ማኅበረ ቅዱሳን በጀርመን ዐውደ ርእይ አካሔደ።

ነሐሴ 14 ቀን 2006 ዓ.ም.

በጀርመን ቀጠና ማእክል

a kassel 1በማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል ሐምሌ 26 እና 27 2006 ዓ.ም በጀርመን ካስል ደብረ ቀራንዮ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ያሉበትን ሁኔታ፣ የማኅበረ ቅዱሳንን ታሪክ፣ አገልግሎትና በየጊዜው ያጋጠሙትን ችግሮች እንዲሁም የቤተክርስቲያን አገልግሎት በአውሮፓ በተለይም በጀርመን ያለበትን ሁኔታ፣ የአመሠራረት ታሪከ እና መንፈሳዊ እንቅስቃሴ የሚያስቃኝ ዐውደ ርእይ ተካሔደ።

ዐውደ ርእዩ በካስል ደብረ ቀራንዮ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ በመጋቤ ምሥጢር ኅሩይ ኤርምያስ ተከፍቷል። ምእመናን ዐውደ ርእዩን ከተመለከቱ በኋላ ስለ ማኅበረ ቅዱሳን አመሠራረት፣ ገዳማትና የአብነት ትምህር ቤቶችን ለመደገፍ እያደረገ ስላለው እንቅስቃሴ በቂ መረጃ ማግኘታቸውን ገልጠው የማኅበሩን አገልግሎት ለመደገፍ ፍላጎት እንደላቸው ገልጸዋል። መጋቤ ምሥጢር ኅሩይ ኤርምያስ በበኩላቸው ራሳቸው ያለፉበት የአብነት ትምህርት ቤት ለቤተክርስቲያንም ሆነ ለሀገር ያበረከቱት አስተዋጽኦ ተመልካች ሊረዳው በሚችል መልኩ መቅረቡን አድንቀው ማእከሉ ዐውደ ርእዩን በደብሩ ስላካሔደ በስበካ ጉባኤው ስም ምሥጋና አቅርበዋል፤ የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት የቤተክርስቲያን አገልግሎት በመሆኑ አቅማቸው የፈቀደውን ሁሉ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል::

a koeln 1ዐውደ ርእዩ ነሐሴ 3 እና 4 ቀን 2006 ዓ.ም በኮሎኝ ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ላይ በአጥቢያው ሰበካ ጉባኤና በሊቀ ካህናት ዶ/ር መርዓዊ ተበጀ በጀርመን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሓላፊ ፈቃድ ለምእመናን ለመታየት በቅቷል። ዐውደ ርእዩን የከፈቱት ሊቀ ካህናት ዶ/ር መርዓዊ ተበጀ ሲሆኑ በዕለቱ የቀረበው ዐውደ ርእይ ጥንታዊ ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ያሉበትን ሁኔታ ምእመናን እንዲረዱት የሚያደርግ በመሆኑ ማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእዩን በዚህ ቤተክርስቲያን ማካሔዱ ያስደሰታቸው መሆኑን ተናግረዋል። በመቀጠልም የድጓ እና የአቋቋም መምህር የሆኑት እና ከካርል ስሩህ አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተክርስቲያን የመጡት ሊቀ ጠበብት ተክሌ ሲራክ ስለአብነት ትምህርት ቤቶች ሥርዓተ ትምህርት እና በአሁኑ ወቀት ተማሪዎች ስላሉባቸው ቸግሮች ሰፊ ገለጻ አድርገዋል፡፡ ችግሮቹን ለመፍታት አባቶች፣ ምእመናንና ማኅበራት ሊያደርጓቸው ይገባል ያሏቸውን የመፍትሔ ሐሳቦች ጠቁመዋል::

በኮሎኝ ደ/ሰ/ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን የሚገኙ ምእመናን ዐውደ ርእዩን ከተከታተሉ በኋላ ማኅበረ ቅዱሳን በገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ላይ ከፍተኛ ሥራ መሥራቱን የሚያሳይ መረጃ ሳያገኙ የቆዩ መሆናቸውን ገልጸው ወደ ፊት ግን ከማኅበሩ ጋር በመተባበር በጋራ ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶችን ለመርዳት ቃል ገብተዋል። ዐውደ ርእዩ ለሁለት ቀናት ክፍት ሆኖ በምእመናን የተጎበኘ ሲሆን ከ150 በላይ የሚሆኑ የአጥቢያው ምእመናን እንደጎበኙት የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ በነበሩ አንዳንድ ክፍተቶች ማኅበረ ቅዱሳን በአጥቢያው ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ ሳያደርግ የቆየ ቢሆንም ከዚህ በኋላ ግን በአዲስ መልክ ከደብሩ አስተዳዳሪ፣ ከሰበካ ጉባኤው እንዲሁም ከምእመናን ጋር ለመሥራት ከስምምነት ላይ ተደርሷል። ከዚህ በፊት በማኅበሩ ላይ ቅሬታ የነበራቸው ምእመናንም ከዐውደ ርእዩ በኋላ ጥያቄና አስተያየት አቅርበው በቂ ማብራሪያና ምላሽ በማግኘታቸው በቀጣይ ከማኅበሩ ጋር ለመሥራት በጎ ፍላጎት ያላቸው መሆኑን ተናግረዋል።

ተመሳሳይ የዐውደ ርእይ ዝግጅቶች በግሪክ አቴንስና በቤልጂየም ብራስልስ አብያተ ክርስቲያናት የሚካሔድ መሆኑ ተጠቅሷል።

 

የማቴዎስ ወንጌል

 ነሐሴ 9 ቀን 2006 ዓ.ም.

ምዕራፍ ስድስት

በዚህ ምዕራፍ ውስጥ የሚከተሉት አሳቦች ተጠቃልለው ይገኛሉ፡፡

  1. የምጽዋት ሥርዓት

  2. ጠቅላላ የጸሎት ሥርዓት

  3. የአባታችን ሆይ ጸሎት

  4. ስለ ይቅርታ

  5. የጾም ሥርዓት

  6. ስለ ሰማያዊ መዝገብ

  7. የሰውነት መብራት

  8. ስለ ሁለት ጌቶች

  9. የዕለት ጉርስና የዓመት ልብስ

1. የምጽዋት ሥርዓት፡- ጌታችን በዚህ ትምህርቱ እንደ ግብዞች መመጽወት እንደማይገባ ተናግሯል፡፡ ግብዞች የሚመጸውቱት ሰው ሰብስበው፣ ቀን ቀጥረው በተመሳቀለ ጉዳና በአደባባይ ነው፡፡ የሚመጸዉቱትም ለመጽደቅ ሳይሆን ለውዳሴ ከንቱ ስለሆነ፤ ስለዚህም አንተ በምትመጸውትበት ጊዜ ቀኝ እጅህ የምትሠራውን ግራ እጅህ አትወቀው ብሏል፡፡ እንዲህም ያለበት ምክንያት፡-

ሀ. በቀኝ አጅህ የያዝኸውን በግራ እጅህ አትያዘው ማለቱ ነው፡፡ ምክንያቱም ግራ ደካማ ስለሆነ ጥቂቱን ብዙ አስመስሎ ልቀንስለት ይሆን ያሰኛል፡፡ ቀኝ ግን ኃያል ስለሆነ ብዙውን ጥቂት አስመስሎ አንሷል ልጨምርበት ያሰኛል፡፡

 

ለ. ግራ እጅ የተባለች ሚስት ናት፤ ሚስት በክርስትና ሕይወት ካልበሰለች ሀብቱ እኮ የጋራችን ነው፣ ለምን እንዲህ ታበዛዋለህ? እያለች ታደክማለች፡፡ ከሰጠ በኋላ ግን ከሚስት የሚሰወር ነገር ስለሌለ ይነግራት ዘንድ ይገባል፡፡ ብትስማማ እሰየው፤ ባትስማማ ግን መለየት ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም ጥንቱን የተጋቡት እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው ሰጥተው መጽውተው ለመጽደቅ ነውና፡፡ 

 

ሐ. ግራ እጅ የተባሉት ልጆች ናቸው፤ የአባታችን “የቁም ወራሽ የሙት አልቃሽ” እያሉ ያደክማሉና፡፡

 

መ. ግራ እጅ የተባሉት ቤተሰቦች ናቸው፤ የጌታችን ወርቁ ለዝና፣ ልብሱ ለእርዝና እህሉ ለቀጠና እያሉ ያዳክማሉና፡፡

 

ይህን ሁሉ አውቀን ተጠንቅቀን የምንመጸውት ከሆነ በስውር ስንመጸውት የሚያየን ሰማያዊ አባታችን በጻድቃን፣ በሰማዕታትና በመላአክት ፊት ዋጋችንን በግልጥ ይሰጠናል፡፡

 

2. የጸሎት ሥርዓት፡- ግብዞች የሚጸልዩት ለታይታ ነው፤ አንተ ግን ከቤትህ ገብተህ ደጅህን ዘግተህ በስውር ላለው አባትህ ጸልይ፡፡ በስውር የሚያይ አባትህም በግልጥ ያስረክብሃል፡፡ ብሏል፡፡ ይህም ማለት የምትጸልይበት ጊዜ ሕዋሳትህን ሰብስበህ፣ በሰቂለ ልቡና ሆነህ ወደ ሰማያዊ ወደ እግዚአብሔር አመልክት፤ ተሰውረህም ስትጸልይ የሚያይ አባትህ ዋጋህን ይሰጥሃል ማለት ነው፡፡ ይህ የግል ጸሎትን የተመለከተ ነው እንጂ በቤተ ክርስቲያን የሚደረግ የማኅበር ጸሎትን አይመለከትም፡፡

 

