕርይ አላቸው፡፡

መላእክት ትጉኃን ናቸው፡፡

“መላእክት ሁሉ ረቂቃን አይደሉምን የዘላለም ሕይወትን ይወርሱ ዘንድ ላላቸው ለአገልግሎት ይላኩ የለምን” ዕብ.1፡14 እንዳለ እረፍታቸው ምስጋና ምስጋናቸው እረፍት ሆኖ ሌት ተቀን ይተጋሉ፡፡

መላእክት በእግዚአብሐር ፊት ይቆማሉ፡፡

መላእክት ለምሕረት በእግዚአብሐር ፊት ይቆማሉ፡፡ “በእግዚአብሔር ፊት የቆሙ ሰባት መላእክት አየሁ፡፡” ራዕ.8፡2፡፡እኔ በእግዚአብሔር ፊት የምቆመው ገብርኤል ነኝ ሉቃ.1፡19፣ ዘካ.1፡12 ፡፡
መላእክት ተራዳኢ ናቸው፡፡

ቅዱስ ዳዊት “የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሰፍራሉ ያድናቸውማል” መዝ.33፡7፡፡ ሲል በዘፍ.48፡16 “ከክፉ ነገር የዳነን የእግዚአብሔር መልአክ እርሱ እኒህን ሕፃናት ይባርክ” በማለት ተራዳኢነታቸውንና በረከትን የሚያሳድሩ መሆናቸውን ያስረዳል፡፡ “ያን ጊዜም የጴጥሮስ ልቡና ተመልከትና እግዚአብሔር በዕውነት መልአኩን ልኮ ከሄሮድስ እጅና ከአይሁድ ሕዝብ ምኞት ሁሉ እንዳዳነኝ አወቅሁ አለ ሐዋ.12፡16፡፡ እነሆ ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ ዳን.10፡13 ማቴ.18፡10 የመላእክትን ተራዳኢነት ያስረዳል፡፡

ጠባቂዎቻቸው ዘወትር የአባቴን ፊት ያያሉ፡፡

መላእክት ይጠብቁናል

በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁን ዘንድ መላእክቱን ስላንተ ያዛቸዋልና እግርህም በድንጋይ እንዳትሰናከል በእጆቻቸው ያነሡናል” መዝ.90፡11-12፡፡ “ከነዚህ ከታናናሾቹ አንዱን እንዳትንቁ ተጠንቀቁ፤ መላእክቶቻቸው በሰማያት ዘወትር በሰማያት ያለውን የአባቴን ፊት ያያሉ እላችኋለሁና። ማቴ18፡10

“በመንገድህ ይጠብቅህ ዘንድ ወዳዘጋጀ ቤት ሥፍራ ያገንህ ዘንድ እነሆ አኔ መልአኩን በፊትህ እሰዳለሁ በፊቱ ተጠንቀቁ ቃሉንም አድምጡ ስሜም በእርሱ ስለሆነ ኃጢአት አትሥሩ ይቅር አይልምና አታስመርሩት ዘፀ.23፡20-22 መላእክት ዕጣንን ያሳርጋሉ፣ ራዕይ.5፡8፣ 8፣3 ፡፡ መላእክት የጸጋ ስግደት ይሰገድላቸዋል ዳን.5፡፡ኢያ.5፡13፣ ነገ.19፡6 15፣ ዘፍ.22፡3 መላእክት የምንመገበውን ይሰጡናል/ይመሩናል/ ት.ዳ.3 መላእክት ከእስር ያስፈታሉ ሐዋ.12፡6፡፡ መላእክት ይፈውሳሉ “እግዚአብሔር የበለዓምን ዐይን ከፈተ ዘሁ.22፡31

የመላእክትን አፈጣጠራቸውን፣አገልግሎታቸውን በመጠኑ ከተረዳን ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ የሆነው ቅዱስ ገብርኤል ሐምሌ 19 ቀን ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስና እናቱ ኢየሉጣን ያዳነበት፣የጸናናበት ለክብር ያበቃበትን ቀን በድርሳነ ገብርኤል የተገለጸውን እንዲህ አቅርበነዋል፡፡

ድርሳነ ገብርኤል ዘሐምሌ

በአገዛዝና በቅድምና ትክክል የሆነ፣ ከመታሰቡ አስቀድሞ ሁሉን መርምሮ የሚያውቅ፣ ክረምትን በየዓመቱ የሚያመጣ፣ ሰማይን በደመና የሚጋርድ፣ ምድርን በልምላሜ የሚሸፍናት፣ የባሕርን ውኃ በእፍኙ የሚለካ፣ ምድርን በስንዝሩ የሚመጥናት ከኛ ዘንድ ለሱ ምስጋና የሚገባው፣ ለኛ ሕይወትን የሚሰጠን አንድ አምላክ በሚሆን በአብ፣ በወልድ፣ በመንፈስ ቅዱስ ስም አምነን በሐምሌ 19 ቀን የሚነበብ የሚጸለይ የሰማያውያን አለቃ የሚሆን የቅዱስ ገብርኤል ድርሳን ይህ ነው፡፡

እለ እስክንድሮስ የተባለ መኰንን በኢየሱስ ክርስቶስ ያመኑትን ክርስቲኖች ለመቀጣትና ሌሎችም ፈርተው ክርስትናን እንዳይፈልጉ ለማድረግ አስቦ ሰም፣ ጨው፣ ባሩድ፣ ሙጫ፣ የዶሮ ማር፣ እርሳስ፣ ብረት፣ ቅንጭብ፣ ቁልቋል አንድ ላይ ተቀላቅሎ በብረት ጋን እንዲፈላ አዝዞ ነበር፡፡ ጭፍሮቹም እለስክንድሮስ እንዳዘዛቸው ከአደረጉ በኋላ ያዘዝኸንን ሁሉ ፈጽመን እሳቱ ነዶ ፈልቷል፤ ድምፁ እንደነጐድጓድ ይጮሃል፤ ወላፈኑም እንደ ፀሐይ ነፀብራቅ በሩቅ ይጋረፋል፤ የፍላቱም ኀይል አሥራ ዐራት ክንድ ያህል ከፍታ ወደላይ ይዘላል፤ እንግዲህ በውስጡ የሚጣሉትን እዘዝ አሉት፡፡

በዚህ ጊዜ ሕፃን ቂርቆስና እናቱ ኢየሉጣ በክርስቶስ ስም ስለሚያምኑ አሥረዋቸው ነበርና ከፍላቱ ሊጨምሯቸው ከእሥር ቤት አወጧቸው፡፡ ፍላቱ ወደ ላይ በሚዘል ብረት ጋን ውስጥ ለመጨመር ሲወስዷቸው የእነዚህን ቅዱሳን አሟሟት ያዩ ዘንድ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች እንዲሰበሰቡ ታዘዘ፡፡

በዚህ ጊዜ ቅድስት ኢየሉጣ የፍላቱን ጩኸት በሰማችና ባየች ጊዜ ተሸበረች፤ ተዘጋጅቶላት ከነበረውም ክብር ልታፈገፍግ ሞከረች፡፡

ልጅዋ ቅዱስ ቂርቆስ ግን እናት ሆይ ከዚህ የብረት ጋር ግርማ የተነሣ አትፍሪ፤ ድንጋፄም አይደርብሽ፤ አናንያንና አዛርያን፣ ሚሳኤልንም እግዚአብሔር ከዕቶነ አሳት እንዳወጣቸው ሁሉ እኛንም ከዚህ ከብረት ጋን ሊያወጣን ችሎታ ያለው መሆኑን አትጠራጠሪ ፡፡ እናት ሆይ ከዚህ ከሚያልፈው ዓለም ጭንቅና መከራ ለማዳን ስትይ በማያልፈው በዘለዓለም እሳት ለመቀጣት ትመርጫለሸን? ይህስ አይሆንም፤ ይቅርብሽ፤ በአሁኑ ጊዜ እግዚአብሔር በመካከላችን አለና ይረዳናል፡፡ እናቴ ሆይ ሶስናን ከእደ ረበናት፣ /መምህራነ አይሁድ/ ዳንኤልን ከአፈ አናብስት ያዳነ እሱ እኛንም ከዚህ የጋን ፍላት ያወጣናል፡፡ ይልቁንም እግዚአብሔር በዚህ የብረት ጋን ውስጥ ግዳጃችንን ልንፈጽም ፈቅዶ ከሆነ ኢዮብ ንብረቱንና ገንዘቡን፣ ልጆቹንና ሚስቱን፣ በመጨረሻም የተፈጥሮ አካሉን ባጣ ጊዜ እግዚአብሔርን አመሰግነዋለሁ፤ እግዚአብሔር ሰጠ፤ እግዚአብሔር ነሣ፤ /ወሰደ/ እግዚአብሔርም እንደ ወደደ አደረገ፤ ከማለት በስተቀር ምንም የተናገረው ክፉ ነገር እንደሌለ ሁሉ እኛም የሱን ዓላማ በመከተል ይህን መከራ ልንታገሥ ይገባናል፤ አላት፡፡

ነገር ግን እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ በዚህ ምክር ልትጽናና ባለመቻሏ ቅዱስ ቂርቆስ ዓይኑን ወደ ሰማይ አቅንቶ አቤቱ አምላኬ ሆይ ይህችን ባሪያህን ከርስትህ የምትለያት ከሆነ ከባለሟልነትህ መጽሐፍ ፋቀኝ፤ አቤቱ አዝመራውን አቃጥለህ ፍሬውን ልትባርክ ትወዳለህን ይህን እንዳታደርግ ግን ቸርነትህ ትከለክልሃለች፡፡

አቤቱ እንጨቱን ቆርጣችሁ አንድዱት፤ ቅጠሉን ግን ጠብቁት፤ ብለህ ልታዝ መለኮታዊ ባሕርይህ አይደለም፤ ነገር ግን እንጨቱንም ቅጠሉንም ባንድ ጠብቁት፤ ብለህ ታዝዛለህ እንጂ፤ እንግዲህ በዚህ ምክንያት ይህን ያየ ሁሉ ማዳን የሚችል አምላክ ቢኖራቸውስ ኖሮ ከዚህ ከእሳት ባልሸሹም ነበር ብሎ አይጠራጠር፡፡

አቤቱ ዲያብሎስም ከባለሥልጣኑ ይልቅ እኔ በረታሁ፤ ቅዱሳኖቹንም ድል ነሣኋቸው፤ ብሎ እንዳይመካ ከመንጋውም አንድ በግ ቀማሁ፤ በማለት እንዳይደነፋ ለናቴ ጽኑ የሆነ ኃይለ መንፈስ ቅዱስን ስጣት፤ ብሎ በጸለየ ጊዜ ዲያብሎስ ከኢየሉጣ አጠገብ ብን ብሎ ጠፋ፡፡

ከዚህ በኋላ ቅድስት እናቱ በሰማያዊ መንግሥት አባት የሆንከኝ ልጄ ሆይ ጌታህ ኃይልን ሰጥቶኛልና የሚጠብቀንን ገድላችንን ፈጽመን ድል እናድርግ፤ እነሆ በብረት ጋኑ ውስጥ የሚነደውን እሳት በማይበት ጊዜ በለምለም /በምንጭ/ ላይ እንደሚወርድ ጠል ሆኖ አይቼዋለሁና አለችው፡፡

እኒህም ቅዱሳን ይህን በሚነጋገሩበት ጊዜ በውስጡ አንገትን የሚቆለምም፣ ልብን የሚያቀልጥ፣ ሆድን የሚሠነጥቅ፣ ሥርን የሚበጣጥስ መሣሪያ ካለበት የብረት ጋን ውስጥ ጨመሯቸው፡፡ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ከሰማይ ወረደና የብረቱን ጋን እሳት አጠፋው፤ ከቅዱሳኑም አንዳቸውንም ሳያቃጥላቸው የብረቱ ጋን ማቃጠሉና መፍላቱም ፀጥ አለ፡፡

ወንድሞቻችን ሆይ እንግዲህ በጭንቃቸው ጊዜ ገድላቸውን እስኪፈጽሙ ድረስ ይህ መልአክ ከሰማዕታትና ከጻድቃን ጎን እንደማይለይ እወቁ፡፡ ለኃጥአንም ኃጢአታቸውን ይቅር ይላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ይጸልይላቸዋል፡፡ እኛም የዚህን የሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል በዓሉን በየወሩ እያከበርን አማላጅና ወዳጅ እናድርገው፤ በዚህም በሚመጣውም ዓለም ሊረዳን ይችላልና፡፡

ዳግመኛም እለ እስክንድሮስ ሀሳቡ ሳይሳካለት ስለቀረ አሥራ አራት የሾሉና የጋሉ የብረት ችንካሮች አምጥተው ሰባቱን በእናቱ በኢየሉጣ አካል፣ ሰባቱን በቂርቆስ አካል ይቸነክሯቸው ዘንድ ጭፍሮቹን አዘዘ፡፡

ዳግመኛም የሕፃንን የእራስ ቆዳ ገፈው እሳት ውስጥ ይጨምሩት ዘንድ አዘዘ፡፡ አሁንም መልአኩ መጥቶ ይህን መከራ አራቀለት፡፡ ቀጥሎም በመቃን ውስጥ ጨምረው በገመድ እንዲጎትቱት አዘዘ፤ በዚህም ጊዜ መልአኩ አዳነው፡፡ ሕዝቡም ይህን ሁሉ ተአምር በአዩ ጊዜ እግዚአብሔርን አመሰገኑት፤ ቅዱስ ገብርኤልንም አከበሩት፡፡ እነዚህን ቅዱሳን ረድቶ ለክብር ያበቃ ቅዱስ ገብርኤል እኛንም በሃይማኖት ጸንተን ለክብር እንድንበቃ ይርዳን፡፡

የቅዱስ ገብርኤል፣የቅድስት ኢየሉጣና የቅዱስ ቂርቆስ በረከት አማላጅነት አይለየን፡፡

 

ክረምት

 ሐምሌ 15 ቀን 2006 ዓ.ም.

