ለካህናት የዐቅም ማጎልበቻ ስልጠና ተሰጠ

ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም.

ከደሴ ማእከል

በደሴ ከተማ ቤተ ክህነት፤ በማኅረ ቅዱሳን ደሴ ማእከልና ደሴ ወረዳ ማእከል አስተባባሪነት ሚያዚያ 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ደሴ ከተማ ለሚገኙ ከሰባ በላይ ለሚደርሱ የደብር አስተዳዳሪዎች፣ ካህናት በተለያዩ ርእሰ ጉዳዮች ላይ የአንድ ቀን ስልጠና ተሰጠ፡፡

ስልጠናው የተዘጋጀበትን ዓላማ የደሴ ከተማ ቤተ ከህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ መምህር ቆሞስ አባ ለይኩን ወንድይፍራው ሲገልጹ በከተማው ከዐሥር በላይ አብያተ ክርስቲያናት እና በርካታ ካህናት ስለሚገኙ በዞን ከተማነቱም ለምዕራብ ወሎ እና ለሌሎችም አጎራባች አካባቢዎች መጋቢ ነው፡፡ በዚህም መሠረት የካህናትን አቅም በሥልጠና ማገዝ እያጋጠሙን ባሉት ችግሮችና መፍትሔዎቻቸው ዙሪያ መወያየት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ መርሐ ግብሩ እንደተዘጋጀ ገልጸዋል፡፡

ለአንድ ቀን በቆየው ሥልጠና ትምህርተ ኖሎት፤ የካህናት ሚና ከቤተ ክርስቲያን ፈተናዎች እና ከዓለም አቀፍ ነባራዊ ሁኔታዎች አንጻር በሚል ርእስ ቤተ ክርስቲያን ከውጭ እና ከውስጥ እያገጠሟት ባሉ ፈተናዎች እና መፍትሔዎቻቸው እንዲሁም የካህናት ድርሻ ምን መሆን አለበት በሚሉት ርእሰ ጉዳዮች ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

በውይይቱ ወቅት በንስሓ ልጆች አያያዝ ዙሪያ እያጋጠሟቸው ስላሉ ችግሮችና መፍትሔዎቻቸው፣ ዐሥራት አለመክፈል በቤተ ክርስቲያን ላይ እያደረሰ ስላለው ጉዳት፣ የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ አሁን ያለበት ደረጃ፣ የአብነት መምህራንና ተማሪዎች እያጋጠማቸው ስላሉ ፈተናዎች እና ሌሎችም ቤተ ክርስቲያንን ከውጭና ከውስጥ እያጋጠሟት ስላሉ ፈተናዎች እና መፍትሔዎቻቸው በማንሳት የጉባኤው ተሳታፊዎች ሰፊ ውይይት አድርገዋል፡፡