3. የአባታችን ሆይ ጸሎት፡- ጌታችን ማንም ቢሆን ሲቆምና ሲቀመጥ፣ ሲተኛና ሲነሣ ሊጸልይ የሚችለውን አጭር የኅሊና ጸሎት አስተማረ፡፡ ይህንንም በዝርዝር እንመለከተዋለን፡-

ሀ. አባታችን ሆይ፡- ጌታችን ከግብርናተ ዲያብሎስ /ከዲያብሎስ ባርነት/ ነጻ እንዳወጣን፣ አጥተነው የነበረውን ልጅነት እንዳገኘን ሲያጠይቅ አቡነ /አባታችን/ በሉኝ አለ፡፡ ጌታ ሎሌውን መምህር ደቀመዝሙሩን ምን ቢወደው ያበላዋል፣ ያጠጣዋል፣ የልቡናውን ምሥጢር ያጫውተዋል እንጂ ርስቱን አያወርሰውም፡፡ ርስቱን የሚያወርሰው ለልጁ ነው፡፡ እርሱ ግን ጌታችን እና አምላካችን ሲሆን የማታልፍ ርስት መንግሥተ ሰማያትን የሚያወርሰን ስለሆነ አቡነ በሉኝ አለ፡፡ አባት ለወለደው ልጁ እንዲራራ የሚራራልን ስለሆነ አቡነ በሉኝ አለ፡፡

ለ. በሰማያት የምትኖር፡- እንዲህ ማለቱ ራሱ ከምድራዊ አባት ሲለይ ነው፡፡ ምድራዊ አባት ሲወልድ በግዘፍ ሲያሳድግ በግዘፍ ነው፡፡ ኋላም ሓላፊ ርስቱን ያወርሳል፡፡ ጌታችን ግን ሲወልደን በረቂቅ፣ ሲያሳድገንም በረቂቅ ነው፡፡ ኋላም የማታልፍ ርስቱን መንግሥተ ሰማይን ያወርሰናል፡፡ በተጨማሪም ጌታ በሁሉ ምሉዕ ሲሆን ስለ ልዕልናው በሰማይ የምትኖር ይባላል፡፡

ሐ. ስምህ ይቀደስ፡- ይህም “ስምየሰ መሐሪ ወመስተሠፀል” ስሜ መሐሪና ይቅር ባይ ነው፡፡” ያልኸው ይድናልና፤ መላእክት ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ብለው ስምህን አመስግነው ቅድስናህን ተሳትፈው እንዲኖሩ፣ እኛም ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ ብለን አመሰግነንህ ቅድስናህን ተሳትፈን እንድንኖር አድርገን በሉ ሲለን ነው፡፡

መ. መንግሥትህ ትምጣ፡- መንግሥተ ሰማይ ትምጣልን ልጅነት ትሰጠን በሉ ሲል ነው፡፡ እንዲህም ማለቱ መንግሠተ ሰማይ ከወዲያ ወዲህ የምትመጣ፣ ከወዲህም ወዲያ የምትሔድ ሆና ሳይሆን ትገለጽልን በሉ ማለቱ ነው፡፡

ሠ. ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነ እንዲሁም በምድር ይሁን፡- መላእክት በሰማይ ሊያመሰግኑህ ፈቃድህ እንደሆነ እኛም በምድር ያለን ደቂቀ አዳም እናመሰግንህ ዘንድ ፈቃድህ ይሁን፡፡ ኋላ ሙተን ተነሥተን እንድናመሰግንህ ዘንድ ፈቃድህ ይሁን በሉ ሲል ነው፡፡

 

ረ. የዕለት እንጀራችንን ስጠን ዛሬ፡- በዚህ ዓለም ሳለን ለዕለት የሚሆነን ምግባችንን ስጠን በሉ ሲል ነው፡፡

 

ሰ. በደላችንን ይቅር በለን እኛም የበደሉንን ይቅር እንደምንል፡- ማረን፣ ይቅር በለን፣ ኃጢአታችንን አስተስርይልን፣ በደላችንን ደምስስልን መተላለፋችንን ሁሉ ይቅር በለን፤ ይቅርታን እናገኝ ዘንድ እኛም የበደሉንን ሁሉ ይቅር እንላለን ሲል ነው፡፡

 

ሸ. አቤቱ ወደ ፈተናም አታግባን፡- ከክፉ ሁሉ አድነን እንጂ ወደ ኃጢአት፣ ወደ ክህደት፣ ወደ መከራ፣ ወደ ገሃነም አታግባን ከዚህ ሁሉ አድነን እንጂ በሉኝ ሲል ነው፡፡

 

ቀ. መንግሥት ያንተ ናትና፡- መንግሥተ ሰማያት ያንተ ገንዘብህ ናትና በሉኝ ሲል ነው፡፡

 

በ. ኃይል ምስጋናም ለዘላለሙ፡- ከሃሊነት፣ ጌትነት፣ ለዘላለሙ ገንዘብህ ናትና፤ አሜን በእውነት በሉኝ ሲል ነው፡፡

 

4. ስለ ይቅርታ የሰውን ኃጢአት ይቅር ባትሉ የሰማይ አባታችሁ እናንተንም ይቅር አይላችሁም፡፡ የሰውን ኃጢአት ይቅር ብትሉ ግን እናንተም የሰማይ አባታችሁ ይቅር ይላችኋል ብሏል፡፡

 

5. የጾም ሥርዓት፡- ግብዞች በሚጾሙበት ጊዜ ሰው እንዲያውቅላቸው ፊታቸውን አጠውልገው፣ ግንባራቸውን ቋጥረው፣ ሰውነታቸውን ለውጠው የታያሉ፡፡ እነዚህም በዚህ ዓለም የሚቀረውን ውዳሴ ከንቱ በማግኘታቸው የወዲያኛውን ዓለም ዋጋ ያጡታል፡፡ እናንተስ በምትጾሙበት ጊዜ ራሳችሁን ተቀቡ፣ ፊታችሁንም ታጠቡ፡፡ የተቀባ የታጠበ እንዳይታወቅበት አይታወቅባችሁ አለ፡፡ ይህስ በአዋጅ ጾም ነው ወይስ በፈቃድ ጾም ነው ቢሉ በፈቃድ ጾም ነው እንጂ በዓዋጅ ጾምስ ምንም ውዳሴ ከንቱ የለበትም ምክንያቱም ሁሉ ይጾመዋልና፡፡ አንድም በገዳም ነው ወይስ በከተማ ቢሉ በከተማ ነው እንጂ በገዳምስ ምንም ውዳሴ ከንቱ የለበትም፡፡ የምሥጢራዊ መልእክቱም ታጠቡ ንጽሕናን ያዙ፣ ተቀቡ ደግሞ ፍቅርን ገንዘብ አድርጉ ማለት ነው፡፡ እንዲህም በማድረጋችሁ ማለት ጾመ ፈቃድን ተሰውራችሁ በመጾማችሁ ተሰውሮ የሚያያችሁ አባታችሁ በቅዱሳን መካከለ ዋጋችሁን ይሰጣችኋል አለ፡፡

 

6. ሰማያዊ መዝገብ፡- ጌታችን ሰማያዊ መዝገብ ያለው አንቀጸ ምጽዋትን ነው፡፡ ኅልፈት፣ ጥፋት ያለበትን፣ ብል የሚበላውን ነቀዝ የሚያበላሸውን ምድራዊ ድልብ፤ ሌቦች ግንቡን አፍርሰው ግድግዳውን ምሰው የሚወስዱትን ቦታ አታደልቡ አለ፡፡ ይህም ስለ ሦስት ነገር ተናግሮታል፡፡

 

ሀ. እህሉን፡- ነዳያን ከሚበሉት ብለው ብለው፣ ልብሱንም ነዳያን ከሚለብሱት ብለው አኑረውት ብል ቢበላው ወይም ነቀዝ ቢያበላሸው ምቀኝነት ነውና፡፡

 

ለ.ለክፉ ጊዜ ይሆነኛል ብሎ ሰስቶ ነፍጎ ማኖር በዝናብ አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ የሚመግበውን ለጋስ አምላክ እግዚአብሔርን ከዳተኛ ማድረግ ነውና፡፡

 

ሐ. ምንም እጅ እግር ባያወጡለት ገንዘብን ማኖር ጣዖትን ማኖር ነውና ስለሆነም ኅልፈት ጥፋት የሌለበትን፣ ሰማያዊ ድልብ ሌቦች ግንቡን አፍርሰው ግድግዳውን ምሰው ከማይወስዱት ቦታ አደልቡ፤ ገንዘባችሁ ካለበት ዘንድ ልባችሁ በዚያ ይኖራልና አለ፡፡ ምሥጢራዊ መልእክቱም ውዳሴ ከንቱ ያለበትን ውዳሴ ከንቱ የሚያስቀርባችሁን፣ ሌቦች /አጋንንት/ በውዳሴ ከንቱ የሚያስቀሩባችሁን ምጽዋት አትመጽውቱ፤ ውዳሴ ከንቱ የማያስቀርባችሁን፣ ውዳሴ ከንቱ የሌለበትን ሌቦች /አጋንንት/ በውዳሴ ከንቱ የማያስቀሩባችሁን ምጽዋት መጽውቱ፤ መጽውታችሁ ባለበት ልባችሁ ከዚያ ይኖራልና ማለት ነው፡፡

7. የሰውነት መብራት፡- የሥጋህ ፋና ዓይንህ ነው፤ ዓይንህ ነው፤ ዓይንህ ብሩህ ይሆናል፤ ዓይንህ የቀና እንደሆነ ሥራህ ሁሉ የቀና ይሆናል፡፡ ዓይንህ የታመመ ከሆነ ጨለማ እንደምን ይጸናብህ? የታመመው ዓይንህ የታመመ ከሆነ ጨለማ እንደምን ይጸናብህ የታመመው ዓይንህ እንደምን ያይልሃል አለ፡፡ ምሥጢራዊ መልእክቱም እንደሚከተለው ነው፡፡