ካለፈው የቀጠለ

ከሐምሌ 19 እስከ ነሐሴ 21 ቀን ድረስ ያለው መካከለኛ ክረምት በመባል ይታወቃል፡፡ የክረምት ኃይልና ብርታት እንዲሁም ክረምትን ጥግ አድርገው የሚከሰቱ የተፈጥሮ ኃይላት ዑደት ያጸናበታል፡፡\ የዕለቱ ቁጥርም 33 ዕለት ነው፡፡ በዚህ ጊዜ መብረቅ፣ ነጎድጓድ ባሕርና አፍላግ ይሰለጥናሉ፡፡

መብረቅ የአምላክን ፈጣንነት፣ ነጎድጓድ የግርማውን አስፈሪነት፣ ባሕር የምሕረቱን ብዛት የሚያመለክቱ የእግዚአብሔር ባሕርይ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ በዚህ ወቅት ጥልቆቹ የውኃ ቦታዎች መጠናቸው ያድጋል፣ የወንዞች ሙላት ይጨምራል፣ ምንጮች ይመነጫሉ፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድም “ዘይመይጦ ለመብረቅ ወያጸንኦ ለነጎድጓድ ዘርዋነ ያስተጋብዕ ወያበርህ ለመሃይምናን” /ድጓ ዘክረምት/ መብረቅን የሚመልሰው፣ ነጎድጓድን የሚያበረታው የተበታተኑትን ይሰበስባል፣ ለሚያምኑባትም ዕውቀትን ያድላል በማለት ብርሃንን ከምዕራብ ወደምሥራቅ እንደሚመልሰው ሁሉ መብረቅንም ካልነበረበት በጋ ወደሚኖርበት ክረምት የሚያመጣውና መገኛውን ደመና የሚፈጥርለት እርሱ ብቻ መሆኑን ያስረዳል፡፡

ፍጻሜ ክረምት

ፍጻሜ ክረምት ከነሐሴ 22 አስከ መስከረም 25 ያለው 39 ዕለት ነው፡፡ ይህ ሦስተኛው ክፍል በሁለት ይከፈላል፡፡ አንደኛው ዕጓለ ቋዓት፣ ደሰያት፣ ዐይነ ኲሉ ይባላል፡፡ ሁለተኛው ክፍል ደግሞ ብርሃን፣ ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ በመባል ይታወቃሉ፡፡

ከነሐሴ 22 እስከ ነሐሴ 29 ቀን ድረስ ያሉት ዕለታት ውስጥ ሕይወት ያላቸው ፍጥረታትና በባሕር የተከበቡ ደሴቶች ይታወሳሉ፡፡ ዕጓለ ቋዓት ቁራን /የቁራ ግልገልን/ ሲያመለክት በሥነ ፍጥረት አቆጣጠርን ግን በክንፍ የሚበሩ አዕዋፍን ሁሉ ይወክላል፡፡

ቁራ ሲወለድ ያለ ጸጉር በሥጋው ብቻ ይወለድና ከጊዜ በኋላ ጸጉር ያወጣል፡፡ በዚህ ጊዜ እነዚህ ጥቋቁሮች አሞሮች እነርሱን ባለመምሰሉ ደንግጠው እናቱም አባቱም ጥለውት ይሸሻሉ፡፡ “እናቴና አባቴ ትተውኛልና እግዚአብሔር ግን ተቀብሎኛል” /መዝ.26፡10/ የሚለው የንጉሥ ዳዊት ቃል እናትና አባቱ ለጣሉትና ለጠሉት፣ ትተውት ለሞቱበት ሰው ብቻ ሳይሆን እንዲህ ዓይነት ድርጊት በሚፈጽመባቸው ሕያዋን ፍጥረታት ሁሉ በአምላክነቱ የሚያደርግላቸውን ርኅራኄ የሚያሳይ ቃል ነው፡፡ በዚህ ጊዜ የሚከባከበው የሚመግበው ሲያጣ እግዚአብሔር በረድኤት አፍን ከፍቶ ምግብ ሲሻ ተሕዋስያንን ብር ብር አያደረገ ከአፉ ያስገባለታል፡፡ እዮብ “ልጆቹ ወደ እግዚአብሔር ሲጮኹ የሚበሉትም አጥተው ሲቅበዘበዙ ለቁራ መብልን የሚሰጠው ማን ነው” ብሏል /ኢዮብ 38፡41/፡፡ ቁራው እግዚአብሔር የሚሰጠውን እየተመገበ ቆይቶ ሲጠነክር እንደ እናትና አባቱ ያለ ፀጉር ያወጣል፣ በዚህን ጊዜ እናትና አባቱ መጥተው ይከባከቡታል፡፡

ደስያት ማለት በውኃ የተከበቡ ጠባብ ቦታዎች ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ ኖኅ መርከብ ለፍጥረት መብዛት ምንጭ የሆኑ ነፍሳትን እንደያዘች ሁሉ አንዲት ደሴትም በውስጧ ብዙ ፍጥረታትን ትይዛለችና፡፡ ደሴት የኖኅ መርከብ ያረፈችበት የዓራራት ተራራ ምሳሌ ናት፡፡ እንዲሁም ከደሴያት የተጠጉ ድኅነትን እንደሚያገኙ ሁሉ በጥምቀት አማካኝነት ወደ ቤተ ክርስቲያን የተጠጉ ሁሉ ከሞት ሥጋና ከሞተ ነፍስ የሚጠብቃቸው የነፍሳቸውን እረኛ ኢየሱስ ክርስቶስን ያገኛሉና ደሴት የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናት፡፡
ዓይን /ዓይነ ኲሉ፣ የሁሉ ዓይን/ የተጠቀሰው ሥጋዊ ዓይንን ለማመልከት ሳይሆን “ገንዘብህ ባለበት በዚያ ልብህ ይሆናል” /ማቴ.6፡21/ እንደተባለ የሥጋንም ሆነ የነፍስን ፍላጎት ለማሟላት የሚረዳ የሕሊና መሸትንና የመንፈስ ስብራትን የተመለከተ ፈቃደ መንፈስ ነው፡፡ “ልብ ካላየ ዓይን አያይም” እንዲሉ፡፡ /መዝ.136፡25/ ለሥጋ ምግብን የሚሰጥ “የሁሉ ዓይን አንተን ተስፋ ያደርጋል አንተም ምግባቸውን በየጊዜው ትሰጣቸዋለህ” መዝሙረኛው እንዳለ፡፡ ቅዱስ ያሬድም “ውኃውን በደመና አቁማዳ ይቋጥራል፣ ነገር ግን ደመናውን አይቀደድም፡፡ በዚህ መጋቢነት የሁሉ ነፍስ ዓይን እርሱን ተስፋ ያደርጋል” አለ፡፡ የእግዚአብሔር ቸርነቱን እያሰብን ሳንታክት ወደ እርሱ ብንመለስ እርሱ ወደ እኛ ይመለሳል፣ ብንለመነውም ይሰጠናል በማለት ሊቁ ተናግሮአል፡፡

ከላይ ያየነው ፍጻሜ ክረምት የመጀመሪያው ክፍል ሲሆን ሁለተኛው ክፍል የሚባሉት ብርሃን፣ ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ ይባላሉ፡፡ ቅዱስ ያሬድ በድርሰቱ ስለብርሃን ተፈጥሮና የሥራ ባሕርይ አስመልክቶ “ዘአንተ ታመጽእ ርእየቱ ብርሃን ወፈለጥከ ብርሃነ ለአዝማን ወለጊዜያት፣ የብርሃንን ወገግታ የምታመጣው አንተ ነህ ዘመናትንና ጊዜያትን በብርሃን ማእከላዊነት የለየሃቸውም አንተ ነህ” /ድጓ ዘክረምት/ በማለት ሊቁ እንዲል፡፡

ድጓ ዘክረምት “እስመ ብርሃን ሠረቀ ሎሙ” እግዚአብሔርን መፍራት እንድታውቅ በጠዋት ፀሐይ፣ በነግህ ብርሃን ይወጣልሃል እንዲሁም ሆኖ ብርሃን ወጥቶአልና ሰው ወደ ሥራው ተሠማርቶ እስኪመሽ ድረስ ይውላል እንዲል ቅዱስ ያሬድ፡፡

ማጠቃለያ

በዚህ አጭር ጽሑፍ ሙሉ የቅዱስ ያሬድን ትምህርት መግለጽ ባይቻልም ለቅምሻ ያህል ቅዱስ ያሬድ በዘመነ ክረምት አስተምሮቱ ምን እንደሚመስል ተመልክተናል፡፡ ይህ ዘመን ጠልና የልምላሜ የዘርና የቡቃያ ጊዜ በመሆኑ ከቅጠል በቀር በምድር ላይ ከወደቁት ዘሮች አብዛኛው ፍሬ አይገኝባቸውም፡፡ ዘመኑ ለመንግሥተ ሰማያት ያልተዘጋጀ፣ የንስሐ ፍሬ ያላፈራ ሰው ምሳሌ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሸሽታችሁ በክረምት /ሞታችሁ ያለመልካም ሥራ/ እንዳይሆን ተግታችሁ ጸልዩ ያለው በደላችንን ባለማወቅ ለንስሐ ሕይወት ሳንበቃ በለጋነት ዕድሜያችን የምንሞተው ሞት አሳዛኝ መሆኑን ሲገልጽ ነው፡፡ ሊቁ በዚህ ክረምት /ዘመናችን/ ገና በቅጠል /ያለ ሥራ/ ሳለን ሽሽታችን /ሞታችን/ ያለፍሬ አይሁን በማለት ቅዱስ ያሬድ ድርሰቱን ከወንጌሉና ከዘመኑ ጋር በማጣጣም አስቀምጦልናል፡፡

 

trinity 2

በዓለ ሥላሴ

ሐምሌ 7 ቀን 2006 ዓ.ም.

መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

 trinity 2

ወበዛቲ ዕለት ቦኡ ሥሉስ ቅዱስ ውስተ ቤተ አብርሃም ወተሴሰዩ ዘአቅረቦ ሎሙ፡፡ በከመ መጽሐፍ ውስተ ኦሪት ወአብሠርዎ ልደቶ ለይስሐቅ ወባረክዎ፡፡ በዚችም ቀን ልዩ የሆኑ ሦስቱ አካላት /ቅድስት ሥላሴ/ በኦሪት መጽሐፍ እንደ ተጻፈ ወደ አብርሃም ቤት ገቡ ያቀረበላቸውንም ተመገቡ፡፡ የይስሐቅንም ልደት አበሠሩት ባረኩት አከበሩትም፡፡

መጽሐፈ ስንክሳር ዘሐምሌ ሰባት

ሥላሴ ማለት በቅዱሳት መጻሕፍት መሠረት አንድ አምላክ በሦስት አካላት እንዳለ ለአበው ለነቢያትና ለሐዋርያት መገለጡን አምነን የምንማረው ትምህርት ነው፡፡ሥላሴ ማለት የግእዝ ቃል ሲሆን ሦስት፤ ሦስትነት ማለት ነው፡፡

የአንድ አምላክ በሦስትነት መገለጥን ለመረዳት በኦሪት ዘፍጥረት 1፡26 ላይ በተገለጠው መሠረት “እግዚአብሔርም አለ ሰውን በመልካችን እንደምሳሌችን እንፍጠር” ይላል ይህ አገላለጽ “እግዚአብሔርም አለ” ሲል አንድነትን (አንድነታቸውን) “እንፍጠር” ሲል ከአንድ በላይ (ሦስትነትን) መሆንን ያስረዳል፡፡

በኦሪት ዘፍጥረት 3፡22 ላይ “አዳም ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ” የሚለው አገላለጽ ከአንድ በላይ መሆንን የሚያስረዳ ነው፡፡በኦሪት ዘፍጥረት 11፡5-7 የተጠቀሰው “ኑ እንውረድ ቋንቋቸውን እንደባልቅ”በማለት ሥላሴ የተናገሩት ከአንድ በላይ (ሦስትነት) መሆንን የሚያመለክት ነው፡፡

በኦሪት ዘፍጥረት18 ላይ ሥላሴ ለአብርሃም እንደተገጹለት የሚያስረዳ ሀሳብ የያዘ አገላለጽ ሲሆን ሥላሴ ለአብርሃም በመገለጻቸው አብርሃም ሥላሴን በእንግድነት አሰተናግዷል፡፡የሥላሴ ባለሟል መሆኑ ተረጋግጧል፡፡ በእርግናው ጊዜ ልጅ እንደሚያገን ተበስሮለታል፡፡ ዘሩ እንደ ሰማይ ከዋክብት እንደ ምድር አሸዋ እንደሚበዛ በሥላሴ ቃል ተገብቶለታል፡፡

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሚጠመቅበት ጊዜም የሥላሴ ምስጢር ተገልጧል፡፡ “እግዚአብሔር አብ የምወደው ልጄ ይህ ነው” ሲል እግዚአብሔር ወልድ ሲመጠቅ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል ተገልጧል፡፡ ማቴ.3፡13 አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያትን ሂዱና በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችሁ ደቀመዛሙርቴ አድርጉ” ማቴ. 14፡28 ሲል ሦስትነት የሚገልጽ መልእክት አስተላልፏል፡፡ እንግዲህ ሥላሴ ስንል በስም በአካል፣ በግብር የተለዩ መሆናቸውን ያስረዳል፡፡ ይኸውም፡-

የአካል ሦስትነት፡-

    • አብ የራሱ መልክ፣ ገጽ፣ አካል አለው፡፡

    • ወልድ  የራሱ መልክ፣ ገጽ፣ አካል አለው፡፡

    • መንፈስ ቅዱስ፡- የራሱ መልክ፣ ገጽ አካል አለው፡፡

የስም ሦስትነት ስንል፡- የአንዱ ስም ለአንዱ የማይሆን አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ በመባል ይጠራሉ፡፡

የግብር ሦስትነት ስንል፡- አብ ወላዲ፣ አስራጺ ሲሆን ወልድ ተወላዲ ነው የተወለደውም ከአብ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ሰራጺ ነው፡፡ የሰረጸውም ከአብ ነው፡፡

የሥላሴን አንድነትና ሦስትነት ለመረዳት በሥላሴ ፈቃድ መጻሕፍት እንዳስተማሩ ሊቃውንት እንደተረጉሙልን እንጂ ማንም በገዛ ፈቃዱ ተመራምሮ አይደርስበትም፡፡

በዓለ ሥላሴ

በዓላት የሰው ልጅ በእግዚአብሔር የተደረገለትን የቸርነት ሥራ በማሰብ ቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታት ያደረጉትን ተጋድሎና ተአምራት በመስማትና በማሰማት የተደረገውን ድንቅ ነገር በመዘከር በደስታ የሚከበሩ ዕለታት ናቸው፡፡ “በቃለ አሜን ወበትፍስሕት ድምፁ እለ ይገብሩ በዓለ፡- በዓለ የሚያደርጉ ሰዎች የደስታና የምስጋና ቃል አለው” እንዳለ ቅዱስ ዳዊት መዝ.41፡5 የበዓል መከበርን ያሳወቁት ሥላሴ ሲሆኑ፤ ሥላሴ ፍጥረታትን ስድስት ቀናት ፈጥረው ሰባተኛውን ቀን ቀዳሚትን አርፈውበታል፡፡ “በሰባተኛውም ቀን ከሥራው ሁሉ ዐረፈ፡፡ እግዚአብሔር ሰባተኛውን ቀን ባርከውም ቀድሰውም እግዚአብሔር ሊያደርገው ከፈጠረው ሥራ ሁሉ በእርሱ ዐርፏልና” ዘፍ.1፡1-3 እንዲል

በዚህ መሠረትነት በዓል እንዲከበር የመደቡት ሥላሴ ሲሆኑ የመጀመሪያው የሥላሴ መታሰቢያና የበዓል አከባበር መጀመሪያ የሆነችው ቀዳሚት ናት፡፡

የዛሬው ሐምሌ 7 ቀንም ሥላሴ በአብርሃም ቤት ገብተው ቸርነታቸውና ፍቅራቸውን የገለጹበት፣ አብርሃምን የባረኩትና ልጅ እንደሚወልድ፣ መጻዒው ሕይወቱን የነገሩት ዕለት ስለሆነ በዓሉን ስናዘክር ሥላሴን እናመሰግናለን፡፡ ቸርነታቸው፣ ፍቅራቸው፣ ትድግናቸው እንዳይለየን እንማጸናለን፡፡ የቅድስት ሥላሴ ቸርነት አይለየን፡፡

“ሰማዕታት የዚህችን ዓለም ጣዕም በእውነት ናቁ፤ ደማቸውን ስለ እግዚአብሔር አፈሰሱ፤ ስለ መንግሥተ ሰማያት መራራ ሞትን ታገሱ፡፡” ውዳሴ ማርያም ዘሐሙስ ቁ.6

 

ሶሪያዊው ቅዱስ ኤፍሬም በቅዱስ ዳዊት ሕይወት የተከወናውን በምሥጢር ስቦ አምጥቶ የሰማዕታትን ክብር አጎልቶ ተናግሮበታል፡፡ ታሪኩ እንዲህ ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊትን እግዚአብሔር አምላክ ለእስራኤል አነገሠው፡፡ በዙሪያው የነበሩ ኤሎፍላዊያንን አጥፍቶ ደብረ ጽዮንን /መናገሻ ከተማውን/ አቅንቶ ሲኖር ከዕለታት አንድ ቀን ዳዊት ታመመ፡፡የዳዊትን መታመም ሰምተው፣ ካሉበት ተነስተው የዳዊትን ከተማ በተለይም ቤተልሔምን ከበቧት፡፡ ዳዊት ይህን ሰምቶ “ወይ እኔ ዳዊት! ድሮ ታመምሁና ጠላቶቼ ሰለጠኑ ሲል የኀያላኑን ልቦና ለመፈተን ከቤተልሔም ምንጭ ውኃ ማን ባመጣልኝ?” አለ፡፡ በዚህ ጊዜ የጭፍሮቹ አለቆች ሦስቱ ማለትም አዲኖን፣ ኢያቡስቴ ኤልያና ረዋታቸውን /የውኃ መያዣ/ ይዘው፣ ጦራቸውን አሰልፈው፣ ጠላቶቹን ድል ነስተው፣ ዳዊት ሊጠጣ የወደደውን ውኃ አመጡለት፡፡ቅዱስ ዳዊትም ያንን ውኃ አፈሰሰው “ለምን አፈሰስከው?” ቢሉት “ደማችሁን መጣጠት አይደለምን?” ብሎ፤ ይህም ከጽድቅ ገብቶ ተቆጠረለት፡፡ 2ሳሙ.23፥13-17

አባቶቻችን ይህንን ሲያመሰጥሩት የፍጥረት ሁሉ ቁንጮ አባታችን አዳም ከተድላ ገነት ወደ ምድረ ፋይድ፥ ከነጻነት ወደ መገዛት፥ ከልጅነት ወደ ባርነት፥ በወረደና ፍትወታት እኩያት ኀጣውእ በጠላትነት በተነሱበት ጊዜ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ከተገኘ ከጌታ ጎን የተገኘ ማየ ገቦ ይጠጣ ዘንድ ወደደ፡፡ የትሩፋት አበጋዞች ሃይማኖት፣ ተስፋ፣ ፍቅር፣ ፈጥነው ተነሱ፡፡ በአጋንንት ከተማ ተዋጉለት ይጠጣው ዘንድ የወደደውን ማየ ገቦ አመጡለት፡፡ ማለትም የአዳም ልጅነት በከበረው የክርስቶስ የደሙ ፈሳሽነት የሥጋው መሥዋዕትነት ተመለሰለት፡፡ ይህንን ለአዳምና ለልጆቹ የባህርይ አምላክ ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተቀበለውን ፀዋትወ መከራ እያሰቡ ሰማዕታት በእግዚአብሔር ፍቅር ተቃጥለው “እግዚአብሔርን ካዱ ለጣዖት ሰገዱ” ሲባሉ “እግዚአብሔርን አንክድም ለጣዖት አንሰግድም” ብለው ደማቸውን አፈሰሱ ይህም ጽድቅ ሆኖ ተቆጠረላቸው፡፡ /ውዳሴ ማርያም ትርጓሜ ዘሐሙስ/

“ሰማዕት” ማለት ምስክር ማለት ነው፡፡ ይህ ደማቸውን ስለ እግዚአብሔር ፍቅር ብሎ ማፍሰስ ጽድቅ ሆኖ ተቆጠረላቸው፥ የዳዊት ወታደሮች ስለ ዳዊት ፍቅር ብለው “ደማችን ይፍሰስ” እንዲሉ፤ ዳዊትም ያመጡለትን ውኃ መጠጣት ደማችሁን እንደመጠጣት ነው ብሎ በፍቅር ምክንያት ውኃውን እንዳፈሰሰው፥ ይህም ጽድቅ ሆኖ እንደተቆጠረለት፥ የእግዚአብሔር ወዳጆች የሆኑ ቅዱሳን ሰማዕታትም እግዚአብሔርንና የእግዚአብሔር ሃይማኖት የሆነችው እውነተኛይቱን ሃይማኖት ወደው ደማቸውን አፈሰሱ፣ አጥንታቸውን ከሰከሱ፣ ስለዚህ እንደ ፀሐይ አብርተው በሰማያት ዛሬም ስለ እኛ እየማለዱ አሉ፡፡

ከእነዚህም መካከል ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታስባቸዋለች፡፡ ሐምሌ 5 ሰማእትነት የተቀበሉበት ቀን መታሰቢያቸውን ታዘክራለች፡፡ ከመጽሐፈ ስንክሳር ዘርኀ ሐምሌ ዕለቱን በማስመለከት ያገኘነውን መረጃ እንዲህ ተዘጋጅቷል፡፡

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሐምሌ አምስት በዚች ቀን የክቡራንና የዐበይት አባቶቻችን ሐዋርያት የጴጥሮስና የጳውሎስ የሰማዕትነታቸው መታሰቢያ ነው፡፡ ሰላም ለከ ጴጥሮስ ተልሚድ፡፡ ዘኢያቅበጽከ ተስፋ ነገረ ኑፋቄ ወካህድ፡፡ እንዘ ትረውጽ ጥቡዐ ለመልእክተ ክርስቶስ ወልድ፡፡ አመ ለሊከ ወሬዛ ቀነትከ በእድ፡፡ ወአመ ልህቀ አቅነትከ ባዕድ፡፡

ይህም ጴጥሮስ ከቤተ ሳይዳ ነበር ዓሣ አጥማጅም ነበር ጌታችንም ከተጠመቀባት ዕለት ማግሥት አግኝቶ መረጠው፤ ከእርሱ አስቀድሞም ወንድሙ እንድርያስን አግኝቶ መረጠው፡፡ መድኃኒታችንንም እስከ መከራው ጊዜ ሲአገለግለው ኖረ፤ ፍጹም ሃይማኖት፣ ለጌታውም ቅንዓትና ፍቅር ነበረው፡፡ ስለዚህም በሐዋርያት ሁሉ ላይ አለቃ አድርጎ ሾመው፡፡

