ማቴዎስ ወንጌል

 ሐምሌ 9 ቀን 2006 ዓ.ም.

ምዕራፍ አምስት

የተራራው ስብከት /አንቀጸ ብፁዓን/

ይህ ምዕራፍ ልዑለ ባሕርይ አምላክ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ተራራ ወጥቶ ከፍ ካለ ቦታ ተቀምጦ ያስተማረው ትምህርት በመሆኑ የተራራው ስብከት በመባል ይታወቃል፡፡ ብፁዓን እያለ በማስተማሩም አንቀጸ ብፁዓን ይባላል፡፡ ጌታችን ከፍ ካለ ቦታ ተቀምጦ ያስተማረበት ምክንያት፣ መምህር ከፍ ካለ ቦታ ተማሪዎች ደግሞ ዝቅ ካለ ቦታ ተቀምጠው የሚማሩት ትምህርት ስለሚገባ ነው፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ትምህርቱ አንቀጸ ብፁዓንን እንደሚከተለው አስተምሯል፡፡

  1. “በመንፈስ ድሆች የሆኑ ብፁዓን ናቸው፣ መንግሥተ ሰማያት የእነርሱ ናትና፡፡” ሀብትና ዕውቀት፣ ሥልጣንና ጉልበት እያላቸው የማይታበዩና የማይኮሩ፣ ሁሉ የእግዚአብሔር ነው ብለው ለእግዚአብሔር አሳልፈው የሚሰጡ ሰዎች ብፁዓን ይባላሉ፡፡ በመንፈስ ድሆች የሆኑ የተባለውም ለዚህ ነው፡፡ ጌዴዎን ኀያል ሲሆን እግዚአብሔርም እስራኤልን እንዲያድን በመረጠው ጊዜ በመንፈስ ድሃ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ “ጌታ ሆይ እስራኤልን በምን አድናለሁ? ወገኔ ከምናሤ ነገድ ከሁሉ ይልቅ የተጠቃ ነው፡፡ እኔ በአባቴ ቤት የሁሉ ታናሽ ነኝ፡፡” ሲል ነው ለተገለጠለት የእግዚአብሔር መልአክ የመለሰው፡፡ መሳ.6፡12-15፡፡ በእግዚአብሔር ኃይል በሦስት መቶ ሰው ብቻ ምድያማውያንን ድል ካደረገ በኋላ የእስራኤል ልጆች ተሰብስበው አንተ ልጅህም የልጅህም ደግሞ ግዙን ባሉት ጊዜ በመንፈስ ድሃ ሆኖ የተገኘው የጌድዮን መልስ “እኔ አልገዛችሁም፣ ልጄም አይገዛችሁም እግዚአብሔር ይገዛችኋል፡፡” የሚል ነበር፡፡ እንዲህም በማድረጉ እስከ እድሜው ፍጻሜ ድረስ ለአርባ ዘመናት ሰላምና በረከት ዘመንን አሳለፈ፡፡ መሳ.8፡22-28፡፡ አብርሃም በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ ያገኘ የእግዚአብሔር ወዳጅ ሲሆን በመንፈስ ድሃ የሆነ ሰው በመሆኑ እኔ አፈርና አመድ ነኝ ብሏል፡፡ ዘፍ.18፡3፣ ዘፍ.18፡25፣ ያዕ.2፡23፡፡ ልበ አምላክ ዳዊት ሰባት ሀብታት ፍጹም ጸጋ የተሰጠው የእግዚአብሔር የልብ ሰው ሲሆን በሰውም ሆነ በእግዚአብሔር ፊት ራሱን ድሃ ያደረገ ሰው ነበር፡፡ ንጉሡ ሳኦል ልጁን ሊድርለት ባለ ጊዜ “ለንጉሥ አማች እሆን ዘንድ እኔ ማነኝ? ሰውነቴስ ምንድነው?” ሲል ለንጉሡ መልሶለታል፡፡1ኛ.ሳሙ.18፡18፡፡ በእግዚአብሔር ፊት ሲዘምርም “እኔ ግን ትል ነኝ ሰውም አይደለሁም፤ ማላገጫ በሕዝብም ዘንድ የተናቅሁ ነኝ” ብሏል፡፡ መዝ.21፡6፡፡

  2. “የሚያዝኑ ብፁዓን ናቸው፡፡ መጽናናትን ያገኛሉና፡፡” ኃጢአታቸውን እያሰቡ እንደ አዳም፣ እንደ ዳዊትና እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ የባልንጀራቸውን ኃጢአት እያሰቡ ለንጉሥ ሳኦል እንዳለቀ ሰው እንደ ሳሙኤል /1ኛ ሳሙ.16፡1/ ሰማዕታትን አያሰቡ ለቅዱስ እስጢፋኖስ እንዳለቀሱት ደጋግ ሰዎች፣ መከራ መስቀልን እያሰበ ሰባ ዘመን እንዳለቀሰው እንደ ፍቁረ እግዚእ ዮሐንስ የሚያዝኑ ሰዎች ብፁዓን ይባላሉ፡፡

  3. የዋሆች ብፁዓን ናቸው ምድርን ይወርሳሉና፡፡” ቂም በቀል የማያውቁ፣ አንድም ሰውነታችንን መክረን አስተምረን ማኖር እንደምን ይቻለናል? ብለው በምክረ ካህን በፈቃደ ካህን የሚኖሩ፣ በሞኝነት ሳይሆን አውቀው ስለ እግዚአብሔር ብለው የሚተው ኃዳግያነ በቀል የሆኑ ሰዎች ብፁዓን ናቸው፡፡ ዳዊት እግዚአብሔር በእጁ የጣለለትን ጠላቱን ሳኦልን መግደል ሲችል እራርቶ የተወው በሞኝነት ሳይሆን በየዋህነት ነው፡፡ 1ኛ.ሳሙ.24፡1-22፡፡ ጸሎቱም “አቤቱ ዳዊትን ገርነቱንም ሁሉ አስብ፤” የሚል ነበር መዝ.131፡1፡፡ የዋሃን ይወርሷታል የተባለችው ምድር መንግሥተ ሰማያት ናት፡፡ ምድር መባሏም ምድር አልፋ እርሷ የምትተካ፣ በምድር በሚሰራ የጽድቅ ሥራ የምትወረስ፣ ምድራውያን ጻድቃንም የሚወርሷት ስለሆነች ነው፡፡ “አዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርንም አየሁ፣ ፊተኛው ሰማይና ፊተኛየቱ ምድር አልፈዋልና” ራእ.21፡1፣ “ምድርና ሰማይም ከፊቱ ሸሹ ስፍራም አልተገኘላቸውም” ራእ.20፡11፣ “እነሆ አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር እፈጥራለሁና፡፡ የቀደሙትም አይታሰቡም፡፡” ኢሳ.65፡17፣ “ስለዚያ ቀን ሰማያት ተቃጥለው ይቀልጣሉ የሰማይም ፍጥረት በትልቅ ትኩሳት ይፈታል፡፡ ነገር ግን ጽድቅ የሚኖርባትን አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር እንደተስፋ ቃሉ እንጠብቃለን፡፡”