 

ሀ. ብርሃን የተባለው አእምሮ ጠባይዕ ነው፤ እዕምሮ ጠባይህ ያልቀና እንደሆነ ሥራህ ያለቀና ይሆናል፤ በተፈጥሮ የተሰጠህ አእምሮ ጠባይህ እንደምን መክበሪያ መጽደቂያ ይሆንሃል ማለት ነው፡፡

 

ለ. ብርሃን የተባለው ምጽዋት ነው፤ ምጽዋትህ ውዳሴ ከንቱ የሌለበት እንደሆነ ሥራህ ሁሉ የቀና ይሆናል፡፡ ምጽዋትህ ግን ውዳሴ ከንቱ ያለበት እንደሆነ ሥራህ ሁሉ ያልቀና ይሆናል፤ ከአንተ የሚሰጥ ምጽዋትህ ውዳሴ ከንቱ ያለበት ከሆነ ፍዳ እንደምን ይጸናብህ ይሆን እንዴትስ መክበሪያ መጽደቂያ ይሆንልሃል ማለት ነው፡፡

 

8. ስለ ሁለት ጌቶች፡- ለሁለት ጌታ መገዛት አይቻለውም፤ ይህም ባይሆን ማለት እገዛለሁም ቢል አንዱን ይጠላል ሌላውን ይወዳል፤ ለአንዱ ይታዘዛል ለሌላው አይታዘዝም ምክንያቱም አንዱ ቆላ ውረድ ሲለው ሌላው ደግሞ ደጋ ውጣ ቢለው ከሁለት ለመሆን ስለማይችል ነው፡፡ እንደዚህም ሁሉ ለእናንተም ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አይቻላችሁም አለ፡፡

 

9. የዕለት ጉርስና የዓመት ልብስ ነፍሳችሁ በምትበሉትና በምትጠጡት ወይም ስለ ሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፤ ነፍስ ከመብል ሰውነትም ከልብስ አይበልጥምን ምግብ ከመስጠትማ ነፍስን እም ኀበ አልቦ አምጥቶ መፍጠር አይበልጥምን ልብስ ከመስጠትማ ሥጋን ከአራቱ ባሕርያት አዋሕዶ መፍጠር አይበልጥምን ነፍስንና ሥጋን አዋሕጄ የፈጠርኳችሁ እኔ ትንሹን ነገር ምግብና ልብስን እንዴት እነሳችኋለሁ አለ ምሥጢራዊ መልእክቱም እንደሚከተለው ነው፡፡

 

ሀ. ምግብ ከመስጠትማ ነፍስን ካለችበት ማምጣት አይበልጥምን ልብስ አይበልጥምን ታዲያ ነፍስን ካለችበት አምጥቼ ሥጋን ከመቃብር አስነሥቼ አዋሕጄ በመንግሥተ ሰማይ በክብር የማኖራችሁ እንዴት ምግብና ልብስ እነሳችኋለሁ ማለት ነው፡፡

 

ለ. ሥጋዬን ደሜን ከመስጠትማ ነፍስንና ሥጋን ማዋሐድ አይበልጥምን ታዲያ ነፍስንና ሥጋን ተዋሕጄ ሰው የሆንኩላቸው እኔ እንዴት ሥጋዬንና ደሜን እነሳችኋለሁ ማለት ነው፡፡

 

ስለሆነም ዘር መከር የሌላቸውን፣ በጎታ በጎተራ በሪቅ የማይሰበስቡትን፣ ሰማያዊ አባታችሁ የሚመግባቸውን አዕዋፉን አብነት አድርጉ፡፡ እናንተ ከእነርሱ አትበልጡምን ከተፈጥሮ አዕዋፍ ተፈጠሮተ ሰብእ አይበልጥምን ለኒያ ምግብ የሰጠ ለእናንተ ይነሣችኋልን አለ፡፡ ምሥጢራዊ መልእክቱም እግዚአብሔር በምድረ በዳ የመገባቸውን እሥራኤል ዘሥጋን አስቡ፤ በዘመነ ብሉይ ከነበሩት ከእነርሱ በዘመነ ሐዲስ ያላችሁት እናንተ እስራኤል ዘነፍስ የተባላችሁት አትበልጡም ለእኒያ የሰጠሁ ለእናንተ እነሳችኋለሁን ማለት ነው፡፡

ስለ ልብስስ ለምን ትጨነቃላችሁ የሜዳ አበቦች እንዴት እንዲያድጉ ልብ አድርጋችሁ ተመልከቱ፤አይደክሙም አይፈትሉም ነገር ግን እላችኋለሁ ሰሎሞንስ እንኳ በክብሩ ሁሉ ከነዚህ እንደ አንዱ አልለበሰም፡፡ እግዚአብሔር ግን ዛሬ ያለውን ነገርም ወደ ዕቶን የሚጣለውን የሜዳን ሣር እንዲህ የሚያለብሰው ከሆነ እናንተ ሃይማኖት የጎደላችሁ ለእናንተማ እንዴት ልብስ ይነሳችኋል ስለሆነም ምን እንበላለን ምን እንጠጣለን ምን እንለብሳለን ብላችሁ አትጨነቁ፡፡ ይህንንስ ሁሉ ሃይማኖትና ምግባር የሌላቸው አሕዛብ ይፈልጉታል፡፡ እናንተስ አስቀድማችሁ መንግሥቱንና ጽድቁን እሹ፡፡ አስቀድማችሁ ሃይማኖት ምግባርን፣ ልጅነትንና መንግሥተ ሰማያትን ፈለጉ የዚህ ዓለምስ ነገር ሁሉ በራት ላይ ዳራጐት እንዲጨመር ይጨመርላችኋል፡፡ ነገ ለራሱ ይጨነቃልና አትጨነቁ፤ ለቀኑ ክፋቱ ይበቃዋል አለ ይህም ለነገ ያጸናናል ብላችሁ አብዝታችሁ አትመገቡ የነገውን ነገ ትመገቡታላችሁና አንድም ነገ እንናዘዘዋለን ብላችሁ ኃጢአታችሁን አታሳድሩ የነገውን ነገ ትናገራላችሁ ማለት ነው፡፡

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 4ኛ ዓመት ታኅሣሥ 1989 ዓ.ም.

 

በሐዋሳ በተለያዩ ቋንቋዎች የሚያስተምሩ ሰባኪያነ ወንጌል ተመረቁ

ነሐሴ 2 ቀን 2006 ዓ.ም.

በዲ/ን ያለው ታምራት ከሐዋሳ ማእከል

awa mer 2006 1በማኅበረ ቅዳሳን ሐዋሳ ማዕከል በተለያዩ አምስት ቋንቋዎች የሚያስተምሩ 33  ሰባኪያነ ወንጌል በሐዋሳ ካህናት ማሠልጠኛ ለአንድ ወር በቀንና በማታ ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ትምህርቶችን እና ሥልጠናዎችን ሲከታተሉ ቆይተው ብፁዕ አቡነ ገብርኤል  የሲዳማ፣ የጌዲኦ፣ የአማሮና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በተገኙበት  ሐምሌ 27 ቀን 2006 ዓ.ም በሐዋሳ ደብረ ምጥማቅ  መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን በድምቀት አስመረቀ፡፡

awa mer 2006 2ተመራቂ ሰልጣኞቹ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ባልተስፋፋባቸው የገጠር አብያተ ክርስቲያናት መካከል ከሲዳማ፣ ከጌዲኦ፣ ከአማሮና ከቡርጂ ሀገረ ስብከት የተውጣጡ ሲሆን፤ በሲዳምኛ፤ በጌዲኦኛ፤በኩየርኛ፤በቡርጂኛና በኦሮምኛ ቋንቋዎች የሚያገለግሉ ናቸው፡፡ በአንድ ወር ቆይታቸውም ከሚሰጣቸው መንፈሳዊ ትምህርት በተጨማሪ በስብከት ዘዴ ላይ ያተኮረ የልምምድ ልውውጥ አድርገዋል፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ገብርኤል ለተመራቂዎቹ የምስክር ወረቀት፤ ለአገልግሎት የሚጠቀሙበት መጽሐፍ ቅዱስ እና ማጣቀሻ መጸሕፍትን ከሰጡ በኋላ ባስተላለፉት መልእክት “ከአማርኛ እና ግዕዝ በተጨማሪ በልዩ ልዩ ቋንቋዎች ማስተማር ግዴታችን ነው፤ ሥልጠናውም ወደፊት ተጠናክሮ በመቀጠል አለበት” ብለዋል፡፡

 

በዕለቱ ተመራቂ ሠልጣኞች በደብረ ምጥማቅ መድኃኒዓለም ቤተክርስቲያን ለተገኘኙ ምእመናን በቋንቋቸው በማስተማር ያገለገሉ ሲሆን፤ ምዕመናንም ይህን ላደረገ እግዚአብሔር በእልልታ እና በጭብጨባ ምስጋና አቅርበዋል፡፡

 