ጌታችንም ሰዎች ማን እንደሆነ ማንም እንደሚሉት ስለ ራሱ በጠየቃቸው ጊዜ ሌሎቹ ኤርምያስ ይሉሃል ወይም ኤልያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው ይሉሃል አሉት፡፡ ጴጥሮስ ግን የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ አንተ ነህ አለ፡፡ ጌታችንም የሃይማኖት አለት የቤተ ክርስቲያንም መሠረት ነህ ብሎ ብፅዕና ሰጠው የመንግሥተ ሰማያትንም መክፈቻ ቁልፍ ሰጥቼሃለሁ አለው፡፡

አጽናኝ የሆነ የመንፈስ ቅዱስንም ጸጋ ከተቀበለ በኋላ ተናጋሪዎች በሆኑ በዚህ ዓለም ተኲላዎች መካከል ገባ በውስጣቸውም ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ሰበከ፤ ቊጥር የሌላቸው ብዙዎች አሕዛብንም መልሶ የዋሆች ምእመናን አደረጋቸው፡፡

ጌታችንም የማይቈጠሩ ታላላቅ ድንቆችና ተአምራቶችን በእጆቹ አደረገ፤ ጥቅም ያላቸው ሦስት መልእክቶችንም ጽፎ ለምእመናን ላካቸው፡፡ ለማርቆስም ወንጌሉን ተርጒሞ አጽፎታል፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ ሮሜ ከተማ ገባ፤ የከተማው መኳንንት ወደሚሰበሰቡበት ወደ ታላቁ የጨዋታ ቦታም ሔዶ በታላቅ ድምፅ እንዲህ ብሎ ተናገረ የሚራሩ ብፁዓን ናቸው ለርሳቸውም ይራሩላቸዋልና የዚህንም ተከታታይ ቃሎች ተናገረ፡፡ ከዚያም ከዚያ የነበሩ አራት የደንጊያ ምሰሶዎችም በሚያስፈራ ድምፅ አሜን አሉ፤ የተሰበሰቡትም ይህን ቃል በሰሙ ጊዜ ደነገጡ፡፡ ከሰባ ዓመት ጀምሮ ሰይጣን ያደረበት አንድ ሰው ነበረ፤ ከእነዚያ ደንጋዮች ቃልን ስለ ሰማ ያን ጊዜ ጋኔኑ ጣለው ከእርሱም ወጥቶ ሔደ፡፡ መኳንንቱም ፈርተዋልና ስለዚህ ነገር እያደነቁ ወደ ቤታቸው ገቡ፡፡

ከከተማ መኳንንቶችም ቀውስጦስ የሚባል አንዱ ወደ ቤቱ በገባ ጊዜ ስሟ አክሮስያ ለምትባል ሚስቱ ዓለምን ስለ መተው ለድኆችም ስለመራራትና የመሳሰለውን ቃል ጴጠሮስ እንዴት እንዳስተማረ ነገራት፡፡ እርሷም በሰማች ጊዜ በልቧ ነቅታ ይህ ነገር መልካምና ድንቅ ነው አለች፡፡ ጴጥሮስ ያስተማረውንም ሁሉ ያደርጉ ዘንድ በአንድነት ተስማሙ ከዚህም በኋላ ገንዘባቸውን ሁሉ ለድኆች ሰጡ ከዕለት ራት በቀር ምንም አላስቀሩም፡፡ ከጥቂት ቀኖችም በኋላ ንጉሡ ስለ መንግሥት ሥራ ከርሱ ጋራ ለመማከር በቶሎ እንዲደርስ ወደርሱ መልእክትን ላከ፡፡

ቀውስጦስም ይህን በሰማ ጊዜ ገንዘብ ስላልነበረው ፈርቶ ደነገጠ ተጨነቀም፡፡ ምክንያትም አመካኝቶ ይሠወር ዘንድ ከሚስቱ ጋራ ተማከረ፡፡ እርሷ ግን ምክንያት አታድርግ ነገር ግን ወደ ንጉሡ ሒድ የጴጥሮስም አምላክ ጐዳናህን ያቅናልህ አለችው፤ እርሱም ነገርዋን ተቀብሎ ወደ ንጉሡ ሔደ፤ በመንገድም ከእግዚአብሔር የታዘዘ ብዙ በረከትን አገኘ፡፡ ወደ ንጉሡም ደረሰ፤ ንጉሡም በደስታና በክብር ተቀበለው፡፡

ከሦስት ዓመት በኋላም ወደ ቤቱ በተመለሰ ጊዜ ሁለቱ ልጆቹ የተመረዘ ውኃ ጠጥተው እነሆ ሙተው ነበር፤ ሚስቱም ለእርሱ መንገርን ፈራች ብዙ ምሳሌዎችን ከመሰለችለት በኋላ ነገረችው፡፡ በሰማ ጊዜም እጅግ አዝኖ አለቀሰ፡፡ ሚስቱም እንዲህ አለችው ጌታዬ ሆይ ልባችን የሚጽናናበትን እርሱ ያደርግልናልና የጴጥሮስን ፈጣሪ እግዚአብሔርን እንለምነው፡፡ ሊጸልዩም በጀመሩ ጊዜ ቀውስጦስና አክሮስያ ሆይ የደቀ መዝሙሬ የጴጥሮስን ቃል ስለሰማችሁና ስለተቀበላችሁት ስለዚህ ልጆቻችሁን በሕይወታቸው እሰጣችኋለሁ የሚል ቃልን ከሰማይ ሰሙ ያን ጊዜም ልጆቻቸው ድነው ተነሡ ቀውስጦስና ሚስቱም ደስ አላቸው የተመሰገነ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት፡፡

አሊህም ከሞት የተነሡ ልጆች ለቅዱስ ጴጥሮስ ደቀ መዝሙሮቹ ሆኑ፤ የአንዱ ስሙ ቀሌምንጦስ ነው እርሱም ቅዱስ ጴጥሮስ ያየውንና ጌታችን በሥጋ ወደ ሰማይ በሚዐርግ ጊዜ የገለጠለትን ምሥጢር ሁሉ የነገረው ነው፤ ሰዎች ሊያዩአቸው የማይገባቸውን መጻሕፍትን አስረከበው፡፡ ይህንም ቀሌምንጦስን ሊቀ ጵጵስና ወንድሙን ዲቁና ሾማቸው፡ ከዚህም በኋላ ዳግመኛ ቅዱስ ጴጥሮስ አምላክን የወለደች የንጽሕት ድንግል እመቤታችን ማርያም ክብርዋን በምሳሌ አየ፡፡

በቀስት አምሳል ደመናን አይቷልና በላይዋም የብርሃን ድንኳን ነበረ በድንኳኑም ውስጥ አምላክን የወለደች ቅድስት ድንግል ማርያም ተቀምጣለች፡፡ በእጆቻቸው ውስጥ የነበልባል ጦሮችንና ሰይፎችን የያዙ መላእክትና የመላእክት አለቆች በዙሪያዋ ነበሩ፡፡ እንዲህም እያሉ ያመሰግኗት ነበር ከእርሷ የድኅነት ፍሬ የተገኘ የሠመረች የወይን ተክል አንች ነሽ፡፡ ማሕፀንሽ የእግዚአብሔርን በግ የተሸከመ ንጽሕት አዳራሽ አንቺ ነሽ፡፡

ሁለተኛም እንዲህ ይሏት ነበር፡፡ የብርሃን እናቱ ሆይ የምሕረት መገኛ ሆይ ደስ ይበልሽ የአማልክት አምላክ የፍጥረት ሁሉ ጌታ የሆነ የመድኅን ዙፋን ሆይ ደስ ይበልሽ ክብርና ምሥጋናን የተመላሽ የፍጥረት ሁሉ እመቤት ደስ ይበልሽ፡፡

መላእክትም ምሥጋናዋንና ሰላምታዋን በአደረሱ ጊዜ ክብር ምሥጋና ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእርስዋ ተገልጦ ከእርስዋ በቀር ማንም ሊያውቀው የማይቻል ነገርን ነገራት ወዲያውኑም ምድር ተናወጸች ሊነገር የማይቻል ምሥጢራትንም ገለጠላት፡፡

ከዚህም በኋላ መድኃኒታችን በሀገሩ ሁሉ ቅዱስ ወንጌልን ይሰብክ ዘንድ ጴጥሮስን አዘዘው፡ ጴጥሮስም ወጥቶ ሔደ፤ ኢዮጴ ወደምትባል የባሕር ዳርቻና ልድያ ወደምትባል አገር ደረሰ፡፡

በአንዲት ዕለትም በኢዮጴ ሳለ ብርህት ደመና ዞረችው፡፡ እነሆም ሰፊ መጋረጃ ወደ እርሱ ወረደች፤ በውሰጥዋም የእንስሳት የምድረበዳ አውሬዎችና የሰማይ አዕዋፍ አምሳል ነበረ፡፡ ጴጥሮስ ሆይ ተነስና አርደህ ብላ የሚል ቃልም ከሰማይ ጠራው፡፡ ጴጥሮስም አቤቱ አይገባኝም ርኩስ ነገር አልበላም ወደ አፌም ከቶ አልገባም አለ፡፡

ያም ቃል ዳግመኛ ጠራውና እግዚአብሔር ንጹሕ ያደረገውን አንተ ርኩስ ነው አትበል አለው፡፡ ያም ቃል ሦስት ጊዜ መላልሶ እንዲህ ነገረው፡፡ በየንግግሩም ወደ እሪያዎች ወደ አራዊትና ወደ አዕዋፍ ስዕሎች ያመለክተው ነበር፤ ከዚህም በኋላ ያቺ መጋረጃ ወደ ሰማይ ተመለሰች፡፡

ጴጥሮስም ስላየው ራዕይ አደነቀ፤ ይህም ራዕይ ወደ ፈጣሪያቸው እግዚአብሔር የሚመለሱ አሕዛብን ስለመቀበል እንደሆነ አስተዋለ፤ ለወንሞቹ ሐዋርያትም አሕዛብ የእግዚአብሔርን ቃል እንደተቀበሉ የመቶ አለቃ ቆርኔሌዎስንም ከወገኖቹ ጋር እንዳጠመቀው ነገራቸው፡፡

ከዚህ በኋላም ጴጥሮስ ከዮሐንስ ጋራ ጌታችን እንዳዘዛቸው ወደ አንጾኪያ ከተማ ገቡ፡፡ የአገሪቱንም ሁኔታ ይጠይቅ ዘንድ ጴጥሮስ ዮሐንስን ላከው ሰዎችንም አግኝቶ ክፉ ነገር ተናገሩት፡፡ ሊገድሉትም ፈለጉ፤ እያለቀሰም ተመለሰ፤ ሰውነቱም ተበሳጨች ጴጥሮስንም አለው አባቴ ሆይ የእሊህ ጎስቋሎች ክፋታቸው እንዲህ ከሆነ ወደ ነገሥታቱና ወደ መኳንንቱ ገብተን በጌታችን ስም በሰበክን ጊዜ ምን እንሆን ይሆን እንዴትስ ሃይማኖትን እናስተምራለን፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም ወዳጄ ሆይ የሃያውን ቀን መንገድ በአንዲት ሌሊት ያመጣን እርሱ ሥራችንን በአንዲት መልካም ያደርግልናልና አትፍራ፤ አትዘንም አለው፡፡ከዚህም በኋላ ወደ ከተማ መካከል ገብተው ክብር ይግባውና በጌታችን ስም ሰበኩ የከተማው ሰዎችና የጣዖታቱ አገልጋዮችም በእነርሱ ላይ ተሰበሰቡ ታላቅ ድብደባንም ደበደቧቸው፤ አጎሳቆሏቸውም፤ ግማሽ የራስ ጠጉራቸውንም ላጭተው ተዘባበቱባቸው፤ አሥውም በግንብ ውስጥ ጣሏቸው፡፡