  4. “ስለጽድቅ የሚራቡና የሚጠሙ ብፁዓን ናቸው ይጠግባሉና፡፡” ስለጽድቅ ብለው ረኃቡንና ጥሙን ታግሰው፣ የእግዚአብሔር መንግሥት በመብል በመጠጥ አትወረስም፣ አንድም ቢፈጽማት የእግዚአብሔርን መንግሥት የምታሰጥ አትወረስም፣ አንድም ቢፈጽሟት የእግዚአብሔርን መንግሥት የምታሰጥ ወንጌል በመንፈስ ቅዱስ የሆነ እምነትን ተስፋንና ፍቅርን እንጂ መብል መጠጥን አትሰብክም አንድም ልብላ ልጠጣ በምትል ሰውነት ወንጌል አትዋሐድም /ሮሜ.14፡19/ መብል ግን ወደ እግዚአብሔር አያቀርበንም ባንበላ ምንም አይጐድልብንም ብንበላም ምንም አናተርፍም /1ኛ.ቆሮ.8፡8/፡፡ መብል ለሆድ ነው፣ ሆድም ለመብል ነው፤ እግዚአብሔር ግን ይህንም ያንም ያጠፋቸዋል፡፡ ብለው የሚጾሙ ሰዎች ብፁዓን ይባላሉ፡፡ “ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ” ሲልም እውነት በሕይወታቸው ነግሣባቸው የሚኖሩትን ያመለክታል፡፡ ጾመ ሙሴ ዘዳ.9፡9፣ ጾመ አስቴር 4፡16፣ 9፡31 ጾመ ዳንኤል፣ ዳን.10፡2 ጾመ ዳዊት፣ 2ኛ ሳሙ.12፡22 መዝ.108፡24፣ ጾመ ሐዋርያት የሐዋ.13፡2 ወዘተ ተመልከት፡፡

  5. “የሚምሩ ብፁዓን ናቸው፡ ይማራሉና” የሚምሩ ሲል ምሕረት ሥጋዊ፣ ምሕረት መንፈሳዊና ምሕረት ነፍሳዊ የሚያደርጉትን ማለቱ ነው፡፡ ምሕረት ሥጋዊ ቀድዶ ማልበስ፣ ቆርሶ ማጉረስ፣ ቢበድሉ ማሩኝታ እና ቢበድሉ ይቅርታ ነው፡፡ ምሕረት መንፈሳዊ ክፉው ምግባር በጐ ምግባር መስሎት ይዞት የሚኖረውን ሰው መክሮ አስተምሮ ከክፋት ወደ በጐነት መመለስ ነው፡፡ ምሕረት ነፍሳዊ ደግሞ ክፉ ሃይማኖት በጐ ሃይማኖት መስሎት የሚኖረውን ሰው መክሮ አስተምሮ ወደ ቀናው ሃይማኖት መመለስ ነው፡፡

  6. “ልበ ንጹሖች ብፁዓን ናቸው፡፡ እግዚአብሔርን ያዩታልና፡፡” በንስሐ ከኃጢአት እንዲሁም ከቂምና ከበቀል ንጹሓን የሆኑ ከንጽሐ ልቡና የደረሱ ሰዎች ብፁዓን ይባላሉ፡፡ “ሁል ጊዜ እግዚአብሔርን በፊቴ አየዋለሁ፤ በቀኜ ነውና አልታወክም፡፡ ስለዚህ ልቤን ደስ አለው ምላሴም ሐሴት አደረገች፡፡ ሥጋዬ ደግሞ በተስፋ ታድራለች፡፡” መዝ.15፡8፡፡ እነቅዱስ እስጢፋኖስ ለነጽሮተ ሥሉስ ቅዱስ የደረሱት ልበ ንጹሐን በመሆናቸው ነው የሐዋ.7፡56፡፡

  7. “የሚያስተራርቁ ብፁዓን ናቸው የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉና፡፡” ሰውን ከሰው፣ ሰውን ከእግዚአብሔር የሚያስታርቁ ሰዎች ብፁዓን ይባላሉ፡፡ መልከጼዴቅ የተጣሉትን ሲያስታርቅ ይውል ነበር፡፡

  8. “ስለ ጽድቅ የሚሰደዱ ብፁዓን ናቸው መንግሥተ ሰማያት የእነርሱ ናትና፡፡” ለመማር፣ ለማስተማር፣ ለምናኔ እንዲሁም በሃይማኖት ምክንያት ሀገራቸውን ጥለው የሚሰደዱ ሰዎች ብፁዓን ይባላሉ፡፡ “ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ፣ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፡፡ ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፣ በዋሻና በምድር ጉድጓድ ተቅበዘበዙ፡፡” ዕብ.11፡37፡፡ ብሎ ቅዱስ ጳውሎስ የተናገራቸው ስለ ጽድቅ ብለው የተሰደዱትን ነው፡፡ አብርሃም ከከለዳውያን ዑር ከሀገሩ ወጥቶ በባዕድ ሀገር ሲንከራተት የኖረው ተጠብቆ የሚቆየው ተስፋ ጸንቶ ነበር፡፡ የተስፋውም ባለቤት እግዚአብሔር የተስፋውን ዋጋ እንዲያገኝ አደረገው፡፡ ያዕ.2፡23፣ ዘፍ.15፡6፣ ኢሳ.41፡8፡፡

  9. “ሲነቅፏችሁና ሲያሳድዷችሁ በእኔ ምክንያት ክፉውን ሁሉ በውሸት ሲናገሩባችሁ ብፁዓን ናችሁ ዋጋችሁ በሰማያት ታላቅ ነውና ደስ ይበላችሁ፣ ሐሴትም አድርጉ፤ ከእናንተ በፊት የነበሩትን ነቢያትን እንዲህ አሳደዋቸዋልና፡፡” በመነቀፍ፣ በመሰደድ፣ በአሉባልታ የሚፈተኑትን ፈተና በትዕግስት ማሸነፍ እና ስለ እውነት መከራን መቀበል የማያልፍና የማይለወጥ ፈጹም ሀብትን ከእግዚአብሔር ዘንድ ያሰጣል፡፡ ለዚህም ነው ጌታችን ዋጋችሁ በሰማያት ታላቅ ነውና ደስ ይበላችሁ፡፡” ሲል ያስተማረው፡፡

ክርስቲያን የምድር ጨው ሆኖ በምግባሩ አልጫ ሕይወት ያላቸውን ሰዎች ሕይወት ማጣፈጥ እንደሚገባውም ያስተማረው በዚሁ ክፍል ነው፡፡ ነገር ግን ጨውነቱን ትቶ አልጫ ሆኖ ቢገኝ እንኳን ሌላውን ሊያጣፍጥ ለራሱም ወደውጭ ተወርውሮ እንደሚረገጥ ከመንግሥተ ሰማያት በአፍአ እንደሚቀር ለምንም እንደማይጠቅም አስገንዝቧል፡፡

 

በመቀጠልም እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ፡፡ በተራራ ላይ ያለች ከተማ እንዳትሰወር ተራራው ይገልጣታል፡፡ መብራትን ከእንቅብ በታች ሣይሆን በቤቱ ላሉ ሁሉ እንዲያበራ በመቅረዝ ያኖሩታል፡፡ መቅርዙም ከፍታ ፋናውን ይገልጸዋል ሲል ተናግሯል፡፡

 

ፍሬ ነገሩም ያለው በተራራ ላይ ያለች ከተማ እና በመቅረዝ ላይ ያለ መብራት አይሰወሩም፤ የተራራውና የመቅረዙ ከፍታ ይገልጣቸዋል የሚለው ላይ ነው፡፡ ምሥጢሩም፡-

  • እናንተ ሥራውን አብዝታችሁ ሥሩ ግድ በተአምራት ይገልጻችኋል፣

  • ከሥጋ ጋር የተዋሐደች ነፍስ ሥራ ሠርታ ልትገለጽ ነው እንጂ ተሰውራ ልትቀር አይደለም፣

  • ከሥጋ ጋር የተዋሐደ መለኮት አስተምሮ ተአምራት አድርጐ አምላክነቱን ሊገልጽ ነው እንጂ ተሰውሮ ሊቀር አይደለም፡፡

  • የተሰቀለ ጌታ ሞቶ ተነሥቶ አምላክነቱን ሊገልጽ ነው እንጂ ሞቶ ሊቀር አይደለም፡፡

  • ወንጌል በአደባባይ ተገልጻ ልትነገር ነው እንጂ ተሰውራ በልባችሁ ልትቀር አይደለም፡፡ ማለት ነው፡፡ “መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ፡፡” በማለትም እግዚአብሔር የሚከበርበትንና የሚመሰገንበትን ሥራ እንዲሠሩ ተናግሯል፡፡