የሐዋሳ ማእከል ሰብሳቢ ቀሲስ ደረጀ ሚደቅሶ በበኩላቸው ማኅበረ ቅዱሳን የሐዋሳ ማእከል በተከታታይ ለስድስት ዓመታት በተመሳሳይ መልኩ በተለያዩ ቋንቋዎች ያሰለጠናቸው ሰባኪያነ ወንጌል ቁጥር 274 ማድረሱን ገልጸዋል፡፡ ሠልጣኞችም ወደ መጡበት የገጠር አብያተ ክርስቲያናት ተመልሰው ምእመናን በሚገባቸው ቋንቋ እያስተማሩ በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ፤ ወደ ሌላ እምነት የተቀየሩትንም አስተምረው ወደ እናት ቤተክርስቲያናቸው እንዲመልሱ የአደራ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ ከሀገረ ሰብከቱ ሊቀ ጳጳስ በተጨማሪ የሀገረ ሰብከቱ ሥራ አስኪያጅ፣ የደብር አለቆች፣ ካህናትና ምእመናን ተገኝተዋል፡፡

 

የአዳማ አቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርት ቤትን ለመገንባት የመሠረት ድንጋይ ተቀመጠ

ነሐሴ 2 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

adama 2006 1በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን የአዳማ ማእከል ለሚያስገነባው የአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የአጸደ ሕፃናትና የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሣልሳይ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የበላይ ሓላፊ ሐምሌ 27 ቀን 2006 ዓ.ም. የመሠረት ድንጋይ አኖሩ፡፡

adama 2006 2በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሣልሳይ መሪነት፤ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች፤ የናዝሬት ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ካህናትና አገልጋዮች፤ የማእከሉ አባላትና ጥሪ የተደረገላቸው ምእመናን በተገኙበት ጸሎተ ወንጌል በማድረስ ብፁዕነታቸው የመሠረት ድንጋይ ባኖሩበት ወቅት በሰጡት ቃለ ምእዳን “ከሁሉም ነገር በፊት የሰው ሀብት ዕውቀት ነው፡፡ ዕውቀት ደግሞ የማይሠረቅ ሀብት በመሆኑ የማይሠረቀውን፤ የማይዘረፈውን ሀብተ እግዚአብሔርን መያዝ መልካም ነው፤ የመሠረት ድንጋይ የምናኖረውም ድንቁርናን ለማጥፋት ነው” ብለዋል፡፡

ማኅበሩ የሚያከናውናቸው ዘርፈ ብዙ ተግባራትና ለቤተ ክርስቲያን እያበረከተ ያለው ጠቀሜታ ከፍተኛ መሆኑን የገለጹት ብፁዕነታቸው “ሁላችንም የምንሠራው የቤተ ክርስቲያናችንን ሥራ በመሆኑ፤ መሠረቱም፤ ጣሪያውም አንድ ነው፡፡ የማኅበሩ አባላት ቤተ ክርስቲያናችሁን እንደምትወዱ፤ እንደምታከብሩም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታውቃለች፤ ሁላችንም እንመሠክራለን፡፡ ትውልድን በሃይማኖትና በሥነ ምግባር ኮትኩቶ ማሳደግ ተገቢ በመሆኑ ከጎናችሁ ነን፤ በርቱ” በማለት የትምህርት ቤቱ ሕንፃ ግንባታ በፍጥነት ተጀምሮ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት እንዲበቃ ተመኝተዋል፡፡

adama 2006 3ቀሲስ እሸቱ ታደሰ የማኅበሩን መልእክት ሲያስተላልፉ “ማኅበረ ቅዱሳን የተማረ ትውልድን ለመቅረጽ፤ ትምህርት ለማስፋፋት እንደ አንድ ዓላማ አድርጎ በመያዝ በየአኅጉረ ስብከቱ ዐሥር ትምህርት ቤቶችን በመክፈት ቤተ ክርስቲያንን የሚያውቅና በዕውቀት የበለጸገ ትውልድ ለማፍራት በመሥራት ላይ ነው፡፡ የአዳማ ማእከል ከ2004 ዓ.ም. ጀምሮ ቤት ተከራይቶ የዐፀደ ሕፃናትና የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በመክፈት አገልግሎት እየሠጠ ቢሆንም፤ የተማሪዎቹ ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተበራከተ በመምጣቱ ሰፋ ያለ ቦታ ማግኘት አማራጭ የሌለው ጉዳይ ሆነ፡፡ በዚህም መሠረት የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስን በማስፈቀድ በአንድ ሚሊዮን ብር ከአባላት በማሰባሰብ በአዳማ ከተማ መሬት በመግዛት በዛሬው እለት በብፁዕነታቸው የመሠረት ድንጋይ ለማኖር በቅተናል” ብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ ሕፃናትን በቃለ እግዚአብሔር ኮትኩቶ ማሣደግን ከፍተኛ ትኩረት ይሰጡ እንደነበር የገለጹት ቀሲስ እሸቱ ከብፁዕነታቸው ኅልፈት በኋላም በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሣልሣይ ቀጣይነት ኖሮት በዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የካህናት ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት፤ እንዲሁም በሀገረ ስብከታቸው የሚያከናውኗቸው የትምህርትና የልማት ሥራዎች ለሁሉም አርአያ እንደሚሆኑ ተናግረዋል፡፡

የአዳማ አቡነ ጎርጎርዮስ የአጸደ ሕፃናትና አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በ2004 ዓ.ም. ቤት ተከራይቶ 32 ተማሪዎችን ተቀብሎ ማስተማር የጀመረ ሲሆን፤ የማእከሉ አባላት የቤት ኪራይ በመክፈል፤ የጽዳት ሥራውን በማሰራት፤ እንዲሁም ጊዜያቸውን መሥዋዕት በማድረግ በነጻ ያስተምሩ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትዝታቸው እንደሆነ አባላቱ ይገልጻሉ፡፡

በ2300 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ የሚገነባው ባለ4 ፎቅ የተማሪዎች መማሪያ ሕንፃ 12 ሚሊዮን ብር እንደሚፈጅም ከማእከሉ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

 

ለአብነት ተማሪዎች የአልባሳትና የንጽሕና መጠበቂያ ድጋፍ በመደረግ ላይ ነው

 ሐምሌ 28 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

  • በ150 አብነት ትምህርት ቤቶች ውስጥ ለሚገኙ ለ10 ሺህ የአብነት ትምህርት ተማሪዎች ለማዳረስ ሥርጭቱ ይቀጥላል፡፡

  • “ያለኝ አንድ የተቀደደ ሱሪና አንድ ሸሚዝ ብቻ ነበር ፤ ቅያሪ ስለሌለኝ በመጨነቅ ላይ ሳለሁ በመድረሳችሁ እግዚአብሔር ይስጥልኝ” ከአብነት ተማሪዎች አንዱ::

abnet 2006 2
በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባባሪነት “ሁለት ልብሶች ያሉት” በሚል መሪ ቃል ከምእመናን አልባሳትና ቁሳቁሶችን በማሰባሰብ በየአኅጉረ ስብከቱ ለሚገኙ የአብነት ትምህርት ተማሪዎች የአልባሳትና የንጽሕና መጠበቂያ ቁሳቁስ ድጋፍ በመደረግ ላይ ይገኛል፡፡

“ሁለት ልብሶች ያሉት” በሚል መሪ ቃል ለሁለተኛ ጊዜ ከሐምሌ 18 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ በመካሔድ ላይ ባለው የሥርጭት መርሐ ግብር የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል ውስጥ በሚገኙ አገልጋዮችና በየማእከላቱ ተወካዮች አማካይነት በየአኅጉረ ስብከቱ በመንቀሳቀስ በማሰራጨት ላይ ይገኛሉ፡፡

abnet 2006 1በዚህም መሠረት በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት /ለሐይቅ እስጠፋኖስ አቡነ ኢየሱስ ሞዓ አንድነት ገዳም፤ ለቦሩ ደብረ ብርሃን ሥላሴ፤ ለከሚሴ ደብረ ገነት ቅዱስ ገብርኤል አብያተ ክርስቲያናት/፤ በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት /ለመርሳ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን፤ ለራማ ደብረ ሲና ኪዳነ ምሕረት አንድነት ገዳም/፤ በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት /ለደብረ ብርሃን ሥላሴ፤ ለአቡን ቤት ቅዱስ ገብርኤል፤ ለአበራ ቅዱስ ጊዮርጊስ፤ ለመንበረ መንግስት መድኃኔዓለም፤ ለግምጃ ቤት ቅድስት ማርያም አብያተ ክርስቲያናት/ ውስጥ ለሚገኙ የአብነት ትምህርት ተማሪዎች የአልባሳትና የሳሙና ድጋፍ ተደርጎላቸዋል፡፡

በደቡብ ጎንደር /ለመንበረ ልዑል አስቻ ቅዱስ ሚካኤል፤ ለጽርሐ አርያም ዙር አባ አቡነ አረጋዊ ገዳም፤ ለቅድስት ቤተልሔም፤ ለደብረ ልዑላን መድኃኔዓለም፤ ለእስቴ ደብረ ሃይማኖት መካነ ኢየሱስ፤ መሸለሚያ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፤ አባይ ማዶ ቅዱስ ገብርኤል፤ ለማቢ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፤ ለቆማ ፋሲለደስ፤ ለእስቴ ቅዱስ ሚካኤል ወቅዱስ ጊዮርጊስ አብያተ ክርስቲያናት/፤ በምዕራብ ጎጃም /ለናዳ ቅድስት ማርያም ገዳም፤ ለብጡላ ኢየሱስ፤ ለቆጋ ቅዱስ ጊዮርጊስ/፤ እንዲሁ ተመሳሳይ ድጋፍ የተደረገላቸው ሲሆን፤ በአራቱ ጉባኤያትና በማስመስከሪያ ትምህርት ቤቶች ከአልባሳትና ከሳሙና በተጨማሪ የጫማ፤ የክብሪት፤ የውኃ አጋርና ልብስ መስፊያ ክሮች አሠራጭቷል፡፡