ከዘህም በኋላ ተነሥተው ይረዳቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ጸለዩ፤ ወዲያውኑም ክብር ይግባውና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኪሩቤልና ሱራፌል እያጀቡት ተገለጠላቸውና እንዲህ አላቸው፡፡ መረጥኋችሁ ጴጥሮስና ዮሐንስ ሆይ በዘመኑ ሁሉ እኔ ከእናነተ ጋራ እኖራለሁና አትፍሩ፤ አትዘኑም፡፡ ለመዘባበቻም በራሳችሁ መካከል ስለላጩአችሁ አታድንቁ ይህም መመኪያና ክብርን የክህነት ሥርዓትና ምልክትንም ይሆናችኋል፡፡ ካህን የሚሆን ሁሉ ያለዚህ ምልክት ሥጋዬንና ደሜን ማቀበል አይችልም፡፡

ይህ ምልክት እያለው የሚሞት ካህንም ኃጢአቱ ይሠረይለታል፡፡ ይህን ካላቸው በኋላ ከእርሳቸው ዘንድ በክብር ዐረገ፡፡ ከዚህም በኋላ ጳውሎስ መጥቶ ዮሃንስን ተገናኘው የዚህ አገር ሰዎች ያደረጉብህ ምንድነው እርሱም ስለ እኔ አታድንቅ የሐዋርያትንም አለቃ በእኔ ላይ ባደረጉት አምሳል አድርገውበታልና አለው፡፡ ጳውሎስም አጽናናቸው እንዲህም አላቸው እኔ በጌታችን ፈቃድ ወደ ከተማ ውስጥ ገብቼ እናንተንም አስገባችኋለሁ፡፡

ከዚህም በኋላ ጳውሎስ ሔዶ ምክንያትን ፈጠረ ጣዖታቸውንም እንደሚያመልክ መስሎ ሐዋርያትን እንዲያቀርቡለትና ስለ ሥራቸውም እንዲጠይቃቸው የከተማውን መኳንንት አነጋገራቸው፡፡መኳንንቱም ወደ ጳውሎስ እንዲያቀርቧቸው አዘዙ፤ በቀረቡም ጊዜ ጳውሎስ ስለ ሥራቸው ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም ድንቆችንና ተአምራቶችን ለሚያደርግ ለክርስቶስ ደቀ መዝሙሮቹ እንደሆኑ ነገሩት፡፡ ዳግመኛም እናንተ እንደርሱ ማድረግ ትችላላችሁን አላቸው፡፡ እነርሱም አዎ በእርሱ ስም ሁሉን ሥራ መሥራት እንችላለን አሉት፡፡

ከዚህም በኋላ ከእናቱ ማሕፀን ዕውር ሆኖ የተወለደውን ዐይኑን አበሩ፡፡ የንጉሡንም ልጅ ከሞተ በሦስት ወሩ ሥጋውም ከተበላሸ በኃላ ከመቃብር አስነሡት፡፡ ንጉሡና የከተማ ሰዎች ሁሉ ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ፡፡ ጴጥሮስም ምድሩን ረግጦ ውኃን አፈለቀ፤ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቋቸው በቀናች ሃማኖትም እንዲጸኑ አደረጓቸው፡፡

ከዚህም በኋላ በሎዶቅያ ያሉ ምእመናን የቂሳሮስ ባሕር ከወሰኑ አልፎ ብዙ ሰዎችን ከአትክልት ቦታዎቻቸውና ከከብቶቻቸው ጋራ እንዳሰጠማቸው ወደ ቅዱስ ጴጥሮስ ላኩ፤ ጴጥሮስም ተወዳጅ ዮሐንስን ወደ እነርሱ ላከ፡፡ዮሐንስም ወደ እነርሱ ሲጓዝ ዳና በግ አገኘ፤ በጉንም እንዲህ ብሎ ላከው፤ ወደ ቂሳሮስም ወንዝ ሒድ የክርስቶስ ደቀ መዝሙሩ ወደ አንተ ልኮናል ወደ ቀድሞው ወሰንህ ትገባ ዘንድ አንተ በእግዚአብሔር ቃል የታሰርክ ነህ ብሎሃል በለው፡፡ ያን ጊዜ በጉ እንዳዘዘው አደረገ፤ ወንዙም ሸሽቶ ወደ ቦታው ተመለሰ፡፡ ቁጥር የሌላቸው ብዙዎች የከተማ ሰዎችም ይህን አይተው በጌታ አመኑ፡፡

ከዚህም በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ አልፎ ወደ ሮሜ ከተማ ገባ በዚህም ሥፍራ መሠሪው ሲሞን ተቃወመው፤ እርሱንም ከአየር ላይ አውርዶ ጥሎ አጠፋው፤ ይህንንም ድንቅ ሥራ አይተው ብዙዎች ሕዝቦች አመኑ፡፡ የከተማው ገዥ የአክሪጶስ ቁባቶችም የጴጥሮስን ትምህርት ተቀበሉ፡፡ ሌሎችም የከበሩ ብዙዎች ሴቶች ትምህርቱን በመቀበል ከባሎቻቸው ርቀው ንጽሕናቸውን ጠበቁ፡፡

ስለዚህም ነገር ቅዱስ ጴጥሮስን ሊገድሉት የሮሜ መኳንንት ተማከሩ፡፡ የአልታብዮስ ሚስትም እንዳይገድሉት ከሮሜ ከተማ ወጥቶ እንዲሔድ ወደ ቅዱስ ጴጥሮስ ላከች፤ ምእመናን ወንድሞችም ውጣ አሉት፤ እርሱም ቃላቸውን ተቀበለ፡፡ ትጥቁንም ለውጦ ከከተማው ወጣ፡፡ በሚወጣበትም ጊዜ መስቀል ተሸክሞ ወደ ከተማ ሲገባ ጌታችንን አገኘውና አቤቱ ጌታዬ ወዴት ትሔዳለህ አለው፡፡ ጌታም ልሰቀል ወደ ሮሜ ከተማ እሔዳለሁ ብሎ መለሰለት፤ ቅዱስ ጴጥሮስም አቤቱ ዳግመኛ ትሰቀላለህን አለው፡፡

ያን ጊዜም ጎልማሳ ሳለህ ወገብህን በገዛ እጅህ ታጥቀህ ወደ ወደድከው ትሔዳለህ በሸመገልክ ጊዜ ግን እጅህን ታነሣና ሌላ ያስታጥቅሃል፤ ወደማትወደውም ይወስድሃል ያለውን የጌታችንን ቃል አሰበ አስተዋለውም፡፡ያን ጊዜም ወደ ከተማው ተመልሶ ክብር ይግባውና ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የሆነውን ለወንድሞች ነገራቸው እነርሱም እጅግ አዘኑ፡፡

ንጉስ ኔሮን ቅዱስ ጴጥሮስን እንዲሰቅሉት አዘዘ፡፡ ሊሰቅሉትም በያዙት ጊዜ ወታደሮችን እንዲህ ብሎ ለመናቸው፡፤ የክብር ንጉስ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ላይ ሆኖ ስለተሰቀለ እኔ ቁልቁል ልሰቀል ይገባኛል፡፡ ወዲያውም እንደነገራቸው ሰቀሉት፡፡ ተሰቅሎ ሳለም ለምእመናን የሕይወትን ቃል አስተማራቸው በቀናች ሃማኖትም እንዲጸኑ አዘዛቸው ከዚህም በኋላ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባታችን በቅዱስ ጴጥሮስ ጸሎት ይማረን፤ በረከቱም ከእኛ ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን፡፡ ሰላም ለጳውሎስ ሃይማኖተ ክርስቶስ ዘአግሀደ፡፡ እስከ አቁሰልዎ በሰይፍ ወመተርዎ ክሣደ፡ ከመ ያግብእ ሕዝበ ሕየንተ ቀዳሚ ሰደደ፡፡ በላዕለ አብዳን ተመሰለ አብደ፡፡ ወለአይሁድኒ ኮኖሙ አይሁድ፡፡

በዚህችም ቀን ዳግመኛ ልሳነ ዕረፍት የክርስቶስ አንደበት የእውቀት አዘቅት የቤተ ክርስቲያን መብራት የቅዱስ ሐዋርያው ጳውሎስ የሰማዕትነቱ መታሰቢያ ነው፡፡ እንደ ስሙም ትርጓሜ መሪ አመስጋኝ ወደብ ጸጥታ ነው፡፡ይህም ጳውሎስ አስቀድሞ በክርስቶስ ያመኑትን የሚያሳድድ ነበረ፡፡ እርሱም ከብንያም ወገን የፈሪሳዊ ልጅ ነው፡፡ ወላጆቹም ሳውል ብለው ስም አወጡለት፤ ትርጓሜውም ስጦታ ማለት ነው፡፡ ቁመቱ ቀጥ ያለ፤ መልኩ ያማረ፤ ፊቱ ብሩህ፤ ቅላቱ እንደ ሮማን ቅርፍት ደበብ ያለ፤ ዐይኑም የተኳለ የሚመስል አፍንጫው ቀጥ ያለ ሸንጎበታም፤ ጉንጩ እንደ ጽጌረዳ ነበረ፡፡

እርሱም ሕገ ኦሪትን አዋቂ ነበረ፡፡ ለሕጉም ቀናተኛ ሆኖ ምእመናን አሳዳጅ ነበረ፡፡ ወደ ሊቀ ካህናቱም ሔዶ በመንገድ የሚያገኘው ሰው ቢኖር ወንዶችንና ሴቶችን እንደታሠሩ ወደ ኢየሩሳሌም ይመልሳቸው ዘንድ ለደማስቆ ከተማና ለምኩራቦች የፈቃድ ደብዳቤ ለመነ፡፡

ሲሔድም ወደ ደማስቆ ከተማ አቅራቢያ በደረሰ ጊዜ ድንገት ከሰማይ መብረቅ ድንገት ብልጭ አለበት፤ በምድር ላይም ወደቀ፤ ወዲያውም ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ የሚለውን ቃል ሰማ፡፡ ሳውልም አቤቱ አንተ ማነህ አለው፤ አንተ የምታሳድደኝ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ፤ በሾለው ብረት ላይ ብትረግጥ አንተን ይጎዳሃል አለው፡፡

እየተንቀጠቀጠም አደነቀ፤ አቤቱ ምን እንዳደርግ ትሻለህ አለው፡፡ ጌታም ተነሥና ወደ ከተማ ግባ ልታደርግ የሚገባህን ከዚያ ይነግሩሃል አለው፡፡ ከእርሱ ጋር ቆመው የነበሩ ሰዎችም ንግገሩን ይሰሙ ነበር፤ ነገር ግን የሚያዩት አልነበረም፡፡ ሳውልም ከምድር ተነሣ ዓይኖቹም ተገልጠው ሳሉ አያይም ነበር፤ እየመሩም ወደ ደማስቆ አስገቡት፡፡ በዚያም ሳያይ ሳይበላና ሳይጠጣ ሦስት ቀን ሰነበተ፡፡

በዚያም በደማስቆ ከደቀ መዛሙርት ወገን ሐናንያ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፤ ጌታም በራእይ ተገለጠለትና ሐናንያ ብሎ ጠራው፡፡ እርሱም ጌታዬ እነሆኝ አለ፡፡ ተነሥና ቀጥተኛ ወደምትባለው መንገድ ሒድ በይሁዳ ቤትም ጠርሴስ ከሚባል አገር የመጣ ሳውል የሚባል ሰው ፈልግ፤ እርሱ አሁን ይጸልያልና አለው፡፡

ሐናንያ ግን መልሶ እንዲህ አለ፤ አቤቱ ስለዚህ ሰው በኢየሩሳሌም በቅዱሳኖችህ ላይ የሚያደርገውን ክፉ ነገር ሁሉ ከብዙ ሰዎች ሰምቻለሁ፤ ወደዚህም ከካህናቱ አለቃ አስፈቅዶ የመጣ ስምህን የሚጠሩትን ሁሉ ሊያስር ነው፡፡ ጌታችንም ተነሥና ሒድ በአሕዛብና በነገሥታት በእስራኤልም ልጆች ፊት ስሜን ይሸከም ዘንድ ለእኔ የተመረጠ ዕቃ አድርጌዋለሁና እኔም ስለ ስሜ መከራ ይቀበል ዘንድ እንዳለው አሳየዋለሁ፡፡

ያን ጊዜም ሐናንያ ሔደ፤ ወደ ቤትም ገባ፡፡ ወንድሜ ሳውል በመንገድ ስትመጣ የታየህ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታ ዘንድ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ይሞላብህ ዘንድ ወዳነተ ልኮኛል አለው፡፡ ያን ጊዜም የሸረሪት ድር የመሰለ ከዐይኖቹ ላይ ተገፎ ወደቀ፡፡ዐይኖቹም ተገለጡ፡፡ ወዲያውም አየ ተነሥቶም ተጠመቀ፡፡ እህልም በልቶ በረታ፡፡ ከደቀ መዛሙርትም ጋር በደማስቆ ለጥቂት ቀን ሰነበተ፡፡ በዚያው ጊዜ የእግዚአብሔር ልጅ ነው ብሎ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ሰበከ፤ አስተማረም፡፡