 “ሕግንና ነቢያትን ለመሻር ነው የመጣው” የሚለውን የአይሁድ አሉባልታ ለማጥፋት ሕገ ኦሪትንና ትንቢተ ነቢያትን ለመሻር ሳይሆን ለመፈጸም የመጣ መሆኑን ያስረዳውም በዚሁ ክፍል ነው፡፡ ሰማይና ምድር እስኪያልፍ ድረስ ከሕግ አንዲት የውጣ አንዲት ነጥብ እንደማታልፍ አረጋግጧል፡፡ አትግደልን በአትቆጣ /ማቴ.5፡22/፣ አታመንዝርን “ወደሴት ያየ ሁሉ የተመኛትም ያን ጊዜ በልቡ አመንዝሯል” /ማቴ.5፡28/ በሚለው ላጸናቸው መጥቻለሁ ማለቱ ነው፡፡ ከዚህ የወጣ ግን ከመንግሥተ ሰማያት በአፍአ እንደሚቀር አስገንዝቧል፡፡ ይህም ሕገ ኦሪትን ሽሯል ለሚሉ ለዘመናችንም ተረፈ አይሁድ ታላቅ መልስ ነው፡፡ ስለመሰናክል ሲያስተምርም ዓይንህ ብታሰናክልህ አውልቀህ ጣላት፡፡ እጅና እግርህም ቢያሰናክሉህ ቆርጠህ ጣላቸው ብሏል፡፡ 

 

ዓይን የተባለች ሚስት ናት እጅ የተባለ ልጆች፣ እግር የተባሉ ቤተሰቦች ናቸው፡፡ ምሥጢሩም ሚስትህ ያልሆነ ሥራ ላሰራህ ብትለህ ፈቃዷን አፍርስባት፡፡ ዛሬ በዚህ ዓለም የሚስትህን ፈቃድ ፈጽመህ ኖረህ ኋላ ገሃነም ከምትገባ በዚህ ዓለም የሚስትህን ፈቃድ አፍርሰህ ኖረህ ኋላ መንግሥተ ሰማያት ብትገባ ይሻልሃልና፡፡ ወድቀው ይነሱ በእጅ ዘግይተው ይከብሩ በልጅ እንዲሉ ልጆችህ ያልሆነ ሥራ እናሰራህ ቢሉ ፈቃዳቸውን አፍርስባቸው፡፡ በዚህ ዓለም የልጆችህን ፈቃድ ፈጽመህ ኖረህ ኋላ ገሃነም ከምትወርድ በዚህ ዓለም የልጆችህን ፈቃድ አፍርሰህ ኖረህ ኋላ መንግሥተ ሰማያት ብትገባ ይሻልሃልና፡፡ እግር የተባሉ ቤተሰቦችህ ምክንያተ ስሕተት ሆነው ያልሆነ ሥራ እናሠራህ ቢሉህ ፈቃዳቸውን አፍርስባቸው፤ በዚህ ዓለም የእነሱን ፈቃድ ፈጽመህ ኖረህ ኋላ ገሃነም ከምትገባ ፈቃዳቸውን አፍርሰህ ኖረህ ኋላ መንግሥተ ሰማያት ብትገባ ይሻልሃልና አንድም እንደ ዓይንህ፣ እንደ እጅህ እና እንደ እግርህ ማለትም እንደራስህ የምትወደው ባልንጀራህ ያልሆነ ሥራ አሠራሃለሁ ቢልህ ፈቃዱን አፍርስበት ማለት ነው፡፡

 

በመጨረሻም ዓይን ያጠፋ ዓይኑ ይጥፋ፤ ጥርስ የሰበረም ጥርስ ይሰበር የሚለው፣ ጠላትህ ቢራብ አብላው ቢጠማም አጠጣው” በሚል ሕገ ትሩፋት ወንጀል መተካት እንደሚገባውና በቀልም የክርስቲያኖች ገንዘብ አለመሆኑን አስተምሯል፡፡

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 4ኛ ዓመት ቁጥር 2 ኅዳር 1989 ዓ.ም.

 

የማቴዎስ ወንጌል

 ሐምሌ 3 ቀን 2006 ዓ.ም.

ምዕራፍ አራት

በዚህ ምዕራፍ መጀመሪያ ያለው ንባብ የሚተርክልን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ ሳይውል ሳያድር በኢያሪኮ አካባቢ ወደሚገኘው /ሣራንደርዮን/ የአርባ ቀን ተራራ ተብሎ ወደሚታወቀው ሥፍራ ወጣ፡፡ በዚያም ዐርባ መዓልትና ዐርባ ሌሊት ጾመ፣ ከዚህ በኋላ ተራበ፤ ጸላኤ ሠናይት ዲያብሎስ ሦስት ፈተናዎችን አቀረበለት፡፡

የመጀመሪያው ፈተና መራቡን አይቶ ድንጋይ በማቅረብ እነዚህን ባርከህ ወደ ዳቦነት ለውጥ አለው፡፡ ጌታችንም የሰይጣን ታዛዥ በመሆን የሚገኘውን ሲሳይ በመንቀፍ “ሰው በእግዚአብሔር ቃል እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም” አለው፡፡ በሦስት ሲፈትነው በትዕግሥት አሸነፈው፡፡

ዳግመኛው በትዕቢት ይፈትነው ዘንድ አሰበ፡፡ ጌታም ሐሳቡን ዐውቆ ወደ መቅደስ ጫፍ ሄደለት፡፡ ፈታኙም ከቤተ መቅደስ ጫፍ ዘሎ እንዲወርድ የመጽሐፍ ቅዱስን ጥቅስ ጠቅሶ ጠየቀው፡፡ ጌታም “ጌታ አምላክህን አትፈታተነው ተብሎ ተጽፎብሃል” ብሎ ጠቅሶ መዞ የመጣውን ሰይጣን ጥቅስ ጠቅሶ አፉን አስያዘው መዝ.90፡11፤ ዘዳ.6፡16፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለሚጠይቋችሁ ሁሉ መልስ ለመስጠት የተዘጋጃችሁ ሁኑ ማለቱ ይህንን ይዞ ነው፡፡ 1ኛ ጴጥ.3፡15፡፡

ፈታኝ ዲያብሎስም የቀደሙት ሁለቱ ፈተናዎቹ ጌታን እንዳልጣሉት ባየ ጊዜ ሦስተኛ ፈተናውን አቀረበ፡፡ የዓለምን ግዛት ከነክብሩ አሳየውና “ወድቀህ ብትሰግድልኝ ይህን ሁሉ እሰጥሃለሁ” አለው፡፡ ጌታም “ሂድ አንተ ሰይጣን ለጌታህ ለአምላክህ ስገድ እርሱንም ብቻ አምለክ ተብሏል” ብሎ በመመለስ በፍቅረ ንዋይ ያቀረበለትን ፈተና ገንዘብን በመጥላት አሸንፎታል፡፡

እነዚህም ጌታ የተፈተነባቸው ሦስቱ ፈተናዎች ዛሬ ሰው የሚፈተንባቸው ዋና ዋና ኃጢአቶች ናቸው፡፡ እርሱም እነዚህን መርጦ የተፈተነበት ለአርአያ ነው፡፡ ድል ማድረግ የምንችልበትን መንገድም አብነት ሆኖ አሳይቶናል፡፡ ከዚህ በኋላ የማስተማር ሥራውን በተለያዩ ቦታዎች ጀመረ፡፡ ደቀ መዛሙርቱንም ከየቦታው ጠራ፡፡

 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 4ኛ ዓመት ቁጥር 1 መስከረም 1989 ዓ.ም.

 

የንባብ ባህልን ለማሳደግ ቤተ ክርስቲያን የሚኖራት ድርሻ ከፍተኛ መሆኑ ተገለጸ

 ሐምሌ 1 ቀን 2006 ዓ.ም.