የአብነት ትምህርት ተማሪዎች የሚያጋጥማቸውን የአልባሳት እጥረት ለመቅረፍ ከምእመናን አልባሳትን “ሁለት ልብሶች ያሉት” በሚል መሪ ቃል በማሰባበስብ እየተሠራጨ በሚገኝበት ወቅት ከየማእከላቱ በተውጣጡ የጤና ባለሙያዎች የአብነት ተማሪዎች እንዴት የአካባቢና የግል ንጽሕናቸውን መጠበቅ እንደሚገባቸው ትምህርት እየተሰጣቸውም ይገኛል፡፡

በ150 አብነት ትምህርት ቤቶች ውስጥ ለሚገኙ 10 ሺህ ተማሪዎች የአልባሳትና የንጽሕና መጠበቂያ ቁሳቁስ ለማሠራጨት ታቅዶ እየተሠራ ሲሆን፤ በዚህ ሥርጭት እስካሁን በ23 አድባራትና ገዳማት ውስጥ ለሚገኙ 4110 /አራት ሺህ አንድ መቶ አሥር/ በላይ ለሚሆኑ የአብነት ትምህርት ተማሪዎች ለማዳረስ ተችሏል፡፡ ሥርጭቱ በየአኅጉረ ስብከቱ የሚገኙ አብነት ትምህርት ቤቶችን ያካተተ በመሆኑ እንቅስቃሴው ቀጥሏል፡፡

የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እንድርያስ በደብረ ልዑላን መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ለአብነት ተማሪዎቹ አልባሳትና የንጽሕና መጠበቂያ ቁሳቁስ ሲሰጥ ተገኝተዋል፡፡ ብፁዕነታቸው ባስተላለፉት መልእክት “ሥጦታው መልካም ነው፤ መሆንም የሚገባው ነው፡፡ ንቃትና ትጋት ከተማሪዎች የሚጠበቅ ሲሆን፤ ጤናቸው ተጠብቆ ውጤታማ ሆነው እንዲወጡ ማስተማርም ያስፈልጋል” ብለዋል፡፡

በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት በመርሳ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን የቅኔ መምህር የሆኑት መጋቤ ምሥጢር መምህር ፍሬ ስብሐት ምሥጋናው በበኩላቸው “በችግር ምክንያት ትምህርታቸውን ሳይጨርሱ በሚወጡትና ወደ ከተማ ኮብልለው በሚቀሩት ተማሪዎች ባዝንም፤ አንድ ገበሬ አርሶ ፍሬውን ሲሰበስብ እንደሚደሰተው ሁሉ ተማሪዎቼ ለጥሩ ውጤት ሲበቁ ነፍሴ ይደሰታል፡፡ ያሳደገኝም፤ ያስተማረኝም ማኅበረ ቅዱሳን ነው፡፡ እንድማር፤ እዚህ ደረጃ እንድደርስ ድጎማ እያደረገልኝ ለዚህ አብቅቶኛል፡፡ የተዘረጋው ወንበር በችግር ምክንያት እንዳይታጠፍ ማኅበሩ ለተማሪዎች ባደረገው ድጋፍ በጣም ተደስቻለሁ” ብለዋል፡፡

“መምህራኖቻችን በችግር ውስጥ ይገኛሉ፡፡ እኛም ተምረን የእነሱ እጣ እንዳይደርሰን እንሠጋለን፡፡ ችግሩን መቋቋም የተሳናቸው ወደ ከተማ እየኮበለሉ በጥበቃ ወይም በቀን ሠራተኛነት እየተቀጠሩ ነው፡፡ እኛ ግን የልብሳችንና የቀለባችን መሸፈን ተስኖናል፡፡ እኔን እንደ ምሳሌ መውሰድ ይቻላል፤ ያለኝ አንድ የተቀደደ ሱሪና አንድ ሸሚዝ ብቻ ነበር፤ ቅያሪ ስለሌለኝ በመጨነቅ ላይ ሳለሁ በመድረሳችሁ እግዚአብሔር ይስጥልኝ” ሲል በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት በራማ ደብረ ሲና ኪዳነ ምሕረት abenet 2006 4አንድነት ገዳም ከሚገኙ የቅዳሴ ተማሪዎች አንዱ ይገልጻል፡፡

በቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባባሪነት የመጀመሪያው ዙር “ሁለት ልብሶች ያሉት” በሚል መሪ ቃል የአልባሳት ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር በ2003 ዓ.ም. በማካሔድ ለበርካታ አብነት ትምህርት ተማሪዎች ማዳረስ መቻሉ ይታወሳል፡፡

ይህ መርሐ ግብር ወደፊትም እንደሚቀጥል ከዋና ክፍሉ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

 

ቅዱስ ፓትርያርኩ ጾመ ፍለሰታን አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጡ

 ሐምሌ 28 ቀን 2006 ዓ.ም.

ዲ/ን ፍቃዱ ዓለሙ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶከስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መሠረት በየዓመቱ ከነሐሴ 1 እስከ 16 የሚጾመው የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ጾም ዘንድሮም የፊታችን ሐሙስ ይጀምራል፡፡

meg 28 2006 01 ይህን አስመልክቶ በቅዱስ ፓትርያርኩ ልዩ ጽሕፈት ቤት በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ወቅትብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ “የቅድስት ድንግል ማርያምን በዓለ ትንሣኤ ምክንያት አድርገን የምንጾመው ይህ ጾም ለሀገራችን፤ ለሕዝባችንና ለዓለሙ ሁሉ መዳንን፤ ምሕረትንና ይቅርታን ለማስገኘት ነው” ሲሉ ተናግረዋል፡፡

ቅዱስነታቸው፣ በጾሙ ወቅት ሁሉም ክርስቲያን የተራቡትን በማጉረስ፣ የታረዙትን በማልበስና የተቸገሩትን በመርዳት ጾሙን ለመጾም ከወዲሁ ቅድመ ዝግጅት ማድረግ እደሚገባቸው አሳስበዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊትና ጥንታዊት እንደመሆኗ መጠን ከጥንት ጀምሮ ይህንን ክብረ ቅድስት ድንግል ማርያም ጠብቃ እስካሁን አቆይታለች፤ ለወደፊትም እስከ ዕለተ ምጽአት በዚሁ ትቀጥላለች ብለዋል፡፡ ጾመ ፍልሰታ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያን በአዋጅ ከሚጾሙ ሰባቱ አጽዋማት መካከል አንዱ ሲሆን ከሕጻናት ጀምሮ ሁሉም ሕዝበ ክርስቲያን በፍጹም ትጋት የሚጾሙት የበረከት ጾም ነው፡፡

 

 

ከጠረፋማ አካባቢዎችና ከግቢ ጉባኤያት ለተውጣጡ ተተኪ መምህራን ሥልጠና እየተሰጠ ነው

 ሐምሌ 17 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

  • 850 የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ድቁና ተቀብለዋል፡፡

a seltagn 2006 01በማኅበረ ቅዱሳን የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባባሪነት ከጠረፋማ ኣካባቢዎችና ከግቢ ጉባኤያት ለተውጣጡ ተተኪ መምህራን በአቡነ ጎርጎርዮስ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል፤ እንዲሁም በስድስት ማእከላት ሥልጠና እየተሰጠ ይገኛል፡፡

አርባ ዘጠኝ ከተለያዩ ጠረፋማ አካባቢዎች የመጡ ተተኪ መምህራን ከሠኔ 30 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ አዲስ አበባ በሚገኘው አቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርትና ሥልጠና ማእከል ሥልጠናቸውን እየተከታተሉ ሲሆን፤ እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2006 ዓ.ም. ይቆያሉ፡፡ በአንድ ወር ቆይታቸውም ትምህርተ ሃይማኖት፤ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፤ አምስቱ አዕማደ ምሥጢራት፤ ሐዋርዊ ተልእኮ፤ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፤ ነገረ ቅዱሳን፤ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን፤ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንና ኦርቶዶክሳዊ መዝሙር በተሰኙ ርዕሶች ዙሪያ ሥልጠና እየወሰዱ ይገኛሉ፡፡

ከአርባ ዘጠኙ ሠልጣኞች መካከል ሁለቱ ቀሳውስት ሲሆኑ፤ ዐሥራ ሦስቱ ዲያቆናት ናቸው፡፡ ከጋምቤላ ክልል የመጣው ዲያቆን ቶንግ በሥልጠናው ገንቢ ዕውቀት ማግኘቱንና ከተለያዩ አካባቢዎች ከመጡት ሠልጣኞች ጋር ባለው ቆይታ ከፍተኛ የልምድ ልውውጥ ማድረጉን ገልጧል፡፡

ለሥልጠናው መሳካት የደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን አንቀጸ ብርሃን ሰንበት ትምህርት ቤት የጎልማሶች ክፍል የስልሣ ሺህ (60,000) ብር ድጋፍ አድርጓል፡፡

በተመሣሣይ ሁኔታ ከግቢ ጉባኤያት ለተውጣጡ 361 ተተኪ መምህራን በስድስት ማእከላት በአሰላ (በኦሮምኛ ቋንቋ)፤ እንዲሁም በዝዋይ፤ በጅማ፤ በባሕር ዳር፤ በደቡብ ማስተባበሪያ (ሐዋሳ)፤ በማይጨው እና ከኬንያ ማእከል አንድ ሰልጣኝ ሥልጠናውን እየተከታተሉ ይገኛሉ፡፡

በተያያዘ ዜና ማኅበረ ቅዱሳን ኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኙ ከ340 በላይ ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆች ውስጥ ለሚገኙ ተማሪዎች የቤተ ክርስቲያን ትምህርት የሚሰጥ ሲሆን፤ በ2006 ዓ.ም. በግቢ ጉባኤያት የሚሰጠውን ትምህርት ካጠናቀቁ 40,000 ተማሪዎች ውስጥ 850ዎቹ ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የድቁና ማዕረግ ተቀብለዋል፡፡

 

የአውሮፓ ማእከል ጠቅላላ ጉባኤ ተደረገ

 ሐምሌ 17 ቀን 2006 ዓ.ም.