የሰሙትም ሁሉ አደነቁ እንዲህም አሉ፤ በኢየሩሳሌም ይህን ስም የሚጠሩትን ያሳድድ የነበረ ይህ አልነበረምን ወደዚህስ የመጣው እያሠረ ወደ ሊቀ ካህናቱ ሊወስዳቸው አይደለምን፡፡ አጽናኝ መንፈስ ቅዱሰም አደረበት ዕውነተኛውንም ሃይማኖት ግልጽ አድርጎ አስተማረ፡፡

ለኦሪት ሕግ የሚቀና እንደነበረ እንዲሁ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሠራት ሕገ ወንጌል ዕጽፍ ድርብ ቅንዓትን የሚቀና ሆነ፡፡ ከዚህም በኋላ በአገሮች ሁሉ እየዞረ ሰበከ፤ በጌታችንም ስም ሰበከ፡፡ ድንቆችንና ተአምራትንም አደረገ፡፡ ቁጥር የሌላቸው አሕዛብንም አሳመናቸው ነገር ግን ብዙ ጊዜ በመገረፍ በመደብደብና በመታሠር ብዙ መከራ ደረሰበት፤ መከራውንም ሁሉ ታግሶ በሁሉ ቦታ ዞሮ አስተማረ፡፡

በሐዋርያት ሥራ መጽሐፍ እንደተጻፈ የእግዚአብሔርን ሥራ ሲሠሩ ሲጾሙና ሲጸልዩ መንፈስ ቅዱስ እኔ እነርሱን ለመረጥሁለት ሥራ ሳውልንና በርናባስን ለዩልኝ አላቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ጾመውና ጸልየው እጃቸውንም በራሳቸው ላይ ጭነው ሾሙአቸው፤ ከመንፈስ ቅዱስም ተሹመው ወደ ሴሌውቅያ ወረዱ፡፡

በደሴቱም ሁሉ ሲዘዋወሩ ጳፉ ወደምትባል አገር ደረሱ፡፡ በዚያም ሐሰተኛ ነቢይ የሆነ ስሙ በርያሱስ የሚባል አንድ ሥራየኛ አይሁዳዊ ሰው አገኙ፤ እርሱም ሰርግዮስ ጳውሎስ ከሚባል ብልህ ሰው ከሆነ አገረ ገዥ ዘንድ የነበረ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ሊሰማ ወዶ በርናባስንና ሳውልን ጠራቸው፡፡ የስሙ ትርጓሜ እንዲህ ነበርና ኤልማስ የሚሉት ያ ሥራየኛ ሰው ይከራከራቸው ነበረ፤ ገዥውንም ማመን ሊከለክለው ወዶ ነበረ፡፡

ጳውሎስ በተባለው ሳውል ላይም መንፈስ ቅዱስ መላበት፡፡ አተኩሮም ተመለከተው፤ ኃጢአትንና ክፋትን ሁሉ የተመላህ የሰይጣን ልጅ የጽድቅ ሁሉ ጠላት ሆይ የቀናውን የእግዚአብሔርን መንገድ እያጣመምህ ተው ብትባል እምቢ አልህ እነሆ አሁን የእግዚአብሔር እጅ በአንተ ላይ ተቃጥታለች፤ ትታወራለህ እስከ ዕድሜ ልክህም ፀሐይን አታይም አለው፡፡ ወዲያውኑም ታወረ ጨለማም ዋጠው የሚመራውንም ፈለገ፤ አገረ ገዢውም የሆነውን አይቶ ደነገጠ በጌታችንም አመነ፡፡

ከዚህ በኋላ ሒደው ወደ ሊቃኦንያ ከዚያም ወደ ልስጥራንና ደርቤን ከተማ ወደ አውራጃውም ሁሉ ገብተው አስተማሩ፡፡ በልስጥራን ከተማም ከእናቱ ማሕፀን ጀምሮ እግሩ ልምሾ የሆነ አንድ ሰው ነበረ ተቀምጦ ይኖር ነበር እንጂ ልምሾ ከሆነ ጀምሮ ቆሞ አልሔደም፡፡ ጳውሎስንም ሲያስተምር ተመልከቶ ሃይማኖት እንዳለው እንደሚድንም ተረዳ፡፡ ድምጹንም ከፍ አድርጎ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሥና ቀጥ ብለህ ቁም እልሃለሁ አለው፤ ወዲያውኑ ተነሥቶ ሔደ፡፡

አሕዛብም ጳውሎስ ያደረገውን አይተው በጌታችን አመኑ፡፡ እርሱም በዚያ ሳለ አይሁድ ከአንጾኪያና ከኢቆንያ መጥተው ልባቸውን እንዲያስጨክኑባቸው አሕዛብንም አባበሉአቸው፡፡ ጳውሎስንም በደንጊያ ደበደቡት፤ ጎትተው ወደ ውጭ አወጡት፡፡በማግስቱም ከበርናባስ ጋራ ደርቤን ከተማ ሔዱ፡፡ በዚያችም ከተማ አስተማሩ ብዙ አሕዛብንም ሃይማኖት አስገቡ ለቤተ ክርስቲያንም ቀሳውስትን ሾሙላቸው፤ ከዚያም ወደ መቄዶንያ አልፈው ሔዱ ጋኔን ሟርት የሚያሥራትን አንዲት ልጅ አገኙ ከምታገኘው ዋጋ ለጌቶቿ ብዙ ትርፍን ታስገባ ነበር፡፡ እነዚህ ሰዎች የልዑል እግዚአብሔር አገልጋዮች ናቸው የሕይወትንም መንገድ ያስተምሯችኋል ብላ እየጮኸች ከጳውሎስ ኋላ ተከተለች፤ ብዙ ቀንም እንዲሁ ታደርግ ነበር፡፡ ጳውሎስንም አሳዘነችው መለስ ብሎም መንፈሰ ርኩስን በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንድትወጣ አዝዤሃለሁ አለው ወዲያውኑም ተዋት፡፡

ከዚህ በኋላም ሐለብ ከሚባል አገር ደረሰ፤ የጢሞቴዎስንም እናት ስሟ በድሮናን ከሞት አስነሣት፡፡ በዚያም ያዙት ለዚያች አገር ጣኦትም ሊሠዉት ወድደው በሚነድ እሳት ውስጥ ጨመሩት፡፡ ስለ እነርሱም እየማለደ እጆቹን በመስቀል ምልክት አምሳል ዘረጋ፡፡ አሕዛብም በአዩት ጊዜ ስለዚህ ድንቅ ሥራ አደነቁ፤ ከእሳት መካከልም እንዲወጣ ማለዱት፤ ምንም ምን ሳይነካው ወጣ ሰገዱለትም ክብር ይግባውና በጌታችንም አመኑ የአገሩ ሹም አርስጦስም አመነ፡፡

ሰባቱ የጣዖት ካህናት ግን ሸሽተው ተሠወሩ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም በጭላት አምሳል የተቀረጸውን ምስል ጠራው ምስሉም በአንባሳ አምሳል መጥቶ በምኩራቡ መካከል በጳውሎስ ፊት ቆመ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም የሚያመልኩህ ካህናቶችህ ወዴት አሉ አለው፤ አንበሳውም ያሉበትን አስክነግርህ ድረስ ጌታዬ ጥቂት ታገሠኝ፤ አለው፡፡ ካህናቱም ወደተሸሸጉበት ሔዶ አንዱን አንገቱን በአፉ ይዞ እየጎተተ አምጥቶ እንደ በድን በአደባባዩ መካከል ጣለው፡፡ ሰባቱንም እንዲሁ እያንዳንዱን እየጎተተ አመጣቸው፡፡

ሕዝቡም ሊገድሏቸው ወደዱ፡፡ ጳውሎስም ዛሬ በዚህች ከተማ ማዳን እንጂ መግደል አይገባም አለ፤ ከዚህም በኋላ ሁሉንም አጠመቃቸው፤ ሃይማኖትንም አስተማራቸው፡፡ ያንንም አንበሳ የሆነ የጭላት ምስል አንበሳ ሆይ አትፍራ ስለ አገለገልከኝ እሰከምሻህ ድረስ ኑሮህ በበረሀ ይሁን አለው ያን ጊዜም ወደ በረሀ ሔደ፡፡

ጳውሎስም ከዚያ ተነስቶ አካ ወደሚባል ከተማ ሔደ፡፡ ስክንትስ ከሚባል ደቀ መዝሙርም ጋር ተገናኘ፤ አይሁድም ዜናውን ሰምተው ከአሕዛብ ጋራ ተሰበሰቡ ይዘውም ጭንቅ የሆነ ስቃይን አሰቃዩት፤ ዳግመኛም ሁለት በሮችን አመጡ ከስክንጥስ ጋራም አሥረው በከተማው ጥጋጥግ በስለታም ድንጋይ ላይ አስጎተቷቸው ደማቸውም እንደ ውኃ ፈሰሰ፤ አጥንታቸውም እሰከሚታይ ድረስ ሥጋቸውም ተቆራረጠ፡፡ ወደ ጌታም ጸለዩ፤ ያን ጊዜም በሮቹ ከሚነዳቸው ጋራ ደንጊያ ሆኑ፡፡

ሕዝቡም በአዩ ጊዜ ለመኮንኑ ነገሩት እርሱም ተቆጣ ወደ እርሱም እንዲያቀርቧቸውና በደንጊያ እንዲወግሯቸው አዘዘ፤ በቅዱስ ጻውሎስም ላይ እጅግ ተቆጥቶ አንተ የሥራይ ሰው እነሆ አሠቃይሃለሁ አለው፡፡ በበሬ ቅርጽ የተሠሩ ሁለት ቀፎዎችንም ያመጡ ዘንድ አዘዘ፡፡ ዝፍት ሙጫና ድኝ አምጥተው በውጭ ቀላለቅለው ሁለቱን የናስ ቀፎዎች በውስጥም በውጭም ቀቧቸው፡፡ ሐዋርያትንም በውስጥ ጨምረው በእሳት ምድጃ ውስጥ አስገቧቸው፤ ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊትም እሳት አነደዱባቸው፡፡

መድኃኒታን ኢየሱስ ክርስቶስም ከመላእክቶቹ ጋራ መጣ እሳቱንም ከዚያ ፈልሶ ወደ ከተማ ውሰጥ ገብቶ የከተማውን ሰዎች ሁሉ እንዲከባቸው አደረገው፤ በተጨነቁም ጊዜ ጮኹ፤ አለቀሱም፡፡ መዳንን ከፈለጋችሁ ፈጥናችሁ በአደባባዩ በአንድነት ተሰብሰቡ የሚል ቃል ከሰማይ ጠራቸው፡፡ ጳውሎስም ወደ በረሀ አሰናብቶት የነበረው አንበሳ መጣ፤ ጳውሎስ በስሙ በሚያስተምርበት ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እመኑ እያለ ጮኸ፡ ከዚህም በኋላ ወደ እሳቱ ምድጃ ተመልሶ ጳውሎስንና ስክንጥስን ከእሳቱ ውስጥ ውጡ አላቸው፤ ያን ጊዜም የራሳቸው ጠጉር እንኳ ሳይቀነብር ወጡ፤ በላያቸውም ላይ የቃጠሎ ሽታ የለም፡፡

ይህንን ድንቅ ሥራ አይተው በጌታችን በናዝሬቱ ኢየሱስ ክርስቶስ እናምናለን እያሉ ጮኹ፤ ከዚህም በኋላ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠመቃቸው ስክንጥስንም ቅስና ሾመላቸው፡፡ከዚህ በኋላም ከሐዋርያ ፊልጶስ ጋራ ወደ ሁለት አገሮች በአንድነት ሔዱ፤ በዚያም በጌታችን ስም ሰበኩ የአገሩ አለቆችም ያዙአቸው እጆቻቸውንና እግሮቻቸውንም አሠሩአቸው በአንገቶቻቸውም የብረት ሰንሰለቶችንም አስገቡ ራሳቸውንም የሚሸፍን የብረት ቆብን ሠሩላቸው ዳግመኛም በእጅና በመሐል እጅ ጣቶችም ምሳሌ ሠርተው በእጆቻቸውና በክንዶቻቸው እያንዳንዱን የብረት እጅ ጨመሩ፡፡ ከብረቶችም ጋር ቸነከሩአቸው፡፡