ይብረሁ ይጥና

a tenat 2006 1ከፍተኛ ድር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትርጉም ያለው የንባብ ባሕልን ለማሳደግ ከፍተኛውን ድርሻ መያዝ እንደሚገባት በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል ባዘጋጀው የንባብ ባሕል አስመልክቶ በቀረበ የጥናት ጉባኤ ላይ ተገለጸ፡፡

ሠኔ 28 ቀን 2006 ዓ.ም. ለግማሽ ቀን በማኅበሩ ሕንፃ ላይ በተካሔደው ጉባኤ ትርጉም ያለው የንባብ ባሕል በዕውቀት እና በሥነ ምግባር የታነፀ ዜጋ ለማፍራት በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀ ሲሆን፤ “የንባብ ባሕልን ለማሳደግ የተለያዩ አካላት ሚና” ፤ እንዲሁም “ትርጉም ያለው የንባብ ባሕል በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን” በሚሉ ሁለት ርእሰ ጉዳች ላይ የተደረጉ ጥናቶች ቀርበዋል፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የአማርኛ ቋንቋ፤ ሥነ ጽሑፍና ፎክሎር መምህር የሆኑት መምህር ደረጀ ገብሬ “የንባብ ባህል ለማሳደግ የተለያዩ አካላት ሚና” በሚል ርእስ ባቀረቡት ጥናት፤ የንባብ ምንነት፤ የንባብ ክሂል የእድገት ደረጃዎች፤ የማንበብ ጠቃሚነት፤ የማንበብ ባሕልን የማሳደግና የማዳበሪያ ሥልቶቹ ምን እንደሆኑ በስፋት ዳስሰዋል፡፡ በተለይም ሕፃናት የቋንቋ ችሎታቸውን በማዳበር በየጊዜው የማዳመጥና የማንበብ ፍላጎታቸውን ማሳደግ እንደሚቻል ገልጠዋል፡፡

ለንባብ ባሕል መዳበር ትምህርት ቤቶችና ወላጆች፤ መንግሥትና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ትኩረት ሠጥተው መሥራት እንደሚገባቸውም በጥናታቸው አመልክተዋል፡፡ “ትርጉም ያለው የንባብ ባህል በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን” በሚል ርእስ ጥናታቸውን ያቀረቡት አቶ ጸጋዘአብ ለምለም ደግሞ ትርጉም ያለው የንባብ ባሕል ለፈጣሪነት፤ ለውጤታማነት፤ ለብቁ ተወዳደሪነትና ለሀገር ሁለንተናዊ ብልጽግና ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

ዓለም አቀፋዊት የሆነችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የብዙ መጻሕፍትና መዛግብት እንዲሁም ቅርሶች ባለቤት እንደመሆኗ መጠን አገልግሎቷን ካለንባብ ማሰብ አስቸጋሪ እንደሚያደርገው አመልክተው፤ ቤተ ክርስቲያን በርካታ ምሥጢራት እንዳሏት ሁሉ እነዚህን ምሥጢራት ለአገልግሎት ለማብቃት ትርጉም ያለው የንባብ ባሕል አስፈላጊነትና ንባብ የቤተ ክርስቲያኗ አንዱ አካል መሆኑን በጥናታቸው ዳስሰዋል፡፡

ንባብ ሲባል ከፊደል ቆጠራ ጀምሮ ያለው ሲሆን፤ ቤተ ክርስቲያን የፊደል ባለቤት ሆና ብትቀጥልም ትርጉም ያለው የንባብ ባሕል አድማሷን አለማስፋፋቷን በስፋት አቅርበዋል፡፡ የዐቅም ማጣት ሳይሆን ዐቅምን አለማወቅ፤ የአጠቃቀም ችግር፤ ተቋማዊ የሆነ አስተዳደር አለመዘርጋት፤ ቤተ ክርስቲያን ከዘመኑ ቴክኖሎጂ ጋር አለመተሳሰሯ፤ ንባብን እንደ አንድ የአገልግሎት አካል አለመመልከት እንደ ምክንያትነት ተጠቅሰዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያን ትርጉም ያለው የንባብ ባሕል አድማስን ለማስፋፋት ንባብን እንደ ሃይማኖታዊ በዓል አከባበራችን ባሕል ማድረግ፤ ዐቅምን ማሳደግና ማበልጸግ፤ ጠንካራ ተቋማዊ አስተዳደርን መዘርጋት፤ ከዘመኑ ቴክኖሎጂ ጋር ማስተሳሰር፤ የጥናትና ምርምር ማእከላትን ማበራከት የመሳሰሉትን ጥናት አቅራቢው እንደ መፍትሔ አቅርበዋል፡፡

በቀረቡት ሁለቱም ጥናታዊ ጽሑፎች ላይ ከተሳታፊዎች ጥያቄዎች ቀረበው በባለሙያዎቹ ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

 

የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀመዛሙርትን አስመረቀ

 ሰኔ 30 ቀን 2006 ዓ.ም.

ዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

a menfesawy 2006 1በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በቀንና በማታ መርሐ ግብር ያስተማራቸውን ሦስት መቶ ደቀመዛሙርት አስመረቀ፡፡

ሰኔ 28 ቀን 2006 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ተገኝተው ለተመራቂ ተማሪዎች የእንኳን ደስ ያላችሁ መልእክት ያስተላለፉት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት “የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እምነቷን፤ ትውፊቷንና ታሪኳን እንደተጠበቀ ለትውልዱ ሁሉ እንድታደርሱላት አደራ ተረክባችኋል” ብለዋል፡፡

የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ በበኩላቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ያሏትን ሦስት ኮሌጆች አቅም ለማሳደግ ከዚህ ቀደም የሰጠችውን ትኩረት በማጠናከር ውጤታማ ማድረግ ይኖርባታል ሲሉ ተናግረዋል፡፡

ከተመራቂ ደቀመዛሙርቱ መካከል ከዚህ በፊት ከነበረው በተሻለ ሁኔታ የሴት ተማሪዎች ቁጥር ከፍ ማለቱንና በማስተርስና በዲፕሎማ መርሐ ግብር ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገብ መቻላቸው ተገልጧል፡፡

በዚህ ዓመት ኮሌጁ ካስመረቃቸው ደቀመዛሙርት መካከል 25 በማስተርስ፤ 71 በመጀመሪያ ዲግሪ፤ 114 በዲፕሎማ፤ 7 በግእዝ ዲፕሎማ፤ እንዲሁም 83 በርቀት ትምህርት በሰርተፊኬት ትምህርታቸውን ተከታትለው መመረቃቸውን ከኮሌጁ ሬጅስትራር ክፍል የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡

 

 

ዐውደ ርዕዩ ተጠናቀቀ

ሰኔ 30 ቀን 2006 ዓ.ም.

አውሮፓ ማእከል የጀርመን ቀጠና ማእከል

በሀገረ ጀርመን ፍራንክፈርት ከተማ ለሦስት ቀናት ለሕዝብ ክፍት ሆኖ የቆየው ዐውደ ርዕይ ተጠናቀቀ፡፡

ge awd 2006 44
“ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት የድርሻችንን እንወጣ” በሚል ርዕስ ተዘጋጅቶ ሲታይ የሰነበተው ዐውደ ርእይ በፍራንክፈርትና አካባቢው በሚኖሩ በርካታ ምእመናን ተጎብኝቷል፡፡ ዐውደ ርእዩን የጎበኙ ምእመናንም ባዩት ነገር እንደተደሰቱና ብዙ ትምህርት እንዳገኙበት ገልጸዋል፡፡

ዝግጅቱ በልዩ ልዩ የጀርመንና የአውሮፓ ከተሞች ቢደረግ ምእመናን ስለ ቤተ ክርስቲያናቸውና እምነታቸው በቂ ግንዛቤ እንዲያገኙ ስለሚረዳቸው በተከታታይ እንዲቀርብ የዐውደ ርዕዩ ተሳታፊዎቹ ለኮሚቴው የአደራ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡ ከዐውደ ርዕዩ ጎን ለጎንም ሰፊ የስብከተ ወንጌልና የምክር አገልግሎት ከኢትዮጵያ በመጡ መምህራን ሲሰጥ ሰንብቷል፡፡

በአጠቃላይ ዐውደ ርዕዩ እንደታሰበው የተከናወነና ውጤታማ እንደነበር ዐውደ ርእዩን ያዘጋጀው በማኅበረ ቅዱሳን የጀርመን ቀጠና ማእከል አባላት ገልጸዋል፡፡

 

“ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት የድርሻችንን እንወጣ” ዐውደ ርዕይ ተከፈተ

ሰኔ 28 ቀን 2006 ዓ.ም.