በአውሮፓ ማእከል ሚድያና ቴክኖሎጂ ክፍል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል 14ኛ ጠቅላላ ጉባኤውን ከሐምሌ 11 እስከ 14 ቀን 2006 ዓ.ም. በኢጣልያ ዋና ማእከል ሮሜ ማእከል አካሄደ፡፡

erope teklala 2006 01በምእራብ አውሮፓ ልዩ ልዩ ሀገራት የሚገኙ ከሰማንያ በላይ አባላት፤ ከዋናው ማእከልና ከአሜሪካ ማእከል የተላኩ ልዑካን በተሳተፉበት ጉባኤ የማእከሉን የ2006 ዓ.ም. የአገልግሎት ሪፖርት ሰምቷል፤ የቀጣዩንም ዓመት ዕቅድና በጀት አጽድቋል፡፡ በተጨማሪም የማኅበሩ አገልግሎት በአኀጉሩ በሚፋጠንበት ዙሪያና በልዩ ልዩ አጀንዳዎች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

በጉባኤው ላይ በሀገር ቤት እየተቸገሩ የሚገኙ ቅዱሳት መካናትንና አብነት ት/ቤቶችን ስለ መርዳት፣ በልዩ ልዩ ምክንያት ከሀገራቸው ተሰደው ያሉ ኢትዮጵያውያን ሊደረግላቸው ስለሚገባው መንፈሳዊ እርዳታ እና አውሮፓ ያለው የቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ እንቅስቃሴ በሚፋጠንበት ሁኔታ ላይ የማኅበሩ አባላት ሊኖራቸው ስለሚገባቸው ድርሻ ትኩረት ከተሰጣቸው ጉዳዮች መካከል ይገኙባቸዋል፡፡ የጉባኤው ታዳሚዎች በቀረቡላቸው አጀንዳዎች ላይ ውይይት በማድረግ የውሳኔ ሐሳቦችንም አሳልፈዋል፡፡ በማኅበሩ መተዳደሪያ ደንብ መሠረትም የአገልግሎት ዘመኑን የፈጸመውን የማእከሉን ሥራ አስፈጻሚ በአዲስ ተክቷል፡፡

በጉባኤው ማጠቃለያ እንደተገለጠው የዘንድሮው ጠቅላላ ጉባኤ በእጅጉ የተሳካ እና በማእከሉ የጠቅላላ ጉባኤ ታሪክ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ተሳታፊ የተገኘበት ሲሆን ዝግጅቱም በአግባቡ የተከናወነ እንደ ነበር የማእከሉ ሰብሳቢ ዲ/ን ሰሎሞን አስረስ ገልጸዋል፡፡

እንደ ሰብሳቢው ገለጻ «ጉባኤው የማእከሉን አገልግሎት በሚያጠናክሩና አባላት በያሉበት ኾነው በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ላይ ሊያደርጉት ስለሚገባው ተግባራዊ ሱታፌ እንዲወያዩ በማሰብ የተተለመ ነበር፡፡ አባለት በቀረቡላቸው የመወያያ ርእሰ ጉዳዮች ዙሪያ ጠቃሚ ውይይት በማድረግ ያሳለለፏቸው ውሳኔዎች ተግባራዊ እንዲኾኑ ክትትል ይደረጋል» ብለዋል፡፡

በጉባኤው አዘጋጅ ኮሚቴ በታቀደው መሠረት የጉባኤው ታዲሚዎች ሰኞ ሐምሌ 13 ቀን 2006 ዓ.ም በጋራ የጥንታዊቷን የሮሜ ከተማ ጎብኝተዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በውጪው ዓለም አራት ማእከላትና ዐሥር ግንኙነት ጣቢያዎች ያሉት ሲሆን፤ የአውሮፓ ማእከል ከአራቱ ማእከላት አንዱ ነው፡፡ ቀጣዩ 15ኛ የማእከሉ ጉባኤ በፊንላንድ ዋና ከተማ ሄልሲንኪ እንዲከናወን ተወስኗል፡፡

 

ሊቁ አለቃ ወልደ ሰንበት ተገኝ አረፉ

 ሐምሌ 15 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

aleka 2006 1የብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ፤ እንዲሁም በርካታ ጳጳሳትንና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን በማስተማር የሚታወቁት ሊቁ አለቃ ወልደ ሰንበት ተገኝ በተወለዱ በ99 ዓመታቸው ሐምሌ 8 ቀን 2006 ዓ.ም. አረፉ፡፡ ስርዓተ ቀብራቸው ለ35 ዓመታት ሲያገለግሉበት በነበረው ሽሮ ሜዳ መንበረ ስብሐት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን የቤተ ክርስቲያኗ ሊቃውንት፤ ቤተሰቦቻቸውና ምእመናን በተገኙበት ሐምሌ 9 ቀን 2006 ዓ.ም ከቀኑ 9፡00 ሰዓት ተፈጽሟል፡፡

አለቃ ወልደ ሰንበት ተገኝ ከሕፃንነታቸው ጀምሮ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በመማር፤ እንዲሁም ወንበር ዘርግተው በማስተማር በርካታ ሊቃውንትን በማፍራት ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን የቀሰሙትን እውቀት ለተተኪው ትውልድ በማስተላለፍ የበኩላቸውን ተወጥተዋል፡፡

በተለያዩ ቦታዎች በመማርና በማስተማር በርካታ ዓመታትን አሳልፈው ከ1971 ዓ.ም. ጀምሮ አዲስ አበባ ሽሮ ሜዳ በሚገኘው መንበረ ስብሐት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን እስከ እለተ እረፍታቸው ድረስ በመሪ ጌታነት ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡አለቃ ወልደ ሰንበት ለስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 19ኛ ዓመት፤ ቁጥር 22/ ቅጽ 19፤ ቁጥር 254 ከነሐሴ 1- 15 ቀን 2004 ዓ.ም. እትም ለአብርሐም ቤት ዓምድ የሰጡትን ቃለ ምልልስ እንደሚከተለው አቀናብረነዋል፡፡

ሰኔ 16 ቀን 2004 ዓ.ም. “ዝክረ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልእ” የተሰኘ መርሐ ግብር በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል አስተባባሪነት በቀሲስ ሰሎሞን ወንድሙ ጥናት አቅራቢነት በኢትዮጵያ ቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን አዳራሽ ተካሒዶ ነበር፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይ ከተገኙት ተጋባዥ እንግዶች መካከል አንድ አባት ላይ ዐይኖቼ አረፉ፡፡ የሀገር ባሕል ሙሉ ነጭ ልብስ ለብሰው፤ከላይ ጥቁር ካባ ደርበዋል፡፡ ጥቁር መነጽር አጥልቀው፤ ከዘራቸውን ተመርኩዘው በዕድሜ የበለጸገውን ሰውነታቸውን በጥንቃቄ እየተቆጣጠሩ፤ በቀስታ እግሮቻችን አንስተው እየጣሉ ወደ አዳራሹ ዘለቁ፡፡

ውስጤ ማነታቸውን በማወቅ ጉጉት ተወረረ፡፡ ይዟቸው የመጣው ወንድም ከመድረኩ ፊት ለፊት ካለው የመጀመሪያ ረድፍ ወንበር ላይ እንዲቀመጡ ረዳቸው፡፡ ተከትያቸው በመግባት ሲረዳቸው የነበረውን ወንድም ማንነታቸውን ጠየቅሁት፡፡ አንዲት ቁራጭ ወረቀት ከኪሱ አውጥቶ ሰጥቶኝ ወደ እንክብካቤው ተመለሰ፡፡

አነበብኩት፤ በአግራሞት እንደተሞላሁ ደጋግሜ ተመለከትኳቸው፡፡ በዕድሜ ገፍተዋል፤ በዝምታ ተውጠው የመርሐ ግብሩን መጀመር በትእግስት ይጠባበቃሉ፡፡ በአዕምሯቸው የተሸከሙት የዕውቀት ዶሴ ማን ገልጦ አንብቦት ይሆን? ለዘመናት ሲጨልፉት ከኖሩበት ከቤተ ክርስቲያን የዕውቀት ባሕር ለስንቱ አጠጥተው አርክተው ይሆን? ከሕሊናዬ ጋር ተሟገትኩ፡፡ ከዚህ በፊት ታላላቅ ቤተ መጻሕፍቶቻችን የተባሉት አባቶች ለገለጣቸው ሁሉ ተነበዋል፡፡ ለትውልድ ዕውቀታቸው ተላልፏል፤ በመተላለፍም ላይ ይገኛል፡፡ እኚህ አባት ከደቂቃዎች በኋላ የማጣቸው ስለመሰለኝ ውስጤን ስጋት ናጠው፡፡

መርሐ ግብሩ እንደተጠናቀቀ ቀረብ ብዬ ላናግራቸው ብሞክርም ለረጅም ስዓት ከመድረኩ የሚተላለፉ መልእክቶች ሲከታተሉ በመቆየታቸው ተዳክመዋል፡፡ ማነጋር አልቻልኩም፡፡ ነገር ግን የሚገኙበትን ደብር ማንነታቸው ከሚገልጸው ወረቀት ላይ ስላገኘሁ ተረጋጋሁ፡፡