ሁለተኛም እስከ አንገት የሚደርስ በትከሻ አምሳል ሠሩ፤ በፊትና በኋላም ቸነከሩአቸው፡፡ ደግሞም መላ አካላቸው ምንም እንዳይታይ የሚሽፍን የብረት ሠሌዳ ሠሩ፡፡ ከወገቦቻቸውም ጋራ ቸነከሩት፤ ችንካሮችም ተረከዛቸውን ነድለው ወደ ጭኖቻቸው እስከሚደርሱና እሰከ አቆሰላቸው ድረስ የብረት ጫማ ሠርተው እግሮቻቸውን ቸነከሩ፡፡

ደግሞ በመሸፈኛ አምሳል የብረት ሰናፊል ሠሩ፤ ቀማሚዎችም መጡ አንድ መክሊት የሚመዝን እርሳስንም አመጡ ታላቅ የብረት ጋንንም ሰባት ልጥር የሰሊጥ ቅባትን አመጡ፡፡ ስቡንና አደሮ ማሩን የእሳቱንም ኃይል አብዝቶ የሚነደውን ቅመሙን ከሙጫውና ከድኙ ጋር ቀላቀሉ፤ ከዋርካና ከቁልቋል ከቅንጭብም ደም ሰባት ልጥር አንድ የወይን አረግንና ቅባት ያላቸውን ዕንጨቶች ሁሉ አመጡ፡፡ በጋን ውስጥ ያበሰሉትንና ያሟሙትንም ልዩ ልዩ ቅመማ ቅመም አምጥተው ከሥጋቸው ጋራ እሰከሚጣበቅ በቅዱሳን ሐዋርያት ሥጋ ላይ ባሉት ሠሌዳዎች ውስጥ ጨመሩት፡፡ ከእግራቸው አስከ ራሳቸውም ከፍ ከፍ እስከሚል ድረስ በእሳት ያቃጠሉትን ያንን እርሳስ ጨመሩ፡፡ ርዝመቱ ዐስራ አምስት ክንድ በሆነ ወፍራም የጥድ ምሰሶ ላይም አቆሟቸውና ከበታቻቸው ፍሬ በሌለው በወይን ሐረግና በተልባ እሳቱን አቀጣጥለው አነደዱ፡፡ የእሳቱ ነበልባልም ከሥጋቸው በላይ ከፍ ከፍ አለ ሐዋርያ ግን ወደ እግዚአብሔር ይጸልዩ ነበር፡፡

ከመኳንንቱም በአንዱ ልብ ርኅራኄን አሳደረና እንዲፈቷቸው አዝዞ ፈቷቸው፡፡ በፈቷቸውና ሠሌዳውን ከሥጋቸው ላይ ባስወገዱ ጊዜ ቆዳቸው ተገፈፈና ከብረቱ ሠሌዳዎች ጋራ ወጣ፡፡ ብዙ ደምም ከሥጋቸው ጋር ፈሰሰ፡፡ ሰይጣንም በከተማው ሰዎች ልብ አደረና ሐዋርያትን ወደ እሳት ውስጥ መለሱአቸው፤ ያን ጊዜ ጌታችን ወርዶ የእሳቱን ነበልባል አጠፋው፡፡ ዝናምን የተመላች ብርህት ደመናም መጥታ ቅዱሳን ሐዋርያትን ከበበቻቸው፤ በዚያችም አገር አንድ ጊዜ በደንጊያ በመውገር አንድ ጊዜም በፍላጻ በመንደፍ ብዙ ተሠቃዩ፡፡ ከዚህም በኋላ ሙታንን በአነሡ ጊዜ የከተማው ሰዎች ሁሉ አመኑ፤ አጠመቋቸውም፤ ቤተ ክርስቲያንንም ሠሩላቸው፤ ካህናትንም ሾሙላቸው በቀናች ሃይማኖትም እስቲጸኑ አስተማሩአቸው፡፡ ከዚያም ወጥተው ጌታችን ወዳዘዛቸው ወደ ሌላ አገር ሔዱ፡፡

ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለጳውሎስ ተገለጠለትና የመረጥኩህ ጳውሎስ ሆይ ሰላም ላንተ ይሁን፡፡ መታሰቢያህን የሚያደርገውን፤ በስምህ ቤተ ክርስቲያን የሚሠራውንና፤ በውስጧም የሚጸልየውን ስለትንና መባንም የሚሰጠውን በመታሰቢያህም ቀን ለድሆች የሚመጸውተውን ሁሉ ካንተ ጋራ በመንግሥተ ሰማያት አኖራቸዋለሁ አለው፡ በስምህ የታነጹትንም አብያተ ክርስቲያናት መላእክቶቼን እንዲጠብቋቸው አደርጋቸዋለሁ፤ ብዙ ቃል ኪዳንም ሰጠው፡፡ በመለኮታዊ አፉ አፉን ሳመውና ከእርሱ ዘንድ ወደሰማያት በክብር ዐረገ፡፡

ከዚህም በኋላ እልዋሪቆን ወደምትባል ታላቅ ሀገር እስከሚደርስ በብዙ አገሮች ውስጥ ተመላለሰ፡፡ በዚያም የብርሃን እናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተገልጻለት አረጋጋቸው፤ ረዳቸውም፡፡ በመጋቢት 29 እንደጻፍነው የአገሩን ሰዎች እንዲያጠምቃቸውና እንዲያስተምራቸው አዘዘችው፡፡

ከዚህም በኋላ ወደ ሮሜ ከተማ ገብቶ በውስጧ ሰበከ፤ በስብከቱም ብዙ ሰዎች አምነው የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው፡፡ በመጻሕፍትነት ያታወቁ ዐሥራ አራት መልእክቶችን ጻፈ፤ የመጀመሪያ መልእክቱም ለሮሜ የተጻፈችው ናት፡፡ መልካም ሩጫውንም ከፈጸመ በኋላ ንጉሥ ኔሮን ይዞ ጽኑ ሥቃይን አሠቃየው፡፡ ራሱንም በሰይፍ እንድቆርጡት ለሰያፊ ሰጠው፤ ከሰያፊውም ጋራ አልፎ ሲሔድ ከንጉሥ ኔሮን ዘመዶች ወገን የሆች አንዲት ብላቴና አገኘቸው፤ እርሷም ክብር ይግባውና በጌታችን ያመነች ነበረች፤ ለእርሱም አለቀሰች፡፡ እርሱ ግን መጎናጸፊያሽን ስጪኝ እኔም ዛሬ እመልስልሻለሁ አላት፡፡ እርሷም መጎናጸፊያዋን ሰጠችውና ራስ ወደሚቆርጡበት ቦታ ሔደ፡፡ ለሰያፊውም ራሱን ባዘነበለ ጊዜ በመጎናጸፊያዋ ፊቱን ሸፈነ፤ ሰያፊውም የቅዱስ ጳውሎስን ራስ ቆርጦ በዚያች ብላቴና መጎናጸፊያ እንደተሸፈነ ጣለው፡፡

ሰያፊውም ጳውሎስን እንደገደለው ለንጉሥ ሊነግረው በተመለሰ ጊዜ ያቺ ብላቴና አገኘቸው፤ ያ ጳውሎስ ወዴት አለ አለችው ራስ በሚቆረጥበት ቦታ ወድቋል ራሱም በመጎናጸፊያሽ ተሸፍኗል አላት፡፡ እርሷም እንዲህ ብላ መለሰችለት፤ ዋሽተሃል እነሆ ጴጥሮስና ጳውሎስ በእኔ ዘንድ አልፈው ሔዱ እነርሱም የመንግሥት ልብሶችን ለብሰዋል፤ በራሳቸውም ላይ በዕንቁ የተጌጡ ዐይንን የሚበዘብዙ አክሊላትን አድርገዋል፡፡ መጎናጸፊያዬንም ሰጡኝ፤ አርሷም እነኋት ተመልከታት ብላ ለዚያ ሰያፊ አሳየችው ከእርሱ ጋራ ለነበሩትም አሳየቻቸው፡፡ አይተውም አደነቁ፤ ስለዚህም ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ፡፡የዚህም ሐዋርያ ጳውሎስ ተአምራቶቹ ቁጥር የሌላቸው እጅግ የበዙ ናቸው፡፡

ለእግዚአብሔር ምሥጋና ይሁን እኛንም በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት፤ ከሁሉም ሊቃነ ጳጳሳት፤ እና የቅድስት የሐዋርያት ቤተ ክርስቲያን ልጆች ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን፡፡

  • ምንጭ፡- መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኀ ሐምሌ

 

 

ክረምት

ሰኔ 25 ቀን 2006 ዓ.ም.

መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ በዕለተ ረቡዕ የተፈጠሩት ፀሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብት ቀን ለመቁጠር፣ዘመንን፣ ወራትን፣ በዓላትንና አጽዋማትን ለማወቅ ወሳኝ ፍጥረቶች ናቸው፡፡ ዘፍ.14-19፣ ዘዳ.12፡1፡፡

እንደ ቤተ ክርስቲያናችን አቆጣጠር አንድ ዓመት በፀሐይ አቆጣጠር 365 1/4 ቀናት፡፡ በጨረቃ አቆጣጠር 354 ቀናት፡፡ በከዋክብት አቆጣጠር ጸደይ፣በጋ፣መጸውና ክረምት የተባሉ አራት ወቅቶች አሉ፡፡

ወቅት እንዲፈራረቅ በዘመን ላይ የተሾሙ ዓመቱን በአራት ክፍለ ዘመን የሚገዙት አራት ከዋክብት ሲሆኑ በእያንዳንዱ ወር ላይ የሰለጠኑ ከአራቱ ከዋክብት ሥር እንደ ወታደር የሚያገለግሉ ሦስት ሦስት ወታደሮች በድምሩ 12 ከዋክብት አሉ፡፡ እነዚህ ከዋክብት ወቅቶቹ ሥርዐታቸውን ጠብቀው እንዲሸጋገሩ የሚያደርጉና የእግዚአብሔር ጸጋ ለፍጥረቱ እንዲደርስ የሚያደርጉ ናቸው፡፡

ዓመቱን ለአራት ወቅቶች የሚከፈሉትና የሚመግቡት ከዋክብት የሚከተሉት ናቸው፡-

ምልክኤል፡-

በጸደይ የሰለጠነው ኮከብ ምልክኤል ሲሆን በሥሩ ያሉት ሦስት ከዋክብት/ወታደሮች/ ሚዛን በመስከረም ወጥቶ 30 ዕለት ከ 10 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ሚዛን ነው፡፡ አቅራብ በጥቅምት ወጥቶ 29 ዕለት ከ40 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ጊንጥ ነው ፡፡ ቀውስ በኅዳር ወጥቶ 29 ዕለት ከ28 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ቀስት ነው፡፡ (ኬኪሮስ ማለት ረጅም መስመር ማለት ሲሆን የቀንና የሌሊት ሰዓቶች ክፍል ነው፡፡ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ ተዘርግቶ 60 ክፍሎች አሉት፡፡ ፀሐይ ጨረቃ ከዋክብት ሁል ጊዜ እየሄዱበት በየቀኑ አንድ ጊዜ ያልፍበታል፡፡ 5 ኬክሮስ 1 ሰዓት ነው፡፡)

ናርኤል፡-

በበጋ የሰለጠነው ኮከብ ናርኤል ሲሆን በሥሩ ያሉት ሦስት ከዋክብት ወታደሮች ገዳ/ጀዲ በታኅሣሥ ወጥቶ 29 ዕለት ከ28 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ፍየል፡፡ ደላዊ በጥር ወጥቶ 29 ዕለት ከ41 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ውኃ መቅጃ ባልዲ፡፡ ሑት በየካቲት ወጥቶ 31 ዕለት ከ10 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ዓሣ ነው፡፡

ምልኤል ፡-

በመጸው የሰለጠነው ኮከብ ምልኤል ሲሆን በሥሩ ያሉት ሦስት ከዋክብት ሐመል በመጋቢት ወጥቶ 30 ዕለት ከ43 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ በሬነው፡፡ ገውዝ/ጀውዝ በግንቦት ወጥቶ 31 ዕለት ከ30 ኬክሮስ የሚታይ መልኩእንደ ባልና ሚስት ጥንድ ነው፡፡