አውሮፓ ማእከል የጀርመን ቀጠና ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል የጀርመን ቀጠና ማእከል በፍራንክፈርት ከተማ ኢኮነን ሙዚየም ያዘጋጀው ዐውደ ርእይ ተከፈተ፡፡ge awd 2006 2

 

ከሰኔ 27- 29 ቀን 2006 ዓ.ም./July 4-6, 2014/ እንዲታይ የተዘጋጀው ዐውደ ርእይ ጥሪ የተደረገላቸው ካህናትና ምእመናን በተገኙበት በልዩ ልዩ ዝግጅቶች ተከፍቷል፡፡ ጸሎተ ወንጌል በቦታው በተገኙ ካህናት ተደርጓል፤ የዐውደ ርእዩን የዝግጅት ሒደትና ይዘት አስመልክቶም አቶ ቃለ አብ ታደሰ የዝግጅት ኮሚቴው ሰብሳቢ የመክፈቻ ንግግር አድርገዋል፡፡

እንደ አቶ ቃለ አብ ገለጻ የጥንታዊቷንና የሐዋርያዊቷን ቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ባሕልና ትውፊት ማስተዋወቅን ዓላማው ያደረገው ዝግጅቱ በሦስት ዋና ዋና ክፍሎች ተከፋፍሎ የተዘጋጀ ነው፡፡ የመጀመሪያው ክፍል የቤተ ክርስቲያኗን ታሪክ በአጭሩና ተመልካች በቀላሉ ሊረዳው በሚችለው መንገድ የቀረበበት የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ነው፡፡  ሁለተኛው ደግሞ የዕውቀትና የጽድቅ እንዲሁም የልማት መሠረቶች የነበሩት ገዳማትና አድባራት እንዲሁም አብነት ት/ቤቶች ያደረጉትን አስተዋጽዖና በአሁኑ ወቅት እያጋጠማቸው ያለው ተግዳሮቶች በዝርዝር የቀረቡበት ነው፡፡ የመጨረሻው ደግሞ ከግንቦት 1984 ዓ.ም ጀምሮ ሰፊ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎቶችን ሲሰጥ የቆየውና ወደፊትም የሚሰጠው ማኅበረ ቅዱሳን ታሪክ፣ አገልግሎትና በየጊዜው ያጋጠሙት ችግሮች የቀረቡበት ክፍል ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን በአውሮፓ ያላት የአገልግሎት ታሪክ የተዳሰሰበት አንዱ የመርሐ ግብሩ አካል ነበር፡፡

 

ge awd 2006 1በክብር እንግድነት ተገኝተው ዐውደ ርዕዩን በጸሎት የከፈቱት መልዐከ ፀሐይ ቆሞስ አባ ሲራክ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምስራቅና ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት የፍራንክፈርት ደብረ ፀሐይ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ናቸው፡፡ መልአከ ፀሐይ በመክፈቻ መርሐ ግብሩ ላይ የተከፈተው ዐውደ ርዕይ በፍራንክ ፈርት ከተማ ለአራተኛ ጊዜ እንደኾነ በማውሳት፤ ሁሉንም ዐውደ ርእዮች አዘጋጅቶ ለፍራንክፈርት ከተማና አካባቢው ሕዝብ ለዕይታ ያቀረበው በማኅበረ ቅዱሳን የጀርመን ቀጠና ማእከል ምስጋና ይገባዋል ብለዋል፡፡ ማኅበሩ ለቤተ ክርስቲያን እየሰጠ ያለው አገልግሎት ሰፊና ጠቃሚ ነው ያሉት መልአከ ፀሐይ ቆሞስ አባ ሲራክ፤ ለዚሁ ደግሞ እኔ ራሴ ምስክር ነኝ በማለት በቅርብ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ሔደው ማኅበሩ በአቡነ  ቶማስ ዘደብረ ሃይዳ ገዳም እያደረገ ያለውን የልማት እንቅስቃሴ በአብነት ጠቅሰዋል፡፡

 

የዐውደ ርእዩን መከፈት አስመልክቶ አስተያየት እንዲሰጡ የተጠየቁት ምእመናንም በዝግጅቱ እንደተደሰቱ ገልጸዋል፡፡ በፍራንክፈርት ከተማ ነዋሪ የኾኑት አቶ ነቢዩ የማነ፤ ላለፉት ሦስት ጊዜያት የቀረቡትን ዝግጅቶች እንደተመለከቱ አውስተው «ይኸኛውም ዝግጅት ብዙ ያላወኳቸውን ነገሮች አሳውቆኛል፡፡ ይልቁንም የቤተ ክርስቲያኗ ልጆች ምን ያህል ሓላፊነታችንን እንዳልተወጣን አስገንዝቦኛል፤ ይህም በእውነት ቁጭት ፈጥሮብኛል፡፡  ማኅበረ ቅዱሳን በሀገር ቤትም ይሁን በውጭ የሚሰጠው አገልግሎት በእጅጉ እየጠቀመን ነውና ሁሉም ቢደግፈው» በማለት ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

በተመሳሳይ ሁኔታም በከተማው ነዋሪ የኾኑት ወ/ሮ እጥፍ ወርቅ ወልዴ ባዩት ዝግጅት ብዙ ነገር እንዳወቁና «ሁሉም በውጭ የሚኖረው ምእመን በሀገራችን በችግር ላይ ያሉትን ገዳማትንና አድባራትን እንዲሁም አብነት ት/ቤቶችን ለዕረፍትም ይሁን ለልዩ ልዩ ጉዳዮች ወደ ሀገር ቤት ስንሔድ በአካል በመገኘት ልናያቸው ይገባል፤ አይተንም መርዳት ይጠበቅብናል፤» ብለዋል፡፡  አቶ ኤልያስ መሸሻ ደግሞ በስዊዘርላን ነዋሪ የኾኑና ዝግጅቱ ብቁ ቁም ነገሮችን እንዳሳወቃቸው ጠቅሰው፤ «ይህን መሰሉ ድንቅና ጠቃሚ ዝግጅት በሁሉም የአውሮፓ ከተሞች ተዘዋውሮ ሊታይ ይገባዋል» ብለዋል፡፡

 

እስከ እሑድ ሰኔ 29 ቀን 2006 ዓ.ም. /July 6, 2014/ ድረስ የሚቆየውና በበርካታ ምእመናንና ጀርመናውያን እንደሚጎበኝ የሚበሚጠበቀው በዚህ ዝግጅት ጥናታዊ ጽሑፎችና የቤተ ክርስቲያኗን ልዩ ልዩ ባሕሎች የሚያስተዋውቁ ትዕይንቶችና ስብከተ ወንጌል ይቀርባሉ፡፡

 

በሀገረ ጀርመን አስራ አንድ አብያተ ክርስቲያናት የሚገኙ ሲኾን ሁሉም በደቡብ ምስራቅና ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት ስር የታቀፉና አገልግሎት የሚሰጡ ናቸው፡፡ መንበረ ጵጵስናውን በፍራንክፈርት ከተማ ያደረገው ሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስም ብፁዕ አቡነ ሙሴ ናቸው፡፡        