ከቀናት በኋላ ታላቁን ሊቅ ሽሮ ሜዳ ከሚገኘው መንበረ ስብሐት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን አጠገብ ከሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው አገኘኋቸው፡፡ በሕይወት ተሚክሯቸው ዙሪያም ቆይታ አደረግን፡-

ስምዐ ጽድቅ፡- ስለ ሕጻንነት ዘመንዎ ቢያጫውቱን?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- የተወለድኩት ዋድላ ደላንታ ሸደሆ ቅዱስ ሚካኤል አጥቢያ በዐፄ ምኒልክ ዘመን በ1907 ዓ.ም ነው፡፡ አባቴ ተገኝ፤ እናቴ ደግሞ እንደሀብትሽ ትባላለች፡፡ የሕፃንነት ዘመኔ አስቸጋሪ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ በሕፃንነቴ ገና ዳዴ እያልኩ ነው ሁለቱም ዓይኖቼ ባልታወቀ ምክንያት የጠፉት፡፡ እናቴ እያለቀሰች ወደ እግዚአብሔር ከመጮኽ ሌላ ምርጫ አልነበራትም፡፡ አዝላኝ ትውላለች፤ ከጀርባዋ አታወርደኝም ነበር፡፡ በሀገራችን ታቦቱ ሰሚ የሆነ የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን አለ፡፡ እዚያ ይዘሽው ሔደሽ ለምን አታስጠምቂውም፤ ከዳነልሽ የታቦቱ አገልጋይ ይሆናል ተብላ ወሰደችኝ፡፡ ወዲያውኑ አንደኛው ዓይኔ በራልኝ፡፡ ሌላኛው ግን በድንግዝግዝ ነበር የሚያይልኝ፡፡ እናቴም በተደረገላት ተዓምራት በመደሰት ከከብቶቿ መካከል አንዱን ወይፈን ወስዳ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ስዕለቷን ሰጠች፡፡ ብዙም ሳይቆይ ኩፍኝ ያዘኝና በድንግዝግዝ የነበረው አንዱ ዓይኔ ሙሉ ለሙሉ ጠፋ፡፡ አንዱ ብቻ ቀረ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡– የቤተ ክርስቲያን ትምህርት አጀማመርዎ እንዴት ነበር?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- ለቤተ ክርስቲያን የተለየ ፍቅር በውስጤ ያደረው ገና በሕፃንነቴ ነው፤ ወደ ትምህርቱም አደላሁ፡፡ የተማርኩት ብዙ ቦታ ነው፡፡ ዙር አምባ ቅዱስ ያሬድ ካስተማረበት ቦታ ጀምሮ ከብዙ መምህራንም እውቀት ቀስሜአለሁ፡፡ ከየኔታ ክፍሌና ከየኔታ ተካልኝ ጽጌ ምዕራፍ፤ ድጓ፤ ጾመ ድጓ፤ ዝማሬ መዋዕስት ተምሬአለሁ፤ አቋቋምም ከእነሱ ሞካክሬአለሁ፡፡ ለአቋቋም ልዩ ፍቅር ነበረኝ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡– አቋቋምን ከማን ተማሩ?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- አቋቋም የነፍሴ ምግብ ሆኖ ይሰማኛል፡፡ ከዜማ ይልቅ ወደ አቋቋም አዘነበልኩ፡፡ ደብረ ታቦር መልአከ ገነት ጥሩነህ ዘንድ አምስት ሆነን አቋቋም ለመማር ገባን፡፡ እሳቸው በየቦታው የሚያገኟቸውን የአቋቋም አይነቶችን ተምረዋል፡፡ የጎንደር ቀለም ግን እዚያ አይቆምም፡፡ እኔም ሁሉንም ለመማር ጥረት አድርጌአለሁ፡፡ ነገር ግን ሲያስተምሩን የጎንደርን የታች ቤትንና የተክሌን አደበላለቁብን፡፡ ለምን እንዲህ ይሆናል ብዬ አምስት ዓመት ከእሳቸው ጋር ከቆየሁበት ጥዬ በመውጣት አለቃ መንገሻ ዘንድ ሔድኩ፡፡

አለቃ መንገሻ ዘንድ ለሁለት ወራት ደጅ ስጠና ቆየሁ፡፡ ከሁለት ወራት ቆይታ በኋላ አስጠርተውኝ ከየት እንደመጣሁ፤ የት እንደተማርኩ ጠይቀውኝ ሁሉንም ነገርኳቸው፡፡ በመጨረሻም ፈቅደውልኝ የአቋቋም ትምህርቴን ቀጠልኩ፡፡ በተለይም የላይ ቤት፤ የተክሌ አቋቀቋም ላይ ትኩረት ሰጥቼ ተማርኩ፡፡ ከአለቃ መንገሻ ዘንድ ለአስራ ሰባት ዓመታት ተቀምጫለሁ፡፡ ዝማሬ መዋስዕት፤ ድጓ፤ ጾመ ድጓንና ሌሎችንም ለተማሪዎች አስተምር ነበር፡፡ ቅኔ ከሦስት ሊቃውንት ነው የተማርኩት፡፡ ከአለቃ ብሩ፤ ከአለቃ መጽሔትና የአቋቋም ተማሪዬ ከነበረው ሊቀ ጠበብት ወልደ ሰንበት ተምሬአለሁ፡፡እኔ አቋቋም እያስተማርኩት እሱ ደግሞ ቅኔ አስተምሮኝ ተመረቅሁ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ወንበር ዘርግተው ማስተማሩን እንዴት ጀመሩ?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- መምህሬ አለቃ መንገሻ ከአዲስ አበባ ከሚገኘው በዓታ ለማርያም እንዲመጡ ጥሪ ተደርጎላቸው ስለነበር አብረን እንድንሔድ ቢጠይቁኝም እምቢ በማለት ጸናሁ፡፡ የሚቀረኝን ትምህርት ለመማር ስለፈለግሁ ዙር አምባ ወፋሻ ኪዳነ ምሕረት የእድሜ ባለጸጋ ከነበሩት አባት ዘንድ ሃያ አምስት ሆነን ለመሔድ ተስማምተን መልእክት ሰደድንላቸው፡፡ እሳቸውም ጥያቄአችንን ተቀበሉን፡፡

አለቃ መንገሻ በድምጼ በጣም ይገረሙ ስለነበር ጨጨሆ ላይ ብታዜም ዋድላ ደላንታ ይሰማል ይሉኝ ስለነበር “መድፉ”፤ “ወልደ ነጎድጓድ” በማለት ይጠሩኛል፡፡ በአቋሜ እንደጸናሁ ስለተረዱም “ልጄ አብረን ብንሆን መልካም ነበር፤ ይቅናህ” በማለት ግንባሬን ስመው አሰናበቱኝ፡፡ ዙር አምባ ኪዳነ ምሕረት የተወሰነ ጊዜ ከቆየሁ በኋላ በደብረ ታቦር አጋጥ ኪዳነ ምሕረት ወንበር ዘርግቼ አቋቋም ማስተማር ጀመርኩ፡፡

ደብረ ታቦር እያለሁ ዐሥራ ሦስት የሚደርሱ አብያተ ክርስቲያናት መምህር ስላልነበራቸው እየተዟዟርኩ አገልግያለሁ፡፡ ነገር ግን ከተወሰኑ ጊዜያት በኋላ ያንን አካባቢ ተውኩና ጋይንት ልዳ ጊዮርጊስ ለማስተማር ወረድኩ፡፡ እልም ያለ በረሃ ነው፡፡ ጥቂት እያስተማርኩ ቆይቼ ተማሪዎቹ በረሃውን መቋቋም እየተሳናቸው ጥለውኝ ሔዱ፡፡ በዚህ ሁኔታ መቀጠል ባለመቻሌ በ1941 ዓ.ም. ወደ ዳውንት ሔድኩ፡፡ ዳውንት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን እስከ 1945 ዓ.ም. ተማሪዎችን ሰብስቤ ወንበር በመዘርጋት አቋቋም፤ ዝማሬ መዋስዕት፤ ድጓ፤ ጾመ ድጓ ማስተማሬን ቀጠልኩ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ከብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልእ ጋር እንዴት ተገናኛችሁ?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡– በ1943 ዓ.ም. ተከስተ ብርሃን /ተከስተ ብርሃን የሚለው ስያሜ አለቃ ወልደ ሰንበት ያወጡላቸው ስም ነው፡፡ መምህራን ተማሪዎቻቸውን በምግባራቸውና በትምህርት አቀባበላቸው ተነስተው ስም ማውጣት የተለመደ ነው፡፡/ ዳውንት ቅዱስ ጊዮርጊስ ከማስተምርበት መጣ፡፡ ታዲያ እርሱና የአሁኑ ዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አበምኔት አባ ሐረገ ወይን ጸናጽሉ ቢቀላቸውም ዘንጉ ይከብዳቸው ነበር፡፡ ተከስተ ብርሃን የሚለውን ስያሜ ያወጣሁለት በወቅቱ በነበረው የትምህርት አቀባበል ፍጥነቱንና ኃይለኛነቱን ተመልክቼ ነው፡፡በትምህርት እርሱ ዘንድ ቀልድ የለም፡፡ ተማሪዎቼ ሲያለምጡ የሚገስጻቸው እርሱ ነበር፡፡

ተከስተ ብርሃን ለትምህርትና ለሥራ ልዩ ፍቅር ነበረው፡፡ ፈቀደ /መቂ የደብረ አለቃ ሆኖ ነበር አሁን ግን አርፏል/ ከሚባል ተማሪ ጋር ሆነው “ተማሪው በትርፍ ጊዜው እየተንጫጫ ለምን ያስቸግራል፤ ለምን እርሻ አናርስም፤ በማለት ሃሳብ አቅርበው ዶማና መጥረቢያ ፈልገው ተማሪውን ሰብስበው ጫካውን እየመነጠሩ በበሬ አረሱት፡፡ ምሥር ዘርተውበት ሃምሳ ቁምጣ አስገብተዋል፡፡