ሕልመልመሌክ፡-

በክረምት የሰለጠነው ኮከብ ሕልመልመሌክ ሲሆን በሥሩ ያሉት ከዋክብት/ወታደሮች ሰርጣን/ ድርጣን በሰኔ ወጥቶ 31 ዕለት ከ26 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ ጎርምጥ ነው፡፡ አሰድ በሐምሌ ወጥቶ 31 ዕለት ከ10 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ አንበሳ ሰንበላ በነሐሴ ወጥቶ 30 ዕለት ከ42 ኬክሮስ የሚታይ መልኩ እንደ እሸት ዛላ ነው ፡፡

በዚህ መነሻነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የወቅት አቆጣጠር እንደሚከተለው ይገለጻል፡፡

  • የመጸው ወቅት ከመስከረም 26 ቀን እስከ ታኅሣሥ 25

  • የበጋ ወቅት ከታኅሣሥ 26 ቀን አስከ መጋቢት 25

  • የጸደይ ወቅት ከመጋቢት 26 ቀን እስከ ሰኔ 25

  • የክረምት ወቅት ከሰኔ 26 ቀን እስከ መስከረም 25 ቀን ሲሆኑ እነዚህን ወቅቶች በማወቅ ዘመኑን በመዋጀት ሥራው ድንቅ የሆነ አምላክ ይመሰገንበታል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ሥርዐት ሠርታ በጸሎቱ በማኅሌቱ በቅዳሴው ወዘተ. ትጠቀምበታለች፡፡

ቤተክርስቲያን ወቅቶች ሲፈራረቁ አዲሱን ወቅት ለመቀበል ምኅላ (ጸሎት) ታደርጋለች ፡፡ ለምሳሌ ምኅላ በአተ ክረምት (የክረምት መግቢያ ምኅላ) እንደየ ዕለቶቹ እየታየ ከሰኔ 12 እስከ ሰኔ 23 ቀን ምኅላ ይያዛል፡፡ ይኸውም መጪው ክረምት እግዚአብሔር የሚመሰገንበትና የሚዘንበው ዝናብ ጥሩ ምርት የሚያስገኝ እንዲሆን ነው፡፡

ቅዱስ ጳውሎስም በመልእክቱ እንደጻፈው “ምድርም ብዙ ጊዜ በርስዋ የወረደውን ዝናም ከጠጣች መልካም ፍሬ ለደከሙበት ላረስዋትም ብታበቅል ከእግዚአብሔር ዘንድ በረከት ትቀበላለች” ብሏል ዕብ.6፡7 ፡፡ ቅዱስ ዳዊትም ወአንተ ገበርከ አድባረ ወምድረ ኵሎ፡፡ ክረምተ ወሐጋየ ዘአንተ ፈጠርከ ወተዘከር ዘንተ ተግባረከ፡፡ አንተ የምድርን ዳርቻ ሁሉ ሠራህ በጋንም ክረምትንም አንተ አደረግህ።ይህን ፍጥረትህን አስብ። (መዘ 74፡፡17)

“ክረምት” በደስታ ተክለ ወልድ መጽሐፈ ሰዋሰው ወግስ በሚለው መጽሐፋቸው ሲፈታው ክረምት ከረመ ዝናም የዝናብ ወቅት በፀደይና በመጸው መካከል ያለ ክፍለ ዓመት ከሰኔ 25 እስከ መስከረም 25 ድረስ ያለው ወቅት ሲለው ቅዱስ ያሬድም በድጓው ወያስተዴሉ ክረምተ ለምድር ዘያበቁል ሣዕረ ውስተ አድባር ይለዋል፡፡

ጥዑመ ልሳን ካሳ ደግሞ “ክረምት” የሚለው ቃል ከርመ፣ ከረመ ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን ትርጓሜውም ወርሃ ዝናም፣ ወርኃ ነጎድጓድ፣ ዘመነ ባሕር፣ ዘመነ ነጎድጓድ፣ ዘመነ አፍላግ፣ ዘመነ ጠል፣ ዘመነ ደመና፣ ዘመነ መብረቅ… ይሉታል፡፡ ዘመነ ክረምት/ የዝናብ ወቅት በዘጠኝ ይከፈላል አራቱ በሚጠናቀቀው ዓመት እስከ ጳጉሜ መጨረሻ ሲሆን አምስቱ ደግሞ በሚቀጥለው ዓመት ውስጥ በመስከረም ናቸው፡፡ በያዝነው ዓመት ውስጥ ያለው ክፍል ፡-

  1. ዘር፣ ደመና እስከ ሐምሌ 18 ቀን

  2. መብረቅ፣ ባሕር፣ ወንዞች እስከ ነሐሴ 9 ቀን

  3. እጓለ ቁአት ፣ደሰያት ፣የሁሉም ዓይኖች እስከ ነሐሴ 27

  4. ንጋት፣ቀን፣ፍጥረት በሚል እስከ ጳጉሜን 5 ወይም 6 ናቸው፡፡ እነዚህ አራት ጊዜዎች እንደ አንድ ይቆጠራሉ፡፡

የዝናብ/የክረምት ወቅት ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔርን በልዩ ሁኔታ የምታከብርበት ወቅት ነው፡፡

ቤተክርስቲያን እግዚአብሔር የሰማይና የምድር ፈጣሪ መጋቢ መሆኑን በዝናብ ምልክትነት /አስረጅነት ታስተምራለች፡፡ በግብርና የሚተዳደሩ የሀገራችን ሰዎች በክረምት የዘሩት ዘር ፍሬ የሚያፈራው በክረምት እግዚአብሔር በሚሰጠው ዝናብ ስለሆነ ቸርነቱ መጋቢነቱ በዚህ ይመሰላል፡፡

ድሃ ስንሆን ተስፋችንን በእግዚአብሔር ላይ እናደርጋለን እርሱ ዝናቡን ይሰጠናል፡፡ ዘር እግዚአብሔርን ተስፋ በማድረግ በአፈር ውስጥ ይቀበራል ዝናብ ሲያገኝ አድጐ ለፍሬ ይበቃል፡፡ ስለዚህ ከሰኔ 25 – ሐምሌ 18 ያለው ወቅት ዘርዕ ደመና ተብሎ መጻሕፍት ይነበባሉ፡፡ መዝሙሮች ይዘመራሉ፡፡

የሚቀርበው ምስጋና የዝናብን ወቅት እግዚአብሔር ሰጠን ምሕረትን አደረገልን ሰንበትን ለሰዎች ሠራልን ስለዚህ እርሱን ከፍ ከፍ እናድርገው እናመስግነው በማለት ነው፡፡ እንዲሁም ሰማዩን በደመናት ይሸፍናል ለምድርም ዝናብን ያዘጋጃል ሣርን በተራሮች ላይ ያበቅላል ለምለሙንም ለሰው ልጆች ጥቅም። በማለት ቤተክርስቲያን በቅዱስ ዳዊት ምስጋና ታመሰግነዋለች፡፡ መዝ 147፡8 ፡፡

በሐምሌ 2፣5፣20፣ 15 16 አሠርገዎሙ ለሐዋርያት እየተባለ ሐዋርያት በመዝሙር ይታሰባሉ፡፡ 2ጴጥ.1፡12-18 ሐዋ.23፡10-35 ከሐምሌ 19-ነሐሴ 9 መብረቅ ነጎድጓድ ባሕር አፍላግ ጠል እየተባለ ይዘመራል መጻሕፍት ይነበባሉ ፡፡ 1ጴጥ.2፡1-12፣ ሐዋ.20፡1-2፡፡

በዘመነ ክረምት ውኃ ይሰለጥናል፣ ውኃ አፈርን ያጥባል፣ እሳትን ያጠፋል፡፡ ሆኖም ግን በብሩህነቱ ከእሳት፤ በቀዝቃዛነቱ ከነፋስ፤ በእርጥብነቱ ከመሬት ጋር ተስማምቶ ከሦስቱ ባሕርያት ጋር ይኖራል፡፡ ይህ ዘመን ስለ ሥነ ፍጥረት ዘርዘር ባለ መልኩ የሚነገርበት ዘመን ስለሆነ ፍጡርን ከፈጣሪ መናን ከተመጋቢ ለይቶ የሚያሳይና የሚያሳውቅ ዘመን ነው፡፡

ወርኃ ክረምት የክርስትና ምሳሌ ነው፤ ገበሬ በወርሃ ክረምት ብርዱንና ዝናሙን ሳይሰቀቅ ለሥራ ይሰማራል፤ በበጋው የእጁን ፍሬ ያገኝ ዘንድ የክረምቱን መከራ ይታገሳል፡፡ ክርስቲያንም በዚህ ምድር ላይ የሚደርስበትን መከራ ሁሉ ይታገሳል፤ ክርስቲያንም በዚህ ምድር የሚደርስበትን መከራ ሁሉ በጸጋ የሚቀበለው በዚያኛው ዓለም ስለሚያገኘው ተድላና ደስታ ነው፡፡

ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ፡- “እለ ይዘርኡ በአንብዕ ወበኃሤት የአርሩ፡፡ ሶበሰ የሐውሩ ወፈሩ እንዘ ይበክዩ፡፡ ወፆሩ ዘርኦሙ፡፡ ወሶበ የአትዉ መጽኡ እንዘ ይትፌሥሑ፡፡ በሔዱ ጊዜ ዘራቸውን ተሸክመው እያለቀሱ ተሰማሩ፤ በተመለሱ ጊዜ ግን ነዶአቸውን ተሸክመው ደስ እያላቸው ይመጣሉ፡፡” በማለት የመንፈሳዊ ጉዞ ምሥጠርን ከግብርና ሙያ አንጻር አመልክቶአል፡፡(መዝ.125)

“ምድርን ጎበኘሃት አጠጣሃትም ብልፅግናዋንም እጅግ አበዛህ የእግዚአብሔር ወንዝ ውኃን የተሞላ ነው ከምድር ዳር ደመናትን ያወጣል፣ በዝናም ጊዜ መብረቅን አደረገ፤ ነፋሳቱንም ከመዛግብቱ ያወጣል ” (መዝ.64፥9) በማለት እግዚአብሔር በነጎድጓድና በመብረቅ በባሕርና በሐይቅ ሁሉ ላይ ሥልጣን ያለው አምላክ መሆኑንና የሚታዩና የማይታዩ ፍጥረታት ሁሉ የኃይሉ መገለጫዎች እንደሆኑ የሚያስተምሩ መዝሙራት ይዘመራሉ፡፡

እግዚአብሔር ክረምትን ሲያመጣና ዝናምን ሲያዘንም ብዙ ነገሮችን ልናስተውል ይገባናል፡፡ ፈጣሪያችን ፈጣሪ ዓለማት ብቻ ሳይሆን መጋቢ ዓለማት መሆኑን መረዳት ያሻል፡፡ መግቦቱም ከፍጥረቱ እንዳልተለየ ይህ አማናዊ መግቦቱም ፍጥረቱን እንደሚያስተምር እንረዳለን፡፡

በምድር ዘመን ሁሉ መዝራትና ማጨድ፤ ብርድና ሙቀት፤ በጋና ክረምት፤ ቀንና ሌሊት አይቋረጡም፡፡” (ዘፍ.8፥22) በማለት አምላካችን እግዚአብሔር ለኖኅ በገባለት ቃል ኪዳን መሠረት በጋና ክረምቱ ብርድና ሙቀቱ ቀንና ሌሊቱ በተወሰነላቸው ጊዜ እየተፈራረቁ ለሰው ልጆች ጥቅም እንዲሰጡ አድርጓቸዋል፡፡

በዚህ መሠረት ኢትዮጵያዊያን በአንድ ዓመት ውስጥ እየተፈራረቁ በሚመጡ አራት ወቅቶች ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ከቅዱሳት መጻሕፍት ምሥጢርና ምሳሌ ጋር በማስማማት ለየወቅቱና ለዕለታቱ ምንባባትን በማዘጋጀት እግዚአብሔርን ታመሰግናለች፡፡ ስለዚህ በክረምት ወቅት እግዚአብሔርን እያመሰገንን እንድናሳልፍ እግዚአብሔር ይርዳን፡፡

ይቆየን

  • ምንጭ :-ባሕረ ሐሳብ የዘመን ቆጠራ ቅርሳችን