ከአጤ ዋሻ ተዘርፎ የነበረው ታቦተ መድኃኔዓለም ወደ መንበረ ክብሩ ተመለሰ

 ሰኔ 27 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

a 27 2006 1 1ከሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ደብረ ብርሃን ከተማ በአሥር ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከሚገኘው የአጤ ዋሻ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ተዘርፎ ጅቡቲ ውስጥ ለ17 ዓመታት ተደብቆ የነበረው ታቦተ መድኃኔዓለም ወደ አዲስ አበባ ተመልሶ ሰኔ 21 ቀን 2006 ዓ.ም. ወደ መንበረ ክብሩ ገብቷል፡፡ /ሚያዚያ 17 ቀን 2006 ዓ.ም. ታቦቱ ከጅቡቲ ወደ አዲስ አበባ መግባቱን ከዚህ በፊት መዘገባችን ይታወሳል/፡፡ 

ታቦቱ ሐምሌ 27 ቀን 1989 ዓ.ም. ሌሊት ማንነታቸው ባልታወቁ ግለሰቦች ተሰርቆ ለ17 ዓመታት ጅቡቲ ውስጥ በአንድ የሌላ እምነት ተከታይ ቤት ውስጥ ተደብቆ ከቆየ በኋላ ጅቡቲ ለሚገኘው ለምሥራቀ ፀሐይ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳደሪ ለአባ ዮናስ መልከ ጼዲቅ ከቤተሰቡ መካከል በአንዱ መረጃው ይደርሳቸዋል፡፡ አባ ዮናስ በደረሳቸው መረጃ መሠረት ለጠቅላይ ቤተ ክህነት በማሳወቅ ታቦቱን ለማስመለስ ከፍተኛ ጥረት ተደርጓል፡፡

a 27 2006 1 2ሚያዚያ 17 ቀን 2006 ዓ.ም. ወደ አዲስ አበባ ተመልሶ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የቅርስ ጥበቃና ቤተ መዘክር ለጊዜው እንዲቀመጥ በማድረግ፤ በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ሰኔ 21 ቀን 2006 ዓ.ም. በከፍተኛ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ወደ አጤ ዋሻ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አሸኛኘት ተደርጎለታል፡፡

የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ መዘምራንና ምእመናን በደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ለታቦቱ ደማቅ አቀባበል በማድረግ በአጤ ዋሻ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ወደ መንበረ በክብሩ አስገብተውታል፡፡

ብፁዕነታቸው በሰጡት ቃለ ምእዳን ለታቦቱ መመለስ ከፍተኛ ጥረት ላደረጉ አካላት ምሥጋናቸውን አቅርበው ምእመናን በተለይም በየአጥቢያው የሚገኙ ወጣቶች ቤተ ክርስቲያንን እንዲጠብቁ የአደራ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ወደ አጤ ዋሻ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ለመድረስ በጣም አስቸጋሪና ውጣ ውረድ የተሞላበት ገደልን መውረድ ስለሚጠይቅ በርካታ የቤተ ክርስቲያን የከበሩ ንዋያተ ቅድሳት በኢጣሊያ ወረራ ወቅት ተሸሽገውበት እንደነበር የቤተ ክርስቲያኑ አገልጋይ አባቶች ይገልጻሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል የኢጣሊያ ጦር በአድዋ ጦርነት ድል እንዲነሱ ካደረጋቸው አንዱ የመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ታቦት በመሆኑ ይህንን ታቦት ለመዝረፍ ከ1928 ዓ.ም. ጀምሮ የኢጣሊያ ጦር ኢትዮጵያን በወረረበት ወቅት ከፍተኛ ጥረት አድርጓል፡፡ ነገር ግን ለሃይማኖታቸውና ለሀገራቸው ፍጹም ፍቅር የነበራቸው አባቶች ታቦቱን ከቤተ መቅደስ በማውጣት ጦርነቱ እስኪያበቃ አጤ ዋሻ ወስደው ሸሽገውታል፡፡

ከጦርነቱ ማብቃት በኋላ በ1937 ዓ.ም. ካህናቱ ታቦቱን አጅበው ከአጤ ዋሻ ወደ አዲስ አበባ መልሰውታል፡፡ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ካህናቱ በታማኝነት ታቦቱን ጠብቀው በማኖርና በክብር በመመለሳቸው በወርቅ የተለበጠ የመድኃኔዓለም ታቦት ይዘው እንዲመለሱ አድርገዋል፡፡

ከ1937 ዓ.ም. ጀምሮ አገልግሎት ሲሰጥ የነበረው ይህ ታቦት በ1989 ዓ.ም. ተሰርቆ ጅቡቲ ውስጥ በሌላ እምነት ተከታይ ቤት ውስጥ ተደብቆ ቆይቷል፡፡ በቤቱ ውስጥ ደብቆ ያስቀመጠው ግለሰብ የተሰደደ ሲሆን፤ ሚስቱ ስታብድ ልጁ ሞቶበታል፡፡ በዚህ የተደናገጠው ሌላው የሰውየው ልጅ በቤታቸው ውስጥ ታቦት እንዳለና ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲወሰድ ራሱ መጥቶ መረጃ በመሥጠቱ ታቦቱ ወደነበረበት በክብር ተመልሷል፡፡

 

ልዩ ዐውደ ርዕይ በጀርመን ፍራንክፈርት ከተማ ይካሔዳል

ሰኔ 25 ቀን 2006 ዓ.ም.

አውሮፓ ማእከል

mkgermany exhibition 2በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል የጀርመን ቀጠና ማእከል “ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት የድርሻችንን እንወጣ” በሚል መሪ ቃል ልዩ ዐውደ ርዕይ፤ ዐውደ ጥናትና የስብከተ ወንጌል መርሐ ግብር በፍራንክፈርት ከተማ ኢኮነን ሙዚየም ከሰኔ 27- 29 ቀን 2006 ዓ.ም./July 4-6, 2014/ እንደሚካሔድ ቀጠና ማእከሉ አስታወቀ፡፡

በዝግጅቱም የኢትዮጵያ ጥንታዊ ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ታሪክ አስተዋጽኦና ወቅታዊ ሁኔታ፤ የቤተ ክርስቲያኒቱ እንቅስቃሴ በጀርመንና በአውሮፓ፤ የቅዱስ ያሬድ አጠቃላይ የዜማ ባሕል እና ሌሎችም ጥናታዊ ጽሑፎች ይቀርባሉ፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ በአውሮፓ ሀገራት የሚገኙ የማኅበሩ አባላትና ምእመናን ታዳሚ እንደሚሆኑ ይጠበቃል፡፡

 

ሰበካ ጉባኤው ለካህናት ደመወዝ ለመክፈል እንደተቸገረ አስታወቀ

ሠኔ 25 ቀን 2006 ዓ.ም.

ዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ

entoto ragualeሠኔ 22 ቀን 2006 ዓ.ም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ በተደረገው ጉባኤ ላይ የእንጦጦ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ወኤልያስ ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት ለካህናት ደመወዝ ለመክፈል በመቸገሩ በቤተ ክርስቲያኑ ተገቢውን መንፈሳዊ አገልግሎት ለመስጠት ችግር እያጋጠመው መሆኑን ገለጠ፡፡

entoto ragual 4የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ አባ ወልደ መድኅን ተክለ ብርሃን የእንጦጦ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ወኤልያስ ቤተ ክርስቲያንና የርዕሰ አድባራት እንጦጦ መንበረ ፀሐይ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ከግቢያቸው አጥር ውጭ ምንም ይዞታ የሌላቸው በመሆኑ እና ቀደም ሲል የነበረው 270.9 ሄክታር ይዞታ በመነጠቁ ምክንያት አልምተን የገቢ ምንጭ የምንፈልግበት ሁኔታ የለም ሲሉ ተናግረዋል፡፡

አስተዳዳሪው ደብሩ ይዞታው ከተመለሰ የልማት ሥራ በመሥራት ከችግር መላቀቅ የሚቻል መሆኑን ጠቁመው፣ ጉዳዩንም ለሚመለከተው አካል ማሳሰባቸውን አስታውቀዋል፡፡

የሰበካ ጉባኤው ምክትል ሊቀ መንበር አቶ ወንዳፍራሽ ኃይሉ የአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን ቁጥር ከ150 የማይበልጡ በመሆናቸው ከምእመናኑ በሚገኘው አስተዋጽኦ የካህናቱን ደምወዝ መክፈል አልተቻለም፡፡ የቅዱስ ራጉኤል ወኤልያስ ወዳጆች በሚያደርጉት አስተዋጽኦ እንጂ ደብሩ ከከተማ ራቅ ያለ በመሆኑ ምንም የገቢ ምንጭ የለውም ብለዋል፡፡

ደብሩ በአሁኑ ሰዓት 51 አገልጋዮች አሉት፡፡ አገልጋዮቹ ቀን ከሌሊት በትጋት ቢያገለግሉም ሰበካ ጉባኤው ካለው ዐቅም አንጻር ደምወዝ ከከፈላቸው ሦስት ወር እንደሆናቸው ገልጸዋል፡፡ አገልጋዮቹም በችግር ምክንያት የቀን ሥራ እየሠሩ እንደሚገኙ አስታውቀዋል፡፡

የቤተ ክርስቲያኑ ፀሐፊ የሆኑት መጋቤ ምሥጢር አባ ፍሬ ስብሐት አድማሱ በበኩላቸው ቤተ ክርስቲያኑ ከተተከለ መቶ ሠላሳ ዐራት ዓመታትን አስቆጥሯል፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ በዐፄ ምኒልክ ዘመን የመጻሐፍት፣ የቅኔና የድጓ መምህራን እንዲሁም ሦስት መቶ ሊቃውንት የነበሩት መሆኑን ጠቁመው፣ ዛሬ ላይ የአብነት ትምህርት ቤቶቹ ፈራርሰዋል፡፡ ተማሪዎችና መምህራን ፈልሰዋል ብለዋል፡፡

ቀደም ሲል በአዲስ አበባ ከሚገኙ ሊቃውንት አብዛኛዎቹ ከእንጦጦ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ወኤልያስ ቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ቤት የተገኙ ናቸው ያሉት ጸሐፊው በአሁን ሰዓት ጉባኤዎቹ ታጥፈዋል፡፡ ይህ የሆነው ከገንዘብ ማጣት ጋር የተያያዘ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በ14ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በሀገራችን ነግሠው የነበሩት ዐፄ ዳዊት በእንጦጦ ተራራ ላይ መናገሻ ከተማቸውንና ቤተ መንግሥታቸውን አድርገው ይኖሩ ነበር፡፡ ንጉሡ ከቋጥኝ ድንጊያ ዋሻ ፈልፍለው ቤተ መቅደስ አሠርተው ሲያስቀድሱ ነበር፡፡ በ1860 entoto ragual 3ዓ.ም መጨረሻ ዐፄ ምኒልክ እንጦጦ ከተማ ከቆረቆሩ በኋላ፣ የልዑል እግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ለማሳነጽ በነበራቸው ምኞት ከደብረ ሊባኖስ ገዳም አባቶችን አስመጥተውና ቦታውን አስባርከው የእንጦጦ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ወኤልያስ ቤተ ክርስቲያን ሊታነጽ መቻሉን ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

ቤተ ክርስቲያኑ በውስጡ የቋጥኝ ፍልፍል ዋሻ ቤተ መቅደስ፣ የነገሥታት ዘውድና አልባሳት፣ የወርቅ፣ የብር፣ የነሀስና የዕፅ ንዋያተ ቅድሳትንና ቅርሶችን የያዘ ነው፡፡ ደብሩ እነዚህን ቅርሶች ሙዝየም በማስገንባት ለጎብኚዎች ክፍት ያደረገ ሲሆን ሕዝበ entoto raguale 2.jpgክርስቲያኑ ወደዚህ የተቀደሰ ቦታ በመምጣት፣ በመሳለምና የበኩላቸውን አስተዋጽኦ በማበርከት የበረከቱ ተሳታፊ ይሆኑ ዘንድ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ደብሩን መርዳት ለምትፈልጉ የልማት ባንክ ቁጥርን ይጠቀሙ፡፡ 0173060913900

 

የማቴዎስ ወንጌል

ሰኔ 24 ቀን 2006 ዓ.ም.

ምዕራፍ 3

ይህ ምዕራፍ ስለጌታ መጠመቅ ይናገራል፡፡ አጥማቂው ቅዱስ ዮሐንስ የንስሐ ስብከት እየሰበከ ከምድረ በዳ የመጣ ነው፡፡ አስቀድሞ በነብየ ልዑል ኢሳይያስ ስለ ዮሐንስ ተነግሮ ነበር፡፡ ኢሳ.41፡3፡፡ ልብሱ የግመል ጠጉር በወገቡም ጠፍር ይታጠቅ ስለነበር ይህ ሁኔታው ከነብዩ ኢሳይያስ ጋር ያመሳስለው ስለነበር በኤልያስ ስም ተጠርቷል፡፡ ሚል.4፡5፣6፡፡

ኤልያስና መጥምቀ መለኮት ዮሐንስን የሚያመሳስላቸው ሌላም ነገር አለ፡፡

  • ኤልያስ አክዓብና ኤልዛቤልን ሳይፈራ ሳያፍር በመጥፎ ሥራቸው እንደገሰጻቸው መጥምቁ ዮሐንስም ሄሮድስን የወንድምህን የፊልጶስም ሄሮድስን የወንድምህን የፊልጶስን ሚስት ልታገባ አልተፈቀደልህም በማለት ገስጾታል፡፡

  • ኤልያስ ንጹሕ ድንግላዊ እንደ ነበር ሁሉ መጥምቁ ዮሐንስም ንጹሕ ድንግል ነው፡፡

ዮሐንስ ያጠምቅ የነበረው ጥምቀት የንስሐ ጥምቀት በመሆኑ በኢየሩሳሌምና በይሁደ የነበሩ ሁሉ ኃጢአታቸው እየተናዘዙ ከእርሱ ዘንድ ይጠመቁ ነበር፡፡

ፈሪሳውያን ሊጠመቁ ወደ እርሱ ዘንድ ሲመጡ አይቶ “እናንተ የእፉኝት ልጆች” በማለት ገሰጻቸው፡፡ ከእፉኝት ልጆች ጋር አይሁድን ያመሳስላቸው ያለምክንያት አልነበረም፡፡ እፉኝት አፈማኅፀንዋ ጠባብ ስለሆነ ከወንዱ እፉኝት አባላዘር ከስሜትዋ የተነሣ ስለምትቆርጠው ወንዱ እፉኝት በፅንስ ጊዜ ይሞታል፡፡ የእፉኝት ልጆች አባታቸውን ገድለው ይፀነሳሉ፡፡ ኋላም የመወለጃቸው ጊዜ ሲደርስ ቀደም ተብሎ እንደተገለጸው አፈማኅፀንዋ ጠባብ ስለሆነ የእናታቸውን ሆድ ቀደው ይወጣሉ፡፡ ያን ጊዜ እናታቸው ትሞታለች፡፡ አይሁድም እንደ አባት የሆኑአቸውን ነብያትን /እነኤርሚያስን/ የጌታን ልደት በመናገራቸው ገድለዋቸዋል፡፡ ኋላም እንደ እናት የሚራራላቸውንና የሚወዳቸውን ጌታ ቀንተው ተመቅኝተው ይገድላሉና በእፉኝት ተመሰሉ፡፡