በተጨማሪ ከቤተ ክርስቲያኑ በላይ በኩል ዳገታማ ሥፍራ ላይ ተማሪውን አስቆፍረው ገብስ ዘሩበት፡፡ “እባካችሁ ተማሪውን በሥራ እያማረራችሁ አታፈናቅሉብኝ” እላቸዋለሁ፡፡ እነሱ ግን ሦስት ኩንታል ገብስ አምርተው አስገቡ፡፡ ከትምህርታቸው በተጓዳኝ ጥጥ ገዝተው እያመጡ ለአካባቢው ሴቶች እያስፈተሉ ጋቢና ኩታ ያሰሩ ነበር፡፡ ተዉ ብላቸውም አሸነፉኝ፡፡ ተማሪ ሥራ ሲፈታ ስለማይወዱ ነበር ይህንን የሚያደርጉት፡፡

በተለይ ተከስተ ብርሃን ተማሪዎቹን ስለሚገስጽ ተማሪዎቹ “ይኼ ጥቁር ፈጀን እኮ” እያሉ ስሞታ ያቀርባሉ፡፡ እኔም ጠባዩን ስላወቅሁት “አንድ ስህተት አግኝቶባችሁ ይሆናል እንጂ ያለ ምክንያት አይቆጣችሁም” እያልኩ ፊት አልሰጣቸውም ነበር፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- እርስዎ ምን አይነት መምህር ነበሩ?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- እኔም ኃይለኛ ነበርኩ፡፡ ተማሪዎቼ ሲያጠፉ በኃይል ነበር የምገርፋቸው፡፡ አስቸጋሪ ተማሪ ካጋጠመኝም አባርራለሁ፡፡ ይህን የማደርገው ለእውቀት ከፍተኛ ፍቅር ስለነበረኝ የእኔን አርአያነት እንዲከተሉ ለማድረግ እንጂ በክፋት አልነበረም እርምጃውን የምወስደው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ለተማሪውና ለእርስዎ ድርጎ ከየት ያገኙ ነበር?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- ቀዳማዊ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ለተማሪዎች አቡጀዲና ለቀለብ የሚሆን ገንዘብ ይልኩልኛል፡፡ “የኢትዮጵያ መድፏና መትረየሷ ጸሎት ነው” በማለት በጸሎት እንድንበረታ መልእክት ይሰዱልኛል፡፡ እኔም በታማኝነት የቻልኩትን ሁሉ አደርግ ነበር፡፡ በተጨማሪም ዋድላ ደላንታ ላይ የተሰጠኝ እስከ ሠላሳ ጥማድ የሚያሳርስ የእርሻ መሬት ነበረኝ፤ የተመረተውን አስመጥቼ ለተማሪዎቼ ቀለብ አደርገው ነበር፡፡ ተማሪዎቼም የለመኑትን ያመጣሉ፤ በዚህ ሁኔታ ችግራችንን እንወጣ ነበር፡፡
ስምዐ ጽድቅ ፡- ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ እርስዎ ዘንድ ለምን ያህል ጊዜ ቆይተዋል?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡– ተከስተ ብርሃን ለሁለት ዓመታት አቋቋም ካስተማርኩት በኋላ ነው የተለያየነው፡፡ ከዚያ በኋላ የት እንዳለ ሳላውቅ በደርግ ዘመን ጵጵስና መሾማቸውን ሰማሁ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ስለ ቤተሰብዎ ጥቂት ቢያጫውቱን

አለቃ ወልደ ሰንበት፡– በ1947 ዓ.ም. ነው ትዳር የመሠረትኩት፡፡ ስምንት ልጆችን ወልጃለሁ፡፡ አራቱ አርፈዋል፡፡ የልጅ ልጆችም አሉኝ፡፡ አንዱ የልጅ ልጄ ደሴ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ቅኔ ቤት ገብቶ እየተማረ ነው፡፡ ለአባቱ ያሉኝን መጻሕፍት ልስደድለት እለዋለሁ፡፡ እሱ ደግሞ ቆይ ይደርሳል እያለኝ ነው፡፡ አያቴ ገብረ ተክሌ የታወቁ የድጓ መምህር ነበሩ፤ እኔም የእሳቸውን ፈለግ ተከትያለሁ፡፡ በተራዬ እኔን የሚተካ ከልጅ ልጆቼ መካከል በመገኘቱ ተደስቻለሁ፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ሓላፊነት ይሸከም ዘንድ ተገኘልኝ፡፡ እግዚአብሔር መጨረሻውን ያሳምርለት፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- አዲስ አበባ እንዴት መጡ?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- ባለቤቴም አረፈች፡፡ እመነኩሳለሁ ብዬ ደብረ ሊባኖስ ገብቼ ነበር፡፡ የእግዚአብሔር ፈቃድ ስላልነበር አልተሳካልኝም፡፡ ሔኖክ የሚባል አቋቋም ያስተማርኩት ልጅ ደብረ ሊባኖስ አግኝቶኝ በ1971 ዓ.ም. አዲስ አበባ ሽሮ ሜዳ መንበረ ስብሐት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ወስዶ በመሪ ጌትነት እንዳገለግል አደረገ፡፡ እስከ ዛሬ ድረስ በዚሁ ቤተ ክርስቲያን እያገለገልኩ ቆይቻለሁ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡– በቅርብ የሚረዳዎት ሰው አለ?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- የመጨረሻዋ ልጄ ከእኔው ጋር ናት፤ እግዚአብሔር እሷን አጠገቤ አኖረልኝ፡፡ እኔም ሰውም እየመረቅናት ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡– ካስተማሯቸው ተማሪዎችዎ ማንን ያስታውሳሉ?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ፤ ብፁዕ አቡነ ሳሙኤል /የቀድሞው/ ዝዋይ የነበሩት፤ ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ /አሁን የወልዲያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ በርካታ የደብር አለቃ የሆኑ ሊቃውንትን አፍርቻለሁ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡– የሚያስተላልፉት መልእክት ካለዎት?

አለቃ ወልደ ሰንበት፡- እኔ የጋን ውስጥ መብራት ሆኜ ነው የኖርኩት፡፡ ተደብቄ ነው ያለሁት፡፡ ቅንነት መልካም ነገር ነው፤ ለሰው ልጅ እጅግ ያስፈልጉታል፤ ኖሬበታለሁም፡፡ ዕድሜና የሰው ፍቅር ሰጥቶኛል፤ ለእናንተም ይስጣችሁ፡፡ ከተደበቅሁበት አስታውሳችሁኛልና አምላከ ጎርጎርዮስ የማኅበሩን አገልግሎት ይባርክ፡፡ አሜን፡፡

 

 

ማኅበረ ቅዱሳን ከ40,000 በላይ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን አስመረቀ

 ሐምሌ 15 ቀን 2006 ዓ.ም.

እንዳለ ደምስስ

ማኅበረ ቅዱሳን በመላው ኢትዮጵያ በሚገኙ ዩኒቨርስቲዎች ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የነበሩ ከ40,000 በላይ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን አስመረቀ ፡፡

gebi 2006 1ማኅበረ ቅዱሳን ካሉት 46 የሀገር ውስጥ ማእከላት መካከል በ38ቱ ማእከላት አስተባባሪነት በዩኒቨርስቲ ቆይታቸው የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ ትምህርት ሲከታተሉ የነበሩ ተማሪዎች አብዛኛዎቹ ዩኒቨርስቲዎች ከፍተኛውን ውጤት በማስመዝገብ የዋንጫና የሜዳልያ ተሸላሚ ሆነዋል፡፡ ከዩኒቨርስቲ ትምህርታቸው በተጓዳኝ መንፈሳዊ ዕውቀትን እንዲገበዩ በማድረግ ወደ ሥራ በሚሰማሩበትም ወቅት ራሳቸውን በመንፈሳዊውም በዓለማዊው ዕውቀት አዳብረው፤ በሥነ ምግባር ታንጸው ቤተ ክርስቲያንና ሀገራቸውን በታማኝነት እንዲያገለግሉ እንደሚረዳቸው በርካታ ተመራቂ ተማሪዎች ይገልጻሉ፡፡

የወልዲያ ዩኒቨርስቲ ለመጀመሪያ ጊዜ ካስመረቃቸው 250 ተማሪዎች መካከል 50ዎቹ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ሲሆኑ፤ ከእነዚህም ውስጥ 17ቱ በማዕረግ የተመረቁ ናቸው፡፡ በአምቦ ዩኒቨርስቲ የወሊሶ ካምፓስ በከፍተኛ ማዕረግ ተመርቀው የሜዳልያ ተሸላሚ ከሆኑት 6ቱ ተመራቂዎች ውስጥ 4ቱ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች መሆናቸውን ከየማእከላቱ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ በተጨማሪም የወልቂጤ ዩኒቨርስቲ ሁለት ትምህርት ክፍሎችን ብቻ በዚህ ዓመት የሚያስመርቅ ሲሆን፤ ከሚመረቁት 70 ተማሪዎች መካከል 14ቱ ከፍተኛ ማዕረግ የሚመረቁ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ሲሆኑ ከ1-3 በመውጣትም የሜዳልያና የዋንጫ ተሸላሚዎች ናቸው፡፡ በተያያዘ ዜና ከደብረ ብርሃን ዩኒቨርስቲ ከተመረቁት ተማሪዎች መካከል ከ7 ዮኒቨርሲቲዎችና ኮሌጆች 3 የወርቅ ሜዳሊያ 2 ዋንጫ ያገኙት የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ናቸው፡፡