መንፈስ ቅዱስንም በእሳት መስሎ ተናግሯል፡፡ መንፈስ ቅዱስ በእሳት የተመሰለበትም ምክንያት፡-

እሳት ምሉዕ ነው፡፡ በየትም ቦታ ይገኛል፡፡ መንፈስ ቅዱስም ምሉዕ ነው፡፡ የማይገኝበት ሥፍራ የለም፡፡

እሳት በምልዓት ሳለ ቡላድ ክብሪት ካልመቱ አይገለጽም፡፡ መንፈስ ቅዱስም ቋንቋ ሲያናግር፣ ምስጢር ሲያስተረጉም፣ ተአምር ሲያሠራ እንጂ በእኛ ላይ አድሮ ሳለ አይታወቅምና፡፡

እሳት ከመነሻው ማለትም ክብሪት ጭረን ስንለኩሰው በመጠን ነው፡፡ ገለባውን ወረቀቱን እንጨቱን እየጨማመርን ስናቀጣጥለው ግን ኃይሉ እየጨመረ፣ እየሰፋ እየተስፋፋ ይሄዳል፡፡

መንፈስ ቅዱስም መጀመሪያ በ40 ቀን ለወንዶች በ80 ቀን ለሴቶች በጥምቀት ጊዜ ጸጋውን ሲሰጥ በመጠኑ ነው፡፡ ኋላ ግን በገድል በትሩፋት ጸጋ መንፈስ ቅዱስ በሕይወታችን እያደገ ይመጣል፡፡

እሳት የነካው ምግብ ይጣፍጣል፡፡ ማለትም አሳት ጣዕምን መዓዛን ያመጣል፡፡ እንደዚሁም ሁሉ በሕይወታችን ጣዕመ ጸጋንና መዓዛ ጸጋን የምናገኘው በመንፈስ ቅዱስ ነው፡፡

  • እሳት በአግባቡ ቢጠቀሙበት ለሰው ልጅ ጥቅም ይውላል፡፡ ዳሩ ግን አያያዙን ካላወቁበት ጉዳቱ ያመዝናል፡፡ መንፈስ ቅዱስም በአግባቡ በወንጌል የተጻፈውን መሠረት አድርገው ለሚመረምሩት ሁሉ ሕይወትን ይሰጣል፡፡ ጸጋን ያጐናጽፋል፡፡ ነገር ግን ከተጻፈው ውጭ በአጉል ፍልስፍና በትዕቢት ሊመረመሩ የሚነሡ ሁሉ ትልቅ ጥፋት በሕይወታቸው ያመጣሉ፡፡

  • እሳት ገለባም ይሁን እንጨት፣ እርጥብ ይሁን ደረቅ ያቀረቡለትን ሁሉ ሳይመርጥ ያቃጥላል፡፡ መንፈስ ቅዱስም በንጹሕ ልቡና ሆኖ ለሚለምነው ሁሉ ሕፃን ዐዋቂ ድኻ ሀብታም ሳይል የጸለዩትን ጸሎት ያቀረቡትን መሥዋዕት ይቀበላል፡፡

  • አሳት የበላው መሬት ለእህል ለተክል ተስማሚ ነው፡፡ ጥሩ ምርት ይገኝበታል፡፡ እንደዚሁም ሁሉ መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ሰውነት ለገድል ለትሩፋት ያመቻል፡፡

  • እሳት ተከፍሎ አይኖርበትም፡፡ ማለትም ከአንዱ የሻማ መብራት ሌላ ሻማ ብናበራ የሻማው መብራት አይጉድልም፡፡ መንፈስ ቅዱስም ተከፍሎ ወይም የጸጋ መጉደል መቀነስ ሳይኖርበት እስከ ምጽአት ድረስ ለምእመናን ጸጋውን ሲሰጥ ይኖራል፡፡

  • ሸክላ ሠሪ ሥራዋን ሠርታ ስትጨርስ ስህተት ያገኘችበት እንደሆነ እንደገና መልሳ ከስክሳ በውኃ ለውሳ በእሳት ታድሰዋለች፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ንጹሕ ሆኖ የተፈጠረ ሰው ከእግዚአብሔር ሕግ ቢወጣና በኃጢአት ቢያድፍ በንስሐ ሳሙና ታጥቦ በመንፈስ ቅዱስ ታድሶ አዲስ ሰው ይሆናል፡፡

መጥምቀ መለኮት ዮሐንስ ስለአጠመቀው ሲመሰክር ጫማውን እሸከም ዘንድ የማይገባኝ ነኝ ብሏል፡፡ በዚህም የኢየሱስ ክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት ተናግሯል፡፡ “መንሹም በእጁ ነው” ሲል ገበሬ በመንሽ ፍሬውን ከገለባው እንደሚለይ ጌታችንም ጻድቃንን ከኃጥአን የመለየት ሥልጣኑ የራሱ ነውና፡፡ በጐተራ መንግሥተ ሰማያትን፣ በስንዴ፣ ጻድቃንን፣ በገለባ፣ ኃጥአንን፣ በማይጠፋ እሳት፣ ገሃነመ እሳትን መስሎ ተናግሯል፡፡

ይጠመቅበት ዘንድ ጌታ በኢየሩሳሌም ካሉት ወንዞች ሁሉ ዮርዳኖስን የመረጠበት ምክንያት፡-

  1. በተነገረው ትንቢት መሠረት ነው፡፡ ልበ አምላክ ዳዊት ጌታ በዮርዳኖስ ወንዝ በሚጠመቅበት ጊዜ የሚሆነውን አስቀድሞ ተንብዮ ነበር፡፡ ያን ለመፈጸም ነው መዝ.113/114፡3-5፡፡

  2. ምሳሌውን ለመፈጸም ነው፡፡ ኤልያስ ዮርዳኖስን ተሻግሮ ወደ ብሔረ ሕያዋን እንደ ዐረገ ምእመናንም አምነው ተጠምቀው ገነት መንግሥተ ሰማይ ለመግባታቸው ምሳሌ ነው፡፡

  3. የእምነት አባት አብርሃም ነገሥተ ኮሎዶጎሞርን ድል ነሥቶ ሲመለስ የጌታን ቀን ሊያይ ወደደ፡፡ ጌታም ምሳሌውን ሊያሳየው ዮርዳኖስን ተሻግሮ እንዲሄድ አዘዘው፡፡ ዮርዳኖስን ተሻግሮ ሲሄድ መልከ ጸዴቅ ኅብስተ በረከት ጽዋዓ አኰቴት ይዞ ተቀብሎታል፡፡ አብርሃም የምእመናን ምሳሌ ሲሆን ዮርዳኖስ የጥምቀት ምሳሌ፣ መልከ ጸዴቅ ደግሞ የካህናት፣ የቀሳውስት ኅብስተ በረከት፣ ጽዋዓ አኰቴት የሥጋው የደሙ ምሳሌ ነው ዘፍ.14፡10-20፡፡

  4. የአዳምና የሔዋንን የዕዳ ደብዳቤ ለመደምሰስ ነው፡፡ ዲያብሎስ አዳምና ሔዋንን የባርነት ስማቸውን እንዲጽፉለት አድርጐ የዕዳ ደብዳቤውን አንዱን በሲኦል ሌላውን በዮርዳኖስ ወንዝ አኑሮት ስለነበር ጌታም በዮርዳኖስ ያለውን የዕዳ ደብዳቤ ለመደምሰስ በዚያ ተጠመቀ ቆላ.2፡14፡፡

ጌታችን በተጠመቀ ጊዜ

ሀ. ሰማይ ተከፈተ፣
ለ. አብ በደመና ሆኖ ስለ ወልድ መሰከረ፣
ሐ. መንፈስ ቅዱስም በጥንተ ተፈጥሮ በውኃ ላይ እንደታየ አሁን በሐዲስ ተፈጥሮ ታየ፡፡

ይህም አስተርእዮ /ኤጲፋንያ/ ይባላል፡፡ የእግዚአብሔር አንድነትና ሦስትነት የተገለጠበት ወቅት ነውና የመገለጥ ዘመን ተብሏል፡፡

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 4ኛ ዓመት ቁጥር 1 መስከረም 1989 ዓ.ም.